“የእግዚአብሔር ቤት” በሚል ርእስ የተሠራው የኢየሱስ ክርስቶስ የስቅለት ፊልም ከቀኖና ቤተ ክርስቲያን ውጭ እንደሆነ ተገለጠ፡፡

ኅዳር 28/2004 ዓ.ም.
በዲ/ን ኅሩይ ባየ

የእግዚአብሔር ቤት /The abode of God/ በሚል ርእስ በጀርመናዊቷ ሚስስ ብሪጅት ማሪያ ማየር ተዘጋጅቶ በተወሰኑ ኢትዮጵያዉያን አርቲስቶች የተሠራው የኢየሱስ ክርስስቶስ የስቅለት ፊልም ከቤተ ክርስቲያን ቀኖና እና ትውፊት ውጭ እንደሆነ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሊቃውንት ጉባኤ ኅዳር 28 ቀን 2004 ዓ.ም የሰጠው መግለጫ ያስረዳል፡፡

 

ሚስስ ብሪጅት ማሪያ ማቶር የተባለችው ጀርመናዊት በኢትዮጵያውያን የኪነ ጥበብ ሰዎች እንዲሠራ ያዘጋጀችው ፊልም በይምርሐነ ክርስቶስ፣ አሸተን ማርያምና በጉንዳጉንዶ ገነተ ማርያም አብያተ ክርስቲያናት ተቀርጾ ለዕይታ እንዲቀርብ የመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት ያቀረቡት ጥያቄ ጉዳዩ ሃይማኖታዊ ስለሆነና ቀረጻው የሚካሔድበት ቦታ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲየን አብያተ ክርስቲያናት ስለሆነ ጉዳዩ በቤተ ክርስቲያኗ እንዲታይና እንዲፈቀድ ማሳሰቢያ ሰጥቷል፡፡

ከመንግስት ኮሚዮኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት በተሰጠው አስተያየት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽሕፈት ቤት በቁጥር ል/ጽ/565/279/03 በቀን 8/11/2003 ዓ.ም በሊቃውንት ጉባኤ እንዲታይ የፊልሙ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡ የሊቃውንት ጉባኤውም በተሰጠው መመሪያ መሠረት ከ11/11/2003 እስከ 15/11/2003 ዓ.ም ለአምስት ተከታታይ ቀናት ባደረገው ጉባኤ 80 ገጾች ያሉትን የፊልም ጽሑፍ መርምሮ የውሳኔ ሐሳቡን ለቋሚ ሲኖዶስ አቅርቧል፡፡

ቋሚ ሲኖዶስም ጳጉሜን 1 ቀን 2003 ዓ.ም ባደረገው ጉባኤ በሊቃውንት ጉባኤ የቀረበውን የውሳኔ ሐሳብ መርምሮ የተዘጋጀው የፊልም ጽሑፍ፡-

• የክርስቶስን ቅዱስ ወንጌል በአግባቡ የማይገልጽ በመሆኑ፣ የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት፣ ትውፊትና ታሪክ ባለመጠበቁ፣ የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነት መከራ መስቀሉን፣ ሕማሙን፣ ሞቱንና ትንሣኤውን ዝቅ አድርጎ በማቅረቡና ባጠቃላይ ከቤተ ክርስቲያናችን ትምህርተ ሃይማኖት፣ ቀኖና ትውፊት ውጭ ስለሆነ የፊልሙ ጽሑፍ ውድቅ ሆኗል ሲል ውሳኔ አስተላልፏል፡፡

 

በቋሚ ሲኖዶስ በተሰጠው ውሳኔ መነሻነት የመንበረ ፖትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በቁጥር 7403/2789/2003 በቀን 18/11/2003 ዓ.ም ቀረጻው ሊካሔድበት ለታሰቡት አህጉረ ስብከቶች ማለትም ለትግራይ ምሥራቃዊ ዞን ሀገረ ስብከትና ለሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ጽ/ቤት ፊልሙ እንዳይሠራና ቀረጻው ተጀምሮ ከሆነም ቀረጻው እንዲቆም በደብዳቤ አስታውቋል፡፡

 

የመንበረ ፖትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የፊልሙን ኢ-ሥርዐታዊነት ገልጦ መስከረም 4 ቀን 2004 ዓ.ም ለጀርመን ኢምባሲ፤ መስከረም 11 ቀን 2004 ዓ.ም ደግሞ በኢትዮጵያ ውስጥ ላሉ አህጉረ ስብከቶች በደብዳቤ መግለጡን የሊቃውንት ጉባኤው በሰጠው መግለጫ አስገንዝቧል፡፡

 

በመሆኑም የተሠራው ፊልም በማንኛውም አጋጣሚ ለዕይታ ቢቀርብ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማታውቀውና የማትቀበለው መሆኑን ምእመናን ተገንዝበው ሕዝበ ክርስቲያኑ ራሳቸውን ከስሕተት እንዲጠብቁ የሊቃውንት ጉባኤው ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

ሐመረ ኖህ በቅዱስ ኤፍሬም ክፍል 4.

ኅዳር 28/2004 ዓ.ም

ትርጉም

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ


ቅዱስ ኤፍሬም በዚህ ቅኔያዊ ድርሰቱ ኖህ ከጥፋት ውኃ የዳነባትን መርከብ በቤተክርስቲያንና በመስቀሉ እንዲሁም በእምነት መስሎ ድንቅ በሆነ መልኩ አቅርቦት እንመለከታለን፡፡

 

  1. የኖህ ተምሳሌትነት በዘመኑ ከነበሩት ሕዝቦች ጋር ሲነጻጸር እንዴት ታላቅ ነበር፤

    ንጽሕናን እንደጥሩር ከለበሰው ኖህ ጋር በፍትሕ ሚዛን ሲመዘኑ እንደማይጠቅሙ እንደማይረቡ ሆነው ተቆጠሩ፤

    ፈጽሞ የማይነጻጸሩ ነበሩና በጥፋት ውኃው ሥር ዘቅጠው ቀሩ፤

    የኖህን ንጽሕና ከፍታ ለማሳየትም ኖህ በመርከብ ሆኖ ወደ ላይ ከፍ ከፍ አለ፤

    በኖህ ንጽሕና ደስ ለተሰኘህ ለአንተ ለእግዚብሔር ክብር ይሁን፤

    ለገዢነትህም ምስጋና ይገባል፡፡

  2. ኖህ ከጥፋት ውኃ በፊትና ከጥፋት ውኃው በኋላ ተምሳሌትነቱ ቀጥሎ ነበር፤

    ያለፈው ዳግም እንዳይመለስ እንደታተመ፤ አዲስ የሆነ ሕይወትም እንደተሰጠን ጥላ ሆነን፤

    እርሱ ለሁለቱ ትውልዶች እንደምሳሌ ነው፤ ያለፈው እንደተቋጨ፤ መጪውም ሕይወት እንደተዘጋጀ ጥላ ነበር፤

    እርሱ አሮጌውን ትውልድ ሲቀብረው፤ ለአዲሱ ትውልድ መጋቢ ሆነ፤

    እርሱን ለዚህ ታላቅ ክብር ለመረጠው ፈጣሪ ምስጋና ይሁን፡፡

  3. የሁሉ ጌታ ያነፃት መርከብ ከጥፋት ውኃው በላይ ከፍ ከፍ በማለት ተነሳፈፈች፤

    ከምሥራቅ ተነቀሳቅሳ ከምዕራብ አረፈች፤

    ከደቡብም ተንቀሳቅሳ ሰሜንን በጉዞዋ ዳሰሰችው፤

    ለምድሪቱ ትንቢትን እየተናገረች በውኃይቱ ላይ ቀዘፈች፤

    አዲሱ ትውልድ እንዴት እንደሚፈጠር እየሰበከች ሀገራትን ሁሉ እያካለለች ዞረች፤

    ኖህን ከጥፋት ላዳነው ጌታ ምስጋና ይሁን፡፡

  4. መርከቢቱ በዙረቱዋ የእግዚአብሔር አዳኝነት ሰበከች፤

    በውኃ ላይ ቤተክርስቲያንን ሊመሠርት የመጣው በመስቀል ለተመሰለችው መርከብ መሪ ነበር፤ እርሱም ክርስቶስ ነው፤

    በዚች መርከብ የተጠለሉትን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ከጥፋት አዳናቸው፤

    በርግቢቱ ምትክ መንፈስ ቅዱስ በእርሱዋ የከበሩትን አገለገላቸው፤

    የክርስቶስን የማዳን ሥራ አከናወነው፤

    ለአዳነን ለጌታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ክብር ምስጋና ይሁን፡፡

  5. የእርሱ ምሳሌ በኦሪት ሕግ ውስጥ ነበር፤ የእርሱ ጥላ በመርከቢቱ ላይ ነበር፤

    አንዱ ለአንዱ አስረጂ ይሆናል፤ መርከቢቱ ከጥፋት ውኃ በኋላ ባዶ እንደነበረች፣ ለክርስቶስ የተመሰሉት ምሳሌዎች በእርሱ መምጣት ፍጻሜ በማግኘታቸው በአማናዊው ተተካ፤

    መርከቢቱም የእርሱ ለሆነች ቤተክርስቲያን ምሳሌነቷ እውን ሆነ፤

    አምላክ ሆይ ለእኛን ለማዳን ስትል ወደዚህ ዓለም መምጣትህ የተመሰገነ ይሁን፡፡

  6. ሕሊናዬ በአዳኛችን የማዳኑ ኃይል ውቅያኖስ ውስጥ በመስጠምዋ በአድንቆት ተሞላች፤

    በጥፋት ውኃው ላይ በመርከቡ የተንሳፈፈ ተመስጦው ያልተወሰደበት ኖህ ብሩክ ነው፤

    ጌታ ሆይ ለእኔም እምነቴ እንደ መርከብ ትሁነኝ የኃጢአትን ባሕርን ቀዝፋ ታሻግረኝ ፤

    ሰነፎች ግን በአንተ ላይ በማፌዛቸው ሰምጠው ወደጥልቁ ወረዱ፤

    አንተን ለወለደህ ለባሕርይ አባትህ ምስጋና ይሁን !!

     

     

     

     

    ቅድስት ድንግል ማርያም በቅዱስ ኤፍሬም ክፍል 3

    ኅዳር 28/2004 ዓ.ም

    በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

     

    በዚህ ክፍል ቅዱስ ኤፍሬም በቅድስት ድንግል ማርያም የተፈጸመውን የተዋሕዶ ምሥጢር በማድነቅና በማመስገን የጻፈውን የቅኔ ድርሰት እንመለከታለን፡፡

    1. ጌታ ሆይ አንተን ምን ብሎ መጥራት እንዳለበት የሚያውቅ ሰው ማን ነው?

      ጌታ ሆይ እናትህን ድንግል ብለን እንጥራትን?

      እንዲያ ብለን እንዳንጠራት የአንተ እናት መሆኑዋ ምስክር ይሆንብናል፤

      ጌታ ሆይ እናት እንበላትን? እንዲህ እንዳንል ወንድ የማታውቅ ድንግል ናት፤

      የእናትህ ነገር ለመረዳት የረቀቀ ከሆነ አንተን ሊረዳ የሚችል ሰው ማን ነው?

      ሁሉን በቀላሉ የምታከናውን የሁሉ አስገኝ የሆንክ ክብር ምስጋና ለአንተ ይሁን፡፡እርሱዋ ብቻ ያንተ እናት ናት፤

    2. ከሁሉ ጋር ደግሞ እኅትህም ናት፤ ስለዚህም እርሱዋ ለአንተ  እናትም፣ እኅትም፣ ሙሽራም ሆናለች፤

      እንደሌሎች ቅዱሳኖችህ፤ የእናትህን ደም ግባት ገንዘብህ ያደረግህ አንተ እርሱዋን በበረከት ሁሉ አስጌጥኻት፡፡አንተ ወደ እርሱዋ ከመምጣትህ በፊት ቅድስት ድንግል ማርያም በልማዳዊ መንገድ ይጠብቃት ዘንድ ለዮሴፍ ተሰጠች፤

    3. አንተ ወደ እርሱዋ ከመጣህ በኋላ ግን ከተፈጥሮአዊ ሥርዐት ውጪ አንተን በድንግልና ፀነሰችህ፤

      አንተ ብቻ ቅዱስ የሆንክ ጌታ ሆይ እርሷ አንተን ቅዱስ በሆነ ልደት በድንግልና ወለደችህ፤ጌታ ሆይ  ቅድስት እናትህ ድንግል ሳለች አንተን ፀንሳ በመውለድ እናትህነትን ገንዘቡዋ አደረገች፤

    4. ድንግል ሆና ሳለች ከጡቶቹዋ ወተት ፈሰሰ፤

      ድንግል ከሆነች መሬት ንጹሕ ምንጭ እንዲፈልቅ፤

      እንዲሁ ድንግል ከሆነችው እናትህ ጡቶች ወተት ፈለቀ፡፡እርሱዋ አንተን ብትሸከምህ አንተ ጽንዕ ሰጥተሃት ነው፤

    5. በተራብክ ጊዜ አንተን ከጡቶቹዋ ትመግብህ ዘንድ፣

      ነቢዩ ዳንኤል በታላቅ ተራራ የመሰለህ አንተን አንደ ሕፃናት ታቀፈችህ፤

      በፈቃድህ የተጠማህ አንተን በእጆቹዋ በፍቅር ትዳብስህ ዘንድ፤

      የምህረት እሳት የሆንኽ አንተ ክንዶቿን መለኮታዊው እሳት እንዳይቃጥላቸው ጠበቅኻቸው፡፡ጌታ ሆይ እናትህ ግሩም የሆኑ ተአምራት የተፈጸሙበት መካን ናት፤

    6. ወደ እርሱዋ የሁሉ ጌታ የሆነው ገባ፤ የአገልጋዩን አርአያ ነስቶ ተወለደ፤

      የእግዚአብሔር ቃሉ የሆነ እርሱ ወደ እርሱዋ ገባ፤ ዝምተኛ ሆኖ ተወለደ፤

      ነጎድጓድ የሆነው እርሱ ወደ እርሱዋ ገባ ፤ጭምት ሆኖ ተወለደ፤

      እረኛ የሆነው እርሱ ወደ እርሱዋ ገባ፤ በግ ሆኖ በመወለድ በአባግዕ ቋንቋ ተናገረ፡፡ጌታ ሆይ የእናትህ ማኅፀን ከተፈጥሮአዊው ሥርዐት በተቃራኒው ፈጸመ፤

    7. ሁሉን ያከናወነ በባለጸግነቱ ወደ እርሷ ገባ፤  ደሃ ሆኖ ተወለደ፤

      ከሁሉ በክብር የሚልቀው እርሱ ወደ እርሷ ገባ፤ ትሑት ሆኖ ተወለደ፤

      በክብሩ ገናና የሆነው እርሱ ወደ እርሱዋ ገባ፤ የባሪያውን መልክ ይዞ ተወለደ፤ብርቱ የሆነው እርሱ ወደ እርሱዋ ገባ፤ ጥበቃ እንደሚያስፈልገው ሕፃን ሆኖ በማኅፀን ተገኘ፤

    8. ፍጥረትን ሁሉ የሚመግበው መራብንና መጠማትን ገንዘቡ አደረገ፤ (አጣጣመ)

      ሁሉን በበረከቱ የሚያለብሰውና የሚያስጌጠው እርሱ ራቁቱን ተወለደ፤

      እኛን ለማዳን ሲል የእኛን ተፈጥሮ ገንዘቡ ላደረገ ለእርሱ ክብር ምስጋና ይሁን፡፡

    በግቢ ጉባኤያት ለሚሰጥ የአብነት ትምህርት አገልግሎት ትኩረት እንስጥ

    ኅዳር 28/2004 ዓ.ም.


    የአብነት ትምህርት የቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎትና የአገልግሎት  ሥርዓት መሠረት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ይህ የአብነት ትምህርት የኢትዮጵያ የትምህርት ታሪክ መሠረትና አንድ አካል ሆኖ ቆይቷል፡፡ የዘመናዊ ትምህርት በሀገራችን መስፋፋቱን ተከትሎ ግን የአብነት ትምህርት ቤቶች ሚና ቤተ ክርስቲያን ለምትፈልገው አገልግሎት በሚያበረክተው ድርሻ ብቻ ተወስኖ እንዲቀር ሆኗል፡፡ ከዚያም አልፎ ቤተ ክርስቲያን የነበራትን የመተዳደሪያ ሀብት ንብረት ማጣቷ በአብነት ትምህርት ቤቶች ጥንካሬ ከዚያም አልፎ በህልውናቸው ላይ ፈተኝ ሁኔታዎች ጋርጧል፡፡

    ከእነዚህ ተጽዕኖዎች በላይ ግን አሳሳቢ የሆነው ከአብነት ትምህርት የሚወጡ ደቀመዛሙርት ዘመናዊውን ትምህርት የሚቀስሙበት አሠራር አለመኖሩ ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ዘመናዊውን ትምህርት የሚከታተሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ለአብነት ትምህርቱ ባዕድ ሲሆኑ መታየታቸው ነው፡፡ እነዚህ ሁለት ዓለማት በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ውስጥ እየታዩ መምጣታቸው በአገልግሎት አሰጣጡ እና አቀባበሉ አለመግባባት፣ በቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት አንድነት ላይ ፈተና የማስከተል አዝማሚያ እንዲታይ አድርጓል፡፡ በተጨማሪም ቤተ ክርስቲያን በዘመኑ ልትጠቀምበት የሚገባውን የአሠራር፣ የአደረጃጀት፣ የአመራርና የአስተዳደር ዘይቤ ከዘመናዊው የትምህርት ሥርዓት እንዳትወስድ አድርጓታል፡፡

    እነዚህ መራራቆች በቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችና አገልግሎቱን በሚቀበሉ ምእመናን መካከል ያለው ግንኙነት ላይ ችግሮች ሊያስከትሉ የሚችሉ ናቸው፡፡ በመጀመሪያ በአገልግሎት አሰጣጡ የሚያስፈልገውን ሥነልቦናዊ አንድነት ያሳጣል፡፡ ከዚያ ውጭ አንዱ የትምሀርት ምንጭ ለሌላው ያለው አተያይ የተዛባ እንዲሆን ያደርጋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም ዘመናዊ የሚባለው ዓለም ያመጣውን ዕሴት ሁሉ በጭፍን የምትቃወም፣ የምትጸየፍም ያስመስላል፡፡ በአንጻሩ ዘመናዊ የሚባለው ዓለም የቤተ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ ኋላቀር አድርጎ የማሰቡ አዝማሚያ ይታያል፡፡ ስለዚህ ይህንን የአመለካከት መራራቅ አጥፍቶ ቀጣይነት ያለው መፍትሔ ለማምጣት እንዲሁም በዘመናዊው ትምህርት ደቀመዛሙርትና በአብነት ትምህርት ደቀመዛሙርት መካከል በአገልግሎት አሰጣጥና አቀባበል ያለውን የመንፈስ አንድነት ለማምጣት ርእይ ይዞ፣ የሚጠይቀ ውን ስልታዊ ዕቅድ አውጥቶ ወደ ሥራ መግባት ተገቢ ነው፡፡

    ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን ርእይ እውን ለማድረግ የሚቻለው በሁለቱም ዓይነት ትምህርት ምንጭ በሆኑ ትምህርት ቤቶች ማለትም በአብነት ትምህርት ቤቶችና በዘመናዊው ትምህርት ተቋማት /ዩኒቨርሲቲዎችና ኮሌጆች/ ላይ ቢሠራ እንደሆነ ያምናል፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሁለት ተቋማት ማኅበሩ ያለውን የአገልግሎት ርእይ እውን ለማድረግ የመረጣቸው ስልታዊ ተቋማት ናቸው፡፡

    በመሆኑም የአብነት ትምህርት የሚሰጥባቸው ጉባኤያት በተለያዩ ምክንያቶች እንዳይፈቱ ለማድረግ ምእመናንን በማስተባበር ለትምህርት ቤቶቹ እድገት፣ ለመምህራኑ እና ለደቀመዛሙርቱ ኑሮ ከሚያደርገው ቁሳዊ ድጋፍ በተጨማሪ በጉባኤያቱ ከሚሰጠው መንፈሳዊ የአገልግሎት ትምህርት ጎን ለጎን የዘመናዊው ትምህርት ዕሴቶች ከሆኑት የአስተዳደር፣ የአመራር እና የሙያ ሥልጠናዎችን እንዲያገኙ እየተጋ ነው፡፡

    ዘመናዊው የትምህርት ሥርዓት ተግባራዊ በሚደረግባቸው ኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች ላሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች ደግሞ ባቅራቢያቸው ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ሰብስቦ የተለያዩ መንፈሳዊ አገልግሎቶችን በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ ከእነዚህ አገልግሎቶች አንዱ ደግሞ የአብነት ትምህርት ነው፡፡ ተማሪዎች ዘመናዊ ትምህርት በሚከታተሉባቸው የትምህርት ተቋማት ውስጥ ሆነው  ከአብነት ትምህርት ጉባኤያት ጋር እንዲተዋወቁ፤ ከዚያም ባለፈ በጉባኤያቱ ተምረው አስመስክረው እንዲወጡ፤ የዲቁናና የቅስና መዓርገ ክህነት እንዲቀበሉ ለማድረግ ጥረት እያደረገ ነው፡፡ የአብነት ትምህርት ጣዕምና መዓዛ ስበት ቀላል ባለመሆኑ በትምህርት ቆይታቸው ጊዜ ብቻ ሳይሆን ከትምህርት ገበታም ውጭ በሥራ ላይ እያሉ የመከታተል፣ የማስፋት፣ የማሳደግ ፍላጎት እንዲያድርባቸው ያደርጋል፡፡

    የዚህ ተግባር ዋነኛ ግቦችም አስቀድመን የጠቀስነውን የአብነት ትምህርቱን ክብርና አስፈላጊነት ከኮሌጅና ዩኒቨርሲቲዎች የሚወጡ፣ ሀገሪቱ ወደፊት ከፍተኛ ሓላፊነት የምትሰጣቸው፣ የሀገራ ችን ዕድገት ፖሊሲ አውጪና አስፈጻሚ ልሂቃን እንዲያውቁት፣ እንዲወዱት፣ እንዲያከብሩት፣ እንዲያገለግሉበትና እንዲገለገሉበ ትም ማድረግ ነው፡፡ የኮሌጅና የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች እነዚህን ጉባኤያት ባወቋቸው ቁጥር እንደሚወዷቸው ይታመናል፡፡ ከወደዷቸው ደግሞ ይንከባከቧቸዋል፤ ያበለጽጓቸዋል፡፡ ስለዚህ የአብነት ትምህርቱን ህልውና ከማስጠበቅም አንጻር ታላቅ ሚና ይኖራቸዋል፡፡ ከዚያ ባለፈ ግን የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት በሀገሪቱ የተለያዩ ሓላፊነትን፣ የሙያ ስምሪትንም ይዘው ከሚሠሩ ልሂቃን ጋር በአንዲት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት ውስጥ ተግባብተው የማየት ርእይ እውን ይሆናል፡፡

    ማኅበረ ቅዱሳን ይህ ርእይ የሁሉም የቤተ ክርስቲያን ወገን ርእይ መሆኑንም ያምናል፡፡ ከዚህ እምነት በመነሣትም የሁሉም ወገን ርእይ እውን እንዲሆን ደረጃ በደረጃ በሚፈጸሙ ተግባራት ውስጥ ሁሉም የድርሻውን እንዲወጣ ይሻል፡፡ የሁሉም አካላት ድርሻ የሚመነጨው ደግሞ ካለን አቅም ነው፡፡ ለዚህች ሀገር ዕድገት በጎ ሐሳብ ያላቸው መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች የአብነት ትምህርት የቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት ዕውቀት ብቻ ሳይሆን የሀገሪቱ መንፈሳዊ ቅርሶች አንዱ አካል፣ ለማኅበረሰቦች የአኗኗር ባህልና ዕሴት አስተዋጽኦ የነበረውና ያለው የትምህርት ሥርዓት በመሆኑና የሀገራችን የትምህርት ታሪክ መሠረት በመ ሆኑ በሚመለከቷቸው ሓላፊነቶች በኩል ሊያደርጓቸው የሚገቡ አስተዋጽኦዎችን ማበርከት ይገባቸዋል፡፡

    ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት ድርሻ ግን መተኪያ የሌለው ነው፡፡ በዚህ ረገድ ምእመናንና የቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ከፍተኛ ባለደርሻ ናቸው፡፡ በየደረጃው ያሉ የቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር አካላት በተሰጣቸው የሓላፊነት ደረጃ ልክ የወደፊቱን የቤተ ክርስቲያናችንን የአገልግሎት አካሔድ የተሻለ ለማደረግና ከፈተና ለመጠበቅ መጣር ይገባቸዋል፡፡ በኮሌጆችና ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙ ተማሪዎች የአብነት ትምህርትን ቀስመው እንዲወጡ ከማነሣሣት ጀምሮ አገልግሎቱን እንዲያገኙ ምቹ ሁኔታ መፍጠር፣ ልባዊ ድጋፍም መስጠት ይጠበቅባቸዋል፡፡

    ምእመናን ደግሞ የአብነት ተማሪዎችንና ትምህርት ቤቶችን መምህራንና ደቀመዛሙርቱን ለመደገፍ እንዲቻል ማኅበረ ቅዱሳን የሚያደርገውን ጥረት በገንዘባቸው፣ በጉልበትና በዕውቀታቸው  ለመደገፍ ያለመሰልቸት መንቀሳቀስ ይመበቅባቸዋል፡፡ በኮሌጅና ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙ ተማሪዎችም የአብነት ትምህርት መርኀ ግብሮችን በተጓዳኝ መከታተል እንዲችሉ ማበረታታት ይገባቸዋል፡፡ ወደኮሌጆች ከመግባታቸውም በፊት ተማሪዎች በየትውልድ አካባ ቢያቸው አብነት ትምህርትን ለመከታተል ዝንባሌ እንዲያድር ባቸው ማድረግ ይገባቸዋል፡፡

    በየደረጃው ያሉ የማኅበራችን ማዕከላትም ምቹ ሁኔታ ተፈጥሮ የአብነት ትምህርት ለመከታተል ለተዘጋጁ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ስልታዊ በሆነ መንገድ ተምረው ዘመናዊውን ትምህርት በብቃት የተከታተሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች በአገልጋይነትም ሲሳተፉ ለማየት የያዝነውን ርእይ እውን እንዲሆን ሊተጉ ይገባል፡፡ ለዚህም ተማሪዎቹን ማነሣሣት፣ መምህራንና የትምህርት ቦታውን ማዘጋጀት፣ ከሚከታተሉት ዘመናዊ ትምህርት ጋር የተጣጣመ መርኀ ግብር መንደፍ፣ የተማሩትን ትምህርት ደረጃ እንዲያውቁ በአጥቢያቸው ባሉ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎቶች እንዲሳተፉ ማድረግ የየጊዜውን ሂደት መገምገም እና የመሳሰሉት ተግባራት ሁሉ ይጠበቁብናል፡፡

    በአጠቃላይ በዚህ ረገድ ለተያዘው ርእይ እውን መሆን ድርሻ አለኝ የሚሉ አካላት ሁሉ ባላቸው አቅምና ችሎታ ሚና እንዲጫወቱ ማኅበራችን ይጠይቃል፡፡ ሁሉም ወገን የቤተ ክርስቲያን  አገልጋዮቿ በሁሉም ነገር አቅማቸው የጎለበተ ሆነው በአንድ ሐሳብ በአንድ ልብ ለቤተክርስቲያንና ለሀገር ተስፋ እንዲሆኑ መጣር ይገባል፡፡

     

    ምንጭ፡- ሐመር 19ኛ ዓመት ቁ.6 ጥቅምት 2004 ዓ.ም

    ሥጋ ለነባቢት ነፍስ እንድትታዘዝና የፈቲው ፆርም እንዲደክም- ጾም

    ግንቦት 28ቀን 2007ዓ.ም

    በፍትሐ ነገሥት መንፈሳዊ አንቀጽ 15 እንደተገለጸው ቅዱሳን አባቶቻችን ሥጋ ለነባቢት ነፍስ እንድትታዘዝና የፈቲው ፆርም እንዲደክም የሚያደርግ የሰውን ልጅ ከእግዚአብሔር ጋር እንዲገናኝ የለመነውም ልመና መልስ እንዲኖረው የሰይጣንን ፍላጻ ለመስበር የሚያስችል ኃይል ያለው መሣሪያ ጾም ነው ብለው ጽፈዋል፡፡

    ነቢየ እግዚአብሔር«በእግዚአብሔር አምላካችን ፊት ራሳችንን ዝቅ እናድርግ፣ በእርሱም ዘንድ ጾምን አወጅኩኝ ስለዚህ ነገር ጾምን፣ ወደ እግዚአብሔርም ለመንን እርሱም ተለመነን፡፡» እንዳለ የሰው ልጅ የነፍሱን ነገር በማሰብ በጾም እግዚአብሔርን ሊለምን ሊማጸን የሚፈልገውን ሁሉ ሊጠይቅ ይገባል፡፡ ከነቢዩ ዕዝራ የምንማረው በጾም ለሕዝብና ለራስ ለምኖ ዋጋ ማግኘትን ነው፡፡ 

    ዐወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ «ይህ ነገር ያለጾምና ያለጸሎት አይወጣም» /ማቴ.17-2/ ሲል የሚያስረዳን ትልቅ ምስጢር አለ፡፡ እርስ በእርሳችን የሚያጣላን የሚያቀያይመን ይባስም ብሎ ከአምላካችን ጋር እንድንለይ የሚያደረገውን በዐይናችን የማናየውን የዘወትር ጠላታችን ሰይጣንን ድል መንሳት የምንችለው በጾምና በጸሎት ነው፡፡ ለዚህም ነቢዩ«ጾምን ለዩ ምህላንም አውጁ» እንዳለ /ኢዩ.2-11/ የሰው ልጅ ፈቃደ ሥጋውን ለፈቃደ ነፍሱ ለማስገዛት ጾምን በራሱ ላይ ሊያውጅ ወይም ሊያነግሥ ይገባል፡፡

    ዐበብሉይ ኪዳን ዘመን እጅግ ብዙ ቅዱሳን አባቶቻችን በጾም የጠየቁትን ሁሉ አግኝተዋል፡፡ ለምሳሌ ነቢየ እግዚአብሔር ሙሴ እስራኤልን በሚመራበት ወቅት አሕዛብ እንዳይሰለጥኑበት፣ ወገኖቹም እስራኤል የአሕዛብን አምልኮት ተከትለው ከአምላካቸው ከእግዚአብሔር ዘንድ እንዳይለዩ፣ እንዳይራቡ፣ እንዳይጠሙ፣ በተለይም ዘወትር ለመንፈሳዊ ጉዟቸው የሚያሰፈልጋቸውን ሕጉ የተጻፈበትን ቅዱስ ታቦት የተቀበለው 40 ቀንና 40 ሌሊት በሲና ተራራ በመጾም በመጸለይ ነበር፡፡

    ነቢየ እግዚአብሔር ኤልያስም ይህችን ረብ ጥቅም የሌላትን ጊዜያዊና ኃላፊ ዓለም ትቶ የሚበልጠውን መንፈሳዊውን ዓለም ለማግኘት ወደ ሰማይ ያረገው በጾም ኃይል ነው፡፡ ነቢዩ ዳንኤል መንፈሳዊ ኃይል ተሰጥቶት ታላቋን የባቢሎንን ከተማ በማናወጥ በሥጋ ሐሳብና ኃይል የማይቻለውን ድንቅ ነገር ማድረግ የቻለው የአናብስትን አፍ የዘጋው በጾም በጸሎት ነው፡፡ ሦስቱ ሕፃናትም ሳይቀሩ ከነበልባል እሳት የዳኑት በጾም ኃይል እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡

    ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ የማስተማር ተግባሩን ሳይጀምር ለሥራው ሁሉ ተቀዳሚ ያደረገው ጾምን ነው፡፡ በጾሙም ወቅት ዲያብሎስ ስለተፈታተነው በቀረበለት ፈተና ሁሉ ድል ነሥቶታል፡፡ ከዲያብሎስ የቀረቡለትም ፈተናዎች ስስት፣ ትዕቢትና ፍቅረ ንዋይ ነበሩ፡፡ ክርስቶስም በስስት የመጣውን በትዕግሥት፣ በትዕቢት የመጣውን በትሕትና እንዲሁም በፍቅረ ንዋይ የመጣውን በጸሊአ ንዋይ ዲያብሎስን ድል ነስቶታል፡፡ ማቴ.1-1-11፡፡

    አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከጾመው ጾም የምንማረውም የኃጢአት ሁሉ ሥር የሆነውን ዲያብሎስን ድል መንሣት ሲሆን ይኸውም በጾም፣ በጸሎት፣ በትዕግሥት፣ በትሕትና፣ በሃይማኖት፣ በጸሊአ ንዋይ ወይም ገንዘብን በመጥላት ወዘተ መሆኑን እንረዳለን፡፡ ስለሆነም በዚህ ታላቅ የጾም ወቅት ሁላችንም ትችት፣ ሐሜት፣ ቅናት፣ ተንኮል ወዘተ ፍላጎቱ የሆነውን የሥጋ ፈቃዳችንን ለነባቢት፣ ለባዊትና ሕያዊት ነፍስ ፈቃድ በማስገዛት የሥጋ ፈቃዳት የተባሉትንም በማሸነፍ የፈቲው ጾርንም በማድከም ከልብና በሃይማኖት ልንጾም ይገባል፡፡ ብዙ ሰዎች ከጊዜያዊ እህል ውኃ ይጾማሉ ወይም ያስቀድሳሉ ይጸልያሉ ብዙ መንፈሳዊ ሥራዎችን ይሠራሉ፡፡

    ጾም ክርስቲያኖች የሆኑ ሁሉ በጠባብ በር ወደ ተመሰለው ፈቃደ ነፍስ ለመግባት ሊሽቀዳደሙበት የሚገባ ተግባር ነው፡፡ ክርስቶስ በተራራው ስብከቱ «ብፁዓን ይርኅቡ ወየጸምኡ በእንተ ጽድቅ እስመ እሙንቱ»፤ ስለጽድቅ የሚራቡና የሚጠሙ ብፁዓን ናቸው ይጠግባሉና ሲል አስተምሯል፡፡ /ማቴ.5-6/፡፡ ስለጽድቅና ስለ መንግሥተ ሰማያት ሲሉ ከሚበሉት እየቀነሱ ለጦም አዳሪዎች የሚሰጡ ብፁዓን ይባላሉ፡፡ በመንግሥተ ሰማያት አይራቡምና፡፡ እግዚአብሔር የሰጣቸውን ገንዘብ ሳይሰስቱ ለተራቡ የሚሰጡ፣ በትሕትናቸው ብዙ መንፈሳውያን የትሕትና ሰዎችን የሚያፈሩ በትዕግሥታቸው ሰዎች ወደ እግዚአብሔር እንዲቀርቡ ምክንያት የሚሆኑ ሰዎች ይህን መዋዕለ ጾም አስበውታል የጾም ትርጉሙም ገብቷቸዋል ማለት ያስችላል፡፡ እየጾሙ፣ እየሰበኩ፣ እየዘመሩ፣ እያስተማሩ ለሌሎች ሰዎች ፍቅር ከሌላቸው ክርስቶስን መስለውታል ለማለት ያስቸግራል፡፡ ስለሆነም ጾም ስናውጅ ትርጉም ያለው ለንስሐ የሚያበቃ ጾም እንዲሆንልን ፍቅራችን፣ መተሳሰባችን ሊጨምር ይገባዋል፡፡

    ሁላችንም እንደ ዘኬዎስ ኢየሱስን ለማየት እንፈልጋለን የምንወጣበት ዛፍ ግን እጅግ ያስፈራናል፡፡ ሁሉንም በእግዚአብሔር እንድንችለው ትሕትና፣ ፍቅር ሃይማኖት ሊኖረን ይገባል፡፡ እንዲሁም አቅማችንን በማወቅም ደረጃ ብዙ ይቀረናል፡፡ ሰው ሁል ጊዜ ታናሽ እንደሆነ ክርስትናውም ዕለት ዕለት ማደግ እንዳለበት ካላመነ እጅግ ከባድ አደጋ ውስጥ ይገባል፡፡

    እግዚአብሔር የሌለበት ቦታ የለም፣ የማይኖርበትም ጊዜ የለም ለኃጢአተኛም ይሁን ለጻድቅ ሰው እግዚአብሔር ቅርብ ነው፡፡ በድለን በደላችንን በመንገር የሚደመስስልን ቸር አምላክ፤ ኃጢአት ሠርተን በኃጢአታችን የማያጠፋን ይቅር ባይ ታጋሽ ጌታ ስለሆነ እግዚአብሔርን ከምንምና ከማንም በላይ በፍጹም ፍቅር መቅረብና መማጸን ይገባናል፡፡

    ጾም ከደዌ ሥጋና ከደዌ ነፍስ ለመፈወስ የምንችልበት መንፈሳዊ ኀይል ስላለው የሚሰጠውን ጥቅም ማወቅና መረዳት ይኖርብናል፡፡ ይህም ከሆነ በጾም ሥጋ ለነባቢት ነፍስ እንድትታዘዝና የፈቲው ፆርም እንዲደክም ያስችላል ማለት ነው፡፡ ጾመን የበረከቱ ተሳታፊዎች እንድንሆን በዚህ ለሥጋችንም ፈቃድና ሐሳብ ሳይሆን ለነፍሳችን ዘለዓለማዊ ሕይወት እንድናስብ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ አሜን፡፡

    ወስብሐት ለእግዚአብሔር

    ቅርሶችን በተመለከተ ዐውደ ጥናት ተካሔደ

    ኅዳር 22/2004 ዓ.ም

    በእንዳለ ደምስስ

    የማይዳሰሱ ባሕላዊ ቅርሶች አያያዝ /አተገባበር/ ስምምነት በሀገር አቀፍ ደረጃ /Implementation of the Intangible cultural Heritage convention at national level/ በሚል ርዕስ ዐውደ ጥናት ተካሔደ፡፡ ዐውደ ጥናቱ የባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣን ከተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፣ የሳይንስና የባህል ተቋም /UNESCO/ ጋር በመተባበር ያዘጋጀው ሲሆን፤ ከኅዳር 4-8/2004 ዓ.ም ድረስ ለአምስት ተከታታይ ቀናት ለመካሔድ ችሏል፡፡ በዐውደ ጥናቱ ላይ የዩኒስኮ ተወካይ በሆኑት በፕሮፌሰር አማርሰዋር ጋላ እና በቅርስና ጥበቃ ባለስልጣን ባለሙያዎች ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ሰፊ ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

    በዐውደ ጥናቱ ላይ የየክልሉ የቅርስና ጥበቃ መሥሪያ ቤት ተወካዮችና ባለሙያዎች የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከልና የሚመለከታቸው አካላት የተገኙ ሲሆን፤ በሀገራችን ውስጥ የሚገኙ የማይዳሰሱ /Intangible/ ቅርሶችን ኅብረተሰቡ እንዲያውቃቸው እንዲጠብቃቸው፣ እንዲያስተዋውቃቸውና በዓለም ቅርስነት እንዲያስመዘግባቸው ከዓለም አቀፍ የቅርስና ጥበቃ ስምምነት ጋር በተጣጣመ መልኩ ለማራመድ እንዲቻል ግንዛቤ ለማስጨበጥ ታስቦ የተዘጋጀ ነው፡፡ የሌሎች ሀገራት ተሞክሮዎች በዐውደ ጥናቱ ላይ በሰፊው ተዳሰዋል፡፡

     

    ዐውደ ጥናቱ ያተኮረባቸው መሠረታዊ ነጥቦችን ስንመለከት፣ ጥበቃ የሚያስፈልጋቸው የማይዳሰሱ /intangible/ ባሕላዊና ሃይማኖታዊ ቅርሶችን በተለይም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የምትጠቀምበትን የቅዳሴ፣ የያሬድ ዜማዎች፣ የአቋቋም፣ የቅኔ፣ እንዲሁም ሌሎች የብሔር ብሔረሰቦች ባህላዊ እሴቶቻችንን ለማየት ተሞክሯል፡፡ ለትውልድ ለማስተላለፍ በሀገር አቀፍ ደረጃ ማን ምን ያድርግ? ለሚለው ጥያቄ ማኅበረሰቡ፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች፣ ባለሙያዎችና የጥናትና ምርምር ተቋማት እንዲሁም ግለሰቦች ማከናወን ስለሚገባቸው ተግባራት በስፋት የተዳሰሱ ጉዳዮች ናቸው፡፡ በተጨማሪም የማይዳሰሱ በተሰኙ ቅርሶች ዙሪያ ለሚመለከታቸው አካላት ግንዛቤ ለማስጨበጥ መከናወን ስለሚገባቸው ተግባራት ለይቶ ማውጣትና መለካት፣ ማኅበረሰቡን ማሳተፍ፣ ቀጣይነት ያለው ጥበቃና ክትትል ማድረግ እንደሚያስፈልግ በጥናቱ ተጠቁሟል፡፡

    የማይዳሰሱ /Intangible/ የሆኑ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቅርሶችን በተመለከተ የወጡ ፖሊሲዎችንና አዋጆችን ተግባራዊ ማድረግ፣ ጥናትና ጥበቃ የሚደረግላቸውን ቅርሶች ለመንከባከብ እንዲቻል የተለያዩ ተደራሽ አካላትን መምረጥ፣ ማደራጀትና ማዋቀር፣ ከዓለም አቀፍ ተቋማት ጋር በጋራ በመሥራት ድጋፎችን ማግኘት የሚቻልበት መንገድ ማመቻቸት እንደማገባ ተገልጿል፡፡

    ዐውደ ጥናቱ በባህልና ቱሪዝም የቅርስ ጥበቃ ባለሙያዎችንና ሌሎች ባለድርሻ አካላትን ያካተተ እንደመሆኑ በቡድን በቡድን በመሆን አሉ የተባሉ ጠቃሚና ጎጂ ተጽዕኖዎች በማይዳሰሱ ሃይማኖታዊና ባህላዊ ቅርሶች ዙሪያ /positive and negative impacts to Implement Intangible cultural heritage/ በዝርዝር ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡

    በዐውደ ጥናቱም ከተለያዩ የቅርስና ጥበቃ ባለሙያዎች ጥናቶች ቀርበዋል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማዕከል የተለያዩ ተሞክሮዎችን ለታዳሚው ማካፈል የተቻለ ሲሆን በቀጣይነትም በጋራ ለመሥራት የሚያስችሉ በጎ ገጽታዎችን ለመፍጠር ጥረት ተደርጓል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያሏትን የማይዳሰሱ /Intangible/ ቅርሶች ሃይማኖታዊና ባህላዊ እሴቶችን ለትውልድ ለማስተላለፍ የሚረዳና መንገዶችንም ያመቻቸ ዐውደ ጥናት በመሆኑ ከባለድርሻ አካላት ብዙ ይጠበቃል፡፡ ለአምስት ተከታታይ ቀናት የተካሔደው ዐውደ ጥናት ኅዳር 8/2004 ዓ.ም ተጠናቋል፡፡

    የፍትሕ ነፃነትን የሚያስከብር የመንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች ማጠናከሪያ ሕግ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸደቀ


    ኅዳር 22/2004
    ዓ.ም

    ዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ
    • ረቂቅ ሕጉን የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እንደሚያጸድቀው ይጠበቃል፡፡

    የፍትሕ ነፃነትን የሚያስከብር የመንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች ማጠናከሪያ ሕግን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በሙሉ ድምጽ ማጽደቁ ተገለጸ፡፡

    ሕጉ የጸደቀው የሲኖዶሱ ምልዓተ ጉባኤ ጥቅምት 23 ቀን 2004 ዓ.ም ባደረገው ዓመታዊ የምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ላይ ሲሆን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ፣ 30ኛውን ዓመታዊ አጠቃላይ ሰበካ ጉባኤ ሲከፍቱ በአስተላለፉት ቃለ በረከት “ውኃው ከአጠገባቸው እያለ ተጠምተው የሞቱ ብዙ ናቸው” ብለዋል፡፡ አያይዘውም የሕግ ምንጭ የሆነችው የኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ፍትሕ ፍለጋ የዓለማዊውን ፍርድ ቤት ሲናፍቁና ሲያጨናንቁ ማየት ችግር መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ መፍትሔውም የዳኝነት ነፃነትን የሚያስከብረውን የሕግ ረቂቅ ለቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ  ማቅረብና  ማጽደቅ በመሆኑም ይህንኑ ማድረግ መቻሉም በማኅበረ ክርስቲያኑ ፍትሕን ለማስፈን የቆመ የመሠረት አለት ነው ብለዋል፡፡

    የጠቅላይ ቤተ ክህነት ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ዋና ሰብሳቢ መልአከ ምሕረት አምኃ መኳንንት በበኩላቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ከዘመነ ሕገ ልቡና ጀምሮ የሕግ ምንጭ ሁና ለትውልድና ለሀገር ያበረከተችውን ሁለንተናዊ ሥርዓት የታሪክ መዛግብቱና ሊቃውንቱ የሚመሠክሩት እንደሆነ አስታውሰዋል፡፡ ይህንም መሥመር በመከተል የቤተ ክርስቲያኗን መንፈሳዊ ፍርድ ቤቶች እንደገና ለማቋቋምና ለማጠናከር በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና በሕግ ባለሙያዎች ተጠንቶ የተዘጋጀው ባለ 10 ገጽ የሕግ ረቂቅ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት በኩል እውቅና አግኝቶ በሥራ ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ የሕጉን ረቂቅ በሙሉ ድምጽ ማጽደቁን ጨምረው አስታውቀዋል፡፡

    ሕጉ የሚሰጣቸውን ጠቀሜታዎች አስመልክተው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ይግባኝ ሰሚ ፍርድ ቤት ዋና ሰብሳቢ መልአከ ምሕረት አምኃ መኳንንት ጨምረው  እንዳስታወቁት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ባሉ አገልጋዮች፣ ሠራተኞችና በተቋማቱ መካከል ለሚነሡ ክርክሮች ሕጋዊ መፍትሔ መስጠቱ፤ እንዲሁም ከሞት በኋላ በውርስ ጊዜ በተለይ የመነኮሳትን ሀብት በመፈለግ ብቻ ሕጋዊ ባልሆነ ተዛምዶ /ዝምድና/ ሰበብ የቤተ ክርስቲያንን ክብር ለማስነቀፍ ከሚሞክሩ አካላት መከላከል ስለሚያስችልና በክርክር ጊዜ የተከራካሪዎችን ሃይማኖታዊ ክብር ማስጠበቁ በተጨማሪም በአሁኑ ጊዜ ከ500.000 በላይ የሚሆኑትን የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችና ሠራተኞች መብትና ግዴታ በሕግ ለማስከበር ማገዙ የሚጠቀስ ሲሆን ቤተ ክርስቲያን በራሷ ፍርድ ቤት ፍትሕ ለማስፈን የምታደርገውን ጥረት እንደሚያግዝ ይጠቅማል ብለዋል፡፡

    የዳኝነት ነፃነትን የሚያስከብረው የመንፈሳዊ ፍርድ ቤቶችን ማጠናከሪያ ሕግ እንዲጸድቅ ለሥራው መቃናት ዋናው ፈቃደ እግዚአብሔር ሆኖ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የኢሉባቦርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ፊሊጶስ በሰጡት ቅን አመራር የሕጉ ረቂቅ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደር ጉባኤ ታይቶ በ30ኛው አጠቃላይ ሰበካ ጉባኤ ድጋፍ አግኝቶ ብፁዕነታቸው በሚመሩት ፍትሐዊ አመራር ተመቻችቶና ተዘጋጅቶ እንደቀረበ ለማወቅ ተችሏል፡፡

    DSC01450

    በስልጤና ሀድያ፣ ጉራጌ፣ ከንባታ ሀገረ ስብከት በፖሊሶች የፈረሰው የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን በአክራሪ ሙስሊሞች ፍርስራሹ ተቃጠለ፡፡

    ኅዳር 21/2004 ዓ.ም

    በዲ/ን ኅሩይ ባዬ

    ፠በቃጠሎው ወንጀል የስልጤ ቲትጎራ 1ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት እና የስልጢ 2ኛ ደረጃ ተማሪዎች ተሳትፍበውታል፡፡
    ፠የስልጢ አረጋውያን ሙስሊሞች ድርጊቱን ተቃውመዋል፡፡

    በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በስልጤና ሀድያ፣ ጉራጌ፣ ከንባታ ሀገረ ስብከት በስልጤ ደብረ ስብሐት ቅድስት ማርያምና ቆቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ስር የተመሠረተው የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም ረፋድ ላይ በአክራሪ ሙስሊሞች ሙሉ ለሙሉ መቃጠሉን ለመረዳት ተችሏል፡፡

    DSC01450

    የቤተ ክርስቲያኑ መቃጠል እንደተሰማ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና የማኅበረ ቅዱሳን ልዑካን በቦታው ተገኝተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ወደ ስልጢ ከመሔዳቸው በፊት በቡታጅራ ከተማ ተገኝተው በቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የማጽናኛ መልእክት በማስተላለፍ የቡታ ጅራ ሕዝበ ክርስቲያን እንዲረጋጋ አድርገዋል፡፡

    ቤተ ክርስቲያኑ ለምንና እንዴት እንደተቃጠለ ለማጣራት የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት የጸጥታ አስተዳዳር ምክትል ሓላፊ አቶ ኢዮብ አንበሳ፣ የክልሉ ርእሰ መስተዳድር አማካሪ አቶ ፋሲል ጌታቸውና የክልሉ የጸጥታ ዘርፍ የሥራ ሒደት ሓላፊ አቶ በረከት ጌኤ  ተገኝተዋል፡፡

    ቤተ ክርስቲያኑ እንዲቃጠል ከፍተኛውን ድርሻ ወስደው ተማሪዎችን ሲቀሰቅሱ የነበሩ በስም የሚታወቁ ግለሰቦችና አክራሪ ሙስሊሞች እንደሆኑ ተገንዝበናል፡፡ የወረዳው አስተዳደር ጽ/ቤት ወንጀሉ እንዳይፈጸም የቅድሚያ ዝግጅት ለምን እንዳላደረገ ለቀረበለት ጥያቄ እንደ መንግሥት አስተዳደር በሃይማኖት ጉዳይ ጣልቃ መግባት ስለሌለብን ነው የሚል ምላሽ ሰጥቷል፡፡ በሃይማኖት ጉዳይ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት እስከ የት እንደሆነ በግልጽ ማብራራት ያልቻሉት የስልጤ ወረዳ አስተዳዳሪ አቶ ሐያቱ ሙክታር “የተቃጠለው ቤተ ክርስቲያን አይደለም” የሚል ማስተባበያ ለመስጠት መሞከራቸውን አረጋግጠናል፡፡ ሆኖም የተቃጠለው ቤተ ክርስቲያን ለመሆኑ የፎቶግራፍ ማስረጃ ለክልሉ ባለስልጣናት ሊቀ ጳጳሱ አቅርበዋል፡፡ ዜጎች በሀገራቸው ተከባብረው፣ ተፈቃቅረው ለሰላም       ለልማትና ለእድገት በሚተጉበት በዚህ ወቅት መንግሥት ባለበት ከተማ እንዲህ ያለ ወንጀል መፈጸሙ ያሳዘናቸው ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ወንጀሉን የፈጸሙ አካላትን ጉዳይ ለፍርድ የማቅረቡን ሒደት ከሚመለከታቸው የበላይ የመንግሥት አካላት ጋር በመወያየት ላይ መሆናቸውን አስታውቀዋል፡፡

    ተማሪዎች ከትምህርት ገበታቸው ወጥተው ቤተ ክርስቲያንን ለማቃጠል ያነሣሣቸውን አካል በሕግ መጠየቅ እንዳለበት ያብራሩት የክልሉ የጸጥታ አስተዳዳሪም የሕዝበ ክርስቲያኑን ትእግሥት አድንቀዋል፡፡

    ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም አመሻሽ ላይ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የስልጢ ከተማ ምእመናንና የክልሉ የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት ከ25 እስከ 30 የሚሆኑ የምእመናን ተወካዮች ተመርጠው ከሚመለከታቸው የሕግ አካላት ጋር ወንጀለኞችን ለማጋለጥ የማጣራቱ ሒደት ቀጥሏል፡፡

    ዛሬ በደረሰን መረጃ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስና የመንግሥት ባለሥልጣናት በተገኙበት በምእመናን የተመረጡ ከ25 እስከ 30 የሚሆኑ ሽማግሌዎች ሥራቸውን እንዳይጀምሩ እየተደረገ ነው፡፡ በተለይ ከ1938 ዓ.ም ጀምሮ የደብረ ስብሐት ቅድስት ማርያምና ቆቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ለጥምቀተ ባሕር የሚጠቀሙበት ቦታ ለሌላ አገልግሎት መዋል የለበትም የሚል አቤቱታ ሲያቀርቡ የነበሩ ካህናት በኮሚቴ ውስጥ ቢመረጡም ሥራቸውን መቀጠል አልቻሉም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ጉዳዩን በደንብ የማያውቁት ሰዎች እንዲተኩ መደረጋቸው የችግሩን መንስኤና ዘለቄታዊ መፍትሔ ለማግኘት አጠራጣሪ እንደሆነ የአካባቢው ምእመናን ጠቁመዋል፡፡

     

    ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም የቤተ ክርስቲያኑን መፍረስ የዘገብን መሆኑ ይታወቃል፡፡ የቃጠሎውን ተግባር የፈጸሙት በእድሜ ያልበሰሉ ሕፃናት ናቸው ተብሎ ወንጀሉ እንዲዳፈን መደረጉ እንዳሳዘናቸው የስልጢ ምእመናን እያሳሰቡ ነው፡፡