3p-03

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ታቦተ ጽዮን

ኅዳር 20/2004 ዓ.ም

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

 

እግዚአብሔር አምላክ ሕዝበ እስራኤልን ከግብጽ ባርነት ካወጣቸው በኋላ የአምልኮ ሥርዐታትን ይፈጽሙበት ዘንድ የምስክሩን ድንኳን፣ የቃል ኪዳኗ ታቦትንና ለአምልኮ ሥርዐቱ ማከናወኛ የሚያገለግሉ ልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳትን እንዲሠሩ በሙሴ በኩል ታዘው ነበር፡፡ ከቃል 3p-03ኪዳኗ ታቦት ውስጥም በእግዚአብሔር ጣት ዐሥርቱ ትእዛዛት የተጻፉበት የሕጉ ጽላት፣ አርባ ዓመት ሙሉ እስራኤላውያን በሲና ምድረ በዳ የተመገቡትን መና የያዘች መሶበ-ወርቅ፣ አሮን ለክህነት አገልግሎት ስለመመረጡ ምስክር የሆነችው ለምልማና ፍሬ አፍርታ የተገኘችው የአሮን በትር ይገኙባታል፡፡(ዕብ.9፡4)

ታቦተ ጽዮን በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትመሰላለች፡፡ ይህን ለመረዳት ግን ስለ ታቦተ ጽዮን አሠራርና መንፈሳዊ ትርጉም አስቀድመን ልንረዳ ይገባናል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ታቦተ ጽዮንን እንዲሠራ ብልሃትን፣ ጥበብን፣ ማስተዋልን፣ ዕውቀትን ይለይ ዘንድ መንፈሱን ያሳደረበትን ከይሁዳ ወገን የሆነውን ባስልኤልን መረጠ ፡፡(ዘፀ.25፡9) እርሱም እግዚአብሔር በሰጠው ማስተዋል ከማይነቅዝ እንጨት ርዝመቷ ሁለት ክንድ ተኩል፤ ወርዱዋም አንድ ክንድ ተኩል፣ ቁመቷም አንድ ክንድ ተኩል እንዲኖራት አድርጎ ታቦቷን ሠራት፡፡ በመቀጠል በውስጥም በውጪም በጥሩ ወርቅ ለበጣት፣ ከታቦቷም ዙሪያ የወርቅ አክሊልን አደረገላት፡፡ ካህናት ታቦተ ጽዮንን ለመሸከም እንዲረዳቸውም በአራቱም መዓዘናት በወርቅ የተሠሩ ቀለበቶችንና በእነርሱም ውስጥ የሚገቡ ሁለት መሎጊያዎችን ሠራ፡፡ ከጥሩ ወርቅም የስርየት መክደኛውን በቃል ኪዳን ታቦቷ ላይ በርዝመቷና በወርደዋ ልክ ሠራ፡፡ የስርየት መክደኛውን እንዲጋርዱት አድርጎም ጥሩ ከሆነ ከተቀጠቀጠ ወርቅ ኪሩቤልን ሠራ፤ በስርየት መክደኛው ግራና ቀኝም አደረጋቸው፡፡ እነዚህ በጥሩ ወርቅ የተሠሩት ሁለቱ ኪሩቤል ፊታቸው ወደ ስርየት መክደኛው ሆኖ እርስ በእርሳቸው የሚተያዩ ተደርገው የተሠሩ ናቸው ፡፡ በዚህ በስርየት መክደኛው በሁለቱ ኪሩቤል መካከል  እግዚአብሔር ለሙሴ በመገለጥ ሰው ከባልንጀራው እንደሚነጋገር ያነጋግረው ነበር፤ ለሕዝቡ በደመና አምድ ይታያቸው ነበር፡፡(ዘፀ.25፡22፤33፡8-11)

 

ወደ ትርጓሜው ስንመጣ ታቦተ ጽዮን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ስትሆን፣ በውስጡዋ የያዘችው የሕጉ ጽላት የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ ታቦቷ ከማይነቅዝ እንጨት መሠራቷ የጌታን እናት ንጽሕናን የሚያመለክት ሲሆን በውጪም በውስጧም በጥሩ ወርቅ መለበጡዋ የቅድስናዋና ድንግል በሕሊና ወድንግል በሥጋ መሆኗን የሚያስረዳን ነው፡፡ ታቦቷን አራት  ሌዋውያን ካህናት ይሸከሟት ዘንድ በግራና በቀን በተዘጋጁ አራት ከወርቅ የተሠሩ ቀለበቶች ሲኖሩአት፤ በነዚያ የወርቅ ቀለበቶች ውስጥmariam[1] ሁለት መሎጊያዎች ይገቡባቸዋል፡፡ ታቦተ ጽዮንን ለማንቀሳቀስ ሲፈለግ አራት ካህናት በመሎጊያዎቹ ይሸከሟታል፡፡ይህ ሥርዐት በሰማያትም የሚታይ እውነታ ነው፡፡ የጌታን መንበር ገጸ ንሥር፣  ገጸ ሰብእ፣ ገጸ ላህም፣ ገጸ አንበሳ ያላቸው አርባዕቱ እንስሳት ይሸከሙታል፡፡(ኢሳ.6፡1-5፤ ሕዝ.1፡1-16) እንዲሁም ለአማናዊቷ ታቦት ቅድስት ድንግል ማርያም “የምስራች የሚናገሩ፣ ሰላምንም የሚያወሩ፣ የመልካምንም ወሬ፣ መድኃኒትንም የሚያወሩ፣ ጽዮንንም አምላክሽ ነግሦአል የሚሉ እግሮቻቸው በተራሮች ላይ  እጅግ ያማሩ ናቸው” የተባለላቸው የእርሱዋንና የጌታችን ስም ተሸክመው የሚሰብኩ ወንጌላውያን አሏት፡፡(ኢሳ.52፡7)የስርየት መክደኛው ታቹ መቀመጫው ንጹሐን አንስት ላዩ መክደኛው የንጹሐን አበው ግራና ቀኙ የወላጆቹዋ የሐናና የኢያቄም ምሳሌ ነው፡፡  እርሱን በክንፎቻቸው የጋረዱት  ኪሩቤል  የጠባቂ መልአክ ቅዱስ ሚካኤልና የአብሣሪው መልአክ ቅዱስ ገብርኤል ምሳሌዎች ናቸው፡፡

የስርየት መክደኛው ስርየቱ የሚፈጸምበት ስፍራ ነው፡፡ ነገር ግን እውነታውን ስንመለከት በዚህ ቦታ ምንም ዓይነት መሥዋዕት ሲቀርብ እንዳልነበር እንረዳለን፡፡ ይህም በጊዜው አማናዊው መሥዋዕት ገና እንዳልተሠዋ ያስገነዝበናል፡፡ ይህ ስፍራ እግዚአብሔር ለሙሴ የሚገለጥበት ቦታ ነው፤ ከእርሱ ውጪ ሌላ ነገር በእዚያ ላይ ማረፍ የለበትም፡፡ ይህ በራሱ የሚሰጠን አንድ ማስተዋል አለ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለአዳም የገባውን ቃል ኪዳን ሊፈጽም ሰው በሆነ ጊዜ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ የሚያቀርብበት ልዩ ስፍራ እንዳለ ያመላክተናል፡፡ ስለዚህም ይህ ስፍራ ለዚህ እንደተጠበቀ ወይም በዚህ ምሳሌ አማናዊ መሥዋዕት የሚቀርብበት ሥፍራ እንደሚያስፈልግ የሚያሳስብ ነው፡፡  ይህ እንደሆነ ለማመልከት ሲባል ለኃጢአት የቀረበው መሥዋዕት ከታረደ በኋላ ካህኑ ደሙን በጣቱ በመንከር ሰባት ጊዜ በስርየት መክደኛው አንጻር በመገናኛ ድንኳን ውስጥ ይረጨው ነበር፡፡(ዘሌዋ.4፡6) ነገር ግን ይህ ደም ከዚያ ስርየት መክደኛው ላይ አያርፍም ነበር ምክንያቱም በዚህ ስፍራ መቅረብ ያለበት መሥዋዕት መለኮት የተዋሐደው ነፍስ ግን የተለየው የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ክቡር ሥጋውና ቅዱስ ደሙ ነውና፡፡

ይህ የስርየት መክደኛ ሌላም ለእኛ የሚያስተላለፈው መልእክት አለው፡፡ መልእክቱም አማናዊው መሥዋዕት መቅረቡ እንደማይቀርና፣ መሥዋዕቱ የሚቀርብበት ስፍራ በቅድስተ ቅዱሳን ውስጥ ሆኖ እግዚአብሔር በምህረት በሚገለጥበት በጸጋ ዙፋኑ በጽላቱ  ላይ መሆን እንዳለበት  ነው፡፡(ዕብ.4፡16) በዚህም እግዚአብሔር አምላክ በነቢዩ ሚልክያስ “ከፀሐይ መውጫ ጀምሮ እስከ መግቢያዋ ድረስ ስሜ በአሕዛብ ዘንድ ታላቅ ይሆናልና በየስፍራውም ስለስሜ ዕጣንን ያጥናሉ ንጹሕም ቁርባን ያቀርባሉ”(ሚል.1፡11) እንዳለው  የስርየት መክደኛው  በዓለም ዙሪያ ላለችው አንዲት ቅድስት ቤተክርስቲያን ምሥጢረ ቁርባንን ለምትፈጽምበት ጽላት ወይም ታቦት ምሳሌ መሆኑን ያሳየናል፡፡ በሐዲስ ኪዳን ጽላቱ(ታቦቱ) የሚያርፍበት ስፍራ መንበር ተብሎ ሲጠራ የእግዚአብሔር ስም የተጻፈበትና ቅዱስ ሥጋው ክቡር ደሙ የሚፈተትበት ደግሞ ጽላት ወይም ታቦት ወይም መሠዊያ ተብሎ ይጠራል፡፡

የስርየት መክደኛው በታቦቱ አናት ላይ መሆኑም ቅዱስ ኤፍሬም “ የእኛን ሥጋ ለነሣኸውና ፣ መልሰህ ለእኛ ለሰጠኸን ፣ ለአንተ ክብር ምስጋና ይሁን ፡፡ ከእኛ በሆነው ሥጋህ በኩል እጅግ የበዛውን የአንተን ስጦታ ተቀበልን፡፡” ብሎ እንዳመሰገነ፤ እግዚአብሔር ቃል ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ራሱን መሥዋዕት አድርጎ ማቅረቡን ያሳየናል፡፡ የስርየት መክደኛውን የሚጋርዱት በጥሩ ወርቅ የተሠሩት የኪሩቤል ምስሎችም አማናዊው መሥዋዕት በሚሠዋበት ጊዜ በዙሪያው ረበው የሚገኙ የመላእክት ምሳሌዎች ናቸው፡፡  ይህን ለማስገንዘብ ቅድስት ቤተክርስቲያናችን በመንበረ ታቦቱ ላይ ምስለ ፍቁር ወልዳ እንዲቀመጥ ታዝዛለች፡፡ ምስለ ፍቁር ወልዳን  ላስተዋለ ሰው በትክክል የታቦተ ጽዮንን መንፈሳዊ ትርጉምን ይረዳል፡፡

ይህን ድንቅ የሆነ መንፈሳዊ ትርጉምን ይበልጥ ለመረዳት አንድ ምሳሌ የሚሆነንን እውነታ እንመልከት፡፡ ንጉሥ ዳዊት የእግዚአብሔርን የቃል ኪዳኑ ታቦት ከአቢዳር ቤት ወደ ጽዮን ከተማ ባስመጣበት ጊዜ በታቦተ ጽዮን ፊት ለእግዚአብሔር በሙሉ ኃይሉ በደስታ እየዘለለ መንፈሳዊ መዝሙርን አቅርቦ ነበር ፡፡(2ሳሙ.6፡12-17) ይህን ዓይነት ተመሳሳይ ድርጊት በሐዲስ ኪዳንም ተፈጽሞል ፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቅድስት ኤልሳቤጥን በተሳለመቻት ጊዜ የስድስት ወር ፅንስ የነበረው ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ የጌታችንን እናት የሰላምታ ድምፅ በሰማ ጊዜ እንደ አባቱ እንደ ዳዊት ከእናቱ ማኅፀን ውስጥ ሳለ በደስታ ዘሎአል(ሰግዶአል)፡፡ (ሉቃ.1፡44) ቅዱስ ዳዊት በታቦተ ጽዮን ፊት እንዲያ ደስ መሰኘቱና ለአምላኩ የምስጋና ቅኔን መቀኘቱ ለሰው ልጆች ሁሉ የመዳናቸው ምክንያት የሆነችውን ቅድስት ድንግል ማርያምንና ልጁዋን ኢየሱስ ክርስቶስን በታቦተ ጽዮን በኩል በማየቱ ነበር፡፡

ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን አባቶችም ይህንን እውነታ ይጋሩታል ፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ኤፍሬም፡- “ከአዳም ጎን በተገኘችው አንዲት አጥንት ምክንያት ሰይጣን ከአዳም ማስተዋልን አራቀ፡፡ ነገር ግን ከእርሱ አብራክ በተገኘችው በቅድስት ድንግል ማርያም ምክንያት በእርሱ ላይ ሠልጥኖ የነበረው ሰይጣን እንደ ዳጎን ተሰባብሮ ወደቀ፡፡ ታቦተ ጽዮን በተባለችው በቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን ውስጥ ባደረው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የድል አዋጅ ታወጀ ፡፡ በቃል ኪዳኑዋ ታቦት ሥር ዳጎን ተሰባብሮ እንደተገኘ እንዲሁ ክፉው ሰይጣን በታመኑበት ፊት ድል ተነሳ፡፡ እግዚአብሔር በቃል ኪዳኗ ታቦት ኃይሉን በመግለጥ ዳጎንን ሰባብሮ እንደጣለው እንዲሁ እግዚአብሔር ቃል ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ በመወለድ በኃጢአት ምክንያት በእኛ ላይ ሠልጥኖ የነበረውን ሰይጣንን ድል ነሳው፡፡” (1ሳሙ.5፤6) ሲል ቅዱስ ጀሮም ደግሞ “ቅድስት ድንግል ማርያም ቅድስትና ንጽሕት ነበረች፡፡ በቃል ኪዳኗ ታቦት ውስጥ የሕጉ ጽላት ብቻ እንደነበር እንዲሁ እርሷም በሕሊናዋ ከእግዚአብሔር ሕግጋት ውጪ ሌላ ምንም ሃሳብ አልነበራትም፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያም በውስጥም በውጪም ነውር የሌለባት ንጽሕት ናት፡፡ እንደ ቃል ኪዳኗ ታቦት በውጪም በውስጥም በቅድስና የተጌጠችና ሕጉንም ጠብቃ የተገኘች የክርስቶስ ሙሽራ ናት ፡፡ በቃል ኪዳን ታቦቱ ውስጥ ከሕጉ ፅላት ውጪ ሌላ ምንም ነገር እንደሌለ እንዲሁ አንቺም ቅድስት ሆይ በሕሊናሽ ምንም ነውር የሌለብሽ ቅድስት ነሽ፡፡” ብሎ ሲያመሰግናት፤ የእስክንድርያው ዲዮናስዮስ ደግሞ “ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ካህን ይሆን ዘንድ በሰው እንዳልተመረጠ እንዲሁ ቅድስት ድንግል ማርያም የጌታ ማደሪያ ትሆን ዘንድ በእግዚአብሔር የተመረጠችና በመንፈስ ቅዱስ ለእርሱ ማደሪያነት የተዘጋጀች ናት፡፡ የመለኮት ማደሪያ ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር የከተመባት ከተማ ሆና ትኖር ዘንድ ለዘለዓለም በእግዚአብሔር ታትማለች” በማለት ስለእርሱዋ ይመሰክራል፡፡

አዳም ድኅነቱ ከሴት ወገን በሆነች በቅድስት ድንግል ማርያም በኩል እንደሆነ ተረድቶ  ለሚስቱ “ሔዋን” ብሎ ስም እንደሰጣት እንዲሁ ንጉሥ ዳዊት በቅድስት ድንግል ማርያም በኩል እንደሚድን በመረዳቱ አምባዬና መጠጊያዬ ነሽ ሲላት “ጽዮን” ብሎ ለድንግል ስያሜን እንደሰጣት በመዝሙራቱ ማስተዋል እንችላለን፡፡ጽዮን የንጉሥ ዳዊት ተራራማዋ ከተማ ስትሆን፣ የስሟ ትርጓሜ አምባ፣ መጠጊያ ማለት ነው፡፡ ይህን ይዘው ብዙዎች ነቢያት ስለድንግል ሲናገሩ ጽዮን የሚለውን ስም ተጠቅመዋል፡፡

ነቢያት ስለቅድስት ድንግል ማርያም ሲናገሩ ጽዮን የሚለውን ስም እንደሚጠቀሙ ወደ ብሉይ ኪዳን ሳንገባ በሐዲስ ኪዳን ብቻ ስለ ጽዮን የተጻፉትን በማንሣት ማረጋገጥ እንችላለን፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ ኢሳይያስ ከአይሁድ ወገን የሆኑ የራሳቸውን ሥርዐትና ሕግ ለማቆም ሲሉ በክርስቶስ ከማመን ስለተመለሱት ሲጽፍ፡- “እነሆ በጽዮን የእንቅፋት ድንጋይና የማሰናከያ አለት አኖራለሁ”(ኢሳ28፡16፣8፡14) አለ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን ስለክርስቶስ የተነገረ ነው በማለት በሮሜ 9፡33 ላይ ጠቅሶት እናገኛለን፡፡ስለዚህም ነቢዩ ኢሳይያስና ቅዱስ ጳውሎስ ጽዮን ያሏት ቅድስት ድንግል ማርያምን እንደሆነ በዚህ ኃይለ ቃል  መረዳት እንችላለን፡፡ የማሰናከያ አለት የተባለው ክርስቶስ እንደሆነም “እነሆ የብዙዎች ልብ ሐሳብ ይገለጥ ዘንድ ይህ ለእስራኤል ላሉት ለብዙዎች ለመውደቃቸውና ለመነሣታቸው ለሚቃወሙትም ምልክት ተሾሞአል፡፡”(ሉቃ.2፡34-35) ተብሎ ተጽፎአል፡፡ ስለዚህ የማሰናከያ አለት የተባለውን ክርስቶስን ፀንሳ የወለደችው ቅድስት ድንግል ማርያም ጽዮን መባሉዋን በእነዚህ ጥቅሶች ማረጋገጥ እንችላለን፡፡

ነቢዩ ዳዊትና ኢሳይያስ ጽዮን ከተሰኘች የሙሴ ፅላት ካህኑ በሚያቀርበው መሥዋዕት አማካኝነት አፋዊ ድኅነት እንደተደረገ፣ ከእመቤታችን ከተወለደው አማኑኤል አማናዊ ድኅነት እንዲፈጸምልን“መድኃኒት ከጽዮን ይወጣል ከያዕቆብም ኃጢአተኝነትን ያስወግዳል”(መዝ.13፡10፤ኢሳ.59፡20) በማለት ስለክርስቶስ ትንቢትን ተናግረዋል፡፡ ይህንንም ቅዱስ ጳውሎስ ለጌታችን ለመድኃኒታችን ሰጥቶ በሮሜ.11፡26 ላይ ተጠቅሞበታል፡፡ በዚህም ቦታ ጽዮን ያሏት  ቅድስት ድንግል ማርያምን መሆኑን ማስተዋል እንችላለን፡፡ ምክንያቱም እርሱ ከእርሱዋ እንጂ ከሌላ አልተወለደምና፡፡ ነገር ግን “መድኃኒት” የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለመሆኑ “መልአኩም እንዲህ አላቸው፡-እነሆ ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁ በዳዊት ከተማ መድኅኒት እርሱ ክርስቶስ ተወለደ” (ሉቃ.2፡10)በማለት ገልጾልናል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ኢየሱስ ማለት “መድኃኒት ማለት ነው (ማቴ.1፡21) የኢየሱስም እናት ደግሞ ቅድስት ድንግል ማርያም መሆኑዋን ማንም የማይክደው ሐቅ ነው፡፡ ስለዚህም ነቢያቱ “መድኃኒት ከጽዮን ይወጣል” ሲሉ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጽዮን ከተባለችው ከቅድስት ድንግል ማርያም ይወለዳል ማለታቸው እንደሆነ ግልጽ ነው፡፡

ምንም እንኳ ቅዱስ ዳዊትና ሌሎች ነቢያት ስለቅድስት ድንግል ማርያም ለመናገር ሲሉ ጽዮን የሚለውን ስም አብዝተው ይጠቀሙ እንጂ አልፎ አልፎ ግን ጽዮን በማለት ስለ ከተማዋ ተናግረው እናገኛለን፡፡ ለምሳሌ ሚክያስ “ስለዚህ በእናንተ ምክንያት ጽዮን ትታረሳለች”(ሚክ.3፡12)ይላል፡፡ ይህ በቀጥታ ስለጽዮን ከተማ የተነገረ ነው፡፡  ቅዱስ ጳውሎስ ስለጌታችን መናገር ሲፈልግ ስለእርሱ የሚናገሩትን ብቻ መርጦ እንደተጠቀመ እንመለከታለን፡፡ እኛም እንዲሁ ለቅድስት ድንግል ማርያም የተነገሩትን አስተውለን ልንለያቸው ይጠበቅብናል፡፡ ምክንያቱም አንዳንድ ስለቅድስት ድንግል ማርያም ያልተጻፉ ነገር ግን ጽዮን የሚለውን ስም ይዘው የሚገኙ የመጽሐፍ ቅዱስ ምንባባት አሉና፡፡  ቢሆንም ስለታቦተ ጽዮን የተጻፉ ገቢረ ተአምራት ሁሉ እግዚአብሔር ቃል ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወለዶ ለፈጸማቸው ታላላቅ የድኅነት ሥራዎች ምሳሌዎች ናቸው፡፡

በዚህም መሠረት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በብሉይ ኪዳን በታቦተ ጽዮን የተፈጸሙትን ገቢረ ተአምራት ለድንግል ማርያምና ለጌታችን ለመድኀኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በመስጠት ተርጉማ ለልጆቹዋ ታስተምራለች፡፡ በኅዳር 21 ቀንም በታቦተ ጽዮን የተፈጸሙት ታላላቅ ተአምራት የሚታሰቡበት ቀን ነው፡፡ በዚህ ቀን ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በታቦተ ጽዮን የተፈጸሙትን ታላላቅ ተአምራት እግዚአብሔር ቃል ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ በመወለድ ከፈጸማቸው ታላላቅ የድኅነት ሥራዎች ጋር በማነጻጸር በድኅነታችን ውስጥ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ድርሻ ምን እንደሆነ ትገልጻለች፡፡ ለምሳሌ ታቦተ ጽዮንን የተሸከሙ ካህናት እግራቸው የዮርዳኖስን ባሕር በመንካቱ ባሕሩ ለሁለት እንደተከፈለ እንዲሁ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ ተወልዶ ጥምቀትን በራሱ ጥምቀት በመመሥረት ከሰይጣን ባርነት ወደ እግዚአብሔር ልጅነት እንዳሸጋገረን እናወሳበታለን(ኢያ.3፤ ማቴ.3፡13-17) ፡፡ ፍልስጥዬማውያን ከእስራኤላውያን ጋር ውጊያ በገጠሙ ወቅት ታቦተ ጽዮንን ማርከዋት ዳጎን በሚባለው ቤተ ጣዖታቸው ውስጥ አኑረዋት ነበር፡፡ ነገር ግን ታቦቷ ዳጎኑን በፊቷ ሰባብራ እንደጣለችው እንዲሁ ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደው በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በእኛ ላይ ሠልጥኖ የነበረው ሰይጣን ድል መነሳቱን እናወሳበታለን፡፡ ((1ሳሙ.5፤6)

በዚህ መልክ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን መንጎቹዋን ስለቅድስት ድንግል ማርያምና ስለልጁዋ ስለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እንዲሁም በእርሱ ስለተሰጠን ሰማያዊ የአገልግሎት ሥርዐት፣ ስለታቦት ጥቅምና  አገልግሎት፤ ታቦተ ጽዮንንና ቅድስት ድንግል ማርያምን በማነጻጸር በሰፊው እንደምታስተምር መረዳት እንችላለን ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ረድኤትና በረከት ያሳትፈን፡፡ የእግዚአብሔር አብ ጸጋ የእግዚአብሔር ወልድ ቸርነት የእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ አንድነት በእኛ ላይ ለዘለዓለም ጸንቶ ይኑር አሜን!!                           

DSC00379

በስልጤና ሀድያ ጉራጌ ሀገረ ስብከት የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን በወረዳው ፓሊስ አባላት እንዲፈርስ መደረጉ ተገለጠ፡፡

ኅዳር 19/2004 ዓ.ም

በዲ/ን ኅሩይ ባዬ

•    ቤተ ክርስቲያኑ የፈረሰው እኩለ ሌሊት እንደሆነም ታውቋል፡፡
•    የስልጢ 2ኛ ከፍተኛ ደረጃ ተማሪዎች በቤተ ክርስቲያኑ መፍረስ እንዲተባበሩ እየተቀሰቀሱ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በስልጤና ሀድያ ሀገረ ስብከት በስልጤ የጋራሬ ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ኅዳር 15 ቀን 2004 ዓ.ም ዓርብ ለቅዳሜ አጥቢያ እኩለ ሌሊት ላይ በወረዳው የፓሊስ አባላት የመፍረስ አደጋ እንደተጣለበት ከክልሉ የደረሰን ማስረጃ አረጋገጠ፡፡

በስልጤ ዞን በስልጢ ወረዳ በቆቶ ባለሦ ቀበሌ በቆቶ መንደር በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም የይዞታ ቦታው በሰነድ እንዲረጋገጥ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ለደቡብ ብሔር ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት ለግብርና ገጠር ልማት ቢሮ ለተፈጥሮ ሀብትና የገጠር መሬት አስተዳደር ዘርፍ ባቀረበው ጥያቄ አግባብነት ያለው የመንግሥት የሥልጣን አካል በቀን 15/04/2003 ዓ.ም የይዞታ ማረጋገጫ ሰነዱን ለደብሩ ሰበካ ጉባኤ መስጠቱን መረጃዎች ያስረዳሉ፡፡

DSC00379

በተሰጠው የይዞታ ቦታ ተደጋጋሚ የሆነ ክስ ይቀርብ እንደነበር የሚገልጡት የወረዳው ምእመናን የተፈቀደው ቦታ ለጥምቀተ ባሕር በመሆን ማንኛውም የእምነት ተከታይ አምልኮውን ሊፈጽም እንደሚችል በተቃራኒ ወገን አቤቱታዎች መቅረባቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ሆኖም ከወረዳው ፍርድ ቤት እስከ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ድረስ ጉዳዩ በተደጋጋሚ ታይቶ የቤተ ክርስቲያኑ አገልግሎት በተፈቀደለት ቦታ መንፈሳዊ ሥራውን እንዲቀጥል በመዝገብ ቁጥር 05681 የተወሰነውን ውሳኔ በመጥቀስ የወረዳው ፍርድ ቤት በቀን 13/12/2003 ዓ.ም ከፍተኛ ፍርድ ቤቱ ደግሞ በቁጥር 16/507/23/205 በቀን 13/04/2003 ዓ.ም ባስተላለፈው ትእዛዝ አስታወቋል፡፡

የሕግ አግባብ ባለው መሥሪያ ቤት ተፈቅዶ መሠረቱ ተቀምጦ የተሠራው ቤተ ክርስቲያን ድንገት በመፍረሱ የተደናገጡት የስልጢ ምእመናን ጉዳዩን ለሚመለከተው የበላይ አካል ለማቅረብ ወደ ሐዋሳ አስተዳደር ጽ/ቤት በቀን 18/03/2004 ዓ.ም ጉዞአቸውን አቅንተዋል፡፡ በእለቱም የክልሉ የጸጥታና አስተዳደር ቢሮ የምእመናኑ አቤቱታ አግባብነት ያለው በመሆኑ አጣሪ ኃይል ወደ ቦታው እንደሚላክ ምላሽ እንደተሰጣቸው ተገልጧል፡፡

ኅዳር 19 ቀን 2004 ዓ.ም የደረሰን መረጃ እንደሚያመለክተው በስልጢ ከተማ ጥቂት አክራሪ ሙስሊሞች በሙስሊምና በክርስቲያኑ መካከል ግጭት እንዲፈጠር ቅስቀሳ እያደረጉ ነው፡፡ ከዚህም በተያያዘ በስልጢ ከተማ 1ኛ እና ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት የሚማሩ ተማሪዎች ቤተ ክርስቲያኑ እንዲፈርስ የሚደረገውን ተግባር እንዲፈጽሙ መቀስቀሳቸውንና ተማሪዎቹ ተሰባስበው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ በመሔድ ነዳጅ ጨምረው ቤተ ክርስቲያኑን ሙሉ በሙሉ ማቃጠላቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የስልጢ ምእመናን በሕግ ተፈቅዶ በተሰጣቸው ቦታ ቤተ ክርስቲያን ሠርተው መገልገል ሊጀምሩ በተዘጋጁበት ወቅት ሕጋዊ ነኝ በሚል የፖሊስ አካል በመንፈቀ ሌሊት እንዲፈርስ መደረጉና በሕገ ወጥ ወጣቶች እንዲቃጠል መደረጉ እንዳሳዘናቸው አብራርተዋል፡፡

ቀጣዩ ሒደት እንደደረሰን የምናሳውቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ

ከዲ/ን መስፍን ደበበ
እርሱ እናቴ እኔን ቅሪት እያማጠኝ፤
በልጅነት ሊገላገል በሐሳብ ያረገዘኝ፤
በማኅፀን ሰፋድሉ በትምህርቱ እኔን ስሎ፤
በመዶሻው እኔን ጠርቦ አስተካክሎ፤
እጄን ይዘህ አለማምደህ እንዲያ ስድህ፤
ቃለ ነገር ቃለ ምሥጢር እየጋትህ፤
ጠንካራውን ጥሬ ቃሉን አስቆርጥመህ፤
አንተ አብይ ባሕር የትምህርት ውቅያኖስ፤
ምርጥ ዕቃ ማዕዘን ዕብነ አድማስ፤
በእንቁላል ቅርፊት ቀድቼ የረካሁኝ ከአንደበትህ፤
ርዕሰ እውቀት አንተ አፈ ዝናም በትምህርትህ፡፡
አሕዛበ-ምድር ማንነቴን በጠብታህ ጎበኘሃት፤
የነፍሴን እርሻ አጥግበህ በልምላሜ ከደንካት፡፡
ሕሊናዬን በተመስጦ መንኮርኩር ስታከንፋት፤
ከታችኛው ከእንጡረጦስ ከበርባኖስ ስታጠልቃት፤
ዖፈ ጣጡስ መጥቀህ በረህ የነገርኸኝ፤
እንደ ሙሴ ከእግረ ታቦር ያላቆምኸኝ፤
አለማወቅ ጥቁር ካባ፤ የጨለማን መጋረጃን ያራቅህልኝ፤
ኢትትሃየድ እያለ ወራሴን ስታለምደኝ፤
ምሥጢሩን ስትቀዳ ዘቦቱን ስትነግረኝ፤
የሰብዕና ዘበኛዬ እኔን በትምህርቱ ንቅሳት ሲነትበኝ፤
ያኔ ነበር የነቀሰኝ በልቡናዬ ሕያው ቃሉን የከተበኝ፤
በጉልጓሎ በእርሻው ቦታ የጠመደኝ፤
እያረሰ ጅራፍ ቃሉን ጆሮዬ ላይ ሲያጮህብኝ፤
ከሃያው ክንድ ከመቅደሱ ከሚፈልቀው፤
ከዙፋኑ ከቃል ሥግው ከሚፈሰው፤
እንደ መስኖ ሊቀላቀል ከሚወርደው፤
ከእኔ ሕይወት ከሸለቆ ከአዘቅቱ ሲንዶሎዶል፤
የመብል ዛፍ ፍሬ በኩር ሲያበቅል፤
ያኔ ነበር ስሜ ሽቶ ከጌታ ስም ሲቀላቀል፤
ሃይማኖት የፍቅር እሳት ሲንቀለቀል፤
ተቆጠርኩኝ ግብር ገባሁ ከቤተ ወንጌል፡፡
kidus estifanos

ቅዱስ እሰጢፋኖስ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስተምህሮ

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ዳር 17/2004 ዓ.ም

ስለ ቅዱስ እስጢፋኖስ  ክፍል አንድ ለማንበብ እዚህ ይጫኑ

 

አይሁድን ቀርቦ ለመረመራቸውም አሕዛብ ከሆኑት ከፋርስ ወገን እንደሆኑ እንዲሁም አንድ ሰው ከእግዚአብሔር ተአምራትን ሳይሻ ለእግዚአብሔር መከራዎቹን ሁሉ ታግሦና ተቋቁሞ የተመላለሰው እንደሆነ እግዚአብሔር ልጁ እንደሚያደርገው፣ እንዲሁም የሁሉ አባት አብርሃም እንዳደረገው የአባቶችን መቃብርና ያለንን ሁሉ በመተው ልንታዘዝ እንደሚገባንም ጠቁሞናል ፡፡

kidus estifanos

የአብርሃም አባትና ዘመዶቹ ምንም እንኳ ረጅም ጉዞ ከአብርሃም ጋር ቢጉዋዙም ከንዓንን ይወርሱ ዘንድ የተገባቸው ካልሆኑ ልጆቹስ ላይ እንዴት ይህ እጣ ፈንታ አይደርስባቸው ይሆን? “ነገር ግን ልጅ ሳይኖረው ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ ርስት አድርጎ ይሰጠው ዘንድ ተስፋ ሰጠው፡፡” አለ፡፡ በዚህ የእግዚአብሔርን ድንቅ ስጦታንና የአብርሃምን እምነት ታላቅነት እንመለከታለን፡፡ “ልጅ ሳይኖረው” የሚለው አገላለጽ የእርሱን በእምነት መታዘዝን የሚገልጥ ነው፡፡ “ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ ርስት አድርጎ ይሰጠው ዘንድ”የሚለው በድርጊት ከታየው ጋር ስናነጻጽር የተቃረነ መስሎ ይታየናል፡፡ ምክንያቱም አስቀድሞ “በዚችም የእግር ጫማ ስንኳ የሚያህል ርስት አልሰጠውም” እንዲሁም ልጅም አልነበረውም ይለናልና፡፡ እነዚህ ዐረፍተ ነገሮች አብርሃም በእምነቱ ከተሰጠው ጋር የሚጣጣሙ ላይመስሉን ይችላሉ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ሊሰጥ ያሰበውን ያንኑ ነው የሚሰጠው፡፡ በዚህ ቦታ ግን ቃሉና ድርጊቱ የተቃረኑ ይመስሉናል፡፡ ነገር ግን እንደ እኛ አስተምህሮ ፈጽሞ የሚጣረሱ አይደሉም፡፡ እንደውም ፈጽመው የሚጣጣሙ እንጂ፡፡ እግዚአብሔር አምላክ በዚህ እንደምንደክም ነገር ግን እረፍታችን በላይ በሰማይ እንደሆነ አስተምሮናል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ እስጢፋኖስ እንዲህ አለ፡፡

 

“ስለምን የተስፋው ቃል እንደተፈጸመ እናስባለን ? ስለምን ነገሮችን እናምታታቸዋለን? በዚህም ምድር መከራን ተቀበላችሁን? በድህነት ለመኖር ተገደዳችሁን? አዘናችሁን? በዚህ አትጨነቁ፡፡ ስለ ክርስቶስ ስትሉ በዚህ ምድር የምትቀበሉት መከራ በሚመጣው ዓለም ዕረፍት ያሰጣችኋል፡፡ የዚህ ምድር መከራችሁ ለዘለዓለማዊ ዕረፍታችሁ ምክንያት ነው፡፡ “ይህ ሕመም” ይልና “የእግዚአብሔር ልጅ በእርሱ ይከብር ዘንድ ስለእግዚአብሔር ክብር ነው ለሞት አይደለም”ይለናልና (ዮሐ.11፡ 4) በሚመጣው ዓለም የምንቀበል ከሆነ ፍርዱ ነው፤ ነገር ግን በዚህ ምድር የምንቀበለው መከራ የምንማርበትና የምንታረምበት መከራ ነው፡፡ ፍልሚያው በዚህ ምድር ነው ኃጢአትን ደምን እስከማፍሰስ ደርሶ መዋጋት የእኛ ድርሻ ነው፡፡ ጦርነቱ በዚህ በምድር እንጂ በሰማያት አይደለም፡፡ በውጊያ ላያ ያለ ወታደር ዕረፍትን ሊሻት አይገባም፡፡ በውጊያ ሰፈር እንደንጉሥ የቅምጥልንነት ሕይወትን ሊኖር አይገባውም፣ ሀብትን ለመሰብሰብ ወይም ስለቤተሰቡ በማሰብ ሊጨነቅ አይገባውም፡፡ አንድ ወታደር ውጊያው ላይ ብቻ ሊያተኩር ይገባዋል፡፡ እርሱም በጠላቴ ላይ እንዴት ድልን ልቀዳጅ እችላለሁ የሚለው ነው፡፡ በዚህ ምድር ስንኖር ስንቃችን ይህ ይሁን፡፡ እንዲህ ከሆነ በጠላት ተሸንፈን ከሆነ ተመልሰን ድል እንነሣዋለን፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ሁሉን የጦር ትጥቆች አስታጥቆናል፡፡ ጠላታችንን ዲያብሎስ እንዴት ድል መንሣት እንችላለን የሚለው ብቻ የእኛ ግብ ይሁን፡፡ እንዲህ የምናስብ ከሆነ ልምምዳችንም ይህ ይሆናል፡፡ የእግዚአብሔር ጸጋም ይህን እንድናከናውን የድርሻውን ይወጣል፡፡ ስለዚህም እንዴት የሚረዳንንም የእግዚአብሔር ጸጋ ማቅረብ እንደምንችል እንወቅበት፡፡ እንዲህ ከሆነ “እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ከሆነ ማን ይቃወመናል” (ሮሜ.8፡31) አንድ ነገር ብቻ የእኛ ልምምድ ይሁን እርሱም እግዚአብሔር አምላክ የእኛ ጠላት በመሆን ፊቱን ከእኛ እንዳይመልስ ነው፡፡


መከራን በመቀበላችን ክፉ ደረሰብን ብለን አንመረር፤ ነገር ግን ኃጠአትን በፈጸምን ወቅት መከራ እንደመጣብን እንቁጠር፡፡ ይህ ነው መራሩ መከራ፡፡ እኛ ግን በዚህም ምድር ኑሮአችንን በቅንጦት እያሳለፍን የሚመጣውን ዓለም ሕይወት ለመስበክ አንሻም፡፡ እንዳውም በሚመጣው ዓለም የምንኖረው እንዲህ ዓይነት ሕይወት እንደሆነ እናስተምራለን፡፡ ሕሊናችን እንዴት በኃጢአት እንደተጨማለቀ እስቲ ቆም ብለን እናስብ ፡፡ ይህ ከሌሎች ቅጣቶች ይልቅ አጅግ ከባዱ ቅጣት አይደለምን?

 

በኃጢአት ሕይወት ለሚመላለሱ ወገኖች ምንም እንኳ የራሳቸውን ኃጢአት የማያስተውሉ፣ ስለጽድቅ መከራን ለመቀበል ለሚሰቀቁ ነገር ግን በፍርሃትና በመንቀጥቀጥ ለሚኖሩ … አንድ ጥያቄ ላንሣ፡፡ በወዲያኛው ዓለም ዕረፍትን ማግኘት ትፈልጋላችሁን? በዚህ ምድር ስለክርስቶስ ስትሉ መከራን ተቀበሉ፡፡ ይህን የመሰለ ዕረፍት ፈጽሞ አታገኙም፡፡ ሐዋርያት ስለክርስቶስ ሲሉ በተቀበሉት መከራ ደስተኞች ነበሩ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ “በጌታ ደስ ይበላችሁ” (ፈልጵ.4፡4) አለ፡፡ እየታሰሩ እየተገረፉ በሸንጎ ፊት እየቀረቡ እንዴት ነው ደስ ሊላቸው የቻለው? ሁሉም ደስተኞች ነበሩ ይላልና፡፡ እንዴት እንዲህ ደስ ሊላቸው ቻለ ብለህ ጠይቅ፡፡ እንዴት ደስ ላይላቸው ይችላል፡፡ ሕሊናቸው እኮ ከኃጠአት ንጹሕ ነው፡፡ ስለዚህ እጅግ ልዩ በሆነ ደስታ ውስጥ ይዋኛሉ፡፡ መከራቸው በበዛ ቁጥር እንዲሁ ደስታቸውም ከመከራቸው እጥፍ ይጨምርላቸው ነበር፡፡

 

አንድ ወታደር በጦር ሜዳ ደጋግሞ ቢቆስልና ወደቤቱ በድል አድራጊነት ቢመለስ ደስታው ታላቅ አይሆንምን? በጦር ሜዳ ስለመዋሉ ቁስሉ በግልጥ አይናገርምን? ለትምክህቱስ ምስክር አይሆኑለትምን? አንተም ልክ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ በደስታ “እኔ የኢየሱስን ማኅተም በሥጋዬ ተሸክሜአለሁ”(ገላ.6፡17) ለማለት የበቃህ እንድትሆን ዘንድ ስለክርስቶስ መከራን ለመቀበል አትሰቀቅ እንዲህ ያደረግህ ከሆነ ደስታህ እጅግ ታላቅ በክብር ያጌጠ ይሆናል፤ በአምላክም ዘንድ የታወቅህ ትሆናለህ፡፡

 

ለክብር የማያበቃህ መከራ የለም ስለዚህም አንድ ሰው በአንተ ላይ በጠላትነት ቢነሣብህ ክርስቶስን አስበህ ክፉ ቃል እንዳትናገር ፍራ፤ እናም የትዕቢትን አገዛዝ በጽናት ተቋቋመው፤ ቁጣንና ሴሰኝነትንም በጽናት ተቃወማቸው፡፡ እነዚህ ለአንተ እንደ ማኅተም ናቸው፡፡ እነዚህ ለአንተ እንደግርፋት ናቸው፡፡ አንድ ነገር ልጠይቃችሁ የትኛውን ነው የከፋው ግርፋት የምትሉት? ነፍስ በገሃነም እሳት የምትገረፉትን መገረፍ አይደለምን? በዚህ ምድር መከራ ብንቀበል በሥጋችን ነው፡፡ ነገር ግን በሚመጣው ነፍሳችንም ሥጋችንም ነው መከራ የሚቀበሉት፡፡

 

ሁሉም ክፋቶች ከነፍስ ይመነጫሉ፡፡ አንድ ሰው ቢቆጣ ቢቀና እኒህን የሚመሰሉ ክፋቶችን ቢፈጽም በነፍሱ ላይ ስቃይን እያመጣ ነው፡፡ ምንም እንኳ እነዚህ ክፋቶች ወደ ድርጊት የተመለሱ ባይሆኑም መቆጣትና ቅናት አንዲሁም እነዚህን የመሰሉ ሁሉ ኃጢአቶች ናቸው፡፡ በእርግጥም ቁጣና ቅናት ነፍስን የሚያቆስሉና የሚጎዱ መከራዎችም ናቸው፡፡ ስለዚህም ተቆጥተህ እንደሆነ በመከራው ውስጥ ራስህን እንደጣልህ ቁጠር፡፡ እንዲህ ከሆነ የማይቆጣ ሰው ራሱን መከራ ውስጥ አልጣለም ማለት ነው፡፡

 

የተሰደበ ሰው መከራን በነፍሱ እየተቀበለ ነው ብለህ ታስባለህን ? አይደለም ነገር ግን ከላይ እንዳስተማርኩት ተሳዳቢው በነፍሱ መከራን እየተቀበለ ነው፡፡ ስለዚህም እነዚህ ነገሮችን መፈጸም አንድ ሰውን ኃጠአተኛ የሚሰኙት ከሆነ መከራ አለበት ማለት ነው፡፡ ስለዚህም መከራ እየተቀበለ ያለው ተሰዳቢው ሳይሆን ተሳዳቢው መሆኑን መረዳት ይቻለናል፡፡

 

አንተ “እርሱን ልጄን ሞኝ ብሎ ተሳድቦአል” ልትል ትችላለህ፤ ነገር ግን አንተ ለስድቡ አጸፌታውን በመመለስ በበደል እርሱን አትምሰለው፡፡ አንድ ነገር እጠይቅሃለሁ ይህ ሰው መልካም ነገር አደረገን? አንተ እርሱ መልካም አድርጎአል አትልም፤ ስለዚህም እርሱ የፈጸመው መልካም ካልሆነ አንተ እርሱ የፈጸመውን ከማድረግ በመከልከል መልካምን አድርግ፡፡ ልጅህ በመሰደቡ ምን ያህል ቁጣ በውስጥህ እንደሚቀጣጠል እረዳለሁ፡፡ ነገር ግን አንተ “ እርሱ ልጄን የሰደበ ከሆነ እንዴት ነው ይህን ሰው እኔንም ከመሳደብ የሚመለሰው? ብለህ ትጠይቅ ይሆናል፡፡ እንዲህ ያደረገውን ሰው በትሕትና ገሥጸው፣ ምከረው ብዬ እመክርሃለሁ፡፡ ትሕትና ቁጣ አንዱ ካንዱ የሚቃረኑ ጠባያት ነው፡፡ በትሕትና ቁጣን ማብረድ ይቻልሃል፡፡

 

በእኛ ላይ ክፉ ስለተፈጸመብን በምላሹ እኛም ክፉን ልንፈጽም አይገባንም ነገር ግን ስለሌሎች መዳን ስንል መልካምን ልናደርግ ይገባናል፡፡ ልጅህ በመሰደቡ ምክንያት ራስህም እንደተሰደብክ አድርገህ አትቁጠር፡፡ በእርሱ ምክንያት አንተ ልትቆጣ ትችላለህ፡፡ ነገር ግን ላትሳደብም ትችላለህ፡፡ ልጅህ በመሰደቡ ምክንያት የአንተም ክብር እንደተነካ ልትቆጥር ትችላለህ፡፡ ነገር ግን ነገሩን ስናስተውለው ልጅህ የሰደበው እንጂ የሚጎዳው ልጅ ወይም አንተ አትጎዱም ክብርህም አይዋረድም፡፡

 

ስለዚህም እንደ ሰይፍ የሰላውን የቁጣ ሰይፍህን ከሰገባው ውስጥ መልሰው፡፡ ነገር ግን የቁጣ ሰይፋችንን ብንመዝና ያለጊዜዋ ብንጠቀምባት በእርሱ ተይዘን እኛም እንጠፋለን፡፡ ነገር ግን ቁጣችንን በውስጣችን ይዘን ትዕግሥትን የተላበስን ከሆነ ግን ቁጣው ይከስምልናል፡፡ ክርስቶስ በእርሱ ምክንያት ወደ ቁጣ እንዳንገባ አሳስቦናል፡፡ ጌታችን ለቅዱስ ጴጥሮስ ምን እንዳለው ስማ “ሰይፍ የሚያነሣ ሁሉ በሰይፍ ይጠፋልና ሰይፍህን ወደ ስፍራው መልስ፡፡”(ማቴ.26፡52) አለ፡፡ አንተ ስለልጅህ መነቀፍ ትቆጣለህን? ስለዚህም ልጅህን ምክንያታዊ እንዲሆን አስተምረው፡፡ ስለእርሱ የደረሰብህን ሕማም ንገረው እንዲህ አድርገህ መምህር ክርስቶስን ምሰለው፡፡

 

እርሱ በደቀመዛሙርቱ ላይ መከራ ያጸኑባቸውን ወገኖች “እኔ እበቀላቸዋለሁ አላለም” ነገር ግን “በእኔ እንዳደረጉት በእናንተም ላይ ይፈጽማሉና በትዕግሥት ተቀበሉ፡፡ እናንተ ከእኔ አትበልጡምና” ነበር ያላቸው፡፡ አንተም ለልጅህ አንተ ከጌታችን አትበልጥም ብለህ ልትነግረው ይገባሃል፡፡

 

ይህ መንፈሳዊ ፍልስፍና የአሮጊቶች ተረት ሊመስለን ይችላል ፡፡ በቃል ሰዎችን ከጥፋት ከመመለስ ይልቅ በድርጊት ሰዎችን መመለስ እጅግ ታላቅ ጥበብ አይደለምን? አሁን አንተ በመሃል ቆመሃል፡፡ መከራ ከደረሰባቸው ወገን እንጂ መከራን ከሚያደርሱት ወገን አትሁን፡፡ መከራ ከሚደርስባቸው ወገን በተግባር ካልሆንክ እነርሱ ከሚያገኙት የድል አክሊል ውጪ ትሆናለህ፡፡

 

እግዚአብሔር አምላክህ ቃየንን ስለ ወንድሙ አቤል እንዴት ብሎ በትሕትና እንደጠየቀውና ቃየንም እግዚአብሔር አምላክህን እንዴት ብሎ በንቀት ቃል እንደተናገረው ተመልከት እርሱ “ወንድምህ አቤል ወዴት ነው” ሲለው ቃየን ደግሞ በምላሹ “አላውቅም እኔ የወንድሜ ጠባቂ ነኝን?” ብሎ ነበር የመለሰው፡፡ (ዘፍ.4፡9)ከዚህ መልስ በላይ እጅግ ጸያፍ የሆነ መልስ ምን አለ? ከእናንተስ መካከል እንዲህ ዓይነት ጸያፍ የሆነ መልስን ልጁ ቢመልስለት የሚታገሥ አባት ማን ነው? ከወንድሙስ ቢሰማ እርሱን እንደ ሰደበው አይቆጥርበትምን ? ጌታችን ግን እንዲሀ አላደረገም ነገር ግን በትሕትና ቃል መልሶ ”ምን አደረግህ? የወንድምህ የደሙ ድምፅ ከምድር ወደ እኔ ይጮኻል፡፡” ብሎ ጠየቀው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ከቁጣ በላይ ነው ልትል ትችላለህ፡፡ ትክክል ብለሃል ነገር ግን እንደ ችሎታህ መጠን በጸጋ አምላክ ትሆን ዘንድ ስለአንተ ሲል የእግዚአብሔር ልጅ ሰው ሆኖአል፡፡

 

ነገር ግን ከእናንተ መካከል አንዱ “እኔ ሰው ነኝ አንዴት አምላክ ልሆን እችላለሁ ?ብሎ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ ደህና! ምሳሌ የሚሆኑህን ሰዎች ልጥቀስልህ ስለ ጳውሎስ ወይም ስለ ጴጥሮስ የምናገር አድርገህ አታስብ፡፡ ከእነርሱ በእጅጉ ያነሰውን ሰው እንደምሳሌ አንሥቼ ላስረዳህ ካህኑ ኤሊ የሳሙኤልን እናት ሃናን “ስካርሽ እስከመቼ ነው? የወይን ጠጅሽን ከአንቺ አርቂው፡፡” (1ሳሙ.1፡14) ብሎአት ነበር፡፡ ከዚህ የከፋ የነቀፋ ቃል ምን አለ? ነገር ግን እርሱዋ ምን ብላ መለሰች “ጌታዬ ሆይ አይደለም፣ ጌታ ሆይ እኔ ልቡዋ ያዘነባት ሴት ነኝ” ብላ መለሰችለት በእርግጥ በእርሱዋ ላይ የተሰነዘረው የነቀፋ ቃል እርሱዋ ከምትጓጓለት ጋር የሚሰተካከል አልነበረም፡፡ እርሱዋ ለእውነተኛው መንፈሳዊ ፍልስፍና እናቱ ነበረች፡፡ እቺ ሴት ጣውንት ነበረቻት ነገር ግን እርሱዋን አንድም ቀን ተናግራት አታውቅም ነበር፡፡ ነገር ግን ወደ እግዚአብሔር ተጠጋች፡፡ በፀሎቱዋ ስሙዋን እያነሣች ስለስድቡዋ እግዚአብሔር ይቀጣላት ዘንድ አለመነችውም፡፡ እቺ ሴት አጅግ ድንቅ የሆነች ሴት ነበረች፡፡ እርሰዋን ተመልክተን ወገኖቻችንን በእግዚአብሔር ፊት የምንካሰስ እንፈር፡፡ እንደ ቅናት ብርቱ የሆነ ነገር እንደሌለም አንተ ታውቃለህ ነገር ግን እርሱዋ ቅናት ድል ነስቶአት በጣውንቷ ላይ በጠላትነት አልተነሣችም ነበር፡፡

 

ቀራጩ በፈሪሳዊው ሰው ሲንጓጠጥ እየሰማ እርሱም በምላሹ የስድብን ቃል አልተናገረውም፡፡ እንዲህ ማድረግ አቅቶት ግን አይደለም፡፡ ነገር ግን ልክ እንደ ጥበበኛ ሰው በምስጋና በመቀበል ስለራሱ ግን “አምላክ ሆይ እኔ ኃጢአተኛውን ማረኝ እያለ ደረቱን ይደቃ ነበር፡፡” ለመነ (ሉቃ.18፡13) ሜምፊቦስቴ ምንም ክስና ውንጀላ በባሪያው ቢቀርብበትም በባሪያው ላይ ምንም ክፉ ነገር ወይም ቃል ሊናገርው አልፈቀደም ነበር፡፡ በንጉሥ ዳዊት ፊት እንኳ ሊወቅሰው አልፈቀደም፡፡ (2ሳሙ.19፡26)

 

ድንቅ የሆነ ፍልስፍናን ስለተላበሰችው ስለዘማዊቱዋ ሴት ደግሞ ልንገርህን? ክርስቶስ እግሮቹን በእንባዋ አርሳ በጠጉሮቹዋ ስለአበሰችው ሴት ምን ብሎ አስተማረ “እውነት እላችኋለሁ ቀራጮችና ጋለሞቶች ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በመግባት ይቀድሙአቸዋል” (ማቴ.21፡31)ብሎ አላስተማረምን? እርሱዋ የቆመችበትን ቦታ፣ ጽናቱዋን እንዲሁም ኃጢአቱዋን እንዴት አጥባ እንዳስወገደች አታስተውልምን? በፈሪሳዊው ስምዖን እንዴት ተብላ ስትነቀፍ እንደነበር አስተውል፤ ስምዖን “ይህስ ነቢይ ቢሆን ይህች የምትዳስሰው ሴት ማን አንደሆነች እንዴትስ እንደነበረች ባወቀ ነበር፡፡”(ሉቃ.7፡39) ሲላት “ አንተስ ማነህና አንተ ከኃጢአት ንጹሕ ነህን ? ብላ መልስ አልሰጠችውም፡፡ ነገር ግን ራሱዋን በጌታዋ ፊት ይበልጥ አዋርዳ አብዝታ አለቀሰች ትኩስ የሆነው እንባዋንም በጌታዋ እግር ላይ እንዲፈስ ፈቀደች፡፡

 

ሴቶች፣ ቀራጮች፣ አመንዝሮች ጥምቀት ሳትሠራ በፊት እንኳ መንፈሳውያን ፈላስፎች ሆነው ከሆኑ፤ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋዎች የተሰጣችሁ እናንተ እርስ በእርሳችሁ ከአራዊት በከፋ መልኩ እርስ በእርሳችሁ በመፋጀታችሁ፣ አንዱ አንዱን በማሳዘኑና በመምታቱ እንዴት የባሰ ፍርድ አይጠብቃችሁ ይሆን? ከቁጣ በላይ የሚከፋ፣ የሚያዋርድ፣ የሚያስፈራ፣ የሚያሳዝን፣ የሚጎዳም ምንም የለም፡፡

 

ይህን በውጭ ላሉ ሰዎች የምናሳየው ብቻ አይደለም፤ ነገር ግን ሚስታችን ተናገሪ ከሆነች ለእርሱዋም ይህን ትዕግሥት ልናሳያት ይገባናል፡፡ ሚስትህ ለአንተ ቁጣን ከሰውነትህ የምታስወግድባት ትምህርት ቤትህ ትሁን፡፡ ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? ታጋሽ ሁን ሥጋን ብቻ ለሚጠቅም ነገር ታጋሾች ለመሆን ልምምዶችንና ጽኑ የሆኑ መከራዎችን የምንቀበል ስንሆን ነገር ግን ይህን ትዕግሥት በቤታችን የማንፈጸመው ከሆነ ማን ነው የድሉን አክሊል በራሳችን ላይ ሊደፋልን የሚችለው? ሚስትህ ትሰድብሃለችን? እርሱዋን መልሰህ በመሳደብ አንተው እርሱዋን አትምሰላት፡፡ ራስን ከክብር ማሳነሥ የነፍስ ደዌ ነው፡፡ ሚስት ስትሰድብህ አንተ እርሱዋን መልሰህ መሳደብ የተገባ እንዳልሆነ ልብ በል፡፡ በተቃራኒው አንተ እርሱዋን አየተሳደብኽ እርሱዋ የታገሰች ከሆነም ከዚህ የሚበልጥ ውርደት የለም፡፡ እናም እርሷ አንተን በመስደቡዋ የማይገባና የሚያዋርድ ነገርን በመናገርህ በራስህ ላይ የባስ ፍርድን ታመጣለህን፡፡ እርሷ ስትሳደብ ብትታገሣት ግን ያንተን ጽናት ታላቅነት ማረጋገጥ ትችላለህ፡፡ እንዲህ ስል ግን ሚስቶች ተሳዳቢዎች ይሁኑ ማለቴ ግን አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ይህን ማለትን ከእኔ ያርቅ፡፡ ነገር ግን በሰይጣን ግፊት ይህ ተፈጽሞ እንደሆነ እንዲህ አድርጉ ማለቴ ነው፡፡ የሚስትን ድክመት መሸከም የባል ድርሻ ነው፡፡

 

ሠራተኛህ ከአንተ ጋር ቢጋጭ በጥበብ ታገሠው፡፡ ለእርሱ ማድረግ የሚገባህን ወይም መናገር የሚገባህን አትናገር ማለቴ ግን አይደለም፡፡ ነገር ግን ከአንደበትህ በእርሱ ላይ የነቀፋ ቃል አይውጣ፡፡ ሴትን ልጅ የሚያዋርድ ንግግርን አትናገራት፡፡ አገልጋይ ሠራተኛህን በንቀት ቃል አትጥራው፡፡ እንዲህ ብታደርግ ግን እርሱን እያዋረድካት አይደለህም ራስህን እንጂ፡፡

 

ቁጡ ሰው ሆኖ ራስን ገዝቶ መኖር አይቻልም፡፡ ከተራራ ላይ ቁልቁል እየተምዘገዘገ እንደሚወርድ ውኃ ምንም የጠራ ቢሆን ተንደርድሮ አፈሩን ሲመታው ውኃው ደፍርሶ ከጭቃው ጋር ይቀየጥና የማይጠጣና ቆሻሻ ውኃ እንዲሆን የቁጡ ሰውም እጣ ፈንታ እንዲሁ ነው፡፡ ወዳጅህን በቁጣ ገንፍለህ ልትመታው ኮቱንም ልትቀድበት ትችላለህ፤ ነገር ግን የከፋውን ቅጣት የምትጠጣው አንተው ትሆናለህ፡፡ ያንተ ቡጢ በእርሱ ሥጋ ላይ፣ ቁጣህም በእርሱ ልብስ ላይ አርፎ ይሆናል፤ ነገር ግን በአንተ ነፍስ ላይ ቅጣቱ እንዲሁ ይሆንብሃል፡፡ ከሁለት የምትተረትራት የራስህን ነፍስ ነው፡፡ ስቃይህም በውስጥ ሰውነትህ ውስጥ ይሆናል፡፡

 

አንተ የሰረገላው መሪ ከወንበሩ ላይ ፈንግለህ ጥለኸዋል፡፡ ሰረገላህም ነፍስህን ከምድር ላይ ጥሎ እየጎተታት ነው፡፡ በቁጣ ሰረገላውን የሚመራ ሰው እጣ ፈንታው ነፍሱ ተዋርዳ በመሬት ላይ መጎተት ይሆናል፡፡ ልትገሥጽ ፡ ልትመክር ሌላም ልታደርግ ብትፈልግ ሁሉን ያለቁጣ ከስሜታዊነት ወጥተህ ፈጽም፡፡ለራሱ ሐኪም እያስፈለገው ሌላውን ሊፈውስ እንዴት ይቻለዋል፡፡ ራሱን አቁስሎ ሳለ የሌላውን ቁስል ሊፈውስ የሚጥር ይህ ሰው ራሱን የሚያድነው መቼ ነው? አንድ ሐኪም ሌላውን ለማዳን በሚሄድበት ጊዜ የራሱን እጅ ያቆስላልን? አስቀድሞ የራሱን ዐይን አሳውሮ የሌላውን ዐይን ለማዳን የሚሄድ ሐኪም አለን? እንዲህ ከማድርግ እግዚአብሔር ይጠብቀን፡፡ ቢሆንም ሌላውን ከመገሠጽህና ከመምከርህ በፊት የራስህ ዐይኖች አጥርተው የሚያዩና ንጹሐን ይሁኑ፡፡

 

እእምሮህን ከጭቃው ጋር አትደባልቀው እንዲህ አድርገህ እንደሆነ እንዴት ተብሎ ነው አንተን መፈወስ የሚቻለው?ቁጡና ከቁጣ ንጹሕ መሆን ልዩነታቸው በጭራሽ የሚነጻጸሩ አይደሉም፡፡ ያንተን ጌታ አስቀድመህ ከዙፋኑ ላይ ጥለህና ከጭቃው ጋር ለውሰህ ስታበቃ እንዴት ብለህ ነው ከእርሱ እርዳታን የምትሻው? ዳኞች የዳኝነት ካባቸውን ደርበው ከፍርድ ዙፋናቸው ላይ ከመቀመጥ ይልቅ በአፈር ላይ ይቀመጣሉን? አንተም ነፍስህን የዳኝነት ልብስን አልብሰሃት በተገቢው ቦታዋ ልታስቀምጣት ይገባሃል፡፡ እርሱም የማስተዋል ልብስ ነው፡፡ ነገር ግን “እንዲህ ባደርግ ሠራተኛዬ እኔን ሊፈራኝ አይችልም ትለኝ” ይሆናል፡፡ ይበልጥ ይፈራሃል፡፡ አንተ ሠራተኛህን ለምን እንዲህ እንዲህ አላደረግህ በቀጥታ ብትናገረው ባንተ ላይ ሊቆጣ ይችላል፡፡ ነገር ግን በትሕትና የተናገርኸው ከሆነ በስህተቱ ራሱን ይወቅሳል፡፡ እንዲህ በማደርግህ የመጀመሪያህ ጥቅምህ ምንድን ነው? እግዚአብሔር አንተን ያከብርሃል ከዘለዓለማዊውም በረከቶቹ ተሳታፊ ያደርግሃል፡፡ በጌታችን በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ፍቅር ለእግዚአብሔር አብና ለእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ክብር ምስጋና አገዛዝ ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን፡፡

የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ያስገነባው ሕንፃ ተመረቀ

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

•    የብፁዕ አቡነ ቄርሎስ 25ኛ ዓመት የብር እዩቤልዩ በዓልም ተያይዞ ተከብሯል

{gallery count=1 width=350 height=300 counter=1 links=0 alignment=center animation=3000}abunekerilos{/gallery}

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ያስገነባው ባለ ሁለት ፎቅ ሁለገብ ሕንፃ፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ተወካዮች፣ የመንግሥት አመራር አካላት፣ የአድባራትና የገዳማት አስተዳዳሪዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት ህዳር 10/2004 ዓ.ም የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ አትናቴዎስና በአቶ ሓየሎም ጣውዬ የወልድያ ከተማ ከንቲባ ተመረቀ፡፡

 

መልአከ ሐይል ስጦታው ሞላ በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ ክፍል ኃላፊ  የአዳጎ ሕንፃ መሠራቱ ቤተ ክርስቲያኒቱ በስብከተ ወንጌል የምታደርገውን እንቅስቃሴ በጉልህ የሚደግፍ ነው ብለዋል ፡፡ የወልድያ ከተማ ከንቲባ አቶ ሓየሎም ጣውዬ በምረቃው ወቅት ‹‹ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሕዝቡን በእምነቱ የጸና፣ ሀገር ወዳድና በልማት ዋነኛ ተሳታፊ ለማድረግ እያከናወናቸው ያለው አበረታች የልማት ተግባራት መንግሥት ከያዛቸው የድኅነት ማስወገጃ ስትራቴጂዎች አንፃር የሚሄዱ ለመሆናቸው ምስክርነት የሚያሻው ጉዳይ አይደለም፡፡ ሀገረ ስብከቱ ከጀመራቸው የልማት ሥራዎች መካከል የወልድያ ከተማችን የኢንቬስትመንት እድገት የሚያሠራውን አዳጎ ላይ የተገነባው ሕንፃ ለሌሎችም አርአያ ከመሆን አልፎ ለብዙ ዜጎች የሥራ ዕድል ፈጥሮ ያለፈና አሁንም እየፈጠረ ያለነው ቢባል መጋነን አይሆንም ›› በማለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

 

ቦታው የሀገረ ስብከቱ ይዞታ በመሆኑ፣ በመሐል ከተማ ያለ ሆኖ ሕንፃው መገንባት ስላለበት እንዲሁም በመንግሥት አካላት በሕንፃ እንድትሰሩ እድሉ የእናንተ ነው ስለተባለ፤ ሕንፃውን ልንሠራ ችለናል በማለት መልአከ ሐይል ስጦታው ሞላ ተናግረዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የሕንፃውን ፕላን በነጻ ሠርቶ መስጠቱ የሚያስመሰግነው ነው በማለትም አክለዋል ፡፡

 

ሀገረ ስብከቱ ያስገነባው አዳጎ ሕንፃ ባለሁለት ዘመናዊ ፎቅ ሲሆን ስድስት ሱቆች፤ አንድ ካፍቴሪያና ሬስቶራንት ፣ አንድ መለስተኛ አዳራሽ እና ሃያ ስድስት ለጽ/ቤት አገልግሎት የሚሰጡ ክፍሎች ያሉት ነው ፡፡ ሕንፃውን ለመሥራት ሁለት ዓመት የወሰደ ሲሆን በአጠቃላይም በ3.8 ሚሊዮን ብር ተጠናቋል፡፡

 

ከዚህ በፊት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ከበጎ አድራጊዎች ጠይቀው ባገኙት ከ300,000.00 ባላነሰ ወጪ የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና (ባለ አንድ ፎቅ ሕንፃ) እንዲሁም የካህናት ማሠልጠኛ በብር 260,000.00 መሠራቱ የሚታወስ ነው፡፡ ተያይዞም የብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣ የቅዱስ ላሊበላ ደብር የበላይ ጠባቂና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል 25ኛ ዓመት የብር ኢዩቤልዩ በዓልም በደማቅ ሁኔታ ተከብሯል ፡፡

 

በሰሜን ወሎ ሀገረ ስበከት ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ ከመሾማቸው በፊት በወሎ ሀገረ ስብከት ሥር የነበረ መሆኑና ብፁዕነታቸው ከተሾሙ ጊዜ ጀምሮ ከህዳር ወር 1980 ዓ.ም ጀምሮ ከሀገረ ስብከቱ ባለመለየት በትጋት የወንጌል አገልግሎታቸውን እየተወጡ ያሉ አባት መሆናቸውን የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መልአከ ገነት ዓለሙ አስማረ በወልድያ ከተማ ባህል አዳራሽ በተካሄደው ዝግጅት ተናግረዋል፡፡ ሥራ አስኪያጁ አያይዘው ብፁዕነታቸው ሊቀ ጳጳስ ሆነው ከተመደቡ ከ1980 ዓ.ም ጀምሮ ቀድሞ አንድ ብቻ የነበረውን ሰ/ት/ቤት አሁን ላይ አራት መቶ ሦስት መሆናቸውን ፣ አራት መቶ ሠላሳ አንድ  መምህራን መሰልጠናቸው፣ ከመቶ 20% ከብር 70,220.41 ወደ ብር 3,236,486.48 ማደጉን፣ በወረዳ ቤተ ክህነት ሠራተኞች ከሠላሳ አራት ወደ ሠባ ስድስት፣ ሀገረ ስብከቱ ሲመሰረት አምስት ሠራተኞች የነበሩ ሲሆን አሁን ሃያ ሁለት ሠራተኞች መጨመሩን፣ አጎራባች አህጉረ ስብከቶችን ሳይጨምር ለሀገረ ስብከቱ አገልጋዮች 7,618 የዲቁናና የቅስና ማዕረግ መስጠታቸውን፣ በምዕመናን ቁጥር በ173,791 ዕድገት መታየቱን፣ በወረዳ ደረጃ፣ በልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን በኩልና ሐዋርያዊ ጉዞ ያደረጉትን ግልጋሎት በሪፖርት አቅርበዋል፡፡

 

ከበዓሉ ታዳሚዎች ቅኔና መወድስ የቀረበ ሲሆን ምዕመናንም ለብፁዕነታቸው ረጅም የአገልግሎት ዕድሜን ከጤና ጋር እግዚአብሔር እንዲሰጣቸው ተመኝተዋል፡፡

 

ብፁዕነታቸው ያለባቸውን ከፍተኛ ሕመም በመቋቋም ለሠሩት ሥራም ከልዮ ልዮ አካላት ሽልማቶች የተበረከተላቸው ሲሆን የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችም ሙሉ መቀዳሻ አልባስ፣ ቆብና የእጅ መስቀል እንዲሁም ጥና ሲሸልሙ፤ የቅዱስ ላሊበላ ደብር በበኩሉ በትረ ሙሴ አበርክቶላቸዋል፡፡ ተያይዞም በአዳጎ ሕንፃ  አስተዋጽኦ ላደረጉ ልዩ ልዩ አካላት የሽልማትና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷል፡፡

 

በዕለቱም የብፁዕነታቸውን ከልጅነታቸው ጀምሮ እስከአሁን ድረስ ያለውን ሐዋርያዊ አገልግሎት የያዘ መጽሔት ለንባብ በቅቷል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ በብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት እጅ ግንቦት 30/1979 ዓ.ም የበዓለ መንፈስ ቅዱስ ዕለት ከአምስት አባቶች ጋር ለጵጵስ  ሹመት የበቁ ሲሆን እንደተሾሙም የተመደቡት በሰሜን ወሎ ሀገረ ስብከት መሆኑ ይታወቃል፡፡ ብፁነታቸው በሰሜን ወሎና ዋግ ኽምራ አሁጉረ ሰብከት በዋናነት ያገለገሉና እያገለገሉ ያሉ ሲሆን በተጨማሪም የአሰብ፣ የደቡብ ወሎ እና የደቡብ ሸዋ ሀገረ ስብከትን በሊቀ ጵጵስና ደርበው እንዲሁም በ1986 ዓመተ ምሕረት በምሥራቅ ሸዋ ተዛውረው ለስምንት ወራት አገልግለዋል ፡፡

የቅዱስ ኤፍሬም ቅኔያዊ መዝሙራት /ክፍል ሁለት/

ዳር 14/2004 ዓ.ም

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

“እግዚአብሔር በሰው አምሳል የመታየቱ ምሥጢር”

በዚህ ርእስ ግሩም የሆነውን የቅዱስ ኤፍሬም መጽሐፍ ቅዱስን የመረዳት ጸጋውን እንመለከታለን፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለሰዎች በመጽሐፍ ቅዱስ በኩል ሲናገር  የሰውን የአካል ክፍል እና ጠባይ ለራሱ በመጠቀም ነው፡፡ ይህ መዝሙር እንዴት የሰው ልጅ በእርሱና በእግዚአብሔር መካከል ያለውን ታላቅ የሆነውን ልዩነት አልፎ  ስለእግዚአብሔር ባሕርያት ማወቅ ይችላል? ብሎ ይጠይቃል፡፡ በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለውን ልዩነት ቅዱስ ኤፍሬም ታላቅ ገደል ወይም ቅዱሱ ጸጥታ ብሎ ይጠራዋል፡፡ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም አስተምህሮ ለሰው የሚሰጠውን መጠሪያና ተፈጥሮ ለራሱ በመጠቀም  በእርሱና በሰው መካከል ያለውን ሰፊ የሆነ ልዩነት ያጠበበው እግዚአብሔር ራሱ ነው፡፡ እንዲህ ማደርጉ ክብር ይግባውና ለሰው ልጆች ካለው ጥልቅ ፍቅር የተነሣ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን እግዚአብሔር ለሰው የሚሰጠውን መጠሪያና ጠባይ ለራሱ ተጠቅሞበት እናገኛለን፤ እንደ ቅዱስ ኤፍሬም ትምህርት ደግሞ እንደ ልብስ ለብሶአቸው እናገኛቸዋለን፡፡

አስተምህሮውን ከዚህ ቅኔያዊ መዝመር ያገኙታል፡፡
1.በእኛ ምሳሌ በመገኘት ራሱን የገለጠልን እግዚአብሔር አምላክ የተመሰገነ ይሁን፤

መጽሐፍ ቅዱስ እግዚአብሔር እንደሚሰማን ለማስረዳት ሲል ስለጆሮዎቹ ጻፈልን፤ /መዝ. 33፥15/
እኛን ስለመመልከቱ ሊያስተምረንም ስለ ዐይኖቹ ተረከልን፤ /መዝ. 33፥15/
በዚህ መልክ በምሳሌአችን ተገልጦ ለእኛ ታየን፡፡
እርሱ በባሕርይው ቁጣና ጸጸት የሌለበት አምላክ ሲሆን፤ ዘፍ.6፥6
ስለእኛ ደካማነት እነዚህንም ስሞች ለራሱ በመስጠት ተጠቀመባቸው ፡፡ /1ሳሙ.15፥29/

2.እርሱ በእኛ ምሳሌ ተገኝቶ ባያስተምረን እርሱን ባላወቅነው ነበር፤

በምሳሌአችን ተገልጦ ወደኛ ቀረበ እኛም ወደ እርሱ ቀረብን፡፡  
አባት ከልጁ ጋር ሲነጋገር በልጁ ማስተዋል መጠን እንዲናገር፣
እንዲሁ እግዚአብሔር በእኛ ማስተዋል መጠን ስለፈቃዱ አስተማረን፡፡

3. እንደመረዳታችን መጠን አስተማረን ስንል እርሱ እንደእኛ ነው ማለታችን ግን አይደለም፤

እርሱ በእኛ ምሳሌ ተገለጠ ወይም አልተገለጠ እርሱ እርሱ ነው፤ አይለወጥም፡፡
ሲያስፈልግ እኛን ለማስተማር በአንዱ ጠባያችን  ተገልጦ ይታየናል፤
ሌላ ጊዜ ደግሞ አስቀድሞ የተላበሰውን ምሳሌአችንን እንደልብስ አውልቆ ሌላውን ለብሶ ይገለጥልናል፤
እርሱ በምሳሌአችን ተገኝቶ ለእኛ በመናገሩ እርሱ እንዲህ ነው ማለት ግን አይደለም፤
ነገር ግን ባሕርይው የማይመረመር ነውና በምንረዳው በእኛ ምሳሌ ተገኝቶ ፈቃዱን ገለጠልን፡፡

4.በአንድ ቦታ እርሱ በዘመን ርዝማኔ የሸመገለ አረጋዊ መስሎ ሲታየን፤ /ዳን.7፥9/

በሌላ ስፍራ ደግሞ እጅግ ብርቱ የሆነ ተዋጊ ሆኖ ይገለጥልናል፡፡ /ዘፀ.15፥3/
በሽማግሌ አምሳል መታየቱ ፍትሐዊ መሆኑን ለማስተማር ነው፤
ብርቱ ጦረኛ ሆኖ መታየቱ የእርሱን ኃያልነት ለማስረዳት ነው፤
በአንድ ቦታ እንደሚዘገይ በሌላ ቦታ የሚቀድመው የሌለ ፈጣን እንደሆነ መጻፉ፤
በአንድ ቦታ እንዳዘነ በሌላ ቦታ ደግሞ እንዳንቀላፋ ሰፍሮ መገኘቱ፤ኢሳ./7፥13፣ መዝ.43፥23፣ 78፥66/
በአንድ ቦታም  ሁሉን እንዳጣ ምስኪን ሆኖ ስለእርሱ መተረኩ፤
ስለእኛ ጥቅም እንጂ እርሱ ሁሉ የእርሱ የሆነ ባለጠጋ ነው፤
በእውኑ በእኛ ላይ የሚታዩት ጠባያት በእርሱ ላይ አሉን? የሉም፡፡

5.ቸር የሆነው ፈጣሪ አንዳች ሳይቸገር፣ ያለፈቃዳችን እርሱን ደስ የሚያሰኝ ሥራን እንድንፈጽም ማስገደድ ይቻለዋል፤

ከዚህ ይልቅ ግን በፈቃዳችን እርሱን ደስ የሚያሰኝ ሥራን እንድንሠራ ይሻል፤
ስለዚህ እርሱ የሚወደውን የጽድቅ ሥራ እንድንሠራና በጽድቅ ተውበን እንድንገኝ በእኛ አምሳል ተገለጠልን፡፡
አንድ ሠዓሊ የሣለውን ሥዕል በቀለማት እንዲያስውበው፤
አምላካችንም በአምሳላችን ለእኛ በመገለጥ በጽድቅ ሕይወት አስጌጠን፡፡

6.አንድ ሰው በቀቀንን ንግግር ለማስተማር ቢፈልግ ራሱን በመስታወት ጀርባ ይሰውራል፤

በቀቀኑዋን ግን ከመስታወቱ ፊት በማድረግ የሰውን ቋንቋ ያሰማታል፤
በቀቀኑዋም ድምፁን ወደሰማችበት አቅጣጫ ስትዞር የራሱዋን ምስል በመስታወት ውስጥ ታገኛለች፤
ምስሏን ስትመለከት ሌላ በቀቀን እርሱዋን እያነጋገረቻት ይመስላታል፤ስለዚህም አጸፌታውን ትመልሳለች፤
በዚህ መልክ ሰውየው በበቀቀን አምሳል በመገኘት ለበቀቀኑዋ ንግግርን ያስተምራታል፡፡

7.ይቺ በቀቀን ከሰው ጋር ተግባብታ የምትኖር ፍጥረት ነች፤

ነገር ግን እንዲህ እንድትግባባ ከእርሱዋ ተፈጥሮ ውጪ የሆነው ሰው ሊያስተምራት ተገባ፤
እንዲሁ ከሁሉ በላይ እጅግ ከፍ ከፍ ያለው መለኮት፤
ስለፍቅር ከላይ ከከፍታው ራሱን ዝቅ በማድረግ በእኛ ምሳሌና ልማድ ተገኝቶ ፈቃዱን ያስተማረን፤
ሁላችንን  ወደ ጽድቅ ሕይወት ለመምራት በደካማው በሰው አምሳል ለእኛ ተገለጠልን፡፡


8.እርሱ አንድ ጊዜ በእድሜ ርዝማኔ ያረጀ ሽማግሌ መስሎ ሲታይ ሌላ ጊዜ በተዋጊ ተመስሎ ይገለጥልናል፤

በአንድ ቦታ የማያቀላፋ ትጉህ እረኛ ሆኖ ሲታይ፤ በሌላ ስፍራ ደግሞ እንዳንቀላፋ ሆኖ ይገለጥልናል፤/መዝ.12ዐ፥3-4/
በአንድ ቦታ እንደሚጸጸት ሆኖ ሲገለጥልን፤ በሌላ ስፍራ ደግሞ ጸጸት የሌለበት ጌታ እንደሆነ ያስተምረናል፤/ኢሳ.40፥28/
በፈቃዳችን ራሳችንን ለማስተማር እንድንበቃ  እርሱ በሚወሰንና በማይወሰን አምሳል ለእኛ ተገለጠልን፡፡
በአንድ ስፍራ ብሩህ በሆነ የሰንፔር ድንጋይ በሚመስል ወለል ቦታ እንደቆመ ሆኖ ሲታየን፤ /ዘፀ.4፥10/
በሌላ ቦታ ደግሞ ሰማይንና ምድርን የሞላ ፤ ፍጥረት ሁሉ በመሃል እጁ የተያዘች እንደሆነች ይነግረናል፡፡ /ኢሳ.40፥12/

9.ሲፈልግ በተወሰነ ቦታ ለእኛ ሲገለጥ፤

ሲፈልግ ደግሞ በሁሉ ስፍራ ይገልጥልናል፤
በአንድ ስፍራ በአምሳላችን ሲገለጥ በቦታ የተወሰነ ይመስለናል፤  እርሱ ግን በሁሉ ስፍራ ነው፡፡
በሌላ ስፍራ እኛን በቅድስና ሕይወት የበቃን ያደርገን ዘንድ ታናሽ መስሎ ለእኛ ይገለጥልናል፤
በተቃራኒው ደግሞ እኛን እጅግ ባለጠጎች ያደርገን ዘንድ በታላቅነቱ ያታየናል፤
እኛን በክብር ለማላቅ ሲል አንዴ ታናሽ ሌላ ጊዜ ታላቅ ሆኖ ይገለጥልናል፤
እርሱ ታናሽ ሆኖ ብቻ እንጂ ታላቅ ሆኖ ባይገለጥልን፤
ደካማ መስሎን ስለእርሱ ግንዛቤ የተዛባ ይሆን ነበር፡፡
እንዲህ እንዳይሆንም አንዴ ታናሽ ሌላ ጊዜ ታላቅ ሆኖ ይታየናል፡፡


10.ኑ  የእኛን ታናሽ የሆነን ተፈጥሮ ለማላቅ ሲል ታናሽ መስሎ የተገለጠውን አምላክ እናድንቅ፤

ለእኛ ታናሽ መስሎ እንደተገለጠ ሁሉ በታላቅነቱ ለእኛ ባይገልጥልን፤
እርሱን ደካማ አድርገን ስለምንቆጥር ስለእርሱ ያለን ግንዛቤ ያነሰ ይሆን ነበር፡፡
አይደለም በታላቅነቱ በእኛ አምሳል ተገልጦልን እንኳ ስለእርሱ መለኮታዊ ባሕርይ መረዳት አልተቻለንም፤
ስለእርሱ ታላቅነት በተመራመርን ቁጥር እጅግ እየረቀቅን በእውቀትም እየመጠቅን እንሄዳለን፤
እርሱን የመረዳት አቅማችን እየጫጨ ሲመጣ ፣ ለእኛ አምሳል በመታየት ወደ እርሱ ፈቃድ ይመራናል፡፡

11.እግዚአብሔር በእኛ አምሳል መገለጡ ሁለት ዓበይት ቁምነገሮችን ሊያስተምረን በመሻቱ ነው፤ /ዮሐ.1፥11/

አንደኛው አምላክ ሰው መሆኑን ሁለተኛው ሰው መሆኑ አምላክነቱን እንዳላሳጣው ሲያስተምረን ነው፡፡
ለእኛ ለባሮቹ ካለው ፍቅር የተነሣ በሚታይ አካል ለእኛ ተገለጠ፤
ነገር ግን በሰው አምሳል በመገለጡ እርሱን በማሳነስ እንዳንጎዳ፣
አንዴ በአንዱ አምሳል ሌላ ጊዜ በሌላ አምሳል ለእኛ ይገለጥልናል፤
በዚህም እርሱን የሚመስለው እንደሌለ አስተማረን፤
እርሱ በሰው አምሳል መታየቱን ሳይተው ለእኛ መገለጡ፤
እርሱን በተለያየ አምሳል እንዳይገለጥ አይከለከለውም፡፡

ክፍል ሦስት ይቀጥላል…….

ጾመ ነቢያት

በዲ/ን አሻግሬ አምጤ
ቀን: ህዳር 14/2004ዓ.ም.

ክርስቲያኖች ከእግዚአብሔር በጸጋ እንደተወለዱ በማመን ለእግዚአብሔር ያላቸውን ፍቅር ከሚገልጡባቸው ነገሮች አንዱ ጾም ነው፡፡ ጾም ፍቅረ መብዓ ከመሆኑ በተጨማሪ ታዛዥነትንና የገቡትን ቃል ኪዳን ጠባቂነትንም ማሳያ ነው፡፡ የሰው ልጅ በእግዚአብሔር አርአያ ተፈጥሯአል፡፡ ኃጢአት ሠርቶ የእግዚአብሔር አርአያነቱን ቢያጠፋውም እግዚአብሔር ግን በአርአያው ሲፈጥረው ምን ያህል እንደሚወደው ማረጋገጫ ስለነበር በኃጢአት ሲወድቅም እንደወጣ ይቅር ሳይል ሊፈልገው መጣ፡፡ እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ሊፈልግ የመምጣቱ ተስፋ የተነገረበትንና ሱባኤ የተቆጠረበትን ዕለት ለማየት በመናፈቅ ከቀረበው መሥዋዕት አንዱ ጾም ነበር፡፡

 

ሰው በኃጢአት ቢወድቅም ፈጣሪው ሊያነሳው፤ ቢጠፋ ሊፈልገው እንደሚመጣ በተስፋ ሲጠብቀው ወልደ አምላክ ሰው መሆኑ የተረጋገጠ እውነት ነው፡፡ ስለዚህ አዳም የልደቱን ነገር በትንቢት መነፅርነት ሲመለከተው /በነቢያቱ ትምህርትና ስብከት/፣ በሚኖርበት ዓመተ ፍዳ የምሥጢረ ሥጋዌ  ብርሃን ከሩቅ ሲመለከተው ኖረ፡፡ ምሥጢረ ሥጋዌን በትንቢት መነፅርነት ማየቱም መከራውን እንዲቋቋመው የተስፋ ስንቅ ሆነው፡፡

 

ጾም ሰው ለእግዚአብሔር ያለውን ፍቅር እና ታዛዥነት መግለጫና ማረጋገጫ ብቻ አይደለም፤ አልነበረም፡፡ ሲወድቁ መነሻ ከብልየት መታደሻ፥ ከኃጢአት ቆሻሻ መታጠቢያ /ከንስሓ ጋር አብሮ ሲፈጸም/ ሳሙናም ነው፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ በሲና ተራራ ላይ እግዚአብሔር ወደ ነበረበት ጨለማ የገባው፣ አስፈሪውን መብረቅና ነጐድጓድ የተቋቁመው፣ ጨለማውን አልፎ የሰው ልጅ ያልሠራትን ሰማያዊ መቅደስ የተመለከተውና ወደ ዓለቱ ድንጋይ የቀረበው ራሱን ለእግዚአብሔር በጾም በመቀደስ ጭምር ነው፡፡ /የወገን ፍቅርና ለእግዚአብሔር ታዛዥነቱ እንዳለ ሆኖ/፡፡ ጾም እነዚህንና መሰል መንፈሳዊ በረከትን ስለሚያስገኝ ክርስቲያኖች ይመጣላቸው ዘንድ ይናፍቁታል፡፡ ከእነዚህ የሚናፈቁ አጽዋማት መካከል አንዱ ጾመ ነቢያት ነው፡፡ ጾመ ነቢያት የሚባለው ጾመ ገና፣ ጾመ ማርያም፣ ጾመ አዳም፣ ጾመ ፊልጶስ ተብሎ እንደሚጠራ መምህር ቃኘው ወልዴ ጾምና ምጽዋት በተሰኘው መጽሐፋቸው ገልጠውታል፡፡

 

ጾመ ነቢያትም ሆነ ሌሎች አጽዋማት ሲደርሱ ክርስቲያኖች የሚደሰቱት ጾም የሥጋ ፈቃድ እንዳይሰለጥንባቸው፣ ቁስለ ሥጋን በማከም፣ ቁስለ ነፍስን ስለሚፈውስላቸው ነው፡፡  ጾም የቁስል መፈወሻ ኃይለ መዊዕም ይሆናል፡፡ ከሥጋም ከመንፈስም ተቆራኝቶ ሰውን ወደ ጥፋት የሚወስድን ክፉ መንፈስ ለማራቅም ይጠቅማል፡፡ ጾም የሥጋን ምኞት እስከመሻቱ ቆርጦ የሚጥል፣ ለመንፈስ ልዕልና የሚያበቃውን መሳሪያ የሚያስታጥቅ ነው፡፡ ክርስቲያን ይህን መሰል መንፈሳዊ የጦር እቃ እንዳይለየው አጥብቆ ይለምናል፡፡ የጦር ልምድ እንደሌለው ወታደር ጠላቱን የሚቋቋምበት የጦር ትጥቅ ሳይዝ አውላላ ሜዳ ላይ  ባዶውን አይቆምም፡፡ መንፈሳዊ ውጊያን በሥጋዊ ጥበብ ማሸነፍ ስለማንችል ነው አበው ፍቅረ አጽዋማትን በአስተምህሮአቸውና በሕይወታቸው የሰበኩልን፡፡

 

የጾመ ነቢያት መግቢያ በሊቃውንቱም ሆነ የጠለቀ እውቀት በሌለው ምእመን አነጋጋሪ ሆኖ ቆይቷል፡፡ ችግሩን ለመፍታት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘመነ ፕትርክና ጾመ ነቢያት ኅዳር አስራ አምስት እንዲጀመር ተወስኗል፡፡ ክርስቲያኖችም የአባቶችን ውሳኔ መሠረት በማድረግ እየጾሙት ይገኛሉ፡፡

 

ጾመ ነቢያት ለአዳም የተነገረው ትንቢት፣ የሚጠበቀው ሱባኤ እንደደረሰ የሚያበስር በመሆኑ ጾመ አዳም ይባላል፡፡ አዳም ቢበድልም ንስሐ ገብቶ በማልቀሱ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሀለሁ ብሎ የተነገረው ተስፋ መድረሱን፣ ምሥጢረ ሥጋዌ እውን ሊሆን መቃረቡን የሚያስረዳ ጾም ነው፡፡ ነቢያትም የምሥጢረ ሥጋዌ ነገር ተገለጦ ስለታያቸው፣ ክርስቶስ ለሰው ልጅ የሚከፍለውን የፍቅር ዋጋ በትንቢት ተመልክተው ጾመውታልና ጾመ ነቢያት ይባላል፡፡ ይህ ጾም የራቀውን አቅርቦ፣ የረቀቀውን አጉልቶ ስላሳያቸው እስከሞት ድረስ ቢደበደቡም፣ ከመከራው ጽንአት የተነሣ ዋሻ ለዋሻ፣ ፍርኩታ ለፍርኩታ ቢንከራተቱም፣ የፍየል ሌጦ ለብሰው ቢዞሩም የተስፋው ቃል ሁሉን አስረስቶአቸው ከትንቢቱ ባለቤት ጋር በመንፈስ ተዋሕደው አልፈዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ሐዋርያት ምን ሠርተን የክርስቶስን ልደት እንቀበለው ብለው ስለጾሙት ጾመ ሐዋርያት ተብሎ ይጠራል፡፡

 

ጾመ ነቢያት እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ወልደ አብን ፀንሼ ምን ሠርቼ እወልደዋለሁ በማለት ጾማዋለችና ጾመ ማርያም ይባላል፡፡ ይህን ያለችው በመደነቅ፣ አንድም በትሕትና አንድም ቀደምት አባቶቿ ነቢያት ሲጾሙት አይታ ጾማዋለች፡፡ እንዴት ፀንሼ እወልደዋለሁ ማለት ጥርጥር ሳይሆን ተደሞ፣ መደነቅ የነገረ ልደቱን አይመረመሬነት ይገልጻል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ትሕትና ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ቅድስናዋን አይቶ በብስራተ መልአክ አማካኝነት ክርስቶስን እንደምትወልድ ቢነግራትም የትሕትና እናት ናትና ምን ሠርቼ የሰማይና ምድርን ፈጣሪ እችለዋለሁ ስትል ጾማዋለች፡፡ ይህ ጾም ጾመ ፊልጶስም ይባላል፡፡ ሐዋርያው ፊልጶስ በአረማውያን ዘንድ ገብቶ ሲያስተምር በሰማዕትነት ሲሞት አስከሬኑ ከደቀመዛሙርቱ ስለተሰወረ እግዚአብሔር የተሰወረውን የመምህራቸውን አስከሬን እንዲገልጽላቸው ከኅዳር አስራ ስድስት ጀምረው ሲጾሙ በሦስተኛው ቀን የመምህራቸው አስከሬን ቢመልስላቸውም ጾሙን ግን እስከ ልደት ቀጥለዋል፡፡ የጾመ ነቢያት መግቢያው ኅዳር አስራ አምስት ቢሆንም ማብቂያው ልደት ነው፡፡ ጾምን ትእዛዝ ስለሆነ ብቻ ሳይሆን የፍቅርና የበረከት ምንጭ በመሆኑ ጭምር ደስ እያለን ብንጾመው የቅዱሳኑ በረከት ያድርብናል፡፡

ይቆየን…..

ክብር ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር ስምረቱ ለሰብ

የመንፈስ ልዕልና

በዲ/ን አሻግሬ አምጤ
ግንቦት 2፣2003ዓ.ም

ልዕልና ከተለመደ ነገር ላቅ ማለትን፣ ሰው ሊሠራው ከሚችለው በላይ መስራትን ያመለክታል፡፡ በአስተሳሰብ ምጥቀት፣ በሚፈጸም ጀብዱ ይገለጻል፡፡ ጥብዓት፣ በመንፈሳዊ ቆራጥነት፣ ወኔ፣ በተፋፋመ አካላዊ  ሆነ መንፈሳዊ ጦርነት ለመግባት መጨከን የልዕልና መገለጫዎች ናቸው፡፡ “በሞት ጥላ መካከል እንኳን ባልፍ ክፉን አልፈራም አንተ ከእኔ ጋር ነህና” እንዳለ መዝሙረኛው፡፡

 

ልዕልና ያለፈውን እየረሱ ወደፊት ሊደርሱበት የሚሹትን ለመናፈቅ ይዳርጋል፡፡ በፈተና ተወልውሎ እንደ ወርቅ ጠርቶ ይገኛል፡፡ ለእኔ ብኲርናዬ ምኔ ናት በማለት የተናገረው ብኲርና ልዕልና መሆኗን ባለመረዳቱ ነው፡፡

ሥጋዊ ፈቃድ የጠየቀውን ሁሉ አለመተግበር፣ በስሜት የተፈጠረን ሁሉ ለማስተናገድ አለመሞከር በተቃራኒው መንፈስ በሥጋ ላይ ማሰልጠን ወይም ሥጋን ለመንፈስ ማስገዛት የልዕልና ተግባር ነው፡፡ የሰሙትን ምሥጢር መጠበቅ፣ የተቀበሉትን አደራ መወጣትም እንዲሁ ቃልን መጠበቅ፣ ታምኖ መሰማራት፣ አደራን መመለስ ለሁሉ አይቻለውም፡፡ ልዕልና በፈተና መጽናትን፣ እንደወርቅ መቅለጥን፣ ሌላው እየበላ ጦም ማደርን፣ ሌላው እየዘነጠ በድህነት መማቀቅን ሊያስከትል ይችላል፡፡ የሚያልፈውን በማያልፈው አሸንፈው፣ ጊዜያዊውን በዘለዓለማዊው ተቆጣጥረው የተጋረጠባቸውን ያሸንፉታል ለልዕልና የታጩቱ፡፡

ሰው ለልዕልና የሚታጨው የፈተናን የክብር ምንጭነት አምኖ ሲቀበል ነው፡፡ አደራ ለመቀበል መብቃት፣ አደራም ለመስጠት ሰውን ማመን ልዕልና አይደለም ትላላችሁ? “መተማመን ከሌለ አደራ ሰጪም አደራ ተቀባይም አይኖርም” እንዲሉ አበው፡፡ ይህ ብቻም አይደል “አደራ ጥብቅ ሰማይ ሩቅ” በማለት ታምኖ መገኘትና አደራን መወጣትን ከሰማይ ርቀት ጋር ያነጻጽሩታል፡፡ እኒህ የተጠቀሱት የልዕልናና የአደራ ጥብቅነት ማሳያዎች ምግባርን ከሃይማኖት አዋሕደው፣ ፍቅረ እግዚአብሔርንና አክብሮተ ሰብእን አጣምረው እንዲኖሩ ኅሊናን ገርተው፣ ጊዜያዊ የሥጋ ፍላጎትን ተቆጣጥረው ይኖራሉ፡፡

 

አደራን ለተወጣ ማኅበረሰቡ የሚያቀርብለት ሙገሳ፣ ውዳሴ፣ ሞራላዊ ሽልማት ለልዕልና ያበቃል፡፡ ሌሎች አደራውን ተወጥቶ ክብር የተቸረው ከደረሰበት ለመድረስ አርአያነቱን ይከተላሉ፡፡ እውነትን ከሐሰት የማያቀላቅል፣ የገባውን ቃል የማይከዳ ይከበራል፡፡ እንዲፈራ የሚያደርገው የመንፈስ ልዕልናው ነው፡፡

 

አደራ የመተማመን፣ የጽኑ ፍቅር ውጤት በመሆኑ አደራ የሚሰጠው ለሚታመን ሰው ነው፡፡ በመተማመን የሚተገበረው አደራ የማያልፍ ዘለዓለማዊ ክብር ያጎናጽፋል፡፡

 

ክብሩ ምድራዊም ሰማያዊም ሊሆን ይችላል፡፡ “የምትጸድቅን ነፍስ ጎረቤት ያውቃታል” የሚለው ብሂል ለዚህ ትንታኔ ድጋፍ ይሆናል፡፡ አደራን ሳይወጡ ከመቅረት ይልቅ ሞትን መምረጥና ክብርን ተክሎ ማለፍ መብለጡን ሐዲስ ዓለማየሁ በማይጨው ጦርነት ጊዜ ተመልክተውት በኅሊናቸው ታትሞ የቀረን ክስተት እንዲህ ይተርኩታል፡፡

 

“ጌትየው በጽኑ ቆስለው በጣዕር ውስጥ እንዳሉ እሷ ስታስታምማቸው እንደማይተርፉ ተረድተውት ኖሮ አንቺና ተስፋው ከሞት ተርፋችሁ ሀገራችሁ ለመግባት የበቃችሁ እንደሆነ መሳሪያዬንና አባቴ ሲሞቱ ለመታሰቢያቸው የሰጡኝን ዳዊቴን ለልጄ ለንጋቱ እንድታደርሱልኝ አደራ፡፡ እንግዲህ ያች ሰው ሁሉ ነፍሷን እንድታተርፍ ያን ያህል ሲማጠናት ዐይኗ ዕያየ በቦንብ ተቃጥላ የሞተች የወዳጇን የአደራ ኑዛዜ ለመፈጸም ኖሯል፤ ምን አይነት እስከ ሞት የሚያደርስ ታማኝነት ነው ምን አይነት ሀያል ፍቅር ቢሆን ነው? ለሃይማኖቷ ብላ፣ እንዲያ ተቃጥላ ሞተች፡፡” አለ ሰውየው፡፡ /ሐዲስ፣ 1985፣86ዓ.ም/


በዚያ ፍጥረተ ዓለም በፍርሃት በሚናጥበት፣ ሳር ቅጠሉ፣ ሰው አራዊቱ በሚያረግድበት ሰዓት አደራ መስጠትም ሆነ መቀበል አስቸጋሪ ነበር፡፡ ልጄ ሆይ ሰው ሁን ያለው እንዲህ ላለው ሰዓት ይሆን እንዴ? አደራ ሰጭው የሴትየዋን ፍቅርና ታማኝነት መዝነውታል፡፡ አደራ የተሰጣቸው ሁለት ነገሮች ጠመንጃና ዳዊት ናቸው፡፡ ሁለቱም ከጠላት መጠበቂያ ናቸው፡፡ አንዱ አፍአዊ ሌላው መንፈሳዊ ጠላትን ለመውጋት ያገለግላሉ፡፡ አንደኛው ባህር ተሻግሮ የመጣን ጠላት ለመቆጣጠር፣ ሌላኛው ከርስት መንግሥተ ሰማያት ከሚነጥል ጠላት ጋር ለመዋጋት ጋሻ ጦር የሚሆን ነው፡፡

 

ሴትየዋ በዚያች ቀውጢ ሰዓት የተሰጣትን አደራ ለመፈጸም ተነስታለች፡፡ ታማኝነት፣ አደራና ታላቅ ፍቅር በአንድ በኩል ሞት በሌላ በኩል ትይዩ ሆነው ቀርበዋል፡፡ ሞትን ፈርተው ማፈግፈግ ታማኝነትን ያፈርሳል፣ ታላቅ ፍቅርን ያቀዘቅዛል፣ አደራ በላም ያደርጋል፡፡ ከሁለቱ መምረጥ ስለነበረበት ሞትን ተጋፍጦ ታማኝነትን ማስመስከር ደምቆ ታያት፡፡ ቃልን አጥሮ፣ አደራን በልቶ በቁም ከመሞት ሥጋዊ ዕረፍትን ተቀብሎ ስምን ከመቃብር በላይ ማዋልን መረጠች፡፡ ሞትን ተገዳድረው የወጡት ታማኝነት፣ ሀያል ፍቅርና አደራ የሃይማኖትና የማተብ መገለጫዎች ሆኑ የሴቷ የፍቅር መስዋዕትነት ሀያል ፍቅር እኮ ሞኝም እብድም፣ ሃይማኖተኛም ሁሉንም ያደርጋል ተባለበት፡፡ በምድራዊ አደራ ብላ የፈጸመችው የሃይማኖትና የማኅተብ መገለጫ ሆነ፡፡ ሴትየዋ በዚህ ሰማዕትነቷ ከጊዜያዊ የጭን ገረድነት ወደ ዘለዓለማዊ የፍቅር ተምሳሌትነት ተቀየረች፡፡ ያለውን የሰጠ ይመሰገናል፤ ራሱን የሰጠ ደግሞ ተከብሮ ይኖራልና፡፡ የተሰጣትን አደራ ለመወጣት ያንን መስዋዕትነት ባትከፍል በደራሲው ምናብ ገድሏ ታትሞ ባልቀረ ነበር፡፡

 

የአደራን ጥብቅነት በተመለከተ ሁለት ነጥቦችን በመጨመር ሀሳቤን ላጠቃልል፡፡ ከዛሬ ዐስራ ዐራት ዓመት በፊት በአንድ ወረዳ ውስጥ የመጀመሪያ ደረጃ መምህር ሆኜ ሥሠራ በአደራ ጠባቂነታቸው ሀገር ስለ መሰከረላቸው የትምህርት ቤት ጥበቃ ባልደረባዬ አጫውቶኛል፡፡ እኒህ ሰው የሰው ገንዘብ እንደማይነኩና አደራ እንደሚጠብቁ የሚያውቅ አንድ መምህር ከቦታው ሲቀየር የተረፈችውን ዐራት ቁና ገብስ የሚያደርስበት ያጣል፡፡ ለሌላ እንዳይሰጠው ከማን ለማን ያደላል፡፡ ይዞት እንዳይሄድ የዐስራ ሁለት ሰዓት የእግር መንገድ ከሌላው ጓዙ በተጨማሪ ዐራት ቁና ገብስ መያዝ ሊጠበቅበት ነው፡፡ አማራጭ ሲያጣ የሰው ገንዘብ እንደማይነኩ ለሚታወቁት የጥበቃ ሠራተኛ አደራ ብሎ ይሰጣቸዋል፡፡ ይህን ያደረገው ስቀር ይጠቀሙበታል ብሎ በማሰብ ነው፡፡ ታሪኩን የነገረኝ ባልደረባዬ ተመድቦ ይሄዳል፡፡ አንድ ቀን ለዝክር ቤታቸው ሄዶ ጠላ እየጠጡ ሲጫወቱ ተንጠልጥሎ ጠቀርሻ የጠጣ ነገር ይመለከትና ምንነቱን ይጠይቃቸዋል፡፡ ምን እባክህ ያ እገሌ የሚባል ሰው አደራ አስቀምጦብኝ ይኸው ተንጠልጥሎ ቀረ ይሉታል፡፡ ባልንጀራዬም በዚህ ዘመን እንዲህ ያለ ሰው በማየቱ ተገርሞ በዓመቱ እኔ ካለሁበት ትምህርት ቤት ተቀይሮ ሲመጣ አጫውቶኛል፡፡

 

ቃሌን አጥፌና አደራዬን በልቼ ከችግሬ ላልወጣ ለምን ከፈጣሪዬ እጣላለሁ በማለት ይመስለኛል የሰውየው ጥንቃቄና ታማኝነት ስንቶቻችን ለማይሞላ ሆድ፣ ለማይረካ ፍላጎት ያውም ለነገ ለማይተርፍ ነገር አደራችንን በልተን ከፈጣሪ የተጣላን፤ ሰውም የታዘበን፡፡ 60 ዓመት በፈጣሪያቸው ረድኤት የኖሩ አባት በአንድ እለት ለምሳ ቋጥሯት የነበረችውን አገልግል የዛሬን ይብሉልኝ ብሎ በለመናቸው ጊዜ ዛሬ ያንተን አገኘሁ ብዬ በልቼ 60 ዓመት ከመገበኝ ፈጣሪዬ ልለይ እንዳሉት አባት ማለት ነው፡፡ ላይሞላ፣ ቀዳዳ ላይደፈን፣  ችግር ከልኩ ላያልፍ፣ አምላክ ያለው ላይቀር፣ እኛም ከተፈቀደልን ደረጃ ከፍ ላንል ስንቱን አደራ ኑሮ በላነው?

 

የጽሑፌ ማጠቃለያ የአለቃ ለማ ኃይሉ እና የአለቃ ተጠምቀ ታሪክ ነው፡፡ በትምህርት የኖሩት ሊቁ አለቃ ለማ ዋድላ ድላንታ ቅኔ ሲማሩ ኖረው ዐባይን ተሻግረው በዘመኑ የቅኔና የመጻሕፍት ማስመስከሪያ ከነበሩት መጀመሪያ ሞጣ ጊዮርጊስ ቀጥሎም ዲማ ጊዮርጊስ ይመጣሉ፡፡ ዲማ ጊዮርጊስም ከአለቃ ተጠምቀ ጋር ይገናኛሉ፡፡ አለቃ ተጠምቀ ዐይነስውር ናቸው፡፡ ብሉይ ኪዳንን ከነ አለቃ ለምለም በ6 ወር የወጡ ተጠምቀና ደቀመዝሙሩ አለቃ ለማ ወደ አዲስ አበባ ለመምጣት ይነሳሉ፡፡ ዘመኑ በኢትዮጵያ ታሪክ ክፉ ቀን የተባለው፣ ሰውም ከብቱም ያለቀበት እናት የልጇን ሥጋ ሳይቀር የበላችበት አስቸጋሪ ዘመን ነበር፡፡ በዚህ ዘመን ከዲማ መምህራቸውን እየመሩ ደብረ ሊባኖስ፣ ደብረ ብርሃን፣ ከዚያም አንኮበር መጨረሻም አዲስ አበባ መካነ ሥላሴ በማለት አብረዋቸው ኖረዋል፡፡ በወቅቱ ርሃቡ ከመጽናቱ የተነሣ የሚበላ ጠፍቶ በሦስት ቀንም፣ በአራት ቀንም የሚቀመስ ሲገኝ አብረው እየቀመሱ ምግባቸውን ቃለ እግዚአብሔር አድርገው ክፉውን ቀን አሳልፈዋል፡፡ በጊዜው ወጣት የነበሩት አለቃ ለማ በልቼ ወደ ማድርበት ልሂድ ሳይሉ ከመምህራቸው ጋር ተናንቀው ቀኗን አሳለፏት፡፡ በሚያልፍ ቀን፣ በሚያልፍ ችግር የቀለም አባታቸውን አልለወጧቸውም፡፡ እንዲያውም ለዚህ ደረጃ ያደረሰኝ ከእሳቸው ያገኘሁት በረከት ነው ይላሉ፡፡ ይህን የመንፈስ ልዕልና የሚያገኙና ሲያገኙትም የበረከት ምንጭነቱን ተረድተው የሚገጥማቸውን ጊዜያዊ ፈተና የሚወጡ ምንኛ የተባረኩ ናቸው!

/ምንጭ፡-

  • ሐዲስ ዓለማየሁ ትዝታ፣ 1985ዓ.ም፣ ሜጋ አሳታሚ ድርጅት፣
  • መጽሐፈ ትዝታ ዘአለቃ ለማ ኃይሉ ወልደ ታሪክ 1959ዓ.ም፣
  • ዲ/ን ያረጋል አበጋዝ፣ ከበረሃውያን ሕይወትና አንደበት ጥር 2003ዓ.ም፣
  • ባሕሩ ዘውዴ ዘመናዊ የኢትዮጵያ ታሪክ አ.አ.ዩኒቨርሲቲ 1989ዓ.ም፡፡/

የአትናቴዎስ ትምህርት ስለ መንፈስ ቅዱስ

የቤተ ክርስቲያን ታሪክ በዓለም መድረክ
አባ ጎርጎርዮስ የሸዋ ሊቀ ጳጳስ /M.A/

አትናቴዎስ ስለ መንፈስ ቅዱስም በተናገረበት ባስተማረበት አንቀጽ መንፈስ ቅዱስ እንደ አብ እንደ ወልድ ከአብ ከወልድ ጋር ፍጹም አካል መኾኑን፣ በባሕርይ በህልውና አንድ መኾኑን ይናገራል፡፡ ከቅድስት ሥላሴ ሦስተኛው አካል መንፈስ ቅዱስ ሕጹጽ   ፍጡር አይደለም፡፡ በብሉይ ኪዳን፣ በሐዲስ ኪዳን እንደ አብና እንደ ወልድ አምላካዊ ክብሩ ተነግሮለታልና፡፡ እነ አርዮስ እንደሚሉት መንፈስ ቅዱስ ፍጡር ቢኾን ኑሮ  የፍጡራን ሕይወት ባልኾነም ነበር፤ እንዴትስ የእግዚአብሔርን ምሥጢር ለማወቅ ቻለ? /1ኛቆሮ.2÷10/ ወልድ ከአብ ጋር አንድ ባሕርይ እንደሆነ መንፈስ ቅዱስም ከአብና ከወልድ ጋር አንድ ባሕርይ ነው፡፡ ሦስቱ አካላት /ገጻት/ ባንድ ባሕርይ ባንድ ህላዌ ይኖራሉ፤ አብ በወልድ ቃልነት ዓለምን ፈጠረ፡፡ ሦስቱ አካላት አንድ አምላክ ነው፡፡ በምሥጢረ ሥላሴ ወይም በሦስቱ መካከል ባዕድ ባሕርይ የለምና፡፡

ወልድ ከአብ እንደ ተወለደ መንፈስ ቅዱስም ከአብ የሠረጸ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ ለሐዋርያት ምሥጢር ገልጧል፤ ቋንቋ አናግሯል፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ከበዓለ ጰንጠቆስጤ ጀምሮ የሚመራ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ በአትናቴዎስ ትምህርት የባሕርይና የህላዌ እንዲሁም የአካላት ልዩነት፣ በምሥጢረ ሥላሴ የሚነገሩ ባሕርይ፣ ህላዌ፣ ከዊን  በእስክንድርያ ትምህርት ቤት ከአትናቴዎስ በኋላ ትክክለኛ ፍቻቸው እንደሚከተለው ነው፡፡ /ኡሲያ/ ህላዌ የሚለው ቃል በእስክንድርያ ትምህርት ቤት በነበረው የምሥጢረ ሥላሴ ትምህርት አካል ከባሕርይ ሳይለይ አንዱ ከሌላው ተለይቶ የሚታወቅበት ከዊን ማለት ነው፡፡ በአንጾኪያ ግን ይልቁንም ጳውሎስ ሳምሳጢና ተከታዮቹ «ህላዌ» የሚለውን ቃል በተሳሳተ አተረጓጐም በመተርጎም፤ ብዙዎቹን አሳስተዋል፡፡

ለምሳሌ «ዋሕደ ህላዌ» ማለት ሦስቱ አካላት አንዱ በአንዱ አድሮ የሚኖር ማለት ነው፤ ብለው ያስተምራሉ፡፡ እዚህ ላይ ወልድና መንፈስ ቅዱስ አካላዊና በከዊን የተለየ ህላዌ አልነበራቸውም ለማለት ጳውሎስ ሳምሳጢ ይመቸዋል፡፡ በሱ አስተሳሰብ ወልድና መንፈስ ቅዱስ በአብ ህልዋን ኹነው የሚያገለግሉ ዝርዋን እንጂ አካላውያን አይደሉምና፡፡ ስለዚህም በ260 ዓ.ም እሱን ለማውገዝ የተሰበሰቡ ሊቃውንት «ዋሕደ ህላዌ ምስለ አብ» ብሎ አትናቴዎስ ረትቶበታል፡፡ /አሞኡሲዮን ቶ፣ -ትረ/ ይህም የአትናቴዎስ አባባል ከጳውሎስ ሳምሳጢ ጋር ዝምድና የለውም፡፡ «ዋሕደ ባሕርይ» በማለት የባሕርዩን አንድነት «ምስለ አብ» አብ ማለት የአካልን ልዩነት ያሳያልና «ዋሕደ ህላዌ ምስለ አብ» በአንቀጸ ሃይማኖት «ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ» የምንለው ነው፡፡ እንግዲህ ህላዌ የሚለው ቃል፤ በምሥጢረ ሥላሴ አንዱ አካል በሌላው አድሮ ወይም ጥገኛ ኹኖ የማይኖር፣ ከሥላሴ አንዱም አንዱ፣ እያንዳንዱ አካል በአካሉ፣ በመልኩ፣ በገጹ ፍጹም መኾኑን ያሳያል፣ ያመለክታል፡፡ «ህቡረ ህላዌ ምስለ አበመለኮቱ፣ ኅቡረ ህላዌ ምስሌነ በትስብእቱ» /ተረፈ ቄርሎስ/
በሌላም ቦታ «ህላዌ» ከግብርና ከአካል ስም ጋር ተጣምሮ ይገኛል፤ ለአብ የወላዲነት ለወልድ የተወላዲነት፣ ለመንፈስ ቅዱስ የሠራጺነት ስሙ ነው፡፡ «እስመ አበዊነ ስመይዎን በዝንቱ ገጸ መካን ለህላዌያት አካላተ፤ አትናቴዎስኒ ረሰየ ህላዌ አሐደ አካለ ዘእግዚአብሔር ቃል ዘተሠገወ» እንዲል፡፡
ዳግመኛም ህላዌ አካልና ባሕርይ አንድ ኹነው የቆሙበት አስተጋባኢ ስም ስለሆነ ለአካልም ለባሕርይም ይነገራል፡፡ በአንቀጸ ተዋሕዶ ማለት የሦስቱን አንድነት በምንናገርበት ጊዜ አሐዱ ህላዌ እንላለን፡፡ መውለድና ማሥረጽ፣ መወለድና መሥረጽ በዚያው ባንድ ባሕርይ ውስጥ ነውና፡፡

 

ስለዚህ በምሥጢረ ሥላሴ ባሕርይ አይከፈልም፡፡ አካል አይቀላቀልምና፡፡ ህላዌ ግን ለአካልም ለባሕርይም መነገሩን ገልጠናል፡፡ ባሕርይ ምንጊዜም ቢኾን ለአካል አይነገርም፤ አካልም ለባሕርይ ስም አይኾነውም፣ አለዚያ ግን ባሕርይን መክፈል ስምና ግብርን ማፋለስ ይኾናል፡፡ ወላዲ ባሕርይ፣ ተወላዲ ባሕርይ፣ ሠራጺ ባሕርይ የማይባለውም ስለዚህ ነው፡፡ ከተባለ ግን ሦስት መለኮት፣ ዘጠኝ አካላት ወደ ማለት ይሸነሸናል፤ የምሥጢረ ሥላሴው የግብር ስም ለምሥጢረ ተዋሕዶው የባሕርይ ስም አይሰጥም፡፡ የሦስቱም አካላት መለኮት ወይም ባሕርይ አንድ ነው፡፡ «ሠለስቱ ገጻተ አሐዱ አምላክ» ብሎ ለማመንና ለማሳመን ይህን ኹሉ ጠንቅቆ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ከዚህ በላይ እንዳየነው በእስክንድርያ የትርጓሜ ትምህርት ቤት እነ አትናቴዎስ «ህላዌን» /ኡሲያን/ ለአካልም ለባሕርይም ሰጥተው ይናገራል፡፡ /ኩነት/ ከዊን ግን ለአካል ብቻ ነው /ኢስታሲስ/ በአንጾኪያ ግን «ህላዌን» /አሲያን/ ለባሕርይ ብቻ /ኩነትን/ ከዊንን /ኢስታሲስን/ ለአካል ብቻ ሰጥተው ይናገራሉ፤ በዚህኛው ልዩነት የለም፡፡

«ጾምን ቀድሱ» /ኢዮ.2-15/

ጾም


የሰውን ልጆች የሚወደውና ስለ እነርሱም ብሎ በገነት ያሉትን ዛፎች ሁሉ የፈጠረው እግዚአብሔር በገነት ካሉት ዛፎች መካከል አንዲቱን እንዳይበላ አዳምን አዘዘው፡፡ ይኽ አዳምን ለመጫን፣ ኃይሉን በእርሱ ላይ ለማሳየት ሳይሆን ሰው በመጾም /ባለመብላት/ እና በመታዘዝ ለሚወደው አምላኩ ፍቅሩን ይገልጽ ዘንድ ነው፡፡

 

ከአዳም ድቀት በኋላም በየዘመናቱ የተነሡ መንፈሳውያን ሰዎች እና ሕዝቦች በየግላቸው እንዲሁም በአንድነት /በጋራ/ ሲጾሙ፣ በጾማቸውም ሲጠቀሙ ኖረዋል /ሕዝበ እስራኤል ሙሴ፣ ኤልያስ፣ የነነዌ ሰዎች. . ./፡፡

 

ጌታችንም፣ በእደ ዮሐንስ ከተጠመቀ በኋላ፤ የማስተማር አገልግሎቱን ከመጀመሩ በፊት ጾሟል፡፡ ከዚህ ክርስቲያናዊ ትውፊት በመነሣትም ሐዋርያትና ደቀመዛሙርቱም እንዲሁ አገልግሎታቸውን ከመጀመራቸው በፊትና በአገልግሎታቸው ወቅት ይጾሙ ነበር፡፡

ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርቲያናችን በትውፊት ያገኘነውን፣ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስተማሩንን ጠቃሚ ሥርዓቶችን አውርሳናለች፡፡ ከነዚህ የከበሩ ሀብታት መካከል ሥርዓተ ጾም አንዱ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት የአዋጅ እና የግል /የፈቃድ/ አጽዋማት አሉን፡፡ ቤተክርስቲያናችን መንፈሳዊት ዓለም እንደመሆኗም የጾም አስተምህሮዋ «ለጾም አድሉ» የሚል ነው፡፡ ምእመናንም የዓመቱ ብዙውን ቀናት በዚህ በተቀደሰ መንፈሳዊ ምግባር ያሳልፋሉ፡፡

የጾም ጽንሰ ሐሳብ

1. መጾም ማለት በፈቃድ ለተወሰነ ጊዜ ከምግብ መከልከልና መራብ ማለት ነው፡፡ ጌታችን በጾመ ጊዜ ተርቧል /ማቴ.4-2/፡፡ ሐዋርያትም በጾማቸው ጊዜ ተርበዋል /ሐዋ.10-1/፡፡ ከዚህም በተጨማሪ የተወሰነ ጊዜ /ሰዓታትን፣ ቀናትን. . . / ካሳለፍን በኋላም ቢሆን ሥጋን የሚያለመልሙ ምግቦች አንመገብም፡፡ ከአባቶቻችን እንደተማርነው ከእንስሳትና ከእንሰሳት ውጤቶች፣ እንዲሁም ከሌሎች ለሥጋ እጅግ ከሚመቹ ምግቦች እንርቃለን እንጂ፤

ዳንኤል:-«በዚያም ወራት እኔ ዳንኤል ሦስት ሳምንት ሳዝን ነበርሁ፡፡ ማለፊያ እንጀራ አልበላሁም፣ ሥጋና ጠጅም በአፌ አልገባም፡፡ ሦስቱም ሳምንት እስኪፈጸም ድረስ ዘይት አልተቀባሁም»/ዳን.10-3/፡፡

ዳዊት:- «ሥጋዬ ቅባት በማጣት ከሳ፣ ጉልበቶቼም በጾም ደከሙ»/መዝ.108-24/፡፡

ይኽ እንዳለ ሆኖ ጾም ማለት ከምግብ፣ ከመጠጥና ከምቾት መታቀብ ብቻ ማለት አይደለም፡፡ የግዴታ አንድያ ልጁን ለእኛ እንዲሞት ለሰጠው ለእምላካችን ያለንን ፍቅር የምንገልጥበት መንገድ መሆንም አለበት፡፡ ስለዚህ የጾም ወቅት የበለጠ ስለ እግዚአብሔር የሚያስቡበትና በፍቅሩ የሚመሩበት፤ ወደ እርሱ የሚቀርቡበት ወቅት መሆን አለበት፡፡ የምንጾመው «ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ለእኔ ሞቶልኛል፤ እኔም ቀኑን ሙሉ ፈቃዴን ለእርሱ እገድላለሁ» በሚል አሳብ ነው፡፡

ከዚህም በላይ ጾም ከኃጢአት መራቅን ስለ ቀደሙ በደሎች ንስሓ መግባትን እና በመንፈሳዊነት ማደግን ያካተተ መሆን አለበት፡፡

2. እግዚአብሔር እኛን የፈጠረን ሥጋችንና ነፍሳችን መንፈሳዊ ሆነው በአንድነት ለእርሱ እንዲገዙና ፈቃዱን እንዲፈጽሙ ነው፡፡ መንፈሳዊ መሆን ማለት በመንፈስ ቅዱስ መመራት ማለት ነው፡፡ ነገር ግን የሥጋችንን ፈቃድ በናረ ጊዜ ነፍሳችን ለመንፈስ ቅዱስ /ለእግዚአብሔር/ ፈቃድ ሳይሆን ለሥጋ ፈቃድ ትገዛለች፡፡ እንደ ሥጋውያን መመላለስ ኃጢአት መሥራት እንጀምራለን፡፡ ጾም ይህንን ለማስቀረት ሥጋችንን የምናደክምበትና ፈቃድ እንዳያይል የምናደርግበት መንገድ ነው፡፡

3. የጾም ወቅት የንስሓ እና የሐዘን ወቅት ብቻ ሳይሆን የደስታ ወቅትም ነው፡፡ ምክንያቱም የጾም ወቅት ነፍስን ከሚያስጨንቅ የሥጋ ፈቃድ የምንላቀቅበትና መንፈሳዊ ድል የምናገኝበት እንዲሁም የእግዚአብሔርን ፍቅር የምናጣጥምበት ወቅት ነው፡፡

በነቢዩ ኢዩኤል «የተቀደሰ ጾም» ተብሎ የተገለጠው እንዲህ ያለው ጾም ነው፡፡ /ኢዩ.2.15/፡፡

ሥርዓተ ጾም

ይኽንን በመረዳት ሁላችንም አዘውትረን መጾም አለብን፡፡ በእርግጥም ብዙ ክርስቲያኖች የዓመቱን አብዛኛውን ጊዜ በጾም ያሳልፋሉ፡፡ እናት ቤተክርስቲያንም በመንፈሳዊ ዝለት ይኽንን በሚገባ ሳናደርገው እንዳንቀር በዓመቱ ውስጥ በዐዋጅ የሚጾሙ አጽዋማትን አዘጋጅታለች፡፡ እነዚህም ጾመ ነቢያት፣ ጾመ ጋድ፣ ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ድኀነት /ረቡዕና አርብ/፣ጾመ ሐዋርያት፣ጾመ ፍልሰታ ናቸው፡፡

በእነዚህ የአዋጅ አጽዋማት ወቅት በብሉይ ኪዳን እና በሐዲስ ኪዳን የተደረጉ የተለያዩ ነገሮች ስለሚታሰቡባቸው ይኽም ለመንፈሳዊ ተመስጦ ስለሚጠቅም ጥቅማቸው እጥፍ ድርብ ይሆናል፡፡

ጾመ ነቢያት

ከላይ በተናገርነው መሠረት ከምንጾማቸው የአዋጅ አጽዋማት አንዱ በየዓመቱ ከኅዳር 15 እስከ ታኅሣሥ 28 /በዘመነ ዮሐንስ እስከ ታኅሣሥ 27/ ድረስ የምንጾመው ጾመ ነቢያት ነው፡፡ ይኽን ጾም የምንጾመው ነቢያት በየዘመናቸው ስለ መሲህ መመጣት በናፍቆት ይጾሙ ይጸልዩ ስለነበር የእነርሱን አርአያ ተከትለን ነው፡፡ የክርስቶስን ልደት ከማክበራችን ቀደም ብለን ይኽን ጾም እንድንጾምም ቅድስት ቤተክርስቲያን ወስናለች፡፡ የተቀደሰ ጾም ለመጾም፣ ጾመንም ልደተ እግዚእን ለማክበር እንትጋ፡፡

አምላከ ነቢያት አይለየን፡