«የአሮጊቷ ሣራ» ወለደች ዐዋጅ ተሐድሶ ዘመቻ የጥፋት ፈትል እንደማጠንጠኛ

በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት በብሉያትና በሐዲሳቱም የምትነሣው ሣራ አበ ብዙኃን ሥርወ ሃይማኖት የምንለው የአብርሃም ሚስት ነች፡፡ እግዚአብሔር ለአብርሃም የብዙዎች አባት እንዲሆን ቃል ኪዳን ሳይገባለት በፊት፣ በመካንነት ታዝን፣ ተስፋም አጥታ ትተክዝ በነበረችበት ጊዜ ሦራ ትባል ነበር፡፡

ሦራ ሙቀት ልምላሜ ከተለያት በኋላ ልጅ እንደምትወልድ ከአብርሃም በኩል እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ከገባላት፣ ተስፋም ከተሰጣት በኋላ ሣራ ተብላለች፡፡ እግዚአብሔርም ስለእርሷ ለአብርሃም «የሚስትህን የሦራን ስም ሦራ ብለህ አትጥራ፤ ስምዋ ሣራ ይሆናል እንጂ፤ እባርካታለሁ፤ ደግሞም ከእርሷ ልጅ እሰጥሃለሁ፤ እባርካትማለሁ፤ የአሕዛብ እናት ትሆናለች፤ የአሕዛብ ነገሥታት ከእርሷ ይወጣሉ» በማለት ተናገረው /ዘፍ. 17፥15/፡፡

ሣራ ሦራ ተብላ ትጠራ በነበረበት፣ ያለተስፋ በኖረችበት የቀደመው ዘመኗ ለአብርሃም ልጅ አልወለደችለትም ነበር፡፡ ሦራ ዘር ማጣት ታላቅ ሐዘን በሆነበት በዚያ ዘመን፣ መካንነት ያስንቅ በነበረበት በዚያን ጊዜ አብራም ከሌላ ይወልድ ዘንድ አዘነችለት፡፡ አብራም አጋር ወደ ተባለችው ግብጻዊት ባሪያዋ ይደርስ ዘንድ «እነሆ እንዳልወልድ እግዚአብሔር ዘጋኝ ምናልባት ከእርሷ በልጅ እታነጽ እንደ ሆነ ወደ እርሷ ግባ» አለችው፡፡ /ዘፍ.16፥2/ በትሑቷ ሦራ ምክር አጋር ከአብርሃም በፀነሰችበት ወራት ሦራን አሳዘነቻት፤ አጋርም ተመካች፤ እመቤት የነበረችውን ሦራ ስለመካንነቷ በዓይኗ አቃለለቻት፡፡ ይህ ለሦራ በእግዚአብሔር እና በባሏ በአብራም ፊት ያዘነችበት ሰቆቃዋ ነው፡፡ ሦራም ከሐዘኗ ጽናት የተነሣ አብራምን እንዲህ አለችው «መገፋቴ በአንተ ላይ ይሁን እኔ ባሪያዬን በብብትህ ሰጠሁህ፤ እንዳረገዘችም ባየች ጊዜ እኔን በዓይኗ አቃለለችኝ፤ እግዚአብሔር በእኔና በአንተ መካከል ይፍረድ» አለችው፡፡ በአብራም ፍርድም ሦራ ባሪያዋን አጋርን በመቅጣቷ አጋር ኮበለለች፡፡

እንግዲህ ከላይ አስቀድመን የጠቀስነው ለአብርሃም የተገባው ቃል ኪዳን የተሰጠው ሦራና አብራም በዚህ ሐዘን ውስጥ በነበሩበት ጊዜ ነው፡፡ ያዘነችው ሦራ ከቃል ኪዳኑ በኋላ የብዙኃን እናት ልትሆን ሣራ ተብላ እርሱም የብዙዎች አባት ሊሆን አብርሃም ተብሎ የተስፋው ቃል ተነገረው «በእውነት ሚስትህ ሣራ ወንድ ልጅን ትወልድልሃለች ስሙንም ይስሐቅ ብለህ ትጠራዋለህ ከእርሱ በኋላ ለዘሩ የዘላለም ቃልኪዳን እንዲሆን ቃል ኪዳኔን ከእርሱ ጋር አቆማለሁ» /ዘፍ.17፥19/፡፡

እግዚአብሔር ለአብርሃም ሣራ እንደምትወልድ የነገርውን የተስፋ ቃል በቤቱ በእንግድነት ተገኝቶ አጸና፡፡ «የዛሬ ዓመት እንደ ዛሬው ጊዜ ወደ አንተ በእውነት እመለሳለሁ ሚስትህ ሣራም ልጅን ታገኛለች፡፡»/ዘፍ.18፥10/ አለው፡፡ ሁል ጊዜም ቃሉ የሚታመን እግዚአብሔር ይመስገንና እንደተባለው ሆነ «እግዚአብሔርም እንደተናገረው ሣራን አሰበ እግዚአብሔርም እንደተናገረው ለሣራ አደረገላት ሣራም ፀነሰች እግዚአብሔርም በተናገረው ወራት ለአብርሃም በእርጅናው ወንድ ልጅን ወለደችለት አብርሃም ሣራ የወለደችለትን የልጁን ስም ይስሐቅ ብሎ ጠራው» /ዘፍ.21፥1/ «ሣራም እግዚአብሔር ሳቅ /ደስታ አድርጎልኛል ይህንንም የሚሰማ ሁሉ በእኔ ምክንያት ይስቃል አለች ደግሞም ሣራ ልጆችን እንድታጠባ ለአብርሃም ማን በነገረው በእርጅናው ልጅን ወልጄለታለሁና /ዘፍ. 21፥7/፡፡

እንግዲህ መካኒቱ ሣራ ሙቀት ልምላሜ ከተለያት በኋላ በጨዋነት ወልዳ ለአብርሃም ለዘላለም የገባው ቃል ኪዳን የሚፈጸምበትን ዘር ይስሐቅን አሳድጋለች፡፡ በቃል ኪዳን፣ በተስፋ የተወለደው ይስሐቅ ታላቅ ነውና «የዚህች ባሪያ /የአጋር/ ልጅ ከልጄ ከይስሐቅ ጋር አይወርስም» አለች፡፡ እግዚአብሔርም ቃሏን ተቀብሎ ለአብርሃም «ሣራም የምትነግርህን ቃል ሁሉ ስማ በይስሐቅ ዘር ይጠራልሃልና…» አለው /ዘፍ.21፥1-12/፡፡

እንዲህ በእግዚአብሔር የተስፋ ቃል የከበረችው ሣራ በብሉያት ብቻ ሳይሆን በሐዲሳትም ለተለያዩ ጉዳዮች እንደ አርአያና ምሳሌ ስትጠቀስ እናነባለን፡፡ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ ሚስቶችን ሲመክር በመልካም ትሑት ሰብእናዋ አርአያ የምትሆን አድርጎ የጠቀሳት ሣራን ነው «ጠጉርን በመሸረብ፣ ወርቅን በማንጠልጠል፣ ወይም ልብስን በመጎናጸፍ በውጪ በሆነ ሽልማት» ሳይሆን «በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ» ተጎናጽፋ ውስጧን ያስጌጠች ብፅዕት ሚስት መሆኗን መስክሯል፡፡ «ሣራ ለአብርሃም ጌታዬ ብላ እየጠራችው ታዘዘችለት፤ እናንተም ከሚያስደነግጥ ነገር አንዳች እንኳ ሳትፈሩ መልካም ብታደርጉ ልጆችዋ ናችሁ፡፡» /1ጴጥ. 3፥3-6/ ብሏል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ የክርስቶስ የማዳኑ የምስራች ከታወጀላቸው በኋላ ሕገ ኦሪትን ካልጠበቅን አንድንም የሚሉ ቢጽሐሳውያንን ቃል ሰምተው ያመኑ የገላትያን ሰዎች በገሰጸበት መልእክቱ ሣራን የሕገ ወንጌል ምሳሌ አድርጎ አቅርቧታል፡፡ በአንጻሩ ባሪያዋን አጋርን የሕገ ኦሪት ምሳሌ አድርጎ አቅርቧል /ገላ.4፥21/፡፡

የሣራን ሕይወት በዚህ ጽሑፍ ያነሣንበትንም መሠረታዊ ምክንያትም ይህንን የቅዱስ ጳውሎስን ምሳሌያዊ መልእክት ተንተርሰው ያለአገባቡ እየጠቀሱ የቤተ ክርስቲያናን ልጆች ምእመናንን ግራ ስለሚያጋቡ የተሐድሶ መናፍቃንና ተሐድሶአዊ ትምህርት ስለሚያስተምሩ ሰዎች ሐሳብ ለማንሣት ነው፡፡ በቅድሚያ የቅዱስ ጳውሎስ የመልእክቱን ሐሳብ በአጭሩ እናብራራና፤ ተሐድሶ የዘመቻ ማወራረጃ አድርጎ ስለሚጠቀምበት ጥራዝ ነጠቅ ቃልና አስተሳሰብ ደግሞ ቀጥሎ እናመጣለን፡፡ ሐዋርያው ስለዚህ ነገር ሲናገር የሚከተለውን ብሏል፡፡

«እናንተ ከሕግ በታች ልትኖሩ የምትወዱ ሕጉን አትሰሙምን ? እስኪ ንገሩኝ፤ አንዱ ከባሪያዪቱ አንዱ       ከጨዋዪቱ የሆኑ ሁለት ልጆች ለአብርሃም እንደነበሩት ተጽፏልና፤ ነገር ግን የባሪያዪቱ ልጅ እንደ ሥጋ ተወልዷል፤ የጨዋዪቱ ግን በተስፋው ቃል ተወልዷል፤ ይህም ነገር ምሳሌ ነው እነዚህ ሴቶች እንደ ሁለቱ ኪዳናት ናቸውና፤ ከደብረ ሲና የሆነችው አንዲቱ ለባርነት ልጆችን ትወልዳለች፤ እርሷም አጋር ናት፤ ይህቺም አጋር በዓረብ ምድር ያለችው ደብረ ሲና ናት፤ አሁንም ያለችውን ኢየሩሳሌምን ትመስላለች፤ ከልጆቿ ጋር በባርነት ናትና፤ ላይኛዪቱ ኢየሩሳሌም ግን በነጻነት የምትኖር ናት፤ እርሷም እናታችን ናት… ስለዚህ ወንድሞች ሆይ የጨዋዪቱ ልጆች ነን እንጂ የባሪያዪቱ አይደለንም» /ገላ.4፥21-31/፡፡
በገላትያ መልእክቱ ቅዱስ ጳውሎስ ትኩረት የሰጠው ጉዳይ «የክርስቶስን ሐዋርያት እንዲመስሉ ራሳቸውን እየለወጡ ውሸተኞች ሐዋርያትና ተንኮለኞች ሠራተኞች» ስለነበሩት ከአይሁድ ወገን የሆኑ ካልተገረዛችሁ፣ ሕገ ኦሪትንም ካልፈጸማችሁ አትድኑም እያሉ የሚያስተምሩ ሰዎች ጉዳይ ነው፡፡ እነዚህ ኦሪታዊ ሁኑ የሚሉ ሰዎችን ትምህርት እየሰሙ የወንጌልን ቃል ቸል ያሉት የገላትያን ሰዎች በግልጽ «እግዚአብሔርን ስታውቁ፣ ይልቅስ በእግዚአብሔር ስትታወቁ እንደገና ወደ ደካማ ወደሚናቅም ወደ መጀመሪያ ትምህርት እንዴት ትመለሳላችሁ? እንደገና ባሪያዎች ሆናችሁ ዳግመኛ ለዚያ ልትገዙ ትወዳላችሁን ? ቀንና ወርን ዘመንንም ዓመትንም በጥንቃቄ ትጠብቃላችሁ…» ይላቸዋል፡፡ /ገላ.4፥9-11/
የሐዋርያው ዋነኛ ጉዳይ ሕገ ኦሪት ይጠበቅ አይጠበቅ በመሆኑም ነው «እናንተ ከሕግ በታች ልትኖሩ የምትወዱ ሕጉን አትሰሙምን ?» ያላቸው /ገላ. 1፥21/፡፡ ምክንያቱም ያመኑትን ሁሉ በደሙ የዋጀ የኢየሱስ ክርስቶስ የምስራች ወንጌል ከተነገረች በኋላ ዳግመኛ ወደ ኋላ ተመልሶ ቀንና ወርን ዘመንንም እየቆጠሩ መሥዋዕተ ኦሪትን ለማቅረብ፣ ግዝረትን አበክሮ ለመጠበቅ፣ ያንንም ካልፈጸማችሁ አትድኑም ወደሚል ትምህርት መመለስ ያሳፍራልና፡፡
ስለዚህ እናንተ በኦሪት እንኑር የምትሉ ሆይ! በኦሪት የተነገረውን ምሳሌ አንብቡ ብሎ የሣራን እና የአጋርን ምሳሌነት ያነሣል፡፡ በኦሪት አብርሃም አስቀድመን እንዳየነው ጨዋይቱ ከተባለችው ከእመቤቲቱ ሣራ ይስሐቅን፣ ከባሪያይቱ ከአጋር ደግሞ እስማኤልን ወልዷል፡፡ የሁለቱ ልደት ግን ለየቅል መሆኑን ይነግራቸዋል፡፡ ከባሪያዪቱ የተወለደው አጋር ሙቀት ልምላሜ እያላት ተወልዷልና፤ ከእመቤቲቱ የተወለደው ግን ሙቀት ልምላሜ ከተለያት በዘጠና ዓመቷ/ ከእግዚአብሔር ብቻ በተሰጠው ተስፋ ተአምራትም ተወልዷልና፡፡ እነዚህ ሁለቱ ሴቶች የሕገ ኦሪትና የሕገ ወንጌል ምሳሌ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም በቃሉ «ይህም ነገር ምሳሌ ነው» እንዳለ /ገላ. 4፥24/፡፡ አጋር ኦሪትን ደብረ ሲናን አንድ ወገን ያደርጋል፤ ሣራን፣ ወንጌልን ሰማያዊቱ ኢየሩሳሌምን ደግሞ አንድ ወገን እያደረገ እያነጻጸረ ተናግሯል፡፡
አንዲቱ /ኦሪት/ አምሳል መርገፍ ሆና በደብረ ሲና ተሠርታለችና፤ ደብረ ሲናም ከኢየሩሳሌም ስትነጻጸር በምዕራብ ያለች ተራራ ናትና፤ ስለዚህ ይህች ምድራዊት የምትሆን አምሳል መርገፍ አማናዊት ከምትሆን ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ጋር ስትነጻጸር ዝቅ ያለች ናትና «ወትትቀነይ ምስለ ደቂቃ» አምሳል መርገፍ በመሆን ከልጆቿ ጋር ትገዛለች፡፡ ላዕላዊት የምትሆን ኢየሩሳሌም ግን ከመገዛት ነጻ ናት ብሎ «ወይእቲ እምነ፤ እርስዋም እናታችን ናት» ይላል፡፡ ይቺም እናታችን ሣራ ምሳሌዋ የምትሆን ወንጌል ናት፡፡
ስለዚህ ከሣራ የተወለደው ተስፋውን ወራሽ እንደሆነ ሁሉ እኛም ከወንጌል የተወለድን ክርስቶሳውያን በይስሐቅ አምሳል እንደይስሐቅ ተስፋውን መውረስ የሚገባን የነጻነት ልጆች ነን ማለቱ እንደሆነ ሊቃውንቱ ያስተምራሉ፡፡ የባሪያዪቱ ልጅ ከእመቤት ልጅ ጋር ተካክሎ ርስት አይወርስምና በበግና በፍየሎች ደም ምሳሌያዊ ወይም ጥላ   አገልግሎት በምትሰጥ ገረድ /ሞግዚት/ የተባለች የኦሪት ልጆች አይደለንም፡፡ ክርስቲያኖች በእግዚአብሔር ልጅ ሥጋና ደም ነጻ በምታወጣ አዲስ ኪዳን የወንጌል ልጆች ነንና፡፡
ሐዋርያው ይህንን ሁሉ ያለው ካልተገረዛችሁ አትድኑም የሚለውን የቢጽ ሐሳውያንን ትምህርት በመኮነን ሲሆን ይህንንም በግልጽ «በክርስቶስ ኢየሱስ ሆኖ በፍቅር የሚሠራ እምነት እንጂ መገረዝ ቢሆን ወይም አለመገረዝ አይጠቅምምና /ገላ. 5፥6/ ይላል፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ ሆኖ በፍቅር የሚሠራ ያለው ሕይወትም ፍትወተ ሥጋን አሸንፎ በመንፈሳዊ ተጋድሎ የበቁ ሆኖ በመንፈስ መራመድን ነው፡፡ ይህ ሣራ በተመሰለችባት ሕገ ወንገል ውስጥ የተጠራንበት የመታዘዝ ሕይወት ነው፡፡ ሐዋርያውም ለገላትያ ሰዎች ይህንኑ ተርጉሞ ሲናገር «የክርስቶስ ኢየሱስም የሆኑት ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞቱ ጋር ሰቀሉ» /ገላ. 5፥24/ አለን፡፡ ስለዚህ የቤተክርስቲያን ወገኖች ሁሉ ሥጋን ከክፉ መሻቱና ከምኞት ጋር የሰቀሉ መንፈሳውያን፣ በፍቅር የእግዚብሔርን ትዕዛዝ የሚፈጽመው የጨዋይቱ /የእመቤቲቱ/ የሣራ ልጆች ናቸው፤ እንጂ ሥጋዊ ሥርዓት፣ መርገፍ፣ ጥላ በሆነው ብሉይ ኪዳን ውስጥ የመገረዝ አለመገረዝ ጣጣን የሚሰብኩ፣ የሚሰበኩ በሥጋ ልማድ የወለደችው የባሪያዪቱ የአጋር ልጆች አይደሉም፡፡
እንግዲህ በነጻነት የምትመራውን ላይኛይቱን ኢየሩሳሌምን የመረጡ ክርስቶሳውያን ለ2ሺሕ ዘመናት ያህል ክርስቶስን በመስበክ በስሙም ክርስቲያን ተብለን ስንጠራ ኖረናል፡፡ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች ገና አስቀድሞ በ34 ዓ.ም «ኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ አምናለሁ፡፡ ካለው ጃንደረባው ጀምረው ሠልጥና ከነበረችው ባሪያይቱ አጋር ይልቅ በተስፋው ሥርዓት የወለደችውን እመቤቲቱን ሣራ መርጠው እስከዚህ ዘመን ድረስ ኖረዋል፡፡
ከየካቲት ወር 1990 ዓ.ም ጀምሮ ግን «ተሐድሶ» በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ በይፋ በጀመረው ዘመቻ ውስጥ የዘመቻው አዋጅ ማጠንጠኛ «አሮጊቷ ሣራ እኔ /እኛን/ ወለደች» የሚለው ቃል ነው፡፡ «የተሐድሶ መነኮሳት ኅብረት» የተባለው ቡድን በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ሆኖ ከቤተ ክርስቲያን ማዕድ እየተቋደሰ ነገር ግን በመሠሪነት ለመናፍቃን ተላላኪ ሆኖ የቆየ ሲሆን በየካቲት ወር 1990 ግን በአዲስ አበባ ከተማ በኢግዚብሽን ማዕከል በፕሮቴስታንቶች ተደራጅቶ በተዘጋጀው «ጉባኤ» በይፋ ራሱን ለይቶ የ«ተሐድሶ» ጥሪ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ላይ እንዲደረግ ሲያውጅ ተገኝቷል፡፡ /ይህንን ለማጋለጥ የወጣወን ቪዲዮ ፊልም ወይም ቪሲዲ ይመልከቱ/ በዚህ አዋጅ በጉልህ የሚስማው ድምፅ ከላይ የተጠቀሰው «አሮጊቷ ሣራ እኔን ወለደች» የሚለው ንግግር ነበር፡፡ ይህንን ቃል ደጋግሞ ሲያስተጋባ የነበረው አባ ዮናስ /በለጠ/ የተባለው «መነኩሴ» «ወንጌልን ለመስበክ ተሾምኩ፤… አሮጊቷ ሣራ ወለደች፤ አሮጊቷ ሣራ እኔን ወለደች፣ ዘውዱን ወለደች፣ ፍስሐን ወለደች፣ ገብረ ክርስቶስን ወለደች… ይህ ትውልድ የኢያሪኮን ግንብ ያፈርሳል…» ወዘተ እያለ አብረውት ለጥፋት የተሰለፉ ከሃዲ መነኮሳትን እየጠቀሰ ፎክሯል፡፡
በእነ አባ ዮናስ አዋጅ ውስጥ ያለው ግልጽ መልእክት ግን በሁለት መልኩ የሚታይ ወይም ሊተረጎም የሚችል ነው፡፡
1.    ቤተክርስቲያንን በእርጅና ዘመኗ ከወለደችው ከቅድስት ሣራ ጋር በማነጻጸር ራሳቸውን የዚህችው ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን አድርገው በማቅረብ ከዚህች ቤተክርስቲያንም አካል የተገኙ መሆናቸውን በመግለጥ የቤተክርስቲያን አስተምህሮ እነርሱ የሚሉት እንደሆነ አድርገው ለማደናበር ነው፡፡
2.    ሌላው የድፍረት መልእክት ደግሞ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን በባሪያይቱ በአጋር ምሳሌ ልትጠቀስ የምትችል ኦሪታዊት፤ የጨዋይቱ የተባለች የሣራ የተስፋው ዘር ቅሪት የሌለባት፣ የወንጌል ብርሃን ያልበራባት፤ ክርስቶስን የማታውቅ፣ ጌትነቱንም የማታምን አድርገው አቅርበዋታል፡፡ ራሳቸውንም ለኢትዮጵያ ሕዝብ ወንጌልን ለማድረስ የተሾሙ በኩራት አድርገው አቅርበዋል፡፡
የመጀመሪያውን ትርጉም ወይም መልእክት በማጉላትም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስም የዚህን የ«ተሐድሶ» መሠሪ አካሔድ በውል በመረዳት አውግዞ በመለየትና ውግዘት በማስተላለፍ ለ2ሺሕ ዘመናት ወንጌልን ስትሰብክ የነበረች ቤተ ክርስቲያንን ልዕልናና ክብር አጉድፎ በወንጌል ሰባኪነት ስም በማጭበርበር ፕሮቴስታንታዊ ኑፋቄ ለመዝራት ተሐድሶ እያደባ መሆኑን አጋልጧል፡፡ ጠቅላይ ቤተክህነት ከሰጠው ሰፊ መግለጫ ውስጥ ይህን የተመለከተውን በአጭሩ እንደሚከተለው እናስታውስ፡፡

 

«አሮጊቷ ሣራ ወለደች» የሚል ኃይለ ቃል መናገራቸው ተዘግቧል፤ መናፍቃኑ ይህን የተናገሩት የእነሱን ከጥንታዊቷ ቤተ ክርስቲያናችን አፈንግጦ መውጣት የዘጠና ዓመት እድሜ ከነበራት እና ከቅድስት ሣራ ከተወለደው ከይስሐቅ ልደት ጋር ለማነጻጸር በመፈለግ መሆኑ ግልጽ ነው፡፡


የይስሐቅ እናት ቅድስት ሣራ በመሠረቱ እናትና አባቱን የሚያከብርና የሚያስከብር እንጂ የሚያዋርድ፣ እናትና አባቱን የሚያስመሰግን እንጂ ሰድቦ የሚያሰድብ፣ በእናትና አባቱ እግር የሚተካ እንጂ እናትና አባቱን የሚክድ፣ በወላጆቹ የተመረቀ እንጂ የተረገመ ልጅ እናት አይደለችም፡፡


በቅድስት ሣራ አምሳል የተጠቀሰችው ጥንታዊቷ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም እንዲሁ እናቱን ለመሸጥና ለመለወጥ የሚያስማማ፣ እናቱን ሲሰድብና ሲነቅፍ ሐፍረት የማይሰማው ርጉም ልጅ እናት አይደለችም፤ ቤተ ክርስቲያናችን እንዲህ ያለ ልጅ አልወለደችም፣ አትወልድምም፡፡


ጠላትና አረም ሳይዘሩት ይበቅላል እንደሚባለው፣ በአንድ የስንዴ ማሳ ላይ የበቀለ አረም ቢኖር ያ አረም ሳይዘራ የበቀለ መሆኑን ማረጋገጥ አስቸጋሪ እንደማይሆን ሁሉ እነዚህ መናፍቃንም በቤተ ክርስቲያናችን የስንዴ ማሳ ላይ ሳይዘሩ የበቀሉ ጠላቶች እንደሆኑ መገንዘብ አስቸጋሪ አይሆንም፡፡ በምሳሌ ዘር እንደተጠቀሰው /ማቴ.13፥24-30/ በንጹሕ ስንዴ ማሳ ላይ ጠላት የዘራው ክርዳድ ሊበቅል እንደሚችልም ታውቋል፡፡ እነዚህ መናፍቃንም የጠላት እንጂ የቤተ ክርስቲያናችን አበው ተክል ባለመሆናቸው ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንደ ተወለዱ አድርገው ራሳቸውን ከማስተዋወቅ ይልቅ የማን ልጆች እንደሆኑ ቢጠይቁ ዕውነቱን ለማወቅ በቻሉ ነበር፡፡


አሁንም ቢሆን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለጢሞቴዎስ በጻፈው ሁለተኛ መልእክቱ «በኋላ ዘመን አንዳንድ ሰዎች ገንዘብን የሚወድዱ፣ ራሳቸውን የማይገዙ፣ ሐሜተኞች፣ መልካም የሆነውን ነገር ሁሉ የማይወዱ ከዳተኞች ይሆናሉ፤ የአምልኮት መልክ አላቸው፤ ኃይሉን ግን ይክዱታል፤ ከእነዚህ ደግሞ ራቅ ወደ ቤቶች ሾልከው እየገቡ ኃጢአታቸው የተከመረባቸውን በልዩ ልዩ ምኞትም የሚወሰዱትን፣ ሁልጊዜም እየተማሩ እውነትን ወደ ማወቅ ከቶ ሊደርሱ የማይችሉትን… የሚማርኩ ከእነዚህ ዘንድ ናቸውና» /1ጢሞ. 3.1-7/ ሲል እንደተናገረው እነዚህ መናፍቃን ከዚህ የትንቢት ዘመን የተወለዱ እንጂ የቤተ ክርስቲያናችን ልጆች አለመሆናቸውን በግልጽ መንገር ግዴታ ይሆናል፡፡ /መጋቢት 26 ቀን 1990 ዓ.ም/

ጠቅላይ ቤተክህነት የተነተነበት መንገድ እንዳለ ሆኖ የ«ተሐድሶ» ቡድን «አሮጊቷ» የሚለውን ቃል የመረጠበትን መሠረታዊ ምክንያት በውል ማጤን ይገባል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ወንጌልን የምትሰብክን ቤተ ክርስቲያን ከቅድስት ሣራ ጋር አነጻጽሮ ባቀረበበት መንገድ አስበው ተናግረውት ቢሆንማ ከኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን አፈንግጠው የፕሮቴስታንት ፓስተሮች ባዘጋጁት በዚያ የስድብ ጉባኤ ላይ የቤተ ክርስቲያኒቱን የሃይማኖት ትምህርትና ሥርዓት የምእመ ናንን ሕይወት ባላዋረዱ ባላናናቁ ነበር፡፡ ነገር ግን «አሮጊት /አሮጌ» የሚለውን ቃል የመረጡት ቤተ ክርስቲያን አርጅታለችና ማደስ አለብን ለሚለው አስተሳሰብ መንደርደሪያ ነው፡፡ እነዚህ የተሐድሶ መናፍቃን ተወግዘው ቢለዩም በውጪም በውስጥም ሆነው ቤተ ክርስቲያንን ለመገዝገዝና አስተምህሮአቸውን አንዳንድ የቤተ ክርስቲያኒቱ «መምህራን» አውቀውም ሳያውቁም በየዓውደ ምህረቱ እንዲያስተጋቡ ተፅዕኖ መፍጠራቸውን ቀጥለዋል፡፡

እነ አባ ዮናስ የ«አሮጊቷ ሣራ ወለደች» ቃላቸውን ከአዋጁ ከ12 ዓመታት በኋላ አሁን በይፋ ደግሞ «ቤተ ክርስቲያንን አሪታዊት፣ ጨለማ ውስጥ ናት ሲሉ አሮጊቷ ሣራ ዛሬ እኔን ወለደች፣ እገሌን ወለደች፣ እገሌን ወለደች…» የሚል ከእነ አባ ዮናስ ጋር የቃልና የስሜት ዝምድና ያለው የአዋጅ ቃል በአንዳንድ ሰባኪያን ነን ባዮች ተሰምቷል፡፡ በአባ ዮናስና በእነዚህ ሰባኪያን መካከል ያለው የአቀራረብ ልዩነት የአባ ዮናስ በኤግዚቢሽን ማዕከል፣ እነዚህ ደግሞ በራሷ በቤተ ክርስቲያኒቱ ዓውደ ምህረት ላይ ማወጃቸው ነው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረው ትምህርት ቃሉም ትርጓሜውም የታወቀ ሆኖ ሳለ ቤተ ክርስቲያናችንም ከጨዋይቱ የተወለድን ክርስቲያኖች አንድነት መሆኗ ለ2ሺሕ ዘመን የተመሰከረ ሆኖ ሳለ የአሁኖቹ «ሰባክያን» ራሳቸውንና ጓደኞቻቸውን ነጥለው «የተስፋው ወራሾች የአሮጊቷ የሣራ ልጆች» እያሉ የሚያቀርቡበት ገለጻ ትርጓሜ ይፋ መሆን አለበት፡፡

በመሠረቱ በሐዋርያው በቅዱስ ጳውሎስ የተሰበከውን ምሳሌያዊ ትምህርት ይዞ ተንትኖ ማስተማር ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን ከአርባ ሚሊዮን በላይ ምእመናን ባሉበት ጥንታዊት እና ሐዋርያዊት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ራሳቸውንና እነርሱ የመረጧቸውን የቡድን አባላት አባ ዮናስ ባቀረቡበት መንገድ «የአሮጊቷ ሣራ» ብሎ የጠሩበት ቤተ ክርስቲያን እነርሱን ከመውለዷ በፊት ምን ጎድሎባት፣ ምንስ አጥታ ነበር ? ቅዱስ ጳውሎስ መካኒቱ፣ ጨዋይቱ፣ እመቤቲቱ እያለ የጠራበት ቅጽል እያለ «አሮጊቷ» የሚለውን በማስጮኽ ማቅረብስ ለምን ተፈለገ ? ቀጥተኛ ምንጩስ ማነው ? ምንድነው ? እነዚህ ሁሉ ጥያቄዎች መመለስ ያለባቸው ናቸው፡፡ እነ አባ ዮናስ «አሮጊቷ ሣራ» ያሏትን ቤተ ክርስቲያንን ድንግል ማርያምን፣ ተክለሃይማኖትን፣ ጊዮርጊስን በልብሽ አኑረሻልና አውጪ እያሉ በአደባባይ ድፍረት ተናግረዋል፡፡ በእነዚህ «ሰባክያን» የ«አሮጊቱ ሣራ» አስተምህሮ ውስጥ ያለው አንድምታስ ምንድነው ? እነ አባ ዮናስ በ«አሮጊቷ ሣራ» አስተምህሮአቸው «ቤተክርስቲያኒቱ በ4ኛው ክፍለ ዘመን አባ ሰላማ ከሳቴ ብርሃን ከሰበኩበት ጊዜ በኋላ ወንጌል አልተሰበከችም የወላድ መካን ሆና የኖረች ናት» በማለት አሁን እነርሱ ያንን ለመፈጸም የተወለዱ አድርገው አቅርበዋል፡፡ የእነዚህ ሰባክያን የ«አሮጊቷ ሣራ» አስተምህሮስ ከዚህ አንጻር ምን ይላል ?

ይህ ብቻ ሳይሆን አባ ዮናስ «ይህ ትውልድ የኢያሪኮን ግንብ ያፈርሳል» ያለው ቤተ ክርስቲያኒቱን ዒላማ ያደረገ ፉከራው በእነዚህ ሰባክያን የመዝሙር መንደርደሪያዎች ውስጥ ከሚነገረውና «መዶሻ ያልያዘ ሠራዊት ኢያሪኮን ያፈርሳል…» ከሚሉት አዝማች ቃል ጋር ያለውንም የትርጉም ዝምድና መጤን እንዳለበት         እንድናስብ ያስገድዳል፡፡ በተመሳሳይ ይህንኑ መንገድ ተከትሎ በየደረጃው ምእመናን እነ አባ ዮናስ በግልጽ ያወጁት የ«ተሐድሶ» ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮ ዓውደ ምህረቶቻችን ላይ አሁንም ወደቆሙ «መምህራን» መሻገር አለመሻገሩን ቃሎቻቸውን እያጠኑ ለመመርመር ተገደዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን የሚመለከታቸው አካላትም የእነዚህን «ሰባኪያን» ትምህርት መርምረው ካለማወቅ በስሕተት የቀረበ ትምህርት መሆኑን ወይም በድፍረት የቀረበ ለ«ተሐድሶ» ዘመቻ የጥፋት ፈትል ማጠንጠኛ መሆን አለመሆኑን ለይተው እንደሚያቀርቡ ተስፋ እናደርጋለን፡፡

ምንጭ፦ ሐመር 19ኛ ዓመት ቁጥር 2

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴን አስመልክቶ ቅዱስ ፓትርያሪኩ ከማኅበረ ቅዱሳን አመራር ጋር ውይይት አደረጉ

 

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዚዳንት የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ከማኅበረ ቅድሳን ሥራ አመራርና አስፈጻሚ ጉባኤያት ተወካዮች ጋር ነሐሴ 15 ቀን 2003 ዓ.ም ስለ ማኅበሩ አገልግሎትና በተለይም የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ አስመልክቶ ውይይት ማድረጋቸውን የማኅበሩ ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡

በቅዱስ ፓትርያሪኩ ጽ/ቤት በተካሔደው ውይይት፤ የማኅበሩ አመራር ስለተሐድሶ መናፍቃን እንቅቃሴ አራማጆችና ተቋማት የተዘጋጁ ልዩ ልዩ መጻሕፍት እንዲሁም በምስል ወድምጽ /VCD/ የታገዘ ገለጻና ማብራሪያ ቀርቧል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስም በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ እየተፈጸመ ያለውን ድርጊት ከተመለከቱ በኋላ “ይህ ሁሉ የንብ ሠራዊት እያለ ወረራው ሲካሔድ የት ነበራችሁ?” የሚል የአባትነት ጥያቄያቸውን አቅርበዋል፡፡

ቅዱስነታቸው፤ ቤተ ክርስቲያንን እና ምእመናንን ከእንዲህ ዓይነቱ ተግባር መጠበቅ የሁሉም ሓላፊነት እንደሆነ ጠቅሰው፤ ከዚህም በላይ መብታችንን በሕግ ሳይቀር ማስከበር እንደሚኖርብን ገልጸዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን በልጅነት ድረሻው እያከናወነ ያለው አገልግሎት እንደተጠበቀ ሆኖ፤ የግለሰቦችን ስም እየጠቀሰ “ተሐድሶ ናቸው” ማለት ግን አግባብ እንዳልሆነና ይህም የቤተ ክርስቲያናችንን አሠራር ጠብቆ መፈጸም እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

የማኅበሩ አመራር አባላትም፤ በአሁኑ ወቅት እየተከናወነ ያለው ሥራ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ምንነት፣ በእንዴት ዓይነት ሁኔታና ደረጃ ላይ እንደሚገኝ ምእመናን ግንዛቤ አግኝተው ራሳቸውን እንዲጠብቁ፤ እንዲሁም ፕሮቴስታንታዊ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴን የሚመሩና የሚደግፉ ተቋማትን፣ ስልትና አሠራራቸውን የማሳወቅ ሥራ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በ1990 ዓ.ም የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ የማጋለጥ ሰፊ ሥራ ባከናወነበት ወቅት፤ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሆነው ነገር ግን ፕሮቴስታንታዊ የተሐድሶ ኑፋቄ በምእመኑ ውስጥ በመዝራት ጉልህ ድርሻ የነበራቸው “መነኮሳት” ተወግዘው እንዲለዩ ሲደረግ፤ በቤተ ክርስቲያን ሥርዐትና አሠራር መሠረት ማኅበሩ አስፈላጊውን መረጃና ማስረጃ ለሊቃውንት ጉባኤ አቅርቦ ከዚያም በኋላ በቅዱስ ሲኖዶስ የመጨረሻ ውሳኔ እንዲሰጥ ያደረገበት ሁኔታ እንደነበረ፤ የማኅበሩ አመራር አባላት በውይይቱ ላይ አስታውሰው፤ ማኅበሩ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዐትና አሠራር ጠንቅቆ እንደሚያውቅና ይህንኑ ለማስጠበቅ ጠንክሮ እንደሚሠራ ገልጸዋል፡፡ አሁንም ማኅበረ ቅዱሳን እየሠራ ያለው የግለሰቦችን ስም በመጥቀስ “ተሐድሶ” የማለት ሳይሆን፤ ስለ ተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ምንነትና ስልት ግንዛቤ እንዲኖር በማድረግ ምእመናን ራሳቸውን እንዲጠብቁ የማሳወቅ ሥራ እየተከናወነ እንደሆነ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡
ወደፊትም በዚህ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴና ሥራ ላይ የተጠመዱ ነገር ግን በቤተ ክርስቲያኒቷ ውስጥ የሚገኙ አካላትንና ደጋፊዎችን፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዐትና አሠራር በመጠበቅ ማኅበረ ቅዱሳን ለሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላትና አባቶች እንደሚያቀርብ በማኅበሩ አመራር አባላት ለቅዱስነታቸው ተገልጿል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያሪኩም፤ በበቂ መረጃ በማስደገፍ ለሚመለከተው የቤተ ክርስቲያን አካል በማቅረብ ሁሉም ነገር በሕግና በሥርዐት መከናወን እንዳለበት አባታዊ መመሪያ ሰጥተዋል፡፡

Emebetachin-Eriget

«ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኲሉ»

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

ነሐሴ 15/2003 ዓ.ም

Emebetachin-Erigetፆመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት፣ ትንሣኤና ዕርገቷ የሚታሰብበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ምእመናንን ከአካባቢያቸው ራቅ ብለው በተለያዩ ገዳማትና አድባራት በመሄድ አሊያም በአጥቢያቸው በመሰባሰብ እመቤታችን ለሐዋርያት በተለያዩ ጊዜያት ተገልጻ ሞትና ትንሣኤዋን የገለጸችበትን ሁኔታ ያስባሉ፡፡ ጌታም እናቱን መንበር አድርጎ ቀድሶ ማቁረቡን ይዘክራሉ በዚህ ወቅት በፆም በጸሎት ተወስነው የልጇን ቸርነት የድንግልን አማላጅነት ይማጸናሉ፡፡ ሁሉም እንደሚደረግላቸው ያምናሉ፡፡ የሱባኤው ወቅት ሲፈጸም «በእውነት ተነሥታለች» ብለው በደስታ የፆሙን ወቅት ይፈጽማሉ፡፡

 

 

ሞትና ትንሣኤዋ እንዴት ነው ቢሉ፡-
የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሞትና ትንሣኤ ነገረ ማርያም፣ ስንክሳር እና ተኣምረ ማርያም እንደሚያስረዱት፤ ጥር 21 ቀን ዐርፋለች፡፡ ሞቷ የሚያስደንቅ መሆኑን ታላቁ የቤተክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድ  «ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የሐጽብ ለኲሉ፤ ሞት ለማናቸውም ሰው ሁሉ የተገባ ነው የማርያም ሞት ግን ሁሉን ያስደንቃል» በማለት ገልጾታል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት የእመቤታችንን የከበረ ሥጋዋን ገንዘውና ከፍነው ለማሳረፍ ወደ ጌቴሴማኒ መካነ ዕረፍት (የመቃብር ቦታ) ይዘው ሲሄዱ አይሁድ በቅንአት መንፈስ ተነሣሥተው «ቀድሞ ልጇን በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተነሣ፤ በዐርባኛው ቀን ወደ ሰማይ ዐረገ እንደገናም ተመልሶ ይህን ዓለም ለማሳለፍ ይመጣል  እያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ፡፡ አሁን ደግሞ እርሷንም እንደ ልጇ ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሲያውኩን ሊኖሩ አይደለምን) ኑ ተሰብሰቡና ሥጋዋን በእሳት እናቃጥላት» ብለው ተማክረው መጡ፡፡

ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ የከበረ ሥጋዋን የተሸከሙበትን አጎበር (የአልጋ ሸንኮር) በድፍረት ያዘ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በእሳት ሰይፍ ሁለት እጆቹን ቆረጣቸው፡፡ እጆቹ ተንጠልጥለው ከቆዩ በኋላ በእውነት የአምላክ እናት ናት በማለት ስለ አመነ እጆቹ ተመልሰው እንደነበሩ ሆነውለታል፡፡ ከዚህ በኋላ መልአከ እግዚአብሔር የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ  ከሐዋርያው ዮሐንስ ጋር ነጥቆ ወስዶ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጠው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ከጥቂት ጊዜ በኋላ ወደ ሐዋርያት ሲመጣ የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ በገነት መኖሩን ነገራቸው፡፡  ሐዋርያትም የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አግኝተው  ለመቅበር በነበራቸው ምኞትና ጉጉት  ዮሐንስ አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን ብንጠየቅስ ምን እንመልሳለን በማለት በነሐሴ አንድ ቀን ሱባኤ ጀምረው ሲጾሙና ሲጸልዩ ከሰነበቱ በኋላ በ14 (በሁለተኛው ሱባኤ መጨረሻ) ጌታችን የእመቤታችንን ትኩስ የከበረ ሥጋ አምጥቶ ስለሰጣቸው በታላቅ ዝማሬ፣ በውዳሴ ወስደው ቀድሞ በተዘጋጀው መካነ ዕረፍት  በጌቴሴማኒ ቀበሯት፡፡

የእመቤታችን የቀብር ሥነ ሥርዐት በተፈጸመ ጊዜ ከ12ቱ ሐዋርያት አንዱ የሆነው ቅዱስ ቶማስ አልነበረም፡፡ ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ፣ እመቤታችን በተቀበረች በሦስተኛው ቀን  እንደ ልጇ ትንሣኤ ተነሥታ ስታርግ ያገኛታል፡፡ ቀድሞ የልጅሽን አሁን ደግሞ የአንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ ብሎ ቢያዝን እመቤታችን ከእርሱ በቀር ሌሎች ሐዋርያት ትንሣኤዋን እንዳላዩ ነግራው ቅዱስ ቶማስን አጽናናችው፡፡ ሄዶም ለሐዋርያት የሆነውን ሁሉ እንዲነግራቸው አዝዛው ለምልክት ይሆነው ዘንድ የተገነዘችበትን ሰበኗን ሰጥታው ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት የእመቤታችን ትንሣኤ አስቀድሞ በትንቢት መስታወትነት ታይቶት «ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅድስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት» (መዝ.131፥8)፡፡  ነቢዩ ዳዊት ይህን ቃለ ትንቢት  አስቀድሞ ክርስቶስ እንደሚነሣ ከገለጸ በኋላ ቀጥሎ የመቅደሱ ታቦት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም እንደምትነሣ ይናገራል (ማቴ5፥35፤ ገላ 4፥ 26፤ ዕብ 12፥22፤ ራዕ 3፥12)፡፡

ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅዱስ ቶማስም ሐዋርያት ወደ አሉበት ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ «የእመቤታችን ነገር እነዴት ሆነ?»  ብሎ ቢጠይቃቸው፤ «እመቤታችንን እኮ ቀበርናት» ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ዐውቆ ምስጢሩን ደብቆ «አይደረግም ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር  እንደምን ይሆናል?» አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ መጠራጠር ልማድህ ነው፡፡ ቀድሞ የጌታን ትንሣኤ ተጠራጠርክ አሁንም አታምንም ብሎ  የእመቤታችን መካነ መቃብር ሊያሳዩት ይዘውት ሔዱ፡፡ መቃብሩን ቢከፍቱ የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አጡት፤ ደነገጡም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ «አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሥታ ዐርጋለች» ብሎ  የሆነውን ሁሉ ተረከላቸው፡፡ ከዚያም ምልክት እንዲሆን የሰጠችውን ሰበኗን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ማረጓን አምነው ሰበኗን ለበረከት ከተከፋፈሉ በኋላ ወደየአህጉረ ስብከታቸው ሄዱ፡፡ በየሀገረ ስበከታቸውም ሕሙማንን ሲፈውሱበትና ገቢረ ተአምር ሲያደርጉበት ኖረዋል፡፡

በዓመቱ ትንሣኤሽን ቶማስ አይቶ እንዴት ይቅርብን ብለው ነሐሴ አንድ ቀን ጀምሮ ሱባኤ ገቡ፡፡ በሱባኤው መጨረሻ ነሐሴ 16 ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የለመኑትን ልመና ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቀ (ረዳት) ቄስ)፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገባሬ ሰናይ (ዋና) ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ አቁርቦአቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ እመቤታችንን ሐዋርያት በግልጽ ትንሣኤዋን ዕርገቷን እያዩዋት ከጌታችን ጋር በክብር በይባቤና በመዝሙር ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡ ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ «እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ዐረገች በሰማይም ከልጇ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች»፡፡

የእመቤታችን ትንሣኤ፣ ዕርገት ልዩ የሆነበት ምስጢር
በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት ትንሣኤ ጊዜያዊና ዘለዓለማዊ በመባል ይታወቃል፡፡ ጊዜያዊ ትንሣኤ የሚባለው የእግዚአብሔር ከሃሊነት የሚገለጽበት ተኣምራዊ ሥራ ሆኖ በተወሰኑ ሰዎች ላይ ይፈጸምና ዳግም ሞትን የሚያስከትል ነው፡፡ ለምሳሌ ኤልያስ ያስነሣውን ወልደ መበለት (1ኛ ነገ 17፥8-24) ዐጽመ ኤልሳዕ  ያስነሣውን ሰው (2ኛነገ 13፥20፦21) ትንሣኤ ወለተ ኢያኢሮስን (ማቴ 9፥ 8-26) በዕለተ ስቅለት ከመቃብር ወጥተው በቅድስት ከተማ የታዩ ሙታን (ማቴ 27፥52-53) በቅዱስ ጴጥሮስ ጸሎትና ምልጃ የተነሣች ጣቢታን (ሐዋ ሥ 9፥36-41) እንዲሁም ትንሣኤ አልዓዛርን መጥቀስ ይቻላል፡፡

አልዓዛር ከሞተ በኋላ በአራት ቀን እንደተነሣ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ጽፏል፡፡ «በታላቅ ድምፅ አልዓዛር ሆይ ወደ ውጭ ና ብሎ ጮኸ፡፡ የሞተውም እጆቹና እግሮቹ  በመግነዝ እንደተገነዙ ወጣ፤ ፊቱም በጨርቅ እንደተጠመጠመ ነበር፡፡ ኢየሱስም ፍቱትና ይሂድ ተውት አላቸው(ዮሐ 11፥43-44)፡፡  ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያነሣውም ለማየት በመቃብሩ ዙሪያ የነበሩ አይሁድ ከሞተ በኋላ በአራት ቀን መነሣቱን ተመልክተው አደነቁ የአልዓዛር እኅቶችም  ተደሰቱ፡፡ አልዓዛር ግን ለጊዜው ቢነሣም ቆይቶ ተመልሶ ዐርፏል ወደፊት ትንሣኤ ዘጉባኤ ይጠብቀዋል፡፡

የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ የክብርና የሕይወት ትንሣኤ ሲሆን ሁለተኛ ሞትን አያስከትልም ትንሣኤ ዘጉባኤንም አይጠብቅም፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤያችን በኩር ሆኖ በሞተ በሦስተኛው  ቀን ተነሥቷል፡፡ እናቱ እመቤታችንም በልጇ ሥልጣን፤  እንደ ልጇ ትንሣኤ በሦስተኛው ቀን ተነሥታ ትንሣኤ ዘጉባኤን ሳትጠብቅ በክብር ዐርጋለች፡፡  እንደዚህ ያለውን ትንሣኤ ከእርሷ በቀር ሌሎች ቅዱሳን ወይም ነቢያትና ሐዋርያት አላገኙትም በዚህም ሁኔታ የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ ከማናቸውም ትንሣኤ ልዩ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህም ትንሣኤ ዘለዓለማዊ የሆነ ከዳግም ሞተ ሥጋ ነጻ የሆነ ትንሣኤ ነው፡፡

ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ከመቃብር መነሣት ነሐሴ 16 ቀን የሚነበበው መጽሐፈ ስንክሳር እንደሚያስረዳን አባቷ ዳዊት በገናውን እየደረደረ ጸሐፊው የነበረው ዕዝራም መሰንቆውን ይዞ ቅዱሳን መላእክት ነቢያትና ጻድቃን እያመሰገኗት በብሩህ ደመና ወደ ሰማይ ዐረገች ከዚያም በክብር ተቀመጠች፡፡ በዚያም ስፍራ ሁለተኛ ሞት ወይም ሐዘን ጩኸትና ስቃይ የለም የቀደመው ሥርዐት አልፎአልና (ራዕ 21፥4-5)፡፡

የእመቤታችን ዕርገትም በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው ከእነ ሄኖክና ኤልያስ ዕርገት የተለየ ነው፡፡  ሄኖክ ወደ ሰማይ ያረገው በምድር ሳለ እግዚአብሔርን በእምነቱና በመልካም ሥራው ስለአስደስተና በሥራውም ቅዱስ ሆኖ ስለተገኘ ሞትን እንዳያይ ዐረገ፡፡ ወደፊት ገና ሞት ይጠብቀዋል ሞቶም ትንሣኤ ዘጉባኤ ያስፈልገዋል፡፡ «ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም» (ዕብ 11፥5)፡፡

ነቢዩ ኤልያስም በእሳት ሠረገላ ተነጥቋል «እነሆ የእሳት ሠረገላና የእሳት ፈረሶች በመካከላቸው ገብተው ከፈሉአቸው፤ ኤልያስም በአውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጣ»  (2ኛ ነገ 2፥10)፡፡ ነቢዩ በእሳት ሠረገላም ቢነጠቅም ወደፊት ሞት ይጠብቀዋል፤ ትንሣኤ ዘጉባኤም ያስፈልገዋል፡፡

 

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድም በድርሰቱ ስለ ዕርገትዋ ጽፏል፡፡ በቃልዋ የታመነች በሥራዋም የተወደደች ቅድስት ድንግል ማርያምን መላእክት እያመሰገኗትና በመንፈሳዊ ደስታ እያጀቧት ወደ ሰማይ አሳረጓት ሲል በዘመረው መዝሙር አስረድቶናል፡፡
የእመቤታችን አማላጅነት የትንሣኤያችን በኲር የሆነው የአምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነቱ ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን፡፡

የተራራው ምስጢር/ማቴ 17፡1-9/

ዲያቆን ታደለ ፈንታው


ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊልጶስ ቂሣርያ መነ ይብልዎ ሰብእ ለወልደ እጓለ እመሕያው የሰው ልጅን ማን እንደሆነ ይሉታል ? የሚል ጥያቄን ለደቀ መዛሙርቱ አቀረበላቸው ፡፡ አንዳንዶች ከነቢያት አንዱ ነህ አሉት ፡፡ በሥምም እየጠቀሱ መጥምቁ ዮሐንስ : ኤልያስ : ኤርምያስ ነህ በማለት ግምታቸውን አስቀመጡ፡፡ ደቀመዛሙርቱ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተነገረ ገና በእምነት አልጠነከሩም ነበርና ግምታቸው የተዘበራረቀ ነበረ፡፡

 

ከሐዋርያት አንዱ ሊቀ ሐዋርያት ቅዱስ ጴጥሮስ የእርሱ ተራ በደረሰ ጊዜ የሰጠው ምስክርነት ግን ድንቅ የሆነ ምስክርነት ነበር፡፡ «አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ»/ማቴ 16፡13/ የሚል፡፡ የዮና ልጅ ስምዖን በዚህ ምስክርነቱ ብፁዕ ነህ ተብሎ ተጠርቷል፡፡ ጌታችን እንዲህ አይነቱን ምስክርነት ሥጋና ደም አልገለጸልህም በሰማይ ያለው አባቴ እንጂ አለ ፡፡ በዘመናችን ብዙዎች የሥጋና ደም ሀሳብን ይዘው አምጻኤ አለማትነቱ፤ ከሃሊነቱ፤ ጌትነቱ፤ ተአምራቱ፤ መግቦቱ፤ ዓይን ነሥቶ ዓይን ለሌለው ዓይን ሰጥቶ መመገቡ አልታያቸው ብሎ አማላጅ ነህ ይሉታል፡፡ ያለባሕርይው ባሕርይ ሰጥተው በየመንደሩ፤ በየዳሱ አለ ብለው ይጠሩታል፤ እርሱ ግን «እነሆ ክርስቶስ በመንደር ወይም በእልፍኝ ውስጥ አለ ቢሏችሁ አትመኑ» አለ ፡፡ ከራሳቸው ልቡና አንቅተው ስለጌታችን የተሳሳተ መረዳት ያላቸው ሰውንም የሚያሳስቱ የሥጋና ደም ኃሳባቸውን ቀላቅለው ንፁህ የሆነውን የወንጌል ቃል የሚበርዙ ወገኖች ብፁዓን ናችሁ አልተባሉም ፡፡

 

ይህ ምስክርነት በተሰጠ ማለትም «በቂሣርያ የሰውን ልጅ ማን ይሉታል»ባላቸው በሰባተኛው ቀን ከደቀ መዛሙርቱ ሦስቱን ለብቻቸው ይዞአቸው ወደረጅምና ከፍ ወደአለ ተራራ ወጣ ፡፡ በከፍታው ላይ ያለ ልዑል እግዚአብሔር ረጅምና ከፍ ያለ ነገርን ይወዳል ፡፡ ንጉሡ ዖዝያን በሞተበት ዓመት ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስ እግዚአብሔርን የተመለከተው በረጅምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ነበር»ጌታችን ሰው ሆኖ ሥጋን ሲዋኻድም ከፍጥረታት ሁሉ ከፍ ያለውን አማናዊ ዙፋን እርሱም የእመቤታችንን ማኅጸን ነበረ የመረጠው፡፡ ይኸንን ሁኔታ ሊቁ አባ ሕርያቆስ እንዲህ ብሎ በማድነቅ ይጠይቃል፡፡ «ድንግል ሆይ ሰባት የእሳት መጋረጃ ከሆድሽ በስተየት በኩል ተጋረደ በስተቀኝ ነውን? በስተግራ ነውን ? ታናሽ ሙሽራ ስትሆኝ፡፡ ለአባታችን ያዕቆብም የገለጸለት መሰላል ከምድር ከፍ ያለ መሰላል ነበረ፡፡ ምሳሌነቱን ከፍጥረታት ሁሉ ከፍ ላለች ለእመቤታችን ነው፡፡ የጌታችን ከፍ ያለ ነገር መዉደድ ምሳሌው ልዑለ ባሕርይ ነኝ ሲል ነው፡፡

 

ለምን በደብረ ታቦር ተራራ ላይ ተገለጠ ?


በመጀመሪያ ተራራ የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው ፡፡ ተራራን በብዙ ድካም እንዲወጡት መንግሥተ ሰማያትንም በብዙ መከራ ያገኟታል ፡፡ ይህንን ሁኔታ ቅዱስ ጳውሎስ ሲገልጥ እስመ በብዙህ ጻዕር ወበጻማ ኃለወነ ንባኣ መንግሥተ እግዚአብሔር በብዙ ጭንቅ መከራ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንገባ ዘንድ አለን በማለት አስረድቷል ፡፡ ተራራውን ሐዋያርት በሲኖዶስ ታቦር ብለው ጠርተውታል፡፡ ይህንን ሁኔታ ቅዱስ ጴጥሮስ ሲናገር «የእርሱን ግርማ አይተን እንጂ በብልሃት የተፈጠረውን ተረት ሳንከተል የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ኃይልና መምጣት አስታወቅናችሁ ፡፡ ከገናናው ክብር በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ እርሱ ነው እርሱን ስሙት የሚል ያ ድምጽ በመጣለት ጊዜ ከእግዚአብሔር አብ ክብርንና ምስጋናን ተቀብሎአልና ፤ እኛም በቅዱሱ ተራራ ከእርሱ ጋር ሳለን ይህ ድምጽ ከሰማይ ሲወርድ ሰማን/1ኛ ጴጥ1፤16/ ብሏል ፡፡

 

ጌታችን ምስጢረ መለኮቱን በታቦር ያደረገው በሌላ ተራራ ያላደረገው አስቀድሞ ታቦር ትንቢት የተነገረበት ተራራ በመሆኑ ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት «ታቦር ወአርሞንዔም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ» ብሎ ተናግሯል፡፡ የጌታችን ሰው መሆን የነቢያት ትንቢት ፍጻሜ ማግኘቱን ማሳያ ነው፡፡

 

አሥራ ሁለቱንም ደቀ መዛሙርት የመረጣቸው ጌታችን ነው ፡፡ በመጀመሪያ ሙሴን ለመስፍንነት አሮንን ለክህነት የመረጠበት ግብር እንዳልታወቀ ከደቀመዛሙርቱ ሦስቱን የመረጠበትን ምክንያት የሚያውቀው እርሱ ብቻ ነው ፡፡ እንደ ቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ግን ሦስቱን ወደ ተራራ ይዞአቸው ስምንቱን ከእግረ ተራራ ጥሎአቸው የሄደበት ምክንያት ስለነበራቸው ነው፡፡ የመጀመሪያው ከሌሎቹ የሚበልጡበት ምክንያት ነበራቸውና፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ይወደው ነበርና ቅዱስ ዮሐንስ ጌታ ይወደው የነበረ ደቀ መዝሙር ተብሎ በብዙ ቦታ ተገልጧል፡፡ ቅዱስ ያዕቆብ አንተ የምትጠጣውን ጽዋ እኛም እንጠጣለን ብሏል/ማቴ20፤22/፡፡እንደገናም ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ ብሎ መስክሮ ሥለነበረ ምስክርነቱ በእርሱ ብቻ የሚቀር ሳይሆን እግዚአብሔር አብም በደመና ሆኖ የሰጠው ምስክርነት «በእርሱ ደስ የሚለኝ ልጀ እርሱ ነው እርሱን ስሙት» በማለት የተናገረው ከቅዱስ ጴጥሮስ ምስክርነት ጋር ያለው ድንቅ ስምምነት ይገለጥ ዘንድ ነው፡፡ በዚህም ቅዱስ ጴጥሮስ የሰጠው ምስክርነት ሥጋና ደም ያልገለጠለት መሆኑ በተረዳ ነገር ታውቋል ፡፡ እንደገናም ቅዱስ ዮሐንስንና ያዕቆብን ይዞአቸው ወደተራራ የወጣበት ምክንያት የዘብዴዎስ ልጆች እናት /እናታቸው/ ማርያም ባውፍልያ ጌታችን መንግሥቱ ከዚህ ዓለም መስሎአት ልጆቿን አስከትላ እየማለደች ሰገደችለት ፡፡ እንዲህም የሚል ልመናን ስለልጆችዋ አቀረበች፡፡

 

ወትቤሎ ረቢ ሊተ ከመ ይንበሩ እሉ ደቂቅየ አሐዱ በየማንከ ወአሐዱ በጸጋምከ በመንግሥትከ፡፡

በነገሥህ ጊዜ እኒህ ልጆቸ አንዱ በቀኘህ አንዱ በግራህ እንዲቀመጡ አድርግልኝ፡፡

ወአውሥአ እግዚእ ኢየሱስ ወይቤላ ኢተአምሩ ዘትስእሉ የምትለምኑትን አታውቁም አለ፡፡


ጌታችን መንግሥቱ ሰማያዊት እንጂ ምድራዊት አለመሆኑን ይገልጥላቸው ዘንድ ይዞአቸው ወደተራራ ወጣ፡፡ ስምንቱን ከእግረ ደብር ትቷቸው የወጣበት ምክንያት በይሁዳ ምክንያት ነው፡፡ ክብሩንና መንግሥቱን እንዳያይ ይሁዳ ትንቢት ተነግሮበታልና ለይቶም እንዳይተወው ከምሥጢረ መንግሥቱ ቢለየኝ ከሞቱ ገባሁበት ብሎ ምክንያት እንዳያገኝ ስምንቱን ጥሎአቸው ወጣ፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር ነቢዩ ሙሴን ከእስራኤል ሽማግሌዎች ሕዝቡን ያስተዳድሩ ዘንድ ሰባ ሰዎችን መርጦ ወደ ቅዱሱ ተራራ እንዲያቀርባቸውና ከመንፈሱ ወስዶ በሽማግሌዎቹ ላይ እንዲያፈስባቸውና ሙሴን እንዲያግዙት አዘዘው ፡፡ ከእያንዳንዱ ነገድ ስድስት ሰዎችን መረጠ ከአስራሁለቱ ነገድ የተመረጡት ሰባ ሁለት ሰዎች ሆኑ፤ እንደ እግዚአብሔር ቃል ሰባዎቹን ሰዎች ይዞ የቀሩትን ሁለቱን ኤልዳድንና ሞዳድን ከእግረ ደብር ትቷቸው ወደ ተራራው ወጣ፡፡ በደብረ ሲና ለሰባው ሊቃናት የተገለጠው ምስጢር ከተራራው ሥር ለነበሩ ሁለቱ ሰዎችም ተገልጧል፡፡ በተመሳሳይ ሁኔታ በርእሰ ደብር ለሦስቱ ደቀ መዛሙርት የተገለጠው ምስጢር በእግረ ደብር ላሉ ለስምንቱም ተገልጧል ፡፡

 

ሙሴና ኤልያስ


ሙሴና ኤልያስ በቅዱሱ ተራራ ከጌታችን ጋር የተነጋገሩ ነቢያት ነበሩ ፡፡ በቅዱሱ ተራራ በተከበበ ብርሃን ውስጥ ሆነው ስማቸውን የጠቀስናቸውን ነቢያትን እንመለከታለን ፡፡ እነዚህ ፆም የሚያስገኘውን ጥቅም ያሳዩ ናቸው አርባ አርባ ቀናትን ጾመዋል ፡፡ በቅዱሱም ተራራ ከተገኙት ቅዱሳን መካከል ናቸው ፡፡ እነዚህ ለመገኘታቸው ምክንያት ነበራቸው ፡፡ ጌታችን አስቀድሞ እውነት እውነት እላችኋለሁ ኃለው እምእለ ይቀዉሙ ዝየ እለ ኢይጥዕምዎ ለሞት እስከ ይሬእይዎ ለመንግሥተ እግዚአብሔር ከዚህ ቁመው ካሉት የእግዚአብሔርን መንግሥት እስኪያዩ ድረስ የማይሞቱ አሉ ብሎ ተናግሮ ነበርና ነቢዩ ኤልያስን፥ ሙሴ እባክህ ክብርህን አሳየኝ ብሎ ለምኖ ነበርና ፊቴን ማየት አይቻልህም ነገር ግን ክብሬን በዓለቱ ላይ እተውልሃለሁ ብሎ ተናግሮት ስለነበረ እግዚአብሔር የተናገረው ቃል ከሞት በኋላ እንኳን ተፈጻሚነቱ የማያጠያይቅ መሆኑ ይታወቅ ዘንድ ሙሴም በቅዱሱ ተራራ ላይ ተገኘ፡፡ እንደገናም ጌታችን ስለማንነቱ ሲጠየቅ ሙሴ ነህ ኤልያስ ነህ ብለውት ስለነበረ እርሱ አምላከ ሙሴና አምላከ ኤልያስ መሆኑ ይታወቅ ዘንድ ከነቢያት ሁለቱ ተገኙ፡፡ እንደገናም ሙሴ የሕጋውያን ኤልያስ የደናግል ምሳሌ ነው፤ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የተጠሩት ሁለቱም ወገኖች ናቸውና ፡፡

 

ስለምን ግርማ መለኮቱን ገለጠ ?


ጸሐፍት ፈሪሳውያን የሕጉ ባለቤት ሠራዔ ሕግ እርሱ መሆኑን ባለመገንዘባቸው በተደጋጋሚ ሕጉን ጥሷል በማለት ይከሱት ነበረ ፡፡አይሁድ ይህ ሰው ከእግዚአብሔር አይደለም ፤ ከእርሱስ ቢሆን ሰንበትን አይሽርም ነበር ብለዋልና ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደወጣ የሰንበትም ጌታዋ መሆኑ ይታወቅ ዘንድ ክብሩን መግለጥ ነበረበት፡፡ እንደገናም ቃሌን የሚጠብቅ ቢኖር ለዘላለም ሞትን አይቀምስም በማለት ሲያስተምራቸው በውኑ አንተ ከሞተው ከአባታችን ከአብርሐም ትበልጣለህን ? በማለት ጠየቁት ፡፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ ብሎአቸው ነበርና ክብሩን መግለጥ ነበረበት ፡፡ በሕይወት ካሉት ኤልያስን ከሞቱት ሙሴን የማምጣቱ ምስጢር በሞትና በሕይወት ላይ ስልጣን ያለኝ እኔ ነኝ ሲል ነው፡፡ ሙሴን ከመቃብር ኤልያስን ከብሔረ ሕያውያን ማምጣቱ የሰማይና የምድር ገዢ እኔ ነኝ ሲል ነው፡፡ እንደገናም በሐዋርያቱ የተሰጠውን ምስክርነት በባሕርይ አባቱ በአብ ለማስመስከር ነው፡፡ አስቀድሞ «የሁለት ወገኖች ምስክርነት እውነት እንደሆነ ተጽፏል ስለእራሴ የምመሰክር እኔ ነኝ አብ ስለእኔ ይመሰክራል /ዮሐ.8፥17/ ብሎአቸው ነበርና ነው ፡፡

 

በቅዱሱ ተራራ ላይ


ከሐዋርያት ሦስቱ ከነቢያት ሁለቱ በተገኙበት ልብሱ እሳት ክዳኑ እሳት የሆነ እግዚአብሔር ወልድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በፊታቸው ተለወጠ፡፡ አካሉ ሙሉ ብርሃን ሆነ፡፡ ጽጌያት ከአዕጹቃቸው እንዲፈነዱ፥ፊቱም እንደ ፀሐይ ብሩህ ሆነ፡፡ ልብሱም እንደበረድ ነጭ ሆነ፤ ክብሩን ግርማውን ጌትነቱን ገለጠ፡፡ ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ሲነጋገሩ ተሰሙ፡፡ ከደመናውም ውስጥ «ዝንቱ ውእቱ ወልድ ዘአፈቅር ዘቦቱ ሠመርኩ፤ ልመለክበት የወደድሁት ለተዋሕዶ የመረጥሁት ልጄ ይህ ነው፡፡ ወሎቱ ስምዕዎ እርሱን ስሙት የሚል አስፈሪ ድምጽ መጣ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው አለው አንተ የአምላክነት ሥራህን እየሠራህ ብንራብ እያበላኸን፣ ብንታመም እየፈወስከን፣ ብንሞት እያነሣኸን፤ ሙሴ የወትሮ ሥራውን እየሠራ፣ ደመና እየጋረደ፣ መና እያወረደ፣ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላት እየገደለ፡፡ ኤልያስ የወትሮ ሥራውን እየሠራ፣ ሰማይ እየለጎመ፣ እሳትን እያዘነመ፣ ዝናም እያቆመ፣ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው፡፡ ወእመሰ ትፈቅድ ንግበር በዝየ ሠለስተ ማኅደረ ከዚህ ሦስት አዳራሽ እንሥራ፤ አሐደ ለከ አንዱን ለአንተ፤ ወአሐደ ለሙሴ አንዱን ለሙሴ፤ ወአሐደ ለኤልያስ አንዱን ለኤልያስ አለ፡፡ ይህንን ገና እየተናገረ እንዳለ ብሩህ ደመና መጥቶ ጋረዳቸው፡፡ አብ የሠጠው ምስክርነት ተሰማ፡፡ እመቤታችን በገሊላ ቃና እርሱን ስሙት /ዮሐ. 2፡5/ በማለት ስለ ልጅዋ የሰጠቸው ምስክርነት ይኸው ነበረ፡፡ የተዓምረ ማርያም ደራሲ የእመቤታችን ሀሳብ እንደ እግዚአብሔር ሀሳብ ነው የሚለው መንፈስ ቅዱስ የሚያናግረውን እንዲህ ዓይነቱን ታላቅ ሀሳብና ምስክርነት ነው ፡፡

 

ከዚህ ትምህርት የምንማረው ምንድር ነው ?


አስተምህሮአችን መሠረቱን በነቢያትና ሐዋርያት ላይ ያደረገ መሆኑን በቅዱሱ ተራራ ላይ የተገኙት ነቢያትና ሐዋርያት ምስክሮች ናቸው፡፡ እኛም በነቢያትና ሐዋያርት መሠረት ላይ ታንጻችኋል ተባለልን፡፡ ስለጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ማንነት የታመነ ምስክርነት አግኘተናል፡፡ አስቀድሞ ሐዋርያው «በመጀመሪያ ቃል ነበረ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ/ዮሐ1፡1/ በማለት የሰጠንን ምስክርነት እንደገናም ጸጋንና እውነትን ተመልቶ በእኛ ላይ አደረ በማለት ያመጣውን ቅድመ ዓለም ከአብ ያለእናት በዚህ ዓለም ቅድስት ከምትሆን ከእመቤታችን ከድንግል ማርያም ያለአባት የተወለደውን አምላክ ወልደ አምላክ በማመን የወንጌል ጋሻን ደፍተን የእምነት ወንጌልን ተጫምተን በማመን እንበረታለን እንጂ ባለማመን ምክንያት አንጠፋም፡፡ ክርስቲያኖች ምስጢረ መለኮቱን የገለጠበትን ከጌታችን ዓበይት በዓላት አንዱ የሆነውን የደብረ ታቦርን በዐል የምናከብረው በዚህ መንፈስ ነው ፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጠብቃ ለትውልድ ካስተላለፈችው ታላላቅ መንፈሳውያት እሴቶች መካከል በጌታችን  በእመቤታችንና በቅዱሳኑ ሥም በዓላትን ማክበር ነው ፡፡ ከእነዚህም በዓላት መካከል አንዱ የደብረ ታቦር በዐል ነው፡፡ በዓሉም በተለየ መልኩ ይከበራል፤ ዳቦ በመድፋት፤ ጠላ በመጥመቅ፤ በተለይም የአብነት ተማሪዎች ከሕዝቡ በመለመን ስሙን ይጠራሉ፡፡ ይህ ልንጠብቀው የሚገባን መንፈሳዊ እሴታችን ነው፡፡ ጌታችን የቅዱሳኑን መታሠቢያ በተመለከተ ሲናገር በደቀ መዝሙር ሥም ቀዝቃዛ ዉኃ ብቻ ያጠጣ ዋጋው አይጠፋበትም እንዳለ /ማቴ.10፥42/ በባለቤቱ ሥም የሚደረገውማ እንደምን አብዝቶ ዋጋ አያሰጥ፡፡ ለሚወዱኝ እስከሺህ ትውልድ ድረስ ምሕረትን የማደርግ እኔ እግዚአብሔር ነኝ /ዘጸ.21፥6/ ስላለ በዓሉን በማክበር የበረከቱ ተሳታፊ መሆን ይገባል::

ወስብሃት ለእግዚአብሔር
Normal 0 false false false EN-US X-NONE X-NONE MicrosoftInternetExplorer4

Normal 0 false false false EN-US X-NONE X-NONE MicrosoftInternetExplorer4

ብፁዕ አቡነ ሚካኤል አረፉ፡፡

የሰሜን ምዕራብ ትግራይ ሽሬ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ሚካኤል ነሐሴ 8 ቀን 2003 ዓ.ም አርፈዋል። በአንብሮተ እድ ከተሾሙበት ከነሐሴ 22 ቀን 1997 ዓ.ም ጀምሮ በአሁኑ ሀገረ ስብከታቸው የተሾሙ ሲሆን በመካከል ለተወሰኑ ወራት የወላይታ፣ ዳውሮና ኮንታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው አገልግለዋል።

የሐሞት ጠጠር ሕመም የነበረባቸው ብፁዕነታቸው የቀዶ ጥገና ህክምናቸውን በቅዱስ ገብርኤል ሆስፒታል በመከታተል ላይ የነበሩ ሲሆን በመካከል ከሰመመናቸው መንቃት ሳይችሉ እንደቀሩ ምንጮቻችን ገልጸዋል። ቀጣይ የአስከሬን ምርመራ ከተደረገ በኋላ ምክንያቱ ሊገለጽ እንደሚችልም ይገመታል።

በቅዱስ ሲኖዶስ ምርጫ በትግራይ ክልል ሰሜናዊ ምዕራብ ዞን የተሾሙት የቀድሞው ሊቀ ሥልጣናት አባ ተክለሚካኤል ዓባይ አሁን ብፁዕ አቡነ ሚካኤል በቀድሞው አድዋ አውራጃ በአምባ ሰነይቲ ወረዳ በላውሳ ቅዱስ ገብርኤል አካባቢ ከአለቃ ዓባይ ወ/ገብርኤልና ከወ/ሮ ታደለች ንጉሤ በ1942 ዓ.ም ተወለዱ፡፡

በታላቁ በደብረ ዓባይ ገዳም ከመምህር አበራና ከመምህር ገብረ እግዚአብሔር ከመሠረተ ትምህርት እስከ ጸዋትወ ዜማ፣ ከመምህር የኔታ የኋላእሸት መዝገበ ቅዳሴ ጠንቅቀው ከተማሩ በኋላ በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡

በዋልድባ ገዳም መዓርገ ምንኩስና ተቀብለዋል፡፡ ጎንደር ክፍለ ሀገር በወገራ አውራጃ በጉንተር አቦ ከመሪጌታ ሐረገወይን፣ ጎንደር ከተማ ከመምህር እፁብ ቅኔ ተምረው ተቀኝተዋል፡፡

በሐረርጌ ክፍለ ሀገር ቁልቢ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም እያገለገሉ የአንደኛና መለስተኛ ሁለተኛ ደረጃ ዘመናዊ ትምህርታቸውን ተከታትለዋል፡፡ በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ ት/ቤት በአዳሪነት ገብተው የሁለተኛ ደረጃ ትምህርታቸውን አጠናቀዋል፡፡

በውጪ አገር እንግሊዝ ለንደን ሴንት ኤድዋርድስ ኮሌጅ የመጽሐፍ ቅዱስ ኮርስና የእንግሊዝኛ ቋንቋ ለአንድ ዓመት፣ ግሪክ አገር በአቴንስ ዩኒቨርስቲ ለስድስት ዓመታት ከፍተኛ መንፈሳዊ ትምህርት በመማር በቲኦሎጂ ማስትሬት ዲግሪ፣ በአሜሪካ ሆሊ ክሮስ በተባለው የግሪክ ሴሚናሪ ከሲስተማቲክ ቲኦሎጂ ዲፕሎማ፣ በቦስተን ዩኒቨርስቲ የኤስ.ቲኤም ወይም በፓስተራል ካውንስሊንግ /ሳይኮሎጂ/ በማስተርስ ዲግሪ ተመርቀዋል፡፡

በተለያዩ ጊዜያት በጠቅላይ ቤተ ክህነት የእስኮላር ሽፕ ዋና ክፍል ኃላፊ፣ የኢትዮጵያ ገዳማት መምሪያ ኃላፊ፣ የቅዱስ ጳውሎስ ከፍተኛ መንፈሳዊ ት/ቤት ዲን፣ በወቅቱ የኤርትራ ሀገረ ስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የዕቅድና ጥናት መምሪያ ኃላፊ፣ የትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የበላይ ኃላፊ፣ የቅድስት ሥላሴ ካቴድራል አስተዳዳሪ፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የካህናት አስተዳደር መምሪያ ኃላፊ፣ የትምህርትና ሥልጠና መምሪያ ሐላፊ በመሆን አገልግለዋል፡፡

የብፁዕነታቸው የቀብር ሥነሥርዓት ዛሬ ነሐሴ 10 ቀን 2003 ዓ.ም ከዘጠኝ ሰዓት ጀምሮ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና እንግዶች እንዲሁም ምእመናን በተገኙበት በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ይፈጸማል።

ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 19ኛ ዓመት ቁጥር 12

ዓሣ አጥማጁ ስምዖን(ለሕፃናት)

በአዜብ ገብሩ

በአንድ ወቅት ምን ሆነ መሰላችሁ ጌታችን በባህር ዳር ቆሞ ሕዝብን ያስተምር ነበር ሕዝቡም ጌታችን የሚያስተምረውን ትምህርት በደንብ ይከታተሉት ነበር፡፡ ጌታችንም ድምጹ ለብዙ ሰዎች እንዲሰማ ወደ ስምዖን ታንኳ ላይ ወጣ፡፡ በታንኳይቱም ውስጥ ተቀምጦ ሕዝቡን አስተማራቸው፡፡ ትምህርቱንም ሲጨርስ ሁሉም ሰው ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ሲማሩ ከነበሩት መካከል አንዱ ስምዖን ነበር፡፡ ቀኑን ሙሉ ሌሊቱን ሁሉ ምንም ዓሣ ስላላጠመደ ተጨንቆ ነበር፡፡ ለምን መሰላችሁ ልጆች የስምዖን ቤተሰቦች ስምዖን የሚያመጣውን ዓሣ ይጠባበቁ ስለነበረ ነው፡፡ ስምዖን ዓሣ ሳይዝ ወደ ቤቱ ከገባ ቤተሰብ ሁሉ ሳይበላ ነው የሚያድረው ማለት ነው፡፡ ነገር ግን ልጆች እግዚአብሔር የስምዖን ቤተ ሰቦች ተርበው እንዲያድሩ አላደረጋቸውም፡፡

 

ሌላው ደግሞ ልጆች ስምዖን ታንኳውን ጌታችን እንዲያስተምርበት ትቶለት ነበር፡፡ በጣም ታዛዥ ስለነበር እግዚአብሔር ዝም አላለውም፡፡ ጌታችን ስምዖንን መረብህን ጣልና ዓሣ አጥምድ አለው፡፡ ስምዖንም “መምህር ሌሊቱን ሁሉ ደክሜያለሁ ነገር ግን ምንም ዓሣ አልያዝኩም አንተ ስላዘዝከኝ ግን መረቤን እጥላለሁ” አለው፡፡ ስምዖን ምንም እንኳን ይሆናል ብሎ ባያምንም ለጌታችን ግን ታዘዘው፡፡ እንዳዘዘውም ባደረገ ጊዜ መረብ እስኪቀደድ ዓሣ ያዘ፡፡ ስምዖንም ይህን አይቶ ለጌታችን ሰገደለት፡፡ ከስምዖን ጋር የነበሩት ሰዎች ሁሉ በአዩት ነገር ተደነቁ፡፡

 

አያችሁ ልጆች ስምዖን ጌታችን ያለውን ነገር ሁሉ ስላደረገ ሌሊቱን ሙሉ ማጥመድ ያቃተውን ዓሣ መረብ እስኪቀደድ ድረስ ማጥመድ ቻለ፡፡ እኛም እግዚአብሔር አምላክ የሚያዘውን ነገር ብንሠራ ከምንፈልገው በላይ ይሰጠናል፡፡

ልጆች በመጨረሻም ዓሣ አጥማጅ የነበሩት ስምዖን ያዕቆብና ዮሐንስ ዓሣ ማጥመዳቸውን ትተው ጌታችንን ተከተሉት፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

አትዋሹ(ለሕፃናት)

 

በአዜብ ገብሩ

በድሮ ጊዜ ክርስቲያኖች በአንድነት ይኖሩ ነበር፡፡ በመካከላቸውም የሁሉ ገንዘብ በአንድነት ነበር አንጂ “ይህ የእኔ ገንዘብ ነው” የሚል አልነበረም ከእነርሱም አንድም ችግረኛ አልነበረም፤ ቤትና መሬት ያላቸው ሁሉ እየሸጡ ገንዘቡን ያመጡ ነበር፡፡

 

 

አምጥተውም በሐዋርያት እግር ስር ያስቀምጡ ነበር፡፡ ሐዋርያትም ለእያንዳንዱ እንደፍላጎቱ ይሰጡ ነበር፡፡ ሐዋርያት ስሙን ዮሴፍ እያሉ የሚጠሩት በርናባስ የተባለ ሰው ነበር፡፡ የእርሻ መሬትም ነበረው፡፡መሬቱንም ሸጦ ገንዘቡን በሐዋርያት እግር ስር አስቀመጠው ከሐዋርያትም ማኅበር ተቀላቀለ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ልጆች ሐናንያና ሰጲራ የተባሉ ባልና ሚስቶች ነበሩ፡፡ እነዚህ ባልና ሚስቶች መሬታቸውን ሸጡ፡፡ እርስ በርሳቸውም ተማከሩና ከሸጡት ዋጋ ግማሹን ለራሳቸው ወሰዱና የሸጥነው በዚህ ዋጋ ነው ብለው ግማሹን በሐዋርያት እግር ስር አስቀምጠው ከማኅበሩ ለማቀላቀል ይዘው ሄዱ፡፡ ያደረጉትን ማንም የሚያውቅባቸው አልመሰላቸውም ነበር፡፡ ነገር ግን ይህን ሁሉ ነገር እግዚአብሔር ያውቃል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ውስጥ ነበርና ያደረጉትን ነገር ያውቅ ነበር፡፡

 

ቅዱስ ጴጥሮስም ለሐናንያ እንዲህ አለው “ሰውን ሳይሆን መንፈስ ቅዱስን ለምን ታታልላለህ መጀመሪያም ሳትሸጠው ያንተ አልነበረምን አሁንስ ከሸጥነው በኋላ ያንተ አይደለምን ይህንን ነገር ለምን በልብህ አሰብሀ” አለው ሐናንያም ይህን በሰማ ጊዜ ወድቆ ሞተ፤ ሰዎችም ተሸክመው ወስደው ቀበሩት፡፡ ይህ ከሆነ ከሦስት ሰዓት በኋላም ሚስቱ ሰጲራ መጣች፡፡ ባልዋ የሆነውን ሳታውቅ ገባች፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “እስኪ ንገሪኝ መሬታችሁን የሸጣችሁት በዚህ ዋጋ ነውን” አላት፡፡ እርሷም “አዎ” አለች፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “የእግዚአብሔርን መንፈስ ትፈታተኑት ዘንድ እንዴት ተባበራችሁ አነሆ ባልሽን የቀበሩት ሰዎች በበር ናቸው አንቺንም ይወስዱሻል” አላት፡፡ ወዲያውም ወድቃ ሞተች፤ ሰዎቹም ወስደው ቀበሩአት፡፡

 

ልጆች እኛም ውሸት ስንናገር እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ሥራ እየሰራን እና የሌሎች ሰዎችን እምነት እያጣን መሆኑን ልናውቅ ይገባል፡፡ የምንዋሽ ከሆነ እግዚአብሔር በጣም ስለሚወደን ከውሸታችን እንድንመለስ ይታገሰናል፡፡ ካልተመለስን ግን በረከቱን ከእኛ ይወስድብናል፡፡ ስለዚህ ይህን ማስወገድ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ስለሚያስቷችሁ ሰዎች ይህንን ጽፌላችኋለሁ 1ኛ ዮሐ.2፥27

ቀን፡ ነሐሴ 6/2003 ዓ.ም.

ሐሰት አንናገርም፤ እውነትንም አንደብቅም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ የተነጣጠረው የ”ተሐድሶ” ዘመቻ ውጥን ብዙ ዐሥርት ዓመታት ያለፉት ቢሆንም ከ1992 ዓ.ም. የካቲቲ ወር ጀምሮ ግን ማኅበረ ቅዱሳን ተጨባጭ በሆኑ የምስልና የድምፅ ማስረጃዎች ዘመቻውን በማጋለጥ የቤተ ክርስቲያናችን ቅዱስ ሲኖዶስ ውግዘት ማስተላለፉ ይታወቃል፡፡ ከዚያ በኋላ “ተሐድሶ” ስልቶቹን በመቀያየር ሃይማኖታችንን ለማጥፋትና በሌላ ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮ ለመተካት የሚያደርገውን ሩጫ ቀጥሏል፡፡ በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን ካለፈው ነሐሴ 2002 ዓ.ም ጀምሮ ይፋዊ የሆነ ከእነዚህ ሴረኞች ቤተ ክርስቲያንን የመጠበቅ እንቅቃሴ ጀምሯል፡፡ የሐመር መጽሔት ልዩ እትምን በማዘጋጀት የተጀመረውን አገልግሎት በሌሎችም በኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች ከካህናቱ ከሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ፊት ለፊት በተደረጉ ውይይቶች በመታገዝ ሰፊ ግንዛቤ መፍጠር ተችሏል፡፡ በዚህም የ”ተሐድሶ”ን ምንነት፣ መሠረት፣ ግብና ዓላማ፣ ስልት፣ ያለበትን ደረጃ፣ በሌሎች እኅት አብያተ ክርስቲያናት ፈጥሮት የነበረውን ቀውስና መዘዝ፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ዒላማ ለማድረግ በይፋ በተለያዩ የኅትመት ውጤቶች እያደረገ ያለውን እንቅስቃሴ ለማብራራት ጥረት ተደርጓል፡፡

ይህንን በማድረግ ሂደት ውስጥ ይህንን ቤተ ክርስቲያንን የመጠበቁን እንቅስቃሴ ለማጨናገፍ የተሐድሶ” አራማጅ ቡድኖች የተለያዩ ስያሜዎችንና አካላትን በመጠቀምና “የተሐድሶ” እንደ ሸረሪት ድር ሠርቶት የነበረውን የጥፋት መረብ ሳይበጣጠስና በውስጥም በውጭም የሠራው መሠረት ሳይናድ ለማስቀጠል ባለ በሌለ ኃይሉ እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡ ይሁን እንጂ እያንዳንዱ ምእመን በእግዚአብሔር ረድኤት የዕለት ከዕለት ተግባሩን ከማከናወን ጋር የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ በንቃት መከታተልና መቆጣጠር በሚችልበት ደረጃ ላይ እየደረሰ ነው፡፡

 

በዚህ ተስፋ እየቆረጠ ያለው የ”ተሐድሶ” መሠሪ ኃይል ከቅርብ ጊዜ ጀምሮ በተለያዩ ተላላኪዎቹ በኩል ሊነዛ የፈለገው ተራ ማታለያ “ተሐድሶ የለም”፣ “ተሐድሶ” የሚል ነገርን የፈጠረው ማኅበረ ቅዱሳን ነው” የሚለውን አባባል ነው፡፡ ይህን አካሔድ ተራ ማታለያ ነው የምንለው የ”ተሐድሶ” መኖር ሊስተባበልበት የማይችልበት ደረጃ ላይ መሆኑን ራሱ “ተሐድሶ” አለመረዳቱ ነው፡፡ መሣሪያ አድርጎ የተጠቀመባቸው መነኮሳትና ካህናት በየፕሮቴስታንቱ አዳራሽ ሲጨፍሩ እየታየ፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የቅዱሳንን ገድልና ድርሳን እንደልቦለድ የሚቆጥሩ ጋዜጣና መጻሕፈት እንዳሸን እየተሠራጩ፣ ዕቅድና ስልት አውጥቶ እየሠራ መሆኑን ራሱ “ተሐድሶ” በሚዲያዎቹ እየገለጸልን፣ ቤተ ክርስቲያን ከዕለት ዕለት እየተፈተነችበት፣ ከጥቅመኞችና የሥነ ምግባር ችግር ካለባቸው በቤተ ክርስቲያንኒቱ አስተዳደር ውስጥ ካሉ አንዳንድ ግለሰቦች ጋር በማበር አያወካት እየታየ “ተሐድሶ የለም” የሚለው ልፈፋ የዘገየ ስልትና ተራ ማታለያ ከመሆን አይዘልም፡፡

 

ከዚሁ ጋር ተያይዞ የታየው ሌላው አስደንጋጭ ነገር በቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር ውስጥ ያሉ አንዳንድ አካላት “ተሐድሶ የለም” በሚለው ሐሳብ ተስማምተው በአንዳንድ መድረኮች በቀጥታና በተዘዋዋሪ ይህንኑ አስተሳሰብ የሚያጸና አስተያየት ሲሰጡ መታየታቸው ነው፡፡ እነዚህ አካላት ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ ቀደም የችግሩን መኖር አምኖ፣ አሳማኝ ማስረጃዎች ቀርበውለት ውግዘት ማስተላለፉን ዘንግተውና በተለያዩ ዘመቻዎች “ተሐድሶ” ቤተ ክርስቲያን ላይ የሚወረውረውን ፍላጻ ከምንም በመቁጠር የ”ተሐድሶ” ሴራ ታይቶ እንዳልታየ፣ ተሰምቶ እንዳልተሰማ ሆኖ በምእመናን እንዲታለፍ በመቀስቀሳቸው ብዙዎችን ከማሳዘናቸውም ባለፈ ከፍተኛ ጥርጣሬ አሳድሯል፡፡ እነዚሁ ወገኖች ሐሰትን ሊነግሩን እውነትንም ሊደብቁን የፈለጉበት ምክንያት በሂደት ግልጽ እየሆነ የሚሔድ ሆኖ ሁሉም አካላት ግን የእነዚህን ወገኖችና የመሰሎቻቸውን አቋም እንዲያጤኑ ማኅበረቅዱሳን መልእክት ለማስተላለፍ ተገዷል፡፡

 

“ተሐድሶ የለም” እያሉ በተለያየ መንገድ ለሚነዙት ማደናገሪያዎች ማብራሪያና ማስተባበያ እንዲሰጥባቸው የአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ያነሡትን ጥያቄ ተገቢ መሆኑን ማኅበራችንም ያምንበታል፡፡ እነዚሁ አካላት በዚሁ አቋማቸው የመጽናት ፍላጎት ካላቸው ግን “ተሐድሶ” በአደባባይ በሠራቸው ፀረ ቤተ ክርስቲያን ዐዋጆች፣ ስድቦች፣ በጋዜጣ፣ በመጽሔትና በመጻሕፍት በሚያሠራጫቸው የተደበላለቁ ፕሮቴስታንታዊ አስተምህሮዎች ይስማማሉ ወደሚል መደምደሚያ ሊያደርስ ይችላል፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ በተሐድሶ ላይ የምናደርገውን ዘመቻ የሚያደናቅፍ ለየትኛውም ፀረ ቤተ ክርስቲያን እንቅስቃሴ በር የሚከፍት በመሆኑ ለቤተ ክርስቲያን ህልውና፣ አስተምህሮ እና ሥርዐት በመቆም ችግሩን በመቅረፍ ሂደት ማኅበረ ቅዱሳን እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ የድርሻውን ለመወጣት ያለውን መንፈሳዊ ቅናት ምን ጊዜም ይገልጻል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን ማኅበር ሆኖ በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ የተቋቋመበት ዓላማ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ነው፡፡ የአገልግሎቱ መገለጫ ደግሞ ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት የቤተክርስቲያኒቱን ዶግማና ቀኖና መጠበቅና ማስጠበቅ እንዲሁም ከአጽራረ ቤተ ክርስቲያን መጠበቅ ካልቻልን የምናገለግላት ቤተ ክርስቲያን ወዴት አለች? በመሆኑም የአዲስ አበባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች የያዙትን “ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ” የሚለው የቅዱሳን መሓላ በእኛና በሁሉም አማኝ ክርስቲያን ደም ውስጥ ማደሩ የግድ ነው፡፡ ስለዚህ በዚሁ ረገድ እውነት እንዲደበቅ፣ ሐሰትም እንዲነገር የሚወዱ አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን መገሰጽ፣ መምከርና ከአባቶች ጋር በመመካከር አስፈላጊውን ክርስቲያናዊ እርምጃ በየደረጃው መውሰድ የሁሉም የክርስቲያን ወገን ግዴታ ነው፡፡ በመሆኑም “ተሐድሶ” በሚል ሥያሜ በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን የረጅም ጊዜ ዕቅድና ስልት የቤተ ክርስቲያንን ህልውና ለመፈታተን፣ አስተምህሮዋንና ሥርዐቷን ለመናድ በከፍተኛ መዋዕለ ንዋይ እና ዕቅድ እየተደረገ ያለው ዘመቻ ያለና ተጨባጭ እውነታ እንጂ ማኅበረ ቅዱሳን ከመሬት ተነሥቶ ያወራው አለመሆኑን ማኅበረ ቅዱሳን በአጽንኦት ያሳስባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- ሐመር 19ኛ ዓመት ቁ.3 ሐምሌ 2003 ዓ.ም

የ6 ወር የሥራ አመራር ስብሰባ ውሳኔዎችን አስመልክቶ ከማኅበሩ የሕዝብ ግንኙነት አገልግሎት የተሰጠ መግለጫ

በማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት ያደረገው የ6ወሩ የሥራ አመራር ስብሰባ ወሳኔዎችን አስመልቶ ከማኅበሩ ሕዝብ ግንኙነት አገልግሎት የተሰጠ መግለጫ።
mariam[1].gif

አስደናቂው ሞት

ዲ/ን ታደለ ፋንታው
ነሐሴ 1/ 2003 ዓ.ም.

ክብረ ድንግል ማርያም

እግዚአብሔር ዘላለማዊ ኃይሉንና አምላክነቱን ለዓለም ከገለጸበት ታላቅ ሥራ መካከል በእመቤታችን በቅድስት ድንግል mariam[1].gifማርያም የገለጸው ድንቅ ሥራው በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ቀዳሚውን ሥፍራ ይይዛል፡፡ ይህንን ሁኔታ ድንግል ማርያም “ብርቱ የሆነ እርሱ ታላቅ ሥራን በእኔ አድርጓል ስለዚህም ምክንያት ፍጥረት ሁሉ ያመሰግኑኛል” ሉቃ.፩፥፵፱/1፥9/ በማለት ገለጸችው፡፡ ቅድሰት ኤልሳቤጥም የጌታዬ እናት” አለቻት /ሉቃ.፩፥፵፫/1፥43/ “መልአኩ ቅዲስ ገብርኤል ከሴቶች መካከል ተለይተሽ የተባረክሽ ነሽ” /ሉቃ.፩፥፳፰/1፥28/ አላት፡፡ ቅዱስ ዳዊት ልጄ ይላታል መዝ.፵፬፥፱/44፥9/ ሰሎሞን እኅቴ ይላታል /መኃ.፭፥፩/5፥1/ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስም እናት ሆና ተሰጠችው /ዮሐ.፲፱፥፳፮/19፥26/ ይህንን ድንቅ ሥራ ውስንና ደካማ የሆነ አእምሮ ሊገነዘበው ከሚችለው በላይ ነው፡፡

ቅዱስ አግናጢዎስ ዘአንጾኪያ ለኤፌሶን ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ እንደገለጸው” የቅድስት ማርያም ዘለዓለማዊ ድንግልና፤ አማኑኤልን መውለዷ፤ የማይሞተው ጌታ ሞት” እነዚህ ሦስቱ ከዚህ ዓለም ጥበበኞችና ገዢዎች የተሰወሩ ምሥጢራት ነበሩ፤ እነዚህ ድንቅ ምሥጢሮች በራሳቸው ከንግግርና ከቋንቋዎች ሁሉ በላይ ሁነው የሚነገሩ በእግዚአብሔር የዝምታ መጎናጸፊያ የተጠቀለሉ ድብቅና ጣፋጭ ምሥጢሮች ናቸው ይላል፡፡

ምስጋናዋ የበዛለት ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊ “አቤቱ መሰንቆ ልቡናዬን አነቃቃ የልቤንም እንዚራ፤ ድምፁን ከፍ አድርጎ የዳዊት ልጅ የሆነችውን የጌታውን እናት ድንግል ማርያምን ያመሰግናት ዘንድ፥ ለዓለም ሕይወት የሚሰጠውን የወለደች እናቱ የሆነች እርሷን ከፍ ከፍ ያደርጋት ዘንድ” ብሏል፡፡ በሌላም አንቀጽ “ከሕሊናት ሁሉ በላይ ለሆነ ለዚህ ነገር አንክሮ ይገባል፤ ምድራዊት ሴት ፈጣሪዋን ወለደችው እርሱም እናቱን ፈጠረ” አለ፡፡ ስለ እነዚህ ነገሮች ሁሉ ምን ማለትን እንችላለን? እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ስለ ድንግል ማርያም ያልተናገረበት ጊዜ ያላናገረው ቅዱስ እንደሌለ እንመለከታለን፡፡

በእግዚአብሔር በሰውና በመላእክቱ ፊት የከበረ ሰው መታሰቢያው ለዘለዓለም ነው፡፡ በቤቱ በቅጥሩ የማይጠፋ የዘለዓለም ስምን ይቀበላልና፡፡ /ኢሳ.፶፭፥፫/55፥3/ ይህንን ታላቅ በረከት እንደሚሰጣቸው የተናገረ የማይዋሸው ቅዱስ እግዚአብሔር ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ወልድ እናት ከድንግል ማርያም የበለጠ በሰውና በእግዚአብሔር ዘንድ የከበረ ማንን ልንጠራ እንችላለን? ከእርሷስ ሲታሰብ ሊከበርም የሚችል በቅድስና ሕይወት ያለፈ ማን ይኖራል?

አስቀድሞ ሁሉን ያዘጋጀ እግዚአብሔር ነው፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ፍጥረቱንና ዓለሙን ለማዳን የመረጠው ጊዜ በደረሰ ጊዜ ከድንግል ማርያም በድንግልና ተወለደ፡፡ አስቀድሞ በመልአኩ አፍ እንዳናገረ ክብሩ በእርሷ ላይ ታየ /ኢሳ.፷፥፪/60፥2/ ማኅፀኗን ከተማ አድርጎ ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በእርስዋ አደረ፡፡ በእመቤታችን ያደረ መንፈስ ቅዱስ “ያነጻቸው ዘንድ ይቀድሳቸውም ዘንድ በሥጋም በነፍስም መርቶ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ያገባቸው ዘንድ በነቢያት በሐዋርያት ላይ እንዳደረው አይደለም፤ ከሦስቱ አካል አንዱ አካል እግዚአብሔር ወልድ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየስስ ክርስቶስ ከሥጋዋ ሥጋን ከነፍስዋ ነፍስን ነስቶ ፍጹም ሰው ፍጹም አምላክ ሆነ እንጂ፡፡ ቅዱስ ሉቃስ ይህን ዘለዓለማዊ እውነት “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፤ የልዑል ኃይልም ይጸልልሻል ስለዚህ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል” /ሉቃ.፩፥፵፭/1፥45/ በማለት ገልጾታል፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ደራሲና ገጣሚ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ “የእስራኤል ንጉሥ በእስራኤል ልጅ አደረ፤ የዳዊት አምላክ ከዳዊት ልጅ ሥጋን ለበሰ፤ የዕብራውያን ጌታ በዕብራውያን ልጅ ማኅፀን ተወሰነ፡፡ ለአብርሃም የዕብራይስጥ ልሳን ያስተማረው ከቀድሞም ያልሰማውን ልሳን እንዲናገር አፉን ጆሮውን የከፈተለት ከዕብራዊት ድንግል ተወለደ፤ በድንግልና ወተት አደገ፤ ጥቂት ጥቂት እያለ አደገ፥ የሕፃናትን ሥርዓት እንዳያጎድል አፉን የሚፈታባት ዘመን እስኪፈጸም ጥቂት ጥቂት እያለ በዕብራይስጥ ልሳን ሲናገር ኖረ፡፡ ለሙሴ በዕብራይስጥ ልሳን በጣቶቹ የተጻፉትን ዐሠርቱ ቃላት በድንጋይ ሰሌዳ የተጻፈውን የሰጠው የዕብራይስጥ ፊደል ለመማር ከመምህር እግር በታች ተቀመጠ፡፡ የባቢሎን አውራጃ በምትሆን ሰናዖርም የፍጥረትን ሁሉ ቋንቋ የበተነ እርሱ የአሕዛብን ቋንቋ እንደማያውቅ ሁሉ እናቱ አፍ በፈታችበት ልሳን በዕብራይስጥ ልሳን ሲናገር ኖረ፤ ጆሮ ይህንን ነገር ከመስማት የተነሣ የሚለመልምበት ይህ ነገር ዕጹብ ድንቅ ነው፡፡ ለዚህ አንክሮ ይገባል አለ፡፡ ይህ በሰው ጥበብ በብራናና በቀለም የተጻፈ እውነት ሳይሆን ለድኅነት በተጠሩ ሰዎች ሁሉ ልቡና በአምላክ ጥበብ የተጻፈ እውነት ነው፡፡

አስደናቂው የድንግል ማርያም ሞት

ኢትዮጵያዊው ሊቅ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በመጽሐፈ አርጋኖን ድርሰቱ ከሚያሰጥመው ባሕር ሞገድ የተነሣ የማትነቀነቅ፥ መልኅቆቿም በሦስቱ ሥላሴ ገመድ የተሸረቡ ናቸው ይህቺ ደግሞ ከነፋሳት ኃይል የተነሣ የማትናወጥ በጭንጫ ላይ ያለች የዕንቈ ባሕርይ ምሰሶ ናት፤ እርሷን የተጠጋ መውደቅ መሰናከል የለበትም” የሚላት እመቤታችን ሞት አይቀርምና እርሷም እንደሰው የምትሞትበት ጊዜ ደረሰ፡፡ እግዚአብሔር አያዳላምና፡፡ /ሮሜ.፪፥፲፩/2፥11/ ቅድስት ድንግል ማርያም የኃያሉ እግዚአብሔር እናቱ፥ መቅደሱ፥ ታቦቱ፥ መንበሩ ሆና እያለ ሞትን መቅመሷ በራሱ የሚያስገርም ምሥጢር ነው፡፡ ከቤተ ክርስትያን ወገን ሞትን እንዳያዩ የተወሰዱ ቅዱሳን ሄኖክ፥ ኤልያስ፥ ሌሎችም እንዳሉ የቅዱሳት መጻሕፍት ምስክርነት አለ፡፡ ይህ ከኅሊናት ሁሉ በላይ የሆነው ምሥጢር ርቀቱ በመጽሐፈ ዚቅ እንዲህ ተብሏል፡፡ “ለምንት ይዜኃር ኃያል በኃይሉ ወባዕል በብዝኃ ብዕሉ ኢያድለወ  ሞት ክርስቶስ ለሥጋ አባሉ ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የአጽብ ለኩሉ፡፡ ኃይለኛ በኃይሉ ለምን ይታጀራል? ባለ ጸጋም በሀብቱ ብዛት፡፡ ክርስቶስ ለአካሉ አላዳላም፤ ሞትስ ለሟች ይገባዋል የእመቤታችን የቅድስት ማርያም ሞት ግን አስደናቂ ነው”

እመቤታችን ያረፈችው በጥር ሃያ አንድ ቀን ነው፤ በአባት በእናቷ ቤት ሦስት ዓመት ኖረች፤ ዐሠራ ሁለት ዓመት በቤተ መቅደስ ኖረች፤ ከልጇ ጋር ሠላሣ ሦስት ዓመት ከሦስት ወራት፤ ከጌታ ስቅለት በኋላ ዐሥራ አምስት ዓመታት ኖረች፤ ጌታን የጸነሰችበትን ወራት ስንጨምር በዚህ ዓለም በሥጋ የቆየችበት ጊዜ ስድሳ አራት ዓመት ይሆናል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ትውፊት የድንግል ማርያም ሞት በሚከተሉት ምክንያቶች እንደሆነ ያስረዳል፤ የመጀመሪያው “ለመለኮት ማደርያ ለመሆን የበቃችው ኃይል አርያማዊት ብትሆን ነው እንዷ ምድራዊት ሴትማ እንደምን ሰማይና ምድር የማይችለውን ልትሸከመው ይቻላታል?” የሚሉ ወገኖች ነበሩና በርግጥም እግዚአብሔር ወልድ የተዋሐደው የሰው ልጆችን ሥጋ እንጂ የመላእክትን አለመሆኑን ለማጠየቅ ነው፡፡ ይህንን ሁኔታ ቅዱስ ጳውሎስ ሲያስረዳ “እንግዲህ ልጆቹ በሥጋና በደም ስለሚካፈሉ፥ እርሱ ደግሞ በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን በሞት እንዲሽር፥ ይኸውም ዲያብሎስ ነው፥በሕይወታቸው ሁሉ ስለሞት ፍርሃት በባርነት ይታሰሩ የነበሩትን ሁሉ ነጻ እንዲያወጣ፥ በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ፡፡ የአብርሃምን ዘር ይዟል እንጂ የያዘው የመላእክትን አይደለም” አለ፡፡ /ዕብ.፪፥፲፬-፲፭/2፥14-15/ በዚህም ድንግል ማርያም የአዳም ዘር መሆኗ ታወቀ፡፡ ሁለተኛው ቅዱስ ያሬድ እንዳለው ጌታችን በፍርዱ አድልዎ የሌለበት መሆኑ ይታወቅ ዘንድ ነው፡፡ ሥጋ የለበሰ ሁሉ በለበሰው ሥጋ ሞትን ይቀምስ ዘንድ የግድ ነውና፡፡

ትንሣኤ

በቃል መነገሩ በአንደበት መዘከሩ ለአምላካችን ለልዑል እግዚአብሔር ክብር ምስጋና ይግባውና “ከሞት ወጥመድ በላይ እንኳን የሆነ ሌላ ኃይል አለ፤ ይሄውም ሞት ፈጽሞ ሊያሸንፈውና ሊገዳደረው የማይችል የእግዚአብሔር መለኮታዊ ኃይል ነው፡፡ በሰይጣን ዘንድ ያለው የሞት ኃይል ነው ሕያው እግዚአብሔር የሕያዋን አምላክ ነውና ሞት ሊያሸንፈው ሊደርስበትም የማይችለውን ሕይወት ይሰጣል፡፡ ይህንን እግዚአብሔር የሚሰጠውን ሕይወት ሰይጣን በእጁ ሊነካው ከቶውንም አይችልም፡፡ እግዚአብሔር ለሙታን ሕይወትን ይሰጣል የሞትና የሕይወት ባለቤት ነው፡፡” የእመቤታችን ድንግል ማርያም ዕርገት

ከሞት ሥልጣንና ኃይል በላይ የሆነው ይኸው የእግዚአብሔር መለኮታዊ ሥልጣን የድንግል ማርያምን ሥጋ መልካምም ሆነ ክፉ ለሠሩ ሰዎች ዋጋ ይከፍል ዘንድ ለፍርድ እስከሚመጣበት ጊዜ ድረስ በመቃብር ውስጥ ተጠብቆ እንዲቆይ፤ ፈርሶና በስብሶ በምድር ላይ እንዲቀር አላደረገም፡፡ ከሙታን መካከል ተለይታ ተነሥታለች፡፡ እንድትነሣም ያደረገ የጌታ ኃይል ነው፤ በራሷ የተነሣች አይደለችም፡፡ መንፈስ ቅዱስ በድንግልና ጸንሳ በድንግልና መውለዷን በትንቢት እንዳናገረ ትንሣኤዋንም በትንቢት ሲያናግር ኑሯል፡፡ ይህ ታላቅ ምሥጢር በቅዱስ ዳዊት አንደበት “ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅደስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦትም” /መዝ.፻፴፩፥፰/131፥8/ ብሎ ገልጾታል፡፡ ቅዱስ ዳዊት በዚህ የትንቢት ክፍል ትንሣኤዋን አስረድቷል፡፡ ታቦት የጽላቱ ማደሪያ ነው፡፡ በታቦቱ ውስጥ የሚያድረው በእግዚአብሔር ጣቶች የተጻፈው ሕጉ ነው፡፡ ይህ እግዚአብሔር ያከበረው ነገር ሆኖ ሊመጣ ላለው ነገር ማሳያ ነው፡፡ እውነተኛዋ ታቦት ማርያም ናት፡፡ ሙሴ በተቀበለው ታቦት ውስጥ ያለው ጽላት በውስጡ የያዘው ሕጉን ነው፤ በድንግል ማርያም ላይ ያደረው ግን የሕጉ ባለቤት ነውና፡፡ ከፍጡራን ከፍ ከፍ የማለቷ ድንቅ ምሥጢርም ይህ ነውና፡፡ ትምክህቷም፣ ትውክልቷም ጌታ እግዚአብሔር እንደሆነ በወንጌላውያኑ ተነግሮላታል፡፡ መንፈስ ቅዱስ ያላናገራቸውን ከልባቸው አንቅተው አይጽፉምና፡፡ እርሷም” ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴትን ታደርጋለች” አለችን /ሉቃ.፩፥፵፯/1፥47/፡፡ ይህ ቃል ንጽህናዋ ቅድስናዋ በተረዳ ነገር ታውቆ ፍጥረት ሁሉ ከልቡ ከሚያከብራት እመቤት የተነገረ ቃል እንጂ ራሳቸውን ያለአጥርና ያለከልካይ አድርገው ቃሉን ከሚሸቃቅጡ ሰዎች ወገን የተሰጠ ምስክርነት አይደለም፡፡

እርስዋ ከኪሩቤል ትበልጣለች፤ ከሱራፌልም ትከብራለች ጌታችን የሱራፌልን፥ ኪሩቤልን ባሕርይ ባሕርዩ አላደረገም፡፡ የመላእክትንም ባሕርይ እንደዚሁ፥ የእርሷን አካል ባሕርዩ አደረገ እንጂ፡፡

የክርስቲያኖችን ትንሣኤ ሙታን የሚመሰክር ልዕልና

ከምድር ሰዎች ሁሉ ጥበበኛ የሆነው ሰሎሞን እንዲህ አለ፡- “ወዳጄ ሆይ ተነሽ፤ ውበቴ ሆይ ነይ፡፡ እነሆ ክረምት አለፈ፥ ዝናሙም አልፎ ሄደ አበቦች በምድር ላይ ተገለጡ፥ የዜማም ጊዜ ደረሰ፥ የቁርዬም ቃል በምድር ላይ ተሰማ”፡፡ /መኃ.፪፥፲-፲፬/2፥10-14/ ይህ ትንቢት የዚህ ዓለም ድካሟ ሁሉ መፈጸሙን ያስረዳል፡፡ ልጇን ይዛ ከሀገር ሀገር በረሀብና ጥም የተንከራተተችበት ጊዜ አሁን አለፈ፡፡ ታናሽ ብላቴና ሳለች ልጇን አዝላ በግብጽ በረሃ የተቀበለችው መከራ ሁሉ ፍጻሜ አገኘ፡፡ ከእግረ መስቀል ሥር ወድቃ የልጇን የቆሰለ ገላ እየተመለከተች የደረሰባት ልብ የሚሰነጥቅ ኀዘን ወደ ደስታ ተለወጠ፡፡ በነፍሷ ሰይፍ ያልፋል ተብሎ የተነገረው ልብ የሚሰነጥቅ መከራ እንደ ነቢዩ ቃል ትንቢት የሚቀጥልበት ጊዜ ተፈጸመ፡፡ እርሷ ባለችበት ሥፍራ የሕይወት ትንሣኤ ያላቸው ሰዎች ይሆኑ ዘንድ አስቀድማ ከሙታን ተለይታ በመነሣት የተጠበቀልን ተስፋ ማሳያ ሆነችን፡፡ በእግዚአብሔር መንግሥት ስደት መከራ ኃዘን ሰቆቃ የለም፤ መገፋት መግፋትም የለም፡፡

እመቤታችን ትንቢቱ የተፈጸመባት ሁና እያለ ከማንኛውም ሐዋርያ በላይ ለእግዚአብሔር ቃል መስፋፋት የወንጌል ዘር በተዘራበት ቦታ ሁሉ ነበረች፡፡ ለመንግሥቱም እንደሚገባ ሁና ኑራለች፡፡ በማኅፀን የተጀመረው የማዳን ሥራ፤ ፍጻሜውን ያገኘው በቀራንዮ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ የጌታ ልደቱና ጥምቀቱ፣ ሞቱ ትንሣኤው ዕርገቱና ዳግመኛ መምጣቱ በነገረ ድኅነት ትምህርታችን እጅግ ጠቃሚ የሆኑ ምሥጢራት ናቸው፡፡ ቤተልሔም የሥጋዌውን ምሥጢር ሲያሳይ ዮርዳኖስ ቀዳማዊ ልደቱን ያሳያል፡፡ የመጀመርያው የእኛ ባሕርይ ሲሆን ሁለተኛ የጌታ የራሱ የባሕርይ ገንዘቡ የሆነ ነው፡፡ እርሱ የሰው ልጅ ሆነ፤ እኛ ደግሞ የእግዚአብሔር ልጆች ሆንን ይህ ሁሉ የተደረገው ከድንግል ማርያም በነሳው ሥጋ ነው፡፡ እርሱ የእኛን ተፈጠሮ ገንዘቡ ስላደረገ፤ እኛ ደግሞ የእርሱን ቅድስና ገንዘብ በማድረግ የመንግሥቱ ተካፋዮች ሆንን፡፡ የእኛ የሆነው ሁሉ የእርሱ የእርሱ የሆነው የእኛ በመሆኑ ከፍ ከፍ እናደርገዋለን፡፡ ለዚህ ክብር በቀታ ያከበረችንን ከእግዚአብሔር ጋር ያዛመደችንን እመቤት እንደምን አናከብራትም?

የእኛ መንፈሳዊ ልደት የተገኘው ጌታ በሥጋ ከቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደው ልደት ነው፡፡ “የቅድስት ድንግል ማርያም ማኅጸን አምላክና የሰው ልጆች የተገናኙበት፤ አምላክና ሰው የተዋሐዱበት መካነ ምሕረት ነው፡፡ እግዚአብሔር ዙፋኑን ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀናት የዘረጋበት መካነ ሰላም ነው፤ የእግዚአብሔር ዙፋን ፍጹም በማይናወጥና ጸጥታ በነገሠበት ስፍራ የሚዘረጋ የክብር ዙፋን ነው፡፡ ይህም ዙፋን የቅድስት ድንግል ማርያም ማኅጸን ነው፡፡”

በቀራንዮ አደባባይም በኀዘን ነበረች፡፡ ሐዋርያት ጉባኤያትን ሲያበዙ አብራቸው ነበረች፤ ይህ ሁሉ ታላቅ ሥራ ከተፈጸመ በኋላ ዓረፍተ ዘመን ገታት፡፡ በሥጋ ዓረፈች፡፡ ያረፈችው በጥር ሃያ አንድ ቀን ነው፤ ሐዋርያትም ሊቀብሯት ሲሹም ከአይሁድ ክፋት የተነሣ ልጇ ሌላ ክብርን ደረበላት ከጌቴሴማኒ ሥጋዋ ተነጥቆ በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር እስከ ነሐሴ ዐሥራ ስድስት ቀን ለሁለት መቶ አምስት ቀናት ቆይታለች፡፡ ልጇ ወዳጇ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን በሥልጣኑ እንዳሸነፈ የልጇ መለኮታዊ ኃይል ሞትን አሸንፋ እንድትነሣ አደረጋት፤ ጠቢቡ ሰሎሞን ስለ ትንሣኤዋ የተናገረው ቃል ተፈጸመ፡፡ ሊቁ “ለዛቲ ብእሲት ሠረቀ ላዕሌሃ ብዕለ ጸጋሁ ለአብ ወአግዓዛ እምእኩይ ውስተ ሰናይ እሞት ውስተ ሕይወት፤ በድንግል ማርያም ላይ የአብ የባለጸግነቱ ብዛት ተገለጠ ከሞት ወደ ሕይወት ከክፉ ዓለም ወደ በጎ ዓለም አሸጋግሯታልና፤ ያለው ይኸንን ነው”፡፡ ከእንግዲህ ወዲያ ልጇ ሲንገላታ፣ ሲሰደድ ሲገረፍ፣ ሲሰቀል፣ ሲቸነከር ያየችበት ዓለም አለፈ፡፡ አሁን የልጇን ልዕልና ከሚያደንቁ ጋር ታደንቃለች፤ ከፍ ከፍ ከሚያደርጉት ጋር ታከብረዋለች፡፡ ይኸም ከገቡ የማይወጡበት ኀዘን መከራ ችግር በሌለበት ሰማያዊት ሃገር ነው፡፡ ቅዱሳን ሩጫቸውን ጨርሰው የድል አክሊልን የሚቀዳጁበት ሥፍራ ነው፡፡ በዚህም ከፍጡራን ሁሉ ከፍ ባለ በታላቅ ክብርና ጸጋ ለዘላለም እንደምትኖር እናምናለን፡፡

ልመናዋ ክብሯ ፍቅሯ አማላጅነቷ የልጇም ቸርነት በሁላችንም ላይ አድሮ ይኑር፡፡

ምንጭ ፡ ሐመር 18ኛ ዓመት ቁጥር 5