ሦስት አራተኛው መሬት

እንግዳ ተቀባዩ አባ ቢሾይ(ለሕፃናት)

ሐምሌ23፣2003 ዓ.ም
                                                                               አዜብ ገብሩ

እግዚአብሔርን ከሚፈሩ ጻድቅ ከሆኑ ሰዎች የተወለደ አባ ቢሾይ የሚባል አባት ነበረ፡፡ ይህ አባት ለቤተሰቦቹ ሰባተኛ እና የመጨረሻ ልጅ ነው፡፡ አንድ ሌሊት ምን ሆነ መሰላችሁ ልጆች የአባ ቢሾይ እናት ሕልም አየች የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸ፡፡ ጌታ እንዲህ ብሏል፤ “ያገለግለኝ ዘንድ ከልጆችሽ አንዱን ስጭኝ” እናቱም እንዲህ አለች “ሰባቱም ልጆቼ አሉ፤ የፈለግኸውን መርጠህ እንዲያገለግልህ ውሰድ”
መልአኩም አባ ቢሾይን ነካው፤ እናቱ ግን እንዲህ አለች “ከልጆቼ ሁሉ እርሱ ደካማ ነው፤ እግዚአብሔርን የበለጠ እንዲያገለግሉት ከሌሎቹ ልጆቼ ምረጥ” መልአኩም እንዲህ አላት “እግዚአብሔር ያገለግለው ዘንድ የመረጠው እርሱን ነው” ከዚያም አባ ቢሾይ ሃያ ዓመት ሲሆነው ወደ ገዳም ገባ፡፡ አባ ቢሾይ ለእግዚአብሔር ታማኝ የሆነ ሰው ነበረ፡፡ ሁሌም ይጸልያል፣ ለረዥም ሰዓት ይጾማል፣ ቅዱሳት መጻሕፍን ይማራል፣ በቤቱ እንግዳ ተቀብሎ ያስተናግዳል፡፡ እግዚአብሔርን የሚያስደስት  ብዙ መልካም ሥራ ይሠራል፡፡

 

ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቢሾይ ከበአቱ በር ላይ ተቀምጦ ሳለ በጣም የደከመው ሰው ወደ እርሱ ሲመጣ ተመለከተ፡፡ ከተቀመጠበት ተነሣና ያን ሰው ወደ በአቱ እንዲገባና እንዲያርፍ ጠየቀው፡፡ ከዚያም ያን በጣም የደከመው ሰው ውሃ አቅርቦ እግሩን ማጠብ ጀመረ፡፡ እግሩን እያጠበው ሳለም የእግዚአብሔር ድምጽ እንዲህ ሲል ሰማ “የተወደድክ ልጄ ቢሾይ ሆይ አንተ የተከበርክ ሰው ነህ” ወዲያውም የአምላካችንን እግር እያጠበ እንደነበር አስተዋለ፡፡ ተንሥቶም ተንበረከከ እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ እግዚአብሔርም ሰላምን ሰጠው፡፡
 
አያችሁ ልጆች አባ ቢሾይ እግዚአብሔርን አየው ምክንያቱም ትሑት ስለነበረና ዝቅ ብሎ የሌሎችን ሰዎች እግር ያጥብ ስለነበረ ነው፡፡ እኛም እንደ አባ ቢሾይ ትሑት መሆንና ወደቤታችን ለሚመጡት ሰዎች ሁሉ ደግ መሆን አለብን ይህን ካደረግን እግዚአብሔር ለእኛ መልካምን ነገር ያደርግልናል፡፡ በመንግሥተ ሰማይም ስለ ሠራነው መልካም ነገር ሽልማትን ይሸልመናል፡፡

                                                          ወስብሐት ለእግዚአብሔር  

ክብረ ገዳማት

ክብረ ገዳማት( ነሐሴ 1/2003 ዓ.ም

ክብረ ገዳማት

መሠልጠን ማለት ግን ምን ማለት ነው?!

በዲ/ን ቴዎድሮስ በየነ

ሥልጣኔ ሲተነተን አንድ ገጽታ፣ አንድ መልክ፣ አንድ ወጥ ሳይሆን ብዙ መልኮች፣ ብዙ ገጽታዎች እንዳሉት ማጤን ይገባል፡፡

ሥልጣኔ የሰው ልጅ አካባቢውን ለኑሮ እንዲስማማው፣ እንዲመቸው ለማድረግና ለሕይወቱ የተመቻቸ ሥፍራ ለማድረግ የዕለት ተዕለት ተግባር ውስጥ ቀስ በቀስ የተከሰተ ነው፡፡ በዚህ ረገድ ሥልጣኔ ጥንትም የነበረ፣ ዛሬም ያለ፣ ለወደፊትም የሚኖር የሰው ልጅ የተፈጥሮ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ሆኖም ግን ስለ ሥልጣኔ ብይን ሲሰጥ፣ ስለ መግለጫው ሲነገር፣ ስለ ጥቅሙ ሲዘመር፣ ስለ ግቡ /መዳረሻው/ ሲታተት፤ ሥልጣኔ ከቁሳዊ ነገር መሟላትና ከሥጋዊ ድሎትና ምቾት ጋር ብቻ ሲያያዝ ይስተዋላል፡፡ ለዚህም ይመስላል የሥልጣኔን ክስተት በዓይን በሚታዩ፣ አብረቅራቂና ሜካኒካዊ በሆኑ ነገሮች ብቻ እንድናይ ከታች ጀምሮ በትምህርት ቤት እንድንማረው የሆነው፡፡ በሚዲያ ዘወትር እንድንሰማው የተደረገው፡፡ከበደ ሚካኤል ስለ ሥልጣኔ ምንነት ሲናገሩ እንዲህ ይላሉ፡፡

“ሰዎች ራሳቸውን ለማረምና ኑሯቸውን ለማሻሻል ሲሉ በሥጋና በመንፈስ ያፈሩት ከመጀመሪያ ጀምሮ አሁን ድረስ የተከማቸው የሥራ ፍሬ ሥልጣኔ ይባላል፡፡”

በእኚህ ኢትዮጵያዊ ጸሐፊ የሥልጣኔ ምንነት ገለጻ ውስጥ በዚህ ዘመን ሚዛን ላይ ያልወጡ ታላላቅ ቁምነገሮችን አምቆ ይዟል፡፡ ከነዚህም ውስጥ “በሥጋና በመንፈስ” በማለት ለሰው ልጅ የህላዌው መሠረት፣ የደስታው ምንጭ ሥጋዊ ፣/ቁሳዊ/ ነገር ብቻ እንዳልሆነ አስምረውበታል፡፡ መንፈሳዊም ፍሬም ሥልጣኔ እንደሆነ፡፡ ሥልጣኔ ከመጀመሪያ ጀምሮ አሁን ድረስ የተከማቸ የሥራ ፍሬ ነው ሲሉም፤ ሥልጣኔ የዛሬ ሦስት መቶ ወይም አራት መቶ ዓመት ክስተት ብቻ አይደለም ማለታቸው ነው፡፡

ዘመናዊ ሥልጣኔን ከምዕራባውያን ሥልጣኔ ጋር ብቻ አያይዞ የሥልጣኔ መልክና ገጽታ በምዕራባውያን መስታወት ብቻ የሚታይ እንዳልሆነም የጸሐፊው እይታ ያሳያል ፡፡

ዛሬ በብዙ ኢትዮጵያውያን ዘንድ ሥልጣኔ ማለት ምዕራባዊ መስሎ መቅረብ፣ የምዕራብ ቋንቋን መናገር፣ የምዕራባውያንን የአኗኗር ዘይቤ መያዝ ይመስላል፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በኢትዮጵያውያን ሠርግ ሲዘፈን እንደነበረው “የእኛ ሙሽራ ኩሪባቸው በእንግሊዝ አናግሪአቸው” የምዕራብ ቋንቋ መናገር የኩራት ምልክት፣ የሥልጣኔ ምልክት ነበር፡፡ ይህ ግን ስህተት እንደሆነ ኤቪሊንዎ የተባለ አንድ ምዕራባዊ ጸሐፊ ኢትዮጵያ ኋላቀር ነች እያሉ የሚተቹትን በነቀፈበት ጽሑፉ እንዲህ ይላል፡-

“የአንድን ኅብረተሰብ ትልቅነት የምትገምተው አውሮፓን ስላልመሰለ ወይም የ”ሰለጠኑ” አገራትን ስላልመሰለ ሳይሆን በራሱ እምነትና የእሴት ስልት ውስጥ የተቃረነ ነገር ሲሠራ ነው፡፡”

የዚህ መጣጥፍ ዐቢይ ጭብጥ ሥልጣኔ ከራስ እሴት አለመቃረን ነው የሚል ነው፡፡ ሃይማኖታዊ ትውፊታችን፣ ባህላችንና ታሪካችን የኢትዮጵያውያን እሴቶች ምንነትን ይነግሩናል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ዛሬ እዚህ ላይ የምናየው ስለ ከበረው የዳኝነት /ፍትሕ/ ሥርዓት እሴታችን ነው፡፡ በኢትዮጵያ ረዥም ዘመን ታሪካችን የዳኝነት ሥርዓት የተከበረ ነው፡፡ ፈረንጆች “the rule of law /ሕጋዊ ሥርዓት/” የሚሉትን የኢትዮጵያ ሕዝብ “የሕግ አምላክ” ይለዋል፡፡

በቆየው የኢትዮጵያ ባሕል አንድ ሰው ከመንገድ ላይ ባላጋራውን ካየ “በሕግ አምላክ ቁም” በማለት ብቻ ባላጋራውን አስቁሞ የነጠላዎቻቸውን ጫፍ ቋጥረው /ተቆራኝተው/ ያለ ፖሊስ አጀብ ወደ መረጡት ዳኛ ዘንድ ሄደው ፍርዳቸውን ይቀበሉ ነበር፡፡

“በቆረጡት በትር ቢመቱ፤ በመረጡት ዳኛ ቢረቱ፤ የእግዜር ግቡ ከብቱ፡፡” የሚባለውም ለዚህ ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን በቀድሞ ዘመን “የተበደለ ከነጋሽ፤ የተጠማ ከፈሳሽ” ብለው፤ የተጠማ ውሃን እንደሚሻ ሁሉ የተበደለም ጉዳቱን ለንጉሡ አሰምቶ ትክክለኛ ፍርድ እንደሚያገኝ ያምኑ ነበር፡፡ በዚህም ምኞትና ሐሳቡን የፈጸሙ የመንፈስ ልዕልና ደረጃቸውን ያሳዩ ፈታሔ ጽድቅ /እውነተኛ ዳኞች/ በታሪኩ አይቷል፡፡ አጼ ዘርአያዕቆብ /15ኛው መቶ ክ/ዘ/፤ ልጃቸው የደሀ ልጅ ገድሎ በዳኞቻቸው ዘንድ በቀላል ፍርድ ስለ ተለቀቀ ይግባኙን ንጉሡ ወስደው የሞት በቃ ፈርደው እንዳስገደሉት ይታወቃል፡፡ ይህ ምንም ርትዕ ቢሆን፤ ከአብራክ በተከፈለ ልጅ ላይ ሞትን መፍረድ ሐቀኝነት ነው፡፡ በሌላ ዘመንና ቦታም ይህ ተመሳሳይ ታሪክ በትግራዩ ራስ ልዑል ሚካኤል ስሑል /18ኛው መ/ክ/ ተፈጽሟል፡፡ ሁለቱም ከግል ጥቅማቸው በተቃራኒ ቆመዋል፡፡ ይህ ነው ኢትዮጵያዊው መልካም እሴት፡፡ ሁለቱም መሪዎች የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍትሕ ሲጓደል በብርቱ እንደሚያዝን፤ ምንም የተወሰደው ሀብት ዋጋው ያነሰ ቢሆን በዳኝነት መዛባት እጅግ አድርጎ እንደሚቆጭ ያውቃሉ፡፡ “በፍርድ ከሄደችው በቅሎዬ፤ ያለ ፍርድ የሄዳችው ጭብጦዬ ታሳዝነኛለች” የሚል ጽኑ የፍትሕ ጥማት እምነቱ እንደሆነ ያውቃሉ፡፡ እነርሱም የርትዕ ፍርድ ታላቅነት አሳዩት፡፡

ስለዚህም የአንድ ሥልጡን ማኅበረሰብ አንዱ መገለጫው ይህን ከመሰለ ባሕላዊ እሴቱ ጋር አለመጋጨቱ፤ አለመቃረኑ ነው፡፡ ስለ ሥልጣኔ ስናወራ ለሥጋ እርካታ መገለጫ የሆነችውን የአብረቅራቂ ቁስ ሙሌትን ብቻ ይዘን መጓዝ የለብንም፡፡ የከበሩ የባሕልና የታሪክ እሴቶቻችንም የሥልጣኔ ማነጸሪያዎች ናቸው፡፡ የሰው ልጅን ማንነትና ፍላጎት በቁሳዊ ነገር ብቻ መመዘንም፤ ሰውን ከሰውነት ደረጃ ማውረድ ነው፡፡ በዚህ መተማመን ከተደረሰ አንድ ሥልጡን ማኅበረሰብ ለመገንባት በምናደርገው ጉዞ ውስጥ ሥልጣኔን በግንጥል ጌጧ ሳይሆን በሙሉ ክብሯ እንረዳታለን ማለት ነው፡፡

ዛሬ ጊዜና ታሪክ በሰጡን ኃላፊነት ላይ ያለን ሁሉ “ደሀ ተበደለ ፍርድ ተጓደለ” የማንል ከሆነ፤ ከግል ጥቅም ይልቅ ለብዙኃኑ ጥቅም ካልቆምን? የሰው እንባ እሳት ነው ያቃጥላል ካላልን? ከራሳችን የእምነትና የእሴት ስሌት በተቃራኒ ስለቆምን በእውነት አልሰለጠንም፡፡

ውድ አንባቢዎች አፄ ዘርአያዕቆብና ራስ ልዑል ሚካኤል ስሑል በልባቸው ካለው የእምነትና የእሴት ስሌት በተቃራኒ ያልቆሙበት ምክንያት /ሠልጥነው የታዩበት ምሥጢር/ የሚከተሉት አራቱ ይመስሉኛል፡፡

1. እግዚአብሔር አለ፤ እሱ ይፈርዳል፤ በምንሰጠው ፍርድ እሱ ይመለከታል ብለው ማመናቸው፡፡

2.  ሕሊና አለ፤ እሱን ማምለጥ አይቻልምና ብለው ለሕሊናቸው በመገዛታቸው፡፡

3. ታሪክ አለ፤ ታሪክ ይፋረደናል፤ የምንሠራውን ነገር ለታሪክ ትተነው የምንሄድ ነን፤ ከታሪክ ማምለጥ አንችልም ብለው በጽናት መቆማቸውና፣

4.  ሕዝብ አለ፤ የተደረገውን ስለሚያውቅ ይመለከተናል፡፡ ይታዘበናል፡፡ ከእነዚህ ነገሮች ማምለጥ አንችልም ብለው በመንፈሳዊ ወኔ መቆማቸው ነው፡፡

ስለ እውነተኛ ዳኝነት ከቱባ ባሕላችን ውስጥ መዘን ስናጠና የምናገኘው የትልልቆቹን መሪዎች፣ የከበሩት አበውና፣ የሚደነቁት እመው ያልተዛባ ፍርድ ክዋኔ ምሥጢሩ፤ በምንሠራው ሥራ፤ በምንሰጠው ፍርድ እግዚአብሔር፣ ሕሊና፣ ታሪክና ሕዝብ አለ ብለው ማመናቸው ነው፡፡ ከሰፈር የዕቁብ ዳኝነት እስከ ሀገር ማስተዳደር፤ ከማኅበር ሙሴነት እስከ ቤተ ክርስቲያን መምራት የቻለ ሰው በሚያስተላልፈው ውሳኔና በሚሰጠው ፍርድ ውስጥ ከላይ ያየናቸውን አራቱን የባሕላችንን እሴቶች በልቡናው ጽላት ቀርጾ በእነርሱ መመራት ካልቻለ፡፡ ፍትሕ ትጨነግፋለች፡፡ እውነት ከምድሩ ትጠፋለች፡፡ ፍቅር ጓዟን ጠቅልላ ትበናለች፡፡ ክህደት ታብባለች፡፡ ማስመሰል ትነግሳለች፡፡ ውሸት ትወፍራለች፡፡ ሥልጣኔ ቅዥት ትሆናለች፡፡

ይቆየን…..

 

«ጠቅላላ ጉባኤው አንድነታችንን ፍቅራችንን የምናጸናበት ነው፡፡» ዲ/ን ሙሉዓለም ካሣ

የአዲስ አበባ ማዕከል 17ኛ ጠቅላላ ጉባኤውን ሐምሌ 23 እና 24/ 2003 ዓ.ም ያደርጋል። ጉባኤውን በተመለከተ በማዕከሉ የአባላትና አገልግሎት ማስተባበሪያ ክፍል ኃላፊ ከሆኑት ዲ/ን ሙሉዓለም ካሣ ጋር ያደረግነውን ቆይታ ይዘን ቀርበናልና መልካም ንባብ።

በዘንድሮው ጠቅላላ ጉባኤ የእርስዎ ድርሻ ምንድን ነው?

ለጠቅላላ ጉባኤው አባላትን የሚጠራው የአባላትና አገልግሎት ማስተባበሪያ ክፍል ነው፡፡ በተጨማሪም በተዋቀረው ዐቢይ ኮሚቴ ጥሪዎችንና ቅስቀሳዎችን ማድረግ ነው፡፡

በጠቅላላ ጉባኤው ምን ምን ክንዋኔዎች ይካሄዳሉ?

በጠቅላላ ጉባኤያት እንደማንኛውም ጊዜ የተለመዱ አሠራሮች አሉ፡፡ ለአባላቱ የማዕከሉ የ1 ዓመት የሥራ ክንውን ይቀርባል፡፡ በዚያም ላይ አባላት ይወያያሉ፡፡ ከዚያ ውጭ ለሚቀጥለው ዓመት የተዘጋጀ ዕቅድ ይቀርባል፡፡ ያንንም እቅድ ጠቅላላ ጉባኤው ያጸድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ማዕከሉ ለአባላቱ የሚያዘጋጃቸው የመወያያ አጀንዳዎች ይኖራሉ፡፡ በዚያም ላይ ይወያያሉ፡፡ ተጨማሪ መረጃዎች ካሉ እንዲሁ ለአባላት ይቀርባል፡፡ ከዚያም ውጭ የዋናው ማዕከል ተወካይ የሚያቀርበው ግምገማ ከዚያው ጋር የሚታይ ሲሆን አዲስ የሥራ አስፈጻሚ ምርጫም ይኖራል፡፡

ከጠቅላላ ጉባኤው ጋር በተያያዘ የሚከናወኑ እንቅስቃሴዎች ይኖራሉ?

ከሌላው ጊዜ በተለየ መልኩ ዝግጅት ተደርጓል። አባላት በብዛት ይገኛሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡ ከ2000 በላይ ለሆኑ አባላት ጥሪ አድርገናል፡፡ በደብዳቤና በወረዳ ማዕከላት ደረጃ በአጭር የስልክ ጽሑፍ /SMS/ መልእክት አስተላልፈናል። ከጠቅላላ ጉባኤ አስቀድመን የአዲስ አበባ ማዕከልን አጠቃላይ አገልግሎት የሚዳስስ ዓውደ ርእይ ይፋ ሆኖ እስከ ጠቅላላ ጉባኤ ይቀጥላል። በዚህም አባላት አስተያየታቸውን በመስጠት ሱታፌያቸውን ያሳያሉ ብለን እንጠብቃለን፡፡ ከዚህ ውጭ ለጠቅላላ ጉባኤው አባላት እንደከዚህ በፊት ሁሉ ሙሉ ቀን ስለሚውሉ የሚያስፈልጋቸውን የምሳና የመሳሰሉት ዝግጅቶች ከወዲሁ ተጠናቋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ካለበት ዘርፈ ብዙ ኃላፊነት አንጻርና የአ.አ ማዕከልም ካሉት የአባላት ብዛት አንጻር ጠቅላላ ጉባኤው ምን ዓይነት ወሳኝነት /ውጤት/ ይኖረዋል?

እንደሚታወቀው የአ.አ ማዕከል ለዋናው ማዕከል መቀመጫ ነው፡፡ ወይም አ.አ. ማዕከል ያሉ አባላት በዋናው ማዕከል ያገለግላሉ፤ ስለዚህ በርካታ ሐሳቦች የሚንሸራሸሩት፣ ታላላቅ ሥራዎች ይሠራሉ ተብሎ የሚጠበቀው አ.አ ማዕከል ነው፡፡ እንደ አባላት ብዛትም ሲታይ በሺዎች የሚቆጠሩ አባላት የሚገኙት በዚህ ማዕከል ነው፡፡ ስለዚህ ለዋናው ማዕከል ዘርፈ ብዙ አገልግሎት በመስጠት የአዲስ አበባ ማዕከል አባላት ይጠቀሳሉ፡፡ በዚህ መሠረት ለሚቀጥለው ጊዜ ለማኅበሩም ሆነ ለቅድስት ቤ/ክን በጎ ይሆናሉ ብለን በምናስባቸው ጉዳዮች ላይ አባሉ ጥሩ ሱታፌ በማድረግ ውሳኔዎችን ያስተላልፋል ብለን እንጠብቃለን፡፡ በዋናው ማዕከል፣ በአ.አ. ማዕከልና በወረዳ ማዕከል ያሉ አባላት በዚህ ጠቅላላ ጉባኤ ተሳታፊዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ የሚያነሷቸው ሐሳቦች በሙሉ በአጠቃላይ ማኅበሩ አዲስ አበባ ላይ ለሚሰጠው አገልግሎት ወሳኝነት ይኖረዋል፡፡ ይኸም አጠቃላይ ውጤቱ በማኅበሩ የሚያበረክተው ፋይዳ የጎላ ነው ብለን እናምናለን፡፡

ከጉባኤው ከአባላት ምን ዓይነት ተሳትፎ ይጠበቃል?

ይህንን ጊዜ ከባለፈው ጊዜ ተጠንቅቀን የመረጥንበት ምክንያት አለን፡፡ በተለይ ባለፈው ሳምንት ያላደረግነው በምረቃ ምክንያት ነው። ወቅቱ የዩኒቨርስቲ ተማሪዎች የሚመረቁበት ነበር፤ የማኅበሩ አባላት ተመራቂዎችና አስመራቂዎች መሆን እድል ስላላቸው መርሐ ግብሩን ሐምሌ 23 እና 24 አድርገነዋል። ስለሆነም፣ በመጀመሪያ ደረጃ መገኘት የአባልነት ድርሻ በመሆኑ ግዴታቸውን ይወጣሉ፡፡ መገኘት አንዱ መብትም ግዴታም ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ ከዚያ ውጭ በሚኖሩ ውይይቶች ላይ አስተያየታቸውን በመስጠት፣ የቀረ ነገር ካለ በመሙላት፣ የተጣመመውን በማቃናት በሚቀጥለው ደግሞ እንዲህ ይሁን በማለት ያለፈውን አስተያየት በመስጠት በሚመጣውም በመምከር ሱታፌያቸውን ያሳያሉ፡፡ ከዚህ ውጭ የማዕከሉ ሥራ ማስፈጸሚያ ወይም ለዚህ የሚያስፈልገው አጠቃላይ በጀት ሙሉ በሙሉ በማዕከሉ የሚሸፈን አይደለም፡፡ አባላት በሚያደርጓቸው አስተዋጽኦዎች፣ ለመስተንግዶ የሚሆኑትን ሁሉ በማበርከት ነው፡፡ ስለዚህ ይህም ሌላኛው የአባላት ሱታፌ የሚጠበቅበት ይሆናል፡፡ ከምንም በላይ በዘንድሮው የሥራ አስፈጻሚ ምርጫ ስላለ አባላት ለማዕከሉ አገልግሎት ይሆናሉ የሚሏቸውን ወንድሞችና እኅቶች ከወዲሁ በጸሎታቸው እንዲያግዙ ይጠበቃል፡፡ በእነዚህ ዙሪያ የአባላት ተሳትፎ ከሚጀመርበት ከቅዳሜ ጠዋት 2፡00 ጀምሮ እስከ እሑድ ማታ 12፡00 ምንም ዓይነት መርሐ ግብር ሳይኖራቸው ይህንን እንደግዴታ ወስደው ከወዲሁ መርሐ ግብራቸውን አመቻችተው በዚህ እለት እንዲገኙ ይጠበቃል፡፡

ቀደም ብለው ጠቀስ እንዳደረጉት ዘንድሮ የሥራ አስፈጻሚ ምርጫ ይደረጋል፡፡ ያለፈው ሥራ አስፈጻሚ ነገሮችን ተደማምጦ በመቻቻልና በመንፈሳዊነት በማከናወን በቀጣዩ ምን ዓይነት ተመክሮ ያስተላልፋል?

የማኅበረ ቅዱሳን አንዱ ትልቁ እሴት መደማመጥ ነው። ከእኔ ይልቅ ወንድሜ ይሻላል እኅቴ ትሻላለች፤ የወንድሜ ይሰማ የእኅቴ ይሰማ አንዱ እሴታችን ነው፡፡ ተነጋግረን እንኳን መግባባት ቢያቅተን እግዚአብሔር ይግለጥልን ብለን አጀንዳዎችን እናሳድራለን፡፡
እኔ በግሌ በማዕከሉ አገልግሎት ውስጥ የተደሰትኩበት መግባባቱ መስማማቱ ነው፡፡ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ እንደ አንድ ልብ መካሪ የሚያሰኝ መግባባትና ስምምነት ነበረን፡፡ ስለዚህ የሚቀጥለውም ሥራ አስፈጻሚ ይሄን ያደርጋል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ እኛም የተረከብናቸው ወንድሞችና እኅቶች ይህንን ሲያደርጉ ነበር እርሱም ከቀደምቱ እንዲሁ ተቀብለው ነበር። በዚህ መልኩ ይኸው ይቀጥላል፡፡

አንድ የመጨረሻ ጥያቄ ላንሳ፤ በፊት ለዋናው ማዕከል የአገልግሎት ክፍሎች እንዲሁም የሥራ አስፈጻሚና አመራር የሚመረጡት ወንድሞችና እኅቶች በአዲስ አበባ ማዕከልና በሌሎች ማዕከላት የአገልግሎትና የሕይወት ትሞክሮ ተፈትነው አልፈው ነው፤ ስለዚህ ብዙውን ጊዜ አዲስ አበባ ማዕከል እነዚህን ወንድሞችና እህቶች በአብዛኛው አሰልጥኖ የማቅረብ ልምድ አለው፡፡ አሁንስ ያለው አካሔድ ምን ይመስላል?

በማዕከላችን በኩል በዘንድሮው ተጠናክሯል ብዬ አስባለሁ፡፡ ምክንያቱም ልምድ የሚያስፈልጋቸው የአገልግሎት ሁኔታዎች አሉ፡፡ ወደ ሥራ አስፈጻሚ ሲመጣ የማኅበሩን አሠራር፥ የቤ/ክንን ጠቅላላ ሁኔታ፥ ሌሎችንም ነገሮች ግንዛቤ ውስጥ ያስገባ ሁለገብ እይታን የሚፈልግ ነው፡፡ ስለዚህ እንዲህ ዓይነት ጥንካሬዎች በአገልግሎት፣ በሒደት፣ በውጣ ውረድ ውስጥ የሚመጡ አሉ፡፡ በትምህርት በሥልጠናዎች የምናገኛቸው ብርታቶችም አሉ፡፡ ስለዚህ ከእነዚህ ሁኔታዎች ይታያል እንጂ ከምንም አንስተህ ወደ ሥራ አስፈጻሚ አታስገባም። የዘንድሮው ተጠናክሯል ብዬ የማስበው የአ.አ. ማዕከል ከሌሎቹ በተለየ መልኩ የተተኪ አመራር ሥልጠና አድርጓል፡፡ በዚህም መሠረት ለዋናው ማዕከል የአገልግሎት ክፍሎችና ለአ.አ ማዕከል አገልግሎት ክፍሎች የሚሆኑ የተተኪ አመራር አባላትን ተዘጋጅተዋል፡፡ በተወሰነ መልኩ የዘንድሮ ሥራ አስፈጻሚም ጠቅላላ ጉባኤው እነዚህን አባላትንና ሌሎችንም ያካትታል ብዬ አስባለሁ፡፡ ስለዚህ በአገልግሎት የተፈተኑና ልምድ ያላቸውን ወንድሞችና እኅቶች የተተኪ አመራር ሥልጠና የወሰዱት ወደ ሥራ አስፈጻሚ ይገባሉ ብየም እገምታለሁ፡፡ ለተተኪ አመራርነት ስናሰለጥን ቀድሞውኑ ያሉበትን ሁኔታ የንዑስ ክፍል ኃላፊዎች፣ የክፍል ኃላፊዎች የመሠከሩላቸው ወንድሞችና እኅቶች ናቸው፡፡ በአጠቃላይ አንተም እንዳነሳኸው ለዋናው ማዕከልም ሆነ ለአዲስ አበባ ማዕከል አገልግሎት ክፍሎች በልምድና በሥልጠና የተዘጋጁ አባላት ወደ ኃላፊነት ይሔዳሉ።

በመጨረሻ የሚያስተላልፉት ነገር ካለ?

የዘንድሮው ጠቅላላ ጉባኤ ሐምሌ 23 እና 24 2003 ዓ.ም ይካሔዳል፡፡ ሁለቱንም ቀን አባላት ራሳቸውን ዝግጁ አድርገው እንዲቆዩ፤ እኛም እንደ ሥራ አስፈጻሚም ሆነ እንደማዕከሉ ጓጉተን የምንጠብቀው ዕለት ነው፡፡ አንድነታችንን ፍቅራችንን የምናጸናበት ነው፡፡ እንደሚታወቀው ጠቅላላ ጉባኤ ሁሉም ሰው የሚገናኝበት ስለሆነ በደስታና በፍቅር የምንጠብቀው ነው፡፡ ለዚህ አገልግሎት መስተንግዶዎች ይኖራሉ በተዘጋጁ መስተንግዶዎች ለመስተናገድ፣ ጥያቄም ሐሳብም ያላቸው ደግሞ የሚመለከተውን አካል እየጠየቁ በዚያ መልኩ እንዲስተናገዱ እያሳሰብኩ ከሁሉም በላይ የጠቅላላ ጉባኤው ቀናት እስከሚደርስና በዚያው ጊዜም አባላት በጸሎታቸው እንዲያስቡን እንጠይቃለን፡፡

እግዚአብሔር ይስጥልን

አሜን አብሮ ይሰጠን፡፡
 

Temerakiwoch.JPG

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከ15,000 በላይ የከፍተኛ ተቋማት ተማሪዎችን አስመረቀች።

ተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
Temerakiwoch.JPG

ማኅበረ ቅዱሳን በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የነበሩና በግቢ ጉባኤያት ትምህርተ ሃይማኖት ያስተማራቸውን ከ15,000 በላይ ተማሪዎች በአባቶች ቡራኬ አስመረቀ። ተመራቂዎች የአደራ ቃልም ተሰጥቷቸዋል።

በአዲስ አበባና አካባቢዋ በሚገኙ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሲማሩ የነበሩ ተማሪዎች ዛሬ እሑድ ሐምሌ 17 ቀን 2003 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽና በማኅደረ ስብሐት ልደታ ለማርያም ቤተ ክርስቲያን ተክለ ሳዊሮስ ሰ/ት/ቤት አዳራሽ ተመርቀዋል።

በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ በተደረገው መርሐግብር የደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስና የሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ተገኝተዋል።
BitsuanAbatoch2.JPG

ብፁዕ አቡነ አትናቴዎስ በሰጡት ቃለ ምዕዳን «ደክመው ያስተማሯችሁን ቤተ ክርስቲያናችሁንና ማኅበራችሁን እንዳታሳፍሩ በሕይወታችሁ ልትበረቱ ልትጸኑ ያስፈልጋል።» በማለት አባታዊ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል።

የማኅበሩ ሰብሳቢ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም ለተመራቂዎች ባስተላለፉት መልእክት ”በዕድሜ ዘመናችሁ ሁሉ በክርስትና እምነት እና ሥርዓተ አምልኮ መጽናትን ዐቢይ ዓላማችሁ አድርጋችሁ እንድትይዙና እንድትመላለሱበት፤ በክርስቲያናዊ ሕይወት ከመጽናት በተጨማሪም ባገኛችሁት ዕውቀት ሥጋዊ ወመንፈሳዊ ተጠቅማችሁ ሀገራችንን ኢትዮጵያን ይልቁንም እናት ቤተ ክርስቲያናችሁን በምትችሉት ሁሉ እንድታገለግሉ ይኸውም ቃለ ዐዋዲያችን በሚያዘው መሠረት በሰ/ት/ቤትና በሰበካ ጉባኤ ተጨባጭ ተሳትፎ እንድታደርጉ” ብለዋል።
Dn.Yaregal.JPGዲ/ን ያረጋል አበጋዝ “ይዞ የተገኘው ወጣት” በሚል ርእስ የዕለቱን ትምህርት አስተምረዋል። “ጌታችን 5 እንጀራና 2 ዓሣ ሲያበረክት እነዚያን ይዞ እንደተገኘው ወጣት 5ቱን የስሜት ሕዋሳት ለእግዚአብሔር ማስገዛት ይዘን መገኘት ይኖርብናል።፡ከዚህም በተጨማሪ በ2 ዓሣዎች የተመሰሉትን ዕውቀት ሥጋዊና መንፈሳዊ እንዲባርክልን መለመን አለብን” ብለዋል።
በመርሐ ግብሩ ላይ በማኅበሩ የአዲስ አበባ ማዕከል መዘምራን “ወይቤሎሙ ሑሩ ወመሀሩና ሌሎችን መዝሙሮችን አቅርበዋል።”
ከግቢ ጉባኤያት የተውጣጡ ተመራቂ ተማሪዎችም በብፁዓን አባቶቻቸው፣ በቤተሠቦቻቸው፣ በወንድምና እህቶቻቸው ፊት።
«ጸውዖሙ ወባረኮሙ ወይቤሎሙ አማልክት አንትሙ ወደቂቀ ልዑል ኩልክሙ፣
 ወሰኑ ወሠርዑ ሃይማኖተ እንተ ኢትጠፍዕ።
ጠራቸው፣ ባረካቸውም እናንተ አማልክት ናችሁ፤ ሁላችሁ የልዑል ልጆች ናችሁ አላቸው። እነርሱም የማትጠፋ ሃይማኖትን ደነገጉ።» የሚለውንና ስለ አባቶቻችን ቅዱሳን ሐዋርያት የሚናገረውን ወረብ በቁም ዜማና ጽፋት ዘምረው ወርበውታል።
 
በማኅበሩ የሀገር ውስጥ ማዕከላትና ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል የግቢ ጉባኤያት ክፍል አስተባባሪ አቶ እንዳለ ደጀኔ እንደገለጡት ምንም እንኳን በግቢ ጉባኤያቱ የሚሰጡትን የትምህርት ዓይነቶች በአግባቡ በመማር ለምርቃት መጽሔት የበቁት ከ15,000 በላይ ቢሆኑም ማዕከላቱ በሚያዘጋጇቸው የቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸው የምረቃ መርሐ ግብር የአደራ መስቀል የሚቀበሉት ከ32,000 ተማሪዎች በላይ እንደሆኑ ገልጸዋል።
ማኅበረ ቅዱሳን በሀገር ውስጥ 42 ማዕከላትን፣ ከ400 በላይ ወረዳ ማዕከላትና ግንኙነት ጣቢያዎችን እንዲሁም 300 ግቢ ጉባኤያት ያቀፈ ሲሆን በዛሬው ዕለት የሚመረቁትን ጨምሮ ከ120,000 በላይ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን በየአጥቢያቸው አስተምሮ በአባቶች ቡራኬ አስመርቋል። በአሁኑ ወቅትም ከ150,000 በላይ ተማሪዎችን በግቢ ጉባኤያት ሰብስቦ በማስተማር ላይ ይገኛል። ከሀገር ወጭ ደግሞ 4 ማዕከላትና 4 ግንኙነት ጣቢያዎች አሉት።
 

የአባቴ ተረቶች

ሕይወት ቦጋለ

ሐምሌ 16/2003 ዓ.ም.

 
ሌሊቱን ለረጅም ሰዓታት የዘነበው ዝናብ አባርቶ ቦታውን ለንጋት አብሳሪዋ ፀሐይ ከለቀቀ ቆየት ብሏል፡፡
ከመኝታዬ የተነሣሁት አረፋፍጄ ቢሆንም አሁንም የመኝታ ቤቴን መስኮት ከፍቼ አውራ መንገዱን እየቃኘሁ ነው፡፡ ለምን እንደሆነ ባላውቅም ዘወትር ከእንቅልፌ ስነሣ ሰፈራችን ሰላም ለመሆኗ ማረጋገጫዬ የመኝታ ቤቴ መስኮት ናት፡፡
ሁሉም ወደየ ጉዳዩ እንደየ ሐሳቡ መለስ ቀለስ ይለዋል፡፡ የቸኮለ ይሮጣል፣ ቀደም ብሎ የተነሣው ዘና ብሎ ይራመዳል፡፡ ሥራ ፈቱ ይንገላወድበታል ብቻ መንገዱ ለሁሉም ያው መንገድ ነው፡፡ እንደ እኔ ላጤነው ከቁም ነገር ቆጥሮ ላየው ደግሞ ለዓይን ወይም ለአእምሮ የሚሆን አንድ ጉዳይ አይታጣበትም፡፡ ያባቴን ተረቶች ናፋቂ ነኝና ወደሳሎን ወጣሁ፡፡

“አቤቱ ቃሌን አድምጥ፣
ጩኸቴንም አስተውል፣
የልመናዬን ቃል አድምጥ፣
ንጉሤና አምላኬ ሆይ
አቤቱ ወደ አንተ እጸልያለሁና
በማለዳ ቃሌን ስማኝ፤
በማለዳ ፊትህ እቆማለሁ…”

አባቴ አሁንም የጠዋት ጸሎቱን አልጨረሰም እናቴ ደግሞ እንደወትሮዋ ቁርስ ለማዘጋጀት ተፍ… ተፍ እያለች ነው፡፡ ከእናቴ ፈጣንና ፍልቅልቅነት ጋር ያባቴ የእርጋታና የዝምተኝነት ባህሪ ተስማምቶ መኖሩ የሚገርመኝ ነገር ነው፡፡ ለነገሩ “ዓለም የተቃራኒ ነገሮች ድምር ውጤት ናት” ይላል አንድ ስሙ የጠፋኝ ፈላስፋ፡፡
አባቴ ጸሎቱን ጨርሶ ወደ ቤት ዘልቆ አሮጌው ሶፋ ላይ ተቀምጧል፡፡

“እንደምን አደርክ አባባ”
እግዚአብሔር ይመስገን ልጄ አንቺስ እንዴት አደርሽ?”

እናቴ ቁርስ አቅርባለች እኔም ዘወትር እንደማደርገው ከአባቴ እግር ስር ቁጭ ብዬ ጉርሻውን እየተቀበልኩ ቁርሴን እየበላሁ ነው፡፡
በአባቴ የሚነገሩ ታሪኮችና ተረቶች ከኋላቸው የሚያስከትሉትን ምክሮችና ቁም ነገሮችን ሳስብ እነዚህ ቱባ እውቀቶች ለሁሉም ቢደርሱ እንዴት ይጠቅሙ ነበር አያልኩ አስባለሁ፡፡
ዘወትር ከአባቴ የምከትባቸውን ተረቶች መጽሐፍ ለማድረግ ድንገት ሐሳቡ በአእምሮዬ ሽው ያለ እንደሆን ከእጅ ወደ አፍ የሆነውን የኛን ቤት ኑሮ አስታውሼ ተስፋ እቆርጣለሁ፡፡

“ጎሽ ልጄ የሚጠጣ ውሃ በጠርሙስ ሞልተሽ አምጭልኝ” የሚለው ያባቴ ትእዛዝ ከገባሁበት የሐሳብ ማዕበል መንጥቆ አወጣኝ፡፡
“የሚሚዬ አባት ለሚካኤል የጠመኩት ጠላ እኮ አላለቀም.. ከሱ ይጠጡ” እናቴ ነበረች፡፡
“ከዘንድሮስ ጠላ ውሃው ይሻለኛል ተይው” የሚለውን ያባቴን ምላሽ ስሰማ አባቴ በዘንድሮ ላይ ያለው ምሬት የተለየ መሆኑ እየገረመኝ ውሃውን አቀረብኩለት፡፡
“እሰይ እሰይ! እሰይ!” እያለ ጥሙን ይቆርጣል፡፡

“በአባቶቻችን ጊዜ ብዙ ሠርቶ እንዳልሠራ የሚሆን ሰው ማግኘት ቀላል ነበር፡፡ ስለ ብቁና ጎበዝ ሰው ምስክሩ ሥራው ብቻ ነበር ልጄ፡፡ ቢሆንም የዝና ናፋቂዎች ጥቂቶች አልነበሩም፡፡ ብዙኃኑ ግን ያለ አግባብ ሙገሳን እንደ ስድብ እንቆጥር ነበር፡፡ እከሌ እኮ ጀግና ነው ቢሉን ስለ ጀግንነቱ ማረጋገጫ ከእርሱው እንጂ በዝናው አናምንም ነበር፡፡

“ልጄ ዘንድሮ በዓይን የሚታይ በጎ ሥራ ጠፋ፤ እስቲ ከዓይን ተርፎ ልብን የሚሞላ ተግባር የሠራውን ሰው አሳይኝ?”  ድንገተኛው ያባቴ ጥያቄ አስደነገጠኝ፡፡ አባቴ የከበደኝን ጥያቄ ከኔ ምላሽ ሳይጠብቅ መንገሩን ቀጠለ፡፡

“ዘንድሮ ጥቂት ተሠርቶ ለስምና ለዝና የሚሮጥበት ጊዜ ነው፡፡ ከተግባር ስም የቀደመበት የውዳሴ ከንቱ ዘመን፡፡” እያለ አባቴ መናገሩን ቀጠለ፡፡ “ልጄ ስላንቺ ተግባርሽ እንጂ ዝናሽ አይመስክር” የምትለዋን የዘወትር ንግግሩን አስተውያት ባላውቅም ዘወትር መስማቴን አስታውሳለሁ የዛሬው አባቴ ገፅታ ከወትሮው በተለየ መልኩ ትካዜና ደስታ አልባ ሆኗል፡፡

ምን ሊመክረኝ ይሆን እያልኩ ወደ ጉልበቱ ተጠጋሁ

“ከአባቶቻችን ሐዋርያት ትሕትናን፣ ባለብዙ ዕውቀት ሆነው እንዳላወቁ፤ ባለጸጋ ሆነው እንዳልሆኑ መምሰልን መማር ይገባናል ልጄ ስም ከሥራ መቅደም የለበትም ልጄ…”

ቀበሮ ሥጋ በአፏ የያዘች ቁራ ትመለከትና ከመሬት ሆና “እሜት ቁራ ከአእዋፍ መካከል እንዳንቺ ያለ ውብና ቆንጆ፤ አስተዋይና ባለ አእምሮ የለም” እያለች ታሞግሳት ጀመር፡፡የቁራን ዝምታ ያልወደደችው እሜት ቀበሮ ውዳሴዋን ግን አላቆመችም

“እሜት ቁራ ሆይ በምድር ለሚገ አእዋፍ ሁሉ ንግሥት የምትሆን ፈለግን፤ በምድር ሁሉ ዞርን ግን አላገኘንም ድንገት አንቺን አየን፡፡ በዚህ ውበትሽ ላይ ድምፅሽ ቢያምር አንቺን ለንግሥትነት እንመርጥሻለንና እስቲ ድምፅሽን አሰሚኝ አለች ቀበሮ”

ንግሥት ለመሆን የተመኘችው ቁራ በቀበሮ ሙገሳ ተታላ “ቁኢኢ..” ብላ ብትጮኸ የነከሰችው ሥጋ ወደቀ፡፡ ያሰበችው የተሳካላት እመት ቀበሮ “በዚህ ድምፅና ውበት ላይ ማስተዋል ቢጨመርበት ኖሮ እንዳንቺ ያለ የአእዋፍ ንግሥት እግር እስኪነቃ ቢኬድ አይገኝም ነበር” ብላ ተመጻደቀችባት ይባላል፡፡

ልጄ ስንቱ በውዳሴ ከንቱ ጸጋውን ተነጥቆ ከክብር ተዋርዶ ይሆን? የሰው ስስ ብልት ዝና ናፋቂ መሆኑን የተገነዘበው ዲያብሎስም እንደ ልቡ እየተጫወተብን ነው፡፡ ስንት የት ይደርሳሉ የተባሉ ሰዎች ካቅማቸው በላይ ባገኙት ዝና ተልፈስፍሰው ከእርምጃው ተገተው ይሆን?

ውሃ የሞላ ብርጭቆውን አነሣና ተጎነጨለት

እሰይ! ይኸውልሽ ልጄ ለሰው ውድቀቱ ውዳሴ ከንቱ ነው፡፡ ምእመናን ጥቂት መንፈሳዊ አገልግሎት ሠርተው የበቁ የሚመስላቸው፤ አገልግለው የማንጠቅም ባሪያዎች ነን የሚሉ እንዳልነበሩ፤ ትንሽ አስተምረው /አገልግለው/ ታይታን የሚፈልጉ አገልጋዮች በቤተ ክርስቲያናችን ሞሉ፡፡ ታዲያ ትውልድ ምን ይማር ልጄ?

ለእናት ሀገሩ በቅንነት ከመሥራት ይልቅ ሀብቷን የሚቀራመታት ለድሆች ከቆመው ይልቅ ያለ አግባብ ኪሱን በጉቦ ያደለበው ስሙ ሲገን ከማየት የደለበ ምን የሚያሳዝን ነገር አለ?

ከአባቴ አንደበት የሚወጡት ቃላት ፍላጻቸው ለልቤ ደርሰው አእምሮዬን ሲሞሉት ራሴን ዘወትር ብወቅስም ያለመለወጤ አናደደኝ፡፡

“ብዙ መሥራት የሚችለው ወጣት ተጧሪ ሆነ ለኔ የሚገባኝ ከመሥራት ይልቅ መዝናናትና በሱስ መጠመድ ብቻ ነው ብሎ የሚያስብ ነው የበዛው ልጄ..”

ከአባቴ ተረት ውስጥ ራሴን መመልከት ጀመርኩ ሁሌም አንድ ተጨባጭ ነገር ላይ መድረስ ሲያቅተኝ ልኬቴ እዚህ ድረስ ነው ብዬ ሳምን፤ በራሴ መጠራጠር ጀምሬ ነበር፡፡ ትእግስት በስሜቴ ውስጥ ሲገረጅፍ ደግሞ ግን ለምን የሚለኝ አእምሮዬ ውድቀቴን ያለ ሥራና ያለ መልካም ምግባር ዛሬም በአባቴ  ቤት ተጧሪ መሆኔን አከበደብኝ፡፡

ለስማቸው የሚጨነቁት ጥቂት ሠርተው ብዙ ስም ፈለጉ እኔ ግን ያለ ሥራ ቁጭ ብያለሁ፡፡ እስከ ዛሬ የአባቴ ተረቶች እውነታቸው ከማስበው በተለየ ዘልቆ ሲታወቀኝ፣ ጠልቆ ሲዳሰሰኝ፣ ርቆም ሲታየኝ፣ ቀርቤም ሆኖ ብዥ ሲልብኝ ኖሬያለሁ፡፡ ዛሬ ግን ራሴን ተመለከትኩ፡፡

ከአባቴ ተረቶች መሠረት ዛሬ ላይ ሆኖ ትናነትን ከመናፈቅ ይልቅ የዛሬን የተግባር ሰው መሆን እንደሚገባኝ ተገነዘብኩ፡፡ የአባቴ ቃላት ተራ ተረቶች መስለውኝ ቢኖሩም ዛሬ ግን ተጨባጭ በሆነው ዓለም ውስጥ እንዴት መኖር እንደሚገባኝ ሲጠቁሙኝ የኖሩ የተዋቡ ምክሮች ናቸው፡፡ አባቴ በኋሊት መነጽር ትናንትን የሚያሰቃኘኝ የተግባር ሰው በውዳሴ ከንቱ ያልተበገረች ጠንካራ ሠራተኛ ጥሩ መንፈሳዊ ሰው እንድሆን ነው፡፡

አሁን አባቴ ካጠገቤ ተነሥቶ በረንዳ ላይ ተቀምጧል ዓይኖቹን ቡዝዝ አድርሀጎ የፊት ለፊቱን ያያል፡፡ እኔ ግን ዓይኖቹ በትውስታ ፈረስ ትናንትን፤ የሱን ዘመን እያሰቃኙት ይመስለኛል፡፡

የሱ በትናንት ዘመን መኖርና የድሮ ተረቶቹ ከተዘፈቅሁበት ከንቱነት ከግድ የለሽነትና ከተመጻዳቂነት የሚያወጡኝ የማንቂያ ደውሎች ናቸው ለካ!! አልኩ፡፡

ለወትሮው ሠርቼ ራሱን ከመለወጥ ይልቅ ሀብታም የትዳር ጓደኛና ዝና ፈላጊነቴ ገዝፎ አእምሮዬን የሞላኝ ነበርኩ፡፡ ለዚህ ነው ከሁሉም ነገር ውስጥ ሳልሆን ጠባቂ ሆኜ መኖሬ እስከ አሁን ከልብ ሳልሆን በማስታወሻ ደብተሬ ላይ የከተብኳቸውን በርካታ ያባቴን ተረቶች መልሼ ማንበብ እንደሚጠቅመኝ አሰብኩ፡፡

“ልጄ?”

አቤት አባባ

አሁን እንግዲህ 34 ዓመት ሞላሽ አይደል?

አዎን አባባ

አባቴ ከዚህ በላይ አልጠየቀኝም መልእክቱ ገብቶኛል ትንሽ ለሀገርሽና ለቤተ ክርስቲያንሽ የሚሆን በጎ ሥራ ሳትሠሪ ጊዜ ቀድሞሻል ማለቱ ነው፡፡

አባዬ?

“አቤት ልጄ”

ለካ እስካሁን ከኖሩት ተርታ አልተመደብኩም?

“እንደሱ ነው ልጄ እንደሱ!!

/ምንጭ፡- ሐመር 18ኛ ዓመት ቁጥር 5

 

 

በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች የአቋም መግለጫ አወጡ።

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
ሐምሌ 11፣ 2003 ዓ.ም
የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች ወቅታዊውን የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴና ተዛማጅ ጉዳዮችን አስመልክተው መግለጫ አወጡ። በሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ በልዩ ልዩ የመገናኛ ብዙሃን ከመምሪያው ሊቀ ጳጳስ እውቅና ውጭ «ተሐድሶ የሚባል ነገር የለም» በሚል የተሰጠው መግለጫ ሰ/ት/ቤቶች የማይቀበሉት መሆኑን አሳወቁ።
 
ሐምሌ 11 ቀን 2003 ዓ.ም በአድራሻ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፥ በግልባጭ ለሚመለከታቸው የጠቅላይ ቤተ ክህነትና የመንግስት አካላት የተሰራጨው ደብዳቤ፥ ሀገረ ስብከቱ ከቤተ ክርስቲያን የበላይ አካላት ጋር በመመካከር አስቸኳይ እልባት እንዲያመጣና ለሕዝብ፣ ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን የሚበጅ ሥራ እንዲሰራ አጽንኦት ሰጥቶ ያሳስባል።

«የኢትዮጵያ ሀገራችን የአፍሪካ ኩራትነት፥ ለመላው ጥቁር ሕዝብ አለኝታና መመኪያ መሆኗን፥ በዚህም ሠይጣናዊ ቅናት ያደረባቸው ጠብ ያለሽ በዳቦ የሚሉ ምዕራባዊያን ይህችን ለሀገራችን ታላቅ የታሪክ አሻራ ያስቀመጠች ቤተ ክርስቲያን ለማጥፋት የማይፈነቅሉት ድንጋይና የማይቆፍሩት ጉድጓድ የለም።» በማለት የሚያወሳው ደብዳቤው «በየዘመኑ በነበሩና ረድኤተ እግዚአብሔር ባልተለያቸው ቆራጥ ልጆቿ ተጋድሎ ፈተናዎችን በጽናት በማለፍ እስከ ዘመናቸን ደርሳለች» ይላል።

«ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የወላድ መካን አይደለችምና፥ ‘ዛሬም ከቤተ ክርስቲያን በፊት እኛን ያስቀድመን፣ የቤተ ክርስቲያንን ጥፋት አያሳየን’ የሚሉ እስከ ሰማዕትነት ራሳቸውን ያዘጋጁ እንደሚኖሩ ማሰቡ ሳይበጅ አይቀርም» በማለት እምነቱን ይገልጻል።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያና አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፥ ሕገ ወጥ ሰባክያንንና ዘማርያንን ለማስቆም ደረጃውን ጠብቆ የጻፉትን ደብዳቤና የሰንበት ትምህርት ቤቶችን አንድነት ለማጠናከር የሚያደርጉትን ጥረት የሚያመሰግነው መግለጫው፤ ከተሾሙ ጊዜ አንስቶ እስከ ዛሬ ድረስ አንዳች የሚጠቀስና የሚጠቅም ሥራ አላበረክቱም ያላቸውን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ አባ ሠረቀ ብርሃን ግንቦት 23 ቀን 2003 ዓ.ም የሰጡትን መግለጫ አስደንጋጭና አሳዛኝ እንደሆነበት ያወሳል።

የአባ ሠረቀ መግለጫ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን የማይወክል ከመሆኑም በላይ፥ በአሁኑ ወቅት በየአድባራቱና በየገዳማቱ ተፋፍሞ የቤተ ክርስቲያኗን ሰላምና አንድነት በመፈታተን ላይ የሚገኘውን የመናፍቃን ሴራ ጆሮ ዳባ ልበስ እንደማለት አለዚያም እንደመደገፍ ይቆጠራል፤ በዚህም በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ ላይ የነበረን እምነትም እንዲጠፋ ሆኗል ይላል።

ለዚህ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ እየሰጡት ያለው ሽፋን ምእመናንን በከፍተኛ ሁኔታ በማስቆጣቱ በየቦታው ሁከት እየተፈጠረ ይገኛል በማለት የሚጠቁመው መግለጫው፥ በተለያዩ አካባቢዎች ለተከሰተው ችግር ተዋንያን በመሆን የሚታወቁ ግለሰቦችን በተለያዩ የጠቅላይ ቤተ ክህነት መምሪያዎች ላይ በኃላፊነት የማስቀመጥ ሂደት እየተካሄደ መሆኑን መረጃዎች እንደሚያመለክቱ ጠቅሶ፥ የከፋ ችግር ሊያመጣ እንደሚችልና ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ያስገነዝባል።

በአሁኑ ሰዓት የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ ለመግታት ብሎም ከቤተ ክርስቲያን ለማጽዳት ባለድርሻ አካላትና ሰንበት ትምህርት ቤቶች እያደረጉ ያለውን ጥረት የሚያደናቅፉት የማደራጃ መምሪያው ኃላፊ የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር/የእዝ ሰንሰለት/ ሳይጥብቁ ለአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የሚሰጡት አደናጋሪ መመሪያዎች፥ ሰ/ት/ቤቶች የተሃድሶ መናፍቃንን ዘመቻ ለመግታት የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ አስቸጋሪ እንዳደረገባቸው ይገልጻል።

የተሐድሶ መናፍቃን የዘመቻ ምልክቶች የሆኑት የቤተ ክርስቲያናችንን ሥርዓት ያልጠበቁ ስብከቶችና ዝማሬዎች በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት በከፍተኛ ሁኔታ በመስፋፋት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንንና የሰ/ት/ቤቶችን ህልዉና በመፈታተን ላይ ይገኛል እንደሚገኝ የሚያሳስበው መግለጫው፥ ችግሩን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የአቋም መግለጫ አውጥተናል በማለት ይገልጻል።

ሰ/ት/ቤቶቹ ባወጡት ባለ 6 ነጥብ መግለጫ፥ ቅዱስ ሲኖዶስ በተለያዩ ጉባኤያት ያስተላለፈውና የሚያስተላልፋቸው ውሳኔዎች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲከበሩና እንዲተገበሩ፥ በሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ በልዩ ልዩ የመገናኛ ብዙኃን ከመምሪያው ሊቀ ጳጳስ እውቅና ውጭ «ተሐድሶ የሚባል ነገር የለም» በሚል የተሰጠው መግለጫ ሰ/ት/ቤቶች የማይቀበሉት መሆኑን እያሳወቅን ተገቢው እርማት በመገናኛ ብዙኃን እንዲሰጥበት፥ አውቀውም ሆነ ሳያውቁ የተሐድሶ መናፍቃንን ጉዳይ በማስፈጸም ላይ የሚገኙ ሕገ-ወጥ ሰባክያንና ዘማርያን በየትናውም የቤተ ክርስቲያናችን ዓውደ ምሕረት ላይ እንዳይቆሙ ለተመሳሳይ ዓላማ በሚንቀሳቀሱትም ተጣርቶ የማያዳግም እርምጃ እንዲወሰድ፥ የተሐድሶ መናፍቃንን ሴራ የማጋለጥ የምእመኑን በቅድስት ተዋሕዶ እምነቱ የማጽናት ሥራ ተጠናክሮ እንዲሠራ፥ ከቤተ ክርስቲያን እውቅና ውጭ በቤተ ክርስቲያኗ ስም የሚተላልፉ የቴሌቪዥን ፕሮግራም፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተምሮ የሚያፋልሱና በኑፋቄ የታጀቡ መጻሕፍት ጋዜጦች፣ ካሴቶችና ቪሲዲዎች እንዲሁም መካነ-ድሮች የቤተ ክርስቲያንን ስም እንዳይጠቀሙ፣ ተጠቅመው ከተገኙ በሕግ እንዲጠየቁ የሚሉና ሌሎች ነጥቦችንም አካትቷል።

መግለጫው በማጠቃለያው እነዚህን ችግሮች ጊዜውን የጠበቀ መፍትሔ ሳይሰጣቸው ቢቀርና ተዳፍነው ቢቆዩ የምእመናንና የሰ/ት/ቤቶች አባላት ቁጣ ውስጥ ውስጡን ሲቀጣጠል ቆይቶ ድንገት ከፈነዳ አደጋው በቤተ ክርስቲያንና በሀገር ላይ የከፋ ጉዳት ስለሚያደርስ ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ ዛሬ ነገ ሳይባል የእርምት እርምጃ መውሰድ ይበጃል በማለት ይገልጻል።

hammer site Home .JPG

ለሐመር መጽሔት መካነ ድር /website/ ተሠራለት፡፡

ለ18 ዓመታት ትምህርተ ሃይማኖታዊ ክርስቲያናዊ ሕይወትን፣ ማኅበራዊ ኑሮንና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን ምዕመኑን ስታስተምር የዘለቀችው ሐመር መጽሔት ለራሷ የሚያገለግል መካነ ድር ተዘጋጀላት፡፡የመካነ ድሩም አድራሻ(URL) http://hamer.eotc-mkidusan.org ነው።

በቀደመው ጊዜ ብዙ የተደከመባቸውና ዋጋ የተከፈለባቸው የኅትመት ውጤቶች ምዕመናን እንዲጠቀሙበት ታስቦ እንደተሠራ በማኅበረ ቅዱሳን የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ሓላፊ ዲ/ን ዘላለም ቻላቸው ተናግረዋል፡፡

ለወደፊቱም የሚወጡትን የመጽሔቷን ዝግጅቶች በሽፋን /cover/ ገጽ በማስተዋወቅ ሥርጭቷን ከፍ የማድረግና በዚህም ስብከተ ወንጌልን የማስፋፋት ተልዕኮን የበለጠ ማሳለጥን ዓላማ ያደረገ እንደሆነ የገለጹት ዲ/ን ዘላለም ቤተ ክርስቲያን በየዘመናቱ የጽሕፈትና የመገናኛ ቴክኖሎጂውን በቀዳሚነት ስትጠቀም ቆይታለች፡፡ አሁን ደግሞ የሰዎች ኢንተርኔትን የመጠቀም እውነታ ቤተ ክርስቲያንን ተወዳዳሪ ሊያደርጋት ይገባል በማለት አያይዘው አስረድተዋል፡፡ 1985 content preview.JPG

በአንዳንድ አቻ መካነ ድሮች ከጥንት አባቶች እስከ ቅርብ ጊዜ ያሉት ጽሑፎችና ሥራዎችን ማግኘት ይቻላል፡፡ በአገራችንም አንዳንድ የኅትመት ውጤቶች የቀጥታ የኢንተርኔት/Online Journalism/ ዘገባ እየጀመሩ እንደሆነ ሌሎችም የቆዩ ሕትመቶቻቸውን የሚያስነብቡበት መካነ ድር እንዳላቸው ይታወቃል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ቅድሚያ እንደሚሰጥ የሚገልጹት ዲ/ን ዘላለም በብዙ ሀገሮች መድረስ የሚችል መካነ ድር በአሁኑ ጊዜ ተመራጭ ሚዲያ እንደሆነ ነው፡፡

ለወደፊቱም ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ለጥናትና ምርምር ማእከል፣ ለቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት እንዲሁም ለሌሎች ዋና ክፍሎች ድረ ገጾችን የመሥራት ሐሳብ እንዳለ ሓላፊው አስታውቀዋል፡፡

መካነ ድሩን ያዘጋጁት አቶ ደመላሽ ጋሻው በኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ክፍል የቴክኖሎጂ ንዑስ ክፍል አባል ሲሆኑ በዚህ ወቅት መካነ ድሩ ከ45 እትሞች የሚበልጡ ከ1985 እስከ 2001 ዓ.ም የሚገኙ እትሞችን /ከጠቅላላው እትም ከ45-50% የሚሆን /እንዳካተተ ተናግረዋል፡፡ በሰው ኃይል እጥረት፣ በአንዳንድ እትሞች አለመገኘት ወይም ተጠርዘው መቀመጣቸው ስካን /Scan/ ለማድረግ አለመመቸቱ ሁሉንም የቀድሞ እትም መልቀቅ አልተቻለም በማለት አስረድተዋል፡፡ያልተሟሉ ቀሪ ሕትመቶችም በየጊዜው ስካን እየተደረጉ እንደሚጨመሩ አክለው ገልጸዋል።

መካነ ድሩ በአሁኑ ጊዜ ለመጠቀም ምቹና ቀላል ሲሆን እትሞቹንም በዓመት ማግኘት ይቻላል፡፡ በተጨማሪም ምን እንደተለወጠ የሚገልጽ አካል አካቷል፡፡ ለወደፊትም የሕትመት ውጤቶችን በደራሲ፣ በእትም ቁጥር፣ በውስጡ ይዘት /content/፣ የመጽሔቱን ዓምዶች መሠረት ባደረገ ክፍፍል የፍለጋ /Search/ ሥርዓትን ያካትታል፡፡ ከዚህም በላይ የቀጥታ ሽያጭ /Online selling/ እና የቀጥታ ምዝገባ /Online Registration/ እንደ ቴክኖሎጂው ተጨባጭ ሁኔታ ይይዛል በማለት አቶ ደመላሽ አስታውቀዋል፡፡ 1985 no 1 content .JPG

መካነ ድሩን ለመስራት የሚያስፈልገው ወጪ ከ10,000-15,000 ብር የሚገመት ሲሆን ሥራውም ከዓመት በፊት እንደተጀመረ ታውቋል፡፡ ሐመር መጽሔት በ20ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻና በ21ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት፣ በእቅበተ ቤተ ክርስቲያን /Apology/፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንዲጠበቅ በማሳሰብ /በማስተማር/ ታዋቂነት ያላት መጽሔት ናት።

መጽሔቷም በስርጭት ስፋትና በሽያጭ የመጀመሪያ ስትሆን ላለፉት ተከታታይ 18 ዓመታትም ያለ ማቋረጥ በማገልገል ታሪካዊ ናት፡፡