አማኑኤል፥ ጌታ መድኃኒት

ታኅሣሥ 21 ቀን 2007 ዓ.ም.

 

ዲ/ን ታደለ ፈንታው

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ እነሆ ድንግል በድንግልና ትጸንሳለች ወንድ ልጅንም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች፡፡/ኢሳ፯፥፲፬/ የሚለው የነቢያት ቃል ፍጻሜውን አገኘ፡፡ይህ ትንቢት የይሁዳ መንግሥት በጦርነት ከበባ ላይ በነበረበት ጊዜ ሁለቱ የሦርያና የእስራኤል ነገሥታት የኢየሩሳሌም ቅጥር ሊያፈርሱ በተነሡበት ጊዜ የተነገረ ትንቢት ነው፡፡

 

ንጉሡ አካዝ በታላቅ ጭንቀት ላይ ነበር፡፡ ከተማዋን ለማዳን ያለ የሌለ ጥበቡን ሊጠቀም አሰበ፡፡ የከበቡትን ወገኖች በውኃ ጥም ያሸንፍ ዘንድ ዋናውን ምንጭ መቆጣጠር ዓይነተኛ መፍትሔ እንደሆነ እቅድ አወጣ፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ እግዚአብሔር ሁለቱንም ነገሥታት ያጠፋቸዋልና አትፍራ አለው፡፡ አግዚአብሔር ከሰማይ ሠረገላና ሠራዊት ቢልክ እንኳን ይህ ይፈጸማልን) አለው፡፡

 

እግዚአብሔር የንጉሡን እምነት ማነሥ ተመልክቶ ምልክትን እንዲለምን ነገረው፡፡ ከጥልቁ ወይም ከከፍታውም ቢሆን ከአምላክህ ከእግዚአብሔር ዘንድ ምልክትን ለምን አለው፡፡ ፀሐይን ዐሥር ዲግሪ ወደኋላ መመለስ፣ ጨረቃም በመንፈቀ ሌሊት እንዳያበራ ከዋክብትም መንገዳቸውን ይቀይሩ ዘንድ መለመን ይቻላል፡፡ ይህ ሁሉ ነገር ግን እግዚአብሔር ከሰማይ ከወረደበትና በሰው ልጆች መካከል ከተመላለሰበት ምስጢር ጋር ቢነጻጸር እዚህ ግባ የሚሉት አይደለም፡፡ እግዚአብሔር አካዝን ያስደሰተህን ሁሉ ጠይቅ አለው፡፡ ጠይቅ የተባለው ምልክት ብቻ ቢሆን ቀላል ነበር፤ ነገር ግን ከዚህ በላይ የሆነ ስለሆነ ጌታ ራሱ ምልክት ይሰጣችኋል ተባለ፡፡ ይህ ምልክት ድንግል በድንግልና የወለደችው በቤተ ልሔም ይሁዳ የተወለደ መድኅን ክርስቶስ ጌታ መድኃኒት ነው፡፡

ጌታ መድኃኒት/ሉቃ 2፥፲፩/

ስለመድኅን ክርስቶስ በመላእክት የተነገረው ነገር እጅግ ያስደንቃል፡፡  ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ እንደሚከተለው ተርኮታል፡፡ « በዚያም ሌሊት መንጋቸውን በሌሊት ሲጠብቁ ያደሩ እረኞች ነበሩ፡፡ እነሆም የጌታ መልአክ ወደእነርሱ ቀረበ፤ የጌታ ክብርም በዙሪያቸው አበራ፥ ታላቅ ፍርሃትንም ፈሩ፡፡ መልአኩም አላቸው እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ ሆነ ተወልዶላችኋልና፡፡ ይህም ምልክት ይሆንላችኋል ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግም ተኝቶ ታገኛላችሁ፡፡ ድንገትም ብዙ የሰማይ ሰራዊት ከመልአኩ ጋር ነበሩ፡፡ እግዚአብሔርንም እያመሰገኑ ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ አሉ፡፡´/ሉቃ 2፥፰-፲4/

 

ለስም አጠራሩ ምስጋና ይግባውና ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ ጌታ መድኃኒት ያለውን ወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ ኢየሱስ በማለት ጠርቶታል፡፡ ሁለቱም ከመላእክት ሰምተው ነው በዚህ ስም የጠሩት፡፡ ኢየሱስ ማለት ጌታ መድኃኒት እንደሆነ የአዲስ ኪዳን ቤተክርስቲያን ብቻ ሳትሆን በብሉይ ኪዳን ቤተክርስቲያንም ዘንድ ይህ ስም የታወቀ ነበር፡፡  ኢየሱስ የሚለው ስም በብሉይ ኪዳን ቤተክርስቲያን ዘንድ የታወቀ በአዲስ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን የተለየ ስም ነው፡፡

 

ኢየሱስ የሚለው ስም በአይሁድ ዘንድ የታወቀ እንደነበረ ታሪክ ጸሐፊው ዮሴፍ ወልደ ኮርዮን ይናገራል፡፡ በዚህ ስም የሚታወቁ ዐሥራ ሁለት ስሞችን ዘርዝሯል፡፡ አይሁድ ድኅነት ይፈልጉ ጠብቀውም ይሹት እንደነበረ ከስም አወጣጣቸው ይታወቃል፡፡ ልጆቻቸውን መድኃኒት በማለት ጠርተዋቸዋል፡፡ ምንም እንኳን የመሲሑን መምጣት ትንቢት የተናገሩ ከወገኖቻቸው ከአይሁድ ብዙዎችን ያለፉ ቢሆኑም እውነተኛ መድኃኒት ግን አልነበሩም፡፡ እውነተኛው መድኃኒት « በሥጋ ከዳዊት ዘር ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው እንደ ቅድስና መንፈስ በኃይል የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ ሆኖ የተገለጠው/ሮሜ 1፥4/´ መድኅን ክርስቶስ ጌታ ኢየሱስ ነው፡፡

 

በብሉይ ኪዳን ዘመን ለምሳሌ ኢያሱ ማለት መድኃኒት ማለት ነበር፡፡ በዚህ ስም የተጠሩ ሁሉ ስሙ እንጂ አማናዊ የሆነው ኃይሉ በእነርሱ ዘንድ አልነበረም፡፡ አማናዊ ኃይል ያለው እውነተኛው መድኃኒት በተገለጠ ጊዜ ይህን ስም ብቻውን ይጠራበታል፡፡ የነገር ጥላው አማናዊ በሆነው ነገር ተተክቷልና «እርሱ ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ይገባል´/ዮሐ፫፥፴/ የሚለውን የመጥምቁን ቃል ልብ ይሏል፡፡ እርሱ ብቻ ልዑል፥ መድኃኒት ነው፤ ሕዝቡንም ከኃጢአታቸው ፈጽሞ የሚያድናቸው ነው፡፡/ማቴ ፩፥፳፩/
ሌሎች መድኃኒት ተብለው ቢጠሩ የሰው ልጆችን ከዘላለማዊ ሞት መታደግ አልተቻላቸውም፡፡ ስለኃጢአታቸውም ተገብተው ደማቸውን አላፈሱላቸውም፡፡ እርግጥ ነው በብሉይ ኪዳን ዘመን የነበሩ ብዙ ቅዱሳን አጥንታቸውን ከስክሰዋል ደማቸውን አፍስሰዋል ለሕዝቡ ግን እውነተኛ ድኅነትን ማምጣት አልተቻላቸውም፡፡ እርሱ ግን እውነተኛ መድኃነት ጌታም ነው፡፡

 

ኢየሱስ የሚለው ስም ሊሠራ ያለውን የጽድቅ ሥራ ፈጽሞ ያሣየ ነው፡፡

 ስም ግብርን ይገልጣልና መልአኩ « እርሱ ሕዝቡን ከኃጢአታቸው ያድናቸዋልና ስሙን ኢየሱስ ትለዋለህ´/ማቴ ፩፥፳፩/ በማለት እንደተናገረው ስሙ እንዲሁ ሆነ፡፡ እንደገናም ስሙ ክርስቶስ ነው፡፡ መሲሕ ማለት ነው፡፡ አዳኝ መድኃኒት የሚለው ስሙ ግብሩን ሰው የሆነበትን ፣በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ የታየበትንም ምስጢር ይገልጣል፡፡ ለሰው ልጆች ድኅነት ያስፈለጋቸው ከኃጢአታቸው የተነሣ ነው፡፡ ኃጢአትን ባይሠሩ መድኃኒት ባላስፈለጋቸው ነበር፡፡ ኢየሱስ የሚለው የአምላካችንም ስም በምድር ላይ የታወቀ ባልሆነ ነበር፡፡ እንዲህ የሚለው የወንጌል ቃል የታመነ ነው፡-« ክፉ ከሆነ ከአሁኑ ዓለም ያድነን ዘንድ እንደ አምላካችንና እንደአባታችን ፈቃድ ስለ ኃጢአታችን ራሱን ሰጠ´/ገላ ፩/ ከዚህ ክፉ ዓለም ከኃጢአት ነፃ ያወጣን ዘንድ መሞት ነበረበት ለመሞት ደግሞ መወለዱ የግድ ነው፡፡ እኛን ሊያክል እኛን ሊመስል በእኛ ጎስቋላ ሥጋ ይገለጥ ዘንድ ይገባው ነበርና፡፡ኃጢአት ገዳይ መርዝ ነው፤ ነገር ግን መድኅን ክርስቶስ አሸንፎታል፡፡

 

ስለዚህ ከመድኅን ክርስቶስ ጋር ላለን ግንኙነት መሠረቱ ጽድቃችን ሳይሆን መርገማችን፥ መልካምነታችን ሳይሆን ክፋታችን ፥ መቆማችን ሳይሆን ውድቀታችን ነው፡፡ በተጎበኘንም ጊዜ በእኛ ዘንድ የተገኘው በጎነት ሳይሆን ክፋት ጽድቅ ሳይሆን ኃጢአት፥ ጸጋ ሳይሆን ከንቱነት ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ኢየሱስ ክርስቶስ ኃጢአተኞችን ለማዳን ወደዚህ ዓለም መጣ የሚለው ቃል የታመነ ነው ይላል፡፡ ሐዋርያው ይሄን ሲል ከኃጢአት ቅጣት ሊታደገን እንደመጣ ያመለክታል፡፡ምንም እንኳን አእምሮአችን በኃጢአት ምክንያት ቢበላሽም ልቡናችን ቢጨልምም በኃጢአት ምክንያት ምውት ብንሆንም ክፋትን አስወግዶ በጎነትን ይሰጠን ዘንድ፥ ኃጢአትን አስወግዶ ጽድቅን ያለብሰን ዘንድ፥ የጨለመውን ልባችን በፍቅሩ ብርሃን ያበራልን ዘንድ፥ የሕያው የእግዚአብሔር የባሕርይ ልጅ በእርግጥ ሰው ሆነ፡፡ በበረት ተወለደ፥ አድግና ላህም ትንፋሻቸውን ገበሩለት፥ የዐሥራ ዐምስት ዓመት ብላቴና ወሰነችው፥ በመጠቅለያም ጠቀለለችው፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት በእርግጥም ያስደንቃል፡፡

የጌታ ሰው መሆን በጊዜው ጊዜ የተፈጸመ ነው

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይሄንን የክርስቶስን የቸርነት ሥራ እንዲህ በማለት በማያሻማ ቃል የገለጠው ነው፡- «ወአመ በጽሐ ጊዜሁ ፈነወ እግዚአብሔር ወልዶ ዘተወልደ እምብእሲት የዘመኑ መጨረሻ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት የተወለደውን ልጁን ወደ ዓለም ላከ´/ገላ ፬፥4/ በእርግጥም አበው ሰማያትን ቀድደህ ምነው ብትወርድ ፥ ተራሮች ምነው ቢናወጡ፤እሳት ጭራሮውን እንደሚያቃጥል፥ እሳትም ውኃውን እንደሚያፈላ፥ ስምህ ለጠላቶችህ ይገለጥ ዘንድ፥ አሕዛብም በፊትህ ይንቀጠቀጡ ዘንድ፡፡ ያልተጠባበቅነውን የጽድቅ ሥራህን በገለጥህ ጊዜ ወረድህ፥ ተራሮችም በፊትህ ተንቀጠቀጡ፡፡ሰዎች ከጥንት ጀምሮ ለሚጠብቁህ ከምትሠራላቸው ከአንተ በቀር ሌላ አምላክን አልሰሙም በጆሮአቸውም አልተቀበሉም፤ ዓይንም አላየችም፡፡/ኢሳ ፶፫፥፩-፬/ በማለት የመሰከሩለት በተስፋ የጠበቁት ትንቢት የተናገሩለት ሱባኤ የቆጠሩለት አምላክ የዘመኑ መጨረሻ በደረሰ ጊዜ ተገለጠ፡፡

 

ዓለሙ ያለ እርሱ ጨለማ ነበረ፡፡ በኃጢአትም የተያዘ፤ በኃጢአት ፈጽመን የተያዝን ከሆንን እምነት አይገኝብንም፡፡ የብሉይ ኪዳን ቤተ ክርስቲያን ስለዚህ ቀን ብዙ ጮኸች፡፡ ስለዚህ ቀን ደስታ ብዙ መከራን ተቀበለች፤ ትንቢት አናገረች፤ ሱባኤ አስቆጠረች፡፡ መድኀኒታችን ግን በጊዜው እንጂ ያለጊዜው አልመጣም፡፡ «ሳሕሉ ለእግዚአብሔር በጊዜሁ´ በማለት ነቢዩ ዳዊት እንደተናገረ፡፡ በእኛም ሕይወት እንዲሁ ነው፡፡ እግዚአብሔር የቸርነት፣ የምሕረት ሥራውን የሚሠራው በጊዜው እንጂ ያለጊዜው አይደለም፡፡ ስለዚህ ነው ቅድስት ቤተክርስቲያን ይህንን ጊዜ በቅዳሴው በሰዓታቱ በኪዳን ጸሎቱ፣ በጸበሉ፣በጾሙ እያራራች ወደ አምላካችን እንድንቀርብ እያበረታታች ጊዜውን እንድንጠብቅ የምታደርገን፡፡ ጌታችን ከጊዜው ቀድሞ ከጊዜውም ዘግይቶ አይመጣም፤ በጊዜው ጊዜ እንጂ፡፡ እርሱ ፈጽሞ ቀጠሮ አክባሪ ነው፡፡ ሰው የሆነው በፍጹም ቀጠሮው ጊዜ ነው፡፡ ጊዜው ረዘመ ብሎ አይዘነጋም፡፡

 

የጌታ ሰው መሆን ትንቢት የተነገረለት ሱባኤ የተቆጠረለት እንጂ እንዲሁ በድንገት የተከናወነ እንዳልሆነ እንመለከታለን፡፡ ብሉይ ኪዳን ይሄንን የሚመለከቱ ትንቢታትን የተመላ ነው፡፡ የሚወለድበት ሥፍራ፣ የሚወለድበት ጊዜ ፣የአወላለዱ ጠባይ አስቀድሞ የተነገረ ነው፡፡ ክርስቶስ በወሰነው ጊዜ በዚህ ዓለም ተገለጠ፤ የሆነው በእርሱ ፈቃድ በአባቱ ፈቃድ በባሕርይ ሕይወቱ በመንፈስ ቅዱስ ፈቃድ የሆነ ነው፡፡ ሁሉን የሚያውቅ ጌታ የማንኛውንም ድርጊት ጌዜ እርሱ ወስኖታል፡፤ በሕይወታችን የሚከሰተው ማንኛውም ነገር በእርሱ ፈቃድ የሚከናወን በእርሱ ዘንድ ጊዜውም አስቀድሞ የታወቀ ነው፡፡ አንድም ነገር ያለጊዜው አይሆንም ከጊዜውም አንዲት ሴኮንድ እንኳን አይዘገይም፡፡ ፈቃዱ በተወሰነለት ጊዜ ይከናወናል ሊያፈጥነውም ሊያዘገየውም የሚቻለው ወገን የለም፡፡

የክርስቶስ ሰው መሆን ፍርሐትን ያራቀ ነው፡፡

 የጌታ መልአክ ለእረኞች እንዲህ አላቸው፡-« እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ ሆነ ተወልዶላችኋልና´/ሉቃ 2፥፲/ መልአኩ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ምስራች አለ እንጂ ወንድ ሴት፣ ጥቁር ነጭ፣ ባሪያ ጨዋ አይሁዳዊ የግሪክ ሰው አላለም ፡፡ ዘር ነገድ ጎሳ አልተመረጠበትም፤ ጥሪው የተላለፈው ለሁሉም ነው፡፡ ምስራች ዜናው ለሕዝብም ለአሕዛብም ነው ለተቀበሉት ሁሉ የተደረገ ነው፡፡ መልአኩ እረኞችን አትፍሩ አላቸው፡፡እረኞች ወገን ከሆንን ያስፈራን ምንድነው) በኃጢአት መያዛችን አይደለምን፡፡ ስለዚህ ኃጢአታችን ያስወግድልን ዘንድ በርግጥ ሰው ሆነ፡፡ ስለዚህ ምን ያስፈራናል አምላካችን በመካከላችን ሳለ፡፡ አሁን ጌታ ተወልዶአልና ደስታችን እጥፍ ድርብ ነው፡፡

 

አማኑኤል በመካከላችን የሆነ ብቻ አይደለም ሰውን ወደ ቀደመ ክብሩ ይመልሰው ዘንድ የሰውን ባሕርይ ባሕርዩ ያደረገ ጭምር ነው እንጂ፡፡ አሁን አንድ ነገር እናውቃለን እግዚአብሔርን የሚያስቸግረው የኃጢአታችን ብዛት አይደለም ወደእርሱ ለመቅረብ የተከፈለልን ዋጋ ለመቀበል ፈቃደኞች አለመሆናችን እንጂ፡፡ የተወለደው ሁሉን የሚችለው አምላክ ነው፡፡ ለዘላለም በሕይወት እንኖር ዘንድ አንድም እኛ ወደሰማይ መውጣት አለዚያም እግዚአብሔር እኛ ወደአለንበት ስፍራ መውረድ ነበረበት፡፡ ከዚህ ውጪ ከእግዚአብሔር ጋር የምንሆንበት ዕድል የለም፡፡ እኛ ወደ እርሱ ዘንድ መውጣት እንዳልተቻልን በተመለከተ ጊዜ እግዚአብሔር ይፈልገን ዘንድ እኛ ወደ አለንበት ስፍራ መጣ፡፡ በእርግጥም የእግዚአብሔር የቸርነት ሥራ ያስደንቃል፡፡

 

መላእክት ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን የምስራች ያሉት ቅዱስ ወንጌልን ነው፡፡ ክርስቶስ እግዚአብሔር ባይሆን ኖሮ ወንጌል የሚባል ነገር አይኖርም ነበር፡፡ ከጌታ ልደት አስቀድሞ ነቢያት ነበሩ፤ ነገር ግን እነዚህ ነቢያት እውነትን መመስከራቸው ብቻ ዓለም ከኃጢአት እስራት እንዲፈታ አላስቻለውም ነበር፡፡ እግዚአብሔር ለዓለሙ የሆነውን የምስራች እንዲያበስሩ የላካቸው ቅዱሳን መላእክት ጦር የታጠቁ ደገር የነቀነቁ አልነበሩም፡፡ ነገር ግን የሰላም ምልክት በሕፃኑ እጅ በበረት/በከብቶች ግርግም/ የተያዘ ነበር፡፡ ሰዎች እንደጠበቁት በነገሥታት እልፍኝ የተከናወነ አልነበረም፡፡ እግዚአብሔር ከእኛ እንደ አንዱ ሆኖ ራሱን ዝቅ አድርጎ ትሑት ሆኖ መጣ፡፡

 

አስቀድመን እንደተናገርነው ወደ ምስራቹ ቃል የቀረቡ ትጉ፣ ያላንቀላፉ፣ መንጋቸውን በጥንቃቄ ሲጠብቁ የነበሩ እረኞች መድኅን ክርስቶስን ያገኙት በበረት ነው፡፡ የተጠቀለለው በሐር ጨርቅ አልነበረም፡፡ ምድራውያን ነገሥታት ከሚደፉት ዘውድ አንዱን እንኳን አልደፋም የሰማይና የምድር ንጉሥ ሆኖ ሳለ፡፡ እንደ ድኃ የተጠቀለለው በጨርቅ ነው፡፡ የእናቱ ትሕትና ያስደንቃል፡፡ እናንተ ድኆች ሆይ ደስ ይበላችሁ ሀብታም ሳለ ክርስቶስ ስለእናንተ ደኃ ሆኗልና፡፡ እናንተ መሳፍንቶች የምድር ነገሥታት ሆይ ትውልዱ ሰማያዊ የሆነውን ተመልከቱት! በእንግዶች ማረፊያ እንዳልተገኘለት ተመልከቱ! የሰው ልጆች ሆይ እነሆ የእግዚአብሔር አብ የባሕርይ ልጅ /ወልደ አብ ወልደ ማርያም/ አጥንቱ ከአጥንታችሁ ስጋው ከስጋችሁ የሆነ ዝቅ ዝቅ ያለበትን መጠን ተመልከቱ! ክርስቶስ የድኆች፣ የማይጠቅሙ የተናቁ ወገኖች ባልንጀራ ሆነ፤ ከቀራጮች ጋር ተመገበ፡፡
 

የክርስቶስ ልደት የደስታ ምንጭ ነው፡፡

የጌታ መልአክ ለእረኞቹ አላቸው« እነሆ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምስራች እነግራችኋለሁና፡፡/ሉቃ 2፥፲/ በርግጥም የጌታ መልአክ ቃል ለሕዝቡ ሁሉ የደስታ ምንጭ እንደሆነ መመልከት ይቻላል፡፡ መድኃኒት ተወልዶላችኋልና፡፡ ምድራዊ ያይደለ ሰማያዊ የሆነ መድኃኒትን፡፡ በርግጥ የነፍሱን ሐኪም ሲያገኝ ደስታው ፍጹም የማይሆንለት ማነው) በኃጢአት እስር ቤት ያላችሁ ነፃ ሊያወጣችሁ መጥቷል፡፡ ቤተ ልሔም እውነተኛ የእንጀራ ቤት ሆነች፡፡ ቅዱሳኑ ሁሉ ደስ ይበላችሁ ስትጠብቁት የነበረ ተስፋ በእርግጥ እውን ሆኗልና፡፡ ደስታው በእረኞች ዘንድ ተጀመረ፤ ሕዝብና አሕዛብን አዳረሰ፡፡

 

የክርስቶስ መወለድ መላእክትን ያስደነቀ ነው፡፡

መላእክት በታች/በምድር/ በበረት በላይ/በሰማያት/ በአባቱ ቀኝ ተቀምጦ ቢመለከቱት አደነቁ፡፡ « እግዚአብሔርን እያመሰገኑ ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ አሉ፡፡´/ሉቃ 2፥፲፬/ መላእክት የጌታን ልደት እንዴት አስቀድመው እንደሰሙ አናውቅም፤ ነገር ግን የጌታ መወለድ ዜና በሰማያውያን ዘንድ በደረሰ ጊዜ ምን ዓይነት መደነቅ እንደሚፈጠር መገመት እንችላለን፡፡

 

በርግጥም የማይወሰነው ተወስኖ መላእክት ሊያዩት የሚመኙት አምላክ የትሕትናን ሸማ ተጎናጽፎ በበረት መገኘት እጅግ ያስደንቃል፡፡ የጌታ ሕይወቱን ግርፋቱን ሞቱን ሲመለከቱ ምን ያህል ይደነቁ! በርግጥም ለዘመናት ተሰውሮ የነበረውን ይሔንን ታላቅ ምስጢር ተመልክቶ ሊደነቅ የማይችል ማን ይኖራል) ወደ ምድር በመጡና ወደ ቤተልሔም በቀረቡ ጊዜ ከሰው ልጆች ጋር በአንድነት ዘመሩ፡፡ ዘላለማዊው ሕፃን ሆኖ ዘመን ሲቆጠርለት አደነቁ፤ ፍጥረታትን የተሸከመ እርሱ በእናቱ ጀርባ ታዝለ ፡፡

 

ፍጥረታትን የሚመግብ እርሱ የእናቱን ጡት ተመገበ፡፡ ሁሉን በቃሉ የፈጠረ እርሱ ፍጥረታትንም የተሸከመ ደካማ ስጋን ባሕርዩ አድርጎ እናቱ ተሸከመችው፡፡ በሕፃን መጠንም ተወለደ፡፡ የነገሥታት ንጉሥ መሆኑን የምትገነዘቡ ወገኖች አድንቁ! ደኃ ሆኖ ትመለከቱታላችሁ፡፡ ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እንዲህ በማለት ያደንቃል፡- « የዕብራውያን ጌታ ከዕብራዊት ድንግል ተወለደ፥ ሐዋርያቱን በሰባ ሁለት ቋንቋ ያናገረ፥በሰናዖር የአሕዛብን ቋንቋ የተበተነ ቋንቋ እንደማያውቅ ሰው እናቱ በምትናገርበት ልሳን የዕብራውያንን ቋንቋ አፉን ፈታ፤ ይህንንም ቋንቋ እየተናገረ አደገ´፡፡

 

አዲስ የተወለደው ንጉሥ ወዴት ተኛ) የወርቅ ፍራሽ ከዝሆን ጥርስ የተሠራ አልጋ ተዘጋጀለትን) በቄሣሮች ቤተ መንግሥት የተሻለ ክፍል ሰጡትን) አይደለም፡፡ መድኅን ክርስቶስ የተኛው በከብቶች ግርግም ነው፡፡ ከብቶች በሚመገቡት በረት ንጉሡ ክርስቶስ ተኛ፡፡ ክፉ ሰዎች በረትም ማደሪያ ሆኖ ረጅም ጊዜ በዚያ ይቀመጥ ዘንድ አልፈቀዱለትም፡፡ ክፉ ሰዎች እነርሱ ባማረ ቤት ባማረ ኑሮ እየኖሩ ዕረፍት የሚነሣቸው የድሆች ተረጋግቶ መቀመጥ ነው፤ እነርሱን ሳያሳድዱ ወይም ጨርሰው ሳያጠፉ እንቅልፍ የላቸውም፡፡ አይሁድ በጌታ ላይ የፈጸሙት ተመሣሣይ ነገርን ነው፡፡ እናቱ ሕፃኑን ይዛ ወደ ግብፅ ተሰደደች፡፡ በእንግድነት አገር እንግዳ ሆነ፡፡ ከስደት ከተመለሰ በኋላ በናዝሬት አደገ፡፡ መላእክት በዚህ ሁሉ ነገር የሚደነቁ አይመስላችሁም አሳዳጁ ሲሳደድ የትሕትናውን ወሰን ተመልከቱ!
 

የክርስቶስ መወለድ የሰው ልጆች ሁሉ አድናቆት ነው፡፡

መላእክት በጌታ ልደት ከተደነቁ የሰው ልጆችማ በዚህ ታላቅ ምስጢር ምን ያህል እጹብ እጹብ ማለት ይገባቸው ይሆን) እግዚአብሔር የበደሉ የሰው ልጆች ቃሌን ተላልፈዋልና እንደወጡ ይቅሩ ይጥፉ አላለም፡፡ ለድኅነታቸው የሚሆን አስደናቂ የድኅነት መንገድን አዘጋጀ፡፡ የማዳን ሥራውን እርሱ የሚፈጽመው እንጂ ለፍጡር የሚሰጥ አልነበረም፡፡ ፍጡር ይህን ማድረግ የሚቻለው አይደለምና፡፡ ስለዚህም ነው የሰው ልጅ አምላክ በሆነ በክርስቶስ ደም እንጂ በፍጡር ደም ሊድን ያልተቻለው፡፡ የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ቄርሎስ፡፡ «እኛ በጸጋ አማልክት ነን ክርስቶስን ከባሕርይ አምላክነት የሚያሳንስ አንዳችም ነገር አውርዶ ከእኛ ጋር ስለሚያስተካክለው አዳኛችን መሆን አይቻለውም´ ይላል፡፡

 

ስለዚህ ጌታና መድኃኒት ንጉሥም የሆነ እርሱ ተበድሎ እርሱ የሚክስ ሆነ፡፡ ይኼንን ማድረግ የሚቻለው ከእርሱ በቀር ሌላ ስለሌለ አምላክ ስጋን ተዋሓደ፡፡ በርግጥ ራሳችንን ብንመረምር እግዚአብሔር ይሄንን ያህል ይወድደን ዘንድ ራሱንም ለመስቀል ላይ ሞት አሳልፎ ይሰጥልን ዘንድ የሚያደርግ አንዳች ነገር በእኛ ላይ እንደሌለ ትገነዘባላችሁ፡፡ እግዚአብሔር አብዝቶ ቢጠራን አጥብቀን ከፊቱ የሸሸን ወገኖች ነን፡፡/ሆሴ፲፩፥፩/

 

የልዑል እግዚአብሔር ቸርነት የእመቤታችን አማላጅነት አይለየን!

“ወኩኑ ታቦተ መንፈሳዌ ለክህነት ቅድስት ወንጽሕት፤ ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ” /፩ኛ ጴጥ. ፪፥፭/

 

 

ታኅሣሥ 14ቀን 2007 ዓ.ም.

መምህር ኅሩይ ባዬ

የዲያቆናት አለቃ የመጀመሪያው ሰማዕት ቅዱስ እስጢፋኖስ በሠላሳ አምስት ዓመተ ምሕረት በድንጋይ ተወግሮ ሰማዕትነትን ተቀበለ፡፡ ያን ጊዜም በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምነው ክርስቲያን የሆኑ የአይሁድ ወገኖች ተበተኑ፡፡

 

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም መከራ ውን ሳይሠቀቁ እምነታቸውን ጠብቀው በሃይ ማኖት እንዲጸኑ በስድሳ ዓመተ ምሕረት መጀ መሪያይቱን መልእክት ለተበተኑ ምእመናን ጽፎላ ቸዋል፡፡

 

ወኩኑ ታቦተ መንፈሳዌ ለክህነት ቅድስት ወንጽሕት፤ ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ መንፈ ሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ ሲል ሰማያዊ ጥቅም ከማያሰጥ ከክህነተ ኦሪት በተለየ ለክህነተ ወን ጌል መንፈሳዊ ማደሪያ ለመሆን ተዘጋጁ ማለቱ ነው፡፡ ቅድስት ማለቱም ምሳሌያዊ ከሆነው የኦ ሪት ክህነት ተለይቶ አማናዊ ክህነትን ለመ ያዝ የእግዚአብሔር ማደሪያ መንፈሳዊ ቤት ሆኖ መሠራት ስለሚያስፈልግ “ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ” እያለ ይጽፋል፡፡

 

በዚህ ትምህርታዊ ስብከት ካህን የሚለውን ቃል በመተርጐም የካህናትን ተልእኮ በማመልከት የሓላፊነቱን ታላቅነትና ክቡርነት እንመለከታለን፡፡ በሁለተኛው ክፍልም ክህነት ከእግዚአብሔር የተቀበልነው፣ የታደልንለት እና የተጠራንለት አደራ በመሆኑ ሥልጣነ ክህነታችንን ጠብቀን ራሳችንን፣ ቤተ ክርስቲያናችንን፣ እምነታችንን፣ እና ምእመናንን እንዴት መጠበቅ እንዳለብን እንማራለን፡፡

 

“ተክህነ” የሚለው ቃል ተካነ አገለገለ ክህነትን ተሾመ /ተቀበለ/፤ በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል ቆሞ ለማገልገል ካህን ተባለ የሚለውን ትርጓሜ ያመለክታል፡፡ “ክሂን” ከሹመት በኋላ ማገልገልን፤ “ተክህኖ” ከማገልገል በፊት መሾምን የሹመትን ጊዜ የተቀበሉበትን ዕለትና ሰዓት ያሳያል፡፡

 

ክህነት ቢልም መካን ማስካን ካህንነት ተክኖ ማገልገልን ያሳያል፡፡ ካህን የሚለውን ቃል ሶርያ ውያን “ኮሄን”፣ ዕብራውያን “ካህን”፣ ሲሉት ዐረ ቦች ደግሞ ካህና በማለት ይጠሩታል፡፡ ካህን የሚ ለውን ቃል በቁሙ ቄስ ጳጳስ የእግዚአብሔር አገልጋይ የሕዝብ መሪ አስተማሪ መንፈሳዊ ሀብት ብለው አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ይተረጉሙ ታል፡፡

 

እነዚህን የመዝገበ ቃላት ትርጓሜዎች እንደ ዋልታ አቁመን ጠቅላላ ትርጓሜ መስጠት ይቻ ላል፡፡ ክህነት “ተክህነ” አገለገለ ከሚለው የግእዝ ግስ ይወጣል፡፡ ክህነት የሥልጣኑ ስም ሲሆን አገልጋዮቹ ካህናት ይባላሉ፡፡ ክህነቱ የሚገኝበት መንፈሳዊ ምሥጢርም ምሥጢረ ክህነት ይባላል፡፡ በሚታይ የአንብሮተ እድ አገልግሎት የማይታይ የሥልጣነ ክህነት ሐብት ይገኝበታልና ምሥጢር የተባለበት ምክን ያትም በሚታይ አገልግሎት የማይታይ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ስለሚገኝበት ሲሆን ምሥጢረ ክህነትን የጀመረው /የመሠረተው/ ባለቤቱ ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

 

በክቡር ደሙ የዋጃትንና የመሠረታትን ቤተ ክርስቲያን እንዲያገለግሉ ካህናትን የለየ፣ የጠራና የሰየመ አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት ከትንሣኤው በኋላ የመነሣቱን አዋጅ ለማብሰር ወደ ዓለም ሲላኩ በክህነታቸው ታላላቅ ተአምራትን አድርገዋል፡፡ /ማር. ፲፮፥፲፮/ ያስሩም ይፈቱም ነበር፡፡ /ማቴ. ፲፰፥፲፰/ ይህ የማሰርና የመፍታት ሥልጣን እስከ ኅልፈተ ዓለም የሚቀጥል መሆኑን አምላካችን በቅዱስ ወንጌል አስተም ሯል፡፡ /ማቴ. ፳፰፥፳/

 

ክህነት በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ሦስት ደረጃዎች አሉት፡፡ እነርሱም ዲያቆን፣ ቄስ፣ ኤጲስ ቆጶስ በመባል ይታወቃሉ፡፡ የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ አግናጥዮስ እነዚህን ሦስት የክህነት ደረጃ ዎች እንዲህ በማለት ገልጿቸዋል፤ “ለእግዚአብሔር የሚገባችሁን ሁሉ ለማድረግ ፍጠኑ፤ የሚመ ራችሁ ኤጲስ ቆጶስ የእግዚአብሔር እንደራሴ ነው፡፡ ቄሱም እንደሐዋርያት ዲያቆናትም ለክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ባለአደራዎች ናቸውና”

 

በሌላ አገላለጥ ከሦስቱ ጾታ ምእመናን /ወንዶች፣ ሴቶችና ካህናት/ አንዱ ካህን ነው፡፡ ካህን ከወንዶችና ከሴቶች ምእመናን በተለየ ከፍ ያለ ሓላፊነት አለው፡፡ ይህ ሓላፊነት ምድ ራዊ ሳይሆን ሰማያዊ፤ ሥጋዊ ሳይሆን መንፈ ሳዊ ሓላፊነት ነው፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ አንድ ወጣት ቅስና ለመቀበል ፈልጐ ወደ እርሳ ቸው ሔደ፡፡ ቅዱስነታቸውም አሁን የምሰጥህ የክ ህነት ሥልጣን ሹመት ሳይሆን ሓላፊነት ነው በማለት ተናግረዋል፡፡

 

ሹመት ደረት ያቀላል፤ ሆድን ይሞላል፤ ሓላ ፊነት ግን ያሳስባል፣ ያስጨንቃል፣ እንቅልፍ ያሳ ጣል፣ ክህነት ሓላፊነት በመሆኑ አንድ ካህን ሳይ ታክትና ሳይሰለች በጸሎት በጾምና በስግደት ስለ ራሱ ኃጢአት እና ስለ መንፈሳዊ ልጆቹ ክርስቲ ያናዊ ሕይወት ስለሚጨነቅ ምንጊዜም ቢሆን ዕረ ፍት የለውም፡፡ አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ግልገሎቼን አሠማራ፣ ጠቦቶቼን ጠብቅ፣ በጎቼን አሠማራ” /ዮሐ. ፳፩፥፲፮/ ብሎ ለካህናት የኖላዊነትን ሓላፊነት የሰጠበት የአደራ ቃልም እንደዋዛ የሚታይ አይደለም፡፡

 

 

ካህን ካህን ከመሆኑ አስቀድሞ ምእመናንን የማስተማር ብቃቱ፣ ቤተሰቡን የመምራት ችሎ ታው፣ የአንድ ሴት ባል መሆኑ፣ ቤተሰባዊ ሓላፊ ነቱን የመወጣት አቅሙ፣ ልጆቹን የማስተዳደር ክሂሎቱ እና ከሰዎች ጋር ያለው የሠመረ ግንኙ ነቱ ጤናማ ሊሆን እንደሚገባ ቅዱሳት መጻሕ ፍት ያስረዳሉ፡፡

 

ካህን ከሕይወቱ ሊያስወግዳቸው የሚገቡ ክፉ የሆኑ ጠባያትም በመጽሐፍ ተዘርዝረዋል፡፡ ካህን ለብዙ የወይን ጠጅ የማይጎመጅ /የማይ ሰክር/፣ በሁለት ቃል የማይናገር፣ ከፍቅረ ንዋይ የራቀ፣ አጥብቆ ገንዘብን የማይወድ፣ በንጹሕ ሕሊና የሃይማኖትን ምሥጢር የሚጠብቅ፣ ግልፍተኛ ያልሆነ፤ ሊሆን ይገባዋል፡፡ በአንጻሩም ትሑት፣ የማይጋጭ፣ ይቅር የሚል፣ ትዕግሥተኛ የሆነ እንደሆነ ለሚመራቸው ምእመናን ትክክለኛ አርአያ መሆን ይችላል፡፡

 

ካህናት በሐዋርያት መንበር ተቀምጠው የማሠርና የመፍታትን ሓላፊነት ይወጣሉ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እንደጻፈልን “ካህናት በምድር የፈጸሙትን ጌታ በሰማይ ያጸናላቸ ዋል፤ የባሮቹን /የካህናትን/ አሳብ ጌታ ይቀበለ ዋል” በመሆኑም ካህናት በምድር ላይ የሚፈጽሙአ ቸውን ምሥጢራት እግዚአብሔር በሰማያዊ ምሥ ጢር ተቀብሎ ያከብራቸዋል፡፡
ኤጲስ ቆጶሳት መዓርገ ክህነቱን ለሚመለከ ታቸው ወገኖች ከመስጠታቸው በፊት የቅድ ሚያ ጥንቃቄ ሊያደርጉ እንደሚገባ፤ ምእመናንም በጉዳዩ ላይ አሳብና አስተያየታቸውን ለኤጲስ ቆጶሱ ቢናገሩ መልካም እንደሆኑ የሚደነግጉ መጻ ሕፍት አሉ፡፡ ስለሆነም

 

ካህኑ ከመሾሙ በፊት፡

 

1. የሃይማኖትን ምሥጢር ጠንቅቆ የሚያውቅ መሆን እንዳለበት ሐዋርያት በጉባኤ ኒቅያ ደንግገዋል፡፡ /ጉባኤ ኒቅያ ፫፻፳፭ ቀኖና ፲፱/
2. አዲስ አማኒ ያልሆነ /ጉባኤ ኒቅያ ፫፻፳፭ ቀኖና ፪-፱/
3. የመንፈስ ጤንነት ያለው /የሐዋ. ቀኖና ፸፰/
4. ዕድሜው ከሠላሳ ዓመት ያላነሰ፤ ሊሆን እንደ ሚገባ /ስድስተኛው ሲኖዶስ ቀኖና ፲፫/ በግልጥ ያስቀምጣል፡፡

 

የካህናት ተልእኮ

 

የኤጲስ ቆጶሳት ተልእኮ ቀሳውስትን እና ዲያቆናትን ይሾማሉ፣ ያስተምራሉ፣ ያጠምቃሉ፣ ያቆርባሉ፡፡ በሀገረ ስብከታቸው ያሉት ምእመናን ማኅበራዊና መንፈሳዊ ችግር ሲደርስባቸው ይመክ ራሉ፣ ያጽናናሉ “ሕዝቡን ጠዋትና ማታ ለነግህና ለሠርክ ጸሎት በቤተ ክርስቲያን ይገኙ ዘንድ” ያዝዟቸዋል፡፡

 

የቀሳውስት ተልእኮ፡- እንደ ኤጲስ ቆጶሱ ያስተ ምራሉ፤ ያጠምቃሉ፣ ያቆርባሉ፡፡

 

የዲያቆናት ተልእኮ፡– ለኤጲስ ቆጶሱና ለካህኑ ይላላካሉ፤ ምሥጢራትን ግን የመፈጸም ሓላፊነት የላቸውም፡፡
ከእነዚህ መሠረታዊ የክህነት ደረጃዎች ሌላ በቤተ ክርስቲያን የሚታወቁ መዓርጋት አሉ፡፡ እነርሱም ንፍቅ ዲያቆን፣ አንባቢ /አናጉንስጢስ/ መዘምር፣ ኀፃዌ ኆኅት /በረኛ/ በመባል ይታወቃሉ፡፡ ንፍቅ ዲያቆን ዋናውን ዲያቆን ይረዳል፡፡ አንባቢ /

 

አናጉንስጢስ/ በቅዳሴ ጊዜ መልእክታትን ያነብ ባል፡፡ መዘምር ደግሞ የመዝሙር አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ኀፃዌ ኆኅት ቤተ ክርስቲያንን ይጠር ጋል፣ ያጸዳል፣ ያነጥፋል፣ ደወል ይደውላል፣ በጸሎት ጊዜ ቤተ ክርስቲያንን ይከፍታል ይዘጋል፡፡
ከእነዚህ የተቀብዖ ስያሜዎች ውስጥ ፓትር ያርክ የሚባለው መዓርግ ከሊቃነ ጳጳሳት መካከል ለአንዱ በፈቃደ እግዚብሔር በምርጫ ይሰየ ማል፡፡

 

ይህ የመዓርግ ስም የተጀመረው በአምስተ ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሲሆን በዚህ የመዓርግ ስም ይጠሩ የነበሩት የሮም፣ የእስክንድርያና የአን ጾኪያ ታላላቅ ከተሞች አባቶች /መጥሮ ፖሊሶች/ ነበሩ፡፡ በኋላ ግን ራሳቸውን ችለው የሚተዳደሩ አገሮች ሁሉ የየራሳቸውን ፓትርያርክ ሹመዋል፡፡ ፓትርያርክ ማለት በግሪኩ ቋንቋ ርእሰ አበው /አባት/ ማለት ነው፡፡

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስ ቲያን ሥርዐት ሦስቱ ዐበይት የክህነት መዓርጋት ዲቁና ቅስና ኤጲስ ቆጶስ ናቸው፡፡ ንፍቀ ዲቁና አንባቢ፣ መዘምርና ኀጻዌ ኆኅት በመባል የሚታ ወቁት አራቱ ንኡሳን መዓርጋት በአገልግሎት ውስጥ በግልጽ የሚታዩና በዲቁና ወስጥ የሚጠ ቃለሉ መዓርጋት ናቸው፡፡
ሥልጣነ ክህነት የነፍስ ሕክምና አገልግሎት በመሆኑ ልዩ ጥንቃቄና ክብካቤ ያሻዋል፡፡ ሥልጣነ ክህነት በዘመድ፣ በዘር፣ በአገር ልጅነት በገንዘብ አይሰጥም፡፡ ለመሾም ተብሎም እጅ መንሻ መስ ጠትና መቀበል ፈጽሞ የቤተ ክርስቲያን ትው ፊት፣ ሥርዐትና ቀኖና አይደለም፡፡

 

የካህናትን ክብር ካስተማሩን አበው መካከል አንዱ ቅዱስ አትናቴዎስ በቅዳሴው “ኦ ካህናት አንትሙ ውእቱ አዕይንተ እግዚአብሔር ብሩሃት ተናጸሩ በበይናቲክሙ አሐዱ ምስለ ካልዑ፤ ካህ ናት ሆይ ብሩሃን የእግዚአብሔር ዓይኖች እናንተ ናችሁ እርስ በርሳችሁ አንዱ ካንዱ ጋራ /ተያዩ/ ተመለካከቱ” ይላል፡፡ ይህም በችግሮቻችን ዙርያ መወያየት፤ መነጋገርና መደማመጥ የሚያስፈልግ መሆኑን ያስረዳናል፡፡

 

“የኩነኔ አገልግሎት ክብር ከሆነ ይልቅ የጽድቅ አገልግሎት በክብር አብዝቶ ይበልጣልና” /፪ኛ ቆሮ. ፫፥፱/ እንዳለው ሐዋርያው የክህነት አገልግሎት የተለየ እና ክቡር መሆኑን መገንዘብ ይገባል፡፡ ክህ ነት ከእግዚአብሔር የተገኘ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ወደ እግዚአብሔርም የሚያደርስ ታላቅ መሰላል ነው፡፡

 

የሥርዐተ ጥምቀት፤ የሥርዐተ ቁርባን፤ የሥርዐተ ተክሊልና የምሥጢረ ንስሐ መፈጸሚያና ማስፈጸሚያ መንፈሳዊ መሣሪያ ሥልጣነ ክህነት መሆኑን ስንረዳ የምንሰጠው ክብርም የተለየ መሆኑ አያጠራጥርም፡፡ “ወወሀቦሙ ሥልጣነ ዘከማሁ ይእስሩ ወይፍትሑ ኲሎ ማእሠረ አመጻ፤ እንደ እርሱ የኃጢአትን ማሠሪያ ያሥሩና ይፈቱ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው” /ዮሐ. ፳፥፳፪-፳፫/ መዓርጉ ክቡር በመሆኑ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ክቡር የሆነውን ክህነት አክብረን እንድንከብርበት መለኮ ታዊ ኃይሉ ይርዳን፡፡

 

 

የጎንደር ማዕከል 2ኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር አካሄደ

 

 

 

ታኅሣሥ 4 ቀን 2007 ዓ.ም.

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ /ከጎንደር ማእከል/

 

 

በማኅበረ ቅዱሳን የጎንደር ማእከል ሁለተኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በጎንደር ዙሪያ ወረዳ ማክሰኝት ከተማ አቅራቢያ በሚገኘው በጥንታዊው ደብረ ገነት ባሕሪ ግንብ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ኅዳር 28 ቀን 2007 ዓ.ም አካሄደ፡፡

በመርሐ ግብሩ የማኅበሩ መልእክት በአቶ አማረ አበበ የሰሜን ምዕራብ ማዕከል ማስተባበሪያ ክፍል ሓላፊ፣ ትምህርተ ወንጌል በዶ/ር አለማየሁ ዋሴ፣ መዝሙር በማእከሉ መዘምራን ቀርቧል፡፡

ከስዓት በኋላ በቀጠለው መርሐ ግብር ገዳማውያን አባቶች አባ ኃይለ ሚካኤል የማን እንደ አባ አቡነ ያሳይ ገዳም መነኩሴ እና አባ ገብረ ዋሕድ የዋልድባ ገዳም ቤተ ሚናስ አበምኔት መንፈሳዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡ በአብርሐም ቤት እንግዳም ዶ/ር አለማየሁ ዋሴ የሕይወት ልምዳቸውን አካፍለዋል፡፡

ምን እንጠይቅልዎ በተሰኘው መርሐ ግብርም በነገረ ክርስቶስ እና በነገረ ማርያም ዙሪያ ጥያቄዎች ተነስተው በመልአከ ታቦር ኃይለ ኢየሱስ የደብረ ታቦር ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ዋና አስተዳዳሪ መልስ ተሰጥቷል፡፡ በመጨረሻም በአበራ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ ጉባኤ ቤት መምህር ቅኔ ቀርቧል፡፡

በመርሐ ግብሩ ከ1800 በላይ ምእመናን የተሳተፉ ሲሆን፤ በጎንደር ፋና ኤፍ ኤም 98.1 ሬድዮ ጣቢያ ከጉባኤው በፊትና በኋላ የዘገባ ሽፋን አግኝቷል

 

የደሴ ማዕከል ግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያ ክፍል “መራኄ ፍኖት” የአንድነት የጉዞ መርሐ ግብር አካሔደ

ታኅሣሥ 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

 የደሴ ማዕከል ግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያ ክፍል እስከ ዛሬ ከተለመደዉና ግቢ ጉባኤያት ከሚያደርጉት ጉዞ ለየት ባለ መልኩ ደሴና ኮምቦልቻ የሚገኙ 9 ግቢ ጉባኤያትን፣ የደሴ ወረዳ ማዕከል አባላትን፣ አባቶችን እንዲሁም የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትን በአንድነት ያሳተፈ መራኄ ፍኖት የግቢ ጉባኤያት የአንድነት የጉዞ መርሐግብር ኅዳር 14 ቀን 2007 ዓ.ም በደብረ ነጎድጓድ ሐይቅ እስጢፋኖስ አቡነ ኢየሱስ ሞዓ ገዳም አካሄደ፡፡

 

በመርሐ ግብሩ ላይ 1359 የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና ከ70 በላይ የማዕከሉ አባላት፣ አባቶች እና በደሴ ከተማ ሰንበት ት/ቤቶች አንድነት ጉባኤ ሥር ካሉ ሰንበት ትቤቶች የተዉጣጡ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት ተሳታፊ ሆነዋል፡፡

 

መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎት ተጀምሮ በግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ያሬዳዊ ዝማሬ፤ በቦሩ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን መምህር አካለወልድ እና በመምህር ኃ/ማርያም ዘዉዱ ወደ ቅዱሳት መካናት ስንጓዝ ምን ማድረግ እንደሚገባ እና እንዲሁም የመንፈሳዊ ጉዞን ዓላማ መሠረት ያደረገ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡ ከደሴ ከተማ ከሚገኙ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ተጋብዘው በመጡ  መዘምራንም መዝሙር ቀርቧል፡፡

 

የተሳታፊዎችን ቀልብ የሳበዉ ሌላዉ መርሐ ግብር ምክረ አበዉ ሲሆን፤ “ወጣትነትና መንፈሳዊ ሕይወት” በሚል ርዕስ ቆሞስ አባ ኤልያስ ታደሰ፤ መ/ር ኃይለማርያም ዘዉዱ፣ ቀሲስ ጸጋዉ እና መሪጌታ ገብረ ማርያም በጋራ በመሆን በተለይ የወጣቱን ዝንባሌ በማገናዘብ ግቢ ጉባኤያትና ወጣትነት፣ ኦርቶዶክሳዊ  ወጣት ምን መምሰል አለበት፣ ስልጣኔ እና ሃይማኖት፤ እንዲሁም ሃይማኖትና ፍልስፍና በሚሉ ርእሶች ሰፋ ያለ ትምህርተ ሃይማኖትና አባታዊ ምክር ሰጥተዋል፡፡

 

የማዕከሉ የበገና ድርደራ ሠልጣኞች የበገና መዝሙር በማቅረብ ከተማሪዎች የተሰበሰቡ የተለያዩ ጥያቄዎች በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ እንዲሁም በ2006 ዓ.ም በወሎ ዩኒቨርስቲ ደሴ ካምፓስ ግቢ ጉባኤ ሰብሳቢ የነበረዉና የዋንጫና የሜዳሊያ ተሸላሚው ዲ/ን ቶሎሳ ታዬ፤ እንዲሁም በ2006 ዓ.ም የዚሁ ግቢ ጉባኤ ጸሐፊ የነበረችዉ ተማሪ የሺ ሀብተ ሥላሴ ልምዳቸዉንና ተሞክሯቸዉን  ለተሳታፊዎች አካፍለዋል፡፡ በደሴ ደብረ መዊዕ ቅድስት ኪዳነ ምሕረትና ቅዱስ መርቆሪዎስ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር በመሪጌታ ዳዊት አስማረ ቅኔ ቀርቧል፡፡
 

 

ለአብነት ደቀመዛሙርት የሕክምና አገልግሎትና የጤና አጠባበቅ ሥልጠና ተሰጠ

ታኅሣሥ 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ዲ/ን ደስታ ይዲ/ትባረክ /ከወልድያ ማዕከል/

በማኅበረ ቅዱሳን የወልድያ ወረዳ ማዕከል ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ኅዳር 14 ቀን 2007 ዓ.ም. በምሥራቀ ፀሐይ ወይብላ ማርያም ቤተ ክርስቲያን የአቋቋም ጉባኤ ቤት የአቋቋም ትምህርት በመማር ላይ ለሚገኙ ሃምሳ የአብነት ትምህርት ደቀመዛሙርት የሕክምና አገልግሎት፣ የጤና አጠባበቅ ሥልጠና እና የመጸዳጃ ቁሳቁሶች  ድጋፍ አደረገ፡፡

 

በዕለቱ ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ በስፍራው በመገኘት ለደቀመዛሙርቱ ትምህርተ ወንጌል በወልድያ ማእከል ጸሐፊ ዲያቆን ቃለ ጽድቅ ካሳ ማኅበረ ቅዱሳን የሚያደርገውን ድጋፍ እና አገልግሎት በማስመልከት “የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለትውልዱ ይዳረስ ዘንድ የእናንተ ደኅንነት መጠበቅ ቅድሚያ የሚሰጠው ተግባር በመሆኑ ማኅበረ ቅዱሳን የአገልግሎቱ ዋና ትኩረት አድርጎ የተለያዩ ተግባራትን ያከናውናል፡፡ የወረዳ ማእከሉ ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል የተለያዩ የሕክምና ባለሞያ አባላቱን በማስተባበር ይህን ስልጠና ለእናንተ አዘጋጅቷል፡፡ ምንም እናንተ ቃለ እግዚአብሔርን ያወቃችሁ ብትሆኑም ዘመኑን እየዋጀን ራሳችንን ልንጠብቅ እና ክርስትናችንን ልናጸና ስለሚገባ ሥልጠናው ከፍተኛ ጠቀሜታ ይኖረዋል” ብለዋል፡፡

 

ደቀመዛሙርቱ በጉባኤ ቤቱ በሚማሩበት ወቅት የሚያጋጥሟቸውን ችግሮች በተመለከተ ውይይት የተደረገ ሲሆን፤ በዋነኛነትም በተለያየ ምክንያት ከሥነ ምግባር ውጭ በመሆን ከምእመናን ጋር ያላቸውን ግንኙነትም ሆነ የትምህርት ቆይታቸውን ከሚያሰናክሉ ነገሮች ተቆጥበው የጀመሩትን ትምህርት እንዲያጠናክሩ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ጥረት ተደርጓል፡፡

 

በወረዳ ማእከሉ የሚገኙ የማኅበረሰብ ጤና አጠባበቅ፣ የዓይን፣ የሥነ ልቦና፣ የውስጥ ደዌ ሕክምና ባለሞያዎችን በማስተባበር ለደቀመዛሙርቱ ስለ ግል እና አካባቢ ንጽሕና፣ እንዲሁም በተለያየ ምክንያት ሊከሰቱ ስለሚችሉ ተላላፊ በሽታዎች ትምህርት ተስጥቷቸዋል፡፡ በተጨማሪም የዓይን፤ የሥነ ልቦና፣ የውስጥ ደዌ ሕክምና የሚያስፈልጋቸው የሕክምና አገልግሎት አግኝተዋል፡፡ የልብስና የገላ ንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁሶች ለሁሉም ደቀመዛሙርት በማከፋፈል፤ ለሆድ ውስጥ ሕመም የሚሆን መድኃኒት እንዲወስዱም ተደርጓል፡፡

 

ደቀመዛሙርቱም ትምህርተ ወንጌል እርስ በእርስ ለመማማር እና የስብከት ዘዴን ለማጠናከር የመጽሐፍ ቅዱስ ድጋፍ እንዲደረግላቸው ጥያቄ አቅርበዋል፡፡ ክፍሉም ከሚመለከታቸው አካላትና ከማኅበሩ አባላት ጋር በመሆን ለጥያቄያቸው ምላሽ እንደሚሰጥ ተገልጾላቸዋል፡፡

 

በተጨማሪም ለመጠለያ ቤት ግንባታ ፕሮጀት የወረዳ ማእከሉ ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል እንቅስቃሴ እንደሚያካሂድና ለመጸዳጃ ቤት መስሪያ የሚሆኑ ቁሳቁሶችን እንደሚያቀርብም ተገልጿል፡፡

 

የጉባኤ ቤቱ የአቋቋም መምህር መሪጌታ ሀብተ ማርያም በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልእክት “ማኅበሩን ከዚህ በፊት በሚሠራው ተግባር አውቀዋለሁ፡፡ በርካታ ፈተናዎችን እያለፈ ተስፋ ባለመቁረጥ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንዲህ መፋጠኑ ሊያስመሰግነው ይገባል፡፡ ዛሬም በዚህ ጉባኤ ቤት ላለን ይህን የመሰለ ሥልጠና እና የሕክምና አገልግሎት መስጠቱ የቤተ ክርስቲያንን ትንሣኤ የሚናፍቅ እና ለቤተ ክርስቲያን ጥብቅና የቆመ መሆኑን ያስገነዝበናል እና ተማሪዎቼም ብትሆኑ ይህን ልትገነዘቡ ይገባል፡፡ ከዚህ በተለየ በርካታ ችግሮች ስላሉብን ወደፊት ማኅበሩ አይዟችሁ እያለ ከጎናችን እንዳይለየን” ብለዋል፡

abune lukas 01

“ስለ ሃይማኖታችንና ስለ ቤተ ክርስቲያናችን ዘብ የምንቆምበት ወቅት አሁን ነው”

/ብፁዕ አቡነ ሉቃስ/

ኅዳር 26 ቀን 2007 ዓ.ም.

abune lukas 01የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በታሪክ ከገጠሟት ልዩ ልዩ ፈተናዎች ይልቅ በዚህኛው ትውልድ የደረሰባት ፈተና (ሙስናና ብልሹ አሠራር፤ የመልካም አስተዳደር እጦት፣ በውጭ ካሉ አባቶች ጋር ያልተቋጨው ዕርቀ ሰላም) ወደ ፊት እንዳትራመድ አድርጓታል፡፡ በእርግጥ የቤተ ክርስቲያኒቱ ወቅታዊ ችግሮች እነዚህ ብቻ ናቸው ማለት አይደለም፡፡ ችግሮችን ከማውራት ይልቅ መፍትሔው ላይ ማተኮር ለቤተ ክርስቲያኒቱም ለመንጋውም ጠቃሚ ስለሚሆን ነው እንጂ፡፡

 

በዚህ ሒደት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሃይማኖታዊና አስተዳደራዊ ችግሮች በጥልቀት እየተወያየ መፍታሔ የሚሰጠው ቅዱስ ሲኖዶስ በዘንድሮው ጥቅምት 2007 ዓ.ም ባካሔደው ጉባኤ ብዙ ደስ የሚያሰኙ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡ ይህንና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን አስመልክተን የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከሆኑት ከብፁዕ አቡነ ሉቃስ ጋር ያደረግነውን ቃለ ምልልስ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

የሠላሳ ሦስተኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በቅዱስ ሲኖዶስ እይታ ምን ይመስል ነበር?

የሠላሳ ሦስተኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በአህጉረ ስብከት፣ በድርጅቶች፣ በልማት ተቋማት ከፍተኛ ለውጥ የታየበት፣ በማኅበራዊና በሰብአዊ እንቅስቃሴም መልካም ነገሮች የታየበት ነው፡፡ ዕድገት ነበረው፤ ለውጥ ነበረው፡፡ ይሁን እንጂ በስብሰባው ላይ አላስፈላጊ የሆኑ ጎኖች ነበሩት፡፡ ይህም ጥቂት የሚባሉ ታዛቢ ግለሰቦች የፈጠሩት ሁካታ፤ አግባብነት የሌለው ጥያቄ ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ይህን ክፍተት እንደ እጥረት በማየት እርምት እንዲሰጥ በምልዓተ ጉባኤው ወስኗል፡፡

 

ወደፊትም እንዲህ አይነት ችግር እንዳይፈጠር ቃለ ዐዋዲው፤ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ በሚያዘው መሠረት ጉባኤው የሚመለከታቸው ተሳታፊዎችና ታዛቢዎች ቦታ ቦታቸውን ይዘው እንዲቀመጡ ይሆናል፡፡ በጋራ መግለጫው የተወሰኑትንና ቅዱስ ሲኖዶስ እርምት እንዲሰጥባቸው የወሰነባቸውን ተግባራት መፈጸምና አለመፈጸማቸውን ክትትል የሚያደርጉ ቋሚ ሲኖዶስ፣ ጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ የአህጉረ ስብከት ሊቃነ ጳጳሳት ናቸው፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ጊዜ ወስዶ በጥልቀት የተወያየባቸው ነጥቦች ምን ምን ናቸው?


የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የውይይት አጀንዳዎች አጠቃላይ 21 ነበሩ፡፡ በውይይቱ ወቅት ሰፊ ጊዜ የወሰደው አንደኛው አጀንዳ የተረቀቀው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ መወያያ አሳቡም ሊቃነ ጳጳሳቱ ተጠሪነታቸው ለማን ይሁን የሚለው ጉዳይ ነበር፡፡ የፊተኛው ሕገ ቤተ ክርስቲያን ለቅዱስ ሲኖዶስ ይላል፡፡ አሁን ግን ሊቃነ ጳጳሳቱ ተጠሪነታቸው ለፓትርያርኩና ለቅዱስ ሲኖዶስ የሚል አሳብ ተነሥቶ ሰፊ ውይይት ከተደረገ በኋላ ሐዋርያት ተጠሪነታቸው ለአንዱ እግዚአብሔር ነው፡፡ የጉባኤው መሪ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ በፊትም አሁንም ሊቃነ ጳጳሳቱን የሚሾመው ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡ ስለዚህ የሊቃነ ጳጳሳት ተጠሪነት በፊት በነበረው እንዲቀጥል በአንድ ድምፅ ተስማምተዋል፡፡

 

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የሊቃነ ጳጳሳት ዝውውርም ተነሥቷል፡፡ ሊቃነ ጳጳሳትን ማዘዋወር የሚችለው ቋሚ ሲኖዶሱ መሆን እንዳለበት ምልዓተ ጉባኤው ወስኗል፡፡ ለሃይማኖት፣ ለሥርዓት፣ ለምእመናንና ለሀገሪቱ የሚጠቅሙ ብዙ አሳቦች በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ እንዲካተቱ ተደርጓል፡፡

 

ሁለተኛው የማኅበራት ጉዳይ ነው፡፡ በልዩ ልዩ አገልግሎቶች በማኅበር ስም ተደራጅተው ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉ ማኅበራት በምን መልኩ በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ሥር ይሁኑ በሚለው ምልዓተ ጉባኤው በስፋት ተወያይቷል፡፡ እገሌ ጥሩ ነው እገሌ መጥፎ ነው የተባለ ማኅበር የለም፡፡ ልጆቻችን ለቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎት ጠቃሚዎች ናቸው፤ መጀመሪያ ሰዎች ለቤተ ክርስቲያን ያስፈላጓታል በማለት ደስ ደስ የሚሉ አሳቦች ተነሥተዋል፡፡ በዚህም የልጆቻችን አገልግሎት ጠቃሚ እንደሆነ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በደንብ አምኖበታል፡፡

 

ልጆቻችንን ማቅረብና መውደድ እንደሚገባም ሁሉም ተስማምቷል፡፡ ስለዚህ ማኅበራት በሙሉ ተጠሪነታቸው ለሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ እንዲሆን ተወስኗል፡፡ ገቢያቸውንና ወጭያቸውን ቤተ ክርስቲያኒቱ በምትጠቀማቸው ሞዴላ ሞዴሎች እንዲጠቀሙ ተወስኗል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳንስ?


በማኅበረ ቅዱሳንም ላይ የተለየ አቋም የለም፡፡ ልጆቻችን፤ አገልግሎታቸው በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን እያሳየ ያለው ተግባር ጠቃሚ ነው፤ ገደማትን፣ የአብነት ትምህርት ቤቶችንና ሌሎች ልማቶችን በተመለከተ ማንኛውንም ሥራ በአጋርነት እየሠራ ያለ ትልቅ ማኅበር መሆኑን ምልዓተ ጉባኤው አምኗል፡፡ እንዲያውም ምሁራን ያሉበት፣ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለሃይማኖት፣ ለሥርዓት፣ ለሀገር፣ ለልማት የሚጠቅሙ ሰዎች ያሉበት ነው የሚሉ ትልልቅ አሳቦች ተነሥተዋል፡፡ ወደ ፊትም የቤተ ክርስቲያን ጠበቃ ሆኖ እንደሚቀጥል ታምኖበታል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳንን በተመለከተ ምልዓተ ጉባኤው በአንድ ድምፅ በዚህ መልክ ነው የተረዳው፡፡ ለአሁኑ ቀድሞ ወደ ነበረበት ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ሆኖ ተጠሪነቱ ግን ለማደራጃ መምሪያው ሊቀ ጳጳስ እንዲሆን ተወስኗል፡፡ ቁጥጥሩን፣ ግምገማውንና ክትትሉን የሚያደርገው ደግሞ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ነው፡፡

የማኅበራት ሕግ ሲወጣም እንደ ማኅበረ ቅዱሳን ያሉት ማኅበራት ክፍል “ሀ”፣ ሌሎች ማኅበራት ክፍል “ለ” በሚል አደረጃጀት ሥርዓት እንዲይዝ ይደረጋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ገንዘቡን በቤተ ክርስቲያኒቱ ሞዴላ ሞዴሎች እየተጠቀመ ለሚፈለገው አገልግሎት እንዲውል በሚል ተወስኗል፡፡ ገንዘቡ ለምን ለምን አገልግሎት እንደ ዋለ መከታተል እንጂ ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚመጣ የለም፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በጥልቀት አይቶ በስፋት ተመልክቶ አስደሳች በሆነ መልኩ የወሰነው ይኼን ነው፡፡

 

ሌላው ስለ ሰላም ነው፡፡ ያለ ሰላም እግዚአብሔርን ማየት አይቻልም እንዲል ቅዱስ ጳውሎስ በውጭ ያለው ዕርቀ ሰላም እንዲቀጥል ተወስኗል፡፡ ዝርዝር ሁኔታው ወደፊት የሚወሰን ይሆናል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ አጀንዳዎች 21 ሆነው ሳለ በመግለጫው ግን 9ኙ ብቻ ነበር እንዲካተቱ የተደረገው፣ ለምን?


የዚህ ምክንያት ቅዱስ ሲኖዶስ ለዓለም መገለጽ የነበረባቸውን ለይቶ ነው መግለጫ የሰጠው፡፡ ሌላው የቤተ ክርስቲያኒቱ የውስጥ አሠራር ስለሆነ ውሳኔዎቹ ተለይተው ነው የቀረቡት፡፡

ሙስና ቤተ ክርስቲያኗን ምን ያህል ነው የጎዳት?

 

ያለፉትን ጊዜያት ጨምሮ አሁን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ሁኔታ ስናይ በሙሰኞች እየታመሰች ትገኛለች፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ስሟ በማይገባ (በሙስና) እንዲጠራ አድርገዋል፡፡ የእነዚህ ሰዎች ማንነት ሲፈተሸ ደግሞ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያሉ ነገር ግን የቤተ ክርስቲያን ሰዎች ያልሆኑ ገንዘቧን እንደፈለጉ የሚጠቀሙ ናቸው፡፡ በሌላ በኩል ቤተ ክርስቲያኗ የመልካም አስተዳደር ባለቤት እንዳትሆን በተለያየ ስልት ሲያከሽፉ ቆይተዋል፡፡ በተለይ ችግሩ እንደመዥገር ተጣብቆ ያለው አዲስ አበባ ላይ ነው፡፡

 

በቤተ ክህነቱ ቀልጣፋና ዘመናዊ አሠራር እንዳይሰፍንና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የማይገባቸውን ቦታ ስም እንዲሰጣቸው አድርጓል፡፡ የችግሩ ስፋት በዚህ አያበቃም፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱን በዘረኝነትና በጎጠኝነት እንድትተበተብ የፈጠረው ቁርሾ ከባድ ነው፡፡ ገጠር ብትሔድ እንዲህ ዓይነት ችግር የለም፡፡

ካህኑም ምእመኑም ጉቦ አይሰጥም፣ አይቀበልም፡፡ ችግሩ ያለው አዲስ አበባ ዙሪያ ነው፡፡ ለሕዝቡም እየነገርን ከርመናል፤ አንተ ሕዝብ ገንዘብህን ጠብቅ!፤ አንተ ወጣት ቤተ ክርስቲያኗን ከነጣቂዎች ጠብቅ! እኛ ማስተማር ስላለብን ስንናገር ከርመናል፡፡

 

እንደ እውነቱ እኮ እኛ እየመራናቸው፣ ሰንበት ተማሪዎቻችን ጠንካራ ቢሆኑ ኖሮ ከሰባክያን፣ ከቀሳውስትና ከማኅበራት ጋር ተባብረው ሙስናን ከቤተ ክርስቲያን ለማጥፋት ይበቁ ነበር፡፡ በደንብ ተደራጅተው ገንዘቧን የሚበሉትን መቆጣጠር ይችሉ ነበር፡፡ ሌባ ፈሪ ነው፤ ሌባ ግንባር ለግንባር አይዋጋም፡፡ በሙዳየ ምፅዋቱ ብቻ ታጥረው ቀሩ እንጅ እንደቅዳቸው ቢሆንማ ቤተ ክርስቲያኗን ያጠፏት ነበር፤ ግን አልሆነላቸውም፡፡

ወደ ፊት ሙስናን ከቤተ ክርስቲያቱ ለማጥፋት ምን የተጀመረ እንቅስቃሴ አለ?

ይህ የሚያበቃበት ጊዜ በቅርብ ቀን እንደሚሆን እምነት አለኝ፡፡ ሙስና ይቁም እያልን ሁሉ ጊዜ ስንጮህ ቆይተናልና፡፡ መጀመሪያ መሣሪያ ይዞ ማስወጣት ሳይሆን ማስተማር ስላለብን ቀደም ብለን እያንዳንዱ ምእመን እስኪሰርጸው ድረስ እያስተማርን ነው፡፡ አሁን ግን በአባቶቻችን ሊቃውንት እየተረቀቀ ያለው መሪ እቅድ ሲጠናቀቅ የሙሰኞች ሰንሰለት ይበጣጠሳል ብለን እናምናለን፡፡ ምክንያቱም መሪ ዕቅዱ ለካህናቱ፣ ለሰበካ ጉባኤው፣ ለሰንበት ተማሪዎች፣ ለማኅበራቱ ከፍተኛ አቅም ይፈጥርላቸዋል፡፡ እነዚህ አካላት ተባብረው ከሠሩ ቤተ ክርስቲያን ከሙስና ትጸዳለች፡፡

 

በዚህ አሠራር ሁሉም የድርሻውን ከተወጣ የሚፈለገው ለውጥ ይመጣል ባይ ነኝ፡፡ በመሪ ዕቅዱ ካህኑ፣ አለቃው፣ ሒሳብ ሹሙ፣ ፀሐፊው እስከ የት ድረስ ነው ሓላፊነታቸው፣ የተቆጠረው ገንዘብ መዋል ማደር ያለበት የት ነው፤ ገንዘብ ቆጠራው ላይ ማን ይገኝ እና ሌሎች አሳቦች ይካተታሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቷ በምእመናን እጅ፣ በካህናት እጅ ስትሆን ነው ትክክል የምትመጣው፡፡ አለበለዚያ. . . ቤተ ክርስቲያኒቱን ባዶ ያደርጓታል፡፡ ይህ መቆም አለበት፡፡ እስከዛው ግን እያስተማርን እንደሆነ ሙሰኞች ይወቁት፡፡

ይልቅስ?


ቤተ ክርስቲያኒቷ ገና ያልሠራቻቸው ብዙ የቤት ሥራዎች አሉባት፡፡ ይህንን ነው መሥራት፡፡ ቤተ ክርስቲያን ብዙ የልማት ሥራዎች ያስፈልጓታል፡፡ በበቂ ሁኔታ የረዳናቸው ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች የታሉ?፣ የምናሳድጋቸው ዕጓለማውታ ሕፃናት የታሉ? የታለ አረጋውያንን የምንጦረው? ስብከተ ወንጌል ያልተዳረሰባቸውን ጠረፋማ አካባቢዎች የታለ አስተምረን ያስጠመቅናቸው? ቤተ መጻሕፍት አዳራሽ የት ነው ያለው?፤

 

መኪና ጋራዥ ገብቶ ሲለወጥ እኛ ግን ሰውን የምንለውጥበት መንፈሳዊ ጋራዥ የት ነው ያለው? ስለዚህ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ ማኅበራት፣ አባቶት ካህናት እንደዚሁም ደግሞ ከላይም ከታችም ያሉ ምእመናን በሙሉ መጀመሪያ ትኩረታቸው ስለ ቤተ ክርስቲያን እምነትና ሥርዐት፣ ስለ ልማት፣ ስለ አንድነትና ስለ ፍቅር መሆን ይገባዋል፡፡ አበክሬ የምገልጸው የእምነታቸው፣ የሥርዓታቸው፣ የታሪካቸው፣ የሀገራቸው ፍቅር እንዲኖራቸውና ለሃይማኖታቸውና ለሀገራቸው ጠበቃ እንዲሆኑ ነው፡፡

በተለይ ማኅበራት፡- በአሁኑ ጊዜ ቁጥራቸው ቀላል የማይባሉ ማኅበራት አሉ፡፡ መጀመሪያ ቤተ ክርስቲያንን ማስቀደም አለባቸው፡፡ የእኔ መኖር ለቤተ ክርስቲያን ምን ጠቀመ? ማለት አለባቸው፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ተጠግተው የእኔ ድርሻ ምን መሆን አለበት ብለው አባቶችን በመጠየቅ መሥራት ይኖርባቸዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ሁሉም ሰው ለቤተ ክርስቲያን ዘብ መቆም አለበት፡፡ ይህቺ ጥንታዊትና ሐዋርያዊት የሆነች ቤተ ክርስቲያናችን እና አንጋፋ ሀገራችን በልጆቿ ማፈር የለባትም፤ ሌቦች ጥቂት ሆነው ብዙዎች ደጅ ሆነው ሲመለከቱ ያሳፍራል፣ በቤተ ክርስቲያኒቷ ሙስና አለ ማለት ያሳፍራል፣ በቤተ ክርስቲያን ድሆች ሲጦሩ፣ ልጆች ሲማሩ፣ መጻሕፍት ሲነበቡ አለማየት ያሳፍራል፡፡ ስለዚህ በአንድነት ስለቤተ ክርስቲያን ዘብ የምንቆምበት ጊዜ አሁን ነው፡፡

 

በቤተ ክርስቲያኒቷ አሁን ያለው እጥረት ተቀራርቦ አለመሥራት፤ አለ መወያየት ነው፡፡ እኛ በአብዛኛው ያሳለፍነው በመወነጃጀል ነው፡፡ ይሄ ደግሞ አየነው የት እንዳደረሰን፡፡ አንዱ አንዱን ሲወነጅል ቤተ ክርስቲያኗን ምን ያህል እንደጎዳት፤ ምን ያህል እሞት አፋፍ እንዳደረሳት ባለፉት ጊዜያት አይተነዋል፡፡ ሁሉም በየራሱ የሚሔድ ከሆነ በጎ አይሆንም፡፡ ተቀራርቦ መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ትልቅ የመቀራረብ ሥራ መሠራት አለበት፡፡

 

በአባቶቻችን መሪነት አንድ ሆነን አንተ በዚህ ዝመት፤ አንተ በዚህ ሒድ መባባል ይቻላል፡፡ እንደ ገበሬ አረሙን ወደ ውጭ እየጣሉ፣ የወደቀውን ሰው እያነሡ መሔድ ይቀረናል፡፡ ተቀራርቦ አለመተቻቸትም ይቀረናል፡፡ ጥሩ ወተት ለማግኘት እላሟ ሥር ያለውን መዥገር መንቀል ያስፈልጋል፡፡ ሁሉም በየራሱ መቅረት መተው አለበት፡፡ አሁንም ጊዜው አለ ተቀራርበን እንሥራ ነው የምንለው፡፡ ምእመናንን ከተኩላዎች፣ ከነጣቂዎች መጠበቅ አለብን፡፡

 

በተጠራጣሪዎችና አማኝ ባልሆኑ አካላት የሚነገር፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከት ዘለፋ ከቀያጮች፣ ከበራዦች፣ ከስም አጥፊዎች የሚላኩ የኑፋቄ ቃላትን አለመቀበል ነው፡፡ የዘመኑን መሣሪያ ተጠቅመው ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት የሚተጉ ተቃዋሚዎች ብዙዎች ናቸው፡፡ እነዚህን መቃወም መቻል አለብን፡፡ ሌላው ሥርዓቱንና ትውፊትን መጠበቅ ነው፡፡ ኦርቶዶክሳዊ የሆነው ሥርዓቱን እያከበረ ሌሎችን ይወዳል፣ እምነታችን ሁል ጊዜ የአንድነት፣ የሰላም ምልክት ናት፡፡ መሠረታችን ፍቅር ነው፡፡ ቃሉ ሰውን ውደድ ስለሆነ በዚህ እንትጋ ነው የምለው፡፡

ምንጭ፤- ስምዐ ጽድቅ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኅዳር 1-15 ቀን 2007 ዓ. ም.

በአገልግሎታችን የሚከሰቱ ፈተናዎችን የምናልፋቸው በእግዚአብሔር ኃይል ነው

 ኅዳር 23 ቀን 2007 ዓ.ም.

ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠናከር በርካታ ተግባራትን እንደ አንድ የቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ ሲፈጽም የቆየ የአገልግሎት ማኅበር መሆኑ ይታወቃል፡፡ ምንም እንኳን ማኅበሩ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመንፈሳዊ ዓላማ የተቋቋመ ቢሆንም መልካም ነገርን የማይወደው ጥንተ ጠላት ሰይጣን ዲያብሎስ የተለያዩ ፈተናዎችን ሲጋርጥበት ኖሯል፡፡ ማኅበሩም የሚደርሱበትን ፈተናዎች ከምእመናን፣ ከካህናትና ከብፁዓን አባቶች ጋር በመሆን በትዕግሥትና በጸሎት ሲያልፋቸው ቆይቷል፡፡

 

አንዱን ሲያልፍ ሌላው እየተተካም ከዚህ ደርሷል፡፡ ምንም እንኳን በየጊዜው ፈተናው መልኩን እየቀየረ ቢመጣም ማኅበሩ ከኃይለ እግዚአብሔርና ከአባቶች የኖላዊነት ተግባር ውጭ የሚመካበት ነገር የለውምና ይህንኑ አጋዥ አድርጎ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚያስፈልጋትን ያህል ባይሆንም “ጋን በጠጠር ይደገፋል” እንዲሉ የተቻለውን አገልግሎት ለመስጠት ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡

በየጊዜው ከተነሡት ፈተናዎች መካከል አንዱ በቅርቡ የተከሰተውና ማኅበሩን ቅድሚያ በማኮላሸትና በመምታት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለማጥቃት የሸመቀው የአፅራረ ቤተ ክርስቶያንና የተሐድሷውያኑ ዘመቻ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያኒቱን ገንዘብ በመመዝበር የግል ጥቅማቸውን ለማሳካት በሚጥሩ ኃይሎች የተጀመረው የተቀናጀ እንቅሰቃሴ ነው፡፡ እነዚህ አካላት በተደጋጋሚ እያቀዱ የጀመሩት አልሳካ ሲል «እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ባንሔድ፣ ከፈቃዱም ተቃራኒ ብንሆን ነው» ብለው ራሳቸውን ከመመርመር ይልቅ ውስጥ ለውስጥ ሥራቸውን ሲሠሩ ከቆዩ በኋላ በዚህ በያዝነው ዘመን መስከረም ወር መጨረሻ ጀምሮ በስውር ሲያደርጉት የነበረውን ፈተና በስም ማጥፋት መልኩ ወደ ዐደባባይ ማውጣት ጀመሩ፡፡

 

የቤተ ክርስቲያኒቱን አምልኮተ እግዚአብሔር ወደ ተሐድሶ መናፍቅነት ለመቀየርና የግል ጥቅማቸውን ለማካበት የሚፈልጉት እነዚህ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን “ለእንቅስቃሴያችን ማኅበሩ እንቅፋት ነው፤ ማኅበሩ ካለ ያሰብነውን ማሳካት አንችልም” የሚል የጥፋት አቅጣጫ ይዘው በመነሣት ከተለያዩ አካላት ጋር ሊያጋጩት ሞከሩ፡፡ የውሸት ክስ ጸንሰውም በዐደባባይ ማኅበሩን ወቀሱት፡፡ አንደበታቸው ባቀበላቸው ልክ የስድብ ናዳ አወረዱበት፡፡ በሠሩት ጎዳና እንደ ልባቸው ለመመላለስ እንዲረዳቸውም ያሸማቀቅንና ያስፈራራን መስሏቸው አገልጋይ ምእመናንንና ለቤተ ክርስቲያን የሚቆረቆሩ ብፁዓን አባቶችን አሻቅበው ተሣደቡ፡፡

በጣም የሚደንቀውና የሚገርመው እነዚህ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዓመት አንድ ጊዜ የምትጠራውን የአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፣ ዓለማዊ በሆነ ጥበብ መጠቀሚያ ለማድረግና ውጤቱም በቀጣዩ ቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ላይ ተፅፅኖ እንዲፈጥር በማሰብ በስብሰባው ውስጥና በማይጠበቅ ቦታ የማይጠበቅ ተግባር የፈጸሙ መሆኑ ነው፡፡

በዚህ ድርጊት ያዘነው ሕዝበ ክርስቲያን ግን ፈተናዎቹ ዐዲስ ባይሆኑበትም ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ጠብቀው ዐሥራት በኩራታቸውን በሚያዋጡ ምእመናን ገንዘብ የሚኖሩ አገልጋይ ነን ብለው ራሳቸውን በሚያሞካሹ የተወሰኑ ግለሰቦች እንደዚህ ዓይነት አሳፋሪ ተግባር መፈጸሙ እንደ መንፈሳዊነቱ የሚያሳዝን ቢሆንም ለእውነት የቀና ልቡናን ስጣቸው ብሎ ወደ ፈጣሪ ከመጸለይ ውጭ የሚለው የለም፡፡ እግዚአብሔር ዕድሜ ለንስሐ የሚሰጥና ሁሉን የሚፈጽምበት የራሱ ጊዜ አለው፤ እስከዚያው ድረስ ግን ውሸት የሕዝበ ክርስቲያኑን ኃዘን ግምት ውስጥ ሳታስገባና ሕገ ቤተ ክርስቲያን ይገሥጸኛል ሳትል በዐደባባይ ፈረስ መጋለቧን በመቀጠሏ የቤተ ክርስቲያን ልዕልና እየተነካ፣ በቤተ ክርስቲያን የቤተ ክርስቲያን ሰዎች መስለው የሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች መልካም ስም ላላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጥላሸት የሚቀባ እየሆነ መጣ፡፡

 

የራሷን ችግር በራሷ መፍታት የምትችለው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሥርዓት አልባዎች ሥርዓት የሌላት እስከመምሰል ደረሰች፡፡ ማኅበሩ የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ አካል ቅዱስ ሲኖዶስ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት መስፋፋት ውሳኔ እንደሚሰጥና ችግሮችን ሁሉ እንደሚፈታ ያምናልና በመንፈስ ቅዱስ ለሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊ ፍትሕ ያገኝ ዘንድ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ ጥያቄውን አቀረበ፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ ወሳኝ አካል የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስም ሁኔታውን አጥንቶና አጣርቶ በምልዓተ ጉባኤው ውሳኔ ሰጠ፡፡ ይህም በመሆኑ የቤተ ክርስቲያን የሆኑ አካላት ሁሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡

ማኅበሩም በተፈጸመበት የስም ማጥፋት ድርጊት እጅግ ያዘነ ቢሆንም፣ ከንቱ የሆነውን ውንጀላ እንደ ፈተናነቱ ከመቀበል ውጭ አማራጭ አልነበረውም፡፡ ያላደረገውን አደረገ፤ የሠራውን አልሠራም እየተባለ ፍጹም አሳዛኝ የሆኑ የስም ማጥፋት ጾሮች የተወረወሩበት ማኅበረ ቅዱሳን እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት፣ ዕድሜ ለንስሓ ዘመን ለፍስሐ የሚሰጥበት ቀን አለው ብሎ ስለሚያምን እግዚአብሔር እንደፈቀደ አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ ምእመናን በጸሎትና በዕንባ፣ በየበረሃውና በየገዳማቱ ያሉ መነኮሳት በምኅላ፣ የማኅበሩ አገልጋዮች በትዕግሥት፣ ብፁዓን አበው በውሳኔያቸው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያልሆነውን መንፈስ ገሠጹት፡፡

ይህንን ከቅዱስ መንፈስ ያልሆነ ትጋት ቅዱስ ሲኖዶስ መርምሮ እንዲቆምና እንዲታረም አቅጣጫ ባይሰጥበት ኖሮ የቤተ ክርስቲያኒቱን ንጹሕ አገልግሎት አዳክሞና ጥላሸት ቀብቶ የሚያልፍ ነበር፡፡ ይህም አፅራረ ቤተ ክርስቲያን መረባቸውን ከላይ እስከ ታች የዘረጉት የተሐድሶ መናፍቃን አቀንቃኞችና በቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብትና ንብረት የግል ሀብታቸውን ማካበት የለመዱት አማሳኞች በአጭር ጊዜ ውስጥ የቤተ ክርስቲያኒቱን ልዕልና ተደፋፍረው እንዳልሆነች ለማድረግ በመቀናጀት የተንቀሳቀሱበት ነው፡፡ ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ የተደበቀውን መርምሮ፣ የራቀውን አቅርቦ ለጥፋት የተነሣሣውን መንፈስ ገሥጾታል፡፡

በዚህ ለቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት መጠናከር አኩሪ በሆነው መንፈሳዊ ውሳኔ ምእመናን፣ አገልጋይ ካህናትና የገዳማት አባቶች ከእሱ ፈቃድ ውጭ ምንም ማድረግ የማይቻልበትን እግዚአብሔርን በማመስገን፤ እንደ ቀድሞው ሁሉ ተስፋቸውን በዚሁ የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ አካል በሆነው በቅዱስ ሲኖዶስ ላይ አድርገዋል፡፡

ከዚህ በኋላም ቢሆን እንኳን ለእኛ ለደካሞቹ፣ ለጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያልተኛው ጠላት ዲያብሎስ የተቃናውን ለማጣመም፣ የቀረበውን ለማራቅና የተሰበሰበውን ለመበተን ጦሩን ወደ ሰገባው አይመልስምና ባንዱ ሲሸነፍ በሌላ አቅጣጫ እየመጣ የቤተ ክርስቲያናችንን አገልግሎት ለማደናቀፍ ጉድጓድ መቆፈሩ ስለማይቀር እንደነዚህና መሰል ችግሮች ከዚህ በኋላም ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ በመሆኑም እንደ ሰሞኑ ሁሉ ወደ ፊት የሚመጣውን የሰይጣን ፈተና ኃይለ እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጎ እንዲገሠጽ፤ ከላይ እስከ ታች በየተዋረዱ ያሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮችና ምእመናን ፈተናውን በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ለማለፍ በጸሎትና በአገልግሎት ሊተጉ ይገባል፡፡

ክርስቲያን ኃይሉ እግዚአብሔር ነውና እግዚአብሔርን በጸሎት በመጠየቅ እያንዳንዱ ነገር ሲከሰት ምን ይዞ እንደመጣ፣ የተቀነባበረበትን ዓላማ በመረዳትና በመገንዘብ ለቅድስት ቤተክርስቲያን አገልግሎት «እንደ ርግብ የዋኆች እንደ እባብ ልባሞች ሁኑ» ማቴ. 10÷16 ተብሎ የተጻፈውን አምላካዊ ቃል መፈጸም ይሆናል፡፡ የችግሩን ምንጭ ከሥር መሠረቱ ከተረዱ በኋላም ለቤተ ክርስቲያን በመናገርና ቅዱስ ሲኖዶስ በሚሰጠው ውሳኔና አቅጣጫ መሠረት ሐዋርያዊ ተልዕኮዋ የተጠናከረ ሆና ትቀጥል ዘንድ በአገልግሎትና በጸሎት መትጋት ያስፈልጋል፡፡

ምእምናን፣ በየተዋረዱ ያሉ አገልጋይ ካህናት እንዲሁም ብፁዓን አባቶች ለቤተ ክርስቲያን በሚያደርጉት መንፈሳዊ ጽናትና ትጋት የሰይጣን ቀስት እየወደቀ፣ አቅሙ እየደከመ፣ ተስፋ እየቆረጠ ይሔዳል፡፡ በዚህም የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ከመቼውም በላይ የተፋጠነ ሆኖ፤ ክብሯ ሳይነካ፣ ማንነቷ ሳይበረዝ ሥርዓቷና ትውፊቷ እንደተጠበቀ ከትውልድ ወደ ትውልድ ትቀጥላለች፡፡

ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቀናው ማኅበረ ቅዱሳን የፈተናዎቹ ጥንስስና ዝግጅት በአፀደ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የማይጠበቅ በመሆኑ ቢያዝንም በአባላቱ ፅናት፣ በምእመናን ድጋፍና በብፁዓን አባቶች ውሳኔ ሥውሩ ደባ ስለተገለጠ፤ በጨለማ ወይም በግንብ ውስጥ ወይም ማንም አላየኝ በሚል በስውር ሆኖ ማንም ቢሠራ ከእሱ ሊሠወር የማይችለው እግዚአብሔር፣ አፅራረ ቤተ ክርስቲያንን ያስታግሥልን፤ አገልግሎታችንን ይባርክልን፤ አባቶቻችንን ይጠብቅልን ከማለት ውጭ የሚለው ነገር የለም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ፅኑ ዓላማው ኃይለ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመልካም ጎዳና ላይ እንድትራመድ ሲሆን፤ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ የሚያዝነው ደግሞ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መገፋትና የነገረ ሃይማኖት መፋለስ ሲደርስ ነው፡፡

 

በመሆኑም በእውነት በማኅበሩ የተፈጸመው የቤተ ክርስቲያኗ አገልግሎት ከእውነታው ውጭ በሆነ መንገድ በዐደባባይ ሲሰደብና ሲከሰስ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ አዝኗል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ሲሰጥ ደግሞ ውሳኔው ለቤተ ክርስቲያኒቱ ስለሚበጅ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይግባው ብሏል፡፡ ለዚህም የምእመናን ኀዘን፣ በየተዋረዱ ያሉ የአገልጋይ ካህናትና ብፁዓን አባቶች ጥረትና ትጋት እግዚአብሔር ከሰጣቸው ሓላፊነት የሚጠበቅ ቢሆንም፣ ከውንጀላዎቹ በስተጀርባ ከተዘጋጀው ዕቅድ አንፃር የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን አባቶች የኖላዊነት ተግባር ሁላችንም እንድናይ አድርጎናል፡፡

ምንም እንኳን እግዚአብሔር አምላክ ስለ ቤተ ክርስቲያን ለሚገፉና በእውነት ወደ እርሱ ለሚቀርቡ ሰዎች ዋጋ የሚከፍል ቢሆንም፤ በሰው ሰውኛው ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቆጩና የሚያዝኑ ምእመናንንና ደፋ ቀና የሚሉ አባቶችን የአገልግሎት ዘመን ይባርክልን ልንልበት ይገባል፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ምድራዊ ያልሆነ ሰማያዊ ዋጋ ለማግኘት ስለሆነ የሚገፋውና የሚተቸው በዚህ ምክንያት ለቤተ ክርስቲያኒቱ ካለው ቁርጠኛ አቋም የተነሳ ነው፡፡ ዓላማው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትምህርተ ሃይማኖት፣ ሥርዓትና ትውፊት ተጠብቆ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ ማድረግ ነውና ይህንን ዓላማውን እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጎ፣ በብፁዓን አበው ፈቃድ ተመርቶና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እናት አድርጎ እንደ ባለቤቱ ፈቃድ ይቀጥላል፡፡ ክርስትናና ፈተና እስከመጨረሻው ትግል እየገጠሙ የሚኖሩ እንደ መሆናቸው መጠን የቱንም ያህል ለማገልገል በሚያደርገው ሩጫ ስሕተት ከታየበትም በአባቶች ለመታረምና ለመታዘዝ ዝግጁ ሆኖ አገልግሎቱን ይፈጽማል፡፡ ጠላት ቢነሣበትና ስለ ቤተ ክርስቲያን ግፍ ቢደርስበት እግዚአብሔርን እስከ ያዘ ድረስ ከዓላማው ወደ ኋላ አይልም፡፡

በመሆኑም በየወቅቱ ለሚከሰቱ ፈተናዎች ኃይለ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ የምድራዊቷን ሳይሆን የሰማያዊቷን ኢየሩሳሌም ወራሽ ለመሆን በጸሎት ከመትጋት ውጭ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ጠላት ዲያብሎስን የሚያሳፍርበት መንገድ የለውምና በቤተ ክርስቲያናችን ላይ በየጊዜው ለሚከሰቱ ችግሮችና በአፅራረ ቤተ ክርስቲያን ለሚነሱ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለሚሸረሽሩ ፀረ ኦርቶዶክሳዊ አቋሞች ሕዝበ ክርስቲያኑ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ውሳኔ መስጠታቸውን በፅናት የተከታተለበት ሁኔታ ምንጊዜም ከአንድ ሕዝበ ክርስቲያን የሚጠበቅ ነው፡፡

ፈተናው በቤተ ክርስቲያን ላይ እንጂ በማኅበሩ ላይ ብቻ የመጣ ስላልሆነ እያንዳንዳችንም ለምድራዊ ሕይወታችን ስንተጋ ቤተ ክርስቲያንን ስለረሳንና እግዚአብሔር ስለሚወደን ፈተናው ለተግሣፅ፣ ለአመክሮና ለተዘክሮ የመጣ ነው ብለን ማመን አለብን፡፡ በመሆኑም ከቤተ ክርስቲያን የራቅን ቀርበን፤ ራሳችንን በቅዱስ ቃሉ በማነፅ፤ በሰበካ መንፈሳዊ አገልግሎት በትጋት በመሳተፍ፤ ዐሥራት በኩራታችንን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመስጠት፤ ልጆቻችንን ከሕፃንነታቸው ጀምሮ በሰንበት ትምህርት ቤት ተኮትኩተው እንዲያድጉና ተተኪ እንዲሆኑ በማድረግ፤ ሩቅ ሆነን ይህ ጎደለ በሚል ብቻ ጣት ቀሳሪዎች ሳንሆን፤ ባለቤቶችና ችግር ፈቺ እንዲሁም የጎደለ ሞይ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንና የአባቶች ተላላኪና አጋዥ መሆን እንደሚጠበቅብን ልንገነዘብ ይገባል፡፡

 

ይህ ክስተት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘመኑን የዋጀች ሆና አገልግሎቷን በሰፊው ለማድረስ ከሚጠበቅባት አንፃር ያለችበትን ሁኔታ እንድናውቅ ያደረገበት አጋጣሚ ስለሆነ፤ ከምንጊዜውም በላይ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ሁላችንም እንደየአቅማችንና ተሰጥዎአችን ድርሻችንን ልንወጣ ያስፈልጋል፡፡ አላወቅንም እንዳንል በምንወደው ድራማ በሚመስል እውነተኛ ታሪክ የተገለጸልን መልእክት ገና ያልበረታን መሆናችንን እግዚአብሔር በማየቱ ለማስተማር ነውና፤ ዋጋ በመስጠት «የሰው ልጅ ሕይወቱንና ዘለዓለማዊ ቤቱን አጥቶ ዓለሙን ቢያተርፍ ምን ይበጀዋል» ተብሎ እንደተጻፈ ማቴ 16÷26 ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከቀድሞው ይልቅ ልንተጋ ይገባል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ባለማወቅ የእርሱን መለኮታዊ ኃይል በመገዳደር እና በድፍረት ቤተ ክርስቲያኒቱን የሚያሳድዱ አፅራረ ቤተ ክርስቲያንን ልቦናቸውን መልሶ፤ ማስተዋልን ያድልልን፤ ለቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎት ደፋ ቀና የሚሉትን ምእመናንን፣ ካህናትንና ብፁዓን አባቶችን ይጠብቅልን፤ ያበርታልን፡፡

በአጠቃላይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፈተናዋ ብዙ እየሆነ በመምጣቱ ልጆቼ! በማለት በምትጣራበት በዚህ ዘመን ልትልከውና በትክክለኛ አቅጣጫ ልትመራው የሚቻላትን ልጇን፣ እንደ ባዕድ ሰው ቆጥሮ ይህን ያህል ዘመቻ ለማድረግ የተሄደበት ሁኔታ ላላየው ሰው መታመን የማይችል ቢሆንም በመንፈሳዊ ዐይን ከተመለከትነው፡- ፈተናዎቹ የምንማርባቸውና የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ስም ያስነሱ ከመሆናቸው በቀር በግለሰብ ደረጃ አሸናፊም ሆነ ተሸናፊ የሌለባቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም በጉዳዩ ዙሪያ እያንዳንዳችን የቆየንባቸውን መንገዶች አግባብነት በጥበብ ሰማያዊ ደግመን ደጋግመን በመመርመር ለሰማያዊ እንጂ፣ የዚህ ዓለም ለሆነው ከንቱ ነገር እልህ ሳይዘን፣ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማጠናከር የሚያስችሉ ነገሮችን በመተጋገዝና በፍቅር ልንሠራ ይገባል፡፡

 

ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የቆመው ማኅበረ ቅዱሳን ከእግዚአብሔር በቀር ፍጹም የሆነ ማንም እንደሌለ በማመን፣ ካጠፋ ምንጊዜም ለመታረም ዝግጁ፣ በአባቶች ሲታዘዝም የተቻለውን ለመፈጸም የቀና፣ ለሕግና ለሥርዓት ተገዥ ሆኖ የሚሠራ መሆኑን እያረጋገጠ፤ ቀሪ የሆኑት ምድራዊ ሀብቶች እያንዳንዳችንን ጠልፈው ሳይጥሉን፣ የእግዚአብሔርን ኃያልነትና ቻይነት ሳንዘነጋ ራሳችንን እየመረመርን በታሪክ ተወቃሽ፣ በእግዚአብሔርም ተጠያቂ ላለመሆን በሰጠን ጸጋ ለመልካም ነገርና ለተቀደሰው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ቢያንስ እንቅፋት ላለመሆን ከበረታንም በመክሊታችን አትራፊ በመሆን፣ ምድራዊቷን ሳይሆን ሰማያዊቷን ኢየሩሳሌም ለመውረስና ሌሎችም እንዲወርሱ ምክንያት ለመሆን እንትጋ በማለት ማኅበሩ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን

ምንጭ፡- ሐመር ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኅዳር 2007 ዓ.ም.