entoto raguale

ሰበካ ጉባኤው ለካህናት ደመወዝ ለመክፈል እንደተቸገረ አስታወቀ

ሠኔ 25 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

entoto ragualeሠኔ 22 ቀን 2006 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተደረገው ጉባኤ ላይ የእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት ለካህናት ደመወዝ ለመክፈል በመቸገሩ በቤተ ክርስቲያኑ ተገቢውን መንፈሳዊ አገልግሎት ለመስጠት ችግር እያጋጠመው መሆኑን ገለጠ፡፡

entoto ragual 4የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ አባ ወልደ መድኅን ተክለ ብርሃን የእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያንና የርዕሰ አድባራት እንጦጦ መንበረ ፀሐይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከግቢያቸው አጥር ውጭ ምንም ይዞታ የሌላቸው በመሆኑ እና ቀደም ሲል የነበረው 270.9 ሄክታር ይዞታ በመነጠቁ ምክንያት አልምተን የገቢ ምንጭ የምንፈልግበት ሁኔታ የለም ሲሉ ተናግረዋል፡፡

አስተዳዳሪው ደብሩ ይዞታው ከተመለሰ የልማት ሥራ በመሥራት ከችግር መላቀቅ የሚቻል መሆኑን ጠቁመው፣ ጉዳዩንም ለሚመለከተው አካል ማሳሰባቸውን አስታውቀዋል፡፡

የሰበካ ጉባኤው ምክትል ሊቀ መንበር አቶ ወንዳፍራሽ ኃይሉ የአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን ቁጥር ከ150 የማይበልጡ በመሆናቸው ከምእመናኑ በሚገኘው አስተዋጽኦ የካህናቱን ደምወዝ መክፈል አልተቻለም፡፡ የቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ወዳጆች በሚያደርጉት አስተዋጽኦ እንጂ ደብሩ ከከተማ ራቅ ያለ በመሆኑ ምንም የገቢ ምንጭ የለውም ብለዋል፡፡

ደብሩ በአሁኑ ሰዓት 51 አገልጋዮች አሉት፡፡ አገልጋዮቹ ቀን ከሌሊት በትጋት ቢያገለግሉም ሰበካ ጉባኤው ካለው ዐቅም አንጻር ደምወዝ ከከፈላቸው ሦስት ወር እንደሆናቸው ገልጸዋል፡፡ አገልጋዮቹም በችግር ምክንያት የቀን ሥራ እየሠሩ እንደሚገኙ አስታውቀዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያኑ ፀሐፊ የሆኑት መጋቤ ምሥጢር አባ ፍሬ ስብሐት አድማሱ በበኩላቸው ቤተ ክርስቲያኑ ከተተከለ መቶ ሠላሳ ዐራት ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ በዐፄ ምኒልክ ዘመን የመጻሐፍት፣ የቅኔና የድጓ መምህራን እንዲሁም ሦስት መቶ ሊቃውንት የነበሩት መሆኑን ጠቁመው፣ ዛሬ ላይ የአብነት ትምህርት ቤቶቹ ፈራርሰዋል፡፡ ተማሪዎችና መምህራን ፈልሰዋል ብለዋል፡፡

ቀደም ሲል በአዲስ አበባ ከሚገኙ ሊቃውንት አብዛኛዎቹ ከእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤት የተገኙ ናቸው ያሉት ጸሐፊው በአሁን ሰዓት ጉባኤዎቹ ታጥፈዋል፡፡ ይህ የሆነው ከገንዘብ ማጣት ጋር የተያያዘ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በሀገራችን ነግሠው የነበሩት ዐፄ ዳዊት በእንጦጦ ተራራ ላይ መናገሻ ከተማቸውንና ቤተ መንግሥታቸውን አድርገው ይኖሩ ነበር፡፡ ንጉሡ ከቋጥኝ ድንጊያ ዋሻ ፈልፍለው ቤተ መቅደስ አሠርተው ሲያስቀድሱ ነበር፡፡ በ1860 entoto ragual 3ዓ.ም መጨረሻ ዐፄ ምኒልክ እንጦጦ ከተማ ከቆረቆሩ በኋላ፣ የልዑል እግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ለማሳነጽ በነበራቸው ምኞት ከደብረ ሊባኖስ ገዳም አባቶችን አስመጥተውና ቦታውን አስባርከው የእንጦጦ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ወኤልያስ ቤተ ክርስቲያን ሊታነጽ መቻሉን ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ በውስጡ የቋጥኝ ፍልፍል ዋሻ ቤተ መቅደስ፣ የነገሥታት ዘውድና አልባሳት፣ የወርቅ፣ የብር፣ የነሀስና የዕፅ ንዋያተ ቅድሳትንና ቅርሶችን የያዘ ነው፡፡ ደብሩ እነዚህን ቅርሶች ሙዝየም በማስገንባት ለጎብኚዎች ክፍት ያደረገ ሲሆን ሕዝበ entoto raguale 2.jpgክርስቲያኑ ወደዚህ የተቀደሰ ቦታ በመምጣት፣ በመሳለምና የበኩላቸውን አስተዋጽኦ በማበርከት የበረከቱ ተሳታፊ ይሆኑ ዘንድ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ደብሩን መርዳት ለምትፈልጉ የልማት ባንክ ቁጥርን ይጠቀሙ፡፡ 0173060913900

 

የማቴዎስ ወንጌል

ሰኔ 24 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ 3

ይህ ምዕራፍ ስለጌታ መጠመቅ ይናገራል፡፡ አጥማቂው ቅዱስ ዮሐንስ የንስሐ ስብከት እየሰበከ ከምድረ በዳ የመጣ ነው፡፡ አስቀድሞ በነብየ ልዑል ኢሳይያስ ስለ ዮሐንስ ተነግሮ ነበር፡፡ ኢሳ.41፡3፡፡ ልብሱ የግመል ጠጉር በወገቡም ጠፍር ይታጠቅ ስለነበር ይህ ሁኔታው ከነብዩ ኢሳይያስ ጋር ያመሳስለው ስለነበር በኤልያስ ስም ተጠርቷል፡፡ ሚል.4፡5፣6፡፡

ኤልያስና መጥምቀ መለኮት ዮሐንስን የሚያመሳስላቸው ሌላም ነገር አለ፡፡

  • ኤልያስ አክዓብና ኤልዛቤልን ሳይፈራ ሳያፍር በመጥፎ ሥራቸው እንደገሰጻቸው መጥምቁ ዮሐንስም ሄሮድስን የወንድምህን የፊልጶስም ሄሮድስን የወንድምህን የፊልጶስን ሚስት ልታገባ አልተፈቀደልህም በማለት ገስጾታል፡፡

  • ኤልያስ ንጹሕ ድንግላዊ እንደ ነበር ሁሉ መጥምቁ ዮሐንስም ንጹሕ ድንግል ነው፡፡

ዮሐንስ ያጠምቅ የነበረው ጥምቀት የንስሐ ጥምቀት በመሆኑ በኢየሩሳሌምና በይሁደ የነበሩ ሁሉ ኃጢአታቸው እየተናዘዙ ከእርሱ ዘንድ ይጠመቁ ነበር፡፡

ፈሪሳውያን ሊጠመቁ ወደ እርሱ ዘንድ ሲመጡ አይቶ “እናንተ የእፉኝት ልጆች” በማለት ገሰጻቸው፡፡ ከእፉኝት ልጆች ጋር አይሁድን ያመሳስላቸው ያለምክንያት አልነበረም፡፡ እፉኝት አፈማኅፀንዋ ጠባብ ስለሆነ ከወንዱ እፉኝት አባላዘር ከስሜትዋ የተነሣ ስለምትቆርጠው ወንዱ እፉኝት በፅንስ ጊዜ ይሞታል፡፡ የእፉኝት ልጆች አባታቸውን ገድለው ይፀነሳሉ፡፡ ኋላም የመወለጃቸው ጊዜ ሲደርስ ቀደም ተብሎ እንደተገለጸው አፈማኅፀንዋ ጠባብ ስለሆነ የእናታቸውን ሆድ ቀደው ይወጣሉ፡፡ ያን ጊዜ እናታቸው ትሞታለች፡፡ አይሁድም እንደ አባት የሆኑአቸውን ነብያትን /እነኤርሚያስን/ የጌታን ልደት በመናገራቸው ገድለዋቸዋል፡፡ ኋላም እንደ እናት የሚራራላቸውንና የሚወዳቸውን ጌታ ቀንተው ተመቅኝተው ይገድላሉና በእፉኝት ተመሰሉ፡፡

መንፈስ ቅዱስንም በእሳት መስሎ ተናግሯል፡፡ መንፈስ ቅዱስ በእሳት የተመሰለበትም ምክንያት፡-

እሳት ምሉዕ ነው፡፡ በየትም ቦታ ይገኛል፡፡ መንፈስ ቅዱስም ምሉዕ ነው፡፡ የማይገኝበት ሥፍራ የለም፡፡

እሳት በምልዓት ሳለ ቡላድ ክብሪት ካልመቱ አይገለጽም፡፡ መንፈስ ቅዱስም ቋንቋ ሲያናግር፣ ምስጢር ሲያስተረጉም፣ ተአምር ሲያሠራ እንጂ በእኛ ላይ አድሮ ሳለ አይታወቅምና፡፡

እሳት ከመነሻው ማለትም ክብሪት ጭረን ስንለኩሰው በመጠን ነው፡፡ ገለባውን ወረቀቱን እንጨቱን እየጨማመርን ስናቀጣጥለው ግን ኃይሉ እየጨመረ፣ እየሰፋ እየተስፋፋ ይሄዳል፡፡

መንፈስ ቅዱስም መጀመሪያ በ40 ቀን ለወንዶች በ80 ቀን ለሴቶች በጥምቀት ጊዜ ጸጋውን ሲሰጥ በመጠኑ ነው፡፡ ኋላ ግን በገድል በትሩፋት ጸጋ መንፈስ ቅዱስ በሕይወታችን እያደገ ይመጣል፡፡

እሳት የነካው ምግብ ይጣፍጣል፡፡ ማለትም አሳት ጣዕምን መዓዛን ያመጣል፡፡ እንደዚሁም ሁሉ በሕይወታችን ጣዕመ ጸጋንና መዓዛ ጸጋን የምናገኘው በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

  • እሳት በአግባቡ ቢጠቀሙበት ለሰው ልጅ ጥቅም ይውላል፡፡ ዳሩ ግን አያያዙን ካላወቁበት ጉዳቱ ያመዝናል፡፡ መንፈስ ቅዱስም በአግባቡ በወንጌል የተጻፈውን መሠረት አድርገው ለሚመረምሩት ሁሉ ሕይወትን ይሰጣል፡፡ ጸጋን ያጐናጽፋል፡፡ ነገር ግን ከተጻፈው ውጭ በአጉል ፍልስፍና በትዕቢት ሊመረመሩ የሚነሡ ሁሉ ትልቅ ጥፋት በሕይወታቸው ያመጣሉ፡፡

  • እሳት ገለባም ይሁን እንጨት፣ እርጥብ ይሁን ደረቅ ያቀረቡለትን ሁሉ ሳይመርጥ ያቃጥላል፡፡ መንፈስ ቅዱስም በንጹሕ ልቡና ሆኖ ለሚለምነው ሁሉ ሕፃን ዐዋቂ ድኻ ሀብታም ሳይል የጸለዩትን ጸሎት ያቀረቡትን መሥዋዕት ይቀበላል፡፡

  • አሳት የበላው መሬት ለእህል ለተክል ተስማሚ ነው፡፡ ጥሩ ምርት ይገኝበታል፡፡ እንደዚሁም ሁሉ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት ሰውነት ለገድል ለትሩፋት ያመቻል፡፡

  • እሳት ተከፍሎ አይኖርበትም፡፡ ማለትም ከአንዱ የሻማ መብራት ሌላ ሻማ ብናበራ የሻማው መብራት አይጉድልም፡፡ መንፈስ ቅዱስም ተከፍሎ ወይም የጸጋ መጉደል መቀነስ ሳይኖርበት እስከ ምጽአት ድረስ ለምእመናን ጸጋውን ሲሰጥ ይኖራል፡፡

  • ሸክላ ሠሪ ሥራዋን ሠርታ ስትጨርስ ስህተት ያገኘችበት እንደሆነ እንደገና መልሳ ከስክሳ በውኃ ለውሳ በእሳት ታድሰዋለች፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ንጹሕ ሆኖ የተፈጠረ ሰው ከእግዚአብሔር ሕግ ቢወጣና በኃጢአት ቢያድፍ በንስሐ ሳሙና ታጥቦ በመንፈስ ቅዱስ ታድሶ አዲስ ሰው ይሆናል፡፡

መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ ስለአጠመቀው ሲመሰክር ጫማውን እሸከም ዘንድ የማይገባኝ ነኝ ብሏል፡፡ በዚህም የኢየሱስ ክርስቶስን የባሕርይ አምላክነት ተናግሯል፡፡ “መንሹም በእጁ ነው” ሲል ገበሬ በመንሽ ፍሬውን ከገለባው እንደሚለይ ጌታችንም ጻድቃንን ከኃጥአን የመለየት ሥልጣኑ የራሱ ነውና፡፡ በጐተራ መንግሥተ ሰማያትን፣ በስንዴ፣ ጻድቃንን፣ በገለባ፣ ኃጥአንን፣ በማይጠፋ እሳት፣ ገሃነመ እሳትን መስሎ ተናግሯል፡፡

ይጠመቅበት ዘንድ ጌታ በኢየሩሳሌም ካሉት ወንዞች ሁሉ ዮርዳኖስን የመረጠበት ምክንያት፡-

  1. በተነገረው ትንቢት መሠረት ነው፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት ጌታ በዮርዳኖስ ወንዝ በሚጠመቅበት ጊዜ የሚሆነውን አስቀድሞ ተንብዮ ነበር፡፡ ያን ለመፈጸም ነው መዝ.113/114፡3-5፡፡

  2. ምሳሌውን ለመፈጸም ነው፡፡ ኤልያስ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ወደ ብሔረ ሕያዋን እንደ ዐረገ ምእመናንም አምነው ተጠምቀው ገነት መንግሥተ ሰማይ ለመግባታቸው ምሳሌ ነው፡፡

  3. የእምነት አባት አብርሃም ነገሥተ ኮሎዶጎሞርን ድል ነሥቶ ሲመለስ የጌታን ቀን ሊያይ ወደደ፡፡ ጌታም ምሳሌውን ሊያሳየው ዮርዳኖስን ተሻግሮ እንዲሄድ አዘዘው፡፡ ዮርዳኖስን ተሻግሮ ሲሄድ መልከ ጸዴቅ ኅብስተ በረከት ጽዋዓ አኰቴት ይዞ ተቀብሎታል፡፡ አብርሃም የምእመናን ምሳሌ ሲሆን ዮርዳኖስ የጥምቀት ምሳሌ፣ መልከ ጸዴቅ ደግሞ የካህናት፣ የቀሳውስት ኅብስተ በረከት፣ ጽዋዓ አኰቴት የሥጋው የደሙ ምሳሌ ነው ዘፍ.14፡10-20፡፡

  4. የአዳምና የሔዋንን የዕዳ ደብዳቤ ለመደምሰስ ነው፡፡ ዲያብሎስ አዳምና ሔዋንን የባርነት ስማቸውን እንዲጽፉለት አድርጐ የዕዳ ደብዳቤውን አንዱን በሲኦል ሌላውን በዮርዳኖስ ወንዝ አኑሮት ስለነበር ጌታም በዮርዳኖስ ያለውን የዕዳ ደብዳቤ ለመደምሰስ በዚያ ተጠመቀ ቆላ.2፡14፡፡

ጌታችን በተጠመቀ ጊዜ

ሀ. ሰማይ ተከፈተ፣
ለ. አብ በደመና ሆኖ ስለ ወልድ መሰከረ፣
ሐ. መንፈስ ቅዱስም በጥንተ ተፈጥሮ በውኃ ላይ እንደታየ አሁን በሐዲስ ተፈጥሮ ታየ፡፡

ይህም አስተርእዮ /ኤጲፋንያ/ ይባላል፡፡ የእግዚአብሔር አንድነትና ሦስትነት የተገለጠበት ወቅት ነውና የመገለጥ ዘመን ተብሏል፡፡

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 4ኛ ዓመት ቁጥር 1 መስከረም 1989 ዓ.ም.

 

sewa sewe brhan 3

የቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀመዛሙርትን አስመረቀ

 ሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

sewa sewe brhan 3በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በመደበኛና በማታ መርሐ ግብር ትምህርታቸውን የተከታተሉ 212 ደቀመዛሙርትን በዲፕሎማ አስመረቀ፡፡

ሰኔ 21 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተካሔደው የምረቃ መርሐ ግብር ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዲፕሎማና በትምህርታቸው ከፍተኛ ውጤት ላስመዘገቡ ደቀመዛሙርት የተዘጋጀላቸውን ሽልማት ከሰጡ በኋላ ባስተላለፉት ቃለ ምእዳን “ቤተ ክርስቲያን ከአጽናፈ ዓለም አሰባስባ፤ አስተምራ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት ልታሰማራችሁ በዝግጅት ላይ ቆይታችኋል፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያናችን ትልቅ ሐብት በመሆኑ ያገኛችሁትን እውቀት ለወገኖቻችሁ እንድታካፍሉና ቤተ ክርስቲያን የጣለችባችሁን ሓላፊነት እንድትወጡ አደራ እላለሁ” ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ያሬድ የሰዋሰወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ፤ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ፤ የሶማሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ደቀመዛሙርቱ መንፈሳዊ ትምህርት ሲከታተሉ ቆይተው ቤተ ክርስቲያን ለማገልገል የሚዘጋጁበት ወቅት እንደሆነ አስታውሰው፤ በአባቶች ቡራኬ ለመመረቅ በመብቃታቸው እንኳን አደረሳችሁ በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የኮሌጁ ዲን መጋቤ ጥበብ ምናሴ ወልደ ሃና ባቀረቡት ሪፖርት በመማር ማስተማሩ ሂደት ያጋጠሟቸውን ችግሮች ላይ ትኩረት በማድረግ በዝርዝር አቅርበዋል፡፡ በዚህም መሠረት መምህራን ሲለቁ በቦታቸው ቶሎ ተተኪ ያለመመደብ፤ የሚመሩ ደብዳቤዎች ባልታወቀ ሁኔታ መጥፋት፤ ኮሌጁ ለሚጽፋቸው ደብዳቤዎች ምላሽ ያለማግኘት፤ የሥራ ጣልቃ ገብነት ጎልተው ከሚታዩት ችግሮች ውስጥ እንደሚገኙበት ጠቁመዋል፡፡

ኮሌጁ ምሁራንን እያፈራ የሚገኝ ቢሆንም ዘመኑን ባልተከተለ አሠራር እየተጓዘ ከአባቶች እንደተረከብነው ለተተኪ ትውልድ ማስተላለፍ እንችላለን ወይ? በሚል ጥያቄ ውስጥ እንደሚገኙም መጋቤ ጥበብ ምናሴ ስጋታቸውን ገልጸዋል፡፡ ኮሌጁ በየዓመቱ የሚቀበላቸው ደቀመዛሙርት ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ መምጣቱም እንደማሳያነት ጠቅሰዋል፡፡

sewa sewe brhan 2ከተመራቂ ደቀ መዛሙርቱ መካከል አባ ኪሮስ ወልደ አብ የትምህርት ቆይታቸውን አስመልክቶ የተሰማቸው ስሜት ሲገለጡ “ትምህርት ጀመርኩ እንጂ አልጨረስኩትም፤ የበለጠ እንድማር አነሳሥቶኛልና እቀጥልበታለሁ፡፡ በኮሌጁ ቆይታዬም በእቅድ መመራት በመቻሌ በጥሩ ሁኔታ ተምሬ በማዕረግ ለመመረቅ ችያለሁ” ብለዋል፡፡

 

ተመራቂ ደቀመዛሙርት ያወጡትን የጋራ መግለጫ በተወካያቸው አማካይነት ያቀረቡ ሲሆን፤ በኮሌጁ ውስጥ አንዳንድ መልካም ሥራዎች ቢኖሩም በኮሌጁ ቆይታቸው በስፋት ይታያሉ ያሏቸውን ችግሮች ዳስሰዋል፡፡ የትምህርት አሠጣጡ ዘመኑን የዋጀsewa sewe brhan 1 ያለመሆን፤ ለመምህራን በቂ ደሞዝ ያለመከፈል፤ ከሌሎች መሰል የቤተ ክርስቲያኒቱ ኮሌጆች ጋር የልምድ ልውውጥ ያለማድረግ፤ በቤተ መጻሕፍቱ ውስጥ የሚገኙ መጻሕፍት በቂ ያለመሆናቸው፤ የመደበኛ ተማሪዎች ቁጥር መቀነስ እንደ ችግር ከጠቀሷቸው ውስጥ ይገኙበታል፡፡

ደቀመዛሙርቱ እንደመፍትሔ ካቀረቧቸው ውስጥ፤ የትምህርት አሰጣጡ በሚመጥን መልኩ ቢቀረጽ፤ ተቋማዊ አቅሙን ወደ ዩኒቨርስቲነት ቢያሳድግ፤ በከፍተኛ ውጤት ለሚመረቁ ደቀመዛሙርት የነጻ ትምህርት እድል ቢመቻች የሚሉት ሐሳቦች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡

ከ212 ተመራቂ ደቀ መዛሙርት መካከል 12ቱ በመደበኛነት ትምህርታቸውን የተከታተሉ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ አንድ በብሉያት፤ አንድ በሐዲሳት ትርጓሜ የተመረቁ ናቸው፡፡ 200 ደቀመዛሙርት ደግሞ በማታው የትምህርት መርሐ ግብር ትምህርታቸውን የተከታተሉ ናቸው፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የኮሌጁ መምህራንና የተመራቂ ደቀመዛሙርት ቤተሰቦች ተገኝተዋል፡፡

 

የሚዛን ተፈሪ ማዕከል 14ኛውን ጠቅላላ ጉባኤ አካሄደ

 

ሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም.

በሚዛን ተፈሪ ማዕከል ሚዲያ ክፍል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን የሚዛን ተፊሪ ማዕከል ከሰኔ 13 እስከ 15 2006 ዓ.ም 14ኛውን ጠቅላላ ጉባኤ በአቡነ ተክለ ሃይማኖትና ቅዱስ ኡራኤል የእናቶች አንድነት ገዳም የስብከተ ወንጌል አዳራሽ አካሄደ፡፡

ሦስት ቀናት በፈጀው ጉባኤ የማእከሉ 2006 ዓ.ም ሥራ አፈጻጸም ሪፖርት በማዕከሉ ሰብሳቢ በአቶ መስፍን ደጉ የቀረበ ሲሆን፤ በእቅድ አፈጻጸሙ በተገቢው ሁኔታ የተከናወኑትን፤ ያጋጠሙ ችግሮች ፤ የተወሰዱ የመፍትሄ ሃሳቦች እና ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች በሪፖርቱ ተካተዋል፡፡

አብዛኛዎቹ ችግሮች ከአባላት የአገልግሎት ዝለት ጋር የተያያዙ በመሆናቸው ክፍሎች ያቀዷቸውን እቅዶች አባላት የማስፈጸም አቅማቸዉ ያልተመጣጠነ መሆኑም ተጠቁሟል፡፡

በቀረበው ሪፖርት መሠረት የተሻለ የእቅድ አፈጻጸም እንዲሁም ዝቅተኛ የዕቅድ አፈጻጸም ያሳዩ ክፍሎችም ተለይተዋል፡፡ በዚህም መሠረት ለ2007 ዓ.ም. ክፍሎች ራሳቸውን በማጠናከር ያቀዷቸውን እቅዶች ተግባራዊ በማድረግ ጠንክረው እንዲሰሩ ማሳሰቢያ ተሰጥቷል፡፡

የ2007 ዓ.ም ዕቅድ በማዕከሉ የዕቅድ ዝግጅትና ከትትል ክፍል ቀርቦም በውይይት በማዳበር ማስተካከያ ተደርጎበት ጸድቋል፡፡

ከማእከሉ አባላት በተጨማሪም ከሀገረ ስብከት፣ ከወረዳ ቤተ ክህነት፣ ከዋናው ማዕከል፣ ከምዕራብ ማዕከላት ማስተባበርያ፣ ከወረዳ ማዕከላት፣ ከግቢ ጉባኤያትና ከግንኙነት ጣብያዎች ተወክለው የመጡ እንግዶች በጉባኤው ላይ ተሳታፊ ሆነዋል፡፡

 

 

በንባብ ባሕል ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጽሑፎች ይቀርባሉ

ሰኔ 23 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የንባብ ባሕልን ለማሳደግ በሚቻልበት ሁኔታ ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጽሑፎች በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አዘጋጅነት ሰኔ 28 ቀን 2006 ዓ.ም ከ8፡00-11፡00 ሰዓት በማኅበሩ ሕንፃ ላይ እንደሚቀርቡ ማእከሉ አስታወቀ፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ምሁራን የሚቀርቡት ጥናታዊ ጽሑፎች ሁለት ሲሆኑ፤ “ትርጉም ያለው የንባብ ባሕል”፤ እንዲሁም “የንባብ ባሕልን ለማሳደግ የተለያዩ አካላት ሚና” በሚሉ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ትኩረት እንደሚያረጉ የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ሰይፈ አበበ ገልጸዋል፡፡

ትርጉም ያለው ንባብ ምንድን ነው? የንባብ ባሕልን ያሳደጉ አገራት ልምድ ምን ይመስላል? የንባብ ልምድ በሀገራችን እና በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ምን እንደሚመስሉ በጥናቶቹ ይዳሰሳሉ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል በየዓመቱ በሀገራችን የንባብ ባሕልን ለማበረታታት ከሚያዘጋጀው የመርሐ ግብር አካል አንዱ ሲሆን፤ ጥናቶቹም የንባብ ባሕላችን ምን ላይ እንደሚገኝ የሚዳስሱና የሚያነብ ትውልድን ለመፍጠር ምን መደረግ እንዳለበት የሚያመላክቱ መሆናቸውን አቶ ሰይፈ ጠቁመዋል፡፡

ይህ የንባብ ጉባኤ ለሦስተኛ ጊዜ የተዘጋጀ ሲሆን፤ በመርሐ ግብሩ በንባብ ባሕል ላይ የሚሠሩ አካላት፣ ምሁራን፤ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት እና ጥሪ የተደረገላቸው አካላት፤ እንዲሁም ምእመናን ተሳታፊ ይሆናሉ፡፡

 

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት መጽሔት ቊ.፫/፳፻፭ ዳሠሣ

ሰኔ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በዐለም መድረክ የምትታወቀው በጥንታዊነቷ ብቻ ሳይሆን አርቆ አሳቢና ጥበበኛ በሆኑ ሊቃውንት አባቶች አማካኝነት፣ ለዘመናት ተጠብቀው በቆዩ ቁሳዊና ቁሳዊ ባልሆኑ መንፈሳዊ ሀብታት ጭምር ነው፡፡ እነዚህ የቤተክርስቲያን አባቶች በየገዳማቱና አድባራቱ ጠብቀው ያቆዩት የእውቅት ሀብት በዚህ ዘመን ለጥናትና ምርምር ከፍተኛ ምንጭና ገና ያልተነካ የጥናት መዳራሻ ነው፡፡ እነዚህ አባቶች በየድርሳናቱ፣ በየጽሑፉ፤ በሥዕላት እና በቅርሶች ከትበው ያቆዩትን ዕውቀትና ጥበብ ለቤተ ክርስቲያን ልጆችና ለሣይንሱ ማኅበረሰብ ለማስተላለፍ የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የጥናት መጽሔት አሳትሞ ማሠራጨት ከጀመረ ሦስት ዐመታት አልፈዋል፡፡ በዚህ ዐላማ መሠረት ለሦስተኛ ጊዜ ያዘጋጀውን የጥናት መጽሔት በቅርብ ጊዜ አሳትሞ ለሥርጭት አብቅቷል፡፡ ይኽ ሦስተኛ ዕትም ሰባት ጥናታዊ ጽሑፎችን የያዘ ሲሆን ሦስቱ በዐማርኛ ቋንቋ፣ ዐራቱ ደግሞ በእንግሊዘኛ ቋንቋ የተዘጋጁ ናቸው፡፡

የመጀመሪያው ጽሑፍ በሊቀ ኅሩያን በላይ መኮንን የተዘጋጀ ሲኾን ጸሐፊው በቅዱስ ያሬድ ሕይወትና ሥራዎች ዙሪያ የተሠሩ ጥናቶችና ምርምሮች እርስ በርሳቸው ያላቸውን ተዛማጅነትና ልዩነት በጥንቃቄ በመቃኘትና በመረጃ ላይ በመመሥረት የሐሳብ ልዩነታቸውን ለማጥበብ የሞከሩበት ጥናት ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ጥናቱ በቅዱስ ያሬድ የዜማ መጻሕፍትና ትምህርት የተንጸባረቁትን የቅዱስ ያሬድን ኹለንተናዊ አስተምህሮ ከነገረ መለኮት አንጻር ይተነትናል፡፡ ከጥናቱ ግኝቶች መካከል ለኢትዮጵያ ሊቃውንት የዕውቀታቸው፣ የብቃታቸውና የፍልስፍናቸው ልዩ መገለጫ የሆነው የግእዝ ቅኔ ከዜማ ድርሰት ጋር እንደ ተጀመረ በጥናቱ ታይቷል፡፡ በጥናቱ የታየው ዐዲስ ግኝት ደግሞ የቅዱስ ያሬድ የዜማ ድርሰት ለዐማረኛ የግጥም ምጣኔ /ልኬት/ መሠረት መኾኑን ነው፡፡

ቀጣዩ ጽሑፍ የቤተ ክርስቲያንን አሻራ በሸካቾ ብሔረሰብ ውስጥ የሚዳሥሥ ሲኾን የተጻፈውም በቀሲስ ወንድምስሻ አየለ ነው፡፡ ጸሐፊው በጥናታዊ ጽሑፋቸው በብሔረሰቡ የትበሀል፣ ሥርዐተ አምልኮ፣ የባዐላትና የክብረ ቅዱሳን ዕለታት አካባበር፣ የቦታና የቅዱሳን ስያሜ እንዲሁም የቀን አቆጣጠር አደረጃጀትና ስያሜ ላይ ቤተክርስቲያን ያላትን ጉልህ አሻራ በሰፊው ዳሥሥዋል፡፡ በማጠቃለያም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሌሎች ብሔር ብሔረሰቦች ባህል፣ ታሪክና ቋንቋ ላይ ያላትን አሻራ ለማሳየት በሸካቾ ብሔረሰብ የታየው የቤተ ክርስቲያን አሻራ ጠንካራ ማሳያ ሊኾን እንደሚችል በመጠቆም ጽሑፋቸውን ይቋጫሉ፡፡

በዶ/ር ዐለማየሁ ዋሴ የተጻፈው ሥስተኛው ጽሑፍ የተለያዩ የዕፅዋት ዝርያዎችና እንስሳት እንዲሁም ለሰዎች መገለገያ የሆኑ የአረንጓደ ተፈጥሮ ቦታ መገኛ የሆኑ ተፈጥሯዊ ደኖችን በመጠበቅ ቤተ ክርስቲያን ያላትን ረጅም ታሪክና ልዩ ድርሻ የሚዳሥሥ ነው፡፡ ጸሓፊው አብያተ ክርስቲያናት እግዚአብሔርን ማምለክና ሃይማኖታዊ ተግባር መፈጸም ተቀዳሚ ዐላማቸው /ተግባራቸው/ ቢሆንም በዋጋ ሊተመን የማይቻል ልዩ የኾኑና ጥብቅ ሥነ ሕይወታዊ ቦታዎች መገኛ ማእከል በመኾን እንደሚያገለግሉ ይገልጻሉ፡፡ አጥኝው የቤተ ክርስቲያን ደኖች የሀገር በቀለ ዝርያዎችን ያካተቱ ቀደምትና እየጠፉ ያሉ ዛፎች ቅሪት መኾናቸውን አንክሮ በመሥጠት ያስረዳሉ፡፡ እነዚህ ደኖች ክብር ያላቸው የሃይማኖት ቦታዎች ኾነው እንደሚቀጥሉ ሁሉ ተፈጥሯዊ ጥብቅ ደኖችን በመጠበቅም ቀዳሚ ትኩረት ሊያገኙ እንደሚገባ አበክረው ያስረዳሉ፡፡ የሰሜን ኢትዮጵያ ከፍተኛ ቦታዎችን የጥናት ቦታቸው ወሰን በማድረግ የቤተ ክርስቲያኗ ደኖች ባጋጣሚ ተጠብቀው የቆዩ ሳይኾኑ የጥበቃ ጥረታቸውን ሥነ መለኮታዊና መጽሐፍ ቅዱሳዊ አመክንዮ በሚሠጡ የቤተ ክርስቲያኗ ቁርጠኛ ምእመናን/ተከታዮች/ ጥብቅ ጥበቃና ጥረት መኾኑን ይተነትናሉ፡፡ በመጨረሻም አጥኝው በእነዚህ የቤተ ክርስቲያኗ ደኖች ላይ በዛ ያሉ ሥነ ምኅዳራዊና ማኅበረሰባዊ ተፅዕኖዎች እየተጋረጡባቸው እንደኆነ በመግለጽ የመፍትሔ ሐሳብ አስቀምጠዋል፡፡

ይኽ ጥናት በቤተ ክርስቲያን ደኖች ላይ የተጋረጡትን አደጋዎች የሚገልጽ ሲሆን ቀጣዩ የዶ/ር ጥጋብ በዜ ጥናት ደግሞ ቤተ ክርስቲያን እየገጠማት ያለው ሌላኛውን የተግዳሮት ገጽ ያሳየናል፡፡ የመጀመሪያው ተግዳሮት ውስጣዊ፣ ሁለተኛው ደግሞ ዐለማቀፋዊ ይዘት ያለው ሲኾን የሁለቱም ተግዳሮቶች መነሻ ግን በክብካቤ እና የጥበቃ ጉድለት ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከክርስትና መጀመር ጀምሮ በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ስለነበራት ይዞታ በመተንተን ዶ/ር ጥጋብ ብቸኛውንና ዋንኛውን የቤተ ክርስቲያን ይዞታ ማለትም ዴር ሡልጣንን በተመለከተ ስላለው ያልተረጋጋ ሁኔታ በዎፍ በረር ያስቃኙናል፡፡ በጥናቱ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በቅድስት ሀገር የሚገኙ ይዞታዎቻቸውን እንዴት እንዳጡና ከ፲፱ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ ይኽን ቅዱስ ሥፍራ ለማስጠበቅ ከግብጾች ጋር በምን ዐይነት የተንዛዛ ክርክር እንደተጠመዱ ይተርኩልናል፡፡

ወደ ቀጣዩ ጥናት ሥናልፍ ደግሞ በዝዋይ ሐይቅ በሚገኙ ገዳምና አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ ያሉ ጥንታዊ ቅርሶች ላይ ትኩረት አድርጎ የተሠራውን የአቶ ቡሩክ ወልደ ሰማያትን ጥናት እናገኛለን፡፡ ጥናቱ በዝዋይ ደሴያት ውስጥ በሚገኙ ቅዱሳት መካናት የሚገኙ በዋጋ ሊተመኑ ያማይቻሉ ቅዱሳት መጻሕፍትና ንዋያተ ቅዱሳት ዙሪያ ያጠነጥናል፡፡ የጥናቱ አዘጋጅ በቦታው የሚገኙ ጥንታዊ ቅርሶችን በዝርዝር በማስቀመጥና ቅርሶቹ በቊጥር ብዙ፣ በዐይነት ግን የማይተኩ መኾናቸውንና የአጠባበቅና የአያያዝ ሥርዐቱ በቂ ያለመኾኑን በመግለጽ ሊወሰዱ ይገባቸዋል የሚሏቸውን የመፍትሔ ሐሳቦች በመጠቆም ጥናቱን ይቋጫሉ፡፡

በአቶ ሒንጋቡ ሖርዶፋ የተዘጋጀው ስድስተኛው የጥናት ወረቀት በደብረ ሊባኖስ ገዳም ውስጥ በሚገኙ የዕፅዋት ዐይነቶች፣ አጠቃላይ መዋቅርና ብዝኀ ሕይወት ላይ የሚያጠነጥን ነው፡፡ የጽሑፉ ዋና ዐላማም በገዳሙ ውስጥና በአካባቢው ያሉ የዕፅዋት ዘሮችንና አትክልቶችን ዐይነት፣ ስብጥርና መዋቅር መዳሠሥ ነው፡፡ ጥናቱ በገዳሙ ደን ውስጥ ያለው የዕፅዋት ዐይነትና ስብጥር በመንግሥትና በግል ከተያዙት የደን ልማቶች በተሻለ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ አረጋግጧል፡፡ በተጨማሪም በገዳሙ ደን ውስጥ ያሉት የዕፅዋት ዝርያ ልዩ መኾንና ተፈጥሮዊ ስብጥር (መስተጋብር) ጉላ ያለ መኾኑን አሳይቷል፡፡ በመጨረሻም የገዳሙ ደን ከዚህ በተሻለ ትኩረት ቢጠበቅ በውስጡ ያለው ብዝኀ ሕይወት የተፈጥሮን ሚዛን ለመጠበቅና እንደገና ሞተው ሊነሡ የማይችሉ ውድ የዛፍ ዐይነቶች እንዳይጠፉ በመከላከል ረገድ ትልቅ ሚና እንደሚጫወት በመጠቆም ጥናቱን አጠቃልሏል፡፡

በአቶ ዮሐንስ አድገህ የቀረበው የመጨረሻውና ሰባተኛው የጥናት ወረቀት ደግሞ ኦሮምኛ ቋንቋን ለኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ትምህርትና ሃይማኖታዊ አገለግሎት በመጠቀም ረገድ ያሉ ተግዳሮቶችንና ምቹ ኹኔታዎችን ይተነትናል፡፡ ጥናቱ የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ እንደ ተቋም በአጠቃላይ በአፍ መፍቻ ቋንቋ ትምህርት፣ በተለይም በኦሮምኛ ቋንቋ ጠቀሜታ ላይ ያላትን በጎ (አዎንታዊ) አመለካከት አሳይቷል፡፡ ሆኖም ግን የሃይማኖቱን ጽንሰ ሐሳብ የሚሸከሙ አቻ ሙያዊ ቃላት እጥረት፣ የገንዘብና የሰው ሀብት እጥረት፣ ቤተ ክርስቲያን ግልጽ የኾነ የቋንቋ መመርያ የሌላት መኾኑ፣ የተወሰኑ የቤተ ክርስቲያን ሓላፊዎች በአፍ መፍቻ ቋንቋ ትምህርት ላይ ያላቸው የግዛቤ እጥረት፣ የቋንቋ መብዛት ለሀገር አንድነት እንቅፋት ይኾናል የሚል ፍርሃትና የመሳሰሉት የኦሮምኛ ቋንቋ በቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አግልግሎት ላይ በሚጠበቅበት ደራጃ እንዳያገለግል ተግዳሮቶች መኾናቸውን ጥናቱ አመልክቷል፡፡ ይሁን እንጂ ጥናቱ፣ የኦሮምኛ ቋንቋ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ ጥቅም ላይ መዋሉ እየጎለበተ መምጣቱንና በተለይም ማኅበረ ቅዱሳን የኦሮምኛ ቋንቋን በመጠቀም በኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙኃን የቋንቋውን ተናጋሪዎች ለመድረሥ እየተጋ እንደሚገኝ ጠቁሟል፡፡ በመጨረሻም በአፍ መፍቻ ቋንቋ መጠቀም ያለውን ሥነ ትምህርታዊ፣ ሥነ ልቡናዊና ሥነ ማኅበራዊ ጠቀሜታ በመገንዘብ፣ ቤተ ክርስቲያን ኦሮምኛንም ኾነ ለሌሎችንም የሀገሪቱን ቋንቋዎች በመጠቀም ብዙኃኑን ምእመን ማስተማር እንዳለባት በማሳሰብ ጥናቱን ቋጭቷል፡፡

እንግዲህ ለመነሻ ይህን ያህል ካልን ሙሉውን ጽሑፍ ከጥናት መጽሔቱ እንዲያንቡ መልእክታችን ነው፡፡ ጥናት መጽሔቱን ለማግኘትና ጥያቄ ካልዎት በ mkidusantmaekel@yahoo.com ወይንም በ +251-11-155-99-34 ሊያገኙን ይችላሉ፡፡

 

st mary2

በወርቅ ከተለበጠው በድንጋይ ወደ ታነፀው

ሰኔ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መላክ

በምዕራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

st mary2የመጀመሪያውን የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ለመሥራት ከጥንት ሰዎች የተፈቀደው ለሰሎሞን ነው፡፡ ሰሎሞን የተወለደበት ዘመን በንጉሡ ዳዊትና በእግዚአብሔር መካከል የነበረው ጥል ተወግዶ ፍቅር የተመሠረተበት የፍቅር ወቅት ነበር፡፡ በደለኛነቱ በነቢይ የተረጋገጠበት ንጉሥ ዳዊት በበደለኛነቱ ወቅት ከኦርዮን ሚስት በወለደው ልጁ ሞት ምክንያት የእርሱ ሞት ወደ ልጁ ተዛውሮለት እርሱ ከሞት እንዲድን ሆኗል፡፡ የእርሱን ሞት ልጁ ወስዶለት የልጁ ሕይወት ለእርሱ ተሰጥቶታል፡፡ ከዚህ ልጅ ሞት በኋላ ያለው ዘመን የሰላምና የእርቅ ዘመን በመሆኑ የተወለደው ልጅ ሰሎሞን ተብሎ ተጠራ፤ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደ የፍቅር ስም ነው፤1ኛ ነገ12÷24

የንጉሡ ዳዊት ንስሐ ለመጀመሪያው ጊዜ ቤተ መቅደስ በምድር ላይ ለመሥራት ምክንያት ነው፡፡ የምድር ሁሉ ንጉሥ ሆኖ ተሾሞ የነበረው አባታችን አዳም በደለኛ ሳለ በገባው ንስሐ ምክንያት የአምስት ቀን ተኩል (5500 ዘመን) ቀኖናውን ሲፈጽም የተወለደለት አንድ ልጁ ክርስቶስ የእርሱን ሞት ሞቶለት፣ የራሱን ሕይወት ለአዳም ሰጥቶት ባደረገው ካሳ በአዳምና በእግዚአብሔር መካከል ለተፈጠረው ሰላምና ፍቅር መገለጫ የሚሆን ቤተ መቅደስ በሰዎች መካከል ተሠርቷል፡፡ ዘመኑ ከጌታ ልደት በኋላ ሃምሳ አራት ዓመት ገደማ እመቤታችን ባረገች በአራት ዓመት ወንጌልን ለመስማት ከአውሮፓ ከተሞች የሚቀድማት የሌለው እና በመቄዶንያ አውራጃ የምትገኘዋ ግሪካዊቷ የፊልጶስ ከተማ ፊልጵስዩስ፤ በቅዱስ ጳውሎስ ሁለተኛው የወንጌል ጉዞ ወቅት ወንጌልን ሰምታ ካመነች በኋላ የመጀመሪያው የቤተ መቅደስ ሥራ በመካከሏ ተፈጽሞላታል፡፡

ክርስቶስ በምድር ላይ ሰውን የእግዚአብሔር ማደሪያ ቤተ መቅደስ ለማድረግ ሲተጋ ነበር ማደሪያ የሚሆነው ምድራዊ ድንኳን አልሠራም፡፡ ክርስቶስ የመጣው ሰውን ለመሥራት እንጂ በሰማይ ማደሪያ የሌለው ሆኖ ማደሪያ ፍለጋ የመጣ አይደለምና እንዲሁም ጊዜው ገና ስለነበር መጀመሪያ መሠራት ያለበት ሰው ነበር፡፡

ጊዜው ሲደርስ ከላይ በተጠቀሰው ዘመን ቅዱስ ጳውሎስና ቅዱስ በርናባስ አስተምረው ባሳመኗት ከተማ መካከል በጥበበ እግዚአብሔር አዲስ ሕንፃ ለእግዚአብሔር ማደሪያነት ተገነባ፡፡ እስከዚያ ቀን ድረስ ሐዋርያትና ሌሎችም ደቀ መዛሙርት ለመሰብሰቢያነት ይጠቀሙበት የነበረው ካታኮምብ (ግበበ ምድር) ካልሆነ ለክርስቲያኖች ተብሎ የተገነባ ልዩ ሥፍራ አልነበረም፡፡ የአህዛብ መምህር ሆኖ የተመረጠው ቅዱስ ጳውሎስ እስኪነሣ ድረስ ከሐዋርያት አንዳቸውም ለዚህ አገልግሎት አልተመረጡም፡፡ ለእግዚአብሔር ሰዎች የተሰጣቸው ጸጋ ልዩ ልዩ ነውና በአሕዛብ መካከል ቤተ እግዚአብሔር እንዲሠራ የተፈቀደው ለቅዱስ ጳውሎስ ነው፡፡

እርሱ ወንጌልን ሰብኮ ወደ ሌሎቹ ሀገራት ዘወር ሲል ሕዝቡ ተሰብስበው አንድ ጥያቄ ጠየቁ፤ ወደ ቤተ ጣዖት እንዳንሔድ ከልክላችሁናል፤ ሥርዓተ አምልኮ የምንፈጽምበት ቤት ልትሠሩልን ይገባል ብለው ጠየቋቸው፡፡ ጳውሎስና በርናባስ ከሌሎቹ ሐዋርያት ጋር ተማክረው ወደ እግዚአብሔር አመለከቱ፤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰኔ በሃያ ቀን ወርዶ ሐዋርያትን ባንድ ቦታ ሰብስቦ፣ ከተራራ ላይ የተቀመጡ ሦስት ድንጋዮችን ጠቅሶ ወደ እርሱ በማቅረብ ቅድስት፣ መቅደስ፣ ቅኔ ማኅሌት አድርጎ ሠርቶላቸዋል፡፡

ቤተ እግዚአብሔር ለመጀመሪያ ጊዜ ከቤተ እስራኤል ውጭ ተሠራች፤ ከከበሩ እና ተጠርበው አምረው ከቀረቡ ክቡራን ድንጋዮች ሳይሆን ተራራ ላይ ተቀምጠው ከሚኖሩ ተራ ድንጋዮች ተገነባች፡፡ በወርቅ ከተለበጠው በድንጋይ ወደ ታነፀው ተዛወረች፤ በዝግባና በጽድ የታነፀው አገልግሎት ከመስጠት ተከለከለ፤ በጢሮሳዊ የአልባስጥሮስ ግምጃ የተሸፈነው ተናቀ በነኪራም ብልሃት፣ በነባስልኤልና ኤልያብ ጥበብ የተጌጠው የጸሎት ቤት ክብሩን ለቀቀ፤ ሁሉም ነገር ከተጠበቀው ውጭ ሆነ፡፡

በዚህ ሁሉ ነገር ውስጥ የእግዚአብሔር መልዕክት ምንድነው?

ቤተ መቅደሱ በድንጋይ ለምን ተሠራ? ከመሠረት እስከ ጣራና ጉልላት ሌላ ነገር አልተጨመረበትም፤ ድንጋዮቹም ሦስት ብቻ ናቸው፡፡ እግዚአብሔር በአዲስ ኪዳን ዘመን በድንጋይ ላይ የሠራቸው አስደናቂ ነገሮች የተለዩ ናቸው፤ የቃና ዘገሊላውን ተአምር የተመለከትን እንደሆነ፤ የቢታንያ ድንጋዮችንም ያነሣን እንደሆነ በእነርሱ የተደረገው ነገር ድንቅ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ያልተደረገ፣ ወደፊትም የማይደረግ ድንቅ ተአምር በነዚህ ድንጋዮች ውስጥ ሲደረግ እናያለን፡፡ እግዚአብሔር ሊሠራ ከወደደ በድንጋይ ልብ ውስጥም ሥራ መሥራት እንደሚችል አሳየን፡፡ ቀድሞ በነቢያቱ ዘመን ዮናስን በባሕር ልብ ውስጥ አስገብቶ እንዲዘምር አደረገ፣ ኢያሱ ሥራውን እስኪጨርስ ፀሐይን አቆመ፣ በእኛም ዘመን የአቡነ ዘርዐ ቡሩክን የጸሎት መጻሕፍት እስከወደዱት ዘመን ድረስ በዐባይ ውኃ ጉያ ውስጥ ደብቆ አቆየ፡፡

ድንጋይ ሲፈልጡት ይፈለጣል፣ ሲረግጡት ይረገጣል እንጂ መች ቀድሶ ያውቃል? መች ወንጌል ሰብኮ ያውቃል? በቢታንያ የቆመው የድንጋይ ምሰሶ ግን ይሁዳ ንስሐ እንዲገባ ተግቶ የሰበከ ብቸኛ ሐዋርያ ነው፡፡

የክርስቶስ ወደ ዓለም የመምጣት ምክንያት ይህ ነበር፡፡ እንደ ድንጋይ ኃጢአት ያፈዘዘው አዕምሯችንን ሕይወት እንዲኖረው ማድረግ! ድንጋይ ከውጪ እንጂ ከቤት ውስጥ ምን ሙያ አለው? እኛ ሁላችንም በእግዚአብሔር ቤት ውስጥ ሙያ ታጥቶልን በውጭ እንድንጣል የተደረግን ሰዎች ነበርን፤ እንዲህ እንደ ድንጋይ ያለ ፈዛዛ ታሪክ በነበረን ወራት የተወለደው የማዕዘኑ ራስ ክርስቶስ በእኛ በድንጋዮች አድሮ ሥራ እንደሚሠራ ለማስረዳት ለልዩ ልዩ አገልግሎት ድንጋይን ሲጠቀም እንመለከተዋለን፡፡ የበረሃው ሰባኪ ቃለ ዓዋዲ ዮሐንስ እስራኤልን ሲገስጽ ‹‹እብለክሙ ከመ ይክል እግዚአብሔር እምዕላንቱ አዕባን አንሥኦ ውሉድ ለአብርሃም፤ እግዚአብሔር ከነዚህ ድንጋዮች ለአብርሃም ልጅ ማሥነሳት እንደሚችል በእውነት እነግራችኋለሁ›› ማቴ3÷9 እያለ አብርሃም አባት አለን በማለት ብቻ ሊጸድቁ የሚያስቡትን ይዘልፋቸው ነበር፡፡ ሲጀመር ለአብርሃም የተገባው ቃል ኪዳን እንደ ሰማይ ከዋክብት ለሆኑት ልጆቹ ብቻ መች ሆነና! እንደ ባሕር አሸዋ በምድር ላይ ለተነጠፉት ልጆቹም ነው እንጂ፡፡

በእውነት ድንጋዮችን ልጅ አድርጎ ለአብርሃም የሚያስነሣበት ዘመን እንደደረሰ እንዲታወቅ በእነዚህ ድንጋዮች ቤቱን ሠራ፡፡ እኒህ ድንጋዮች እኮ የአሕዛብ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ የሰሎሞን ቤተ መቅደስ በከበሩ ድንጋዮች የተሠራ፣ በዋንዛ፣ በጽድ፣ በዝግባ የተዋበ፣ በወርቅ የተለበጠ ነበር 1ኛነገ. 6÷7፡፡ ለዚህ ግን እነዚህ ሁሉ ጌጣ ጌጦች አላስፈለጉትም፤ ድንጋዮች በቂ ነበሩና፡፡ ለክርስትና የጥንቶቹ ሊቃነ ካህናት ሌዋውያንና ፈሪሳውያን አያስፈልጉትም፤ እግዚአብሔር ከመረጣቸው አሕዛብ ቤተ መቅደሱን ለመሙላት አላስቸገረም፡፡

ከድንጋይስ ምን አለበት የከበሩ ድንጋዮችን ቢመርጥ ኖሮ ሊባል ይቻል ይሆናል፤ ተራራው ላይ ሥራ አጥተው የተቀመጡትን ድንጋዮች ሥራ መስጠትኮ ነው የክርስቶስ ዓላማ፡፡ በማለዳም፣ በሦስት ሰዓትም፣ በቀትርም፣ እስከ ማታ ለወይኑ ቦታ ሠራተኞችን ሊስማማ በወጣ ጊዜ የተዋዋላቸው ሰዎች ሥራ ፈቶች አልነበሩምን? ማቴ20÷1 አሁንስ ለቤቱ የመረጣቸው ድንጋዮች በሰው ዘንድ ያልታሰቡ ቢሆኑ ምን ይገርማል፤ ለክርስቶስ ማደሪያነት ከቤተ አይሁድ ቀድሞ የሚገኝ አለ ተብሎ በሰው ዘንድ ታስቦ ያውቅ ነበር? አሕዛብን እግዚአብሔር ከውሻነት አውጥቶ ልጆች ያደርጋቸዋል ብሎ ማን አስቦ ኖሯል? እግዚአብሔር ብቻ ነው እንጂ፤ ማቴ15÷26፡፡

ዳሩ ግን ሰው እንዳሰበው አልሆነም፤ በቃሉ የጠራቸውን ሦስቱን ድንጋዮች እንዲበቁ አደረጋቸው፤ እርሱ ይበቃል ያለው ይበቃል፤ የከለከለው ደግሞ ወርቅም ቢሆንም ተልጦ ይወድቃል፡፡ ሲፈቀድለት ጣዖት አጣኙ የሞዓብ ልጅ የእግዚአብሔር ካህን ሆኖ ተሾመ፤ ባይፈቀድለት የወርቁን ማዕጠንት በእጁ ይዞ የቃል ኪዳኑን ታቦት ሲያጥን የኖረው የአሮን ልጅ ተከለከለ፤ የእግዚአብሔር ሥራው ድንቅ ነው፡፡

የመጀመሪያው ቤተ መቅደስ ለምን በአሕዛብ ከተማ ተሠራ? አሕዛብ አማልክቶቻቸው ብዙ፣ አጋንንቶቻቸው ብዙ ናቸው፤ ቅዱስ ኤፍሬም እንደተናገረው ኃጢአት ብትበዛባቸው፤ ጸጋ እግዚአብሔር በዝታላቸው ብዙ ነገሮችን ከእስራኤል ቀድመው አግኝተዋል፡፡ ከአዳም ቀድሞ ገነት የገባው ፈያታዊ ዘይማን ከአሕዛብ ወገን ነበር፤ እስራኤል ሞትን ለፈረዱበት ጌታ ምንም እንኳን ማዳን ባይቻለውም ብቻውን የተከራከረለት ጲላጦስም ከአሕዛብ ወገን ነበር፡፡ የመጀመሪያውን የቡራኬ ሥራም የጀመረው በአሕዛብ ሀገር በግብፅ ገዳማት በገዳመ አስቄጥስ ነው፡፡ ለአሕዛብ ምን ያልተደረገ ምን አለ? ይህን ታሪካዊ ቤተ መቅደስም በቤተ አይሁድ መካከል የሠራው አይደለም፤ በአሕዛብ መካከል እንጂ፡፡

ቤተ ክርስቲያን በምኩራብ ማኅፀን ውስጥ ተፀንሶ የቆየ ፅንስ እንጂ አዲስ አይደለም፡፡ ሆኖም ግን የፀነሰችው ምኩራበ አይሁድ ወልዳ መሳም ሳትችል ቀረች፤ ምክንያቱም እንደ ተወለደ በእስራኤል እንቢተኝነት ምክንያት ወደ አሕዛብ ስለገባ ነው፤ ሕንፃው በቅድስቲቷ ምድር ኢየሩሳሌም ሳይሆን ቀረ፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው በረከቱን ከእስራኤል እንዳራቀ፣ ክብራቸውን ወደ አሕዛብ እንደተነጠቀ ለማሳየት ነው ፡፡

አብርሃም በራዕይ የተመለከታቸው በምድራዊ አሸዋ የተመሰሉ ልጆቹ የሰማዩን ተስፋ፣ የቃል ኪዳኑን ምድር እንዲወርሱ የተወለዱለት በዚህ ጊዜ ነው፤ ዘፍ 22÷17፡፡ እንደ ባሕር አሸዋ የመንፈስ ቅዱስ ሙቀት የሌላቸው ቀዝቃዞች፣ በምድር እንጂ በሰማይ እንዳሉት ከዋክብት በላይ ለመኖር ያልታደሉ ብርሃን አልባ ድንጋዮች ናቸው፡፡ ዛሬ ግን ከከበረ የአልማዝ ድንጋይ ይልቅ ያበራሉ፤ ድንጋይነታቸውን እንዳልናቀባቸው ለማስረዳትም በመካከላቸው የመጀመሪያውን ቤተ መቅደስ በድንጋይ ሠርቶ አሳየ፡፡ ለካ ድንጋይም አናጢዎች የናቁት ድንጋይም ለአገልግሎት ይፈለጋል ብለው እምነታቸው እንዲፈጸምላቸው ነው እንጂ ሌላ ምንድነው? ያልታሰቡትን ድንጋዮች ባንድ ቀን ለቤቱ እንዲበቁ አደረጋቸው::

በዚያውም ላይ እግዚአብሔር ሲፈቅድ የቀደሙት ኋለኞች፣ ኋለኞች ደግሞ ፊተኞች ይሆናሉ፤ ቀድመን ወንጌሉን ማወቃችን፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከፍተኛውን የሥልጣን ሥፍራ መያዛችን፣ በቤተ መቅደሱ ማደጋችን ብቻውን ያጸድቀናል የሚመስላቸው ብዙ ወገኖቻችን ናቸው:: በወንጌል ውስጥ ብዙ ኋለኞች ፊተኞች የሆኑ ሲሆን ብዙ ፊተኞች ደግሞ ኋለኞች ሆነዋል፡፡

ቤተ መቅደሱ በእመቤታችን ስም ለምን ተሰየመ? የመጀመሪያው የመላዕክት የምስጋና መሥዋዕት በምድር ላይ የቀረበበት ቤተ መቅደስ ማኅፀነ ማርያም ለመሆኑ ብዙ ማስረጃ መጥቀስ ይቻላል፡፡ አረጋዊ መንፈሳዊ የተባለው የቤተ ክርስቲያናችን ሊቅ “ድንግል አጽነነት ርዕሳ መንገለ ከርሣ ከመ ትስማ ቃለ እመላዕክት፤ ድንግል ከመላዕክት ቅዳሴን ልትሰማ ራሷን ወደ ሆዷ ዘንበል ታደርግ ነበር” በማለት የእመቤታችንን ማኅደረ ቅዳሴነት ይናገራል፤ ጌታችን የሚፀነስበት ወራት በደረሰ ጊዜስ እመቤታችን ከቤተ መቅደስ እንድትወጣ መደረጉ ለምን ይመስላችኋል፤ ቤተ መቅደስ በቤተ መቅደስ ውስጥ መኖር ስለሌለበት እኮ ነው፡፡ በዚያውም ላይ ያኛው ቤተ መቅደስ የሌቦች ዋሻ የወንበዶች መዳረሻ ሆኗል፤ ብቸኛዋ የእግዚአብሔር ከተማ ድንግል ከዚያኛው ጋር ምን ሕብረት አላትና በዚያ ሳለች ትፅነሰው?

ከአይሁድ ቤተ መቅደስ አውጥቶ ቤተ መቅደስ አደረጋት፤ በቤተ መቅደስ ትሰማው የነበረውን የመላእክት ዜማ አሁንም በሆዷ ውስጥ ትሰማው ነበር የምድራውያኑን ካህናት ቅዳሴ በሰማዩ ካህናት ቅዳሴ ለውጣዋለች:: ይህን ለመግለጽ ነው እንግዲህ ቤተ መቅደሱን ከሦስት ድንጋዮች ሠርቶ ሲጨርስ በሰኔ በሃያ አንደኛው ቀን ከሰማያት ወርዶ ቤቱን በእናቱ ስም ሰይሞ ቆርቦ እሷንም እነሱንም አቁርቧቸዋል::

አሕዛብ በሥላሴ ለማመናቸው ምክንያት የሆነች እርሷ ናት እንጅ ሌላ ማን አለ፤ ቅዱስ ኤፍሬም እንደ ተናገረው “ለሥላሴ ስግደትን የምታስተምርላቸው” ድንግል ማርያም ናት በኦሪትና በነቢያት ከተገለጠው ይልቅ የእግዚአብሔር ምሥጢር በዝቶ የተገለጠው ጌታ ከእመቤታችን ከተወለደ በኋላ ነውና፤ በዚያውስ ላይ አሕዛብን ማን ፈልጓቸው ያውቅ ነበር፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ጌታን በእቅፏ ይዛላቸው በከተሞቻቸው መካከል የተገኘች እርሷ እኮ ናት፡፡ ድንጋዮቹ አሕዛብ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንዲሆኑ እመቤታችን ምክንያታቸው ናት፤ ስለዚህ ቤቱ በእርሷ ስም ተሰየመ፡፡ አሁን ሁላችንም እንደ ሐዋርያው ቃል የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ለመሆናችን ምንም ጥርጥር የለንም 1ኛ ቆሮ3÷16፡፡ እግዚአብሔር “መንፈሴ በሰው ላይ ለዘለዓለም አይኖርም እርሱ ሥጋ ነውና” ዘፍ6÷3 ብሎ የማለውን መሀላ እንዲረሳና በሰው ላይ እንዲያድር ሰውም ቅዱስ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ወደ መሆን እንዲያድግ ከእመቤታችን በስተቀር ሌላ ምን ምክንያት አለው፡፡

አምላካችን በድንጋይ ልብ ውስጥም ይመሰገናል ማለትም በአሕዛብም ዘንድ ቅዳሴው አይቋረጥበትም፤ ይህን ስጦታዋን በሰዎች መካከል ሲገልጽላት እግዚአብሔር ቤተ መቅደሱን በስሟ ሰይመላት፤ ከዚያም በኋላ የተነሡ መምህራን ይሄን መነሻ በማድረግ በዐራቱም መዐዝን ወንጌልን ሰብከው ብዙ የመታሰቢያ ቤቶችን በስሟ ከመሥራታቸውም በተጨማሪ ስሟን ለምዕመናን ስም እንዲሆን ፈቅደውላቸው እንዲጠሩበት አድርገዋል፡፡ በነቢይ ስለ እርሷ የተባለውም በዚህ ተፈጽሞላታል “ወይዘክሩ ስመኪ በኩሉ ትውልደ ትውልድ፤ ስምሽን ለልጅ ልጅ ያሳስቡልሻል” መዝ 44÷17፡፡

 

ልሳነ አርድእት

 ሰኔ 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመ/ር ደሴ ቀለብ
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ መምህር

ክፍል ፩

የግእዝ ቋንቋ እድገት ከየት ወዴት?

አንዲት ሀገር የራሷ የሆነው ባህሏ /ሥርዓቷ/ የሚያኮራትና ማንነቷንም የሚያንጸባርቅ በመሆኑ ልትጠብቀውና ከትወልድ ወደ ትውልድ ልታስተላልፈው የባለቤትነት ግዴታዋ ነው፡፡ በመሆኑም ሀገራችን ኢትዮጵያን ለጥቁር ሕዝቦች መኩሪያ እንድትሆን ያደረጋት የልጆቿ ሀገር ወዳድነትና ጀግንነትን የተመላው ባህሏ ብቻ ሳይሆን የሃይማኖት፤ የሥነ ፊደል ሀገር መሆኗም መጻሕፍተ ታሪክን ባነበቡ ሊቃውንት አንደበት ብቻ ሳይሆን በማዳመጥ ትውፊት /ርክክብ/ ለኅብረተሰቡ ኀቡእ ያልሆነ ነገር መሆኑ ነው ፡፡

በተጨማሪም ሀገራችን ኢትዮጵያ የዘመናት ዑደት ስፍር ቀምራ የራሷን አኀዝ ያደላደለች አፍሪካዊት እመቤት ናት ብንል ጽልመት ሊጋርደው የማይችለው ገሀድ ነው፡፡

ይሁን እንጂ እኛ ልጆቿ የትናንቱን ለዛሬ ማበርከት ያልቻልን ይመስላል፡፡ ለዚህም ነው ትናንት የኢትዮጵያ መሠረተ ቋንቋ የነበረው የግእዝ ቋንቋ ከነበረበት የብሔራዊና የውል ቋንቋነት ይቅርና ዛሬ ዛሬ የት ገባ ሊባል የሚያሳፍር ሆኗል፡፡ አበው ለብዙ ዘመናት ይህን ቋንቋ በዜማ ቤቱ፣ በቅኔ ቤቱና በመጻሕፍት ቤቱ እንዳልተጠቀሙበት ሁሉ ዛሬ ግን የአበው ያለህ ብንል፤ አይደለም መግባባት ይቅርና ገና ተማሪው እንኳን ከማለዳው “ኦኾ” /እሽ/ በማለት ፈንታ “ኦኬ” ቢል ይቀድመዋል ፡፡ ይህ ግን “የቆጡን አወርድ ብላ የብብቷን ጣለች” ሳያሠኝ አይቀርም ፡፡

እንደሚታወቀው የኢትዮጵያ ታሪክ መረጃ ሥነ ሐውልቶች የተሸከሙት የግእዝ ቋንቋ ሥነ ጽሑፍ የሀገራችንን ጥንተ ታሪክ የሚያስረዳ መሆኑን ታሪክ ይመሰክራል፡፡ የግእዝ ተፎካካሪ የነበረው የሳባዊያን ቋንቋም በግእዝ ተልቆ /ተበልጦ/ ግእዝ የኢትዮጵያ ነገሥታት ሊቃውንት ኅብረተሰብ መግባቢያ ከመሆኑም አልፎ ከሀገር ውጭም ኢትዮጵያ ሀገረ ፊደል፣ ሀገረ አሚን መሆኗን ያስመሰከረ ልሳን ነበር፡፡ የሆነው ሆኖ ቀድሞ ከ፯ ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ እየተጠናከረ መሄዱ በሚነገርለት በአማርኛ ቋንቋ መሆኑ ቀርቶ በቤተ ክርስቲያንና በተወሰነው የኅብረተሰብ ክፍል ዘንድ እየተገደበ መጣ፡፡ እንዲያውም በተለይ በዘመነ ዓምደጽዮን / ከ፲፫፻፯-፲፫፻፴፯ ዓ.ም./ የንጉሡ ገድል ሁሉ የሚጻፈው በተሰባበረ አማርኛ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ለአብነት ያህል የሚከተለውን ማየት ይቻላል፡፡ 

  • ሐርልኛ ዓመደ ጽዮን
  • መላለሸ የወሰን
  • ወሀ እንዳመሰን መላላሽ የወሰን
  • ከወጅ ዜብደናን ከገንዝጠጠን
  • ምንቀረህ በወሠን ከድያ አምኖን

በተጨማሪም በዐፄ ይስሐቅ /ከ፲፬፻፯-፲፬፻፳፪ ዓ.ም./ ጊዜ ለንጉሡ የሚቀርቡት መወድሶች ከአማርኛው ላይ ያተኮሩ ይምስላሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል፡-

  • ገጽዥን ይስሐቄ ገጽ
  • አርያም ይመስል አንቀጽ
  • እሳት ይመስል ብቁጽ
  • ከመ መደልው ልጽሉጽ
  • ገጹ እንዲያስደነግጽ
  • እስራኤላዊ መደንግጽ
  • ማን አየህ ገጽ በገጽ

 

እነዚህ ግጥሞች ግን እንደምናያቸው ሙሉ በሙሉ አማርኛ አልነበሩም፡፡ ለዚህም ነው ግዊዲ የተባለው የታሪክ ተመራማሪ “ግእዝ -አማርኛ” ጽሑፎች ብሎ የሚጠራቸው፡፡ በእርግጥ ከአማርኛው ላይ ግእዝ መደመር ለአሁኑ ትውልድም የቋንቋ ጣዕም የሥነ ጽሑፍ ቃና መሆኑ አወንታዊ ምላሽ አለው፡፡

ያም ሆኖ ግን ብዙ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የጽሕፈት ሥራቸውን ብራና ዳምጠው ቀለም በጥብጠው ይጠቀሙበት የነበረው በዚህ ቋንቋ መሆኑን አላገደውም፡፡ እንዲያውም በዘመነ ዘርዓያዕቆብ /፲፬፻፳፮-፲፬፻፷ ዓ.ም./ መስፋፋት የነበረበት የሥነ ጽሑፍ እድገት ግእዙን የሙጥኝ ያለ ነበር፡፡ በኋላም ቢሆን በዐፄ ሱስንዮስ / ከ፲፭፻፱፱-፲፮፻፳፬ ዓ.ም./ የሃይማኖት መለወጥ ምክንያት ጋር ተያይዞ ኢየሱሳውያን (Jesuites) ጉልህ ችግር ደርሶባት የነበረችውን የሮማ (ስፔን) ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ተከታዮችን ቁጥር ለማበርከት ሲሉ በአማርኛ በመጻፍ ወረቀቶችን ለመበተን ቢሞክሩም የአንድ ባሕርይ አማኝ የሆነው ዐፄ ፋሲል / ከ፲፮፻፳፬ -፲፮፻፸፬ ዓ.ም/ በመንገሥ የምእመናኑን ፍጹም ቀናዒነት ብሎም የኢየሱሳውያን ከኢትዮጵያ ምድር መውጣት ለልሳነ ግእዝ እንደገና መወለድ መስፋፋት ሆነለት፡፡ ብዙም መጻሕፍተ ግእዝ ተደረሱ፡፡ የቅኔ እድገትም ታየ፡፡ ከዐፄ ፋሲል በኋላም ነገሥታቱ ታላቅ ተሳትፎአቸውን አበርክተዋል፡፡ ስለሆነም ዐፄ ኢያሱ አድያም ሰገድ /ከ፲፮፻፸፬ -፲፮፻፱፱ ዓ.ም./ እና ሌሎችም ነገሥታት የማይጠፋ ስማቸውን በልቡናችን ቀረጸው አልፈዋል፡፡

ዳግመኛ የ፲፮ኛው እና የ፲፯ኛው ክፍለ ዘመናት ቁስር አልሽር ብሎ እንደገና በመሳፍንቱ ዘመን /ከ፲፯፻፸፯-፲፰፻፵፭ ዓ.ም/ ሀገሪቱ እርስ በርሷ በፖለቲካና በሃይማኖት ድልቅልቅ ስትዋጥ ሀገርን አንድ ማድረግ ይችል የነበረውን ነገረ-ሃይማኖት ለመረዳትና ለመወሠን ሊቃውንቱ የግእዝን መጻሕፍት ማገላበጥ ግድ ሆነባቸው፡፡ የመነጋገሪያ /የመከራከሪያ/ ምሥጢራቸው የሆነው ቅኔም ለልሳነ ግእዝ መስፋፋት ጠቀመ፡፡ የአብነት ትምህርት ቤቶችም ተስፋፉ፡፡ ፍጹም የሆነ አንድነትም ታዬ፡፡ ዛሬስ የሃይማኖት ውዝግቡን የሚፈቱት የትኞቹ እውን መጻሕፍት ይሆኑ? በእርግጥ ዛሬ ግእዝ ያወቀው ሁሉ ነገረ ሃይማኖትን ተረዳ ማለት አይደለም፡፡ የሚማረውም ለሕይወት /ለፍቅር/ ወይም ታሪክን ለማወቅ ላይሆን ይችላል፡፡ ነበርኩ ለማለትና ክዶ ለማስካድ እንዲመቸው የሚያስብም አይጠፋምና፡፡ በየዋህነት መማር ግን በአማናውያኑ አበው ቀርቷል፡፡

እንግዲህ ለግእዝ ቋንቋ መዳከም ዐቢይ ምክንያት የአማርኛ መተካት ብቻ ሳይሆን ለቋንቋው የሚሰጠው ትኩረት መላላቱ የማያወላውል ምክንያት መሆኑ ነው፡፡ ዝም ብሎ ግን ቅርስ ቅርስ ማለት ብቻ ዋጋ የለውም፡፡ “ባዶ ብራና” ካልተነበበ ምን ሊሠራልን፡፡ በተጨማሪም መንግሥትም ሆነ ማንኛውም አካል ግእዝ የቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ቅርስ መሆኑን ሊገነዘበው ይገባል፡፡ ቤተ ክህነትም ብትሆን የእነ ቅዱስ ያሬድ የዜማ መጻሕፍት እነ ድጓ፣ የዚቅ ቀለማት፤ የእነ አባ ጊዮርጊስ መጻሕፍት ፣ እነ ሰዓታት በሌላ ቋንቋ ሊዜሙ “ይቻል” ይመስል ለግእዝ የሚሰጠው እንክብካቤ ያሳዝናል፡፡

ድሮ ድሮ የቆሎ ተማሪ ለምኖ አኮፈዳውን፤ ዳዊቱን አንግቦ የሚነጋገረው በዚህ ቋንቋ ነበር፡፡ እንደዛሬው ግን ለወደፊቱ አይደለም የሚነጋገር አባባሉን የሚያጠና /የሚቀጽል/፣ በደንብ ቅኔ የሚቀኝ ይቅርና ዳዊቱን አጣርቶ መድገሙም ራሱ ያጠራጥራል፡፡ በእርግጥ በአንዳንድ የገጠር ቦታዎች የሚያስተምሩ ብዙ የሊቃውንት በረከቶች ቢኖሩም፤ ነገ የሚተካው ግን ከግእዝ ይልቅ ጣሊያንኛ፣ እንግሊዝኛ፣ ፈረንሳይኛ ብቻ ቢማር የሚያተርፈው ይመስለዋል፡፡ ይህ ግን “አባቱን አያውቅ አያቱን ይናፍቅ” ያሠኛል፡፡

ምንጭ መጻሕፍቱ በግእዝ የሆነው የሀገራችን ታሪክንስ አንባቢና ተርጓሚ ማን ይሆን? በዚህ እኮ ነው የሀገራችንን ታሪክ ለማወቅ የውጭ መጻሕፍት ላይ ጥገኛ የምንሆነው፡፡ አንባቢውና ተርጓሚው አላዋቂ ከሆነ ደግሞ ታሪከ ሀገር ቅድምና ሀገር በምልዑ ልብ የማይመሰከርበት ይመስላል፡፡ የሚገርመው ግን ብዙዎቹ የግእዝ መጽሐፎቻችን በፈርንጆቹ ላይ የማያልቅ ፍቅርን አሳድረውባቸው ቋንቋውን እስከ ሃምሳ ዓመት ድረስ ሲያጠኑ እኛ ግን “የሞተ ቋንቋ” እንለዋለን፡፡ ቋንቋው ሞተ ከማለት ግን ታሪከ ሀገር ቅድምና ሀገር ሞተ ብንል ሳይሻል አይቀርም፡፡ ቢያንስ ቢያንስ በቤተ ክርስቲያን ለካህናቱ የምስጋናቸው አንደበት ግእዙ ነውና፡፡

እንግዲህ እናጠቃለውና ማንኛውም ክፍል /አካል/ ይህ ቋንቋ በጥንቱም ሆነ በአዲስ መልክ እንዲያድግ ጥረት ቢያደረግ፤ የቅኔ መምህራኑም የግእዝ መምህራኑም ምንም እንኳን የኑሮ ችግር ቢኖርም ለራስ የሚስማማ ቦታን ከመምረጥ ለተማሪዎች የሚስማማ ቦታን መርጦ በገጠርም ቢሆን ማስተማር ይኖርባቸዋል፡፡ የቋንቋ ምሁራንም ለዚህ እድገት አስተዋጽዖ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን በመካከለኛው ክፍለ ዘመን ላይ የጥንቱ ሰዋስው (Classical Grammar) ይምጣልን፣ ይመለስልን፤ መካከለኛው ክፍለ ዘመን የጨለማ ዘመን ነው እያሉ እንዳማረሩት ሮማውያንና ግሪካውያን እንዳንሆን ያስፈራል፡፡ ስለሆነም ሥርወ ቃላትን ለመመርመር ሰዋስውን ለመለየት ግእዝ ማወቅ ይጠበቅብናል፡፡ ለዚህም ታላላቅ ደራሲያን ምስክሮች ናቸው፡፡ በተረፈ ግን ሁላችንም የታሪክ፣ የሀገር፣ የወገን፣ የቅርስ ባለአደራዎች መሆናችንን አንዘንጋ፤ እንቅልፉም ይብቃን፡፡

ይቆየን

 

የደብረ ሊባኖስ ገዳም አምስቱ ስያሜዎች

 ሰኔ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

የደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንድነት ገዳም ገዳማዊ ሥርዓቱ እንደተጠበቀ ቢሆንም የጎርፍ አደጋ፤ የብዝኅ ሕይወት መመናመን፤ የሕገ ወጥ የመሬት ወረራና ሌሎችም ችግሮች እየተፈታተኑት ይገኛል፡፡ ይህንን ችግር ለመቅረፍና ዘላቂ መፍትሔ ለማምጣት በገዳሙና በማኅበረ ቅዱሳን ባለሙያዎች ፕሮጀክቶች ተቀርጸው ወደ ሥራ ተገብቷል፡፡ 

 

ፕሮጀክቶቹንም በተያዘላቸው እቅድ መሠረት ለማስፈጸም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ሠኔ 8 ቀን 2006 ዓ.ም. የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ላይ ፕሮጀክቶቹንና ገዳሙን አስመልክቶ የተዘጋጀ መጽሔት ለምእመናን ተሰራጭቷል፡፡ ከመጽሔቱ ያገኘናቸውን ጥቂት መረጃዎች እናካፍላችሁ፡-

የደብረ ሊባኖስ አቡነ ተክለ ሃማኖት አንድነት ገዳም በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ከአዲስ አበባ ወደ ጎንደር- ጎጃም መውጫ በ104 ኪሎ ሜትር ርቀት፤ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ 4.5 ኪሎ ሜትር ተገንጥሎ የሚገኝ የአንድነት ገዳም ነው፡፡
ገዳሙ በጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ1296 ዓ.ም. የተቆረቆረ ሲሆን፤ 710 ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ በገዳሙ አስተዳደር ሥር ከአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በተጨማሪ የቅዱስ አማኑኤል እና የቅዱስ ፊልጶስ አብያተ ክርስቲያናት ይገኛሉ፡፡

በገዳሙ ውስጥ የሚጎበኙ የተለያዩ የነገሥታት ሥጦታዎች፤ ቅዱሳት መጻሕፍት፤ ንዋየ ቅድሳት፤ የቅዱሳን አጽም፤ ፈውስ የሚገኝባቸው የጸበል ቦታዎችም ይገኛሉ፡፡

የደብረ ሊባኖስ ገዳም አምስቱ ስያሜዎችን ስንመለከት፡-

ምድረ ግራሪያ፡-
ግራሪያ የሚለውን ስያሜ የሰጠችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከልጇ ከወዳጇ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወደ ምድረ ግብጽ ስትሰደድ በኢትዮጵያ ውስጥ ከቆየችባቸው ቦታዎች አንዱ ይህ ቅዱስ ቦታ ነው፡፡ ለአንድ ሳምንት ቆይታ አድርጋ የቦታውን ስም ምድረ ግራሪያ ስትል ሰይማዋለች፡፡ ግራሪያ ማለት ኩሉ ይገርር ሎቱ፤ ሁሉ ይገዛላታል ማለት ነው፡፡ አንድም ግራር በቁሙ ለሁሉ ጥላ፤ መሰብሰቢያ እንደሆነ ደብረ ሊባኖስም የሁሉ ጥላ መሰብሰቢያ ነውና ምድረ ግራሪያ ተብሏል፡፡

ደብረ አስቦ፡-
ደብረ አስቦ ማለት የዋጋ ተራራ ማለት ሲሆን፤ የሰየመውም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ አባታችን ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ቅዱስ ሥፍራ ሃያ ዘጠኝ ዓመታት ከጸለዩ በኋላ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ቦታውንም ደብረ አስቦ፤ የድካምህ ዋጋ፤ የስምህ መጠሪያ ይሁንልህ በማለት ሰይሞታል፡፡

ኤላም፡-
ኤላም ማለት የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ ማለት ነው፡፡ ይህ ቦታ የአባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት አጽም ለአርባ ዓመታት የቆየበት ቅዱስ ሥፍራ ነው፡፡ ስያሜውም የአቡነ ዮሐንስ ከማ ነው፡፡ ዮሐንስ ከማ የጻድቁ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት የመንፈስ ልጅ ናቸው፡፡ ኤላም የበረከት ቦታ፤ የሰላም ሠፈር ነው፡፡ የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ተሰውሮ ይገኝበታል፡፡

ደብረ ሊባኖስ፡-
ደብረ ሊባኖስ ማለት የሊባኖስ ተራራ ማለት ነው፡፡ ጻድቁ አቡነ ሊባኖስ የተባሉት ሮማዊ አባት ለአርባ ዓመታት የጸለዩበት፤ ብዙ ገቢረ ተአምራት ያደረጉበት፤ ከእግዚአብሔር ጋር የተገናኙበት ነው፡፡ “ትትሌአል ወትከብር እምነ ኲሎን አድባራት ወገዳማት እሞን ለአህጉር፤ ከአድባራትና ገዳማት ትከብራለች፤ ከፍ ከፍም ትላለች፤ ለሀገራትም እናት ትባላለች” ሲል፡፡

አባ ሊባኖስ በጌታ የተወደደውንና የቅዱሳን ከተማ ደብረ ሊባኖስን በጣም ይወዱት ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ ይህ ቦታ ከአንተ በኋላ ለሚመጣው ለተክለ ሃይማኖት ነውና አንተ ወደ ትግራይ ሀገር ሒድ፤ እድል ፈንታህ በዚያ ነው አላቸው፡፡ እርሳቸውም አርባ ዓመታት የደከምኩበት ለከንቱ ነውን? አሉት ቅዱሳን አጽንኦተ በዓት ይወዳሉና፡፡ መልአኩም ስለ ድካምህ ይህ ቦታ ደብረ ሊባኖስ ይባላል እንጂ ደብረ ተክለ ሃይማኖት አይባልም አላቸው፡፡ እሳቸውም ፈቃድህ ይሁን ብለው ወደ ትግራይ ሀገር ሔዱ፡፡ እስከ ዛሬም ድረስ ደብረ ሊባኖስ እየተባለ ይጠራል፤ ስመ ተፋልሶም አላገኘውም፡፡

ዜጋዎ አመል፡-
ዜጋዎ አመል ማለት የአየር ንብረቱ የተመቸ፤ የሚያስደስት፤ ተስማሚና ለኑሮ የሚመች ማለት ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ዜጋዎ አመል ተብሏል፡፡

ምንጭ፡- ልሳነ ደብረ ሊባኖስ፤ ቅጽ-1፤ ቁጥር-1፤ ሠኔ 2006 ዓ.ም.

 

 

 

 

 

 

የማቴዎስ ወንጌል

ሰኔ 16 ቀን 2006 ዓ.ም.

ምዕራፍ ሁለት 

በዚህ ምዕራፍ ውስጥ የምንረዳውና የምንገነዘበው ጌታ በይሁዳ ቤተልሔም በንጉሥ ሄሮድስ ዘመን እንደተወለደ እንረዳለን፡፡ ቤተልሔም ማለት ቤተ ኅብስት ማለት ነው፡፡ ስምዋም የተሰየመው ካሌብ ኤፍራታ የተባለች ሚስት አግብቶ ወንድ ልጅ ከኳ በወለደ ጊዜ እንጀራ እገባ እገባ ብሎት ስለነበር የልጁን ስም ልሔም /ኅብስት/ አለው፡፡ በልሔም ቤተልሔም ተብላለች፡፡

የጥበብ ሰዎች ከሩቅ ምሥራቅ መጥተው የበረከት ሳጥናቸውን ከፍተው ለጌታ ገጸ በረከት አበርክተውለታል፡፡

  • ወርቅ-ለመንግሥቱ

  • ዕጣን ለክህነቱ

  • ከርቤ- ለመራራ ሞቱ፡፡ ምሳሌ ናቸው፡፡

ሰብዓ ሰገል ከሄዱ በኋላ ጌታ ሄሮድስ ሊገድለው ስለሚፈልገው አስቀድሞ በነብያት በተነገረው መሠረት ወደ ግብፅ ተሰደደ ሆሴ.11፡1፡፡

ንጉሡ ሄሮድስም ጌታን ያገኘ መስሎት 144ሺ የቤተልሔም ሕፃናትን አስፈጅቷል፡፡ ከሔሮድስ ሞት በኋላ ጌታ ከስደት ተመለሰ የስደት ዘመኑ 3 ዓመት ከመንፈቅ ነበር፡፡ ራዕይ 12፡7፡፡

እድገቱንም በነቢያት አስቀድሞ እንደተነገረው በናዝሬት ከተማ አደረገ፡፡ ናዝሬት የወንበዴዎች የቀማኞች የተናቁ ሰዎች ከተማ ነበረች፡፡ ጌታም ወደ ተዋረድነው ወደ እኛ መጥቶ ከውርደት ሊያድነን መሆኑን ሊያስገነዝበን በናዝሬት ኖረ፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 3ኛ ዓመት ቁጥር 1 ታኅሥሥ 1988 ዓ.ም.