abh 1

ለአብነት መምህራን የአቅም ማጎልበቻ ስልጠና ተሰጠ

የካቲት 12 ቀን 2006 ዓ.ም.

ህሊና ሲሳይ ከሐዋሳ

 

በማኅበረ ቅዱሳን ሐዋሳ ማዕከል የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ለግቢ ጉባኤያት የአብነት መምህራን ከጥር 21-23 2006 ዓ.ም የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ተሰጠ፡፡

abh 1በሐዋሳ ማዕከል መሰብሰቢያ አዳራሽ ሥልጠናው የተሰጣቸው የአብነት መምህራን ከሲዳማ፣ጌዲኦ፣አማሮና ቡርጂ ሀገረ ስብከት ከበንሳ፣ ዲላ፣ ይርጋጨፌ፣ ወንዶገነት፣ አርቤ ጎና፣ ሀገረ ሰላም፣ አማሮ፣ አለታ ወንዶ፣ እና ሐዋሳ ወረዳ ቤተ ክህነት የተመረጡ 13 የአብነት መምህራን ሲሆኑ የአቅም ማጎልበቻ ስልጠናው ትምህርተ ኖሎት፣የአብነት ትምህርትን የማስተማር ዘዴ፣የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ እና የባለ ድርሻ አካላት ሚና በሚሉ ርእሰ ጉዳዮች በውይይት፣ በገለጻ፣ እና በልምድ ልውውጥ መልክ በአሠልጣኝነት የተጋበዙት የአብነት መምህራንና የዩኒቨርስቲ መምህራን ሥልጠናው ሰጥተዋል፡፡

በሥልጠናው ወቅት የአብነት መምህራኑ በሀገረ ስብከቱ በካህናት እጥረት የተነሳ የገጠረ አብያተ ክርስቲያናት እየተዘጉና አብዛኛዎቹ የተሟላ አገልግሎት እንደማይሰጥባቸው ገልጸው በሀገረ ስብከቱ አዳዲስ የአብነት ትምህርት ቤቶች እንዲከፈቱና ያሉትን ጥቂት ትምህርት ቤቶች ማጠናከር የተሻለ አማራጭ እንደሆነ አስረድተዋል፡፡

በተጨማሪም የአብነት ትምህርት መምህራኑ የመማር ማስተማር ሂደት ላይ በርካታ ችግሮች እንዳሉባቸው ገልጸዋል፡፡ የአብነት ትምህርት ቤቶችና ተማሪዎች ትምህርታቸውን እንዳይከታተሉ ዋና ዋና ፈተናዎች ናቸው ተብለው ከተነሱት መካከል፡-

  1.  የተማሪዎች ቤተሰብ ተጽእኖ፣

  2.  በገጠር አብያተ ክርስትያናት ብቁ እና በቂ መምህራን አለመኖር፣

  3. በተለያየ ምክንያት መምህራን ለማስተማር ያላቸው ተነሳሽነት ዝቅተኛ መሆን፣

  4. የአብነት መምህራን ከከተማ ወደ ገጠር እየተመላለሱ ማስተማር፣

  5. የተማሪዎች የግንዛቤ ችግር እና ፍላጎት ማነስ እንዲሁም ርዕይ አለመኖር፣

  6.  የሰበካ ጉባኤ ለአብነት ትምህርት ትኩረት አለመስጠት፣

  7. ለሚያስተምሩ መምህራን ከሀገረ ስብከቱ ምንም አይነት ማበረታታት አለመኖር፣

  8. ለአብነት መምህራን በቂ ክፍያና ትኩረት አለመኖር 

  9. የአብነት መምህራን ከገጠር ወደ ከተማ መፍለስ የሚሉና ሌሎችም ምክንያቶች ተጠቅሷል፣

 

abh 2የአብነት መምህራኑ አክለው እነዚህን ችግሮች ለመቅረፍ የአብነት ትምህርት ባለድርሻ አካላት ማለትም ሀገረ ስብከቱ፣ወረዳው ቤተ ክህነት፣ ሰበካ ጉባኤ፣ማኅበረ ቅዱሳን፣ የአብነት መምህራንና ተማሪዎች፣ የተማሪ ወላጆች እንዲሁም መላ ህዝበ ክርስቲያን ይህንን ችግር ለዘለቄታው ለመፍታት መረባረብ እንደሚገባ የተነሳ ሲሆን ይህ ሳይሆን ቢቀር ግብ ችግሩ የከፋ ደረጃ እንደሚደርስ የአብነት መምህራኑ አስረድተዋል፡፡

በመጨረሻም እንደዚህ አይነት የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠና ተጠናክሮ ቀጥሎ ሌሎች የአብነት መምህራንም እንዲሳተፍ ማድረግ እንደሚገባና መቋረጥ እንደሌለበት የአብነት መምህራኑ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

ake 4

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ፓትሪያሪክ ዘኢትዮጵያ በሐዋሳ ደማቅ አቀባባል ተደረገላቸው

 የካቲት 12 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ያለው ታምራት ከሐዋሳ

ake 4
ጥር 29 ቀን 2006 ዓ.ም በእምነት ተቋማት ኀብረት በተዘጋጀው የሰላም ጉባኤ ላይ ለመሳተፍ ሐዋሳ ለተገኙት ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ፓትሪያሪክ ርዕሰ ሊቃለ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ እና ለሌሎች ሊቃነ ጳጳሳት በሐዋሳ ከተማ ምዕመናን ደማቅ አቀባበል ተደረገላቸው፡፡

ake 1ከፍተኛ ቁጥር ያለው የከተማው ነዋሪ በሞተር፣በመኪና እንዲሁም በእግር ከከተማ ውጪ በኦሮሚያ ክልል በቶጋ አከባቢ እስከ ሐዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ድረስ በማጀብ ለቅዱስ ፓትርያርኩ ደማቅ አቀባበል አድረገዋል፡፡ የአባቶችን ቡራኬ ለመቀበል በደብረ ምህረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ለረዥም ሰዓት ሲጠባበቁ የነበሩት ምዕመናን በዝማሬ፣በእልልታ ተቀብለዋል፡፡ ቅዱስ ፓትሪያሪኩና ብፁዓን አባቶች ልክ ወደ ሐዋሳ ከተማ ሲገቡ ያልተጠበቀ ዝናብ ጥላሏል፡፡ ይህ ሁኔታ በዝናብ እጦት ሲቸገሩ ለነበሩት ለከተማው ነዋሪዎች ልዩ ስሜትን ፈጥሯል፡፡የአባቶቹንም በረከት አድንቋል፡፡

የአቀባበል መርሐግብሩ በዓውደ ምሕረት ቀጥሎ በሲዳማ፣ጌዲኦ፣አማሮና ቡርጂ እንዲሁም የጉጂ ቦረናና ሊበን ሀገረ ስብከቶች ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ለቅዱስ ፓትሪያሪኩና ለብፁዓን አባቶች የእንኳን ደህና መጣችሁ መልዕክት አስተላልፈዋል፡፡በመቀጠልም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ምዕመናኑን ባርከው ወደ ሐዋሳ የመጡበትን ምክንያት ገልጸው በከተማዋ ለሦስት ቀናት እንደሚቆዩና እሁድ 2/06/2006 ዓ.ም ከምዕመናን ጋር ሰፊ መሐርግብር እንደሚኖራቸው ቃል ገብተዋል፡፡ በመጨረሻም የመዝጊያ ጸሎት ተደርጎ የዕለቱ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

እሑድ የካቲት 2/2006 ዓ.ም የአቀባበል መርሐግብሩ ቀጥሏል፡፡ በዕለቱ ሥርዓተ ቅዳሴው የተከናወነው በብፁዓትን ሊቃነ ጳጳሳት ሲሆን ሥርዓተ ቅዳሴውም ከተፈጸመ በኋላ የዓውደ ምሕረት መርሐ ግብሩ በደማቅ ሁኔታ ተጀምሯል፡፡ ብፁዕ አቡነ ኤልሳ የሰሜን ጎንደረ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የዕለቱን ትምህርተ ወንጌል አስተምረዋል፡፡ በመቀጠልም የቅዱስ ፓትሪያሪኩ የአንደኛ ዓመት በዓለ ሲመት አስመልክቶ በቅዱስ ገብርኤል ገዳም ካህናት ቅኔ መወድስ የቀረበ ሲሆን የገዳሙ አስተዳደርም ለብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ያዘጋጀውን ልዩ ልዩ ስጦታዎችን አበርክቷል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ፓትሪያሪክ ርዕሰ ሊቃለ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ በሐዋሳ ከተማ ከብፁዓን ሊቃ ጳጳሳት ጋር በመገኘታቸው መደሰታቸውንና የተለያዩ የእምነት ተቋማት ባዘጋጁት የሰላም ጉባኤ ላይ ለመሳተፍ በሐዋሳ በነበራቸው የሦስት ቀን ቀይታake 3 ስለ ሰላም አስፈላጊነት በሰፊው ውይይት መደረጉን ገልጸዋል፡፡”ከሁሉ በፊት ሰላም፣ፍቅርና አንድነት ያስፈልጋል፡፡ ሰላም ከሌለ ምንም ነገረ የለም ሰላም ካለ ግን ሁሉ ነገረ አለ፡፡ስለዚህ ሁላችንም ስለ ሰላም ማስተማር መጸለይ አለብን” ብለዋል፡፡
በመጨረሻም ቅዱሳ አባታችን ሕዝቡን ባርከው ከፊት ያሉትን ሱባኤና ጾም ፀሎት ሁላችንም በርትተን መፈጸም አለብን ብለው ስለተደረገላቸው መልካም አቀባበልና ስጦታ በእርሳቸውና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ስም አመስግነዋል፡፡

 

በግዮን ሆቴል ሊካሔድ የነበረው የአብነት መምህራን የምክክር ጉባኤ እንዳይካሔድ ተከለከለ

የካቲት 7 ቀን 2006 ዓ.ም.

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት በየሦስት ዓመቱ የሚካሔደው የአብነት መምህራን የምክክር ጉባኤ ከቅዱስ ፓትርያርኩ በተሰጠ መመሪያ መሠረት እንዳይካሔድ ተደርጓል፡፡

የጉባኤውን መከልከል አስመልክቶ መግለጫ የሰጡት የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ እና የማኅበሩ ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ምክትል ዳይሬክተር ወ/ሮ ዓለምፀሐይ መሠረት በጋራ እንደገለጹት “ማኅበሩ በየሦስት ዓመቱ ይህንን ጉባኤ ያካሒዳል፤ ይህ ለሦስተኛ ጊዜ ነው፡፡ ዓላማውም የአብነት መምህራንን የቀለብ፣ የአልባሳት፣ የፍልሰት ችግሮችን ለመቅረፍ እንዲሁም መምህራኑ በቂ ደመወዝ ስለማይከፈላቸው ድጋፍ ለማድረግና የአቅም ማጐልበቻ ውይይትና ሥልጠና ለማድረግ  የታቀደ ነበር፡፡

ሆኖም ግን ደብዳቤው ደርሶን የጉባኤውን መታገድ ምክንያት ለጊዜው ባንረዳም በቅዱስነታቸው መመሪያ መሠረት ጉባኤው መካሔድ እንደሌለበት ብፁዕ ሥራ አስኪያጁ ደብዳቤ እንደደረሳቸውና መቋረጥ እንዳለበት በቃል ነግረውናል” በማለት ገልጸው የዘንድሮው ጉባኤ ካለፉት ጉባኤያት የሚለየው በምንድን ነው? ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ ሲመልሱ:-

 

“የዘንድሮው ጉባኤ ባለፉት ጉባኤያት ከተነሡት አጀንዳዎች ልዩነት የለውም፡፡ ቀጣይና የሞኒተሪንግ አካል ነው፡፡ ትልልቅ ግንባታዎች የአብነት ት/ቤቶች ይሠራሉ፡፡ በእነዚህ ሥራዎች ላይ ጥያቄ አልቀረበም፡፡ በግዮን ሆቴልም ሆነ በሌሎቹ ማእከላዊ ቦታዎች ምክክር ስናደርግ ቆይተናል፡፡ ስለዚህ አሁን የተከለከለውን ጉባኤ እንደገና ለማካሔድ ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጋርና ከብፁዓን አባቶች ጋር የጀመርነውን ውይይት እንቀጥላለን፡፡ ተመካክረን የምንሠራበትን ሁኔታ እናመቻቻለን፤ ለዚህም ተስፋ አለን” በማለት ገለጻቸውን አጠቃለዋል፡፡

 

addis ab 03

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመዋቅር፣ አደረጃጀትና አሠራር ረቂቅ መመሪያ ርክክብ ተካሔደ

የካቲት 6 ቀን 2006 ዓ.ም.

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

addis ab 03ዐሥራ ሦስት የመመሪያ ረቂቅ ሰነዶችን ከ12/11/2005 ዓ.ም ጀምሮ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሲያጠናና ሲያወያይ የነበረው 18 አባላት ያሉት አጥኚ ኮሚቴ ዛሬ የካቲት 6 ቀን 2006 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመሰብሰቢያ አዳራሽ በተደረገው የመረካከቢያ መርሐ ግብር ረቂቅ ሰነዶችን ለብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ረዳትና የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አስረከቡ፡፡

በርክክቡ ወቅት ንግግር ያደረጉት የአጥኚው ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ታደሰ አሠፋ እንደገለጹት “ቡድኑ የልጅነት ድርሻውን ይወጣ ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት ስትሰጠው ወደ ዋና ጥናቱ ከመግባቱ በፊት ሥራው የተቃና ይሆን ዘንድ በአባቶች ጸሎት እንዲታሰብ መብዓ አሰባስቦ መላኩ ለጥናት ቡድኑ ብርታት እንዲሁም ሥራ መጠናቀቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አድርጐለታል፡፡ ስለዚህም የእግዚአብሔር ቸርነት የቅዱሳን ጸሎት አልተለየንም” ብለዋል፡፡

በመቀጠልም “ጥናቱን እያጠናን ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ አጥቢያ ምእመናን ድረስ በማወያየት 96 በመቶ ተቀባይነት ያገኘ ሲሆን በውይይቱ ወቅት እንዲካተቱ የተነሡ ነጥቦች ተካተውና ተሻሽለው ለዚህ ቀን ደርሰናል፡፡ ጥናቶቹም፡-

  1. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የመዋቅር የአደረጃጀት ጥናትና መመሪያ 119 አንቀጽ

  2. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአብያተ ክርስቲያናት የደረጃ መስፈርት መመሪያ 23 ገጽ

  3. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአገልግሎት መደቦች የሥራ ዝርዝር መመሪያ 120 ገጽ

  4. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሰው ኃይል ትመናና የተፈላጊ ችሎታ መስፈርት መመሪያ 53 ገጽ

  5. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደመወዝ ስኬል ጥናት 99 ገጽ

  6. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የአገልግሎጋዮች ማስተዳደሪያ ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 125 ገጽ

  7. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥልጠናና የሰው ሃብት ልማት ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 30 ገጽ

  8. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የፋይናንስ ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 107 አንቀጽ

  9. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የግዢ፣ ሽያጭና ንብረት አስተዳደር መመሪያ 26 ገጽ

  10. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የልማት ሥራዎች ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 16 ገጽ

  11. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የዕቅድና ሪፖርት ዝግጅት፣ ክትትልና ግምገማ መመሪያ 31 ገጽ

  12. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የኦዲትና ኢንስፔክሽን ፖሊሲና ዝርዝር የአፈጻጸም መመሪያ 57 ገጽ

  13. በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሥልጠና ማእከል፣ ወላጅ አልባ ሕፃናትና የአረጋውያን መርጃ ማእከል ፕሮጀክት ጥናት ሰነድ /የተሠጠ/

ሲሆኑ የዚህ ጥናት ትግበራ ስልትና የእያንዳንዱ መመሪያና ፖሊሲ ማስፈጸሚያ ብዛት ያላቸው ቅጾች ለትግበራ ስለሚያስፈልጉ ወደፊት ተጠናቀው ይቅርባሉ”addis ab 02 በማለት ገልጸው ሰብሳቢው የአጥኚው ቡድን አባላት ለብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጥናት ሰነዱን እንዲያስረክቡ ካደረጉ በኋላ “በዚህ ጥናቱን በሚመለከት ማብራሪያ ለሚጠይቀን አካል ሁሉ ምላሽ ለመስጠትና ለመወያየት ዝግጁ ነን” በማለት ገልጸዋል፡፡

ከአጥኚ ኮሚቴው በመቀጠል ንግግር ያደረጉት የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ አእላፍ በላይ መኰንን “እንደገለጹት ለቤተ ክርስቲያን ብላችሁ ጊዜያችሁን ገንዘባችሁን ሁሉን ነገር አውጥታችሁ የሠራችሁትን እግዚአብሔር ዋጋችሁን ይክፈላችሁ፡፡

እግዚአብሔር ለሥራ ጊዜ አለው፡፡ ሁሉም ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅም ነው፡፡ ቅዱስ አባታችንም ጥናቱ ለምን ቆየ? ከምን ደረሰ? እያሉ እየጠየቁ ነው፡፡ የተቃውሞ ጥያቄ የሚያነሱትም ነፃ አስተሳሰብ ነውና ሊመሰገኑ ይገባል” ብለዋል፡፡

ጥናቱን የተረኩበት ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ባደረጉት ንግግር “መነሻ የሚሆን ነገር እንድናቀርብ በመጠየቃችን እናንተም ይህን በመሥራታችሁ እግዚአብሔር በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስ ያድላችሁ፡፡

በእግዚአብሔር የምንጠየቀው የሚጠብቅብንን ሳንሠራ ስንቀር ነው፤ የታዘዛችሁትን አዘጋጅታችሁ አቀርባችኋል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ተግባራዊ ያደርገዋል፡፡ ሆን ብሎ ለጥፋት የሚሰለፍ የለም አስተሳሰባችን በመለያየቱ እንጂ፡፡ ከዚህ በተመሳሳይ ቃለ ዓዋዲው መጀመሪያ ሲረቀቅ ብዙ ተቃውሞ ቀርቦበት ነበር፤ ግን ተግባራዊ ሆነ፡፡ ከዚህ በኋላ የሚያስፈልገው ሁላችንም ወደ አንድ መጥተን ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅመውን ማድረግ ነው” በማለት አባታዊ ምክር ሰጠተዋል፡፡ በመጨረሻም በርክክቡ መርሐ ግብር ላይ ለተገኙት ተሳታፊዎች የደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ የምሳ ግብዣ አድርገዋል፡፡

01mkBahirDar

መንፈሳዊ ጉባኤ በባሕር ዳር ከተማ

01mkBahirDar

ጾመ ሰብአ ነነዌ

 የካቲት 3 ቀን 2006 ዓ.ም.

ርዕሰ ደብር ብርሃኑ አካል

ጾመ ነነዌ ከአዋጅ አጽዋማት አንዱ ሲሆን የምትጾመውም ለሦስት ቀናት ነው፡፡ ጾሙ የሚጀመርበት ዕለትም ልክ እንደ ዐቢይ ጾም ሰኞን አይለቅም፡፡ ጾሙ የሚጀመርበት ቀን ደግሞ ሲወርድ ወይም ወደ ኋላ ሲመጣ እስከ ጥር 17 ቀን ድረስ ነው፡፡ ሲወጣ ወይም ወደፊት ሲገፉ ደግሞ እስከ የካቲት 21 ድረስ ነው፡፡ በእነዚህ 35 ቀናት/ዕለታት/ ስትመላለስ ትኖራለች፡፡ ከተጠቀሱት ዕለታት አይወርድም አይወጣም ማለት ነው፡፡

የሦስት ቀኑን ጾም የጾሙት በነነዌ ይኖሩ የነበሩ ሕዝቦች ሲሆኑ ከተማዋ በጤግሮስ ወንዝ ዳርቻ የምትገኝ መሥራቿም ናሞሩድ ነው፡፡ ዘፍ.10፥11-12 ጥንታዊቷ የነነዌ ከተማ ለአሦር መነሻ የሆነ ከተማ እጅግ ሰፊና ያማረ ፤ የከተማው ቅጥር ርዝመት አሥራ ሁለት ኪሎ ሜትር ነበር፡፡ ሰናክሬም ብዙ ሕንፃዎችንም ሠርቶበት ነበር፡፡ /ዮናስ. 4፥11/

የነነዌ ሰዎች ኃጢአታቸው ቅድመ እግዚአብሔር ደርሶ በኃጢአታቸው ምክንያት ሊጠፉ ሲሉ ቸርነትና ምህረቱ የማያልቅበት እግዚአብሔር ነቢዩ ዮናስ መክሮ ዘክሮ እንዲመልሳቸውና ንስሐ እንዲገቡ ወደ ነነዌ ሕዝብ ሂድ አለው፡፡ ሉቃ.11፥30 ዮናስ የስሙ ትርጉም “ርግብ” ማለት ነው፡፡ በዳግማዊ ኢዮርብዓም ዘመነ መንግሥት የነበረ ነቢይ ነው፡፡ ኢዮርብዓም ሶርያውያንን አባሮ የእስራኤልን ድንበር እንዲመልስ ትንቢትን ተናግሯል፡፡ ይህ ነቢይ መኖሪያው በገሊላ በጋትሔፌር ድንበር ከተማ ነበረ፡፡ አባቱም አማቴ ይባላል ፡፡ 2ነገ14፥25፣ ት.ዮና1፥1

እግዚአብሔርም “ሄደህ በነነዌ ላይ ስበክ” ባለው ጊዜ “አልሄድም” አለ፡፡ “አንተ መሀሪ ነህ ልትጠፉ ነው ብዬ ተናግሬ ስትምራቸው ሐሰተኛ ነቢይ እባላለሁ፡፡” ብሎ ላለመታዘዝ እስራኤልን ለቆ በመርከብ ወደ ተርሴስ ሸሸ፡፡ እግዚአብሔር ግን ታላቅ ነፋስን አስነሥቶ መርከቧበማዕበል እንድትመታ አደረገ፡፡ ከዮናስ ጋር በመርከቧ ተሳፍረው የነበሩት ነጋድያንም ያላቸውን ሀብት ወደ ባህሩ መጣል ሲጀምሩ ነቢዩ ዮናስ “በእኔ ምክንያት የመጣ ስለሆነ ንብረታችሁን ሳይሆን እኔን ወደ ባህር ጣሉኝ” ብሎ ተማጸናቸው፡፡ እነሱም “የሰው ደም በእጃችን እንይሆንብን አይሆንም” አሉት፡፡ ዕጣም ቢጣጣሉ ዮናስ ላይ ወጣ፡፡ ነጋድያኑ ዮናስን ወደ ባሕሩ ጣሉት፡፡ ወዲያው የእግዚአብሔር የማዳን መልእክት ዮናስ እንዲያደርስ የታዘዘ ታላቅ ዓሣ አንበሪ ዮናስን በአፉ ተቀብሎ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት አሳድሮ ነነዌ አደረሰው፡፡ ዮናስም ከእግዚአብሔር መኮብለል አለመቻሉን ሲረዳና ነነዌ መሬት ላይ መድረሱ ሲነገረው ለነነዌ ሰዎች “ንስሐ ግቡ” ብሎ መስበክ ጀመረ ዮናስ 1እና2 ፡፡ የነነዌ ሰዎች ንስሐ በገቡ ጊዜ እግዚአብሔር ማራቸው /ዮና.3/

ነቢዩ ዮናስም ውሸታም ላለመባል መኮብለሉ ስህተት መሆኑን እግዚአብሔር ቅልን ምሳሌ በማድረግ አስረዳው፡፡ /ዮና.4/ ነቢየ ሐሰት እንዳይባልም እሳቱ እንደ ደመና ሆኖ ታይቶአል፡፡ የታላላቁ ዛፍ ቅጠል እስኪጠወልግ ድረስ አድርቆ ለሕዝቡ አሳይቷቸዋል፡፡ንስሐቸው በከንቱ እንዳልቀረ አስረድቷቸዋል፡፡ በስንክሳር ታኅሣሥ 5 እንደሚነግረን ፤ወበልዓ አሐደ ኀምለ ይላል ንስሐ ያልገቡ አንድ አገር አጥፍቶአል፡፡ ነቢዩ ኤልያስ ያስነሣው የስራጵታ መበለት ሕፃን ዮናስ እንደሆነ /1ነገሥ.17፥19/ ሲያስረዳን ፤ክርስቶስ የዮናስን ከዓሣ ሆድ መውጣት የራሱ ትንሣኤ ምሳሌ አድርጎታል፡፡ /ማቴ.12፥19-42/ ሉቃ.11፥30-32/፡፡

ጾመ ነነዌ የሦስት ቀን ሱባኤ ናት፡፡ ይሄውም አስቴር አስቀድማ ሦስት ቀን ጾማ ጸልያ በእሥራኤል ላይ የመጣውን መቅሠፍት እንዲመለስ አድርጋለች ኢሳ.4፥15-16፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ከበዓል ስትመለስ ልጇ ሕፃኑ ኢየሱስ መንገድ ላይ ጠፍቶአት ከሦስት ቀን ፍለጋ በኋላ በቤተ መቅደስ እንዳገኘችው ሁሉ ሉቃ.2፥46 ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ለሄሮድስ በሰጠው መልስ ሦስት ቀን የሱባኤ ፍጻሜ መሆኑን ገልጿል ሉቃ.13፥32፡፡

የነነዌ ሰዎች የተነሳህየን ምሳሌ ናቸው ይህም ማለት ሰው ጥፋቱን አምኖ ንስሐ ከገባ እግዚአብሔር ይቅር ማለቱን አይተውም፡፡ ለዚህም ነው ዮናስን አንተ ላልደከምክበት እና በአንድ ቀን በቅሎ ላደገ ቅል ስታዝን እነሆ በታላቂቱ ነነዌ ከተማ ያሉ ከአንድ መቶ ሃያ ሺህ በላይ ሕዝቦችና እንስሳቱ የእጄ ፍጥረቶች ስለሆኑ ያሳዝኑኛል ያለው፡፡

ዛሬ ዓለማችን በኃጢአት ማዕበል እየተናወጠች ባለበት ወቅት እኛም ብንመለስ እና ንስሐ በንገባ ቸሩ ፈጣሪያችን ይቅርታና ምሕረት የባሕርይ ገንዘቡ ስለሆነ “ወደኔ ተመለሱ እኔም ይቅር እላችኋለሁ ”ብሎ አስተምሯል፡፡ ቀደምት አባቶቻችን ይህን እና ሌሎች አጽዋማትን እንድንጾም የወሰኑልን ያለ ምክንያት አይደለም፡፡ ለምሳሌ ጾመ ነነዌ የሚከተሉትን ምሳለዎች እናገኝባታለን ታሪኩን በማስታወስ የእግዚአብሔርን ቸርነትና መሀሪነት የምናስታውስበት ነው፡፡ ይኸውም ፍጥረቶቹ በበደልን ጊዜ ፈጽሞ ከማጥፋት ይልቅ ምክንያት ፈልጎ እንድንድን ያደርጋል፡፡ ዮናስ ፈቃደኛ ባይሆን እንኳ በተለየ ጥበቡ እንዲሄድ አድርጎታል፡፡ ሌላ ነቢይ አጥቶም አይደለም እሱንም ጭምር ሊያስተምረው ስለፈለገ እንጂ፡፡

በዮናስ አማካይነት የተደረጉ ተአምራትን መገንዘብና ካለመታዘዝ የሚመጣ ቅጣት ቀላል አለመሆኑን ተገንዝበን ለእግዚአብሔርም ሆነ ለሃይማኖት አባቶች አና ለወላጆች መታዘዝን እንማርበታለን፡፡ እንደ ነነዌ ሰዎች እኛም ጾመን ጸልየን ከኃጢአታችን እንድንነፃ ነው፡፡ ብንጾም እራሳችን፣ ሃገራችንን፣ እጽዋቱንና እንስሳቱም ሳይቀር በኛ በደል ምክንያት በድርቅ በቸነፈር እንዳይጠፋ እግዚአብሔር ይቅር ስለሚል ነው፡፡

ጾመን እንድናበረክት ይርዳን

ይቆየን

 

ሕይወት ተገለጠ አይተንማል

 የካቲት 3 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ታደለ ፈንታው

ስለሕይወት ቃል ከመጀመሪያ የነበረውንና የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን የተመለከትነውም እጆቻችንም የዳሰሱትን እናወራለን፡፡ ሕይወትም ተገለጠ አይተንማል፡፡እንመሰክራለንም፡፡/1ኛ ዮሐ 1፡1/

ቅዱስ ዮሐንስ በቀዳማይ መልእክቱ ለዓለም የሚያስተዋውቀው ሕይወት ዓለም የማያውቀው አስቀድሞ ከእግዚአብሔር አብ ዘንድ የነበረ በኋለኛው ዘመን ሰው ይሆን ዘንድ ሥጋን ተዋሕዶ በምድር ላይ ይመላለስ ዘንድ የወደደ፣ ከአብ ዘንድ የነበረውን፣ ለእኛም የተገለጠውን ሕይወት ነው፡፡ አስቀድሞ በወንጌሉ ይህንን ሕይወት ‹‹ በመጀመሪያ ቃል ነበረ፤ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ፤ ሁሉ በእርሱ ሆነ ከሆነው አንዳች ስንኳ ያለእርሱ አልሆነም/ዮሐ 1፡1/ በማለት የገለጠው ነው፡፡

ወንጌላዊው ከመጀመሪያ የነበረውን ሲል እያስተማረን ያለው ቀዳማዊ ቃል ዘመን የማይቆጠርለት መሆኑንና በየዘመናቱ የሰራው ታላቅ ሥራ መገለጡን የሚያመለክት ነው፡፡ እርሱ ከባህርይ አባቱ ከእግዚአብሔር አብ ጋር ህልው ሆኖ የሚኖር ነው፡፡ አይቀዳደሙም፣ ወደኋላ አይሆኑም፡፡ አብን መስሎ አብን አክሎ የተወለደ ነው፡፡ በኅላዌ ፣በአገዛዝ፣ በመለኮት፣ በአገዛዝ፣ በመለኮት፣ ከባሕርይ አባቱ ጋር የተካከለ ነው፡፡

እርሱ ዘላለማዊ ቃል ነው የሚለው በመጀመሪያ ቃል ነበረ በማለት በወንጌሉአስቀድሞ ገልጦታል፡፡ነገር ገን ዓይኖቻችን የተመለከቱት የሚለው ቃል የሚያመለክተው የጌታን መገለጥ ነው፡፡ እጆቻችን የዳሰሱትንም የሚለው ቃል ተመሳሳይ እሳቤን ይይዛል፡፡ አካላዊ ቃል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገልጦ ስጋን ተዋሕዶ ባይታይ ኑሮ የሰው ልጆች ባልተመለከቱት አብረውት ባልበሉ ባልጠጡም ነበር፡፡ ስለጌታ የሚኖረን እውቀት፣ ስለሃይማኖታችን የሚኖረንም መረዳት በማየት ላይ የሚቆም አይደለም፡፡ የሚመሰከርም ነው እንጂ፡፡ ምስክርነት የሚለው ቃል ሰማእትነትን የሚያመለክት ነው፡፡ አይተንማል ስለዚህ በስምህ ልንሰደድ ፣ልንገረፍ፣ ወደ ወኅኒ ልንጋዝ፣ ልንሰደድ አስፈላጊም ሆኖ ሲገኝ ልንሞት ተዘጋጅተናል ማለት ነው፡፡ ሰማእታት በእውነት ምስክርነታቸው የተቀበሉት መከራ ብዙ ነው፡፡ ምስክርነታቸውም ለሰሙትና ላዩት ቃል ነው፡፡ ምስክርነት በቃል ፣ በኑሮ/በሕይወት/ በሥራ፣ የሚገለጥ ነው፡፡ የክርስቲያኖች ምስክርነት የሚሰሙአቸውን ወጎኖች ያስቆጣቸዋል፤ ይህንን ሁኔታ ተከትሎ የእውነት ምስክር የሚሆን ክርስቲያን ፍጻሜ ሰማእትነት ነው፡፤ ሰዎች ስለእረሱ ይመሰክሩ ዘንድ እግዚአብሄር ፈቃደ ነው፡፡ ስለዚህም ነው መድኃኒታችን ‹‹ በሰው ፊት የሚመሰክርልኝን በሰማይ አባቴና በመላእክቱ ፊት እመሰክርለታለሁ በሰው ሁሉ ፊት የሚክደኝን በሰማይ አባቴና በመላእክቱ ፊት እክደዋለሁ በማለት የተናገረው፡፡››

ከጌታ መገለጥ አስቀድሞ ሰው ልጅ ይኖር የነበረው ከእግዚአብሔር ቁጣ በታች ሆኖ በመርገም ነበር፡፡ እግዚአብሔርን ተግተው ይፈልጉ ያገለግሉ የነበሩ ነቢያት ይህንን ሁኔታ ‹‹ጽድቃችን እንደመርገም ጨርቅ ነው/ኢሳ 64፡6/ በማለት የተናገሩለት ነው፡፡ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር አሕዛብን እርሱን ተመራምረው የሚረዱበትን መንገድ ሳያመለክት እንዲሁ አልተዋቸውም ነበር፡፡ ነገር ግን በዚህየፈጣሪን ሀልወቆት በሚገልተው መንገድ ተጉዘው ወደ እውነተኛው አምላክ መድረስ ሳይቻላቸው ቀርቷል፡፡ እግዚአብሄር ሀልዎቱ የተገለጠበትን ድንቅ ሥራውን የሚመሰክርበትን ዓለም በኃጢአት አቆሸሹት፡፡ ራሳቸውንም በደለኛ አደረጉ፡፡ የእግዚአብሔርም ቁጣ የሚገባቸው ሆኑ፡፡ የአሕዛብም ጣዖት ማምለክ እግዚአብሄርን አስቆጣው፡፡ ምክንያቱም ከፈጣቲ ይልቅ ፍጡርን ፍጡርንም የሚያስተውን አጋንንትን ለማምለክ ፈቅደዋልና፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ጥቁር የኃጢአት መልክ እንደሚከተለው ይገልጠዋል፡- ‹‹እግዚአብሔር ስለገለጠላቸው ስለ እግዚአብሄር ሊታወቅ የሚቻለው በእነርሱ ዘንድ ግልጥ ነውና፡፡ የማይታየው ባህርይ እርሱም የዘላለም ኃይሉ ደግሞም አምላክነቱ ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ ከተሠሩት ታውቆ ግልጥ ሆኖ ይታያልና፤ ስለዚህም እግዚአብሔርነቱን እያወቁ እንደ እግዚአብሔርነቱ ባላከበሩት መጠን ስላላመሰገኑትም የሚያመካኙት አጡ፤ ነገር ግን በአሳባቸው ከንቱዎች ሆኑ፤ የማያሥተውለውም ልባቸው ጨለመ፡፡ ጥበበቦች ነን ሲሉ ደንቆሮዎች ሆኑ፤የማይጠፋውንም የእግዚአብሔር ክብር በሚጠፋ ሰውና በወፎች አራት እግር ባላቸው በሚንቀሳቀሱትም መልክ ለወጡ፡፡/ሮሜ 1፡18-27/

አይሁድ የነበሩበት ሁኔታ ከአሕዛብ እምብዛም የተሻለ አልነበረም፡፡ አይሁድ ከአሕዛብ የሚለዩበት ምቹ ሁኔታዎች ነበሩአቸው፡፡ በብሉይ ዘምን በተለያየ ጌዜ የተደረገው መገለጥ፣ ሕጉ፣ ነቢያት ቀዱሳት መጻሕፍት ነበሩአቸው፡፡ እነዚህ ሁሉ ነገሮች በደላቸውን ከማብዛት ውጪ አንዳች የጠቀሙአቸው ነገር አልነበረም፡፡ አሕዛብ ጣዖት በማምለክ ወጥመድ ሲያዙ ሕጉ ግን ሊመጣ ስላው ክርስቶስ ይናገር እንደነበረ አላስተዋሉም፡፡ አሕዛብ ጣዖት በማምለክ ወጥመድ ሲያዙ አይሁድ የሕጉን ነጠላ ትርጓሜ ፊደልን በማምለክ ተያዙ፡፡ ሕጉ ግን ይመጣ ስላለው ክርስቶስ ይናገር እንደነበረ አላስተዋሉም እንደመሰላቸው ተረጎሙት እንጂ፡፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩ ቅዱሳን ሕጉን ባለና በሌለ ጉልበታቸው በመፈጸም ወደ ቅድስናና ፍጹምነት ለመድረስ ይጣጣሩ ነበር፡፡ ይህ ሰውኛ ጥረት በሕግም እንዲገኝ ይፈለግ የነበረው ጽድቅ ሰዎች ስለራሳቸው የነበረቸው አመለካከት እንዲዛባ፣ ራሳቸውን ከፍ አድርገው እንዲመለከቱ‹‹ ጌታ ሆይ እኔን እንደቀራጩ ስላላደረግኸኝ አመሰግንሃለሁ›› እንዲሉ አድርጓቸዋል፡፡

በአንጻሩ በሕጉ ጥላ ሥር የነበሩ ጉድለታቸውን የተገነዘቡ ወገኖች መራራ የሆነ የኃዘን ስሜት ተሰምቶአቸው ‹‹ እኔ ምንኛ ጎስቋላ ሰው ነኝ፣ ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል? በማለት ጩኸታቸውን አሰምተዋል፡፡ /ሮሜ 7፡24/ አሁን እየጠናገርነው ላለው ነገር ማሳያ ምሁረ ኦረት ከነበረው ለአባቶቹ ወግና ሥርዓት ይጠነቀቅ ከነበረው የቀድሞው ሳውል የኋለኛው ብርሃና ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ የበለጠ ምስክር ሊሆን የሚቻለው ወገን የለም፡፡ ኢክርስቲያናዊ ከሆነው ወግና ልማድ ወጥቶ ክርስቲያናዊ በሆነው መስመር ለመጓዝ ቅዱስ ጳውሎስ የራሱን የሕይወት ተሞክሮ ይነግረናል፡፡ በቅዱስ ጳውሎስ የተደረገ ለውጥ ሥሩን ዘልቆ መሰረቱን ነክቶ የተደረገ ክርስቲያናዊ ለውጥ ነበር፡፡ ካለፈው ወጉና ልማዱ ፈጽሞ የሌው ነው አዲስ የሆነ የሕይወት ፍልስፍና የኑሮ መስመርም እንዲከተል ያደረገው ነው፡፡ ሕይወትና ሞት በማነጻጸር ሊገለጥ የሚችል ለውጥ ነው፡፡ ወደ ክርስቶስ ሞት ይገባ ዘንድ ሞቱንም በሚመስል ሞት ይተባበር ዘንድ እንዳደረገ ክርስቲያኖችም አስቀድመው ከሚገዙለት ዓለም ወጥተው ለዓለም ሊሞቱ ይገባቸዋል፡፡ ሞቱን በሚመስል ሞት ይተባበሩ ዘንድ ይህ ነገር አስፈላጊ ነው፡፡ ከክርስቶስ ገር መሞትም መቀበርም መነሳትም የሚቻለው በዚህ መንገድ ነው፡፡/ሮሜ 6፡2-8፣ ገላ 2፡20፣ቆላ 3፡3/ ከክርስቶስ ጋር የሚነሳው አዲሱ ሰው የሚወለደው በዚህ መንገድ ነው፡፡ እርሱም ክርስቲያን የሚለውን ስም የተሸከመና ከሥምም በላይ የሆነውን ስም ገንዘብ የሚያደርግ ነው ፡፡ የጌታ መገለጥ ዓላማው ይህ ሁኔታ ይፈጸም ዘንደ ነው፡፡

በክርስቶስ መገለጥ አዲስ ስምን ገንዘብ ያደረገው መንፈሳዊው ሰው የራሱ የሆነ ግላዊና ዓለማዊ ጠባያትን አስወግዶ ባህርይውን ከክርስቶስ ባህርይ ጋር ማስማማት የሚያስችለውን የመንፈስ ማሰሪያ ገንዘብ ለማድረግ የሚታገል መላ ዘመኑን በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ የሚመላለስ የእግዚአብሔርንም እውነጠኛ ፍቅሩ በልቡናውቋጥሮ የሚመላለስ ነው፡፡

 

ክርስቲያናዊ ሕይወት ከክርስቶስ ጋር መቀበር ነውና ከዓለምና ከኃጢአት መለየትን ይጠይቃል፡፡/ኤፌ 2፡13/ ይህ ከዓለምና ከኃጢአት መለየት በክርስቶስ የመስቀል ላይ የማዳን ሥራ የተገለጠ ነው፡፡ ‹‹አይዞአችሁ እኔ ዓለሙን አሸንፌዋለሁ››በሚለው እውነተኛ የአዋጅ ቃልም የታጀበ ነው፡፡ አማናዊ የሆነ የአዋጅ ቃልም ነው፡፡ በነፍሳችን መልሕቅ ልዩ ሥፍራ ያለው ነው፡፡ ክርስቲያኖች ክርስቶስን ይለብሱታል፡፡ በመድረክ ላይ የሚጫወት ተዋናይ መድረኩን እንዲያደምቅለት በመድረክ ላይ ሳለ የሚለብሰው ከመድረክ ሲለይ የሚያውቀው የትወና ልብስ ዓይነት አይደለም፡፡ በመሰዊያው ፊት ለፊት ክርስቶስን ወክሎ የክርስቶስ ወኪል እንደሆነው ካህን ነው እንጂ፡፡ ካህኑ ክርስቶስን ወክሎ እንደሚናገር ክርስቶስን የለበሰ ክርስቲያንም በእርሱ የክርስቶስ ሕይወት ይታያል፡፡ በመውጣቱ፣ በመግባቱ፣ በኑሮው፣ በድካሙ የሚታየው መልክ ሕያው የሆነ የክርስቶስ መልክ እንጂ አስቀያሚ የሀኖነ ዓለማዊ ሰው መልክ አይደለም፡፡

በዚህ ሁኔታ ክርስቲያናዊ ሕይወትን ስንመለከተው ተራ የሆነው የዕለት ዕለት የዚህ ዓለም ኑረሮአችን አላፊ ጠፊ የማይጠቀም ሆኖ እንመለከተዋለን፡፡ በዚህ ዓለም የምናደርገው ስጋዊ ሩጫም አንድ ቀን በሞት ፍጻሜውን እንደሚያገኝ እንረዳለን፡፡ ቅዱሳን የዚህ ዓለም ኑሮ ቀናት እየገፉ በሄዱ ቁጥር የማይጠቅም እንደነበረ ተገንዝበዋል፡፡ ይህንም ሁኔታ ለማሰወገድ ጠንካራ ጦርነት ላይ ነበሩ ከዓይን አምሮትን ከሥጋ ፍላጎት ጋር ተዋግተዋል፡፡ ታግለውም አሸንፈዋል፡፡ ይህን ዓለም ተዋግተው ወደ ውጭ በገፉት መጠን በልብ ውስጥ ወዳለው ወደ ተሰወረው የልብ ሰው ይመለከቱ ዘንድ እግዚአብሔር ረድቶአቸዋል፡፡ የቅዱሳን ሕይወትና ሥነ ምግባር የተቀረጸው በልባቸው ላይ በነገሰው በክርስቶስ አማካኝነት ነው፡፡

ከቅዱሳን አንዱ እንዲህ ይላል፡- እግዚአብሄርን በሕይዎታችን ሲሰራ እንመልከተው፡፡ ለሥራው መልስ በመስጠት ምስክር እንሁን፡፡ ክርስቲያናዊ ሃይማኖትንና ምግባርን ይዘን እንገኝ፡፡ የክርስቶስን መልክ ለብሰን ስለእርሱም ዕለት ዕለት የምንሞት ብንሆን በነፍሳችን ተጠቃሚዎች ነን፡፡ በማየትና በማመን መካከል የገዘፈ ልዩነት አለ፡፡ በተግባር የምንኖረው ሕይወት ሰዎች ካልኖሩበት ትርጉሙን ላይረዱት ይችላሉ፡፡ ብዙ ምስጢራትን የምንገነዘባቸው በእምነት ሕይወት በማደግ እንጂበቃላት የመይገለጡ፣ ከቃላትም የመግለጥ አቅም በላይ የሆኑ ጉዳዮች አሉ፡፡ ቃላት የማያውቁትን ነገር ማስረዳት አይቻላቸውምና፡፡ ወደ እርሱ መቅረብ ማንም ወገን የማይቻለው እውነተኛ ብርሃን ዘመዶቹ ሊያደርገን በወደደ ጊዜ በሥጋ ተገለጠ፡፡ ይህም መልካም በመሆኑ ምክንያት እንጂ በጽድቅ ሥራችን የተነሣ አይደለም፡፡ ይህን ሁኔታ አውቀን ከፊታችን ያለውን ሩጫ በእምነት መሮጥ ይቻለን ዘንድ አምላካችን ይርዳን፡፡

 

የሰናፍጭ ቅንጣትማቴ 13÷31

 ጥር 30 ቀን 2006 ዓ.ም.

 

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መላክ
በምዕ/ጎጃም ሀገረ ስብከት
የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

 

 

ታላቅነትን በታናሽነት ሰውራ የያዘች እንከን የለሽ፤ዙሪያዋን ቢመለከቷት ነቅ የማይገኝባት አስደናቂ ፍጥረት ናት፡፡ የሰናፍጭ ቅንጣት፡፡ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስወንጌልን በምሳሌ ካስተማረባቸው መንገዶች አንዱ ሰናፍጭ ነው፡፡ ስትዘራ ታናሽነቷ ስትበቅል ግን ታላቅነቷ የገዘፈ ምሥጢር ያለው በመሆኑ ለዚህ ተመርጣለች በመጽሐፍ እንደተባለ ሰናፍጭ ስትዘራ እጅግ ታናሽናት ስትበቅል ግን ባለብዙ ቅርንጫፍ እስከመሆን ደርሳ ታላቅ ትሆናለች ከታላቅነቷ የተነሳ እጅግ ብዙ አእዋፍ መጥተው መጠጊያ እንደሚያደርጓትም አብሮ ተገልጿል አሁን ታናሽነቷን በታላቅነት መሰወር ችላለችና ብዙዎችን ልታስገርም ትችላለች፡፡

ይህ ምሳሌ ታላቅነትን በታናሽነት ሰውራ ይዛ የኖረችውን የክርስቶስ ቤተ ክርሰቲያን ነው እንጅ ሌላ ምንን ያመለክታል? የሰናፍጭ ቅንጣት ብሎ የጠራት አካሉ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ ምክንያቱም እንደ ሰናፍጭ ሁሉ ሲዘራት ትንሽ ነበረች፡፡ በመቶ ሃያ ቤተሰብ ብቻ የተዘራች ዘር ናት፡፡የእግዚአብሔርን ምሥጢር ልብ አድርጉ ኦሪትን ሲመሰርት እንዲህ ነበርን? በሙሴ ምክንያት በስድስት መቶ ሺህ ህዝብ መካከል የሰራት አይደለምን? ወንጌልን ግን እንዲህ አይደለም ከመቶ ሃያ በማይበልጡ ሰዎች መካከል ሰራት እንጅ ፡፡ወደሕይወት የሚወስደው መንገድ የጥቂቶች ብቻ መሆኑን ሲያሳየን ይህን አደረገ፡፡

ሰናፍጭ ካደገች በኋላ ለብዙዎች መጠጊያ እስኪሆን ድረስ ብዙ ቅርንጫፍ እንድታወጣ ቤተ ክርስቲያንም የዓለም መጠጊያ የሰው ልጆች መጠለያ ናት፡፡ ኦሪት በብዙዎች መካከል የተሰበከች ብትሆንም ቅሉ ቅርንጫፏ ከቤተ እስራኤል ወጥቶ ለሞዓብና ለአሞን ስንኳን መጠጊያ ሊሆን አልቻለም፡፡ ቤተክርስቲያን ግን ቅርንጫፏ ከምድር እስከ ሰማይ ደርሶ ሰማያውያኑንና መሬታውያኑን ባንድ ማስጠለል ይችላል ሙታን ሳይቀር መጠለያቸው ቤተክርስቲያን ናት እንጅ ሌላ ምን አላቸው፡፡ከዚህም የተነሳ‹‹ ሰናይ ለብዕሲ መቅበርቱ ውስተ ርስቱ፤ለሰው በርስቱ ቦታ መቀበሩ መልካም ነው ››እያሉ ሥጋቸውን በቤተክርስቲያን ነፍሳቸውን በገነት እንዲያኖርላቸው ይማጸናሉ፡፡

ቤተ ክርስቲያን እንደ ሰናፍጭ ካልቀመሷት በቀር ጣዕሟ የማይታወቅ ታናሽ የምትመስል የሰናፍጭ ቅንጣት ናት ለቀመሷት ሁሉ ደግሞ ጣዕሟ በአፍ ሳይሆን በልብ የሚመላለስ ከደዌ የሚፈውስ ነውና ቀርባችሁ ጣዕመ ስብከቷን ፣ጣዕመ ዜማዋን ፤ጣዕመ ቅዳሴዋን እንድትቀምሱ አደራ እላችኋለሁ፡፡ከዚሁሉ ጋራ ርስታችሁ ናትና ከአባቶቻችሁ በጥንቃቄ እንደ ተረከባችሁ ለቀጣዩ ትውልድ እስክታስረክቡ ድረስ የተጋችሁ እንድትሆኑና የጀመራችሁን መንፈሳዊ ተጋድሎ በትጋት እንድትፈጽሙ መንፈስ ቅዱስን ዳኛ አድርጌ አሳስባችኋለሁ፡፡

ኃያሉ አምላክ ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር በቸርነቱ የሀገራችን ኢትዮጵያን አንድነት የኦርቶዶክስ ተዋህዶቤተ ክርስቲያናችንን ዕድገት ለዘለዓለሙ ይባርክ፡፡

 

የአብነት መምህራን የምክክር ጉባኤ ሊካሄድ ነው፡፡

 

ጥር 29 ቀን 2006 ዓ.ም.

በታመነ ተ/ዮሐንስ

የማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የአብነት መምህራን የምክክር ጉባኤን ለሦስተኛ ጊዜ በሀገር አቀፍ ደረጃ ሊያካሂድ ነው፡፡ መርሐ ግብሩ ከየካቲት 6 እስከ 9 ቀን 2006 ዓ.ም ለሦስት ተከታታይ ቀናት ይከናወናል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በመርሐ ግብሩ ይዳሰሳሉ ተብለው ከተያዙ አጀንዳዎች መካከል የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ነጻ የትምህርትና ሥልጠና ዕድል፣ የአብነት ት/ቤቶች የጤና ግንዛቤን ባካተተ እና ትርጓሜ መጻሕፍትን በተመለከተ በዋነኝነት የሚነሡ ርዕሰ ጉዳዮች ሲሆኑ፤ የአብነት ት/ቤቶች የምስክር አሰጣጥና የአገልግሎት ሁኔታ እና ሌሎች ተዛማጅ ርዕሰ ጉዳዮችም ይወሳሉ፡፡

ይህ ጉባኤ ከዚህ ቀደም ከተካሄዱት መርሐ ግብራት ለየት የሚያደርገውን የዋና ክፍሉ ዳይሬክተር ዲ/ን አእምሮ ሲገልጹ “የአሁኑ የምክክር ጉባኤ ለየት ባለመልኩ የሚያጠነጥነው ከሀገሪቷ የትምህርትና የጤና ፖሊሲ ጋር ተደጋጋፊነት ባለው መልኩ ሲሆን፤ ይህም በሀገር ልማት ላይ ያለንን ተሳትፎ የሚጨምር ነው፡፡” ብለዋል፡፡ አያይዘውም በዚህ በተያዘው ዕቅድ መሠረት መጓዝ ከተቻለ የአብነት ተማሪዎችን መደበኛ ትምህርት የመደገፍ ትልም ተጠናክሮ በመቀጠል የአንድ ለአንድ የትምህርት አሰጣጥን ከአንደኛ ደረጃ እስከ ሁለተኛ ደረጃ እስኪደርሱ ተግባራዊ ለማድረግ ያስችላል፤ በዚህም የአብነት ተማሪዎቹ በሁለት ወገን የተሳለ ሰይፍ እንዲሆኑ እንደሚያግዛቸው አውስተዋል፡፡ በዚህም መሠረት የነገ የቤተ ክርስቲያን ተረካቢ የሆኑትን የአብነት ተማሪዎች መደገፍ አስፈላጊ መሆኑን አክለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ከተለያዩ አኅጉረ ስብከቶች የተውጣጡ ከ200 በላይ የአብነት መምህራን የሚገኙ ሲሆን ለሦስት ተከታታይ ቀናት በግዮን ሆቴል፣ በቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣንና በስብሰባ ማእከል(6ኪሎ) ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት ይካሂዷል፡፡ በዚህም መሠረት በስብሰባ ማእከል(6ኪሎ) የካቲት 9 ቀን 2006 ዓ.ም ከቀኑ ከ7፡30 ጀምሮ በሚከናወነው የመዝጊያ መርሐ ግብር ላይ ምእመናን በመታደም የበረከቱ ተሳታፊ ይሆኑ ዘንድ ሓላፊው ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

ሐዋርያዊ ጉዞ በምሥራቅ ኢትዮጵያ

 

 ጥር 29 ቀን 2006 ዓ.ም.

በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል አስተባባሪነት ከጥር ፲፮ እስከ ፳፭ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም ለአሥር ተከታታይ ቀናት በምሥራቅ ኢትዮጵያ ሲካሔድ የሰነበተው ሐዋርያዊ ጉዞ ተጠናቀቀ፡፡

በሐዋርያዊ ጉዞው ከጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ክፍል አባላትን ጨምሮ የማኅበረ ቅዱሳን መምህራን፣ መዘምራንና ጋዜጠኛ በድምሩ ሃያ አራት አባላት ያሉት የልዑካን ቡድኑ መነሻውን ከዋናው ማእከል ማኅበረ ቅዱሳን በማድረግ በአፋር፣ ድሬዳዋ፣ ምሥራቅ ሐረርጌና ሱማሌ ሀገረ ስብከት በመዘዋወር ሰፊ የስብከትና መዝሙር አገልግሎት ፈጽሞ ጥር ፳፮ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም ሲመለስ የማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል አባላት ደማቅ አቀባበል አድርገውለታል፡፡

የልዑካን ቡድኑ ጥር ፲፮ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም በአፋር ሀገረ ስብከት አዋሽ ከተማ ሲደርስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዮናስ ጉባኤውን በጸሎትና ቡራኬ ከፍተው ጉባኤው ለሦስት ተከታታይ ቀናት በአዋሽ መንበረ ፀሐይ ቅድስት ሥላሴና ደብረ ሲና ቅድስት ማርያም ተካሒዷል፡፡

በመቀጠልም ጥር ፲፱ ቀን ፳፻፮ ዓ.ም ወደ ድሬዳዋ ሀገረ ስብከት በማምራት በድሬዳዋ ኆኅተ ሰማይ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ለሁለት ቀን አገልግሎት ተሰጥቷል፡፡ በምሥራቅ ሐረርጌ ደብረ አሚን ተክለ ሃይማኖትና ጅግጅጋ ደብረ መዊዕ ቅዱስ ሚካኤል አብያተ ክርስቲያናት ሁለት ሁለት ቀን የፈጀ ተመሳሳይ አገልግሎት ተፈጸሟል፡፡

የልዑካን ቡድኑ ከተያዘለት ዕቅድ በተጨማሪ በአፋር ሀገረ ስብከት መልካ ወረር ደብረ መድኀኒት መድኀኔዓለም፣ በድሬዳዋ ሳባ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል፣ በድሬዳዋ ደብረ መንክራት ቅዱስ ዑራኤል፣ በጅግጅጋ ምሥራቀ ፀሐይ ኪዳነ ምሕረት አብያተ ክርስቲያናት ጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የስብከተ ወንጌል አገልግሎት እንደነበር የልዑካኑ አስተባባሪ መጋቤ ሃይማኖት ለይኩን ገልጸውልናል፡፡

በእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት ጉባኤ ሲካሔድ ምእመኑ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል የፀሐዩን ግለትና የሌሊቱን ውርጭ ተቋቁሞ እስከ ምሽቱ 3፡30 ድረስ ጉባኤውን ታድሟል፡፡