dsc01699

የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍሉ ለአረጋውያን እርዳታ አደረገ፡፡

ሐምሌ 24 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ


በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል ባሳለፍነው ሳምንት ረጅም ዘመናትን በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ ላሳለፉ አረጋውያን ጊዜያዊ የአልባሳትና የሕክምና እርዳታ አደረገ፡፡

የአገልግሎት ክፍሉ አብዛኛውን የእድሜ ዘመናቸውን በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ላይ አድርገው ለኖሩ ሰባት አባቶች የአልባሳት እገዛ dsc01699ያደረገው በ2004 ዓ.ም. መሪ እቅዱ መሠረት መሆኑን የጠቀሱት የክፍሉ ሓላፊ ወይዘሪት መቅደስ ዓለሙ፤ “ይህንን ለማቀድ ምክንያት የሆነን አባቶቻችን ከሰፊ የአገልግሎት ዘመናቸው በኋላ የሚታሰብላቸው የጡረታ አበል አለመኖሩ ነው፡፡ አብዛኛዎቹ አባቶችም በቅርብ የሚረዳቸውና የሚንከባከባቸው ሰው የሌላቸው ናቸው፡፡ ስለሆነም ምንም ዓይነት አገልግሎት እንዳልሰጡ በቂ ትኩረት ተነፍጓቸውና ተረስተው በየመቃብር ቤቱና ንጽሕና በተጓደለባቸው ሥፍራዎች ወድቀው የሚገኙትን አባቶች፤ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር በመተባበር ባካሄድነው ጥናትና ባገኘነው መረጃ መሠረት መርጠን ረድተናል፡፡” በማለት ምክንያቱን አስረድተዋል፡፡

የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍሉ በልዩ ልዩ ቦታዎች ለሚገኙ አረጋውያን ካበረከተው የአልባሳት አስተዋጽኦ በተጨማሪ በበጎ አድራጊdsc01709 ምእመን ቤት ተጠግተው ለሚኖሩ አንድ አባት ሙሉ የሕክምና ወጪ በመሸፈን እንዲታከሙ አድርጓአል፡፡

 

በስተመጨረሻም ወይዘሪት መቅደስ ዓለሙ “ከጊዜያዊ እርዳታ ባለፈ በቀጣይ አረጋውያኑን ለማቋቋምና ኑሮአቸውን ለማሻሻል በክፍሉ ምን ታስቧል?” በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ “እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ይህ እቅድ በ2005 ዓ.ም. ተጠናክሮ የሚቀጥል ይሆናል፡፡ ክፍሉም እንደ ክፍል በአቅም ከፍ ይላል ብለን እናስባለን፡፡ እናም በቀጣዩ ዓመት ከጊዜያዊ እርዳታ ይልቅ የተሻለ እገዛ ማበርከት የምንችልበትን ዝግጅት አጠናቅቀናል፤ ጊዜው ሲደርስም ይህንኑ እንፈጽማለን ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡” ብለዋል፡፡

 

በተያያዘ ዜና የአገልግሎት ክፍሉ በበኪ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤት ለሚገኙ ተማሪዎች ማቋቋሚያ የሚሆን ፕሮጀክት ነድፎ እየሠራ መሆኑን በተለይ  ለመካነ ድራችን በሰጠው መግለጫ አስረድቷል፡፡ ከዚህ ቀደም  በአገልግሎት ክፍሉ አማካኝነት ለተማሪዎች ጊዜያዊ የአልባሳትና የቀለብ እገዛ የተደረገ ሲሆን፤ በዚህ ዓመት ግን ተግባራዊ የሆነውና  በሦስት ሔክታር መሬት ላይ  ያርፈው የእርሻ ሥራ ሙሉ ለሙሉ የተማሪዎችን ችግር ይቀርፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

 

dsc01744በሦስት ሔክታር መሬት ላይ ጤፍ ለመዝራት አስፈላጊውን ቅድመ ዝግጅት መደረጉን ያወሱት የአገልግሎት ክፍሉ ኃላፊ ወይዘሪት መቅደስ “መሬቱን በትራክተር ከታረሰበት ከመጀመሪያው ቀን አንስቶ ለሦስት ተከታታይ ጊዜያት የአከባቢው ገበሬዎች አርባ ጥማድ በሬዎቹን ይዘው እንዲሁም፤  ምእመናን በገንዘባቸውና በጉልበታቸው  አማካኝነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ … ከደብሩ አስተዳደር ጀምሮ ሌሎችም መደበኛ  አገልጋዮችና ምእመናን ለቤተ ክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገት በጋራ እንሥራ የሚለውን መርሕ የተቀበሉ ናቸው፡፡ ይህም በሌሎች ቦታዎች ለሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አካላት መልካም ተሞክሮ ነው፡፡” በማለት በማጠቃለያ መልእክታቸው በፕሮጀክቱ ትግበራ ላይ የተባበሩትን ሁሉ አመስግነዋል፡፡

በዝቋላ ገዳም የወተት ላም እርባታ ፕሮጀክት ተግባራዊ ሊደረግ ነው፡፡

ሐምሌ 24 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስ


ለዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም የወተት ላም እርባታ ፕሮጀክት ለመተግበር ስምምነት ላይ መደረሱ ተገለጸ፡፡

 

በገዳሙ በቅርቡ ከፍተኛ የደን ቃጠሎ ተከስቶ እንደነበር የሚታወስ ሲሆን ገዳሙን ለመርዳት በሀገር ውስጥና በመላው ዓለም የሚገኙ ምእመናን የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ በማድረግ ላይ እንደሆኑ ይታወቃል፡፡ በዚህም መሠረት ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናንን በማስተባበር ከ600,000.00 ብር /ስድስት መቶ ሺህ ብር/ በላይ ለማሰባሰብ መቻሉን የማኅበሩ ዋና ጸሓፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኃይለ ማርያም ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ገንዘብ ውስጥ አብዛኛው በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል አስተባባሪነት በአሜሪካ የሚገኙ የማኅበረ በዓለወልድ እና የሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ያሰባሰቡት መሆኑ ታውቋል፡፡

የተገኘውን እርደታ ወደ ተግባር ለመለወጥ በታቀደው መሠረት “ለገዳሙ ቋሚ ፕሮጀክት እንደሚያስፈልገው ስለታመነበት ቦታው ድረስ ባሙያዎች በመላክ የዳሰሳ ጥት የተደረገ ሲሆን ከገዳሙ ሓላፊዎች ጋር ውይይት ተደርጓል፡፡ በውይይቱም ለገዳሙ ትልቅ ጥቅም የሚሰጠው የትራክተር ግዢ ቢሆንም ለጊዜው የተሰበሰበው ገንዘብ ይህንን ለማስፈጸም የማይበቃ በመሆኑ ከዚህ በፊት ተጀምሮ የነበረው የወተት ላም እርባታ ፕሮጀክት እንዲተገበር ስምምነት ላይ ተደርሷል” በማለት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሓፊ ዲ/ን ሙሉጌታ ኃይለ ማርያም ገልጸዋል፡፡ በስምምነቱ መሠረት የማኅበሩ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ፕሮጀክቱን እንደሚያስፈጽም ተናግረዋል፡፡

 

የገዳሙ ደን በተቃጠለበት ወቅት የቀለብ እጥረት በመከሰቱ ማኅበሩ ምእመናንን በማስተባበር 50 ኩንታል ስንዴ 20 ኩንታል ጤፍ፣ 40 ሺህ ብር የሚገመት መጠጥ ውኃ፣ በሶ፣ ስኳር፣ ዳቦ ድጋፍ ማድረጉን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን የወሰነው ውሳኔ ለማኅበሩ መድረሱ ተገለጸ

ሐምሌ 23ቀን 2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ


የ2004 ዓ.ም. የግንቦቱ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ስለ ማኅበረ ቅዱሳን የወሰነው ውሳኔ   በደብዳቤ የተገለጸ መሆኑን የማኅበሩ ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት፤ የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ለብፁዕ አቡነ ፊልጶስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ የኢሉባቦርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በጻፉት ደብዳቤ ማኅበሩ ለብፁዕነታቸው ተጠሪ እንዲሆን በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ መወሰኑን ጠቅሰው ከማኅበሩ እድገት ጋር አብሮ ሊሄድ እንዲችል የማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ አስጠንተው ለጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲያቀርቡ አሳስበዋል፡፡

 

ቅዱስነታቸው በቁጥር 451/275/2004 በቀን 13/11/2004 ዓ.ም. በጻፉት ደብዳቤ “ማኅበረ ቅዱሳን ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ተለይቶ የራሱ የሆነ መተዳደሪያ ደንብ ተጠንቶ እስኪወጣለት ድረስ ተጠሪነቱ ለብፁዕነትዎ ሆኖ ሲሠራ እንዲቆይ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ተወስኗል፡፡” በማለት ያስታወሱት ቅዱስ ፓትርያርኩ መተዳደሪያ ደንቡን እንዲያጠኑ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ የተመረጡትን የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ስም ዝርዝር ጠቅሰዋል፡፡በዚህም መሠረት ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የሲዳማ፤ ጌዴኦና አማሮ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ገሪማ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት የውጭ ግንኙነት የበላይ ሓላፊ ፤የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንትና የዓለም ሃይማኖቶች ምክር ቤት የክብር ፕሬዚዳንት ቢሮ ዋና ጸሐፊና የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ያሬድ የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ የሰዋሰወ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ የበላይ ሓላፊ፤ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የከምባታ ሐድያና ጉራጌ አህጉረ ስብከት እና የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ፤ ከሕግ ባለሙያዎችና ከማኅበረ ቅዱሳን አባላት ጋር በመሆን መተዳደሪያ ደንቡን አስጠንተው ለጥቅምት ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲያቀርቡ ገልጸዋል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ወጥቶ ለጠቅላይ  ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ  ተጠሪ እንዲሆን  በግንቦቱ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተወሰነ ሲሆን በዚሁ ወቅት ቅዱስ ሲኖዶስ ስለማኅበሩ በሰጠው አስተያየት “ማኅበረ ቅዱሳን የመሥራት አቅሙ ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰና በቤተ ክርስቲያኒቱ እየሠራ ባለው ሥራ ሁሉ አብተ ክርስቲያናትንና ገዳማትን በስፋት እየጠቀመ ያለ በምሁራን የታቀፈ፤ ሁለንተናዊ ዝግጅት ያለው ማኅበር ስለሆነና ብዙ የልማት ሥራዎችን በመሥራት ላይ የሚገኝ በመሆኑ እራሱን የቻለ ድርጅታዊ መዋቅር ሊዘረጋለት ይገባል” ማለቱ ይታወሳል፡፡

1

“ዝክረ ቅዱስ ቂርቆስ” በሚል መሪ ቃል የተዘጋጀው መንፈሳዊ መርሐ ግብር ተጠናቀቀ፡፡


ሐምሌ 17 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

1በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኘው የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ያዘጋጀው መርሐ ግብር ከሐምሌ 12 እስከ ሐምሌ 15 ቀን ተካሄደ፡፡ ዝግጅቱ በሁለት ዐበይት ክፍሎች ተከፍሎ የተካሄደ ሲሆን፡- ይህም ከመክፈቻው ሐምሌ 12-14 በዐውደ ርዕይ፣ እንዲሁም ሐምሌ 15 ቀን 12 ሰንበት ትምህርት ቤቶች የተሳተፉበት መንፈሳዊ መርሐ ግብር የቀረበበት መሆኑ ታውቋል፡፡

 

ለ3 ቀናት የቆየውን ዐውደ ርዕይ በጸሎት የከፈቱት የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን  አስተዳዳሪ መልአከ ገነት አባ ኀይለ ማርያም መንገሻ  ዐውደ ርዕዩን በጸሎት ከከፈቱ በኋላ በሰጡት አስተያየት በዕድሜ ሕፃናት የሆኑት ልጆች ባዘጋጁት መርሐ ግብር ከፍተኛ ደስታና ኩራት እንደተሰማቸው ገልጸው፡- “የዛሬ አበባ የነገ ፍሬ የሆኑ ሕፃናት ልጆቻችንን በደንብ ልንንከባከባቸው ይገባናል፡፡ ይህንንም ካደረግን በመጪው ጊዜ ቤተ ክርስቲያንን የሚረከብ ትውልድ በብዛት ብቻ ሳይሆን በጥራትም እናፈራለን፤ ይህም ታላቅ ተስፋችን ነው፡፡” ብለዋል፡፡ መልአከ ገነት አባ ኀይለ ማርያም በማጠቃለያ መልእክታቸው “የአድባራት አስተዳዳሪዎችን ጨምሮ በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የምንገኝ መሪጌቶችና አገልጋዮች በሙሉ ለሰንበት ትምህርት ቤት አስፈላጊውን ድጋፍ ማድረግ አለብን፡፡ ይህ ካልሆነ ግን የነገዋን ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ፈተና ውስጥ እንደሚገባ ልንረዳ ይገባናል” ብለዋል፡፡

 

5“ሰንበት ትምህርት ቤታችን ከዚህ ቀደም የተለያዩ ዐውደ ርዕዮችን ያዘጋጀ ሲሆን ሕፃናትን በተመለከተ ግን ይህ ዐውደ ርዕይ የመጀመሪያው ነው፡፡ ሕፃናትን የተመለከተ ዐውደ ርዕይ እንድናቀርብ የተፈለገበት ዋነኛው ምክንያት ተገቢውን ትኩረት ለሕፃናት እንዲሰጥ ለመቀስቀስ ነው፡፡” በማለት ዐውደ ርዕዩ በሕፃናት ዙሪያ እንዲከናወን ምክንያት ስለሆነው ሁኔታ ያስረዳው ወጣት ዮሐንስ መረቀኝ የደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤት ምክትል ሰብሳቢ ነው፡፡

 

“በቀደምት ኢትዮጵያውያን ወላጆቻችን ዘንድ እንደ ልምድ ተይዞ የነበረው ልጆችን በሕፃንነት እድሜአቸው ወደ አብነት ትምህርት ቤት የመላክ ሁኔታ አሁን አሁን እየተቀየረ÷ በዘመናዊ ትምህርት ብቻ እንዲማሩ ማድረግ  ‘ባሕል’ እየሆነ የመጣበት ጊዜ ላይ በደረስንበት በዚህ ወቅት ሕፃናት ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን፣ ትምህርተ ሃይማኖትን፣ ጸሎቱንና የመሳሰለውን እንዲማሩና እንዲያውቁ የማስቻል ሓላፊነት ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ወላጆች ልንወጣ ይገባናል፡፡በዐውደ ርዕዩ ላይ የተካተቱት ልዩ ልዩ ክፍሎች ሕፃናት በቤተ ክርስቲያን ያላቸውን ተስፋ ለማመላከት ታስበው የተዘጋጁ ናቸው” በማለት ወጣት ዮሐንስ አስረድቷል፡፡

 

25 የሚደርሱ ሕፃናት በገላጭነት የተሳተፉበት ዐውደ ርዕዩ በ8 ልዩ ልዩ ክፍሎች ተከፋፍሎ የተዘጋጀ ሲሆን በዋነኝነት ሕጻናት ሊቃውንት፣ ሕጻናት ሰማዕታት፣ ሕጻናት በመጽሐፍ ቅዱስ፣ ሕጻናትና ሥራዎቻቸው ፣ ሕጻናትና ጥፋታቸው፣ እንዲሁም ለወላጆች የሚሉና መሰል ሌሎች ክፍሎች የተካተቱበት ነበር፡፡

 

በመዝጊያ መርሐ ግብሩ ላይ በደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ሰንበት ትምህርት ቤት አማካኝነት “ቁጥሮች ለሕፃናት” እንዲሁም 12ቱም ሰንበት ትምህርት ቤቶች በጋራ የተሳተፉበት “ድምፀ ሕፃናት” በሚል ርዕስ የተዘጋጁ የኅትመት ውጤቶች ተመርቀው ለአንባብያን ቀርበዋል፡፡

ክረምት

ሐምሌ 14 ቀን 2004 ዓ.ም.

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ


“ክረምተ ወሐጋየ ዘአንተ ፈጠርከ” መዝ.73÷17 “በጋንም ክረምትንም አንተ አደረግህ” መዝ.71÷17

እግዚአብሔር የዓለምን ምግብ ሥጋዊውንም መንፈሳዊውንም በአራት ከፍሎታል ሥጋዊውን በአራቱ ክፍላተ ዘመን መንፈሳዊውን በአራቱ ወንጌላዊያን ትምህርት፡፡ የሰው ሥጋዊ ምግብና ከአራቱ ክፍላተ ዘመን እንዳይወጣ መንፈሳዊ ምግብናውም ከአራቱ ወንጌላውያን አይወጣም፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር አምላካችን የሥጋም የነፍስም ፈጣሪ፣ መጋቢ ነውና፡፡ አሁን ያለንበት ከአራቱ ክፍላተ ዘመን አንዱ የሆነው ክረምት ነው፡፡ከዚህም የምናገኘው ሥጋዊ ምግብ ብቻ ሳይሆን ከሥጋዊ ምግብ ያለፈ መንፈሳዊ ምግብም አለ፡፡

 

ክረምት ምንድነው?

ክረምት ማለት ከርመ ከረመ ካለው የግዕዝ ቃል የተገኘ ሲሆን መክረም የዓመት መፈጸም፣  ማለቅ መጠናቀቅ ማለት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በፀሐይ አማካኝነት የደረቁ ኮረብቶች ተራሮች በዝናም አማካኝነት ውኃ የሚያገኙበት በዚህም ምክንያት በልምላሜ የሚሸፈኑበት፣ የደረቁ ወንዞች ጉድጓዶች ውኃ የሚሞሉበት፣ በፀሐይ የተቃጠለች ምድር ከሰማይ በሚወርድ ጠለል በረከት የምትረካበት፣ በውኃ ጥም የተሰነጣጠቁ የምድር ጉረሮዎች ውኃን የሚጠግቡበት፣ ሰማይ  በደመና የተራሮች ራስ በጉም  የሚጎናጸፉበት በሙቀት ፋንታ ቅዝቃዜ በድርቅ ፈንታም ልምላሜ የሚነግስበት ተሰባብሮ የወደቀ ሐረግ ቀና ብሎ ከየቦታው የሚሳብበት ወቅት  ነው፡፡

 

ክረምት

1.    ወርኃ ማይነው /የውኃ ወር፣ ወቅት ነው/ ውኃ ደግሞ እግዚአብሔር ለፈጠረው ፍጥረት ሁሉ በጣም አስፈላጊ ነው ከሥጋዊ ምግብና ስንነሣ ያለ ውኃ ለምግብነት የሚውል ነገር በዓለማችን ውስጥ የለም ምድር የዘሩባትን እንድታበቅል የተከሉባትን እንድታጸድቅ ያጸደቀችውን ተክልም ለፍሬ እንድታበቃ ውኃ አስፈላጊ ነው፡፡ ከዚህምበኋላ ያለ ውኃ ምግብ መሆን የሚችል የለም፡፡ እሚቦካው በውኃ የሚጋገረውም በውኃ ወጥ የሚሠራው የሚበላው የሚወራረደውም በውኃ ነው፡፡ የውኃን ጥቅም አበው በምሳሌ እንዲህ በማለት ያብራራሉ፡-  ከ ምላጭ ቢያብጥ በምን ይበጡ ውኃ ቢያንቅ በምን ይውጡ ቁሳቁሱ በውኃ ይታጠባል፤ ከቆሻሻ ይለያል የሚሠራው ቤትም ቢሆን ሰማይ ጠቀስ ሕንፃ፣ ሲሚንቶው፣ ብረቱ፣ ቢኖር ያለውኃ ሊሠራ አይችልም፡፡ በባሕር ውስጥ ለሚኖሩ ዓሣ አንበሪ፣ አዞ፣ ጉማሬ፣ምግብ ለሚሆኑትም ለማይሆኑትም ውኃ አስፈላጊ ነው፡፡ ውኃ ለሁሉም አስፈላጊ መሆኑ የተረጋገጠ ቢሆንም ከፍጡራን በተለየ ውኃ ለሰው ልጅ ያስፈልገዋል፤ ምክንያቱም የሰው ልጅ ከሚጠቀምባቸው ፍጡራን ያለ ውኃ ምግብ ሊሰጥ የሚችል የለምና፡፡ እንስሳት ውኃ ይፈልጋሉ ምድርም ውኃ ትፈልጋለች አትክልት፣ እፅዋት ውኃ ይፈልጋሉና ጠቅላላውን የፍጡራን ሕይወት የውኃ ጥገኛ ነው፡፡

 

ከዚህ አንፃር ከዓለማችን ብዙውን ቦታ የሚሸፍነው ውኃ መሆኑን ሥነፍጥረትም ሳይንስም ይስማሙበታል፤ ምክንያቱም በምድር ላይ ካለፍጡር የማያስፈልገው የለምና ከዚህም በተጨማሪ እቤታችን ውስጥ የሚሠሩ እቃዎች የሸክላም ይሁኑ የብረት በውኃ የተሠሩ ናቸው ከዚህ አለፍ ብለን ስንመለከት በአርዓያ ሥላሴ የተፈጠረ የሰው ልጅ ከተፈጠረባቸው አራት ባሕርያት አንዱ ውኃ ነው፡፡ በመሬትነት ባሕርዩ እየፈረሰና እየተቆረሰ ዓለምን እንዳያጠፋ በውኃነት ባሕርዩ አንድነቱ ጸንቶለት ይኖራል በእሳትነት ባሕርዩ ዓለምን እንዳያቃጥል በውኃነት ባሕርዩ እየቀዘቀዘ ይኖራል፡፡ ሰው ከእናቱ ተወልዶ  የእናቱን ጡት ጠብቶ እንዲያድግ ሰውም ከውኃ፣ ከእሳት፣ ከነፋስና ከመሬት ተፈጥሮ እነዚሁ የተገኘባቸውን ተመግቦ የሚኖር መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ የአራቱ ባሕርያት አስታራቂ ሽማግሌ ውኃ ነው፡፡ጠበኞች የሆኑ ነፋስና መሬት በውኃ ይታረቃሉ ነፋስ መሬትን ይጠርገዋል፡፡ መሬትም ነፋስን ይገድበዋል፡፡ዝናም በዘነመ ጊዜ ትቢያው የመሬት ላይኛው ክፍል በውኃ አማካኝነት ከታችኛው ክፍል ጋር አንድ ይሆናል በነፋስ መጠረጉም ይቀርለታል፡፡

 

ከዚህ በተጨማሪ ስለ ውኃ የእግዚአብሔር መሣሪያነት እናያለን፡፡

በኃጢአት የተበላሸው የቆሸሸው ዓለም የተቀጣው በውኃ መሆኑ መጽሐፍ ቅዱስ የሚመሠክረው እውነት ነው፡፡ ዘፍ.6÷1፣ 7÷1፣ 8÷1 እስከ ፍጻሜያቸው ማንበብ ለዚህ በቂ መልስ እናገኝበታለን፡፡ ኤልያስ አምልኮ እግዚአብሔር በአምልኮተ ጣዖት ተክተው ሃይማኖተ ኦሪትንት ተው የጣዖት ውሽማ አበጅተው ያስቸገሩትን አክአብና ኤልዛቤልን እንዲሁም መሰሎቻቸውን የቀጣው ሰማይ ዝናም ለዘር ጠል ለመከር እንዳይሰጥ ሰማይ ለጉሞ ዝናም አቁሞ ነው፡፡ በአንጻሩ በረድና እሳት አዝንሞ እንደ ነበር መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳናል፡፡

 

“ኤልያስ ዘከማነ ሰብዕ ውእቱ ወጸሎ ተጸለየ ከመ ኢይዝንም ዝናም ወኢዘንመ ዝናም ሠለስተ ዓመተ ወስድስተ አውርሀ ወካዕበ ጸለየ ከመይዝንም ዝናም ወወሀበ ሰማይ ዝናሞ ወምድርኒ አብቆለት ፍሬሃ” ያዕ.5÷17 ኤልያስ እንደኛ የሆነ ሰው ነበር ዝናም እንዳይዘንም አጥብቆ ጸለየ በምድርም ላይ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር ዝናም አልዘነበም ሁለተኛም ጸለየ ሠማዩም ዝናብን ሰጠ ምድር ፍሬዋን አበቀለች፡፡ በማለት የሰው ልጆች ሕገ እግዚአብሔርን ሲጥሉ ትእዛዘ እግዚአብሔርን ሲያፈርሱ ከሕጉ ሲወጡ ከአምልኮቱ ሲያፈነግጡ ውሃ መቅጫ መሳሪያ በመሆኑም ይታወቃል ውኃ እስከ አሁን የተመለከትነው በሥጋዊ ምግብነቱ ያለውን ነው፡፡

 

ከዚህ ውጪ መንፈሳዊ ምግብናውስ ብንል፡፡ አሁን ካየነው የጎላ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡”

ደገኛዋ የሰው ልጆች ጥምቀት በውኃ መሆኑ የውኃን ጥቅም የጎላ መሆኑን ያሳየናል፡፡ ይኸውም እንደምናውቀው የጥምቀታችን መሥራች ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በውኃ ተጠምቆ የአባቶቻችንና በኛ ላይ የነበረው የእዳ ደብዳቤ ያጠፋልን በውኃ በመጠመቁ ነበር ማቴ.3÷13 ከዚህ በኋላ “ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም” ዮሐ.3÷5 ብሎ ውኃ ከሥጋዊ ምግብናው ያለፈ እኛ የእግዚአብሔር ልጆች የምንሆንበት ምሥጢር መፈጸሚያ መሆኑን ይነግረናል፡፡ በሌላ መልኩ ጌታችንን የእኛን ሥጋ ለብሶ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተገልጾ ባስተማረበት ጊዜ እንጀራ ለመነ ሳይሆን ውኃ ለመነ የሚል ነው የተጻፈለት፡፡ “ኢየሱስም ውኃ አጠጭኝ አላት” ዮሐ. 4÷7 አሁን ከዚህ የምንመለከተው እስራኤል 40 ዓመት ውኃ ከጭንጫ ያጠጣ አምላክ ውኃ አጥቶ ይመስላችኋል ውኃ ትልቅ ምሥጢር የሚፈጸምበት መሆኑ ለመግለጽ ነው እንጂ ይኸውም ሊታወቅ “የእግዚአብሔር ስጦታ ውኃ አጠጭኝ የሚልሽ ማን መሆኑንስ ብታውቂ አንቺ ትለምኚው ነበር እንጂ የሕይወት ውኃም ይሰጥሽ ነበር” ከዚህ ውኃ የሚጠጣ ዳግመኛ ይጠማል እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ግን ለዘለዓለም አይጠማም ብሎ አስተምሮአል፡፡” ያውም ውኃ የተባለው ትምህርት ልጅነት በሌላ መልኩ እራሱ መሆኑንም ነው የሚያስረዳን በመስቀል ላይ እያለም ከተናገራቸው 7ቱ የመስቀል ንግግሮች አንዱ “ተጠማሁ የሚል ነበር፡፡ ዮሐ.19÷29 ይኸ ከሥጋ መጠማት ያለፈ የእኛን የነፍሳችን ጥማት እንደአጠፋልን የምንማርበት ነው፡፡ እኛን የሕይወት ውኃ ያጠጣን ዘንድ ተጠማሁ አለም፤ ከዚህም የተነሣ ቀደም ሲል በነቢዩ ኢሳኢያስ እንዲህ ሲል ተናገረ፡፡ “እናንተ የተጠማችሁ ሁሉ ወደ ውኃ ኑ ገንዘብም የሌላችሁ ኑና ግዙ” ኢሳ.55÷1 ብሎ በዓለም ላሉ ፍጡራን ውኃ አስፈላጊ ቢሆንም ቅሉ በተለይ ለሰው ልጆች እጅግ አስፈላጊ እንደሆነ ይናገራል፡፡

 

የተጠማ ይምጣ ይጠጣ የሚለው ብዙ ምሥጢር ያለው ነው ጌታችን የአይሁድ በአል በሚከበርበት ቦታ ተገኝቶ ቀደም ሲል በኢሳይያስ የተነገረውን ቃል ስለ መንፈስ ቅዱስ የተነገረ መሆኑን ገልጾአል፡፡ “ኢየሱስም ቆሞ ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል ብሎ ጮኸ” ይኸን ግን በእርሱ የሚያምኑ ሊቀበሉት ስለአላቸው ስለ መንፈስ ቅዱስ ተናገረ፡፡  ዮሐ.7÷37-39 ስለዚህ ውኃ የመንፈስ ቅዱስ ምሳሌ ሆኖአል ውኃ ከቆሻሻ ከእድፍ እንዲያነጻ መንፈስ ቅዱስም ከኀጢአት ከርኲሰት ከክፋት፣ ከተንኮል፣ ከበደል ሰውን ያነጻልና፡፡ ከክረምት አንደኛው ክፍል ወርኃ ማይ የውኃ ወቅት ይባላል፡፡

 

2.    ክረምት ወርኃ ዘር ነው፡፡ የዘር ወቅት ወይም ጊዜ ነው፡፡ ገበሬው በበጋ ያረሰውን የከሰከሰውን ደረቅ መሬት በዝናብ ወቅት አለስልሶ አዘጋጅቶ ከጎታው ወይም ከጎተራው ያስቀመጠውን ዘር ባዘጋጀው መሬት ላይ አውጥቶ የሚዘራበት መሬቱ ያብቅል አያብቅል ፍሬ ይስጥ አይስጥ ሳያውቅ እግዚአብሔር በዝናብ አብቅሎ በፀሐይ አብስሎ ይመግበኛል ብሎ በማመን ያለምንም ጥርጥር የጎታውን እህል ለመሬት አደራ የሚሰጥበት ከላይ ዝናሙን ከታች ጭቃውን ታግሶ በሬዎችን እየነዳ በትከሻው ላይ ዘርና ቀምበር ተሸክሞ ዘር ለመዝራት ይሰማራል፡፡

 

የገበሬውን ሁኔታ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲህ ብሎ ገልጾታል፡፡ “ናሁ ወጽአ ዘራኢ ከመ ይዝራዕ ዘርዖ” ዘሪ ሊዘራ ወጣ ሲዘራም አንዳንዱ ዘር ከመንገድ ዳር ወደቀ በጭንጫ ላይ የወደቀ ዘር አለ በሾህ መካከል የወደቀ ዘርም አለ በመልካም መሬት ላይም የወደቀ ዘር አለ፡፡ መቶ ስልሳ ሠላሳ ፍሬ ሰጠ” ማቴ.13÷1 ብሎ ራሱን በገበሬ ቃሉን በዘር የሰማዕያን ልቡና በመንገድ፣ በዐለት፣ በእሾህ፣ በለሰለሰ መሬት መስሎ አስተምሯል፡፡ በመንገድ የተመሰለው ሰምተው የማያስተውሉ ሰዎች ልቡና ነው የሰማይ ወፎች የተባሉ ደግሞ አጋንንት ናቸው፡፡ “ኢትህሚ ሰብአ በቤትከ እስመ ዖፈ ሰማይ ያወጽዖ ለነገርከ” መክ.10÷20

 

በቤትህ ውስጥ ንጉሥ አትስደብ የሰማይ ወፍ/ዲያብሎስ/ ቃሉን ነገሩን ይወስደዋልና” እንዲል በዐለት የተመሰሉት ፈጥነው የሚሰሙ ግን ተግባር ላይ የሌሉ በእሾህ የተመሰሉትም የዚህ ዓለም ሀሳብ ምድራዊ ብልጽግና ፍቅረ ዓለም አስሮ የያዛቸው ሰዎች ሲሆኑ በመልካም መሬት የተመሰሉት ቃሉን ሰምተው የጽድቅ ሥራን የሚሠሩ ናቸው፡፡ በወርኃ ዘር የምንማረው ትልቁ ትምህርት ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን ነው፡፡ በወርኃ ማይ ምሥጢረ ጥምቀትን እንደተማርን ገበሬው በጎታው ያከማቸውን እህል ከአፈር ጋር አንድ እንደሚያደርገው ማለት በአፈር ላይ እንደሚዘራው የሰው ዘርም እንዲሁ ውሎ ውሎ ከቤት ኖሮ ኖሮ ከመሬት እንዲሉ ሲሞት በመቃብር ከአፈር ጋር አንድ ይሆናል ይፈርሳል ይበሰብሳል ወደ አፈርነቱ ይመለሳል፡፡ “ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ አፈር ነህና ወደ አፈርነትህም ትመለሳለህና” እንዳለ ዘፍ.3÷19 የተዘራው ዘር በዝናቡና በተዘራበት አፈር አማካኝነት ይፈርሳል ይበቅላል ይለመልማል፣ ያብባል ፣ ፍሬ ይሰጣል ሰውም እንደዚሁ ነው፡፡ ይፀነሳል፣ ይወለዳል፣ ያድጋል ይሞታል፡፡

 

ወደ መሬት ይመለሳል ይፈርሳል፡፡ ትንሣኤ ዘጉባኤን ጠብቆ ይነሣል፡፡ ይህን በተመለከተ ጌታችን ሲያስተምር “ለዕመ ኢወድቀት ህጠተ ስርናይ ውስተ ምድር ወኢሞተት ባህቲታ ትነብር ወእመሰ ሞተት ብዙኀ ፍሬ ትፈሪ” ዮሐ.12÷24 የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች” ሰውም ካልሞተ አይነሣም ካልተነሣም መንግሥተ ሰማያት ሊገባ አይችልምና፡፡ ምክንያቱም ግብር እምግብር ሳይለወጡ መንግሥተ ሰማያት አይገባምና ስለዚህ ሰው ትንሣኤ እንዳለው ገበሬ ከሚዘራው ዘር መማርና ብዙ ፍሬ ማፍራት ይጠበቅበታል ቅዱስ ጳውሎስም ትንሣኤ ሙታንን ባስተማረበት መልእክቱ ይህንኑ ያጎላልናል፡፡ “ኦ አብድ አንተ ዘትዘርዕ ኢየሀዩ ለዕመ ኢሞተ” 1ቆሮ.15÷35 ነገር ግን ሰው ሙታን እንዴት ይነሣሉ? በምንስ አይነት አካል ይመጣሉ? የሚል ይኖር ይሆናል አንተ ሞኝ የቆሮንቶስ ገበሬ አንተ የዘራኸው ካልሞተ ሕያው አይሆንም የምትዘራውም ስንዴ ቢሆን ከሌላም ዓይነት /በቆሎ ኑግ/ የአንዱ ቢሆን ቅንጣት /ፍሬ/ ብቻ ነው እንጂ የምትዘራው የሚሆነውን አካል አይደለም እግዚአብሔር ግን እንደ ወደደ አካልን ይሰጠዋል፡፡

 

ከዘሮችም ለእያንዳንዱ የገዛ አካሉን ይሰጠዋል፣ ሥጋ ሁሉ አንድ አይደለም የሰው ሥጋ ግን አንድ ነው የእንስሳ ሥጋ ሌላ ነው የዓሣም ሥጋ ሌላ ነው ደግሞ ሠማያዊ አካል አለ ምድራዊም አካል አለ ነገር ግን የሰማያዊ አካል ክብር ልዩ ነው፡፡ የምድራዊ አካል ክብርም ልዩ ነው የፀሐይ ክብር አንድ ነው፡፡ የጨረቃ ክብር ሌላ ነው የከዋክብትም ክብር ሌላ ነው በክብር አንዱ ኮከብ ከሌላው ኮከብ ይለያልና፡፡ የሙታን ትንሣኤ ደግሞ እንዲሁ ነው በመበስበስ ይዘራል፣ በአለመበስበስ ይነሣል በውርደት /አራት አምስት ሰው ተሸክሞት/ ይዘራል/ይቀበራል፡፡ በክብር ይነሣል በድካም ይዘራል በኀይል ይነሣል ፍጥረታዊ አካል ይዘራል/ ሟች ፈራሽ በስባሽ አካል ይቀበራል/ መንፈሳዊ አካል ይነሣል ማለት የማይሞት የማይታመም የማይደክም ሆኖ ይነሣል” በማለት ወርኃ ዘር የትንሣኤ ሙታን መማሪያ መሆኑን ጽፎአል ከዚህ ላይ አንድ ገበሬ ስንዴ ከዘራ ስንዴ ጤፍ ከዘራ ደግሞ ጤፍ በቆሎም ከዘራ በቆሎ ኑግ ቢዘራ ኑግ እንደሚሆን አካሉን ለውጦ እንደማይበቅል ሰውም የራሱን ማንነት ይዞ የሚነሳ መሆኑንም ጭምር ነው ያስተማረን ሰው ክፉ የሠራም ሥራው ጽድቅ የሠራም የራሱን ሥራ ይዞ ይነሣል እንጂ ጻድቁ ኀጥዕ ኀጥዑ ጻድቅ ሆኖ  አይነሣም፡፡ እንደ ሥራው ዋጋውን የሚቀበልበት ነውና፡፡ “ሰው የዘራውን ያጭዳል” እንዲል ገላ.6÷7 በሌላም አንቀጽ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡፡ “በጥቂት የሚዘራ በጥቂት ያጭዳል በበረከትም የሚዘራ ደግሞ በበረከት ያጭዳል” 2ቆሮ.9÷6 ይህንም ስለመስጠትና መቀበል አስተምሮታል የዘራ እንደሚሰበስብ የሰጠም ዋጋውን አያጣምና የተዘራባት ምድር የዘሩባት አብዝታ እንደምትሰጥ በምጽዋት መልክ የተቀበሉ ነዳነያንም ትልቅ ዋጋ ያሰጣሉና በሚያልፍ የማያልፍ በሚያልቅ የማያልቅ ዋጋ ያስገኛሉና ምጽዋት በዘር መስሎታል “ዘርን ለዘሪ ለመብላትም እንጀራን በብዙ የሚሰጥ እርሱም የምትዘሩትን ዘር ይሰጣችኋል” 2ቆሮ.9÷10 ጠቅለል አድርገን ከብዙ በጥቂቱ ከረጅሙ ባጭሩ ስናስቀምጠው ወርኃ ዘር በዚህ መልኩ ተገልጿል፡፡ “ብዙ ጊዜ በእርሷ ላይ የሚወርደውን ዝናብ የምትጠጣ መሬት ለሚያርሷትም ደግሞ የምትጠቅመን አትክልት የምታበቅል ከእግዚአብሔር በረከትን ታገኛለችና እሾህንና ኩርንችትን ግን ብታወጣ የተጣለች ናት ለመርገምም ትቀርባለች መጨረሻዋ መቃጠል ነው” ዕብ.6÷7 ከዚህም መሬት የተባለ የሰው ልጅ ዘር የተባለ ቃል እግዚአብሔር ዝናም የተባለ ትምህርት እሾህ የተባለ ኀጢአት ክፋት ነው ምድር የዘሩባት ባታበቅል መጨረሻዋ መቃጠል እንደሆነና የሰው ልጅም አደራውን ባይጠብቅ የንስሓ ፍሬ ባያፈራ ፍጻሜው መከራ ነውና፡፡ ሰው እንደ ዘር ወደ መሬት እንደሚመለስ ዘሩ ፈርሶ በስብሶ ከበቀለ በኋላ ፍሬ እንደሚሰጥ ሰውም ከሞተ በኋላ ትንሣኤ ያለው መሆኑን በማሰብ መልካም ሥራን መሥራት እንደሚገባው እንማራለን፡፡ ከዚህ አለፍ ብለን ዘር የሚለውን ስንመለከተው ድንቅ ምሥጢር ያዘለ መሆኑንም ጭምር  እንገነዘባለን፡፡

 

“የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ዘርን ባያስቀርልን ኖሮ እንደ ሰዶም በሆንን ገሞራንም በመሰልን ነበር” ኢሳ.1÷9 ይህ ዘር ነቢያት፣ ደቂቀ ነቢያት፣ በተለይም እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከእርሷ እኛ ለማዳን የተወለደውን ክርስቶስ ያሳየናል፡፡” የነሣውን ሥጋ ከመላእክት የነሣው አይደለም ከአብርሃም ዘር ነው እንጂ” እንዲል ዕብ.2÷16 ቅዱስ ጴጥሮስ ይህ ዘር ምን ያህል ታላቅ መሆኑን ሲያስረዳ “ዳግመኛ የተወለዳችሁት ከሚጠፋ ዘር አይደለም በሕያውና ለዘለዓለም በእግዚአብሔር ቃል ከማይጠፋ ዘር ነው እንጂ” 1ጴጥ.1÷23 ስለዚህ የማይጠፋ ዘር የተባለው ክርስቶስ ነው፡፡ ከእርሱ ተወልደናልና እርሱንም በመከራው መስለነው በትንሣኤውም ልንመስለው ያስፈልጋል፡፡

 

3.    ክረምት ወርኃ ልምላሜ ነው፡- በክረምት ወቅት ከዘር ተከትሎ ምድር በቅጠል በልዩ ልዩ የልምላሜ ዓይነቶች አሸብርቃ ደምቃ በዋዕየ ፀሐይ የተራቆተ ማንነቷ በቅጠል የሚሸፈንበት ወቅት በመሆኑ ወርኃ ልምላሜ ነው፡፡ ፍሬ ግን የለም ይህን ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ሰማይን በደመና ይሸፍናል፤ ለምድርም ዝናምን ያዘጋጃል ሳርን በተራሮች ላይ ያበቅላል ለምለሙንም ለሰው ልጆች ጥቅም ለሚጠሩት ለቁራዎች ጫጩቶች ለእንስሶችም ምግባቸውን ይሰጣል” መዝ.146÷8-10 በማለት ወቅቱ የልምላሜ የሣርና የቅጠል እንስሳት ሣሩ ቅጠሉን ከማንኛውም ጊዜ በበለጠ የሚያገኙበት እንደሆነ ገልጿል፡፡

 

ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው በቢታንያ መንገድ ላይ በተራበ ጊዜ ያያት በለስ ቅጠል ብቻ እንደነበረች በወንጌል ተጽፏል፡፡ “በማለዳም ወደ ከተማ ሲመለስ ተራበ በመንገድም አጠገብ በለስ አይቶ ወደ እርሷ መጣ ከቅጠል በቀር ምንም ፍሬ አላገኘባትምና ለዘለዓለሙ ፍሬ አይገኝብሽ አላት በለሲቱም ያን ጊዜውን ደረቀች” ማቴ.21÷18 ይላል፡፡ ይኸውም ጊዜው ክረምት ነበር፡፡ ወርኃ ቅጠል የነቢያትን ዘመን ይመስላል በነቢያት በዘመነ ነቢያት ሁሉም በተስፋ ብቻ ይኖሩ እንደነበር እንዲህ ተገልጿአል፡፡ “ብዙ ነቢያትና ጻድቃን ሊያዩ ተመኙ አላዩም የምትሰሙትን ሊሰሙ ተመኝተው አልሰሙም” ማቴ.13÷16 ገበሬውም የዘራውን ዘር ቅጠሉን በተስፋ እየተመለከተ አረሙን እየነቀለ ዙሪያውን እያጠረ እየተንከባከበ ይጠብቃል ደግሞም ፈጣሪውን ከበረድ እንዲጠብቅለት እየተማጸነ የራት ሰዓት እስኪደርስ መቆያ እንዲቀምስ ይህ ቅጠል ፍሬ እስኪሰጥ በተስፋ አለኝ እያለ ቅጠሉን የዐይን ምግብ አድርጎ ይጠባበቃል፡፡ በሌላ መልኩ የእግዚአብሔር መንግሥት ዘሪ በእርሻው ላይ የዘራውን ዘር እንደምትመስል ተጽፏል፡፡

 

“በምድር ዘርን እንደሚዘራ ሰው የእግዚአብሔር መንግሥት እንዲህ ናት ሌሊት ይተኛል ቀን ይነሣል እርሱም /ገበሬውም/ እንዴት እንደሚሆን ሳያውቅ ዘሩ ይበቅላል ያድግማል ምድሪቱም አውቃ በመጀመሪያ ቡቃያ ኋላም ዛላ በዘለላው ፍጹም ፍሬ ታፈራለች ፍሬ ግን ሲበስል መከር ደርሷልና ወዲያው ማጭድ ይልካል፡፡ ማር.4÷26-29 ፍሬ እስከምታፈራ ግን ገበሬው እንደሚጠብቅ ነው የሚያስተምረን በገበሬው የተመሰለው ኢየሱስ ክርስቶስም እኛ በዓለም ላይ ያለን የሰው ዘሮች በሙሉ በመከር ያፈራውም ያላፈራውም እንዲሰበሰብ ያሳየናል፡፡ “እንግዲህ ወንድሞች ሆይ ጌታ እስኪመጣ ድረስ እነሆ ገበሬው የፊተኛውን የኋለኛውን ዝናም እርሱን የታገሰ የከበረውን የምድር ፍሬ ይጠብቃል እናንተም ደግሞ ታገሡ” የዕ.5÷7-9 ገበሬ ቅጠሉ ፍሬ እስከሚሰጥ ምን ያህል መከራን እንደሚታገስ እኛም መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ቅጠል ብቻ የሆነ ማንነታችን የንስሐ ፍሬ እስኪያፈራ ድረስ መከራውን መታገስ እንደሚገባን ያስተምራል፡፡ ምድራዊ ፍሬ ለማግኘት ይህን ያህል መጠበቅ መታገስ ካስፈለገ ሰማያዊ ዋጋ ለመቀበል ምን ያህል መታገስ ያስፈልግ ይሆን? ከወርኃ ቅጠል የምንማረው ያለፍሬ ብንገኝ መርገምን እንደምናተርፍ ብናፈራ ግን ገበሬ ደስ ብሎት ምርቱን ደስ ብሎት እንዲሰበስብ ፈጣሪያችንም በእኛ የሚደሰት መሆኑን እናውቃለን እኛም ዋጋችንን እንደምናገኝ እንማራለን፡፡ ክረምት ጥልቅ ትምህርት የምንማርበት እግዚአብሔር በሰፊው የሚገለጽበት ነው፡፡

 

ይቆየን

ec_members

አውሮፓ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤውን አካሄደ

ሐምሌ 13 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ


  • የማኅበረ ቅዱሳን 20ኛ ዓመት እና የአውሮፓ ማእከል 12ኛ ዓመት ምሥረታ በዓል በስውድን ተከበረ።

በማኅበረ ቅዱሳን የአውሮፓ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤውን ከሰኔ 29 እስከ ሐምሌ 1 ቀን 2004 ዓ.ም. በሀገረ ስዊድን ስቶክሆልም ከተማ አካሄደ። ከመላው አውሮፓ የተሰባሰቡ ec_membersየማኅበሩ አባላት፣ በስዊድን የተለያዩ ከተሞች የሚያገለግሉ ካህናትና ምእመናን በተሳተፉበት በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ የማእከሉ የ2004 ዓ.ም. የአገልግሎት ሪፖርት ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። በውይይቱም ማእከሉ በአገልግሎት ዘመኑ አጠናክሮ የሰጣቸውን አገልግሎቶች በቀጣዩ ዓመትም አጠናክሮ እንዲቀጥልባቸው ሊፈጽማቸው ያቀዳቸው ነገር ግን በልዩ ልዩ ምክንያት መፈጸም ያልቻላቸውን ወይም ከታቀደው በታች ያከናወናቸውን አገልግሎቶች በሚቀጥለው ዓመት እንዲፈጽማቸው ውሳኔ አሳልፏል።

 

ማኅበረ ቅዱሳን በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ በተለይም በሬድዮ እየሰጠ ያለውን ሰፊ አገልግሎት ለመደገፍ ማእከሉ ባቋቋመው የሬድዮ ቤተሰብ አማካይነት እያደረገ ስላለው ድጋፍና ቀጣይ ሂደትም ተወያይቶ ጠቃሚ ውሳኔዎችን አሳልፏል። ከዚህም ጋር በዋናው ማእከል እየተተገበረ ያለው የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮጀክት በታቀደለት ጊዜና ዝርዝር ተግባራት መሠረት ይፈጽም ዘንድ ማእከሉ ባቋቋመው የድጋፍ ሰጪ አስተባባሪ ቡድን አማካይነት በመስጠት ላይ ስላለው ድጋፍ ሪፖርት ቀርቦ ጉባኤው ሰፊ ውይይት በማድረግ ልዩ ልዩ የማሻሻያ ውሳኔዎችን አሳልፏል።

 

ጉባኤው ማኀበረ ቅዱሳን በቅዱሳት መካናትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ድጋፍ ገዳማት ከሚያመርቷቸው ምርቶች የአውሮፓmk_eu_12th_anniversary ምእመናን ተጠቃሚ በሚሆኑበት ሁኔታ ላይም ተወያይቶ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ለተፈጻሚነታቸው በማእከሉ ስር ላለው ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ከባድ ኃላፊነት ሰጥቷል። የጉባኤውን ከፍተኛ ትኩረት አግኝቶ ሰፊ ውይይት የተደረገበት ሌላው አጀንዳ “የአውሮፓ ማእከል አባላት የአገልግሎት ሱታፌ ከማኀበረ ቅዱሳን ተልእኮ አንጻር” በሚል ርእስ የቀረበው ጥናት ነበር። በማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ በተቋቋመው ቡድን ተዘጋጅቶ የቀረበው ይህ ጥናት በሁሉም የአውሮፓ ሀገራት የሚገኙ አባላት በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ሥር ታቅፈው በመስጠት ላይ ያሉትን አገልግሎት የዳሰሰ፣ ጥንካሬዎችንና ድክመቶችን ነቅሶ ያወጣ፣ ወደፊት ሊደረግ የሚገባውን ያመላከተ ሰፊ ጥናት ነበር። ጉባኤው በጥናቱ ላይ ሰፊና ሞቅ ያለ ውይይት አድርጎ ውሳኔዎችን አሳልፏል።

 

ጉባኤው ከዋናው ማእከል የተላከለትን ሪፖርትና መልእክት በተወካዩ አማካይነት በማድመጥ ውይይት አድርጓል። ጉባኤው የማኀበራችንን 20ኛ ዓመት እንዲሁም የአውሮፓ ማዕከልን 12ኛ ዓመት የምሥረታ በዓል ማእከሉ በተመሠረተበት ሀገር በስዊድን በደመቀ ሁኔታ አክብሯል።

 

ga_2004_participantsበመጨረሻም ጉባኤው በቀረበለት የቀጣዩ የ2005 ዓ.ም. የአገልግሎት ዘመን ዕቅድ ላይ ተወያይቶ የማሻሻያ ዐሳቦችን በመስጠት ካጸደቀ በኋላ ማእከሉን ለቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት የሚመራ አዲስ የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ መርጦ የጉባኤው ፍጻሜ ሆኗል። ማእከሉ ስምንት የግንኙነት ጣቢያዎች እና አምስት ቀጠና ማእከላት ያሉት ሲሆን በስዊድን ቀጠና ማእከል የተዘጋጀው የዘንድሮው ጉባኤ የተሳካ እንደነበር የጉባኤው ተሳታፊዎች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል። ቀጠና ማእከሉ ለጉባኤው መሳካት አስተዋጽዖ ያደረጉትን አባላትና ምእመናን እንዲሁም ተቋማት በተለይ ጉባኤው በተመቼ ሁኔታ ይካሄድ ዘንድ መሰብሰቢያ አዳራሽና የተሳታፊዎችን ማረፊያ ቤት ከሙሉ አገልግሎት ጋር በነጻ የሰጠውን በብሬድንግ የስዊድን ቤተ ክርስቲያን አመስግኗል።

 

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን።

hitsanat

ልዩ የሕፃናት መርሐ ግብር ተዘጋጀ

ሐምሌ 10 ቀን 2004 ዓ.ም.

በፍጹም ዓለማየሁ

hitsanat

በ12 የአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የጋራ ጥምረት እና በአፍሪካ ኅብረት ደብረ ምሕረት ቅዱስ ሚካኤል ካቴድራል ሰንበት ትምህርት ቤት አዘጋጅነት ለሕፃናት የሚሆን መርሐ ግብር ተዘጋጅቷል፡፡ መርሐ ግብሩ ከሐምሌ 12-15/2004 ዓ.ም. ለአራት ቀናት የሚካሄድ ሲሆን በሦስቱ የመጀመሪያ ቀናት “ዝክረ ቅዱሳን ሕፃናት በልሣነ ሕፃናት” በሚል መሪ ቃል በአስተናጋጅ ሰንበት ትምህርት ቤት ሕፃናት የተዘጋጀ ዐውደ ርዕይ ይቀርባል፡፡ ከመርሐ ግብሩ አስተባባሪዎች እንደተረዳነው ሐሙስ ሐምሌ 12 ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት የሚከፈተው ይህ ዐውደ ርዕይ የሕፃናቱን የእደ ጥበብ ውጤቶች ጨምሮ 8 ክፍሎች ይኖሩታል፡፡

በተጨማሪም በመርሐ ግብሩ ማጠናቀቂያ ሐምሌ 15 ዕለተ እሑድ ከቀኑ 6፡00 ጀምሮ በሚካሄደው “ዝክረ ቅዱስ ቂርቆስ ወሕፃናት” በተሰኘው የሕፃናት ጉባኤ፣ በመርሐ ግብሩ ተሳታፊ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ሕፃናት የተዘጋጀ ወረብ፣ መንፈሳዊ ቅኔ፣ የኪነ ጥበብ ፍሬዎች በተጨማሪም በሕፃናቱ የተዘጋጀ ስለ ቅዱስ ቂርቆስ ተራኪ የሆነ ፊልም የሚቀርብ ሲሆን በሥዕል የተደገፈ የሕፃናት መጽሐፍ በዕለቱ ይመረቃል፡፡ በዕለቱም ቅዱሳን ሊቃነ ጳጳሳትና የደብር አስተዳዳሪዎች እንደሚገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዕለቱም ሕፃናት ልጆችዎን ይዘው በመርሐ ግብሩ ላይ እንዲገኙ የመርሐ ግብሩ አስተባባሪዎች ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

“ከሁሉ በላይ በምትሆን፤ ሐዋርያት በሰበሰቧት፤ በአንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም እናምናለን”

ሐምሌ 10 ቀን 2004 ዓ.ም.


ይህ አንቀጸ ሃይማኖት የጉባኤ ቁስጥንጥንያ አንቀጸ ሃይማኖት ነው፡፡ የእውነተኛዋ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መታወቂያ ትእምርትም ነው፡፡ ይህን አጉድሎ መገኘት የቤተ ክርስቲያንን ሕግና ሥርዐት ማፍረስ ብቻ ሳይሆን እምነትንም እንደማጉደል ይቆጠራል፡፡ እንዲህ ዐይነት ማንነታዊ ተክለ ቁመናን ገንዘብ ያደረገ ግለሰብም ሆነ ማኅበር ራሱን የክርሰቶስ አካልና አባል አድርጎ አለመቀበሉን ያሳየናል፡፡ በክርስቶስ ብቻ አምኖ በግለኝነት መኖር በቂ አይደለም፡፡ የክርስቶስ አካል በሆነችው ሐዋርያት በሰበሰቧት፣ በአንዲት፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም አምኖ አባል መሆን ሃይማኖታዊ ግዴታ ነው፡፡

 

ይሁንና ይህን አንቀጸ ሃይማኖት ያለ ዐውዱና ከተሸከመው መልእክት ውጪ በመለጠጥና አዲስ የትርጓሜ ቅርጽ በመስጠት በፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ መናፍቃን ቅላጼና ወዝ “ማኅበራት አያስፈልጉም” የሚል እና ራሱን “ጉባኤ አርድእት ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ” ብሎ የሚጠራ የቤተ ክርስቲያናችን ሕመም የሆነ ቡድን ያለ ቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅናና ይሁንታ ከሰሞኑ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት መሽጎና የተለያዩ ስብሰባዎችን እያካሄደ እንደሚገኝ ማረጋገጥ ችለናል፡፡

 

ይህን ተከትሎም ከሰሞኑ የመንበረ ፓትርያርኩ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ምንም ዓይነት ስብሰባ ያለ ቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና በግቢ ውስጥ እንዳይካሄድ የሚከለክል ደብዳቤም ለሚመለከታቸው አካላት ማሰራጨቱንም ለማወቅ ችለናል፡፡

 

የዚህ የጥፋት ቡድን ዋነኛ ዓላማም ራሱን የቤተ ክርስቲያኒቱ ተቆርቋሪ አድርጎ በመሰየም እና በተቆርቋሪነት ሽፋን ሐዋርያት የሰበሰቧትን አንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መከፋፈልና የዚሁ ግብር ተዳባይ የሆኑትን እውነተኛ ማኅበራት ህልውና ማክሰምና ጥብዓት ያላቸውን ብፁዓን አበውንና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን መገዳደር ነው፡፡

 

እንዲህ ዐይነቱን የጥፋት ዓላማ ያነገበው እና “ማኅበር አያስፈልግም” እያለ ራሱን ወደ ማኅበርነት ለማሳደግ ዕቅድ ይዞ የሚንሳቀሰው ቡድን የጠቅላይ ቤተ ክህነቱን ጥቂት የመምሪያ ሓላፊዎችንንና ሠራተኞችን እንዲሁም በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚሠሩ ግለሰቦችን በመሰብሰብ በመመሥረቻ ሰነዱ ላይ ማስፈረሙንም ከሰነዱ ለማወቅ ችለናል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ አብዛኞቹ ስብሰባው ላይ በመገኘት የጥፋት ግንባሩ የተደራጀበት መንገድና ዓላማ ለቤተ ክርስቲያን አደጋ እንዳለው አቋማቸውን ገልጠው የወጡ እንዳሉም መገንዘብ ችለናል፡፡

 

የአደራጆቹን ማንነት ስንመለከት ደግሞ ያው መልኩንና ስልቱን በየጊዜው የሚቀያይረው የፕሮቴስታንታዊ ተሐድሶ ኑፋቄ ሰለባ የሆኑ ግለሰቦች መሆናቸውንም አረጋግጠናል፡፡ እየተጓዙበት ያለው የጥፋት መንገድም የተለመደው የተሐድሶ መናፍቃን ስልተ መንገድ ነው፡፡

 

እናም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሁለት ሺሕ ዓመት ታሪክ ያላት ጥንታዊት ቤተ ክርሰቲያን ትሁን እንጂ መንበሯን ከሊቀ ጵጵስና ወደ ፕትርክና ለማሳደግ አንድ ሺሕ ስድስት መቶ መራራ ዓመታትን ገፍታለች፡፡ በዚህ ማለፏ ደግሞ ሌሎች አኀት አብያተ ክርስቲያናት የደረሱበት የአደረጃጀት ችግር እንዳጋጠማትና ልጆቿን ጊዜው በሚጠይቀው መንገድ ለመሥራት የሚያስችላትን አካሄድ እንዳትጠቀም አድርጓት መቆየቱን በሚገባ እንገነዘባለን፡፡

 

ያለማቋረጥ የተደራረበባት ችግር ሐዋርያዊ ተልእኮዋን እንዳዳከመውና ሊቃውንቷንም ተጠራጣሪና ተከላካይ ብቻ እንዳደረጋቸው ሁሉ የራሷ ሲኖዶስ ሳይኖራት ለረጅም ዓመታት መምጣቷም አሁን ያሉባት ችግሮች የአሁን ብቻ ላለመሆናቸው ጠቋሚ መሆናቸውንም እንረዳለን፡፡

 

እነዚህን ዘመናትን ተሻግረው የመጡ ችግሮች ደግሞ ገና ለጋ ለሆነውና የሃምሳ ዓመታት ተሞክሮ ላለው ቤተ ክህነት ብቻ ትቶ “ብትችል ተወጣው፣ ባትችል የራስህ ጉዳይ” የሚያሰኝ አለመሆኑንም መረዳት ያስፈልጋል፡፡

 

እንኳን የእኛ ቤተ ክርሰቲያን በጠንካራ ሲኖዶስ በመምራትና በሠለጠኑና በተማሩ አማኞቿ የምትታወቀው የግብጽ ቤተ ክርስቲያን በሃያኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ላይ ለተደቀነባት የዓለማዊነትና የፕሮቴስታንት ተሐድሶ ፈተና፣ የርእይ ብዥታና የአስተዳደር ለውጥ ታላቁን አዎንታዊ ድጋፍ ያገኘችው በዘመኑ በነበረው ሊቀ ሐቢብ ጊዮርጊስ አደራጅነት ከተቋቋሙት ማኅበራት እንደነበረም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

 

ይህ ሊቅ አሁን ባለው የግብጽ ሲኖዶስም ታላቅ ከበሬታ ያለውና እርሱ ባስጀመረው እንቅስቃሴ ቤተ ክርስቲያኒቱ በአሁኗ የኢስላም ሀገር ግብጽ ላይ ታላቅ ሚና እንድትጫወትና ከዓለም ሁሉ የሚመጡባትን ፈተናዎች ተቋቁማ ብቻ ሳይሆን ድል እያደረገች እንድትጓዝ አስችሏታል፡፡

 

በተሳሳተና በፈጠራ መረጃ የተሳከሩት የዚህ የጥፋት ቡድን አደራጆች ሊረዱት የሚገባው ነጥብ፤ ለጠንካራዋ የግብጽ ቤተ ክርስቲያን የማኅበራት አስፈላጊነት ይህን ያህል ከሆነና የሶርያና የሕንድ አብያተ ክርስቲያናት ከመቶ ዓመት በፊት ጀምረው ማኅበራትን በዘመናዊ መንገድ እያቋቋሙ ተጠቃሚ ከሆኑ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንማ እንዴት አያስፈልጓት? አንድ ብቻ አይደለም ገና ብዙ ማኅበራት ያስፈልጓታል፡፡

 

ማኅበራቱም ከሁሉ በላይ በምትሆን ሐዋርያት ለሰበሰቧት፤ ለአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግብ የሚንቀሳቀሱ፣ ተልእኮአቸውና ዓላማቸው ተለይቶ የሚታወቅ፣ መንፈሳዊ ተግባርን ብቻ የሚፈጽሙ፣ የሚናበቡና በስልት ለአንድ ውጤት የሚተጉ ሊሆኑ እንደሚገባም እናምናለን፡፡

 

ቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና ሰጥታቸው የሚንቀሳቀሱ ማኅበራትም አስፈላጊነትም የሚነሣው ከዚሁ ነጥብ መሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምትመራበት ቃለ ዓዋዲ የተገለጡትን የወጣቶች ተግባራት መፈጸም እንደተጠበቀ ሆኖ የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ያልሸፈናቸውን ክፍተቶች ለመሙላት ከማገዝ አንጻር አይደለም አንድና ሁለት ማኅበራት የሌሎች ተጨማሪ ማኅበራት አስፈላጊነት ለድርድር የሚቀርብ አለመሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

 

ሐዋርያት የሰበሰቧት አንዲት፣ ቅድስትና ኲላዊት የሆነችው ቤተ ክርስቲያናችን ሦስተኛውን ሺሕ ዘመን እንድትዘልቅ፣ ገዳማትንና አድባራትን የልሂቃን ምንጭ እና የልማት ማእከላት ለማድረግ የሚሠሩ፣ የአብነት ትምህርት ቤቶችንና መንፈሳዊ ኮሌጆቻችን ዘመናዊ ትምህርትን በመጨመር የሚሰጡ የእውቀት ማእከላት ለማድረግ የሚጥሩ፣ ሁለገብ ዕውቀት ያላቸውና ችግር ፈቺ ካህናትን ለማፍራት የሚደረገውን ጥረት የሚያግዙ፣ ዘመናዊ አስተዳደርን በቤተ ክህነቱ በመዘርጋት ተየያዥ ችግሮችን ሁሉ ለመፍታትና ግንዛቤው ያደገና በዕውቀት የበለጸገ ምእመን ማፍራት ግባቸው ያደረጉ በርካታ ማኅበራት ለቤተ ክርሰቲያን ያስፈልጓታል እንላለን፡፡

 

በአንጻሩ ደግሞ “ከሁሉም በላይ በምትሆን፤ ሐዋርያት በሰበሰቧት፤ በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርሰቲያን” ሳያምኑ እኲይ ዓላማቸውን ለማስፈጸም ቤተ ክርስቲያኒቷን ጥግ ያደረጉትን እንደ ሰሞኑን የተሐድሶ መናፍቃን መልክ ያሉትን የጥፋት ቡድኖች ደግሞ እንደ ትናንቱ ሁሉ ዛሬም በሃይማኖታዊ ጥብዓት የምንታገላቸው መሆኑን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

 

ብፁዓን አባቶቻችንም ቀኖና ቤተ ክርስቲያንን እና ሕገ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት አድርገው በፕሮቴስታንታዊ የተሐድሶ ኑፋቄ አራማጆችና እንዲሁም አቀንቃኝ ድርጅቶችና ግለሰቦች ላይ የማያዳግም ውሳኔ ይወስናሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡

 

በተለይ ያለ ይሁንታችሁ እና ባለማወቅ የዚሁ የጥፋት ግንባር አባላት ተደርጋችሁ ስማችሁ የተዘረዘረ የቤተ ክርሰቲያናችን ሊቃውንትም ሆነ የመምሪያ ሓላፊዎች ጊዜው ሳይረፍድ ከዚህ የጥፋት ቡድን ራሳችሁን ነጻ በማድረግ ለቤተ ክርስቲያናችሁ ጥብቅና ትቆሙ ዘንድ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

 

ምእመናንም በየሰነዶቻቸው “ከሁሉም በላይ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰቧት፤ በአንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን” እያሉ ግብራቸው እንደማያምኑ ከገለጠባቸው የጥፋት ቡድኖች ራሳችሁን፣ ቤተሰቦቻችሁንና አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናችሁን ትጠብቁ ዘንድ ጊዜ አሁን ነው እንላለን፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን እንደ መንፈሳዊ ተቋምነቱ፤ አባላቱ ደግሞ እንደ አማኝነታቸው ትናንትም ሆነ ዛሬ እንዲሁም ነገ “ከሁሉ በላይ በምትሆን፤ ሐዋርያት በሰበሰቧት በአንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ማመን ብቻ ሳይሆን መስዋዕትነት እየከፈሉና የሚከፍሉባት ቤታቸው መሆኗንም ጠንቅቀው እንደሚያውቁ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

 

ማኅበሩም ሆነ አባላቱ ቤተ ክርስቲያናቸውን በዕውቀታቸውም ሆነ በገንዘባቸው የሚያገለግሉ እንጂ እንደ  ጥፋት ቡድኑ አፈ ቀላጤዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን ገንዘብ እየበሉ ቤተ ክርስቲያኒቱን በገዛ ገንዘቧ ለማፍረስ በመናፍቃን ደጅ የሚጠኑ አለመሆናቸውን እነዚሁ አካላት /እውነቱ እየመረራቸውም ቢሆኑ/ ሊያውቁ ይገባል፡፡

 

እንግዲህ ቤተ ክርስቲያን አማኞች እንዲድኑባት ያዘጋጀ እግዚአብሔር ነው፡፡ በክርስቶስ መሠረትነት፣ በመንፈስ ቅዱስ አደራጅቶና ቀድሶ እውነተኛይቱን ቤተ ክርስቲያን ሠርቷታል፤ አቋቁሟታል፡፡፡ ስለዚህ እኛም እንደ ዝግጅት ክፍልም ሆነ እንደ አማኝ ከሁሉም በላይ በምትሆን ሐዋርያት በሰበሰቧት፤ በአንዲት፤ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም እናምናለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ 19ኛ ዓመት ቁጥር 20/2004 ዓ.ም.

ቅዱስ ጴጥሮስ እና ቅዱስ ጳውሎስ

 
ዲያቆን ታደሰ ወርቁ
 
እነዚህ ሁለት ቅዱሳን አባቶቻችን የቅድስት ቤተክርስቲያናችን አዕማድ ናቸው፡፡ በመሠረትነት በአጸኗት ቤተክርስቲያን ያላቸው የክብር ሥፍራ ላቅ ያለ ነው፡፡ ይህ የሆነው እንዲሁ አይደለም፡፡ ለቤተክርስቲያንና በቤተክርስቲያን የፈጸሙት አገልግሎት በዚህም የተቀበሉት ሰማዕትነት ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም ይህን መልካም የሆነውን ታሪካቸውን ለእኛ አርአያነት በሚሆን መልኩ ከትበውልናል፡፡ እኛም ለአርአርያነት በሚሆን መልኩ የእነዚህን ደጋግ ሁለት ቅዱሳን አባቶች ታሪክ፣ ዕውቀትና መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን ከዚህ በመቀጠል አቅርበናል፡፡
 
 
1. ሁለቱ ሐዋርያት ሲጠሩ የነበሩበት ሕይወት
 
ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በገሊላ ባሕር ዳር በምትገኘው በቤተ ሳይዳ ሲወለድ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ ደግሞ በጠርሴስ ከተማ ተወለደ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር በገሊላ ባሕር ዓሣ ማሥገር ጀመረ፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ ደግሞ በ 15 ዓመት ዕድሜው በገማልያ ትምህርት ቤት በመግባት የአይሁድን ሕግና ሥርዓት ተምሯል፡፡ በ30 ዓመቱም የአይሁድ ሸንጎ አባል ሆኗል፡፡ /1ቆሮ.1.17፤ሐዋ.22.3/
 
ቅዱስ ጴጥሮስ ባለትዳር ሲሆን ቅዱስ ጳዉሎስ ደግሞ በድንግልና የኖረ አባት ነው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ሕጋዊ /ባለ ትዳር/ ሆኖ ይኖር እንደነበር በማቴዎስ ወንጌል ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የጴጥሮስን አማት ማዳኑ መጠቀሱ አመላካች ሲሆን ጳዉሎስ ድንግል ስለመሆኑ ደግሞ ራሱ ለቆሮንቶስ ምእመናን በጻፈው ላይ ያረጋገጠው ነው፡፡ /ማቴ.8.14-15፣ 1ቆሮ.7.8፣9.5/  ይህም ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያገቡትንም ሆነ በድንግልና የሚኖሩትን ለአገልግሎት እንደሚቀበል አመላካች መሆኑን ልብ ይሏል፡፡
 
2. የሁለቱ ሐዋርያት ተክለ ቁመና
 
ቅዱስ ጴጥሮስ ፊቱ ሰፋ ያለ ሲሆን መካከለኛ ቁመት የነበረው፤ ራሰ በራ ሰው ነው፡፡ በማናቸውም ነገር ፈጣንና ቀልጣፋ ነበር፡፡ ቅዱስ ጳዉሎስ ደግሞ ጭንቅላቱ ትልቅ ሲሆን ራሰ በራ ነበር፡፡ የሁለቱም ቅንድቦቹ ጠጉር የተጋጠሙ፤ ዓይኖቹ ሰማያዊ ቀለም ያላቸው ሲሆኑ ዘወትር ብሩሃን ነበሩ፡፡ አፍንጫው ትልቅና ቀጥ ብሎ የወረደ ጽሕሙና ሪዙም ረጃጅም ናቸው፡፡ አንገቱ አጠር ያለ ሆኖ ትከሻው ክብና ጎባባ፤ ቁመቱም አጠር ያለ እንደነበር ይነገርለታል፡፡ /ቤተ ክርስቲያንህን ዕወቅ ገጽ. 65 እና 125/
 
3.የእግዚአብሔር ጥሪ እና የሁለቱ ሐዋርያት መልስ
 
እግዚአብሔር አምላክ የሰውን ዘር በሙሉ ለቅድስና፣ ለምግባር፣ ለትሩፋትና ለሰማዕትነት በተለያዩ ዘመናት ጠርቷል፡፡ ጥሪውን አድምጠው የተጠሩበትን ዓላማ ተረድተው፤ እንደ እርሱ ፈቃድ የተጓዙ ጥቂቶች ናቸው፡፡ /ማቴ.22.14/ ከጥቂቶቹም መካከል ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳዉሎስ ዋነኞቹ ናቸው፡፡
 
እነዚህ ሁለት የቤተክርስቲያን ፈርጥ የሆኑ ሐዋርያት ለአገልግሎት የተጠሩበት መንገድ ለየቅል ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ከወንድሙ ከእንድርያስ ጋር በገሊላ ባሕር ልዩ ስሟ ጌንሴሬጥ በምትባል መንደር ዓሣ ያሠግሩ ነበር፡፡ በዚህን ወቅት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «በኋላዬ ኑና ሰዎችን አጥማጆች እንድትሆኑ አደርጋችኋለሁ፡፡» በማለት ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስን ከወንድሙ ጋር   ጠራው፡፡ /ማቴ.4.18/ በዚህ ጥሪ መሠረትም መተዳደሪያው የነበረውን መረቡንና ታንኳውን እንዲሁም አባቱን ትቶ ጌታውን ተከተለ፡፡ ለሐዋርያነት አገልግሎት ሲታጭ ዕድሜው 55 ዓመት እንደነበርም ይነገራል፡፡ /ዜና ሐዋርያት ገጽ. 3-15/
 
ምንም እንኳን ቅዱስ ጳዉሎስ ከቅዱስ ጴጥሮስ ጋር የተጠራበት የአገልግሎት ዓላማ አንድ ቢሆንም የተጠራበት መንገድ ከቅዱስ ጴጥሮስ በእጅጉ ይለያል፡፡ ይኸውም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያስተምርበት ዘመን ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ ከጌታ ጋር አልነበረም፤ ቀጥታ ከጌታም አልተማረም ነበር፡፡ በወቅቱ ግን በኢየሩሳሌም ስለነበረ የጌታን አገልግሎት ያውቅ ነበር፡፡ ለኦሪታዊ እምነቱ ቀናተኛ በመሆኑ ክርስቲያኖችን በማናቸውም አጋጣሚ ይቃወም ነበር፡፡ በ32 ዓመት ዕድሜውም ከኢየሩሳሌም ሁለት መቶ ሃያ ሦስት ኪሎ ሜትር ርቀት በስተሰሜን በኩል በምትገኘው የደማስቆ ከተማ ብዙ ክርስቲያኖች መኖራቸውን ሲሰማ፤ ክርስቲያኖችን ለማሳደድ የሚያስችለውን የፈቃድ ደብዳቤ    ከባለሥልጣናቱ አገኘ፡፡
 
እርሱም ክርስቲያኖችን ለማሳደድ ወደ ደማስቆ ከተማ አመራ፡፡ በዚያም ከሰማይ ብርሃን ወረደ፡፡ የወረደውም የብርሃን ነጸብራቅ ቅዱስ ጳዉሎስን ከመሬት ላይ ጣለው፡፡ በብርሃኑ ውስጥም «ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛልህ)» የሚለውን አምላካዊ ድምፅ አሰማው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስም «ጌታ ሆይ ማን ነህ)» ብሎ ጠየቀ፡፡ ለጠየቀውም ጥያቄ «አንተ የምታሳድድኝ እኔ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ፡፡» የሚል  መልስ አገኘ፡፡ ቅዱስ ጳዉሎስም በወደቀበት ሆኖ እየተንቀጠቀጠ «ጌታ ሆይ ምን አደርግ ዘንድ ትወዳለህ)» ሲል ከእርሱ    የሚጠበቀውን ግዴታውን ጠየቀ፡፡ ጌታም ተነሥቶ ወደ ደማስቆ እንዲገባና ማድረግ የሚገባውን ወደሚነግረው ወደ ካህኑ ሐናንያ ላከው፡፡ /የሐዋ.9.1/
 
ቅዱስ ጳዉሎስም በዚህ መልኩ የእግዚአብሔርን የአገልግሎት ጥሪ ተቀብሎ በካህኑ ሐናንያ እጅ   ተጠምቆ ወደ ሐዋርያነት ኅብረት ተቀላቀለ፡፡ አስቀድመን እንደተመለከትነው ቅዱስ ጴጥሮስ የቀደመ ግብሩን እርግፍ አድርጎ ትቶ፣ ጌታን እንደተከተለ ሁሉ ቅዱስ ጳውሎስም የቀደመ የጥፋት ግብሩን በመተው የጌታ ተከታይ የሆኑትን ወንድሞቹን ሐዋርያትን ተቀላቀለ፡፡ እንደ እነርሱም ለጌታ ጥሪ ተገቢውን መልስ ሰጠ፡፡
 
ቅዱስ ጳወሎስ የተጠራው ሦስት ጊዜ ነው፡፡ የተጠራው በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም ነው፡፡ የእርሱ ጥሪ በአብ ስም የተከናወነው በእናቱ ማኅፀን ነው፡፡ ይህንንም ራሱ ቅዱስ ጳዉሎስ ሲገልጽ «ነገር ግን በእናቴ ማኅፀን ሳለሁ የለየኝ፤ በጸጋውም የጠራኝ፤ እግዚአብሔር በአሕዛብ መካከል ስለ እርሱ ወንጌልን እሰብክ ዘንድ በእኔ ልጁን በእኔ ሁኔታ ሊገልጥ በወደደ ጊዜ ወዲያው ከሥጋና ከደም ጋር አልተማከርሁም፤» በማለት ነው፡፡ በዚህም አብ እግዚአብሔር በሚለው አምላካዊ ስሙ እንዳጠራው በምስጢር እንረዳለን፡፡ /ገላ.1.15-16/ ሌላኛው ጥሪ ደግሞ በወልድ የተከናወነው ነው፡፡ አስቀድመን እንደገለጽነው እግዚአብሔር ወልድ በደማስቆ ጎዳና ላይ «ሳውል ሳውል ለምን ታሳድደኛለህ የምታሳድደኝ እኔ ኢየሱስ ነኝ» ብሎ ከገሰጸው በኋላ ወደ ካህኑ ሐናንያ በላከው ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅትም ጌታ ቅዱስ ጳዉሎስን ለምን እንደመረጠው ለካህኑ ሐናንያም ሲያስረዳ «ይህ በአሕዛብም በነገሥታትም በእስራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ ነውና፤» በማለት ነው፡፡ /የሐዋ.9.15/
 
ቅዱስ ጳዉሎስ ከአብና ከወልድ ባሻገር በመንፈስ ቅዱስም ለአገልግሎት የተመረጠ ነው፡፡ ይህም የሆነው መንፈስ ቅዱስ ለአባቶቻችን «በርናባስንና ሳዉልን ለጠራኋቸው ሥራ ለዩልኝ» /ሐዋ.13.21/ ባለበት ወቅት እና እንዲሁም «በዚያን ጊዜም ከጦሙ፤ ከጸለዩም፤ እጃቸውንም ከጫኑ በኋላ አሰናበቱአቸው፡፡ እነርሱም በመንፈስ ቅዱስ ተልከው ወደ ሰሌውቅያ ወረዱ፤» በሚለው  አምላካዊ ቃል መሠረት ነው፡፡ /የሐዋ.13.3-4/ በመሆኑም የቅዱስ ጳዉሎስ መጠራት ከጥሪነት ባሻገር ምሥጢረ ሥላሴ የተገለጠበት ነው፡፡ በእርሱ መመረጥ ውስጥ የቅድስት ሥላሴ ልዩ አንድነትና ሦስትነት ተገልጧል፤ /ተመስክሯል/፡፡
 
4. የአገልግሎት ምድባቸው
 
ግብረ ሐዋርያት የሚጀምረው በቅዱስ ጴጥሮስ ሥራ ሲሆን የምዕራፉም መጨረሻ የሚጠናቀቀው በቅዱስ ጳዉሎስ አገልግሎት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ቅዱስ ጴጥሮስ አይሁድን /የተገረዙትን/ በአባትነት እንዲጠብቅ ሲሾም በተመሳሳይ መልኩ ደግሞ ቅዱስ ጳዉሎስ አሕዛብን /ያልተገረዙትን/ እንዲጠብቅና እንዲያስተምር ተሹሞ ነበር፡፡ ስለዚህም ነገር ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ሰዎች በጻፈው መልእክቱ «… ጴጥሮስ ለተገረዙት የሆነው ወንጌል አደራ እንደተሰጠው እንዲሁ ለእኔ ላልተገረዙት የሆነው ወንጌል አደራ እንደተሰጠኝ እዩ፤ ለተገረዙት ሐዋርያ እንድሆን ለጴጥሮስ የሠራለት ለእኔ ደግሞ ለአሕዛብ ሐዋርያ እንድሆን ሠርቶአልና፡፡» በማለት ነው የገለጸው፡፡/የሐዋ.2.7-9/
 
በዚሁ ምድባቸው መሠረት ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በኢየሩሳሌም፣ በአንጾኪያ፣ በይሁዳና በሰማርያ እንዲሁም በስደት ላሉ አይሁድ መንግሥተ እግዚአብሔርን ሲሰብክ ቅዱስ ጳዉሎስ ደግሞ በቆጵሮስ፣ በመቄዶንያ፣ በግሪክ፣ በተሰሎንቄ በፊልጵስዩስ፣ በቆሮንቶስ፣ በኤፌሶን፣ በሮምና በሌሎችም ቦታዎች ሰብኳል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስና ጳዉሎስ እነዚህን አካባቢዎችና በእነዚህ አካባቢዎች የሚኖሩትን ሕዝብና አሕዛብ ተከፋፍለው ሲያስተምሩ የየራሳቸውን አካባቢያዊ ተጨባጭ ሁኔታ ይጠቀሙም ነበር፡፡
 
ቅዱስ ጴጥሮስ የአይሁድ መምህር እንደመሆኑ መጠን በስብከቱና በጻፈው መልእክቱ አዘውትሮ ከብሉይ ኪዳንና ከመዝሙረ ዳዊት የተለያዩ ጥቅሶችን ይጠቀም ነበር፡፡ ሐዋርያት በይሁዳ ምትክ ሌላ ሰው ለመምረጥ በተገናኙ ወቅት ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ ስለ እርሱ በመዝሙር መጽሐፍ «መኖሪያው ምድረ በዳ ትሁን፤ የሚኖርባትም አይኑር፤ ደግሞም ሹመቱን ሌላ ይውሰዳት ተብሎ ተጽፎአል፡፡» በማለት ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊት የተናገረውን ጠቅሶ ተናግሯል፡፡ /የሐዋ.1.20-22፣ መዝ.68.25፣ መዝ.108.8/
 
ከዚህም በተጨማሪ ቅዱስ ጴጥሮስ በበዓለ ሃምሳ መንፈስ ቅዱስ በሐዋርያቱ ላይ ከወረደ በኋላ ነቢየ እግዚአብሔር ኢዩኤል ስለ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በምዕራፍ 2.2-32 ላይ የተናገረውን ጠቅሶ ጽፏል፡፡ ይኸውም «እግዚአብሔር ይላል- በመጨረሻው ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፣ ጎበዞቻችሁም ራእይ ያያሉ፣ ሸማግሌዎቻችሁም ህልም ያልማሉ፤ ደግሞም በዚያች ወራት በወንዶችና በሴቶች ባሪያዎቼ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ፤ ትንቢትም ይናገራሉ፡፡. .. » የሚለውን ነው፡፡ /የሐዋ.2.17-21/ እንዲሁም በተመሳሳይ መልኩ ቅዱስ ጴጥሮስ ከመዝሙረ ዳዊት ጠቅሶ ተናግሯል፡፡ ይኸውም «ዳዊትም ስለ እርሱ /ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ/ እንዲህ አለ- እግዚአብሔርን ሁልጊዜ በፊቴ አየዋለሁ፤ እንዳልታወክ በቀኜ ነውና፡፡ ስለዚህ ልቤን ደስ አለው፤ አንደበቴም ሐሴት አደረገ፤ ሥጋዬም ደግሞ በተስፋው አደረ፡፡ ነፍሴን በሲኦል አትተዋትምና፣ ጻድቅህንም ጥፋትን ያይ ዘንድ አትሰጠውምና፡፡» የሚለውን በመዝሙር 15.8 የሚገኘውን ሲሆን፤ ይኽም በጌታ መፈጸሙን ለማረጋገጥ የጠቀሰው ነው፡፡
 
ከዚህም በተጨማሪ ቅዱስ ጴጥሮስ ከብሉይ ኪዳን በመጥቀስ የተለያዩ ጥቅሶችን በሁለቱ መልእክታት ላይ ተጠቅሟል፡፡ በሌላ መልኩ ደግሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክታቱ ውስጥ የብሉይ ኪዳን ጥቀሶችን እምብዛም አልጠቀሰም፡፡ ጠቀሰ ቢባል በዕብራውያን መልእክቱ ብቻ ነው፡፡ ይህ ከብሉይ ኪዳን ጥቅሶች መጥቀስና አለመጥቀስ የተከሰተው የትምህርታቸው የትኩረት አቅጣጫ ከሆኑ ሕዝብና አሕዛብ አኳያ መሆኑንን ልብ ይሏል፡፡
 
5. ጌታ እና ሁለቱ ሐዋርያት
 
ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት አንዱ ሲሆን ቅዱስ ጳዉሎስ ደግሞ ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያትና ከሰባ ሁለቱ አርድእት ወገን አይደለም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ከዐሥራ ሁለቱ ሐዋርያት ወገን መሆኑ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር እንዲገናኝ አድርጎታል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ከጌታ ጋር ኖሯል፤ በልቷል ጠጥቷል፡፡ እንዲሁም ከዘመነ ሥጋዌው እስከ ዕርገቱ አብሮት በመሆን የቃሉን ትምህርት እና ስብከቱን አድምጧል፤ የእጁን ተአምራት በዐይኑ ዐይቷል፡፡
 
ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ ግን ይህን ዕድል በወቅቱና በጊዜው እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ አላገኘም፡፡ እርሱ በዚያን ወቅት ቤተክርስቲያንን ያሳድድ ነበር፡፡ /1ጢሞ. 1.13/ በኋላ ግን ቅዱስ ጳዉሎስ በአሳዳጅነቱ አልቀጠለም፡፡ በዚህም ክርስቶስን አወቀው፤ በራእይም ተመልክቶት ነበር፡፡ ምንም እንኳን ጌታ እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በአካል ባያገኘውም በደማስቆ በብርሃን አምሳል ተገልጦ አነጋግሮታል፡፡ /የሐዋ. 9.1/ በቆሮንቶስም በምሽት በራእይ ተገልጦለት አነጋግሮታል፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ «ጌታም በራእይ ጳዉሎስን እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፣ ማንም ክፉ ሊያደርግብህ የሚነሣብህ የለምና አትፍራ፤ ነገር ግን ተናገር፤ ዝምም አትበል፤ በዚህ ከተማ ብዙ ሕዝብ አሉኝና አለው፡፡» እንዲል፡፡ /የሐዋ.18.10/
 
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልክ እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በአካለ ሥጋ አግኝቶት ቅዱስ ጳዉሎስን ባያነጋግረውም ከዚህም በተጨማሪ በኢየሩሳሌም በቤተ መቅደስ ጸሎት ሲያደርስ ተገልጦ አነጋግሮታል፡፡ ቅዱስ መጽሐፍ ይኽን ሲገልጽ «ወደ ኢየሩሳሌምም ከተመለስሁ በኋላ በመቅደስ ስጸልይ ተመስጦ መጣብኝ፣ እርሱም ፍጠን ከኢየሩሳሌምም ቶሎ ውጣ፣ ስለ እኔ የምትመሰክረውን አይቀበሉህምና ሲለኝ አየሁት፡፡ … ሒድ እኔ ወደ አሕዛብ ከዚህ ወደ ሩቅ እልክሃለሁ አለኝ፡፡» በማለት ነው፡፡ /የሐዋ.22.17-21/
 
ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ጴጥሮስን ለአገልግሎት ከመረጠው በኋላ አብሮት ስላለ በየጊዜው ያበረታታው ነበር፡፡ እንዲሁም ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስን በራእይ እየተገለጠለት ያጽናናው ያበረታውም ነበር፡፡ በአንድ ወቅት ጌታ በኢየሩሳሌም በሁለተኛው ሌሊት በአጠገቡ ቆሞ «ጳዉሎስ ሆይ፣ በኢየሩሳሌም ለእኔ እንደመሰከርክ እንዲሁ በሮሜም ትመሰክርልኝ ዘንድ ይገባሀል፤ አይዞህ» በማለት አዝዞታል፤ አጽናንቶታል፡፡/የሐዋ.23.11/
 
 
6. የጴጥሮስ እና የጳዉሎስ መልእክታት
 
እንግዲህ የቅዱስ ጴጥሮስና የቅዱስ ጳዉሎስ ከጌታ ጋር ያላቸው ግንኙነት ይህን ይመስላል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ከጌታ ትምህርቱን፣ ምክሩንና ተግሣጹን ቀጥታ ያገኘ ቢሆንም ቅዱስ ጳዉሎስም የጌታ ትምህርቱ፣ ምክሩና ተግሣጹ አልቀረበትም፡፡ በዚሁ መሠረት የመልእክቶቻቸውንም ጭብጥ ከዚህ ዐውድ አኳያ መመልከቱ ተገቢ ነው፡፡ የትምህርት ትኩረት አቅጣጫዎቻቸው ከምን አንፃር እንደሆነም ማስተዋል ይቻላል፡፡
 
በመሆኑም ቅዱስ ጴጥሮስም ሆነ ቅዱስ ጳዉሎስ የጻፉት ወንጌልን ሳይሆን መልእክታትን ነው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ሁለት መልእክታትን ሲጽፍ ቅዱስ ጳዉሎስ ዐሥራ አራት መልእክታትን ጽፏል፡፡ የአጻጻፍ ስልታቸውም ሆነ የትኩረት አቅጣጫቸው የራሱ የሆነ ዐውድ አለው፡፡ መልእክታቱንም ሲጽፉ ከየራሳቸው ዐውድ አኳያ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በዶግማ በቅድስና ሕይወት ዙሪያ ሲያተኩር ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ ከቅድስና ሕይወት ጎን ለጎን በዶግማና በነገረ እግዚአብሔር ላይ ያተኩራል፡፡
 
ይህን አተያይ ከቅዱስ ጴጥሮስ አኳያ ስንመለከት ራሱ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ በመጀመሪያ መልእክቱ እንደ አሠፈረው ነው፡፡ ይህም «እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ ተብሎ ስለተጻፈ የጠራችሁ ቅዱስ እንደ ሆነ እናንተ ደግሞ በኑሮአችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ፡፡» ብሎ እንደጠቀሰው ነው፡፡ /1ጴጥ.1.15/ ከዚህም በተጨማሪ ሐዋርያው ይኽን ሲገልጽ «… በእንግድነታችሁ ዘመን በፍርሃት ኑሩ፡፡» በማለት ሲሆን በዚሁ ምዕራፍ ላይ «የእምነታቸውን ፍጻሜ እርሱም የነፍሳችሁን መዳን እየተቀበላችሁ…» እና «ጻድቅም በጭንቅ የሚድን ከሆነ ዓመፀኛውና ኃጢአተኛው ወዴት ይታይ ዘንድ አለው)» በማለት ገልጾታል፡፡ /1ጴጥ.1.1-9፤ 4.18/
 
በሌላ መልኩ ደግሞ ከዚህ ከመልእክት የትኩረት አቅጣጫ አኳያ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ ከሌሎች ጉዳዮች ይልቅ በመግለጽና በማብራራት የሚያተኩረው በነገረ እግዚአብሔር ላይ ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ የእርሱ መልእክታት ስለ ጸጋ እግዚአብሔር፣ ስለ ቤተክርስቲያን የክርስቶስ አካልነት፣ የክርስቶስን ሥጋና ደም በመቀበል ስለሚገኝ ድኅነት፣ ስለ ምስጢራተ ቤተክርስቲያን /ስለ ምስጢረ ክህነት፣ ቁርባን፣ ጥምቀት፣ ጋብቻ፣ ትንሣኤ ሙታን/ ያተኩራሉ፡፡ የእነዚህ ሁለት ሐዋርያት መልእክታት በአጭሩ በዚህ መልክ ሊቀመጡ ይችላሉ፡፡
 
7. ቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳዉሎስ በጌታችን ስም ያደረጓቸው ተአምራት
 
እነዚህ ሁለት ሐዋርያት በዘመናቸው ተአምራት ያደርጉ ነበር፡፡ ያደረጓቸውም ተአምራት ለክርስትና ሃይማኖት መስፋፋት ታላቅ አስተዋጽኦ ነበሯቸው፡፡  ሁለቱም በተአምራት ሙት አስነሥተዋል፤ ድውይ ፈውሰዋል፡፡ ለዚህም እንደማሳያ ምሳሌዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ይኸውም ቅዱስ ጴጥሮስ ጣቢታ የተባለች በኢዮጴ የምትኖር አንዲት ሴትን ከሞት በተአምራት አስነሥቷል፡፡ ይህች ሴት ለሰው ሁሉ መልካም የምታደርግ፤ ምጽዋትን የምትሰጥ፣ ለተለያዩ ደሃ ሴቶች የሚሆኑ የተለያዩ አልባሳትን በመሥራት ትለግስም ነበር፡፡ ይህን ሁሉ መልካም ነገር የምትፈጽም ሴት ታማ ሞተች፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም በተአምራት ከሞት አዳናት፡፡ /የሐዋ.9.36-40/
 
ቅዱስ ጳዉሎስም እንዲሁ የሚጠቀስ ተአምር አለው፡፡ ቅዱስ ጳዉሎስም ቃለ እግዚአብሔርን እያስተማረ አውጤኩስ የተባለ አንድ ወጣት አንቀላፋ፡፡ በእንቅልፉም ክብደት ምክንያት ከተቀመጠበት ወድቆ ይሞታል፡፡ ቅዱስ ጳዉሎስም ይህን ወጣት በተአምር ከሞት አስነሥቶታል፡፡ /የሐዋ.20.9-12/
 
ከዚህም በተጨማሪ እነዚህ ሁለት ሐዋርያት በልብሳቸውና በጥላቸው በተአምራት ሕሙማንን እየፈወሱ ሕመምተኞችንም የክርስቶስ የመንግሥቱ ዜጎች ያደርጉ ነበር፡፡ ተአምራቱም ችግረኞቹን ከችግራቸው ከማላቀቅ ባለፈ ለክርስትና ሃይማኖት መስፋፋት እጅጉን ይጠቅም ነበር፡፡ /የሐዋ.5.15-16፤ 19.12/
 
 
ቅዱሰ ጴጥሮስ እና ቅዱስ ጳውሎስ በሮም ሰማዕትነት እንደተቀበሉ የሚያሳዩ
 
8. ሰማዕተ ጽድቅ ጴጥሮስ ወጳዉሎስ
 
የቤተክርስቲያን ጉዞ ሁልጊዜ በመስቀል ላይ ነው፡፡ ይህ የመስቀል ጉዞ ደግሞ መሥዋዕትነትን /መከራ መቀበልን/ ይጠይቃል፡፡ ከዚህም የተነሣ በሰይፍ የተመተሩ፤ በመጋዝ የተተረተሩ፣ በእሳት የተቃጠሉ ለአናብስት የተጣሉ በአጠቃላይ በብዙ ስቃይ የተፈተኑ ቅዱሳን ሐዋርያት አሉ፡፡  ከእነዚህ ሐዋርያት ደግሞ በዋናነት የሚጠቀሱት እነዚህ ሁለት ሐዋርያት ናቸው፡፡ «ሥጋን የሚገድሉትን ነፍስን ግን መግደል የማይቻላቸውን አትፍሩ፤ ይልቅስ ነፍስንም ሥጋንም በገሃነም ሊያጠፋ የሚችለውን ፍሩ፡፡» የሚለውን የጌታችንን ቃል መመሪያ አድርገው ለቤተክርስቲያን ሁሉን አድርገው፤ ሁሉን ሆነው የሰማዕትነትን ጽዋ ተቀብለዋል፡፡
 
ቅዱስ ጴጥሮስ ስለ ክርስትና ሃይማኖት የአይሁድ መሪዎችንና ሊቃነ ካህናቱን ይሞግት፤ ከእነርሱም ፊት ምስክርነት ይሰጥ ነበር፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ የአይሁድን ሊቃነ ካህናት «ከሰው ይልቅ ለእግዚአብሔር ልንታዘዝ ይገባል» እያለ በሸንጎ ይሟገት ነበር፡፡ /የሐዋ.5.29/ በዚህም ብዙውን ጊዜ ይገረፍ ይታሰር ነበር፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ደግሞ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስም የተለያዩ የመከራ ጽዋን ተቀብሏል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ እርሱና ሌሎች ሐዋርያት ስለክርስቶስ መከራ መቀበላቸውን ሲገልጽ «በሁሉ መከራ ስንቀበል አንጨነቅም፣ እንናቃለን አንዋረድም፤ እንሰደዳለን አንጣልም፤ እንጨነቃለን አንጠፋም፡፡» በማለት ነው፡፡ /2ቆሮ 4.8-11/ ከዚህም በተጨማሪ «በብዙ መጽናት፣ በመከራ፣ በችግር፣ በጭንቀት፣ በመገረፍ፣ በወኅኒ፣ በሁከት፣ በድካም፣ እንቅልፍ በማጣትም» በማለት የሰማዕትነት ሕይወቱን ገልጿል፡፡ /2ቆሮ.6.4-5፣ 1ቆሮ. 11.22-28/
 
በአጠቃላይ ቅዱስ ጳውሎስ የደረሰበትን መከራ ሁሉ በዚህ መልኩ ገልጿል፡፡ እነዚህ ሁለት ሐዋርያት በዚህ መልኩ ስለ ወንጌልና ስለክርስቶስ መከራ ከተቀበሉ በኋላ ከዚህ ምድር ያለፉት በሰማዕትነት ነው፡፡ ሁለቱም በሰማዕትነት ያለፉት በዘመነ ኔሮን ሐምሌ 5 ቀን 67 ዓ.ም ነው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በሰማዕትነት ያረፈው የቁልቁሊት ተሰቅሎ ሲሆን ቅዱስ ጳዉሎስ ደግሞ አንገቱን ተሠይፎ ነው፡፡ የእነዚህ ሁለት ታላላቅ የጌታችን ሐዋርያት ረድኤት በረከት አማላጅነት ሁላችንንም አይለየን፤ አሜን፡፡
 
ዲያቆን ታደሰ ወርቁ
 
እነዚህ ሁለት ቅዱሳን አባቶቻችን የቅድስት ቤተክርስቲያናችን አዕማድ ናቸው፡፡ በመሠረትነት በአጸኗት ቤተክርስቲያን ያላቸው የክብር ሥፍራ ላቅ ያለ ነው፡፡ ይህ የሆነው እንዲሁ አይደለም፡፡ ለቤተክርስቲያንና በቤተክርስቲያን የፈጸሙት አገልግሎት በዚህም የተቀበሉት ሰማዕትነት ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም ይህን መልካም የሆነውን ታሪካቸውን ለእኛ አርአያነት በሚሆን መልኩ ከትበውልናል፡፡ እኛም ለአርአርያነት በሚሆን መልኩ የእነዚህን ደጋግ ሁለት ቅዱሳን አባቶች ታሪክ፣ ዕውቀትና መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን ከዚህ በመቀጠል አቅርበናል፡፡
 
 
 
 
 

 

 
 
 
 

 

ወርኃ ክረምት በቤተ ክርስቲያን ትምህርት (ዘመነ ክረምት)

ሐምሌ 4 ቀን 2004 ዓ.ም.

መብዐ ሥላሴ (ከጎላ ሚካኤል)

“ክረምት” የሚለው ቃል ከርመ፣ ከረመ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጓሜውም ወርሃ ዝናም፣ ወርኃ ነጎድጓድ፣ ዘመነ ባሕር፣ ዘመነ ነጎድጓድ፣ ዘመነ አፍላግ፣ ዘመነ ጠል፣ ዘመነ ደመና፣ ዘመነ መብረቅ… ማለት ነው፡፡(ጥዑመ ልሳን ካሳ ያሬድና ዜማው 1981 ዓ.ም ገጽ 53)

 

በዘመነ ክረምት ውኃ ይሰለጥናል፣ ውኃ አፈርን ያጥባል፣ እሳትን ያጠፋል፡፡ ሆኖም ግን በብሩህነቱ ከእሳት፤ በቀዝቃዛነቱ ከነፋስ፤ በእርጥብነቱ ከመሬት ጋር ተስማምቶ ከሦስቱ ባሕርያት ጋር ይኖራል፡፡ ይህ ዘመን ስለ ሥነ ፍጥረት ዘርዘር ባለ መልኩ የሚነገርበት ዘመን ስለሆነ ፍጡርን ከፈጣሪ መናን ከተመጋቢ ለይቶ የሚያሳይና የሚያሳውቅ ዘመን ነው፡፡

 

ዘመነ ክረምት፡- የዝናም፣ የዘርና የአረም ወቅት በመሆኑ ምድር በጠል ዝናም ትረካለች፡፡ ዕፅዋት አዝርዕትና አትክልት በቅለው፣ ለምልመው  የሚያድጉበት፣ ምድር አረንጓዴ ለብሳ በሥነ ጽጌያት የምታሸበርቅበት፣ ወቅት ነው፡፡በመሆኑም በሃገራችን ብዙው የግብርና ሥራ የሚካሄደው በዚህ ጊዜ ነው፡፡

 

ወርኃ ክረምት የክርስትና ምሳሌ ነው፤ ገበሬ በወርሃ ክረምት ብርዱንና ዝናሙን ሳይሰቀቅ ለሥራ ይሰማራል፤ በበጋው የእጁን ፍሬ ያገኝ ዘንድ የክረምቱን መከራ ይታገሳል፡፡ ክርስቲያንም በዚህ ምድር ላይ የሚደርስበትን መከራ ሁሉ ይታገሳል፤ ክርስቲያንም በዚህ ምድር የሚደርስበትን መከራ ሁሉ በጸጋ የሚቀበለው በዚያኛው ዓለም ስለሚያገኘው ተድላና ደስታ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ፡- “እለ ይዘርኡ በአንብዕ ወበኃሤት የአርሩ፡፡ ሶበሰ የሐውሩ ወፈሩ እንዘ ይበክዩ፡፡ ወፆሩ ዘርኦሙ፡፡ ወሶበ የአትዉ መጽኡ እንዘ ይትፌሥሑ፡፡  በሔዱ ጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሰማሩ፤ በተመለሱ ጊዜ ግን ነዶአቸውን ተሸክመው ደስ እያላቸው ይመጣሉ፡፡” በማለት የመንፈሳዊ ጉዞ ምሥጠርን ከግብርና ሙያ አንጻር አመልክቶአል፡፡(መዝ.125)

 

እግዚአብሔር ክረምትን ሲያመጣና ዝናምን ሲያዘንም ብዙ ነገሮችን ልናስተውል ይገባናል፡፡ ፈጣሪያችን ፈጣሪ ዓለማት ብቻ ሳይሆን መጋቢ ዓለማት መሆኑን መረዳት ያሻል፡፡ መግቦቱም ከፍጥረቱ እንዳልተለየ ይህ አማናዊ መግቦቱም ፍጥረቱን እንደሚያስተምር እንረዳለን፡፡ “በምድር ዘመን ሁሉ መዝራትና ማጨድ፤ ብርድና ሙቀት፤ በጋና ክረምት፤ ቀንና ሌሊት አይቋረጡም፡፡” (ዘፍ.8፥22) በማለት አምላካችን እግዚአብሔር ለኖኅ በገባለት ቃል ኪዳን መሠረት በጋና ክረምቱ፤ ብርድና ሙቀቱ፤ ቀንና ሌሊቱ በተወሰነላቸው ጊዜ እየተፈራረቁ ለሰው ልጆች ጥቅም እንዲሰጡ አድርጓቸዋል፡፡

 

በዚህ መሠረት ኢትዮጵያዊያን በአንድ ዓመት ውስጥ እየተፈራረቁ በሚመጡ አራት ወቅቶች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ከቅዱሳት መጻሕፍት ምሥጢርና ምሳሌ ጋር በማስማማት ለየወቅቱና ለዕለታቱ ምንባባትን በማዘጋጀት፣ ከሕብረተሰቡ ሥራና አኗኗር ጋር በማያያዝ እንዲሁም ከወቅታዊው አየር ጠባይ ጋር በማስማማት እያንዳንዳቸውን በ91 ቀን ከ15 ኬክሮስ (አንድ አራተኛ) በመክፈል ለወቅቶቹም ሥያሜ፣ ምሳሌ፣ ትርጉሙንና ምሥጢሩን በማዘጋጀት ትገለገልባቸዋለች፡፡

 

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዓመቱን የከፈለችባቸው ወቅቶች፡-

  1. ዘመነ መጸው (መከር) ከመስከረም 26 ቀን እስከ ታኅሣሥ 25
  2. ዘመነ ሐጋይ (በጋ) ከታኅሣሥ 26 ቀን እስከ መጋቢት 25
  3. ዘመነ ጸደይ (በልግ) ከመጋቢት 26 እስከ ሰኔ 25
  4. ዘመነ ክረምት ሰኔ 26ቀን እስከ መስከረም 25 ናቸው፡፡

 

ወቅቶችን እንዲህ በመከፋፈል በወቅቱ ከሚታየው የተፈጥሮ ሁኔታ ጋር ምእመናን ሕይወታቸውን እንዲመረምሩ ለንስሐ እንዲበቁ አጥብቃ ታስተምራለች፡፡ ያለንበት ወቅትም ክረምት በመሆኑ በቤተ ክርስቲያናችን ሊቃውንት፤ ቅዱሳት መጻሕፍት አማካኝነት የሚሰጠውን ትምህርት በጥቂቱ እንመለከታለን፡፡

 

ወርኃ ክረምት ከላይ በጥቂቱ እንደተመለከትነው በሦስት ንዑሳን ክፍላት ይከፈላሉ፡፡ እነኚህም፡-

1.    መነሻ ክረምት፡- የዝግጅት ወቅት

ሀ. ከበአተ ክረምት እስከ ሐምሌ ቂርቆስ(ከሰኔ 26 እስከ ሐምሌ 19) ያለው ወቅት ነው፡፡  በዚህ ወቅት ዝናምና ደመና ምድርን የሚያለመልሙበት፣ ዘር የሚዘራበት ፣ የተዘራው የሚበቅልበት በፀሐይ ሐሩር የደረቁ ዛፎች ሁሉ የሚያቆጠቁጡበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘርዕን ደመናን ዝናምን የሚያዘክሩ  ምንባባት ይነበባሉ፣ መዝሙራትም ይዘመራሉ፡፡

 

ከእነዚህም ውስጥ ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ “ድምፀ እገሪሁ ለዝናም ሶበ ይዘንም ዝናም ይትፌስሁ ነድያን፣ ይጸግቡ ርሁባን፡፡ የዝናም ድምፅ ተሰማ፤ ዝናም በዘነመ ጊዜ ችግረኞች ይደሰታሉ፤ ረሀብተኞችም ይጠግባሉ፡፡” በማለት በድጓው የዘመረው ይገኝበታል፡፡

 

ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙሩ “ዘይገለብቦ ለሰማይ በደመና፡፡ ወያስተዴሉ ክረምተ ለምድር፡፡ ዘያበቊል ሣዕረ ውስተ አድባር፡፡ወሐመልማለ ለቅኔ እጓለ እምሕያው፡፡ ማለትም፡- ሰማዮችን በደመና ይሸፍናል፤ ለምድርም ዝናምን ያዘጋጃልና፤ ሣርን በተራሮች ላይ ያበቅላል፤ ለምለሙንም ለሰው ልጆች ጥቅም” በማለት የዘመረው ይሰበካል፡፡

 

በምንባበት በኩል ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “በእርስዋ ላይ የሚወርደውን ዝናም የምትጠጣ መሬት ለሚያርሷትም ደግሞ የምትጠቅምን አትክልት የምታበቅል ከእግዚአብሔር በረከት ታገኛለች፤ እሾህንና ኩርንችትን ግን ብታወጣ የተጣለች ናት፡፡ ለመረገምም ትቀርባለች፤ መጨረሻዋም መቃጠል ነው፡፡” በማለት ያስተማረው ትምህርት ይነበባል፡፡(ዕብ.6፥7-8)

 

ለ. ከሐምሌ ቂርቆስ እስከ ማኅበር (ከሐምሌ 19 እስከ ሐምሌ 29) መባርቅት የሚባርቁበት በባሕርና አፍላጋት የሚሞሉበት ምድር ጠል የምትጠግብበት ወቅት ነው፡፡ “ደመናት ድምፁን ሰጡ፣ ፍላጾችህም ወጡ የነጎድጓድህ ድምፅ በዐውሎ ነበር፤ መብረቆች ለዓለም አበሩ” ሲል ቅዱስ ዳዊት የተናገረው ይሰበካል፡፡(መዝ.76፥18) ደመኖች ታይተው ባርቀው የነጎድጓድ ድምፅ እንዲሰማ ጌታችን ከዓለም ጠርቶ አስተምሮ ወንጌለ መንግሥት ተናግረው በኃጢአት ጨለማ የተያዘውን ዓለም በትምህርታቸው እንዲያበሩ የተላኩ የ72ቱ አርድዕት ዝክረ ነገር ይታወሳል፡፡(ሉቃ.10፥17-25)

 

መዝሙሩ፡- “ምድርኒ ርዕየቶ ወአኰተቶ ባህርኒ ሰገደት ሎቱ፤ ምድር አየችው አመሰገነችውም ባሕርም ሰገደችለት” /ድጓ/

“እግዚአብሔር የወደደውን ሁሉ አደረገ በሰማይም በምድርም በባህርም በጥልቅም ቦታ ሁሉ”/መዝ.134፥6-7/

“ምድርን ጎበኘሃት አጠጣሃትም ብልፅግናዋንም እጅግ አበዛህ የእግዚአብሔር ወንዝ ውኃን የተሞላ ነው ከምድር ዳር ደመናትን ያወጣል፣ በዝናም ጊዜ መብረቅን አደረገ፤ ነፋሳቱንም ከመዛግብቱ ያወጣል ” (መዝ.64፥9) በማለት እግዚአብሔር በነጎድጓድና በመብረቅ በባሕርና በሐይቅ ሁሉ ላይ ሥልጣን ያለው አምላክ መሆኑንና የሚታዩና የማይታዩ ፍጥረታት ሁሉ የኃይሉ መገለጫዎች እንደሆኑ የሚያስተምሩ መዝሙራት ይዘመራሉ፡፡

ወንጌል፡- መንግሥተ ሰማያት ወደ ባሕር የተጣለች ከሁሉም ዓይነት የሰበሰበች መረብን ትመስላለች (ማቴ.13፥47)

ደቀ መዛሙርቱም በባሕር ላይ ሲሄድ ባዩት ጊዜ፤ ምትሐት ነው ብለው ታወኩ በፍርሃትም ጮኹ፡፡ ወዲያውም ኢየሱስ ተናገራቸውና አይዞአችሁ፥ እኔ ነኝ፥ አትፍሩ አላቸው፡፡(ማቴ.14፥26-27)

2.    ማዕከለ ክረምት

ሀ. ከማኅበር እስከ አብርሃም (ከሐምሌ 29 እስከ ነሐሴ 29)

ዘመነ ክረምት የሚጋመስበት ነው፡፡ ዝናብ ይቀንሳል፣ ምድሪቱም መቀዝቀዝና መጠንከር ትጀምራለች፡፡ “ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት፤ ቡሄ ካለፈ የለም ክረምት” እንዲሉ በክረምት ዝናሙን ተደብቀው የነበሩ አእዋፍ ከበአታቸው ይወጣሉ፤ ጥበበኛው ሰሎሞን አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፤ የዜማ ጊዜ ደረሰ፤ የቀረርቶውም ቃል በምድራችን ተሰማ (መኃ.2፥12) ሲል እነደተናገረው የአእዋፍ የምስጋና ድምፅ ይሰማል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም “የሁሉም ዐይን አንተን ተስፋ ያደርጋል፣ አንተም ምግባቸውን በየጊዜው ትሰጣቸዋለህ፣ አንተ እጅህን ትከፍታለህ፣ ሕይወት ላለውም ሁሉ መልካምን ታጠግባለህ” እያለች እንደ ቅዱስ ዳዊት ለሥጋ ሁሉ ምግብን የሚሰጥ ምሕረቱም ለዘለዓለም የሆነውን የሰማይ አምላክ ታመስግናለች(መዝ.144፥15-20፣ መዝ 135፥25-26)

 

ለ. ዕጉለ ቋዓት፥ ደስያት

ይህ ክፍለ ክረምት ከነሐሴ 10 እስከ ነሐሴ 27 ቀን ድረስ ያሉት 17 ዕለታት የሚጠሩበት ነው፡፡ በዚህ ክፍለ ክረምት ፍጥረታትና በባሕር የተከበቡ ደሴቶች የሚታወሱበት ሲሆን ወቅቱም ዕጓለ ቋዓት ደስያት ዐይነ ኩሉ ይባላል፡፡ ዕጓለ ቋዓት የሚለው ቃል ቁራን ሲያመለክት፣ ቁራ ሲወለድ ያለ ፀጉር በሥጋው ብቻ ይወለዳል፡፡ እናትና አባቱም እነርሱን ባለመምሰሉ ደንግጠው ይሸሻሉ፤ በዚህ ጊዜ የሚንከባከበው ሲያጣ እግዚአብሔር በረድኤት አፉን ከፍቶ ምግብ ሲሻ ተሐዋስያንን ብር ብር እየደረገ ከአፉ ያስገባለታል፡፡ “ልጆቹ ወደ እግዚአብሔር ሲጮኹ፥ የሚበሉትም አጥተው ሲቅበዘብዙ፥ ለቁራ መብልን የሚሰጠው ማን ነው? ” (ኢዮ.38፥41) ተብሎ እንደ ተገለጠው እግዚአብሔር የሰጠውን እየተመገበ ቆይቶ ሲጠነክር እንደ እናትና አባቱ ያለ ፀጉር ያወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ እናትና አባቱ ቀርበው ይንከባከቡታል፡፡ በሥነ ፍጥረት አቆጣጠር ግን በክንፍ የሚበሩ አዕዋፍን ሁሉ ይወክላል፡፡ ይህም አምላካችን እግዚአብሔር ለፍጥረቱ ሁሉ የሚያስብ በመሆኑ ይህን ዘመን ርኅርሔ ለተመላው አምላክነቱ ሥራው መታሰቢያ እንዲሆን ቤተ ክርስቲያን ዕጓለ ቋዓት በማለት ታስታውሰዋለች፡፡

 

ደስያት ማለት በውኃ የተከበቡ ቦታዎች ማለት ነው፡፡ እነዚህን ቦታዎች በውኃ እንዲሸፈኑ አድርጎ በውስጥቸው ያሉትን ሰዎች እንስሳት አራዊት አዕዋፍ ሁሉ የሚጠብቃቸው፣ በተስፋና በእምነት አበርትቶ የሚያኖራቸው እግዚአብሔር ነው፡፡ ይህን ድንቅ ሥራ ያዩ በውስጥ በውጭ ያሉት ሰዎች እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል፡፡ በደሴት (በቤተ ክርስቲያን) የተጠጉ ሁሉ ከሞተ ሥጋና ከሞተ ነፍስ ይጠበቃሉ፡፡

 

በዚህ ወቅት፡- ክፍለ ክረምቱ እንደተገባደደ፥ ውኃው እየጠራ፣ መሬቱ እየረጋ፣ ደመናውና ጉሙ እየተቃለለ፣ የወንዞች ሙላት እየቀነሰ፣ የክረምት ምግባቸውን ይዘው በየዋሻው የከረሙ ጭልፊቶችን አሞራዎች ድምፃቸውን እየሰሙ ምግብ ፍለጋ ሲወጡ የሚታዩበት ወቅት ነው፡፡

 

በተጨማሪም ከነሐሴ 27-29 ያለው ጊዜን “ሞተ አበው” በመባል ይታወቃል፡፡ ከ22ቱ አርዕስተ አበው የአብርሃም ይስሐቅና ያዕቆብ ቤተሰቦቻቸው ዕረፍት ይታሰባል፡፡ ቅዱስ መጽሐፋችንም “አብርሃም ልጁን ይስሐቅን ሊሰዋ ወጣ፤ እግዚአብሔር ቤዛ አድርጎ ቀንዱ በዕፀ ሳቤቅ የተያዘ በግ አወረደለት” በማለት የአብርሃምን ታዛዥነት የይስሐቅን ቤዛነት ያወሳል፡፡ የተቀበሉትም ቃል ኪዳን “ወተዘከረ ሣህሎ ዘለዓለም ዘሠርዓ ለአብርሃም ወመሐለ ለይስሐቅ ወዐቀመ ስምዐ ለያዕቆብ ያርኁ ክረምተ ይገብር ምሕረተ እም ሰማይ ይሁብ ወእምድር በረከተ ያጸግብ ነፍስ ርኅብት” በማለት ይዘመራል፡፡

 

3.    ፀዓተ ክረምት (ዘመን መለወጫ)

ሀ. ከአብርሃም እስከ ዮሐንስ

ይህ ወቅት የዓመቱ መንገደኛ ነው፣ በሐምሌና በነሐሴ ደመና ተሸፍና የነበረችው ፀሐይ ፍንትው ብላ መውጫዋ የደረሰበት ጊዜ በመሆኑ ጎህ ጽባህ፣ መዓልተ ነግህ፣ ብርሃን ተብሎ የጠራል፡፡ የክረምቱ ጭፍን ጨለማ ሊያከትም ብርሃን ሊበራ የተቃረበበት መሆኑ በቤተ ክርስቲያን ይበሰራል፡፡ በሊቀ መልእክት ቅዱስ ሩፋኤል እጅ የጦቢያን ዓይን እንዳበራ ፤ የምእመናን ዓይነ ልቡና እግዚአብሔር እንዲያበራ ይጸለያል፡፡

 

ከዚሁ ጋር የክረምቱ ደመና ዝናብና ቅዝቃዜ ውርጭ ጭቃው ከብዶባቸው የዘመን መለወጫን፣ የፀሐይ መውጫን ቀን በጉጉት ለሚጠባበቁ ምእመናን ልጆቿ ቅድስት ቤተ ከርስቲያን፡- “ነፍሳችሁን ተመልከቱ፥ ሰውነታችሁን ንጹሕ አድርጉ” ስትል ለበለጠ መንፈሳዊ ትጋት ታነቃቃቸዋለች፡፡ ክረምት ሲያልፍ የሰማዩ ዝናም የምድሩ ጭቃ ሊቀር እንሆ ሁሉ በዚህች ዓለም መከራ ተናዝዘው ላሉ ክርስቲያኖች ሁሉ ክርስቶስ በክብር የሚገለጥበት ዓለም የምታልፍበት ዕለት ባላሰቧት ጊዜ እንደምትመጣ እንዲገነዘቡ ነገረ ምጽአቱን እንዲያሰቡ “ተዘጋጅታችሁ ኑሩ!” እያለች በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር እንዲያብቡ “እግዚአብሔር ግልጥ ሆኖ ይመጣል… አምላካችን ይመጣል ዝምም አይልም እሳት በፊቱ ይነዳል” (መዝ.49፥2-3) እያለች ትመሰክራለች፡፡

 

ለ. ከዮሐንስ እስከ ዘካርያስ (መስከረም 8)

ዘመን መለወጫ አዲስ ተስፋ በምእመናን ልብ የሚለመለምበት ጊዜ ነው፡፡ የተተነበየው ትንቢት፣ የተቆጠረው ሱባኤ ተፈጸመ፤ ከዘመነ ፍዳ ወደ ዘመነ ምሕረት የምትሸጋገሩበት ጊዜ ደረሰ፤ እያለ ያወጀው የመጥምቀ መለኮት ዮሐንስ ዜና ሕይወት ይነገራል፡፡ “ምሕረትና እውነት ተገናኙ፤ ጽድቅና ሰላም ተስማሙ፣ እውነት ከምድር በቀለች” (መዝ.88፥10-11) በማለት ስለ እውነት ሊመሰክር የወጣውን የቅዱስ ዮሐንስን ሕይወት በማውሳት ቤተ ክርስቲያን ልጇቿ እንደርሱ እውነተኞች እንዲሆኑ አርአያነቱን እንዲከተሉ ለእውነት እንዲተጉ ታስተምራለች፡፡ ሰማዩ፣ ውኃው የሚጠራበት ወቅት በመሆኑ በሥነ ፍጥረት በማመለከት ልጆቿን ከብልየት እንዲታደሱ፣ በመንፈስ እንዲጎለምሱ፣ከርኩሰት ከጣኦት አምልኮ፣ከቂም በቀል እንዲጠሩ እንዲነፁ “የአህዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞትም በስካርም በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና” እያለች በሐዋርያው ቃል ታስተምረናለች፡፡(1ኛ ጴጥ.4፥3) ከዚሁ ጋር፡-በርኩሰት የተመላውን ሕይወታችንን ካለፈው ዘመን ጋር አሳልፈን የምድር አበቦች በጊዜው እነደሚያብቡ እኛም በምግባር በሃይማኖት እንድናብብ ትመክረናለች፡፡

 

ሐ. ከዘካርያስ እስከ ማግስተ ሕንፀት

ይህ ንዑስ ወቅት ዘመነ ፍሬ በመባል ይታወቃል፡፡ ከመስከረም 9 እስከ 16 ያሉትን ዕለታት በተለይ በሰኔና በሐምሌ የተዘራው ዘር ለፍሬ መብቃቱን የሚያስብበትና እንደ ቅዱስ ዳዊት “ምድር ፍሬዋን ሰጠች እግዚአብሔር አምላካችንም ይባርከናል”(መዝ.66፥6) ተብሎ እግዚአብሔር የሚመሰገንበት ሳምንት ነው፡፡ ፍሬውም ከቁር ከበረዶና ከትል ተርፎ ለጎተራ እንዲበቃ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጸሎተ ቅዳሴዋ “በእንተ ፍሬ ምድር ናስተበቊእ ከመ እግዚአብሔር ይሁብ ፍሬሃ ለምድር፣ ለዘርና ለመከር ሊሆን እግዚአብሔር ለምድር ፍሬዋን ይሰጣት ዘንድ ስለምድር ፍሬ እንማልዳለን” በማለት አምላኳን ትማጸናለች፡፡

 

ልጇቿ ምእመናንም “ሽሽታችሁ በክረምት ወይም በሰንበት እንዳይሆን ጸልዩ” (ማቴ. 24፥20) ሲል መድኃኔዓለም እንዳስተመረው የሃይማኖት ፍሬ ምግባርን፣ ቱሩፋትን ሳይሠሩ በልምላሜ (በሃይማኖት) ብቻ ሳሉ እንዳይጠሩ ለንስሐ ለሥጋ ወደሙ እንዲበቁ በማስተማር ነገረ ምጽአቱን በማዘከር “ድልዋኒክሙ ንበሩ፣ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ ” በማለት ታስተምራለች፡፡

 

ስለዚህ ይህ ክፍለ ክረምት የዕለተ ምጽአት ምሳሌ ነው፡፡ ወቅቱ የአዝመራ ወቅት ነው፡፡ፍሬ መለያ እንደሆነ ሁሉ የሰው ሥጋ ከተቀበረና ትቢያ ከሆነ በኋላ ተነስቶ በዕለተ ምጽአት በጽድቅና በኃጢአት ይለያልና፡፡(ማቴ.25፥32)

 

መ. ከመስከረም እስከ ፍጻሜ ክረምት(መስከረም 25)

ዘመነ መስቀል ከመስከረም 17 እስከ 25 ያሉት ዘጠኝ ቀናት የሚጠሩበት ሌላው መጠሪያቸው ነው፡፡ ይህ ክፍለ ክረምት ነገረ መስቀሉ የሚነገርበት ነው፡፡ በቅናት ተነሳስተው አይሁድ የቀበሩት የጌታችን መስቀል በንግሥት እሌኒ ጥረትና በፈቃደ እግዚአብሔር ከሦስት መቶ ዓመታት በኋላ ተቆፍሮ የወጣበት መታሰቢያ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያንም የቅዱስ መስቀልን ክብር የሚመለከት ትምህርት ይሰጣል፤ ክቡር ዳዊት “ከቀስት ፊት ያመልጡ ዘንድ ለሚፈሩህ ምልክት ሰጠሃቸው” (መዝ.59፥4) በማለት የተናገረው ይሰበካል፡፡ ጊዜው የክርስቶስና የመስቀል ጠላቶች ያፈሩበት የመስቀሉ ብርሃን ለዓለም ያበራበት በመሆኑ የመስቀሉ እንቅፋት ተወግዷልና ምእመናን በዚህ ይደሰታሉ(ቆላ.2፥14-15) በቅዱስ መስቀሉ ተቀጥቅጦ ኃይሉን ያጣው ዲያብሎስን በትእምርተ መስቀል ከእነርሱ ያርቁታል፡፡ በቅዱስ መስቀል የተደረገላቸውን የእግዚአብሔር ቸርነት እያስታወሱ በአደባባይ በዝማሬ መንፈሳዊ ደስታቸውን ይገልጣሉ፡፡

 

እንግዲህ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በጊዜ ውስጥ ላለነው ራሳችንን ከጊዜው ጋር እንድናነጻጽር ወቅቱን የተመለከተ ትምህርት አዘጋጅታ ልጆቿን ለሰማያዊ መንግሥት ዝግጁ እንዲሆኑ ታስተምራለች፡፡ በዚህም ጊዜ ውስጥ ተፈጥሮን አይተን አገናዝበን የምንማር፣ ለንስሐ የተዘጋጀን ስንቶቻችን ነን? “ቁም! የእግዚአብሔርን ተአምራት አስብም!” እንዳለ (ኢዮ.37፥14) ያለንበትን ሕይወት አስበን ለንስሐ እንበቃ ዘንድ፣ የእግዚአብሔር ቸርነት፥ የድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ጸሎት አይለየን፤