ገነትህን ጠብቅ ዘፍ.2፡15

 

ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም. 

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መላክ
በምዕ/ጎጃም ሀገረ ስብከት
የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

እግዚአብሔር አምላክ ሰውን ካሰለጠነባቸው ስፍራዎች መካከል አንዱ ኤዶም ገነት ነች፡፡ ታላቁ መጽሐፍ እንደሚነግረን “እግዚአብሔር አምላክም በስተምስራቅ ኤዶም ገነትን ተከለ የፈጠረውንም ሰው በዚያ አስቀመጠው” ካለ በኋላ ገነትን እንዲጠብቃትና እንዲንከባከባት ሓላፊነትን ሰጥቶታል፡፡

ገነት የአራቱ አፍላጋት መነሻ ሰው ከፍሬው ተመግቦ ለዘለዓለም ሕያው የሚሆንበት የዕፀ ሕይወት መገኛ ነበረች፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ሐዋርያው አትናቴዎስ በቅዳሴው ስለገነት ውበት ሲገልፅ ዕፅዋቶቻቸው ቅጠላቸው እስከ 15 ክንድ ይደርሳል፡፡ መዓዛቸው ልብን ይመስጣል፡፡ ፍሬአቸው ከጣዕሙ የተነሣ ሁሌም ከአፍ አልጠፋም ብሎ ነበር፡፡

በዚህ ሁኔታ ልዩ ምድራዊ ገጽታ ተሰጥቷት የተፈጠረችውን ቦታ እንዲኖርባት የተፈቀደለት ሰው ብቻ ነበር፡፡ እንዲኖርባትም ብቻ ሳይሆን እንዲጠብቃትም እንዲንከባከባትም rደራ የተባለው እርሱ ነው፡፡ የተበጀችውን ገነት ምኗን ያበጃታል? እንዲያው በሥራው ሁሉ ሲያሰለጥነው ነው እንጂ፡፡ ለጊዜው ያችን ከምድር ሁሉ የሚመስላት የሌለ ገነት የተባለችውን ቦታ እንዲጠብቃት ነበር ትዕዛዝ የተላለፈለት ገነት ሦስት ዓይነት ትርጉም አላት፡፡

 

1ኛ ሕይወተ አዳም፡- የመጀመሪያው የገነት ትርጉም ህይወተ አዳም ነው፡፡ ገነት በአማሩና በተዋቡ እፅዋት የተሞላች ጣፋጭ መዓዛ ፣ ፍሬ የማይታጣባት ቦታ ነበረች ህይወተ አዳምም ስትሰራ ልምላሜ ነፍስ ፤ መዓዛ መንፈስ ቅዱስ ፍሬ ክብር የተሞላች እንደነበረች ያሳያል፡፡ ሰይጣን እስኪያጠወልጋት ድረስ የአዳም ህይወት ልምላሜ ይታይባት ነበር፡፡ እግዚአብሔርም ገነትን ጠብቃት ሲለው ህይወትህን ጠብቃት ሲለው ነው፡፡ ከሁሉም በላይ አዋቂ ነውና በህይወቱ ላይ ስልጣን የተሰጠውም ፍጡር ነበር፡፡ መጠበቅም ብቻ ሳይሆን መንከባከብም ለእርሱ የተሰጠ ሓላፊነት ነበር፡፡ ዐቂበ ህግ (የታዘዘውን ህግ መጠበቅ) የህይወቱ መጠበቂያ መንገድ ሲሆን ለእግዚአብሔር የሚያደርገው አገልግሎት ደግሞ ገነት ለተባለች ህይወቱም መንከባከቢያ መንገድ ነው፡፡
በስተምስራቅ በኩል የተተከለች ምስራቃዊት ቦታ በመሆኗ ደግሞ ሌላው አስደናቂ ምስጢር ነው፡፡ ምስራቅ የብርሃን መውጫ ነው፡፡ ከምስራቅ የወጣው ብርሃን ለአራቱ መዓዘናት ሁሉ ይበቃል፡፡ ሰውም ከርሱ በሚወጣው ጥበብ ዓለምን ለውጦ የሚኖር ልዩ ፍጡር መሆኑን ያመለክታል፡፡

ወንድሜ ሆይ ገነትህን እንዴት እየጠበካት ነው አሁንም ከነሙሉ ክብሯ ነው ያለችው፤ እርግጠኛ ነህ ዛሬም እንደጥንቱ ሁሉ ለማየት ደስ የሚያሰኘውን ለመብላትም መልካም የሆነውን ዛፍ በአንተ ገነት ውስጥ ማግኘት ይቻላል፤ እውነት እልሃለው ያንተን ገነት ለመጎብኘትና ከገነትህም ፍሬ ለመብላ ገነትህን የፈጠረ ጌታ ወደ አንተ እንደሚመጣ ታላቁ መጽሐፍ ይናገራል፡፡

 

‹‹ወልድ አሁየ ወረደ ውዕቱ ገነቱ ወይብላዕ እምፍሬ አቅማሂሁ›› ወደ ገነት ገባ መልካሙንም ፍፌ ይበላ ዘንድ መኃ 4፡16 መልካም ፍሬ ለማስገኘት ምን ያህል ትተጋለህ፤ አንተ ወዳለህበት ገነት ሲመሽ የህይወትህ መዝጊያ ሰርክ ላይ ድምፁን እያሰማ ፈጣሪህ መምጣቱን እንዳትዘነጋ፡፡ ለነገሩማኮ! ያንተገነት መስሎ የተሰራ ሁሉ የተሟላለት ቦታ ማግኘት አይቻልም፡፡ አንተኮ የታዘዝከው እንድትጠብቅና እንድትንከባከብ እንጅ ምንም እንድትጨምር አይደለም፡፡ ምንም እንኳ አንዳንድ ጊዜ ገነትህን ሊያጠወልጉ የሚችሉ ነገሮች ቢኖሩም እግዚአብሔር ግን ያንተን ገነት እንዲሁ አልተዋትም፡፡ መልሰው ወደልምላሜዋና ወደቀድሞ ውበቷ ይመልሷት ዘንድ በውስጧ የሚመላለሱ አራት አፍላጋትን በነዚህ አፍላጋት ህይወት ሰጭነት ገነትህን በህይወት ማኖር ትችላለህ፡፡ አራቱ አፍላጋት የሚባሉት አራቱ ወንጌላውያን ናቸው፡፡ ያንተን ገነት ከልምላሜ አዕምሮ ወደፅጌ ትሩፋት ከፅጌ ቱርፋት ወደፍሬ ክብር እንዲያደርሱ የተፈጠሩ ናቸው፡፡ በገነት ውስጥ በገነትህ ውስጥ እንዲፈሱ አድርጋቸው፡፡ በገነትህ ውስጥ የበቀለው እፀ ህይወትም የተሰጠህን ልጅነት ያመለክታል፡፡ ያንተ ገነት ማለት በነዚህ ሁሉ ስጦታዎች የተሞላች በመሆኗ የጠላት ዓይኖች በደጅ ስለሚያደቡባት ልትጠነቀቅላት ይገባል፡፡ በሀይማኖት ጠብቃት በጾም በጸሎት በስግደት ተንከባከባት፡፡ በገነትህ መካከል የፈጣሪው ድምፅ ሲሰማ የሚሸሸግ እርቃኑን የቆመ አዳም የተሸሸገባት እንዳትሆን ገነትህን ልትመለከታት ይገባሃል፡፡ ገነትህነን ጠብቃት ተንከባከት

 

፪ኛ የገነት ትርጉም ዓለመ ቅዱሳን ገነተ ፃድቃን ክርስቶስ ነው፡፡ ፃድቃን በዚች ምድር ሲሆኑ አረጋዊ መንፈሳዊ እንደተናገረው ክርስቶስን ዓለም አድርገው ይኖራሉ፡፡ ከዕለታት በአንድ ቀን የአረጋዊ መንፈሳዊ ወንድሙ ዮሐንስ በበርሃ የሚኖር ወንድሙ አረጋዊን ራስህን የምታስጠጋበት ጎጆ ልስራልህን፤ ብሎ ላቀረበለት ጥያቄ ሲመልስ ‹‹ የሁሉ ማረፊያ ጌታ ;; ለኔ ማረፊያነት አነሰኝን ብሎ ነበር የመለሰለት ስለዚህ ፃድቅ በአፀደ ስጋ በአፀደ ነፍስ ማረፊያ ገነታቸው ክርስቶስ ነው፡፡ ለዚህም ነው በመጀመሪያ ጊዜ በምድር ላይ ፅድቁ ለተረጋገጠለት ለፈያታዊ ዘየማን ዛሬ በገነት ትኖራለህ ሉቃ 23፡43 የሚል መልስ የተሰጠው ጥበበኛ ሰው ሰለሞንም የክርስቶስን ወደዚህ ዓለም አመጣጥ ሲገልፅ ‹‹ ውዴ በገነቱ መንጋውን ያስማራ ዘንድ ወረደ መኃ 6፡2 በማለት የምፅዓቱን ዓላማ ይገልፃል፡፡ ከርሱ በቀር ምን መሰማሪያ አለን በራችን መሰማሪያ ገነታችን ክርስቶስ ኢየሱስ ነው፡፡ ጠብቅ ማለት እርሱ ከሁለት አካል አንድ አካል ከሁለት ባህሪ አንድ ባህሪ የሆነ አምላክ ነው፡፡ ብለህ እመን ማለት ነው፡፡
በገነት ውስጥ ያሉ አፍላጋት የአራቱ ወንጌላዊያን የምስጢር ምንጭ (መገኛ ክርስቶስ መሆኑን ሲያመለክት ዕፀ ህይወትም የህይወት መገኛ እርሱ መሆኑን ያሳየናል፡፡ በዚህ ገነት ውስጥ መኖር ለሰው ህይወት ነው፡፡ ረሃብ የለም ውኃ ጥምም የለም ሀዘንና ስቃይም የለምና በዚህ ገነት ውስጥ ይኖር ዘንድ ለሁሉም ጥሪ ተላልፎአል፡፡

 

፫ኛ. እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፡- በመጽሐፍት ሁሉ መልካም ስም እና ምሳሌ የተሰጠው ከቅዱሳን ሁሉ እንደመቤታችን ማንም የለም ከነዚህ ስሞቿ መካከል ገነት የሚለው አንዱ ነው፡፡ ከነብያት አንዱ የሆነው አባቷ ሰሎሞን በዘመን ሁሉ ተጠብቆ የሚኖር ንጽሕናዋን በገለፀበት አንቀፅ ነበር፡፡ “ገነት ዕፁት ወአዘቅት ኅትምት›› መኃ 4፡12 የታተመች የውሃ ምንጭ የተዘጋች ገነት የሚል ነው፡፡ ይህንን ይዘው ከዚያም በኋላ የተነሱ ሊቃውንት እነቅዱስ ያሬድ እነ ቅዱስ ኤፍሬም ገነት ይዕቲ ነቅዓ ገነት ዐዘቅተ ማየ ህይወት የህይወት ውኃ ምንጭ የገነት ፈሳሾች መገኛ ገነት ተፈስሂ ኦ ገነት ነባቢት ማኅደሩ ለክርስቶስ የክርስቶስ ማደርያው ነባቢት ገነት አንችነሽ ፡፡ እያሉ በየድርሳናቱ አወድሰዋታል፡፡

ገነትና እመቤታችን በሚከተሉት መንገዶች ይመሳሰላሉ፡፡

  • ገነት ምስራቃዊት ቦታ ነች እመቤታችንም በምስራቃዊ የሀገራችን ክፍል የተገኘች መሆኗን ያመለክታል፡፡ አንድም የፀሐየ ፅድቅ የኢየሱስ ክርስቶስ መገኛ ናትና ነው፡፡

  • በገነት ዕፀ ህይወት ይበቅልባታል፡ ከእመቤታችንም እፀ ህይወት ተብሎ የሚጠራ ስጋውና ደሙ የመገኘቱ ምሳሌ ነው፡፡ ይህንንም ሲያስረዳ ቅዱስ ኤፍሬም ‹‹ ከእፀ-ህይወት እንበላ ዘንድ አደለን ይኸውም የክርስቶስ ስጋና ደሙ ነው ሲል ይገልጸዋል፡፡ የአማናዊት እፀ ህይወት መገኛ ድንግል አማናዊት ገነት

  • በገነት አራት አፍላጋት አሉ ብለን ነበር እነዚህ የአራቱ ንህናዎቿ ሰው የሚበድልባቸው አራት መንገዶች አሉ፡፡ ማየትና መስማት ማሽተትና መዳሰስ ናቸው ሰው በህይወት ዘመኑ በነዚህ አራት መንገዶች ሲበድል ይኖራል፡፡ እመቤታችን ግን በነዚህ ሁሉ አልበደለችውምና አራቱ የገነት አፍላጋት በእመቤታችን አራት ንፅህናዎች ይመሰላሉ ያልነው በዚህ ነው፡፡ ወንድሜ ሆይ የሚበላውን የሚጠጣውን ያስገኘችልን አማናዊት ገነት ድንግል ማርያም ናትና በርሷ ውስጥ ብትኖር ለህይወትህ መልካም ነውና ደግሜ እልሃለው ገነትን ጠብቃት፡፡

 

 

lemena 01

ንዋያተ ቅዱሳቱ የማን ናቸው?

 ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የዜማ መሣሪያዎች ከቅዱስ ያሬድ ጀምሮ በርካታ ሊቃውንት ሲያገለግሉበት የነበረና የሰማያዊውን የዝማሬ ሥርዓት መነሻ ያደረገ፣ ሰማያዊውንም ዓለም የሚያሳስብ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ቃልም መነሻ ተደርጎ የተመረጠ፣ ኢትዮጵያዊ መልክ ኖሯቸውም የተዘጋጁ ናቸው፡፡

እነዚህ የዜማ መሣሪያዎች ቤተክርስቲያናችን ይዛ በምትጠቀምበት ቅርጽና ይዘት የሚገኙት በኢትዮጵያና ኢትጵያውያን እጅ ብቻ ነው፡፡ ይልቁንም ደግሞ የአንድ ቤተ ሃይማኖት ማለትም የኦርቶዶክስ ሃይማኖት መጠቀሚያ ሆነው እያገለገሉ ያሉ ናቸው፡፡

ይህ በእንዲህ እያለ ግን ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ሌሎች ቤተእምነቶች በከበሮ፣ በመቋሚያና ጸናጽሉ በራሳቸው ተጠቅመው በራሳቸው መንገድ የራሳቸውን እምነት ሲያራምዱበት እየታየ ነው፡፡ በመድረኮቻቸው ያንን ሲያደርጉ ታይተዋል፡፡ በቴሌቪዥን ፕሮግራም ሲያስተላልፉ ተስተውሏል፡፡

በተመሳሳይ ዜማው የዝማሬ ሥርዓቱ የበዓላት ሥርዓቱ ንዋየ ቅድሳቱ ሁሉ ደረጃ በደረጃ በተለያዩ ቤተእምነቶች ቁጥጥር ሥር ወድቋል፡፡ የበዓላት ቀናቱ ጭምር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ባሕረ ሐሳብ መሠረት የሚወጣ ቢሆንም እንደራሳቸው አደርገው በዓል ሲያደርጓቸው ልዩ ልዩ መርኀ ግብር ሲፈጸምባቸው ይታያል፡፡ ለዚህ ማሳያ የሚሆነው የመስቀል በዓል ነው፡፡ በዓለ መስቀል ኦርቶዶክሳውያንን ብቻ የሚመለከት በዓል ቢሆንም አሁን ግን በቤተክርስቲያኒቱ የበዓል ዐውድ ውስጥ ሌሎች ቤተእምነቶች የራሳቸውም እንደሆነ በሚያስመስል መንገድ ስለሚቀርቡ ግራ መጋባት እየፈጠረ ነው፡፡ ይሄ ነገር በዚሁ ከቀጠለ ቤተክርስቲያናችን የእኔ የምትለው የራሷ ነገር እየጠፋ ሊመጣ ይችላል፡፡

በመሆኑም የዝግጅት ክፍላችን በተለይ የዜማ መሣሪያ በሆኑ ንዋየ ቅድሳት ጋር በተያያዘ ሁለት ባለሙያዎችን ለማነጋገር ጥረት አድርጓል፡፡ ያነሣናቸው ጥያቄዎችም ከሕግ፣ ከቅርስ ጥበቃና እንክብካቤ አንጻር በመሆኑ ያነጋገርናቸው ባለሙያዎችም በእነዚሁ ጉዳዮች ላይ ባለሙያ የሆኑ ናቸው፡፡ እነሱም የሕግ ባለሙያ የሆኑት አቶ ጌታሁን ወርቁና በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር የሆኑት መምህር መንግሥቱ ጎበዜ ናቸው፡፡ ሁለቱንም ባለሙያዎች ጠይቀን የሰጡንን መልስ እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

 

ሐመር፡- አንዱ ቤተእምነት የሌላውን ቤተእምነት የትኛውንም ዓይነት የአገልግሎት መጠቀሚያ ንዋየ ቅድሳት መጠቀሙ ሕጋዊ ሊሆን የሚችልበት አካሔድ አለ? ሌሎች ከዚህ ጋር ተያያዥ የሆኑ የሕግ ሐሳቦችን ቢያመለክቱን

lemena 01አቶ ጌታሁን ወርቁ፡– የቤተእምነት አገልግሎት መጠቀሚያን በተመለከተ ያሉት ሕግጋት በጣሙን ግልጽነት የሚጎድላቸው ናቸው፡፡ የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምሮ የምትጠቀምባቸው ንዋየ ቅድሳት አሉ፡፡ እነዚህን ንዋየ ቅድሳት ሌሎች ቤተእምነቶች ሲጠቀሙ አስተውያለሁ፡፡ እናም ጥያቄው የመጠቀማቸው ሁኔታ ከምን ሕግ የመነጨ ነው፡፡ ወይም ቤተክርስቲያኗ ንዋየ ቅድሳቱን ራሷ ብቻ እንድትጠቀም የማድረግ መብት ይኖራታል ወይ የሚለው ነው ምላሽ የሚፈልገው ጭብጥ፡፡
በሕግ አንድ ሰው የተፈጥሮ ወይም በሕግ ሰውነት የተሰጠው ተቋም መብት ሊያገኝ የሚችለው ከሕግ አልያም ከውል ነው፡፡ የቤተክርስቲያኗን መብት ሕግ እውቅና ከሰጠውና ስፋትና ወሰኑን ካስቀመጠው መብቷን ለመጠየቅ መነሻ ይሆናል፡፡ ሁለተኛው ውል ሲሆን ሁለት ወይም ከዛ በላይ የሆኑ ሰዎች (ተቋማት) መብቶችንና ግዴታዎችን ለማቋቋም ለማሻሻል ወይም ለማቋረጥ የሚያደርጉት ስምምነት ነው፡፡ እንዲህ ዓይነት ስምምነት በነፃ ፈቃድና በችሎታ ከተደረገ፤ ከሕግና ከሞራል ተቃራኒ ካልሆነ በተዋዋይ ወገኖች መካከል ሕግ ሆኖ የሚያስገድዳቸው ይሆናል፡፡

ንዋያተ ቅድሳትን በተመለከተ በቅድሚያ ግልጽ መሆን ያለባቸው የብያኔና በልማድ የሚታዩ ነጥቦች አሉ፡፡ የመጀመሪያው የንዋያተ ቅድሳት ትርጉም ነው፡፡ ከቃሉ ጥሬ ትርጉም ብንነሳ ንዋያተ ቅድሳት የሚባሉት ለእግዚአብሔር አምልኮ መፈፀሚያ የሚሆኑ ዕቃዎች ናቸው፡፡ በቤተክርስቲያን ትምህርት እነዚህን ንዋያት በቅዱስ ሜሮን የሚከብሩ ለዜማ፣ ለቅዳሴ፣ለምስጋና የተለዩ ዕቃዎች ናቸው፡፡ እነዚህን ንዋያት በተመለከተ ቤተክርስቲያን ብዙም አከራካሪ ያልሆነ መብት አላት፡፡ በተግባርም እነዚህ ንዋያት ሲሰረቁ፣ ሲዘረፉ ወዘተ ለፖሊስና ለፍ/ቤት አቤቱታ በማቅረብ ስታስመልስ የቆየችው ከዚሁ በመነሳት ነው፡፡ በሌላ በኩል ግን በቅዱስ ሜሮን የከበሩም ቢሆን የንዋያተ ቅድሳት ስፋት ከመስቀሉ፣ ከበሮ ጀምሮ ጧፍና እጣንም ሳይቀሩ የሚካተቱበት ነው፡፡ ጧፍ በየቦታው ከመመረቱና ለተለያዩ ማኅበራዊ አገልግሎት ከመዋሉ አንፃር በቅዱስ ሜሮን ቢከብርም እንደሌሎች ንዋያት ጠንካራ የሕግ ጥበቃ ላይሰጠው ይችላል፤ ይህም የሆነው ከማስረጃ አስቸጋሪነት አንጻር ነው፡፡ በቅዱስ ሜሮን ከብረው ንዋያተ ቅድሳት ያልሆኑት ግን የተለየ ምልከታ ሊደረግላቸው ይገባል፡፡ በሜሮን ባይከብሩም በቤተክርስቲያኗ ለዘመናት አምልኮ፣ ምስጋና ለመፈጸም ግብዓት የሚሆኑ ዕቃዎችን ለምሳሌ ከበሮ፣ ጸናጽል፣ መቋሚያ፣ ጥንግ ድርብ ወዘተ የመሳሰሉትን መሳሪያዎች በተመለከተ ግን ቀደም ሲል ያየናቸውን ያህል ግልጽ የሕግ ጥበቃ ሥርዓት አለመኖሩን አምናለሁ፡፡

በሕግ ደረጃ ለቤተክርስቲያኗ መብት መነሻ የሚሆኑት በፍትሐ ብሔር ሕጉ የተደነገገው የንብረት ሕግ፣ ስለቅርስ ጥናትና አጠባበቅ የወጣው አዋጅ እንዲሁም የቅጅና የተዛማጅ መብቶች ጥበቃ አዋጅ ናቸው፡፡ በእነዚህ ሕግጋት ቤተክርስቲያኗ በሕግጋቱ ላይ መብቷ እንዲታወቅና እንዲጠበቅ የተደነገጉትን ሁኔታዎች ካሟላች ባለመብት ሆና ሌሎች እንዳይጠቀሙ የምትከላከልበት ሁኔታ ይኖራል፡፡

በንብረት ሕግ በንብረት ላይ ሰፊ ጥበቃ የሚሰጠው መብት የሀብትነት (ባለቤትነት) (Ownership) መብት ሲሆን ይህ መብት በንብረቱ የመገልገል፣ ንብረቱን ለሌላ መጠቀሚያ የማከራየት ወይም የመሸጥ የመለወጥ መብትን ያጠቃልላል፡፡ በአንድ ዕቃ ላይ የባለቤትነት መብት ያለው ሰው /ተቋም መብት ሳይኖረው እጁ ካደረገው ሰው ወይም ከያዘው ሰው ሀብቱ ይገባኛል ሲል ለመፋለምና ማናቸውንም የኃይል ተግባር ለመቃወም እንደሚችል በፍትሐ ብሔር ሕግ ቁጥር 1206 ተደንግጓል፡፡ በሕጉ ባለሀብትነት (ባለቤትነት) የሚረጋገጠው እንደ ንብረቱ ዓይነት ነው፡፡ የሚንቀሳቀስ ግዙፍ ነገር ባለይዞታ የሆነ ሰው በራሱ ስም እንደያዘውና የዚሁ ነገር ባለቤት/ባለሀብት/ እንደሆነ ይገመታል ሲል ሕጉ በ/ፍ/ብ/ሕ/ቁ 1193 ደንግጓል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት ተራ ተንቀሳቃሽ (Ordinary Corporeal chattels) ባለቤትነት እጅ በማድረግ (በመያዝ) ብቻ ባለቤት ይኮናል፡፡ ሆኖም ሕጉ በልዩ ሁኔታ ልዩ ተንቀሳቃሽ ንብረት በመባል የሚጠሩትን መኪናን የመሰሉትን የምዝገባ መስፈርቶች በልዩ አዋጅ በማስቀመጡ ንብረቱን በእጅ ከማድረግ ባለፈ ካልተመዘገበ የባለቤትነት መብት አያስገኝም፡፡ ሁለተኛው የባለቤትነት ማረጋገጫ የማይንቀሳቀስ ንብረትን የሚመለከት ሲሆን በአስተዳደር ክፍል ባለቤትነቱ ታውቆና ተመዝግቦለት የባለሀብትነት የምስክር ወረቀት የተሰጠው ሰው /ተቋም የንብረቱ ባለቤት ይሆናል፡፡

ንዋያተ ቅድሳትን በተመለከተ (በቅዱስ ሜሮን ያልከበሩትን) የተለየ ሕግ ባለመኖሩ ልዩ ተንቀሳቃሽ ንብረት በሚለው የማይወድቁና የምዝገባ ሥርዓት ያልተመዘገበላቸው ናቸው፡፡ ስለዚህ እነዚህ ዕቃዎች ከገበያው በሽያጭና በስጦታ የሚገኙና የገዛቸው ሰው ባለሀብት (ባለቤት) የሚሆንባቸው በመሆኑ ሁሉም ቤተ-እምነት የዕቃዎቹ ባለቤት የመሆን እድላቸው የተዘጋ አይደለም ማለት ነው፡፡ በዚህ መነሻነት ቤተክርስቲያን የራሷን ንዋያት መጠበቅ፣ ሌላው እንዳይጠቀም የማድረግ መብት ያላት ንዋያተ ቅድሳቱ በእጇ ገብተው እየተጠቀመችባቸው ካሉ ብቻ ይሆናል፡፡

ሁለተኛው ለመብት አጠባበቅ መሠረት የሚሆነው ስለቅርስ አጠባበቅ የወጣው አዋጅ ቁጥር 209 /1992 ዓ.ም ነው፡፡ በዚህ አዋጅ ትርጓሜ መሠረት “ንዋየ ቅድሳት” በአንቀጽ 2(6) “ግዙፍነት ያለው ቅርስ ” በሚለው ምድብ ይወድቃሉ፡፡ ግዙፍነት ያለው ቅርስ ማለት በእጅ የሚዳሰሱ፣ በዓይን የሚታዩ የሚንቀሳቀሱና የማይንቀሳቀሱ ባህላዊና ታሪካዊ ወይም ሰው ሠራሽ ቅርሶችን ይጨምራል፡፡ “የማይንቀሳቀስ ቅርስ” ውስጥ የብራና ጽሑፍ ከወርቅ ፣ ከብር፣ ከነሐስ፣ ወይም ከብረት ወይም ከመዳብ ከሌሎች ንጥረ ነገሮች ከእንጨት፣ ከድንጋይ፣ ከቆዳ፣ ከዝሆን ጥርስ፣ ከቀንድ፣ ከአጥንትና ከአፈር ወይም ከሌሎች ነገሮች የተሰሩ ቅርሶችና ምስሎች ይገኙበታል፡፡ በዚህ ብያኔ መሠረት የቤተክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት የሚንቀሳቀሱ ቅርሶች ናቸው፡፡ በዚህ አዋጅ አንቀጽ 14 መሠረት ቤተ ክርስቲያን የንዋያተ ቅድሳቶቿ ባለቤት መሆን የምትችል ሲሆን ንዋያተ ቅድሳቱ በቅርስ ጥበቃ ባለሥልጣን ተመዝግበው የሕግ ጥበቃ ይሰጣቸዋል፡፡ ቤተክርስቲያን በዚህ አዋጅ መሠረት ያስመዘገበቻቸው ቅርሶች ከመሠረታዊ ዓላማቸው፣ ከታሪካዊ አመጣጣቸውና ሊሰጣቸው ከሚገባው ክብር ዝቅ የሚያደርጉ ተግባራትን ለቅርስ ባለሥልጣን ሪፖርት በማድረግ የንዋያተ ቅድሳቱን አጠቃቀም ጥበቃ እንዲደረግ ለመጠየቅ ትችላለች፡፡

የመስቀል በዓል አከባበር በዓለም ቅርስነት የመመዝገቡ እውነታ ደግሞ ለቤተክርስቲያኗ ተጨማሪ ጥበቃ እንደሚ ያስገኝላት ይታሰባል፡፡ የመስቀል በዓል ምዝገባ ባህላዊና ሃይማ ኖታዊ ሥርዓቶችን አካትቶ የተመዘገበ በመሆኑ ሃይማኖታዊ በሆኑት መጠን ቤተክርስቲያኗ ከምዝገባው መብት ታገኛለች፡፡ ንዋያተ ቅድሳቱ (አለባበሱ፣ ዝማሬው፣ ንዋያተ ቅድሳቱና ውሕደታቸው) በምዝገባው መሠረት በተመሳሳይና በወጥነት ሳይበረዙ እንዲተላለፉ የማድረግ መብት አላት፡፡ ይህ መብት ሥርዓቱን እንዳመጣበት እንዳይቀጥል የማድረግ ውጤት ያላቸውን የአለባበስ፣ የዝማሬ፣ ወይም የንዋያተ ቅድሳት አጠቃቀም እንዲከላከል ለኢትዮጵያ መንግሥት ወይም ለዩኔስኮ እስከማቅረብ እንደሚደርስ መረዳት ይችላል፡፡

ሦስተኛው ለመብት ጥበቃው መሠረት የሚሆነው የቅጅና ተዛማጅ መብቶች ጥበቃ አዋጅ ቁጥር 410/1996 ዓ.ም ነው፡፡ በዚህ አዋጅ መሠረት ንዋያተ ቅድሳቱ በራሳቸው ተለይተው ሳይሆን ከዝማሬ፣ አቋቋም፣ ቅዳሴ ወ.ዘተ ጋር ተዋሕደው ሕጉ ጥበቃ ሊያደርግላቸው ይችላል፡፡ ለምሳሌ ከበሮ፣ መቋሚያ፣ ጸናጽል ከዜማው ጋር በቅኔ ማኅሌት የሚደረገው ክንውን (Performance) መብት ጥበቃ ሊያገኝ ይችላል፡፡ በዚህ አዋጅ መሠረት ጥበቃ ለማግኘት የዜማ ሥራው ወጥ (Original) እንዲሁም የተቀረጸ ወይም ግዙፍነት ያገኘ ሊሆን ይገባዋል፡፡ ይህም ማለት ሥራው ለሕዝብ የቀረበ ወይም የታተመ መሆን አለበት፡፡ በዚህ ረገድ ቤተክርስቲያን ያሉዋትን የንዋያተ ቅድሳት አጠቃቀም በተመለከተ በሚወጡ ቪዲዮዎች፣ ለሕዝብ ሲቀርብ፣ ተቀርጾ ሲተላለፍ ወዘተ ሌሎች በታየው /በቀረበው/ በታተመው መሠረት የንዋያተ ቅድሳቱን ውሕደት እንዳይጠቀሙ የመከላከል መብት ይኖራታል፡፡ ይህ መብት በአብያተ ክርስቲያናቱ ወይም በግለሰብ አማኞች (ማኅበራት፣ ግለሰብ ዘማርያን ወዘተ) ሊጠየቅ ይችላል፡፡

ከላይ በመግቢያው እንደገለጽኩት ሁለተኛው የመብት ምንጭ ውል ሲሆን በሃይማኖት ተቋማት ስለአምልኮ አፈፃፀም፣ ስለአማኞች ስርቆት (Sheep stealing)፣ አንዱ የሌላውን የአምልኮ መፈጸሚያ፣ የአምልኮ ዕቃን ስለመጠቀም አለመጠቀም፤ የጋራ የሆኑ ጉዳዮች ላይ በአንድነት ስለመሥራት የተደረገ ስምምነት ካለ ይህ ገዥ መሆኑ አይቀርም፡፡ እንደሚ ታወቀው በክርስትና ስም ያሉ ቤተ-እምነቶች የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት አባል በመሆናቸው እርስ በርሳቸው ባላቸው ግንኙነት አንዱ ሌላውን የሚጎዳ ድርጊት እንዲሠራ የማይፈቅዱበት ሁኔታ ይኖራል፡፡ እምነት በልብ የሚታመን ብቻ ሳይሆን በአፍ የሚነገር በድርጊት የሚገለጥ ነው፡፡ አለባበስ፣ ዝማሬ፣፣ በተለያዩ ንዋያተ ቅድሳት በመጠቀም አምልኮ መፈፀም የእምነቱ አካል ነው፡፡ አንዱ ቤተ እምነት የሌላውን ፈቃድ ሳያገኝ ለዘመናት ሲጠቀምበት የነበረውን የአምልኮ መፈፀሚያ የሚጠቀም ከሆነ በኅብረት የመኖራቸው ነገር ትርጉም ያጣል፡፡ አንዱ የሌላውን የሆነውን ሀብት፣ ትውፊት ያለፈቃድ የሚወስድ ከሆነ አብያተ ክርስቲያናቱ በጋራ የገቡትን ውል ወይም ስምምነት መጣስ ነው፡፡ ይህ መብቱ የተጣሰበት ቤተ-እምነት ስምምነቱን መሠረት በማድረግ መብቱ እንዲከበርለት የመጠየቅ መብት ይኖረዋል ማለት ነው፡፡ ሙሉ/ ስምምነቱ በአብያተ ክርስቲያናቱ መካከል እንደ ሕግ ስለሚቆጠር መብቱ ለተጣሰበት ቤተ እምነት መፈጸሙ መፍትሔ /Remedy/ እንደሚሆን ማሰብ ይቻላል፡፡

እስካሁን የተመለከትነው ከንብረት መብትና ከቅርስ አንጻር ያለውን የመብትና ግዴታ አተያይ ነው፡፡ አንዱ ቤተእምነት አምልኮውን ከሚፈጽምበት መጠቀሚያ አንጻር መብቱ የሚሰጠው ስለመሆኑ ነው፡፡ በሌላ በኩል ግን በቤተ እምነቶች መካከል አምልኮን ከመፈጸሚያ ዕቃ (መሣሪያ) አንጻር የሚነሱ አለመግባባቶችም ከእምነት ነጻነትና ከሕዝብ ደኅንነት አንጻር ሊታይ ይችላል፡፡ አንዱ ቤተእምነት የሌላውን ቤተእምነት ሀብት ወይም የአምልኮ መሣሪያ መጠቀሙ ለዘመናት ሲጠቀምበት የነበረውን የቤተ እምነት ተከታዮች ቅር የሚያሰኝ ወይም ቁጣ የሚያስነሳ ሊሆን ይችላል፡፡ እንዲህ ዓይነት ጉዳዮች በእኛ ሀገር የሕግ ሥርዓት መፍትሔ የሚያገኙት ደግሞ የእምነት ነፃነትን ጥበቃ የሚሰጠው ሕገ መንግሥቱ ወይም ከሕዝብ ደኅንነትና ሰላም መጠበቅ በወጣው የወንጀል ሕጉ ነው፡፡ በዚህ ረገድ ሁለቱን ሕግጋት ከተነሳንበት አንፃር መፈተሸ ተገቢ ይሆናል የሚል እምነት አለኝ፡፡

የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 27(1) “የሃይማኖት፣ የእምነትና የአመለካከት ነፃነት በሚል ርዕስ” ማንኛውም ሰው የማሰብ የሕሊና እና የሃይማኖት ነፃነት አለው፡፡ ይህ መብት ማንኛውም ሰው የመረጠውን ሃይማኖት ወይም እምነት የመያዝ ወይም የመቀበል ሃይማኖቱንና እምነቱን ለብቻ ወይም ከሌሎች ጋር በመሆን በይፋ ወይም በግል የማምለክ የመከተል የመተግበር፣ የማስተማር ወይም የመግለጽ መብትን ያካትታል» ሲል ይደነግጋል፡፡

ይህ ሕገመንግሥታዊ ድንጋጌ ለሃይማኖት ነፃነት ዋስትና የሚሰጥ ቢሆንም የሃይማኖት ነፃነት ገደብ የለውም ማለት አይደለም” የሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 27(5) “ሃይማኖትንና እምነትን የመግለጽ መብት ሊገደብ የሚቻለው የሕዝብን ደኅንነት፣ ሰላምን፣ ጤናን፣ ትምህርትን፣ የሕዝብን የሞራል ሁኔታ፣ የሌሎች ዜጎችን መሠረታዊ መብቶችና ነፃነቶች እና መንግሥት ከሃይማኖት ነፃ መሆኑን ለማረጋገጥ በሚመጡ ሕጎች ይሆናል” በማለት ደንግጓል፡፡ በዚህ ድንጋጌ መሠረት የሚገደበው የሃይ ማኖት መብት / የመረጡትን እምነት መያዝ ሳይሆን አገላለጹ ነው፡፡ የእምነት /አመለካከት/ መብት ፍጹማዊ በመሆኑ አይገደብም፣ መገደብም አይቻልም፡፡ ሃይማኖትን የመግለጽ መብት ለሕዝብ ሰላምና ደኅንነት ሲባል ገደብ ሊጣልበት ይችላል፡፡ የአንድ እምነት የአምልኮ ሥርዓቶች ኅብረተሰቡን የሚረብሹ፣ የሕዝብን ሥርዓትና ደኅንነት የሚያናጉ፣ በኅብረተሰቡ ሕይወት፣ ህልውና እና ንብረት ላይ ከባድ አደጋ የሚያደርሱ ሆነው ከተገኙ መንግሥት ሕግ ማውጣት እና ገደቡም በአግባቡ እንዲመራ በማድረግ ገደብ ሊጥል ይችላል፡፡

በቤተ እምነት መካከል የሚታየው የአንዱን የአምልኮ መፈፀሚያ መሳሪያ ሌላው ያለፈቃዱ የመጠቀሙንም ነገር እኔ የማየው ከእምነት አገላለጽ ነው፡፡ አንዱ ቤተእምነት ለዘመናት ሲዘምርበት፣ ሲያመሰግንበት የቆየበትን ሥርዓት እና የአገልግሎት መጠቀሚያ ሌላው ሲጠቀም በአማኞቹ መካከል አለመግባበት ይከሰታል፡፡ እምነቱ በኅሊና ብቻ ያለ ሳይሆን አማኙ የሚለብሰውም፣ የሚዘምረውም፣ የሚጠቀምበትን የንዋያተ ቅድሳት ዓይነት የሚያካትት ነው፡፡ ስለዚህ የራሱ ባልሆነው የተጠቀመው ቤተ እምነት የሌላውን ቤተእምነት መብት የሚነካ ነው፡፡ እንዲህ ባለ ጊዜ ታሪክን፣ የቤተ እምነቶቹን ሥርዓት፣ የዳበረ ልማድን መሠረት አድርጎ ክልከላ ካልተደረገበት ሥርዓት አልበኝነት ይነግሣል ለሕዝቡም ሰላምና ደኅንነት ስጋት መሆኑ አይቀርም፡፡ ስለዚህ መንግሥት በሕገ መንግሥቱ በግልጽ የተቀመጠውን የሃይማኖት ነፃነት ገደብን መሠረት በማድረግ ቤተእምነቶች መካከል የሚታየውን አንዱ አንዱን የማንቋሽሽ ድርጊት፣ የአንዱን ቤተእምነት የአምልኮ መጠቀሚያ ያለአግባብ መጠቀምን የመሰሉ በሕዝቡ ውስጥ ረብሻና ሁከት የመፍጠር አቅም ያላቸውን አሠራሮች መስመር ሊያስይዝ ይገባል፡፡ ይህ አካሄድ የሃይማኖት ብዙኅነትንም የሚያስቀር እና የአማኞችን ማንነት በማያሻማ መልኩ እንዲገለጽ የማያደርግ በመሆኑ የሕጉ ጣልቃ ገብነት አስፈላጊ ነው፡፡ በአንዳንድ ሀገራት እንኳን የሃይማኖት መገለጫው (የአምልኮ መሳሪያው) የቃላት አጠቃቀም እንኳን የሕግ ጥበቃ ይሰጠዋል፡፡ ቢቢሲ በድረገጹ እ.ኤ.አ ኦክቶበር 14 ቀን 2013 እንደዘገበው የማሌዥያ ፍርድ ቤት ከሙስሊም እምነት ውጭ ያሉ እምነቶች “አላህ” የሚለውን ቃል መጠቀም እንደማይችሉ ፍርድ ሰጥቷል፡፡ ለፍርዱ መነሻ የተደረገው አመክንዮ ቃሉ ከሙስሊም እምነት ውጭ ያሉ እምነቶች ጥቅም ላይ ቢውል ሕዝባዊ ሥርዓት አልበኝነት (Public disorder) ስለሚያስከትል ነው፡፡ ቴሌግራፍ የፍ/ቤቱን ተጨማሪ ምክንያት ሲገልጹ “The usage of the word will cause confusion in the community” በማለት ዘግቦታል፡፡ የዚህ ፍርድ የፍትሃዊነት ክርክር እንደተጠበቀ ሆኖ ከዚህ ፍርድ በመነሣት የተነሳንበትን ጉዳይ ከመረመርነው የአንዱን ቤተ እምነት የእምነት መፈጸሚያ ሥርዓትና መሳሪያዎች መጠቀም በኅብረተሰቡ ውስጥ የሚመጣውን መደናገርና በማንነት ፍለጋ (ጥበቃ) ሊከተል የሚችለውን ሁከት ማሰብ አስቸጋሪ አይሆንም፡፡

ሕገ መንግሥቱን መሠረት አድርጎ የወጣው የወንጀል ሕግም በተለይ በአደባባይ የሚፈጸሙ የሃይማኖት ሥርዓትን የሚያውክ፣ ወይም ያስተሃቀረን ሰው የሚቀጣ ድንጋጌ አለው፡፡ ሕጉ በአንቀጽ 792 “የሃይማኖት ሰላምና ስሜት መንካት በሚል ርዕስ” ማንም ሰው አስቦ በአደባባይ፡-

ሀ) የተፈቀደውን ሃይማኖታዊ ሥርዓት፣ ሥነ በዓል ወይም ሃይማኖታዊ ተግባር እንዳይፈፅም የከለከለ፣ ያወከ ወይም ያስተሐቀረ እንደሆነ፤ ወይም

ለ) ለሃይማኖታዊ ሥነሥርዓት ብቻ የሚያገለግለውን ቦታ፣ ሥዕል፣ ወይም ዕቃ ያረከሰ እንደሆነ

ከአንድ ሺሕ ብር በማይበልጥ መቀጮ ወይም ከሁለት ዓመት በማይበልጥ ቀላል እስራት ይቀጣል፡፡” ሲል ይደነግጋል፡፡

በዚህ ድንጋጌ መሠረት ‹‹ንዋየ ቅድሳት›› በ “ለ” ለሃይማኖት ሥነ ሥርዓት ብቻ የሚያገለግል ዕቃ” በሚል የሚሸፈኑ ሲሆን እነዚህን ዕቃዎች ‹ያረከሰ› በሕግ ተጠያቂ እንደሚሆን ይደነግጋል፡፡ ‹ያረከሰ› የሚለው ቃል ለዳኞች ትርጉም የተተወ ቢሆንም ከቃሉ ጥሬ ትርጉም ‹ከዓላማው ውጭ የተጠቀመ፣ ከእምነቱ ሥርዓት ያፈነገጠ ወ.ዘ.ተ» አጠቃቀም እንደሚመለከት መገንዘብ አከራካሪ አይሆንም፡፡ ለአብነት በክርስትና ቤተእምነቶች መካከል ያለውን የዶግማና የቀኖና ልዩነት ላስተዋለ ንዋየ ቅድሳቱን (ከበሮውን፣ ጸናጽልና መቋሚያውን› በታሪክ በትውፊት በቆየ ልማድ ከሚጠቀምበት ቤተ እምነት ዓላማ፣ ሥርዓትና አሠራር ውጭ መጠቀም ተገቢ አለመሆኑን መረዳት ይቻላል፡፡ ድርጊቱ በወንጀል ሕጉ የሚያስቀጣ ከሆነ ለማንኛውም ቤተ-እምነት ተከታይ የሌላውን ሥርዓት፣ ትውፊት እና አምልኮ መሣሪያ የመጠቀሚያ መብት እንደማይኖር መገንዘብ ይቻላል፡፡

ሐመር፡- ቤተ ክርስቲያኗ እንዴት የንዋየ ቅድሳቷን ይዞታ ታስከብር?

አቶ ጌታሁን ወርቁ፡- ከላይ እንደተመለከትነው የቤተክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት በሌሎች ቤተ-እምነቶች እየተጠቀሙ መቀጠል የራሱ የሆነ አሉታዊ ውጤት እንዳለው መገንዘብ ከባድ አይደለም፡፡ የቤተ እምነቷ መብት መነካት፣ አማኙ ወደ አልተፈለገ ሁከትና ክርክር መግባት፣ በቤተ እምነት መካከል የጥላቻ ስሜት መዳበር ወ.ዘ.ተ ያልተፈለጉ ውጤቶች ናቸው፡፡ ይህን ለማራቅ ቤተክርስቲያኗ የራሷን ንዋያተ ቅድሳት መጠበቅ አለባት፡፡ ከቤተክርስቲያኗ የሚጠበቀውን ለመመልከት ያህል ቢያንስ ሦስት መፍትሔዎች መጠቆም ይቻላል፡፡

የመጀመሪያው ቤተክርስቲያኗ የራሷን ንዋየ ቅድሳት መለየት፣ መቁጠርና መመዝገብ ነው፡፡ ንዋያት ቅድሳቱን በተመለከተ ታሪካቸውን፣ አመጣጣቸውን፣ ትርጉማቸውን ወ.ዘ.ተ በማጥናት የመለየትና ከመመዝገብ ጋር ትውፊታቸውን እንዲጠብቁ በመቅረጽ (በፎቶ፣ በቪዲዮ ወ.ዘ.ተ) ማተም እና ማሳወቅ ይጠበቅባታል፡፡ እነዚህን ድርጊቶች መከወኗ በአንድ በኩል በቅርስነት ለማስመዝገብ (በሀገር ውስጥም በዓለም አቀፍ ደረጃም) የሚጠቅማት ሲሆን በተጨማሪ በንብረት ሕግ፣ በቅጅና ተዛማጅ መብቶች ጥበቃ አዋጅ መብቷን ለመጠቀም ያስችላታል፡፡

ሁለተኛው መብት የመጠየቅ ሥራ ነው፡፡ ከላይ እንደተመ ለከትነው አንዳንዶቹ ሕግጋት ያለፈቃድ የሌላ ቤተእምነትን ሥርዓትና የአምልኮ መገልገያ እቃዎችን መጠቀምን በአንድም በሌላ ይከለክላሉ፡፡ እንዲህ ዓይነት ድርጊት የሚፈጽሙ ቤተ እምነቶችን በውይይት፣ ካልሆነም በዓለምአቀፍ የአብያተ ክርስቲያናት ኅብረት በኩል መጠየቅ የማይጎረብጥ መፍትሔ ነው፡፡ ከዚህ መፍትሔ ጎን ለጎን ቤተክርስቲያኗ እንደ አግባብነቱ መብቶቿን ከፖሊስ፣ ከመንግሥት (ከፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር)፣ ከኢትዮጵያ አእምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት ወይም ከፍ/ቤት መጠየቅ ትችላለች፡፡

የመጨረሻው ቤተ ክርስቲያኗ ከመንግሥት ጋር በምታ ደርገው ትብብር የሚገኝ መፍትሔ ነው፡፡ ንዋየ ቅድሳትን በሌላ ቤተ እምነት የመጠቀም ድርጊት በዋናነት ሊቆም የሚችለው መንግሥት በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 27 (5) መሠረት የእምነት ነፃነት አገላለጽ ገደብን በሕግ ወይም በመመሪያ መደንገግ ሲችል ነው፡፡ ቤተክርስቲያኗ በቤተ እምነቶች መካከል በዜማ፣ በንዋየ ቅድሳት፣ ወ.ዘ.ተ ጋር በተያያዘ የሚደረጉ ገደቦች የሀገሪቱን ታሪክ፣ ለዘመናት በኅብረተሰቡና በቤተእምነቶቹ የዳበረውን ልማድ ትውፊትና መቻቻል መሠረት ማድረግ እንደሚገባው በመገንዘብ መንግሥት ገደቦቹን በተግባር እንዲተረጉማቸው መጠየቅ ይገባል፡፡ መመሪያውን ወይም ደንቡን ወይም ሕጉን የማውጣት ግዴታ በዋናነት የመንግሥት ቢሆንም ቤተክርስቲያኗ ሕጉ እንዲወጣ ግፊት ማድረግ፣ ከመንግሥትና ከቤተእምነቶች ጋር መተባበር ይጠበቅበታል፡፡ ይህ ግፊት “ሳይቃጠል በቅጠል” እንዲሉ በቀጣይ በስፋት ሊመጡ የሚችሉና የመቻቻልን መርህ የሚቃረኑ የቤተ- እምነት ድርጊቶች እንዳይኖሩ የራሱን አስተዋጽኦ ያደርጋል፡፡

 

ሐመር-የመዝሙር መገልገያ መሣሪያዎችን ጨምሮ ንዋየ ቅድሳት ከቅርስነት አንጻር ያላቸው ቦታና ጥቅም ምንድነው?

መንግሥቱ ጎበዜ፡- ቅርሶች የሰው ልጆች በየዘመናቸው መንፈሳዊ አእምሮአቸውን ለማርካት፣ መሠረታዊ ኑሯቸውን ለማሟላትና ሥነ ልቦናዊ ፍላጎቶቻቸውን ለማሳካት ሲሉ ለረጅም ዘመናት ከአካባ ቢያቸው ጋር በነበራቸው ግንኙነት ያከናወ ኗቸው የሥራና የፈጠራ ውጤቶች ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል ለሥርዓተ አምልኮ መፈጸሚያ ይጠቀሙባቸው የነበሩ ክቡር ዕቃዎች በዋናነት ይጠቀሳሉ፡፡ እነዚህም የከበሩና ውድ ሀብቶች ባላቸው ታሪካዊና ባህላዊ ጠቀሜታ፣ ሥነ ጥበባዊ ይዘት፣ ያላቸው ፋይዳ፣ ምልክታዊነትና ናሙናነ ታቸው እንዲሁም ዕድሜያቸው ታይቶ ቅርስ ተብለው ለመጠራትና ለመታወቅ የሚችሉት ናቸው፡፡

ከዚህ አንጻር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት፣ መምህራንና ምእመናን በየዘርፉ ሠርተውና ጠብቀው ለትውልድ ያስተላለፏቸው ቅርሶች በዓይነትም በብዛትም የትየለሌ ናቸው፡፡ ከእነዚህም መካከል የያሬዳዊ መዝሙር መሣሪያዎች ይጠቀሳሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ለዘመናት ጠብቃ ያቆየቻቸው እነዚህ ቅርሶች ሥርዓተ አምልኮን በሚገባ ለማከናወን፣ ትምህርተ ሃይማኖትን ለማስተላለፍ፣ መንፈሳዊ በረከት ለማግኘትና ለመሳሰሉት ሃይማኖታዊ አገልግሎት የሚውሉ ናቸው፡፡

ከመንፈሳዊ አገልግሎት ሌላ በቤተ ክርስቲያን የሚገኙ ቅርሶች የታሪክ ምስክር፣ የመረጃ ምንጭ፣ የማንነት መገለጫ፣ ዘርፈ ብዙ ዕውቀት የሚሰጡ ትምህርት ቤቶች፣ የልማት መሠረትና የምጣኔ ሀብት የጀርባ አጥንት፣ ዘመናትን የሚያተሳስሩ ድልድዮች፣ የሩቁን አቅርበው የራቀውን አጉልተው የሚያሳዩ መነጽሮች፣ የራስን ማንነት የሚያሳዩ መስታወቶች፣ በተገቢው ሁኔታ ለመኖር የሚያስችሉ የጥበብ መንገዶች፣ የአገርን መልካም ገጽታ ለመገንባት የሚያግዙ የዲፕሎማሲ አውታሮች፣ በመረጃ ላይ ውሳኔ ለመስጠት የሚያስችሉ ጠቃሚ ሰነዶች እና የሀገር አንድነት ግንባታ የማኅበረሰብ ትስስር መሠረቶች ናቸው፡፡

ሐመር-አንዱ ቤተእምነት የሌላውን ንዋየ ቅድሳት ለአገልግሎቱ መጠቀሙ እንደ ራሱ አድርጎ በአደባባይ የመጠቀሙ ልማድ ከቅርስ ጥበቃ አንጻር የሚያስከትላቸው ችግሮች ካሉ ቢያመለክቱን

መንግሥቱ ጎበዜ፡- በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክርስቲያን ቅርሶች ዙሪያ በርካታ ችግሮች የሚታዩ ሲሆን ከእነዚህም መካከል በቅርስ ባለቤትነትና የይዞታ መብት ላይ ከሌሎች አካላት ጋር የሚያወዛግብና የቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ይጠቀሳሉ፡፡ ከዚህ አንጻር የብራlemena 02 መጻሕፍትና ለአክብሮተ ቁርባን የሚውሉ ንዋያተ ቅድሳት በሌሎች የእምነት ተቋማት አገልግሎት ሲሰጡ ይስተዋላሉ፡፡ በመሠረቱ የቤተ ክርስቲያን ቅርሶች ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ፣ ሥርዓተ እምነትና ትውፊት ጋር ከፍተኛና ቀጥተኛ የሆነ ቁርኝት ስላላቸው በሌሎች ቦታ አገልግሎት ላይ መዋላቸው አግባብ ነው ብዬ አላምንም፡፡ ይህ ሁኔታ በሂደት ቤተ ክርስቲያኗን የባለቤትነት መብቷንና መለያ ምልክቶቿን ሊያሳጣት ይችላል የሚል ስጋት አለኝ፡፡ ጉዳዩ በዚህ ከቀጠለ በእምነት ላይም ግራ መጋባት ሊፈጥር ይችላል፡፡ በመሰረቱ የሌላውን ንብረት ሳያስፈቅዱ መውሰድ መጠቀም ከሥርቆት ተለይቶ አይታይም፡፡

ሐመር- ችግሮች አሉ ካልን መወሰድ ያለባቸው መፍት ሔዎች ምንድናቸው?

መንግሥቱ ጎበዜ፡- የኢ/አ/ተ/ቤ/ክርስቲያን የቅርሶች ባለቤነት መብቷን ለማስከበር በርካታ ሥራዎችን መሥራት ይጠበቅባታል፡፡ ከሁሉ በፊት ግን ቅርሶቿ አሁን ያሉበትን አጠቃላይ ሁኔታ ማጥናትና ለአያያዝ፣ ለቆጠራ፣ ለዕይታ፣ በሚመች መንገድ መገኘታቸውን መለየት ይኖርባታል፡፡ ቅርሶችን በዓይነት፣ በቦታ፣ በይዘት፣ በዕድሜና በመሳሰሉት መስፈርቶች መዝግቦ በመያዝ ለቆጠራ፣ ለቁጥጥርና ለአስተዳደር ሥራ አመቺ እንዲሆኑ ማድረግ ይቻላል፡፡ ቅርሶችን በአግባቡ መዝግቦ የትና በምን ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ለይቶ ማወቅም ከዝርፊያ፣ ከአያያዝ ጉድለቶች የሚፈጠሩ ችግሮችን ለመቅረፍ ትልቅ አስተዋጽኦ ይኖረዋል፡፡ ከዚህ ሌላ ዘመናዊ የምስል ወድምፅ ክምችት ሥርዓት እና አገልግሎት መዘርጋት ቅርሶቹ ተለይተው እንዲታወቁ፣ ሕጋዊ ጥበቃ እንዲደረግላቸውና ተገቢውን እንክብካቤ ለማግኘት ይረዳል፡፡ ከዚህ ሌላ ቤተ ክርስቲያኗ በቅርሶች ጥበቃ ዙሪያ ጠንካራ መመሪያዎችን፣ ደንቦችንና ፖሊሲዎችን ቀርጻና ተቋማትን አጠናክራ መንቀሳቀስ ይጠበቅበታል፡፡

እነዚህና የመሳሰሉ ተግባራት ከተከናወኑ በኋላ የቅርሶቿን የባለቤትነትና የይዞታ መብት ለማስከበር አስፈላጊ የሆነውን ሕጋዊ ክትትልና እርምጃ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ተባብራ ማስኬድ ትችላለች የሚል እምነት አለኝ፡፡

 

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 8 2006 ዓ.ም.

 

ሕገ ወጥ ልመናን የሚያስፋፉ ግለሰቦች ላይ እርምጃ እንዲወሰድባቸው ተጠቆመ፡፡

ጥር 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

በቅርቡ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት በቤተ ክርስቲያን ዕድሳት ስም ፈቃድ ሳይሰጣቸው በየዐደባባዩና በአልባሌ ቦታዎች ልመናን የሚያስፋፉ ሕገ ወጥ ግለሰቦች ላይ እርምጃ እንዲወሰድባቸው ተጠቆመ፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ እንዳስታወቁት በየአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ላይ ለሚደርሰው ተፈጥሮአዊና ሰው ሠራሽ አደጋ እንዲሁም አዲስ ለሚታነፁ አብያተ ክርስቲያናት ለማሠሪያ የሚሆን ገንዘብ ምእመናንንና በጐ አድራጊዎችን ለመጠየቅ የሚያስችል ፳፬ አንቀጾች ያሉት ደንብና መመሪያ ተዘጋጅቷል፡፡ ደንቡና መመሪያው ለሁለት ዓመት የሚያገለግል ሲሆን ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ጥያቄ ሲቀርብ ፈቃድ ይሰጣል፡፡

ይሁንና ይኼን አጋጣሚ በመጠቀም ሕገ ወጥ ልመና የሚፈጽሙ ግለሰቦች ከተሰጠው ፈቃድ ውጪ ጊዜ ያለፈበትን የፈቃድ ደብዳቤ በመያዝ በየዐደባባዩ ሥዕለ አድኅኖ በማስቀመጥና ምንጣፍ በማንጠፍ ይለምናሉ፡፡ ድምፅ ማጉያ በመጠቀም በቤተ ክርስቲያኒቱ ስም መጻሕፍት፣ ካሴትና ሲዲ ግዙ በማለት ምእመናንን ያውካሉ፡፡ እነዚህን ግለሰቦች ሕግ አስከባሪው አካል እርምጃ እንዲወሰድባቸው ለሁሉም ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት ፖሊስ ኮሚሽን በቁጥር 435/11686/06 በቀን 08/02/2006 ዓ.ም የተጻፈ ደብዳቤ ተላልፏል፡፡

የዕቅድና ልማት መምሪያ ሓላፊ የሆኑት አቶ እስክንድር ገ/ክርስቶስ በቁጥር 10273/11686/2005 በቀን 24/11/2005 ለፌደራል ፖሊስ ከሚሽንና ለአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በጻፉት ደብዳቤ ያለ አግባብ በየመንገዱ የሚለምኑ አካላት ሕዝበ ክርስቲያኑን ግራ ከማጋባት በተጨማሪ ለጸጥታ አስከባሪዎች ችግር እየፈጠሩ መሆናቸው ከፖሊስና ከጸጥታ አካላት እየተገለጸ መሆኑን አስታውሰዋል፡፡

የከተማውን ሕዝብ በድምፅ ማጉያ እየረበሹ በቤተ ክርስቲያን ስም የሚነግዱትን ሕገ ወጦች እርምጃ እንዲወሰድባቸው እንጠይቃለን በማለት አቶ እስክንድር ተናግረዋል፡፡

ለቤተ ክርስቲያን ግንባታ ፈቃድ የሚሰጠው ለሁለት ዓመት ሲሆን የሚሰበሰበው ገንዘብ ሕጋዊ በሆነ ደረሰኝ በሞዴል 30 ገቢ ይደረጋል፡፡ የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤትም በተሰጠው ፈቃድ መሠረት የተሰበሰበው ገንዘብ በትክክል አገልግሎት ላይ መዋሉን እየተቆጣጠረ እንዲሠራና የቤተ ክርስቲያኑ ሥራ ሲጠናቀቅ ለዕቅድና ልማት መምሪያው እንደሚያሳውቅ ሕገ ደንቡ እንደሚገልጽ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በጎዳና ላይ ልመና እንዲካሔድ ቤተ ክርስቲያን ፈቃድ አትሰጥም፤ ሕጋዊ ባልሆነ መንገድ ሥዕለ ቅዱሳንና ልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳት በመያዝ በየጐዳናው የሚለምኑ ወገ ኖችን በሕግ ለመጠየቅ ከፌደራልና ከክልል ፖሊስ ጋር እየሠራን እንገኛለን ሲሉ አቶ እስክንድር አመልክተዋል፡፡

በልመና ላይ የተሠማሩት ካህናት ሳይሆኑ ካህን መስለው የሚንቀሳቀሱ ግለሰቦች መሆናቸውን የጠቀሱት አቶ እስክንድር ወደፊት የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራዎችን ለመሥራት መታቀዱን ገልጠዋል፡፡

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 21ኛ ዓመት ቁጥር 8 2006 ዓ.ም.

 

limena

የጎዳና ላይ ልመና የቤተ ክርስቲያን ገጽታ የጠቆረበት ሕገ ወጥ ተግባር

 

ዲ/ን ማለደ ዋስይሁን

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የነበራትን መተዳደሪያ በደርግ ዘመን ሙሉ ለሙሉ ማለት በሚያስችል ደረጃ ማጣቷ ይታወቃል፡፡ ይህ በመሆኑ ለብዙ ደካማ ገጽታዎች መፈጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ አጥቢያዎች ለካህናት ደሞዝ፣ ለንዋየ limenaቅድሳት መግዣ፣ በአጠቃላይ ለአገልግሎቱ መስፋትና ማደግ የሚያስፈልገውን መተዳደሪያ ገንዘብ፣ ቁስ፣ ጉልበት ለማግኘት ከምእመናን ገንዘብ መለመን ግድ ሆኖባቸው ቆይቷል፡፡

 

ቤተክርስቲያን አስቀድሞም መተዳደሪያዋን የምታገኘው ቤታቸው ከሆነችላቸው ከተገልጋዮቹ ካህናትና ምእመናን ነው፡፡ አማኞች ዐሥራት በኩራት ማውጣት ሃይማኖታዊ ግዴታቸው ነው፡፡ ይሁን እንጂ በዚያ ደረጃ የምእመናን ተሳትፎ ባልተሟላበት ሁኔታ አገልግሎቱ እንዲቀጥል የሚፈልጉ የቤተክርስቲያን ቤተሰቦች ገንዘብ በመስጠት በመሰብሰብ የአጥቢያቸውን አገልግሎት የሰመረ ያደርጋሉ፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን በማስፋት፣ በማሳደግ ረገድ ነገሥታቱን ጨምሮ በሀገሪቱ ትልቅ ክብርና ስም ከነበራቸው ልጆቿ ጀምሮ የሚበረከትላትን መባዕ ማለትም ገንዘብ፣ መሬት፣ ወርቅ፣ ብር ወዘተ ስትጠቀም ኖራለች፡፡ በኋላ ዘውዳዊ ሥርዓቱ እንዲጠፋ ሲደረግ ቤተክርስቲያን መተዳደሪያዋ ሁሉ በመወረሱ የካህናቱ አገልግሎት ፈተና አጋጥሞታል፡፡ ስለዚህ መውጫ መንገድ ነው የተባለው የሰበካ ጉባኤ አደረጃጀት እንደ አንድ መፍትሔ የደረሰላት ቢሆንም አሁንም ግን በሚፈ ለገው ደረጃ አገልግሎቷን መደገፍ የሚያስችል በቂ ገቢ ባለመኖሩ ችግሩ እንዳለ ነው፡፡

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የበለጠ እየተጎዱ ያሉት ደግሞ የገጠር አብያተ ክርስቲ ያናት ናቸው፡፡ ቤተክርስቲያን የምትሰ በስበውን ገንዘብ አሰባሰብና ሥርጭቱ አጠቃቀሙ የገንዘብ አስተዳደር ሥርዓቱ መሻሻል ያለበት ቢሆንም ባለው ደረጃም ቢሆን በችግር ላይ ያሉ አጥቢያዎች መኖራቸው ይታወቃል፡፡ እነዚህ ችግረኛ ገዳማትና አድባራት የሚያስፈልጋቸውን ገቢ ለማግኘት በዓመታዊ በዓላት ከምእመናን የሚያገኙት ገቢ ብቻውን በቂ ባለመሆኑ ልመና ለማድረግ እየተገደዱ ቆይተዋል፡፡ ልመናውንም በተለያዩ አጥቢያዎች በማድረግ የተወሰነ ገቢ አግኝቶ አገልግሎታቸውን ለማስቀጠል እየተንገዳገዱ ነው፡፡

 

ይሔ በእንዲህ እያለ በተቸገሩ አብያተ ክርስቲያናት ስም በጎዳና ላይ ልመና የማድረግ አካሔድ እየሰፋና እያደገ መምጣቱ ይታያል፡፡ ይሔ አካሔድ እጅግ አደገኛና የቤተክርስቲያንንም ገጽታ እየጎዳ ያለ ሕገወጥ አካሔድ ነው፡፡

በቤተክርስቲያን ስም የሚፈጸም የጎዳና ላይ ልመና ገጽታ ሲገመገም አብዛኛው ስምሪት በአዲስ አበባና በሌሎች ዋና ዋና ከተሞች የሚደረግ ነው፡፡ የሚደረጉት የጎዳና ላይ ልመናዎች በዓላት በሆኑ ጊዜያትም ከበዓላትም ውጪ የሚደረጉ ናቸው፡፡ የሚደረጉት ልመናዎች ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ውጪ በተገኙ ተገቢ ባልሆኑ ጎዳናዎች ላይ ነው፡፡ የሚደረጉትን የጎዳና ላይ ልመናዎች የሚያከናውኑት ካህናት የሚመመስሉም የማይመስሉም ሰዎች ናቸው፡፡ ልመናዎቹ የሚደረጉት በቡድን ወይም በተናጠል ነው፡፡ የጎዳና ላይ ልመናዎች ሲፈፀሙ ጥላ ተዘርግቶ የቅዱሳን ሥዕላት ተይዘው ነው፡፡ እነዚህ ቅዱሳት ሥዕላት በክብር የተያዙ ያልተያዙም ናቸው፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመናዎች ሕገ ወጥነት

የጎዳና ላይ ልመናዎች ሕገ ወጥ የሚሆኑባቸው ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡

1/ የቤተ ክርስቲያኒቱን ፈቃድ ያልያዙ የጎዳና ላይ ለማኞች


በቅዱሳን እና በአብያተክርስቲያናት ስም የሚለምኑ የተወሰኑ ግለሰቦችና ቡድኖች ሁሉም ሕጋዊ የቤተክርስቲያኒቱ ፈቃድ የሌላቸው ናቸው፡፡ እነዚህ ወገኖች ከአጥቢያ ቤተክርስቲያናቸው፣ ከወረዳ ቤተክህነት፣ ከሀገረ ስብከት፣ ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፈ ምንም የፈቃድ ደብዳቤ ሳይዙ በሕገ ወጥነት በማጭበርበር የሚሰ ለፉም ናቸው፡፡ እነዚህ አካላት የራሳቸውን የግል ወይም የቡድን ጥቅም ለማርካት ወይም የቤተክርስቲያንን ስም ለማጉደፍ በድፍረት የተሰለፉ ናቸው፡፡
እነዚህ ወገኖች ምእመናን የቅዱሳን ስም ሲጠራ ራርተው ይሰጣሉ በሚል እምነት በድፍረት ገንዘባቸውን ለመሰ ብሰብ የሚሹ ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት የትኛውም ሕግ በማይደግፋቸው አግባብ በማን አለብኝነት የዋሕ ወገኖችን እያታ ለሉ ያሉ ናቸው፡፡

2/ የተጭበረበሩ ደብዳቤዎች የያዙ የጎዳና ላይ ልመናዎች

አንዳንዶች ደግሞ ሕጋዊ ለማኝ ለመምሰል ከአጥቢያ የተጻፉ የሚመስሉ ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፉ በሚመስሉ ደብዳቤዎችን በጎዳና ላይ ደርድረው የሚለምኑ ናቸው፡፡ እነዚህ ደብዳቤዎች ሕጋዊ ማኅተም የሌላቸው ወይም ማኅተምን ቢኖራቸውም በማጭበርበር በማስመሰል የተዘጋጁ ወይም ከዚህ ቀደም ተጽፈው ቀንና ቁጥራቸው ላይ ለውጥ በማድረግ አመሳስለው የሚይዟቸው ናቸው፡፡ በዚህም ምክንያት ሕገ ወጥ ናቸው፡፡

3/ በመመሳጠር የተዘጋጁ ደብዳቤዎችን መጠቀም

በአንዳንድ አጥቢያዎች ያሉ የሰበካ ጉባኤ ሓላፊዎች ወይም ሰነዶችን ሕጋዊ የማድረግ ዕድል ያላቸው ግለሰቦች ከአጠቃላዩ የሰበካ ጉባኤ፣ ከማኅበረ ካህናቱና ከምእመናን ስምምነት ሳይደ ረስባቸው ቤተክርስቲያኑ በጎዳና ላይ እንዲለምኑለት ለተወሰኑ በስም ለተጠቀሱ ግለሰቦች ፈቃድ የሰጠ በማስ መሰል በሚወጡ ደብዳቤዎች የሚፈጸሙ የጎዳና ላይ ልመናዎች ናቸው፡፡ እነዚህ ደብዳቤዎችን ይዞ አንድ መርማሪ በአጥቢያው ያሉ የሁሉንም የሰበካ ጉባኤ አባላት ወይም የልማት ኮሚቴ ዎች ስምምነት ያገኘ ወይም ያላገኘ ስለመሆኑ ማስረጃ ቢፈልግ በቀላሉ እንዲህ መሰል ደብዳቤዎች የሚወጡበትን የሙስና መንገድ ሊደርስበት ይችላል፡፡

4/ ከያዟቸው ደብዳቤዎች የፈቃድ ሐሳብ በወጣ መልኩ ልመና ማድረግ

ከየትኛውም የቤተክህነት አካል በሕጋ ዊነት የሚወጡ ደብዳቤዎች የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትን የሚፈጽሙ ወገኖች የቤተክርስቲያንን ወይም የቅዱሳንን ስም እየጠሩ ሥዕል ይዘው በጎዳና ላይ እንዲለምኑ ፈቃድ አይሰጥም፡፡ በአብዛኞቹ የምእመናን ድጋፍ እንዲጠይቁ ፈቃድ የሚሰጣቸው አገልጋዮች ከአጥቢያ ቤተክርስቲያን ውጪ እንዲህ ባለ ግብር እንዲገኙ አያዝም፡፡ አብዛኞቹ በተለይም ከጠቅላይ ቤተክህነት የተጻፉ ደብዳቤዎችን ስናይ ልመና እንዲፈጸም የሚያዙት ልመናው ከሚደረግበት አጥቢያ ጋር በመነጋገርና በመስማማት በዚያው በአጥቢያው ውስጥ ነው፡፡ ስለዚህ ከአጥቢያ ውጪ የሚለምኑ ወገኖች ከያዙት የፈቃድ ደብዳቤ ሐሳብ ውጪ የሚራመዱ ከሆነ ሕገ ወጥ መሆናቸው አይቀሬ ነው፡፡

5/ ገንዘብ መቀበያ ደረሰኝ የሌላቸው የጎዳና ላይ ለማኞች

በጎዳና ላይ የሚለምኑ ሁሉም ማለት ይቻላል ግለሰቦችና ቡድኖች በየትኛውም መጠን ለሚቀርብላቸው ምጽዋት የሚቀ በሉበት ሕጋዊ ደረሰኝ የላቸውም፡፡ ስለዚህ በአድባራትና በገዳማት የሚለምኑት ወገኖች የሰበሰቡት የገንዘብ መጠን ሊታወቅ አይችልም ማለት ነው፡፡ በእርግጠኝነት መናገር የሚቻለው ግን ቤተክርስቲያን እውነተኛ ፈቃድ ስትሰጥ በሕጋዊ ደረሰኝ እንዲሰበሰብ እንጂ ከዚያ በመለስ ምንም ያህል መጠን ያለው ገንዘብ ከምእመናን ቢሰበሰብ ለተለመነለት አጥቢያ በተሰበሰበው መጠን መድረሱን ወይም አለመድረሱን ከዚያም አልፎ የግለሰቦቹ መጠቀሚያ ሆኖ ቀርቶም እንደሆነ በውል ማወቅ አያስችልም፡፡

የዚህ ችግር መንሥኤ ምንድ ነው?

1/ የቤተክርስቲያን ቁጥጥር ልል መሆን


ቤተክርስቲያናችን የራሷ አካል በሆኑ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ስም የሚፈጸሙ ይሔን መሰል የማጭበርበር ድርጊቶች ለመቆጣጠር የዘረጋችው ጊዜያዊ ወይም ቋሚ አሠራር የለም፡፡ ቢኖርም በንቃት አልተንቀሳቀሰም፡፡ ችግሩን በቀላሉ መቅጨት የሚቻል ቢሆንም እየተባበሰ መሔዱ የአሠራር ድክመቱን ያሳያል፡፡ ቤተክርስቲያን ይሔንን ችግር መቆጣጠር የሚኖርባት ለቤተክርስ ቲያኒቱ ክብር ብቻ ሳይሆን በቤተክር ስቲያን ስም የሕዝብ ገንዘብ በግለሰቦች እየተመዘበረ በመምጣቱም ጭምር ነው፡፡ በሌላም በኩል ክርስቲያኖች ቤተክርስቲያንን ለመደገፍ የሚሔዱ በትን ፈቃድ በየጎዳናው በመጥለፍ በቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ጸሎት አድርሰው ተባርከው መባቸውን በሥርዓት አስገ ብተው እንዳይሔዱ የሚያደርግ ልማድ ፈጥሯል፡፡ ቤተክርስቲያን በየጎዳናው ላይ ሁሉ እንዳለች እያሰቡ በኪሳቸው ያለውን ገንዘብ እየሰጡ እንዲያልፉ ሆነዋል፡፡ ስለዚህ የዚህ ሁሉ ተጎጂ ራሷ ቤተ ክርስቲያን መሆኗን አውቆ ልል የሆነውን የቁጥጥር ሥርዓት ጠበቅ ማድረግ፣ ምክር መስጠት፣ ካልሆነም ከሕግ አስከባ ሪዎች ጋር በመተባበርም እርምጃ እንዲወሰድ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡

2/ ሙስና

ቤተክርስቲያን እንዲህ መሰል ጥፋቶች በስሟ የሚበቅሉት የግልጽና ስውር የሙስና አሠራሮች በመኖራቸው ነው፡፡ የጎዳና ላይ ልመናዎች እንዲከናወኑ ሕጋዊ ሽፋን ለመስጠት የተሰለፉ በየደረጃው ያሉ የቤተክርስቲያን አስተዳደር ሹማም ንትም እንዳሉ ይጠረጠራሉ፡፡ ለአንድ ቤተክርስቲያን የሚለመንበት በቂ ምክንያት ሳይኖር ወይም ለአንድ ለተወሰነ ጊዜ ችግር የሆነን ነገር ሁሌ እንዳለ በማስመሰል ፈቃድ በመስጠት እንዲለመን የሚያደርጉ ወገኖች አሉ፡፡ ለዚህም ማሳያ የሚሆነው አንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ሕንፃ ቤተክርስቲያን በማሠራት ስም ፕሮጀክቱን በማራዘም ለረጅም ጊዜ እንዲለመንበት በማድረግ ወይም ካለቀም በኋላ ያለ በማስመሰል ልመናዎች እንዲ ቀጥሉ የማድረግ አሠራር አለ፡፡ በዚህም ቢያንስ ዘረፋ ወይም ጥቅማ ጥቅም ለማግኘት የሚሠሩ ወገኖች አሉ፡፡

3/ ሕዝበ ክርስቲያኑ በየዋህነት በማመን መመጽወቱ

ክርስቲያኖች ለለመነ፣ ለጠየቀ መስጠት አግባብና ክርስቲያናዊ ሥነምግባር መሆኑን ስለሚያምኑ በቅዱሳን ስም ተጠርቶ የቅዱሳን ሥዕል ተይዞ ሲለመን ማለፍ ይከብዳቸዋል፡፡ ሌላው ቀርቶ እንዲለምኑበት የተሰጣቸውን የፈቃድ ወረቀት ሐሳብ ወይም የሚቀበሉበትን ሕጋዊ ደረሰኝ የማይጠይቁ ብዙዎች ናቸው፡፡ በሌላም በኩል ለሚሰጡት ሽርፍራፊ ሳንቲም ደረሰኝ መጠየቅ አስፈላጊ ነው ብለው አያምኑም፡፡ ስለዚህም ለእነዚህ ሕገወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች መበራከት የምእመናንንም ድርሻ አለበት፡፡

በእርግጥ አንዳንድ ክርስቲያኖች የተጎዱ አብያተ ክርስቲያናትን ለመርዳት በሚያ ስችል መልክ ተሰባስበው ቀጣይነት ያለው ሕጋዊነትና ሥርዓት ያለው ድጋፍ ችግረኛ ለሆኑ አብያተ ክርስቲ ያናት መስጠት በመጀመራቸው የችግሩ ስፋት የሚቀንስበት ዕድል ሊኖር ይችላል፡፡ የሆነ ሆኖ ግን ምእመናን የጎዳና ላይ ልመና የቤተክርስቲያንን የሃይማኖ ታቸውን ገጽታ የሚያበላሽና ሥርዓት ያጣ ስርቆትንም የሚያባብስ መሆኑን ተረድተው ከዚህ መቆጠብ ካልቻሉ ገንዘባ ቸውን አነሰም በዛም በግልም ይሁን በቡድን ለቤተክርስቲያን በሕጋዊ መንገድ ገቢ ማድረግ እስካልቻሉ ድረስ ችግሩ መቀጠሉ የማይቀር ይሆናል፡፡

limena1የጎዳና ላይ ልመና የሚያስከትለው ችግር

1/ የቤተ ክርስቲያንን ገጽታ ማጥፋቱ

ይህቺ ቅድስትና በቸር ጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሠረተች ቤተክር ስቲያን ክብር ያላት ናት፡፡ ለብዙዎች የእግዚአብሔርን ጸጋ የምታሰጥ ባዕለጸጋ ቤተክርስቲያን ነች፡፡ ‹‹እናንተን እንጂ ያላችሁን አልፈልግም›› እያለች ስታስ ተምር የኖረች ቤተክርስቲያን ነች፡፡ ለምስኪኖች፣ ለተቸገሩ፣ ለደሀ አደጎች ለእጓለ ማውታ ሁሉ የምትደርስ ቤተ ክርስቲያን ነች፡፡ ‹‹ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው›› እያለች የምታሰተምር ቤተክርስቲያን ነች፡፡

 

ቤተክርስቲያን ከምእመናን ዐሥራት በኩራታቸውን ተቀብላ የእግዚአብሔርን ገንዘብ የምታስተዳድር እንጂ ዋነኛ ተግባሯ ሙዳየ ምጽዋት መሰብሰብ አይደለም፡፡ ስብከተ ወንጌልን የማንገሥ እንጂ ማዕድን የማገልገል ፍላጎት ያላት አይደለችም፡፡ ማድረግ ሲገባት ደግሞ በሥርዓትና በታማኝነት የምትፈጽምበት አሠራር አላት፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመናዎች ግን የቤተ ክርስቲያን መገለጫ ሆነው ተስለዋል፡፡ ማንም ጥላ ይዞ የሚለምን፣ ሥዕል ያንጠለጠለ፣ እጁን የዘረጋ ሁሉ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መገለጫ እየሆነ ነው፡፡ ሌሎች ዐበይት ቤተክርስቲያናዊ ተግባራትን ባከናወንን መጠን ክርስቲ ያኖች ሳይጠይቁ የሚያደርጉትን ነገር እኛ ግን ዐበይት ተግባሮቻችንን ቸል ብለን የጎዳና ላይ ልመና ዋነኛ የሥራ ሂደታችን ያደረግነው ያስመስላል፡፡

 

ስለዚህ ነው ቤተክርስቲያናችን የጎዳና ላይ ልመናዎችና መሰል ተገቢ ያልሆኑ ተግባራት ለቤተክርስቲያኒቱ ታሪካዊነት የአርአያነት ሚና የታማኝነት ደረጃ ወዘተን የሚያኮስሱ ይሆናሉ፡፡

2/ የቅዱሳንን ክብር የሚነካ ይሆናል


ቅዱሳንን እግዚአብሔር ያከበራቸው ናቸው፡፡ ሰዎች ክብርን የሚሰጧቸው ወይም የሚቀንሱባቸው አይደሉም፡፡ እነርሱን በማክበር ግን ቤተክርስቲያንና ልጆቿ በረከት ያገኛሉ፤ እግዚአብሔርን ደስ ያሰኛሉ፡፡

ነገር ግን በጎዳና ላይ ልመናዎች የምናየው ነገር የቅዱሳን መላእክትን የቅዱሳን ሰዎችን ስም ጠርተው ሥዕል ይዘው የሚለምኑ ወገኖች በተለያዩ አካሔዶቻቸው ቅዱሳንን ያዋርዳሉ፡፡ በስማቸው ሕገ ወጥ ሥራ የስርቆት ተግባር መፈጸማቸው ጽርፈት ነው፡፡ ንዋየ ቅድሳት ከሥርዓት ውጪ በተያዙ መጠን ይጉላላሉ፡፡ ሥዕሎ ቻቸውን ይዘው አጓጉል ቦታዎች ቆመው መታየታቸው ጽርፈት ነው፡፡ ለቅዱሳት ሥዕላት ክብር በሚነፍግ መልኩ በአያያዝ የተጎዱ በሥርዓት ያልተሠሩ ፀሐይና ዝናብ የተፈራረቀባቸው ሥዕላትን ይዞ መቆም ለሃይማኖት ቤተሰቡም ሆነ ለሚከበሩት ቅዱሳን ክብር አለመስጠት ነው፡፡

3/ የክህነትን ክብር የሚነካ ነው

ብዙ ጊዜ በጎዳና ልመና ላይ የተሰማሩ ግለሰቦችና ቡድኖች ካህናት የሆኑም ያልሆኑም ወገኖች ናቸው፡፡ ነገር ግን አርአያ ክህነትን ተላብሰው ስለሚታዩ ሁልጊዜም በጎዳና ላይ ልመና የሚታዩት ካህናት ናቸው ብሎ ሰዎች እንዲያምኑ እያደረገ ነው፡፡ ካህናት የቤተክርስቲያን መልክና ምልክቶች ናቸው፡፡ በእነርሱ ውስጥ የምትከብረው ወይም ገጽታዋ የሚደበዝዘው የቤተክርስቲያን ነው፡፡ የመላው ካህናት ገጽታ ነው፡፡ ካህናትን ዘወትር የሚሰጡ ሳይሆን የሚቀበሉ፣ የሚመጸውቱ ሳይሆን የሚመጸወቱ አስመስሎ ያቀርባል፡፡ ከዚያም አልፎ በክህነት የሚፈጸመው ዋነኛ ተግባር ልመና እንደሆነ አድርገው በክህነት የሚያምኑም ሆነ የማያምኑ ወገኖች እንዲያስቡ ያደርጋቸዋል፡፡

4/ የሀገርን ገጽታ ይጎዳል


ቤተክርስቲያን በሙዳየ ምጽዋት የምእ መናንን የለጋስነት ስጦታ መሰብሰቧ፣ ዐሥራት በኩራትን መሰብሰቧ በሃይማኖቱ ሕግና ሥርዓት የታወቀ መንፈሳዊ ተግባሯ ነው፡፡ ስለዚህ የትኛውም ተመልካች ቤተክርስቲያን በአጥቢያዋ ካሉ ምእመናን ዐሥራት በኩራት ምጽዋትን ሰበሰበች ብሎ የሚነቅፋት አይኖርም፡፡ ነገር ግን በተገቢው መልኩ በተገቢው ቦታና በሕጋዊ መልክ ካልሆነ ይነቅፋል፡፡

 

የጎዳና ላይ ልመና ግን ከቤተክርስቲያን አልፎ ለሀገርም ገጽታን የሚያጎድፍ በሀገር ውስጥና በውጪ ሀገር ጎብኚዎችም ዘንድ ደስ የማያሰኝ በመሆኑ ለሀገራችን አይጠቅምም፡፡ ሀገር ልመናን በመቀነስ ሥራና ሠራተኛነትን ለማስፋፋት ጥረት ማድረግ የሚገባትም ለሰሚና ተመልካች ሳቢ ሁኔታን ለመፍጠር ነው፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ግን ከአጥቢያ ቤተክር ስቲያን ግቢ ውጪ ወጥቶ ከዕለታዊ ችግራቸው የተነሣ ሕዝብ ባለበት ዐደባባይ ከሚለምኑ ነዳያን ጎን ተሰልፎ ከአማ ኙም ከኢአማኒውም ለቤተክርስቲያን ንዋየ ቅድሳት መግዣ፣ ለሕንፃዋ ማሠሪያ ገንዘብ ለመለመን መሞከር ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለው ነው፡፡

 

5/ የአጥቢያና የሀገረ ስብከቶችን ክብር ይነካል

 

የሚለመንላቸው አጥቢያዎች ስማቸው አለአግባብ በየጎዳናው ለረጅም ጊዜ መነሣቱ ክብር አይሆንላቸውም፡፡ በስማቸው ሕገ ወጥ ተግባር ሲከናወን ሲታይ አጥቢ ያውን ለሚያውቁ ምእመናንና ካህናት የሚያምም ይሆናል፡፡ ለአጥቢያው ብቻ ሳይሆን በዚህ ሀገረ ስብከት በዚህ ወረዳ ለሚገኘው ተብሎ ስለሚለመን ለዚያ ሁሉ ወገን የሚያምም ይሆናል፡፡

6/ ሥራ ፈትነትን ያበረታታል

ቤተክርስቲያን ያላት ትምህርት ‹‹ሊሠራ የማይወድ አይብላ›› የሚል ነው፡፡ ነገር ግን ሕገ ወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች በአቋራጭ መክበርን ያለሥራ ያለድካም መጠቀምን የሚያመጡ ናቸው፡፡ በመሆኑም ጉዳቱ ለዜጎች ሁሉ ነው፡፡ የሚሠራውን ተስፋ የሚያስቆርጥና ተመሳሳይ የአቋራጭ መንገዶችን እየፈለገ ምርታማ ባልሆኑ ሥራዎች በመሰማራት ከዚያም አልፎ በሥራ ፈትነት በሕገ ወጥ ተግባራት ውስጥ እንዲገባ ያበረታታሉ፡፡ የቤተክርስቲያንን አርአ ያነትም ያጎድፋል፡፡

7/ ለቤተ ክርስቲያን ቤተሰቦች ያሳፍራል

ቤተ ክርስቲያንና ቤተሰቦቿ ከሥራ ይልቅ ልመናን የሚመርጡ ስለሚያስ መስል በሌሎች ወገኖች በሚደርስብን ትችት ምእመናን ይሸማቀቃሉ፡፡ ምእመናን የሚፈለገውን ያህል በማይ ወስኑባት በማይመክሩባት ቤተክርስቲያን ውስጥ ይሔ መሆኑ ደግሞ ምእመናንን የሚያስቆጣበት ደረጃ ላይ ያደርሳል፡፡ ካህናት አመኔታ እንዲያጡ በር ይከፍታል፡፡

8/ ምእመናንን ያዘናጋል

ምእመናን ምጽዋትና ዐሥራት በኩራትን ለይተው ማድረግ እንደሚገባቸው በውል ትምህርት በበቂ ባልተሰጠበት ሁኔታ ውስጥ እንዲህ ያሉ ሕገ ወጥ የጎዳና ላይ ልመናዎች ሲበራከቱ የዋህ ምእመናን ቤተክርስቲያንን ያገኙ ስለሚመስላቸው ዐሥራት በኩራታቸውን በአግባቡ ለማውጣት ይቸገራሉ፡፡ በጥቂቱ በመርካት ከአጥቢያ ቤተክርስቲያን በአፍአ ይቀራሉ፡፡ ምጽዋታቸውንም በአግባቡ ሊሰጡ የሚችሉበት ዕድል አይኖራቸውም፡፡

9/ ሌሎች ችግሮች

የጎዳና ላይ ልመናዎች የሚያስከትሉት ሌላው ጉዳት ከሚለምኑት ሰዎች ማንነትና ተግባር ጋር በተያያዘ የሚያስ ከትለው ችግር ነው፡፡ በልመና ላይ የዋሉ ሰዎች የውሏቸው መጨረሻ የት ነው? የት ያመሻሉ? የት ያድራሉ? ከእነማን ጋር ይውላሉ? የሚለው ሌላው አሳሳቢ ነገር ነው፡፡ ያለደረሰኝ በሕገ ወጥ መልክ የተሰበሰበውን ገንዘብ ይዘው በየመጠጥ ቤቶች ተሰይመው የሚያመሹ በርካቶች ናቸው፡፡ ተደራ ጅተው፣ ማደሪያ ተከራይተው በዓላት ባሉበት የአዲስ አበባ ጎዳናዎች ሁሉ ቆመው ውለው ማታ ተሰባስበው ያገኙትን ገንዘብ ተካፍለው የሚበተኑ ቡድኖች አሉ፡፡ የቡድኖቹ አስተባባሪዎችም አሉ፡፡ ያዘጋጁትን የፈቃድ ደብዳቤ የሚመስል ማጭበርበሪያ ይዘው የሚለምኑ ሰዎችን አደራጅተው ደብዳቤውን ፎቶ ኮፒ አድርገው የሚያሰማሩ ከዚያም ከየለማኞቹ የድርሻቸውን ተቀብለው ለቀጣዩ ዙር ልመና ተቀጣጥረው የሚበታተኑ ሁሉ አሉ፡፡ ይህ ሁሉ የሚፈጸመው በቤተክር ስቲያኒቱ ስም መሆኑ ሲታሰብ የሚያሳዝን ነው፡፡

 

ሌላው አሳሳቢው ነገር በየቦታው በሚታዩ ልመናዎች የሚያስተባብሩት ወይም የሚለምኑት ሰዎች ተጠሪነታቸው ለጥቂትና ተመሳሳይ ሰዎች የመሆኑ ነገር ነው፡፡ እነዚህ ግለሰቦች የፈቃድ ደብዳቤ ብለው በሚይዙት ላይ በልዩ ልዩ ሥፍራዎች ያሉ ሰዎች በያዟቸው የፈቃድ ደብዳቤዎች ላይ በአንድም በሌላ መንገድ ተጠቅሰዋል፡፡ እነዚህ ግለሰቦች በተለይም የአዲስ አበባን የጎዳና ላይ ልመናዎች ገዢ ሆነው የተቀመጡ ሰዎች ናቸው፡፡ ምናልባትም ሕጋዊ መልክ እንዲኖራቸው ከቤተክህነቱ አንዳንድ ግለሰቦች ጋር የጥቅም ግንኙነት ያላቸውም ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ስለዚህ የሚለምኑት ከሚያስለምኑ ሕጋዊ ነን ከሚሉ ገዢዎቻቸው ጋር ተቀናጅተው የሚፈጽሙት ጥፋት ነው፡፡

 

ሌላው አሳሳቢው ነገር የሀገሪቱን ሕግ የሚያስከብሩ ደንብ አስከባሪዎችና ፖሊስ ቤተክርስቲያንን እና ክርስቲያኑን ማኅበረሰብ በመፍራት ለመጠየቅ የሚደፍ ሯቸው አለመሆናቸው ነው፡፡ በፊታቸው የሚዘረጓቸውን ማስፈራሪያ ወረቀቶች አይተው ወይም የሚሰጣቸውን መጽዋች ፈርተው ወይም አይመለከተንም በማለት ወዘተ የሕግ አስከባሪዎች ስለሚያልፏቸው ጠያቂ እንደሌላቸው በማሰብ እነዚህ በቤተክርስቲያን ስም በመለመን የብዙዎችን ገንዘብ አለአግባብ እየዘረፉ ይገኛሉ፡፡

መፍትሔ

ቤተክርስቲያን በስሟ የሚፈጸሙ ልመናዎችን ለማስቆም መትጋት ያለባት አሁን ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ሙስናን ከቤተክርስቲያን ለማጥፋት እሠራለሁ ብሎ እየተጋ ባለበት በዚህ ዘመን ከእነዚህ ጥቃቅን ቀበሮዎች ጀምሮ ወደ ታላላቆቹ መገስገስ ይገባዋል፡፡ ታላላቆቹ ሙሰኞች በእነዚህ ጥቃቅን መሠረቶች ላይ የቆሙ ናቸው፡፡

 

ቤተክርስቲያን እንዲህ ያሉ ሕገ ወጦችን ማጥፋት የሚገባት የቅድስና ባለቤት በሆነችው ቤተክርስቲያን ስም የሚፈጸም የስርቆት ተግባር ኃጢአት በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ በልመና ላይ የተሰማሩትን ጨምሮ በዚሁ የጥፋት መንገድ ለመሳተፍ እየተንደረደሩ ያሉትን ለመታደግ ይረዳታል፡፡ በሌላ መልኩ ምእመናን ገንዘባቸውን በቤተክርስቲያን ስም እንዳይዘረፉ ከመጠበቅ አንጻር ነው፡፡ በሌላ መልኩ ደግሞ የቤተክርስቲያንን ገጽታ እንዳይጎድፍ ከመጠበቅ አንጻር ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በቤተክርስቲያኒቱ መሠልጠን ያለበት ሕጋዊ አሠራር ብቻ መሆኑን አስረግጦ ለማስረዳት ለማሳየት ይጠቅማል፡፡

 

ስለዚህም በቅድሚያ በቤተክርስቲያን ስም በጎዳና ላይ መለመን ከብዙ ነገሮች አንጻር ምን ያህል አግባብ ነው የሚለውን በውል በማጤን ግልጽ አቋም መያዝ ከቤተክርስቲያን ይጠበቃል፡፡ ከዚህ አስከትሎም አሁን በጎዳና ላይ እየተፈጸሙ ያሉ ልመናዎችን ሕጋዊነት መመርመር ያስፈልጋል፡፡ ለጎዳና ላይ ልመናዎች ፈቃድ የሚሰጠው ማን ነው? ፈቃዱን ለእነማን ሰጠ? ለምን ዓላማ ሰጠ? ተግባሩ ፈቃድ በተሰጠበት አግባብ ተፈጽሟል? ፈቃዱ እስከ መቼ የሚሠራ ነው? በፈቃዱ የተሰበሰበው ገንዘብ ለታሰበው ዓላማ እየዋለ ነው? በትክክል የፈቃድ ደብዳቤው ወጣ ከተባለበት መዝገብ ቤት ወጥቷል? ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎችን አንሥቶ የቤተክርስቲያኒቱ ታማኝ የሕግ አስከባሪ አካላት ከተለያዩ የሚመለከታቸው አካላት ጋር መመርመርና እርምጃ ማስወሰድ አለባቸው፡፡

ከቤተክርስቲያን አስተዳደር ሌላ ግን ከመንግሥት አካላት ጋር ተባብሮ ቢያንስ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ሌሎች ቁጭቱ ያላቸው አገልጋዮችም የእነዚህን የጎዳና ላይ ልመናዎች ለማስቀረትና የቤተክርስቲያናችንን ክብር ማስጠበቅ አለብን፡፡

መሰናክል ያለበትን ገንዘብ የሚሰበስብ ሰው ገንዘብ በመሰብሰቡ ኃጢአት አድርጓልና እንዳይሰበስብ ይገባዋል/ፍት.ነገ. አንቀ.16 ቁ.648/

ዳግመኛም ገንዘብ እያለው ምጽዋት ለሚቀበል ሰው ወዮለት አለ፤ ራሱን መርዳት እየተቻለው ከሌሎች መቀበልን የሚወድ ሰው ወዮለት እንዲህ ያለውን ግን በፍርድ ቀን እግዚአብሔር ይመረምረውል››/ፍት.ነገ.አንቀ.16 ቁ.634/

ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት፤21ኛ ዓመት ቁጥር 7፤ ኅዳር 2006 ዓ.ም.