“የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሚና በአየር ንብረት ለውጥ” በሚል መሪ ቃል ጥናታዊ የውይይት መድረክ ተካሄደ

ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ
 
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሚና በአየር ንብረት ለውጥ“ በሚል መሪ ቃል ሰኔ 18 ቀን 2003 ዓ.ም በኢትዮጵያ ብሔራዊ ሙዝየም መሰብሰቢያ አዳራሽ ጥናታዊ የውይይት መድረክ ተካሄደ፡፡
 
በዕለቱ አምስት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ ከነዚህም ጥናታዊ ጽሑፎች በጠዋቱ ክፍለ ጊዜ “የዓባይ ወንዝና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን” የሚል ጥናታዊ ጽሑፍ በአቶ ዘሪሁን አበበ ቀርቧል፡፡ አቶ ዘሪሁን በጥናታቸው በዋናነት የውኃ ፖለቲካ ከምሥራቅ አባይ ተፋሰስ/ናይል/ አንጻር፣ በዚህም መሠረት ኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምን ዓይነት ቁርኝት አላት? የውሃው ፖለቲካ እንዴት ነው ተጽዕኖ ሊፈጥርባት የሚችለው? ምን ዓይነት የራሷ የሆነ ጥቅም አላት?  የሚለውን በማሳየት ሰፋ ያለ የጥናት ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡

በመቀጠል በአቶ ወንድወሰን ሚቻጎ “የአየር ንብረት ለውጥና ሃይማኖታዊ እሳቤ” በሚል ጥናታዊ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡ አቶ ወንድወሰን በጥናታቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ቤተ ክርስቲያን በአየር ለውጥ ላይ ምን ዓይነት ሚና አላት? ዕውቀት በአየር ንብረት ለውጥ ላይ ያለው አስተዋጽኦና የሃይማኖት እሳቤ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ አስተዋጽኦ የሚያመጣው ምንድን ነው? በሚል ሰፋ ያለ የጥናታዊ ጽሑፍ መነሻቸውን አቅርበው ጥያቄዎችና አስተያየቶች ከተሰጡ በኋላ የጠዋቱ ክፍለ ጊዜ ተጠናቋል፡፡

ከሰዓት በኋላ በነበረው ክፍለ ጊዜ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፎች የቀረቡ ሲሆን በመጀመሪያው ክፍለ ጊዜ “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ የካርቦን ልቀትን ለመከላከል “በሚል በዲያቆን ቱሉ ቶላ ቀርቧል፡፡ ዲያቆን ቱሉ በአዲስ አበባ በሚገኙ ሰባት ቀደምት አድባራትና ገዳማት ላይ ተመርኩዘው የሠሩትን ጥናት አቅርበዋል፤ በመቀጠል በአቶ ተስፋዬ አራጌ “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሚና ለተፈጥሮ ደን ጥበቃና እንክብካቤ” በሚል በደቡብ ጎንደር በሚገኝ ሦስት በተመረጡ ወረዳዎች ባሉ አስር አብያተ ክርስቲያናት ስለ ደንና አጠባበቅ የተደረገ ጥናት አቅርበዋል፣ በመጨረሻም በአቶ ብርሃኑ በላይ “የቅብዓ ሜሮን ዕፅዋት የዳሰሳ ጥናት” በሚል ጥናት፣ ሜሮንን ለማዘጋጀት የምንጠቀምባቸው ዕፅዋት እነማን ናቸው? በቀጣይስ እነዚህ ዕፅዋቶች እንዴት ነው? ማሳደግና መንከባከብ የምንችለው? በሚል መነሻ ጥናታቸውን አቅርበዋል፡፡

ከጥናታዊ ጽሑፎች ጋር ተያያዥነት ካላቸው ከአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ተቋማት እንዲሁም በግል የተጋበዙ ከ300 በላይ እንግዶች የተገኘበት ሲሆን፣ በመጨረሻም የጥናትና ምርምር ማዕከሉ አማካሪ፣ የሰቲት ሁመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ “ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር” በሚል ርዕስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተሰጥቶ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል ከተመሠረተ ጀምሮ በርካታ ጥናታዊ የውይይት መድረኮችን ያካሄደ ሲሆን ባለፈው ዓመትም የመጀመሪያውን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት መጽሔት አሳትሞ አበርክቷል፡፡

ቀሲስ ለማ በሱፍቃድ

ማኅበረ ቅዱሳን 20ኛውን ሐዋርያዊ ጉዞ በሰሜን ምሥራቅ ኢትዮጵያ በተሳካ ሁኔታ አደረገ

በዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

ሰኔ 20 ቀን 2003ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከግንቦት 19 – ሰኔ 1 ቀን 2003 ዓ.ም ድረስ በሰሜን ወሎ እና ደቡብ ትግራይ አህጉረ ስብከቶች ሃያ ሰባት ልዑካንን በመያዝ ሐዋርያዊ ጉዞ ማድረጉን በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል መደበኛ መምህርና የሐዋርያዊው ጉዞ አስተባባሪ ቀሲስ ለማ በሱ ፍቃድ አስታወቁ፡፡

ቀሲስ ለማ በሱፍቃድቀሲስ ለማ በሱ ፍቃድ እንዳሉት ሐዋረያዊ ጉዞው ከሁለት አህጉረ ስብከቶች በተመረጡ ሰባት ዋና ዋና ከተሞች ማለትም ከደቡብ ወሎ /መርሳ ወልዲያ፣ ፍላቂትና ቆቦ/ እንዲሁም ከደቡብ ትግራይ /አላማጣ፣ ኮረምና ማይጨው/ ማኅበሩ በእነዚህ ሁለት የተመረጡ አህጉረ ስብከቶች ሐዋርያዊ ጉዞ ያካሄደበትን ዓላማ ቀሲስ ለማ እንዲህ በማለት አብራርተዋል፤ ሕዝቡና ካህኑ እንዳለ ተከባብሮ የሚኖርበት ቦታ በመሆኑ፥ አህጉረ ስብከቶቹ የብዙ ሊቃውንት መፍለቂያ፣ የታላላቅ አድባራትና ገዳማት ባለቤት እንዲሁም ብዙ ቅርሶች ያሉባቸው በመሆናቸውና የሕዝቡ ባህል ሃይማኖታዊ ስለሆነ እነዚህ እንዳሉ ተጠብቀው እንዲቆዩ ሕዝቡን ለማጽናት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በዚህ አካባቢ ከወቅታዊ የተሃድሶ እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ ብዙ ፈተናዎች ይበዛሉ፤ ይህንንም በማስገንዘብ ምእመናን ራሳቸውንና ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲጠብቁ ነው ብለዋል፡፡

1600 ኪሎ ሜትር በሸፈነው ሐዋርያዊ ጉዞ የቀረቡት ትምህርቶችና መዝሙሮች በወቅታዊ የቤተ ክርሰቲያን ችግሮች ዙሪያ ያጠነጠኑ፥ ምእመኑ በሚረዳው ቋንቋ የቀረቡና ምእመኑ ለለውጥ የተነሳሳበት፣ ልዑካኑም ከምእመኑ የተማረበት ነበር ያሉት ቀሲስ ለማ በየጉባኤዎቹ መጨረሻ "ሕያው እውነት" መንፈሳዊ ፊልም መታየቱም የራሱ የሆነ ልዩ አስተዋጽኦ እንዳበረከተ ተናግረዋል፡፡

ምንም እንኳን ጉዞው በብዙው ስኬታማ ቢሆንም፥ ምእመናን የሰሟቸውን መዝሙሮች ለመገዛት ቢፈልጉም አለመመቻቸቱ፣ የጋዜጠኛ አብሮ አለመጓዝ፣ የካሜራ ባለሙያ አንድ መሆንና የመሳሰሉት ችግሮችን እንዳአስተዋሉ ቀሲስ አስታውቀው ለወደፊቱ መፍትሔ ሊበጅላቸው ይገባል ብለዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በዋና ክፍሉ ለሐዋርያዊ ጉዞ የሚያስፈልጉ ወጪዎችን በፕሮጀክት እየቀረጸ ለባለሀብቶች፣ በጎ አድራጊዎችና ለመንፈሳዊ ማኅበራት ያቀርባል፡፡ በእነዚህ አካላት ድጋፍ ሐዋርያዊ ጉዞ ያደርጋል፡፡ ለዚህኛውም ሐዋርያዊ ጉዞ 33,000 ያህል የወጣ ሲሆን በኢትዮጵያ አየር መንገድ ሠራተኞች መንፈሳዊ ጉባኤ 25,000 ብር ሲለግሱ  ቀሪውን ወጪ ደግሞ ማኅበሩን መሸፈኑ ታውቋል፡፡ 

ምእመናን

ለሐዋርያዊ ጉዞው መሳካት ከፍተኛውን ድርሻ የሚወስዱት አህጉረ ስብከቶቹ ናቸው ያሉት ቀሲስ ለማ የአህጉረ ስብከቶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ከፍተኛ ቅስቀሳና መመሪያ በመስጠት፤ ሥራ አስኪያጆች፣ ልዩ ልዩ የመምሪያ ኃላፊዎችና የወረዳ ቤተ ክህነት ሊቃነ ካህናት በጉባኤ በመገኘት፣ የሚያስፈልገውን ሁሉ በማድረግ፣ ሕዝቡን በመቀስቀስ ከፍተኛ ቦታ መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑም ከጠዋቱ 11፡00 እስከ ሥራ ሰዓት መግቢያና ከሥራ መልስ በሰዓቱ በመገኘት ሥራውን ሳይፈታ ከትምህርቱም ሳይለይ የሚማር፣ ካህናቱም ሕዝቡን በመቀስቀስና የራሳቸውን አስተዋጽኦ በወረብና ቅኔ በማበርከት የተሳተፉበት ጉባኤ ነበር ብለዋል፡፡

ቀሲስ ለማ በጉባኤው ወቅት በማይጨው መካነ ሰማዕት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ባለው የሰማዕታት አፅም የሰማዕታት መታሰቢያ በዓል ለማክበር የመጡት ባለሥልጣናት ታዳሚ የሆኑበት፣ እኛም ለጊዜው ጉባኤውን አቁመን የአከበርንበት ሁኔታ ነበር ብለዋል፡፡

የሃገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ፣ የከተማው ከንቲባ፣ የአርበኞች ፕሬዝዳንት በአደረጉት ንግግር፣ ቤተ ክርስቲያን በሀገሪቱ የምታደርገውን እንቅስቃሴ አድንቀው ይሄ ዓይነቱ ጉባኤ የከተማውን መንፈሳዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከሚያፋጥኑት ነገሮች አንዱ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ሐዋርያዊ ጉዞ ለቤተ ክርስቲያንዋም ሆነ ለሀገር ከፍተኛ አስተዋዕኦ የሚያበረክት ምዕመናንን በእምነታቸው እንዲጸኑ፣ ባህላቸውንና ቅርሳቸውን እንዲጠብቁ የሚያደርግ መንፈሳዊና ትውፊታዊ የጉዞ ጉባኤ ነው፡፡

 

 

 

በክለሳ ላይ ያለው የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት ትግበራው በ2004 ዓ.ም ይጀመራል ተባለ፡፡

 ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ
 
ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ እየተከናወነ ያለውን የግቢ ጉባኤያት የሥርዓተ ትምህርት ክለሳ በተመለከተ ከማዕከላትና ግቢ ጉባኤያት ተወካዮች ጋር ውይይት ተደረገ፡፡ ሥርዓተ ትምህርቱም ከ2004 ዓ.ም ጀምሮ ተግባራዊ እንደሚደረግ በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋረያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስታወቀ፡፡

ከግንቦት 26 እስከ ግንቦት 27 ቀን 2003 ዓ.ም በተደረገው የውይይትና የምክክር መርሐ ግብር ከ11 ማዕከላት የመጡ የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል ኃላፊዎችና ከ15 ግቢ ጉባኤያት የተወከሉ ተማሪዎች የተሳተፉ ሲሆን ተወካዮቹ ከዚህ በፊት ይነሡ የነበሩ ችግሮች በክለሳውና በዳሰሳ ጥናቱ መታየቱ እንዳስደሰታቸው ገልጸው ለተግባራዊነቱ መፋጠን ይኖርብናል ሲሉ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡
የክፍሉ አስተባባሪ ቀሲስ ታደሰ ጌታሁን እንደገለጡት ክለሳው የተሠራው በ2000 ዓ.ም የተካሄደውን የዳሰሳ ጥናት መሠረት በማድረግ መሆኑን ገልጸው፣ ይህም የዳሰሣ ጥናት ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች፣ ለመምህራን ለክፍሉ አባላት መጠይቆችን በመበተን፣ ቃለ መጠይቅ በማድረግ፣ በአካል ቅኝት በማድረግና በመሳሰሉት እንደተከናወነ አስታውቀዋል፡፡
እስከ አሁን ሲተገበር የነበረው ሥርዓተ ትምህርት ለማኅበሩ የመጀመሪያ በመሆኑ ወጥነትና አንዳንድ መሟላት ያለባቸው ነገሮች ሳይሟሉ ተግባራዊ እንደሆነ የገለጹት አስተባባሪው አሁን እየተከለሰ ባለው ግን አንድ ሥርዓተ ትምህርት ሊያሟላ የሚገባውን አሟልቷል ብለን እናምናለን፡፡ ማኅበሩም ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ምን ዓይነት ፍልስፍና መከተል አለበት የሚለው ግንዛቤ ውስጥ ገብቷል፡፡ በተለይም ወደ ግቢ ጉባኤያት እየገባ ካለው ትውልድ አንጻር ሥርዓተ ትምህርቱ ሰፊ ፍተሻ እንደተደረገበትና ለሙከራም ከሚቀጥለው ዓመት ጀምሮ እንደሚተገበር አጽንኦት ሰጥተው ተናግረዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን ከ1996 ዓ.ም ጀምሮ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚያስተምራቸው የገቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሥርዓተ ትምህርት በመቅረጽ 20 መማሪያ መጻሕፍትን በማዘጋጀት እያስተማረ እንደሚገኝ ቀሲስ ታደሰ አስታውሰው በሚሰጡ ትምህርቶች ድግግሞሽና መሳሳብ እንደሚስተዋል፣ ለትምህርቶቹ የተመደበላቸው ሰዓቶች ከሚሰጡት ትምህርቶች አንጻር የማይመጣጠኑ እንደነበር በዳሰሳ ጥናቱ ወቅት እንደችግር ጎልተው እንደታዩ ጠቅሰዋል፡፡ ከክለሳው በኋላ የነበሩት 20 ትምህርቶችም ወደ 8 ዝቅ ማለታቸውን ያወሱት ቀሲስ ታደሰ በተጨማሪም ሦስት አዳዲስ ትምህርቶች ታክለዋል፡፡ እነዚህም ትምህርተ ክርስትና መግቢያ፣ ትምህርተ አበውና ልሳነ ግዕዝ እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡
ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የሚሰጡ የትምህርት ዓይነቶችም ተማሪዎቹ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የቆይታ ጊዜያቸው የሚወሰን ሲሆን ለእያንዳንዱ ትምህርት ተመጣጣኝ ሰዓት፣ መለያ ቁጥር፣ ቅደም ተከተል እንዲሁም የትኛው የትምህርት ዓይነት ለማን ይሰጥ የሚሉ ጉዳዮች በቀጣይ የሚወሰኑ ናቸው፡፡
በሥርዓተ ትምህርቱ ክለሳ ፕሮጀክት መሠረት አዲሱ ሥርዓተ ትምህርት በዚህ ዓመት ተግባራዊ መሆን አልነበረበትም ወይ? ተብለው የተጠየቁት ቀሲስ ታደሰ ሲመልሱ ፕሮጀክቱ ከተጠበቀው በላይ ጊዜ የሚጠይቅ መሆኑንና በክለሳው የተሳተፉት ባለሙያዎች በሥራ መደራረብ ምክንያት ወደ ትግበራ መግባት እንዳልተቻለ ተናግረዋል፡፡ ቢሆንም ግን በ2004 ዓ.ም በተመረጡ ግቢ ጉባኤያት የሙከራ ትግበራ እንደሚጀመር አሳውቀዋል፡፡
ይህንን ሥርዓተ ትምህርት ከግብ ለማድረስ የግቢ ጉባኤያትና የማዕከላት ሥራ አስፈጻሚ አካላትን ግንዛቤ ማስጨበጥ እንዲሁም በቂ መምህራንን ለማፍራት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
አስተባባሪው እንዳሉት ከሥርዓተ ትምህርት ጋር ተዛማጅ ሙያ ያላቸው አባላት ክለሳውን አጠናቆ ትግበራ ለመጀመር እንዲያስችል በትምህርትና ሐዋረያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በመገኘት በሙያቸው ተሳትፎ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ሲኖዶስ በጸደቀለት መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ ተግባራዊ ካደረገ 7 ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ ይህ ሥርዓተ ትምህርት ከተተገበረ ከ4 ዓመት በኋላ የዳሰሳ ጥናት በማድረግ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ 7 አባላት ያሉት ኃይለ ግብር አቋቁሞ ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ የክለሳ ሥራው እየተከናወነ ይገኛል፡፡ 

የእግዚአብሔር ኃይል(ለሕፃናት)

ሰኔ15 ፣2003 ዓ.ም

ከእመቤት ፈለገ
 
በእስራኤል ሀገር ውስጥ አክዓብ የሚባል ንጉሥ ነበር፡፡ ንጉሡም በዓል የሚባል ጣዖት አምልኮ እግዚአብሔርን አሳዘነው፡፡ በዚሁ ሀገር ውስጥ የሚገኝ የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ የሚፈጽም ኤልያስ የሚባል ነቢይ ነበር፡፡ ንጉሡና ሕዝቦቹ እግዚአብሔርን እንዳስቀየሙት ባየ ጊዜ ዝናብ እንዳይዘንብ ጸለየ፡፡ ከብዙ ቀንም በኋላ በምድር ላይ ዝናብ አልነበረም፡፡ ከብዙ ቀንም በኋላ በሦስተኛው ዓመት “አክዓብ ጋር ሂድ በምድር ላይም ዝናብ እሰጣለሁ” ብሎ እግዚአብሔር ለኤልያስ ነገረው፡፡ በአገሪቱም ውስጥ ከፍተኛ ረሃብ ሆኖ ነበር፡፡

አብድዩ የሚባል እግዚአብሔርን የሚፈራ የንጉሡ አገልጋይ ነበር በመንገድ ሲሄድ ነቢዩ ኤልያስን አገኘው፡፡ አብድዮም ሮጠና የአክብሮት ስግደት ሰገደለት፡፡

ነቢዩ ኤልያስም “ሂድና ለጌታህ ኤልያስ እዚህ አለልህ” ብለህ ንገረው አለው፡፡ አብድዩም እንደታዘዘው አደረገ፡፡ አክአብም ነብዩ ኤልያስን እንዳገኘው “አስራኤልን የምትበጠብጠው አንተ ነህ” አለው ይህንን ያለበትም ምክንያት ዝናብ ለረጅም ጊዜ ስላልነበረ ነው፡፡ ልጆች እንደምታውቁት ዝናብ በጣም አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ እስራኤልን ሲበጠብጧት የነበሩት ግን ሕዝቦቹና ንጉሡ ነበሩ ምክንያቱም እግዚአብሔርን ክደው ሌላ አምላክ /ጣዖት/ ማምለክ ጀምረው ነበር፡፡

ነቢዩ ኤልያስ አክአብን አራት መቶ ሃምሳ የጣዖቱን /የበአልን/ ነቢያትን እንዲጠራቸው ለንጉሡ ነገረውና በአንድ ላይ ተሰበሰቡ፡፡ ከዚያም ነቢዩ ኤልያስ እንዲህ አላቸው “ከእግዚአብሔር ነቢያት የተረፍኩት እኔ ብቻ ነኝ፣ በእናንተ በኩል ግን አራት መቶ ሃምሳ ነቢያት አሉ፡፡ አንድ በሬ ውሰዱ አርዳችሁም በእንጨት ላይ አስቀምጡትና አምላካችሁን እየጠራችሁ ጸሎት አድርጉ እሳት አታንዱበት ከሰማይ አምላካችሁ እሳት አውርዶ ያዘጋጃችሁትን ነገር ከበላው እኔ በእናንተ አምላክ አምናለሁ፡፡ ይሄ ካልሆነና እኔ በአምላኬ በእግዚአብሔር ስም ጸልዬ ያዘጋጀሁትን እሳት ከሰማይ ወርዶ ከበላው በእግዚአብሔር ታምናላችሁ አላቸው፡፡ ሁሉም ሰው ተስማማ፡፡

በአልን ያመልኩ የነበሩት 450 የሐሰት ነብያት ቀኑን ሙሉ ቢጸልዩ ምንም ለውጥ አላመጡም፡፡

ነቢዩ ኤያልስ እሳት ከሰማይ ወርዶ እርሱ  ያስቀመጠውን እንዲወስደው ብዙ ውሃ አደረገበት፡፡ ልጆች እንደምታውቁት ውሃ እሳትን ያጠፋል፡፡ ነቢዩ ኤልያስ ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ሲል ጸሎት አደረገ፡፡  እግዚአብሔር አምላክ ሆይ አንተ የእስራኤል አምላክ መሆንህንና እኔም የአንተ አገልጋይ መሆኔን ያውቁ ዘንድ እግዚአብሔር ሆይ እባክህ ስማኝ ከዚያም የእግዚአብሔር እሳት ወርዳ እንጨቱን፣ ድንጋዩን፣ ዐፈሩን፣ ፈጽማ በላች በጉድጓድ ውስጥ ያለውን ውሃ ላሰች፡፡

ሕዝብም ሁሉ ይህን ሲያይ በግንባራቸው ተደፍተው አምላከ እግዚአብሔር እርሱ እውነተኛ ነው! እግዚአብሔር እርሱ እውነተኛ አምላክ ነው አሉ፡፡

አያችሁ ልጆች እግዚአብሔር በጣም ኃያል አምላክ ነው፡፡ እኛም የእርሱ ትእዛዛት የምንፈጽም ከሆነ ለእኛም ጥሩ ነገሮችን ማድረግ እንድንችልኃይል ይሰጠናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል

ምዕዳነ አበው

በዲ/ን ኅሩይ ባየ እና በደረጀ ትዕዛዙ
 ሰኔ 17 ቀን 2003 ዓ.ም
/ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከግንቦት1-15፣ 2003 ዓ.ም/ 
 
የቅዱስ ሲኖዶስ የርክበ ካህናት ጉባኤ ከግንቦት 10-16 ቀን 2003 ዓ.ም ሲካሔድ ቆይቶ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ተጠናቋል፡፡ ስለ ጉባኤው ሒደት አስተያየታቸውን እንዲሰጡን፤ ተሳታፊ ከነበሩት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ይመለከታቸዋል ብለን ያሰብናቸውን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት አነጋግረን የዚህ ዕትም የአብርሃም ቤት እንግዳ አድርገናቸዋል፡፡

«ያሳለፍናቸው ውሳኔዎች በሥራ ላይ መዋል አለባቸው፡፡»

  የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል

ስምዐ ጽድቅ፡- የግንቦቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የርክበ ካህናት ጉባኤ ስለተወያየባቸው አጀንዳዎች ቢገልጹልን? 

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- ተወያይተን ውሳኔ ያሳለፍንባቸው አጀንዳዎች ወደ ዐሥራ ሦስት ይሆናሉ፡፡ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የጉባኤ መክፈቻ ንግግር፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ዓመታዊ የሥራ ክንውን፣ በቅርቡ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ሠራተኞች ስለተደረገው የደመወዝ ጭማሪ፣ የኢትዮጵያ ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ግንባታ፣ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ችግር፣ መንፈሳዊ ተቋማትን በተመለከተ፣ የልማት እና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን ኤች አይ ቪ/ ኤድስ መከላከያና መቆጣጠሪያ መምሪያ ሥራ አፈጻጸም፣ ልማትን በተመለከተ፣ የስብከተ ወንጌል ጉዳይ፣ የሊቃነ ጳጳሳት ዝውውር፣ በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ እና በማኅበረ ቅዱሳን የተፈጠረውን አለመግባባት በተመለከተ፣ የቀጣዩ ቋሚ ሲኖዶስ አባላት ምርጫና ልዩ ልዩ የሚሉ ናቸው፡፡
 
የደመወዝ ጥያቄን በተመለከተ ማስተካከያ አድርገናል፡፡ የሲዳማ ሀገረ ስብከት ችግር እንዲፈታ ተመድበው የነበሩት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ እና የሐዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪ እንዲነሡ ወስነናል፡፡ ለቀጣዩም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ለሥራው ይስማማል ብለው ያመኑበትን ሥራ አስኪያጅ እንዲያቀርቡ እና በጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ትእዛዝ ሥራውን እንዲጀምሩ ወስነናል፡፡
ዝውውር የጠየቁ ሊቃነ ጳጳሳትም ለጥያቄያቸው ምላሽ አግኝተዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ቁልፍ የሆነው ስብከተ ወንጌል መሆኑ ይታመናል፡፡ በመሆኑም በስብከተ ወንጌል እንቅስቃሴ ቤተ ክርስቲያኒቱ የማታውቃቸው ሕገ ወጥ ሰባክያን እንዳይሰብኩ አግደናል፡፡ ሕገ ወጥ ሰባክያን ብቻ ሳይሆኑ ሕገ ወጥ ዘማርያንም በየትኛውም የስብከተ ወንጌል ዐውደ ምሕረት ቆመው እንዳያገለግሉ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጀ መምሪያ እና በማኅበረ ቅዱሳን መካከል ያለውን አለመግባባት ለመቅረፍ ከሊቃነ ጳጳሳት ሦስት አባቶች ከሊቃውንት ጉባኤ አራት ምሁራን ተመርጠው ጉዳዩን አጣርተው ለጥቅምት ሲኖዶስ እንዲያቀርቡ ኮሚቴዎችን ሰይመናል፡፡

ለቀጣዩ ስድስት ወራት የሚያገለግሉ ቋሚ የሲኖዶስ አባላትም ተመርጠው ሥራቸውን እንዲቀጥሉ አድርገናል፡፡ በተጨማሪም ከገጠሪቱ ክፍሎች ትምህርት ቤታቸውን ለቅቀው ወደ አዲስ አበባ እየፈለሱ የሚመጡ ሊቃውንት ባሉበት እንዲረጉ ለማስቻል በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ እና በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በኩል ችግሩ እንዲቀረፍ አቅጣጫ ሰጥተናል፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ስብከተ ወንጌል በተመለከተ ቀደም ብለው ሲገልጡልን ሕገ ወጥ ሰባክያን እና ዘማርያን ታግደዋል ብለውናል፡፡ ሕገ ወጥ ሰባክያን እና ዘማርያን ሲባል ምን ማለት ነው? ቅዱስ ሲኖዶስ ስለዚህ ጉዳይ ከዚህ ቀደም ወስኖ አልነበረም?

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- ሕገ ወጥ ሰባክያን እና ዘማርያን ማለት ቤተ ክርስቲያኒቱ ያላስተማረቻቸው የማታውቃቸው ያልተፈቀደላቸው ማለት ነው፡፡ እነዚህን ሕገ ወጥ ሰባኪያን እና ዘማርያን ባለፈው ጥቅምት ጉባኤ እንዲታገዱ ብለን መወሰናችን እርግጥ ነው፡፡ አሁን ግን ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ የሆነ ውሳኔ ነው ያስተላለፈው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ሰባክያን እና ዘማርያን ሕጋውያን ናቸው ለማለት መሥፈርቱ ምንድን ነው?

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- ሕጋውያን ሰባኪያን እና ዘማርያን የምንላቸው በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ የተካተቱ /የታቀፉ/ የአሠራር መዋቅርና መመሪያዋን የሚያከብሩ ማለታችን ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በጉባኤው የተወሰኑ ውሳኔዎች አፈጻጸማቸው እንዴት ይከናወናል?

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- ቅዱስ ሲኖዶስ ይሆናል ይጠቅማል እና ይበጃል ያለውን ነገር በሙሉ ወስኗል፡፡ ውሳኔውም በሚመለከታቸው አካላት ተግባራዊ መሆን አለበት፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በጉባኤው ላይ የነበረው ውይይት ውጤታማ ነበር ማለት እንችላለን?

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- አዎ ውጤታማ ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡ በመጨረሻ መግለጽ የምፈልገው፤ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በሕገ ልቡና የነበረ በሕገ ኦሪት የጸና በሕገ ወንጌል በሐዋርያት፣ በሊቃውንት በጳጳሳት እና በካህናት እየተከናወነ ለዚህ ደርሷል፡፡ ከዘመነ መሳፍንት፣ ከዘመነ ነገሥት እና ከዘመነ አበው እየተወራረደ እስከ ዘመነ ሥጋዌ ዘልቆ ለዚህ ትውልድ የተላለፈ ባሕል፣ ሃይማኖት ቀኖና ትውፊት እና ዶግማ አለን፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዚህች ሀገር ታላቅ ድርሻ ያላት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ብዕር ቀርጻ፣ ቀለም በጥብጣ፣ ብራና ዳምጣ፣ የጽሕፈት መሣሪያ በሌለበት ጊዜ አሁን የምንገለገልበትን የብራና መጻሕፍት ጽፋ ታሪክ ጠብቃ ያኖረች ነች፡፡ ፊደልን አዘጋጅታ ሀ ሁ ብላ ያስተማረች ገንዘብ ሚኒስቴር ትምህርት ሚኒስቴር ሆና ያገለገለች ለትውልድ የዕውቀት እንጀራ ጋግራ ያሰናዳች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ የውጭ ወራሪ፣ የውስጥ መስሎ አዳሪ ጠላት በተነሣ ጊዜ ታቦት በራሷ፣ ቃጭል በጥርሷ ይዛ አዋጅ እየነገረች፣ ፍርሃት እንዳይመጣ እያበረታታች ድንኳን ተክላ ሥጋ ወደሙ ለሚገባው ሥጋ ወደሙ እየፈተተች እያቀረበች እያስተማረች እያጽናናች የታመመውን እያስታመመች የሞተውን እየቀበረች የሀገርን አንድነት ያስጠበቀች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ከትናንት እስከ ዛሬ የዘለቀውን የቤተ ክርስቲያን ውለታ እንዘርዝረው ከተባለ ጊዜው አይበቃንም፡፡ ትውልዱም ይኼን ታሪክ አውቆ በማንነቱ ኮርቶ በሃይማኖት ጸንቶ የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ሥርዓት ቀኖና እና ዶግማ እንዲጠብቅ አደራን አስተላልፋለሁ፡፡

 
ስምዐ ጽድቅ፡- ስለነበረን መልካም ቆይታ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

ብፁዕ አቡነ ሕዝቅኤል፡- እናንተንም እግዚአብሔር ይጠብቃችሁ አገልግሎታችሁንም ይባርክ፡፡

«ጅራቱን አትልቀቅ ቀንዱን ትይዘዋለህ»
 

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የምዕራብ ትግራይ ሁመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ 

ስምዐ ጽድቅ፡- የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የተጠበቀውን ያህል ውጤታማ ነበር ማለት ይቻላል?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- ውይይቱ ቢያውልም፣ ቢያሰነብትም፣ ቢያከራክርም፣ ቢያዘገይም፣ ቢጎተትም ለቤተ ክርስቲያን ይጎዳሉ፣ ለምእመናን አይጠቅሙም፣ ለሀገር አይበጁም ያልናቸው ችግሮች ሁሉ እንዲቆሙ አድርገናል፡፡ ስለዚህ ውይይቱ ውጤታማ ነበር ማለት ይቻላል፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ስለ ስብከተ ወንጌል ምን የተወሰነ ነገር አለ?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- ስብከተ ወንጌል የቤተ ክርስቲያኒቱ የጀርባ አጥንት ነው፡፡ በስብከተ ወንጌል ውስጥ የማይመለከታቸው አካላት ሰርገው ገብተው ጥንት የነበረውን ሥርዓታችንን እንዳያበላሹ ጥንቃቄ መደረግ አለበት፡፡ የቆየው ሥርዓታችን ተንዶ አዲስ ሥርዓት መተካት የለበትም፡፡ እነዚህን ሕገወጥ ሰባክያን በተመለከተ ባለፈው የጥቅምት ጉባኤ የተወሰነ ውሳኔ ነበር፡፡ አፈጻጸም ላይ ግን ተግባራዊ ሳይሆን ቆይቷል፡፡ ከአሁን በኋላ ግን በተግባር ላይ እንዲውል ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ወስኗል፡፡ «ጅራቱን አትልቀቅ ቀንዱን ትይዘዋለህ» እንደሚባለው ስብከተ ወንጌል ተዛብቷል፣ አብነት ት/ቤቶች ተዳክመዋል፣ ገዳማቱ ተቸግረዋል፡፡ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን እየጎነተሉን ነው እያልን፤ ከቀላል ወደ ከባድ፣ ከታች ወደ ላይ እየተጓዝን ነው፡፡ በዙሪያችን የሚታዩትን ችግሮችን በጋራ መቅረፍ አለብን፡፡ ሕገ ወጥ ሰባክያኑን በተመለከተ የተወሰነው ውሳኔ በመምሪያው ሊቀ ጳጳስ በኩል ተፈጻሚ እንደሚሆን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- አጠቃላይ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አፈጻጸም እንዴት ሊከናወን ይችላል?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥራዋን የምታንቀሳቅሰው በሕገ ቤተ ክርስቲያን እና በቃለ ዓዋዲው መሠረት ነው፡፡ በተለይ በአፈጻጸም እና በአሠራር በኩል ሙሉ በሙሉ የምታከናውነው በቃለ ዓዋዲው ነው፡፡ ቃለ ዓዋዲው የተመሠረተው በሦስት አካላት ነው፡፡ ሦስቱ አካላትም አንደኛ የካህናት ጉባኤ ሁለተኛ የምእመናን ጉባኤ ሦስተኛ የወጣቶች ጉባኤ በመባል ይታወቃሉ፡፡ እነዚህ ሦስቱ ክፍሎች በመደማመጥ፣ በመቻቻል፣ በመወያየት በመናበብ እና በመተያየት ሥራቸውን ሙሉ በሙሉ ያካሒዱታል፡፡ ከታች እነዚህ አካላት ሆነው ከላይ ያለው የቤተ ክርስቲያኒቱ የሥልጣን አካል ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ምንጊዜም ቢሆን መመሪያ ነው የሚያስተላልፈው፡፡ የሚሠራውና የማይሠራውን የሚሆነውን እና የማይሆነውን ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔውን የሚያስተላልፈው ከላይ ለተገለጡት ሦስት አካላት ነው፡፡ በዚህም መሠረት ከሕፃናት እስከ ዓዋቂ ከካህናት እስከ ምእመን የየራሳችን ድርሻ አለን ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ ገበሬው መገበሪያ ያቀርባል፡፡ ካህኑ ይረከበዋል፡፡ ሊቀ ጳጳሱ ይባርከዋል ለአገልግሎትም ይውላል፡፡ ሸማ ሠሪው ልብስ ይሠራል ለካህኑ ይሰጠዋል ሊቀ ጳጳሱ ይባርከውና ልብሱ ይቀደስበታል፡፡ አንጥረኛው መስቀል ይሠራል፡፡ ሠርቶም ለካህኑ ይሰጠዋል፡፡ ካህኑም ለሊቀ ጳጳሱ ያቀርበዋል ሊቀ ጳጳሱ ባርኮ እንዲባርክበት መልሶ ለካህኑ ይሰጠዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የተሟላ የሚሆነው ሁላችንም ተባብረን ስናገለግል ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ወስኖ ውሳኔውን በተግባር ፈጽሞ እንዲያሳያቸው የሚጠብቁ ሰዎች አሉ፡፡ ይኼ ግን ስሕተት ነው፡፡ የተወሰኑ ውሳኔዎችን መፈጸም እና ማስፈጸም የምእመናን ድርሻም እንደሆነ መታወቅ አለበት፡፡ የስሕተት ትምህርቶች ሲሰጡ፣ የቤተክርስቲያኒቱ ሥርዓት ወዳልተፈለገ ጎዳና ሲያዘነብሉ ምእመናን ዝም ማለት የለባቸውም፡፡ ከሊቃነ ጳጳሳትም ጀምሮ እስከ ምእመናን ድረስ የድርሻችንን ስንወጣ ቤተ ክርስቲያኒቱ በትክክል ትጓዛለች፡፡

ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚነቅፉ፣ ቅዱሳን መላእክትን የሚቃወሙ፣ ቅዱሳኑን የሚተቹ ትምህርቶች በየዐውደ ምሕረቶቻችን ይሰጣሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ምእመናን ዝም ማለት የለባቸውም፡፡ ንስጥሮስ የክሕደት ትምህርት ሲሰጥ ሰምተው የማናውቀውን እንግዳ ትምህርት አንተ ከየት አመጣኸው? ብለው የተቃወሙት ምእመናን ናቸው፡፡ ስለዚህ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተፈጻሚ የሚሆነው በካህናት እና በምእመናን ሲተገበር ነው፡፡ መሐንዲስ ፕላን ማውጣት እንጂ ግንብ መገንባት ላይጠበቅበት ይችላል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ያወጀውን አዋጅ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሐፊ ለጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ያቀርቡታል፡፡ ከጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ድረስ በመሸኛ ይልኩታል፤ በዚህ መልኩ ይፈጸማል ማለት ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በቅርቡ የሐዋሳ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሆነው የተመደቡት ሊቀ ካህናት ጌታቸው ዶኒ ለመነሣታቸው ምክንያቱ ምንድን ነው?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- በቃለ ዓዋዲው እና በሕገ ቤተ ክርስቲያኑ ደንብ መሠረት የሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች የሚሾሙት በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ አቅራቢነት በቅዱስ ፓትርያርኩ ፈቃድ በጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ፈቃድ በምእመናኑ ይሁንታ ሲያገኙ ነው፡፡ የሐዋሳው ሥራ አስኪያጅ ግን ሊቀጳጳሱ ስላልፈቀዱላቸውና ምእመናን መቃወማቸውን ቅዱስ ሲኖዶስ ስለተረዳ ሊነሡ ችለዋል፡፡ የማይሆን ነገር አይሆንም ማለት ነው፡፡ በግዴታ የሚሆን አንዳች ነገር የለም፡፡

ስምዐ ጽድቅ ፡- በመጨረሻ የሚያስተላልፉት መልእክት ካለ?

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- ለቤተ ክርስቲያናችን ሁለንተናዊ ተልእኮ የሁላችንንም ትብብር ይጠይቃል፡፡ እርስ በእርሳችን በመተያየት በመደማመጥ አብረን ለመሥራት እንነሣ፡፡ ገብረ ማርያም ተብለን በስመ ጥምቀት መጠራት ብቻ ሳይሆን ለማርያም ምን አደረግሁ ብለን መጠየቅ አለብን፡፡ ሰይፈ ሚካኤል ከተባልን ለሚካኤል ምን አደረግሁ ማለት ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ የድርሻችንን ለመወጣት ጠንክረን እንሥራ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ስለ ሰጡን ማብራሪያ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፡- እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይቀድሳችሁ ሰላሙንም ያብዛላችሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- አሜን ብፁዕ አባታችን፡፡

«ውሳኔዎቻችን ወረቀት ውጧቸው እንዳይቀሩ የሚያስተገብር አስፈጻሚ ያስፈልጋል»

 

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የሲዳማ፣ ጊዲዮ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ሰብከት ሊቀጳጳስስምዐ ጽድቅ፡- በሲኖዶሱ ጉባኤ ስለእርስዎ ሀገረ ስብከት ምን ተወሰነ? በውሳኔው መሠረት በሀገረ ስብከትዎ ምን ምን ተግባራት ለማከናወን ታስቧል?
ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፡- ያው በሐዋሳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጵጵስናዬን ይዤ እንድቀጥል ተወስኗል፡፡ በፊትም የቆመ ነገር የለም፡፡ የእርስ በርስ ብጥብጥ ስለነበረ ቅዱስ አባታችን እዚህ ቆይ ስላሉኝ ትንሽ እዚህ ቆይቼ ነበረ፡፡ አሁንም ሥራችንን ከቀጠልን ልንሠራቸው ያሰብናቸው ነገሮች አሉ፡፡ የስብከተ ወንጌሉን አገልግሎት ቅድሚያ ሰጥተን፣ ካህናትን እያሠለጠንን ሕይወት ለዋጭ የሆነውን ትምህርተ ወንጌል ለማስፋፋት ነው የምንሠራው፡፡ ሁለተኛ ልማት ላይ እናተኩራለን፡፡ በቀበሌ ኪራይ ላይ ያለውን የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ለማሠራት ዕቅድ አውጥተናል፡፡ ሦስተኛ የተጀመረ ማሠልጠኛ አለ፤ አዳሪ ተማሪዎችን ቁጥራቸውን በማሳደግ ጥራት ያለውን ትምህርት ለመስጠት አቅደናል፡፡ ከዚህ በተረፈ እርቅና ሰላምን በመስበክና በማስታረቅ ሰላም እንዲመጣ መጣር ዋናው ዕቅዳችን ነው፡፡ ይህን ከሁሉ ቀድመን የምንፈጽመው ይሆናል፡፡ ሰላም ከሌለ ምንም የለምና፡፡ ወንጌል ሰላም ነው፣ ትህትና ነው፣ አንድነት ነው፡፡ ቅዱስ ወንጌልን መሠረት ያደረገ ሰላምን ለመስበክ እንጥራለን፡፡ እርቅና ሰላሙ በተግባር መገለጥ ያለበት በመሆኑ ይህንኑ በስፋት እንገባበታለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ይህንን ለመፈፀም ከምእመናኑም ሆነ ከአገልጋዮች ምን ይጠበቃል ይላሉ?

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፡- ምእመናንና ካህናት ሁሌም ኅብረት መፍጠር አለባቸው፡፡ ካህናት በጸሎታቸው ምእመናን በገንዘባቸው በሙያቸው፣ በጉልበታቸው ልማትን ማፋጠን ይችላሉ፡፡ ስለዚህ የተዘረዘሩትን የልማት ዕቅዶች እውን የምናደርገው ኅብረት፣ ፍቅርና አንድነት ሲኖር ነው፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያኒቱ የተመሠረተችው በምእመንና በካህናት ነው፡፡ ካህናት ስንል ብፁዓን አባቶችም በዛ ውስጥ አሉ፡፡ ስለዚህ ኅብረት እንዲኖር መጸለይ፣ መስማማት፣ መታረቅ ያስፈልጋል፡፡ ካለፈው ዓመት ጀምሮ ሁከት ስለነበረ ምንም ሳናለማ ነው የቆየነው፡፡ እርስ በእርስ መስማማቱ ጠፍቶ ነበር፡፡ እኔም ከተመደብኩ ጀምሮ ለማስታረቅ ብዙ ሞከርኩኝ ችግሩ እዛ አካባቢ ሳይሆን ከሌላ አካባቢ የተለኮሰ ስለሆነ በቀላል ሊበርድ አልቻለም፡፡ እዛ ብቻ ቢወሰን ኖሮ ያን ያህል አያስቸግርም ነበር፡፡ ዘርፍ ያለው፣ ሽቅብ ቀንድ ያለው፣ የሚያድግ፣ ቁልቁለትም አቀበትም ያለው ስለሆነ ብዙ አስቸጋሪ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ያ እንዲቀር ነው ጸሎታችን፡፡ ለዚህ ኅብረት ያስፈልጋል፤ ቤተ ክርስቲያናችን መለያየትን አትወድም፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ዐይኖችም እጆችም እግሮችም ሁሉም ሕዋሳት ተባብረው እንዲሠሩ አስተምሮናልና፣ ሳይንሱም ያዘናል፡፡ ይህን አንድነት እንድናገኝ እንጸልይ፡፡ ችግራችንን እንወቅ፣ ከባድ የሆነ አደጋ እንደከበበን ዐውቀን እንጠንቀቅ፣ ይህ አደጋ መለያየት መሆኑን ተገንዝበን እንንቃ፡፡ ስለዚህ መለያየታችንን በትዕግሥትና በእርቅ ማስወገድ ሐዋርያዊ ሥራ፣ ቤተ ክርስቲያናዊ ሥራ፣ ሕዝባዊ ሥራ መሥራት እንችላለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በቀጣይ በአካባቢው ሰላም አንድነትና ሥርዓት ተጠብቆ እንዲሔድ ያስችላል የሚል እምነት አለዎት?

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፡- የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትና ሊቃውንት በቃለ ወንጌል ለማረጋጋት፣ ሰላም ለመስበክ ይሔዳሉ፡፡ እነርሱ ፈጽመው ከተመለሱ በኋላ ሥራችንን ለመቀጠል እንሔዳለን፡፡ ምእመናኑ ዘጠና ዘጠኝ በመቶ ከእኔ ጋር ናቸው፡፡ እነዛም ወንድሞቼ ልጆቼ ናቸው፡፡ አለመግባባት ነው እንጂ፡፡ ስለዚህ የአምላካችን ፈቃድ ከሆነ ሥራችንን እንቀጥላለን፡፡ እና ቅዱስ ሲኖዶስ በሁሉም የሀገሪቱ ክፍል ሰላም፣ አንድነት እንዲሰፍን ጸሎቱም ሥራውም ስለሆነ የታሰበው ይፈጸማል ብዬ አምናለሁ፡፡ በተለይ በደቡብ አካባቢ ትንሽ ስለሆንን ሌትም ቀንም እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ይፈልጋል፡፡ ይህ ፍላጎት እንዲሟላ እግዚአብሔር እንዲረዳን ከልብ እንጸልያለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- እርስዎ በቅዱስ ሲኖዶሱ አንጋፋ አባት እንደመሆንዎና በአገልግሎትም ረጅም ዘመን እንደ መቆየትዎ ከሕገ ቤተ ክርስቲያን አንጻር የሲኖዶሱን ውሳኔዎች አፈጻጸም ካለፉት ዓመታት ጋር እንዴት ያነጻጽሩታል? የሌሎች ሀገሮች ተሞክሮም ካለ ቢያካፍሉን?

ብፁዕ አቡነ ገብርኤል፡- «ሲኖዶስ» በኢትዮጵያ ኦርቶዶስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሕግና ሥርዓት መሠረት የሐዋርያትን ሲኖዶስ ተከትሎ የሚሔድ ነው፡፡ ከሐዋርያት ጀምሮ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚመሰለው በመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ የመንፈስ ቅዱስ ውሳኔ ደግሞ ይግባኝ የለውም፡፡ ግን ሲኖዶስን የሚያጅቡ ፍቅር፣ ጸሎት፣ ሰላም፣ ትህትና፣ ይቅርታ ናቸው፡፡ እነዚህን ሁሉ ተላብሶ ወንጌል እንዲሰብክ የሚወስን ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያንን ዶግማዋን ሥርዓቷን የሚጠብቅ ነው፡፡ ምእመናን በጎቿን የሚጠብቅ፣ የሚያስጠብቅ ነው፡፡ በዚህ መሠረት ከቀደምት ጊዜያት ጀምሮ ውሳኔ ይወሰናል ነገር ግን ውሳኔን ማስፈፀም ላይ ችግር አለ፡፡ በጣም አስፈላጊ የሆኑ ውሳኔዎች ላይ አስፈጻሚ ያስፈልጋቸዋል፡፡ የሲኖዶሱን ውሳኔ ከፓትርያርኩ ጎን ሆኖ የሚያስፈልጽም አካል ያስፈልጋል፡፡

ውሳኔዎቻችን ወረቀት ውጧቸው እንዳይቀር በተግባር የሚያስፈጽም ታላቅ ኃይል የለንም፡፡ ከጠቅላይ ሥራ አስኪያጅ ጋር ተባብረው የሚሠሩ ቢያንስ ዐሥራ ሁለት ሊቃነ ጳጳሳት ያሉበት አስፈጻሚ አካል ያስፈልጋል፡፡

የራሺያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጠንካራ የሆነበት ምክንያት ከፓትርያርኩ ጋራ ዐሥራ ሦስት አባላት ያሉበት አስፈጻሚ በመኖሩ ነው፡፡ እኔ ዘጠኝ ዓመት እዛ ስቀመጥ ያየሁት ጠንካራ ነገር ይህ ነው፡፡ ምልዐተ ጉባኤው ወስኖ ሲሔድ እነዚህ አስፈጻሚዎች ተግባራዊ እንዲሆን ያደርጋሉ፡፡ እያንዳንዱ ውሳኔ አይባክንም፡፡ እንዲህ ዓይነት አሠራር በሲኖዶሳችን ሊኖር ይገባል፡፡ መወሰን ብቻ ዋጋ የለውም፡፡ አፈጻጸሙን መከታተል ይገባል፡፡ መፈጸሙን ማረጋገጥ ይገባል፡፡ ከዚህ አንጻር ሲኖዶሳችን አስፈጻሚ ክፍል እንዲኖረው ይደረግ ነው የምለው፡፡ በሕገ ሲኖዶስ እየተመራ የሚሠራ ጠንካራ አስፈጻሚ ክፍል ቢያንስ መቋቋም አለበት፡፡ ብዙ ወስነን ጥቂቶቹ ብቻ ናቸው ተግባራዊ የሚሆኑት፡፡ ያ ስለሆነ ነው አስፈጻሚ ክፍል አስፈላጊ ነው የምለው፡፡

«ሁሉም የቤተክርስቲያን አካላት ግዴታቸውን መወጣት አለባቸው»

 
የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ማርቆስስምዐ ጽድቅ፡- በስብከተ ወንጌል ረገድ የዘንድሮው ግንቦት የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ውሳኔና ሐዋርያዊ ተልእኮ ምን ይመስላል? አፈጻጸሙስ ላይ ምን ታስቧል?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት ላይ ያለው ችግር ውሎ ያደረ ውዝፍ በመሆኑ ለማስተካከል ጊዜ ይጠይቃል፡፡ መዋቅራዊ ሰንሰለቱን፣ ጠብቆ ማስቀጠል ግድ ይላል፡፡ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና ውጪ የሚንቀሳቀሱ እና ጥልቀት የሌለው ትምህርት ያላቸው፤ ከገንዘብና ከጥቅም ጋር የተያያዘ ችግር ያለባቸው ናቸው ይህን ችግር እየፈጠሩ ያሉት፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ትኩረት እየሰጠ በመዋቅር ደረጃ አገልግሎቱ እንዲሰፋ እያደረገ ነው፡፡ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ በዘርፉ አባት አስቀምጧል፡፡ የአንድ አባት /ሊቀ ጳጳስ/ ዓላማው ወንጌልን መስበክ ነው፡፡ ከጥንተ ስብከት ጀምሮ ወደ ዓለም ሒዱ ነው፡፡ ወንጌል ለሁሉም ነው፡፡ ድኅነት ስለሆነ፡፡ ከዚህ አንጻር ወደ ቤተ ክርስቲያናችን ስንመጣ አፈጻጸሙ ላይ ችግር አለ፡፡ ማእከላዊነቱን አለመጠበቅ አለ፡፡ አምና ተወስኖ ነበር የአፈጻጸም ችግር ስላለ አልተተገበረም፡፡ ዘንድሮም ያንኑ ውሳኔ በማንሳት በበለጠ መሥራት እንዳለብን ስምምነት ላይ ተደርሷል፡፡ ስብከተ ወንጌል መምሪያው ሳያውቀው፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈቃድ ያልሰጠቻቸው ሰባኪያን በየትኛውም ቦታ እንዳይንቀሳቀሱ ተብሎ ውሳኔ ተላልፏል፡፡ ይህንን መምሪያው፣ የየአህጉረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት የሌሎችም የእምነቱ ተከታዮች አፈጻጸሙ ላይ ትኩረት ሰጥተው /ሰጥተን/ በጋራ መሥራት አለብን፡፡ በሴርኩላር የሚተላለፈውን መመሪያ በየደረጃ መፈጸም ግድ ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ከቤተ ክርስቲያን ዕውቅና ውጪ የሚንቀሳቀሱ ሰባክያነ ወንጌል ላይ የተላለፈው ውሳኔ ተግባራዊ አለመሆኑ የሚያስከትለው ተፅዕኖ ምንድነው ይላሉ?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡- ወንጌል ሰላም ነው፡፡ ትርጉሙ አንድነት ነው፡፡ ጉዳቱ በቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያልዘለቁ፣ በመምህራን እግር ሥር ዕውቀትን ያልቀሰሙ እናስተምር ሲሉ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ ትክክለኛው ወንጌል፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተምህሮ ወደ ምእመናን ይደርሳል ለማለት አይቻልም፡፡

አንዳንድ ማሠልጠኛ ገብተው በለብለብ ምኑንም ሳያውቁ እያቋረጡ እየወጡም ገበያው ሲመቻችላቸው ዕውቅና እያገኙ ሲሔዱ ዓውደ ምሕረቱን እንደራሳቸው ያደርጉታል፡፡ ይህ ተገቢ አይደለም፡፡ ተስተካክሎ የሚያገለግል ብናገኝ እሰየው ነው፡፡ ሰው ያንሰናል እንጂ አይበዛብንም፡፡ ሁሉም የቤተ ክርስቲያን ልጆች ናቸው፡፡ ነገር ግን ከታች አጥቢያ ጀምሮ እስከ መንበረ ትርያርኩ ድረስ በመመሪያ የሚመጡ የሚወርዱ መሆን አለባቸው፡፡ ዋናው ተወስኗል፡፡ አፈጻጸሙ ላይ የሁሉም የቤተ ክርስቲያን አካላት ግዴታቸውን መወጣት አለባቸው፡፡

ያለፈቃድ ሊሰብክ የሚወጣ ካለ መቃወም፣ መከልከል ይገባል፡፡ ይህ መምሪያው ብቻውን የሚወጣው አይደለም፡፡ ጥቃቅን ችግሮች ሊያጋጥሙ ይችላሉ፡፡ ሃይማኖቱ ላይ መጠንከር ግን ይገባቸዋል፡፡ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግና ሥርዓት መሠረት አሰረ ክህነት የሌለው ወንጌል አይሰብክም፡፡ ይህ ካልሆነ ከፕሮቴስታንቱ ምን ልዩነት አለን፡፡ አሁን የመጣ እንጂ ቢያንስ ዲቁና የሌለው እንዴት ይሰብካል? በማብቂያ ምን አድርጉ ሊል ነው? የወንጌል ማሰሪያው ንስሐ ግቡ፣ ሥጋውን ደሙን ተቀበሉ ነው፡፡ ያኔ ምእመኑን ምን ሊል ይችላል? ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያንን የማያውቅ፣ ቢያንስ ዲቁና የሌለው ሲያስተምር እናያለን ይህ ጊዜው ዝም ብሎ ያመጣው ነው እንጂ የቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓት አይደለም፡፡

ይህንን መምሪያው እያጣራ ነው፡፡ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ጠብቀው ማኅበር መሥርተው ሲመጡ እንቀበላቸዋለን፤ መምህራኑ ግን ይህን ደረጃ ማለፍ ያለባቸው መሆኑን እናረጋግጣለን፡፡ ይህ የመምሪያው ሓላፊነት ነው፡፡ የወጣቱ ወደ ቤተ ክርስቲያን መምጣት ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ አካሔዱ ግን የመምሪያው ነው፡፡ መዝሙራቸው ሥርዓት መያዝ አለበት፡፡ ትምህርታቸው ሥርዓትን የጠበቀ መሆን አለበት፡፡ ይህ የቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ ነው፡፡ አፈጻጸሙ ጠቅላይ ጽ/ቤቱ፣ መምሪያው እና የየአህጉረ ስብከቶቹ ትብብር እና የምእመኑ እገዛ ላይ የተመሠረተ ነው፡፡ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅና ውጭ የሚንቀሳቀሱ ያመጡት ጉዳት ለተባለው ጤናማውን ምእመን እየበረዙ እየለያዩ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ አደጋ መፍጠር ነው፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለኅብረተሰቡም ሆነ ለመንግስት አደጋ ነው፡፡ ዛሬ በልማት እየተደረገ ያለውን ሩጫ ያደናቅፋል፡፡ ሕዝቡ ሰላም ሳይኖረው ልዩነት ካለ አደጋ ነው፡፡

ይህ ድርጊት በእምነት፣ በቀለም፣ በጎሳም አይደለም፡፡ አጠቃላይ የሰውን ልጅ ሰላም የሚነካ ነው፡፡ ስለዚህ የኛ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓተ ትምህርት ሰላም ስለሆነ ይህንኑ ማስፈጸም ላይ መትጋት ነው፡፡ ሰላማዊውን ሕዝብ ሰላም የሚነሳ ከሆነ ይህ ሰይጣናዊ ስብከት ነው፡፡ ይህን ሕዝቡ ስለሚያውቀው እኛም እግዚአብሔር የፈቀደልንን ያህል ድርጊቱን ለማስቆም እንሔዳለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ የተጠበቀውን ያህል ውጤታማ ነበር ማለት ይቻላል?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡- ጥሩ ነበር፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሩ እድገት እያሳየ ነው፡፡ የአባታዊነትን ግዳጅ እየተወጣ ነው፡፡ ሥርዓተ ቤተክርስቲያን እንዲከበር እየጣረ ነው፡፡ በነገሮች መሰናክል አይጠፋም ነገር ግን በትዕግሥት ነጥቡን እያየን ነገሮች ሁሉ ዓላማቸውን ሳይስቱ ጉባኤው በጥሩ ግብ ላይ ነው የተደመደመው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ ላይ ምን የታሰበ አቅጣጫ አለ?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡- ይህ ጉዳይ ሕጋውያን ሰባኪያን ካልሆኑት ጋር የሚገናኝ ጉዳይ ነው፡፡ ማንኛውም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ በሚሰጠው በየትኛውም ትምህርት አግባብ መስሎ ያልታየውን ተከታትሎ መረጃ መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ ዛሬ ማእከላዊነት ስላልተጠበቀ ማንን ከማን መለየት አስቸግሯል፡፡ ማእከላዊነቱን በጠበቀ መልኩ ሁሉም ነገር ከአጥቢያ እስከ መንበረ ትርያርክ ሲኬድ ሁሉም ግልጽ ይሆናል፡፡ አንዳንዶች በየአጥቢያው ቤተ ክርስቲያን የግል ደጋፊ /ቲፎዞ/ ያበጃሉ፡፡ እነዚህ በገንዘብ፣ በጥቅም… ስለሚገቡ አጥቢያዎች የራሳቸውን ጥረት አድርገው በጥንቃቄ መለየት አለባቸው፡፡ በአሁኑ ወቅት የመናፍቃን እንቅስቃሴ ይህ ነው አይባልም፤ እንደአሸን ፈልተዋል፡፡

በኑሮ እያሳበቡ አንዳንዶች መምህራንና መነኮሳት ጭምር ስም ለውጠው ወደ ሌላ ሔደዋል የሚባል ነገር ይሰማል፡፡ ሃይማኖት ደግሞ ከኑሮ ጋር አይያያዝም፡፡ ይህ እንዲቆም ሁሉም መትጋት አለበት፡፡ ስለዚህ መጠንከር ነው፡፡ በተለይ ብፁዓን አባቶች መጠንከር አለባቸው የሲኖዶስ ጥንካሬ ነው መፍትሔው፡፡ ነገሮችን አይቶ መዝኖ ይወስናል፡፡ አፈጻጸሙን ይከታተላል ያኔ መናፍቃን ይህን መንጋ ይወስዳሉ ብለን አንሰጋም፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የቤተ ክርስቲያኒቱ ልዕልና እንዲከበር፣ ታሪኳ፣ ቅርሷ፣ ትምህርቷ ዶግማዋና ቀኖናዋ ተጠብቆ ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ ከምእመናንም ሆነ ከሌሎች የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮች ምን ይበቃል?

ብፁዕ አቡነ ማርቆስ፡- ከታች እስከ ላይ የወንጌል መረብ እንዲዘረጋ በቀና መንፈስ ነገሮችን መመልከት ነው፡፡ ዘመኑን የዋጀ ትምህርት ለምእመናን ማድረስ ቤተ ክርስቲያን ሓላፊነት አለባት፡፡ ሕዝቡም መመሪያ ጠብቆ መገልገል አለበት፡፡ የጸሎት፣ የንስሐ ትምህርትን ማግኘት አለበት፡፡ ለዚህ ቀና መሆን ነው፡፡ በፍቅር በአንድነት ለአንድ ዓላማ መቆም ነው፡፡ እናት ቤተ ክርስቲያን ሁሉን ትይዛለች፤ የሕዝቡን ሥነ ምግባር፣ ሞራል፣ ሥርዓት ጠብቃ የኖረች ናት፡፡ ይህ አዲስ አይደለም፡፡ አሁን የመጣው ዕውቀት ሳይኖረው ሰባኪ ነኝ እያለ ሕዝቡን ማለያየት ሁከት መፍጠር ነው፡፡ የሚገባው ግን እውነተኛውን ወንጌል፣ የቅዱሳንን ታሪክ ገድላቸውን መስማት ነው፡፡ ይህ ትጥቅ ነው፡፡ ቅዱሳኑ እንዴት ሆነው እንደሞቱ፣ መከራን እንደተቀበሉ እንደሽንኩርት እንደድንች እንደተላጡ መመርመር ያስፈልጋል፡፡ እንዲህ ሆነው ያለፉት ወንጀል ፈጽመው አይደለም ዓለምን ለማዳን ነው። ስለዚህ ብዙ ችግር የለም መዋቅር መጠበቅ ብቻ ነው፡፡ ሰፊ ክፍተት ስንፈጥር ነው ሌላው ያለአግባብ ውስጣችን የሚገባው፡፡

እስካሁን ያለፈው ሳያስጨንቀን ለወደፊቱ ተግቶ መሥራት ነው፡፡ ወንጌል በጥላቻ አይሰበክም፡፡ ፍቅርን ሰላምን ለማምጣት ትክክለኛው የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መጠበቅ ነው፡፡ ዋናው ለቤተ ክርስቲያን መኖር ነው፡፡ መኖር ማለት እናት ለልጇ አባትም ለልጁ እንደሚኖሩት ማለት ነው፡፡ የእነርሱ ተግባር አስፈላጊውን መስዋዕት ከፍሎ ልጅን ማሳደግ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ምእመናንም እንደዚያ መኖር አለባችሁ፡፡ ንስሐ መግባት፣ ሥጋውን ደሙን መቀበል፣ ጥላቻን ማስወገድ፣ እውነተኛ ሰባኪያንን አይዟችሁ ማለት ይገባል፡፡ አይሁድ «ትንሣኤው የለም» በማለት ወንጌል ረጭተዋል፤ ምእመናን ደግሞ «ወንጌል አለ ትንሣኤ አለ» በማለት ገንዘብ ማውጣት አለባቸው፡፡ ስለዚህ እርሱን ነው ለቤተ ክርስቲያን መኖር የምንለው፡፡ በተረፈ በጥላቻ የሚሆን ነገር የለም፤ በውይይት ግን ድል እናደርጋለን እግዚአብሔርም ይረዳናል፡፡

«ሌሎችን ለማምጣት እያሰብን ያሉትን እንዳናጣ መጠንቀቅ ይኖርብናል»

 ብፁዕ አቡነ ቀሌሜንጦስ/ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሊቀ ጳጳስስምዐ ጽድቅ፡- የቅዱስ ሲኖዶስ የርክበ ካህናት ጉባኤ አጀማመርና አጨራረስ ምን ይመስል ነበር?
ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- ጥሩ ነው፤ መጨረሻው ሁሉም እንዲታይ ሆኖ ተካሒዷል፡፡ ውሳኔዎቹ ሁሉም ጥሩ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ የጉባኤው አፈጻጸም ጥሩ ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ከሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ እና ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በተያያዘ የተነሡ አሳቦች እና ውሳኔዎች ምን ይመስሉ ነበር?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡ – አንዱ በአጀንዳነት የተያዘው ይኸው ነበር፡፡ በሁለቱም ወገን ችግሮችና ጥያቄዎች ነበሩ፡፡ ችግሩ ይታይ የሚለው የኛ አቋም ነበር፡፡ ለሁለቱም አካላት ደንብ የሰጠ ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡ ማየትም የሚችለው ቅዱስ ሲኖዶስ በመሆኑ ችግሩ ተጠንቶ ይቅረብ ወደሚለው መደምደሚያ ላይ ተደርሷል፡፡ ውሳኔውም ይኸው ነው፡፡ በአሠራር ማለትም በአገልግሎትም ይሁን በግል ጉዳይ ችግሩ የት እንደሆነ አጥንቶ የሚያቀርብ አካል ተመርጧል፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- አጣሪው አካል ማነው? ማንን ማንን ያካትታል?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- ከአባቶችና ከሊቃውንት የተውጣጣ ነው፡፡ ሦስት ሊቃነ ጳጳሳት ማለትም፤ አቡነ ገሪማ፣ አቡነ ሕዝቅኤል፣ አቡነ ማርቆስ እንዲሁም መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን፣ ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገ/አማኑኤል፣ መልዐከ ምሕረት ዓምደ ብርሃን፣ ከሊቃውንት ጉባኤ፣ ከሕግ ክፍል አቶ ይስሐቅ ናቸው፡፡ ከአሁን ጀምሮ ሥራቸውን ይጀምራሉ ማለት ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በሁለቱም ወገን ያለው ችግር መንሥኤ ምን ይሆናል ብለው ያስባሉ?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- በውጭ ሰፍቶ የምናየው ችግር ውስጡ ገብተን ብናየው ቀላል ሊሆን ይችላል፡፡ ክፍተት ግን አለ፡፡ ምናልባት የአሠራር ወይንም የአፈጻጸም ችግር ጉዳዩን እንዲጎላ አድርጎታል ብዬ አስባለሁ፡፡ ከሁለቱም ወገን ስሕተቱ የት ነው የሚለውን ለመለየት የጥናቱ ውጤት ወሳኝ ነው፡፡ ማን ምንድነው? ደንቡስ ምን ይላል? የሚለው በአጥኚዎች ተፈትሾ ለምልዐተ ጉባኤው ሲቀርብ ውሳኔ ይሰጥበታል፡፡ ዝርዝር ችግሮቻቸው ምንድናቸው የሚለውን አሁን ማወቅ አይቻልም መንሥኤውንም እንዲሁ የአጥኚዎቹ ሥራ ነው፡፡ ለሚቀጥለው ጥቅምት የጥናቱ ውጤት ይታያል ማለት ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ኮሚቴ መዋቀሩና ጥናት መካሔዱ ለችግሩ መፍትሔ ያመጣል ብለው ያስባሉ?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- አዎ ያመጣል ጉዳዩ ሰፋ እያለ ሲሔድ ሁለቱንም አካላት የሚያወዛግባቸው ነገር ግልጥ እያለ ይሔዳል፡፡ ጉባኤውም የጥናት ውጤቱን ተከትሎ የሚሰጠው ውሳኔ መፍትሔን ያመጣል ብዬ አምናለሁ፡፡ ከሕግ ስሕተትም ካለ እየታረመ፣ ማስጠንቀቂያም እየተሰጠ ችግሮች እየወጡ መወያየት የሚቻልበትን ሁኔታ መፍጠር ይገባል፡፡ ማመንም ማሳመንም ይገባል፡፡ ይህ የአሠራር ሒደት ነው፡፡ ስለዚህ ማደራጃ መምሪያው ዋናው ሥራው ወጣቱ ላይ ነው፡፡ አይደለም ያሉትን እና የተያዙትን ሌሎችንም ወጣቶች ወደ ቤተ ክርስቲያኒቱ መሳብ ይገባዋል፡፡ ካሉት ጋራ ውዝግብ ከመፍጠር አገልግሎት ላይ ትኩረት ማድረግ የተሻለ ነው፡፡ ተገቢው ነገር ደንብና ሥርዓት ተከብሮ በመነጋገር ጥቃቅን ችግሮችን መፍታትና ወጣቱን መያዝ የሚገባ ነው፡፡ ሌሎችን ለማምጣት እያሰብን ያሉትን እንዳናጣ መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡ ይህንን ቀላል ጉዳይ ተነጋግረን መፍታት ካልቻልን ሑከት ፈጣሪዎች እኛው ነን ማለት ነው፡፡ ይህ በጣም ለልማት እንቅፋት መሆን ማለት ነው፡፡ እኛ መርዳት እና ለሰላም አስተዋጽኦ ማድረግ ሲገባን እንዲህ ውዝግብ ውስጥ መግባቱ አግባብ አይደለም፡፡ ዓለም እየሮጠ ነው፡፡ ሕዝቡን በሰላምና በፍቅር አሰልፈን መጓዝ አለብን፡ ዋናው ትኩረታችን ወጣቱ ነው፡፡ እነርሱ ላይ መሥራት አለብን ይህ የተደራጀው ኃይል ለሀገርም ለቤተ ክርስቲያንም ጠቃሚ ኃይል ነው፡፡ በአእምሮው፣ በገንዘቡ፣ በጉልበቱ ሀገሩን እና ቤተ ክርስቲያንን የሚያለማውን ወጣት ማገዝ ይገባል፡፡ መምራት ይገባል፡፡ እነርሱ ዘንድ ጥፋት ካለ በእኛ ምክርና ግሳጼ ይታረማሉ ብለን እናምናለን፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- በመጨረሻ የሚያስተላልፉት መልእክት አለ?

ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፡- ሰላም ለሁሉም ወሳኝ ነው፡፡ ሰላም ብለን ስንናገር ቀላል ነው፡፡ ወደ ሥራው ስንገባ ያደክማል፡፡ ሰው ራሱን ለሰላም ማዘጋጀት አለበት፡፡ ስለዚህ ሁለቱም አካላት ለዚህ ተገዢ መሆን አለባቸው፡፡ ደንቡ ሥርዓቱ ሊገዛቸው ይገባል፡፡ ለዚህ መቻቻል መከባበር ይገባል፣ የግል ጉዳይ የለም ሁሉም የሚሠራው ለቤተ ክርስቲያኒቱ ነው፡፡ አጀንዳችን ሁሉ ቤተ ክርስቲያን መሆን አለበት፡፡ ሰላም ካለ ለመደመጥም፣ ለማዳመጥም ለመምራትም ለመመራትም ይበጃል፡፡ የሁለቱም ወገን ሓላፊዎች ለዚህ ተገዢ መሆን አለባቸው፡፡ ያለ ኘሮግራም የሚሠራ ነገር ሁሉ ዋጋ የለውም፡፡ ሁሉም በፕሮግራም መመራት አለባቸው፡፡ ሁለቱም በመመሪያ እና በሕግ ቢመሩ ክብር አላቸው፣ ተወዳጅነት አላቸው፣ ውጤታማ ሥራም ይሠራል፣ ግንኙነታቸውም ይጠብቃል፡፡

hawire_Hiwot2.jpg

ከ 3000 በላይ ምዕመናን ይሳተፉበታል ተብሎ የሚጠበቅ መንፈሳዊ ጉዞ ተዘጋጀ

በተ/ሥላሴ ፀጋ ኪሮስ

ሰኔ 15 ቀን 2003 ዓ.ም

ከ6 ወራት በፊት ተዘጋጅቶ እንደነበረው በርካታ ምእመናን የሚሳተፉበት መንፈሳዊ ጉዞ ተዘጋጀ፡፡ ሐዊረ ሕይወት ቁጥር 2 የሚል ስያሜ ያለው ይህ ጉዞ ሰኔ 19 ቀን 2003 ዓ.ም ይከናወናል፡፡

hawire_Hiwot2.jpg

ከአዲስ አበባ 108 ኪ.ሜ ርቆ ፍቼ ከተማ ወደ ሚገኘው መካነ ሰማዕት አቡነ ጴጥሮስ ገዳም የሚደረገው ይህ ጉዞ መንፈሳዊ ሕይወታችን የምናጠነክርበት ይህም ከሆነ ዘንድ በቤተ ክርስቲያን የእኛ ድርሻ ምንድን ነው? ብለን ራሳችንን እንድንጠይቅና ኃላፊነታችንን እንድንወጣ የሚያስችል እንደሆነ የጉዞው አስተባባሪ ቀሲስ አንተነህ ጌጡ ተናግረዋል፡፡

ሐዊረ ሕይወት ምእመናን ከመኖሪያና ከሥራ ቦታቸው ራቅ ብለው በተሰበሰበ ልቡና የቅዱሳን ሰማዕታትና የጻድቃን በረከት በሚገኝበት ቦታ ተረጋግቶ ራስን እንዲያዩ የሚያስችል፣ የአበውን ተጋድሎ በመመልከትና በማስታወስ ከፍ ወደ አለ ሥነ ልቡና የሚያደርስና የቤተ ክርስቲያንን ጣዕም የሚያሳይ መንፈሳዊ ጉዞ እንዲሆን ታስቦ እየተዘጋጀ እንደሆነ በአስተባባሪዎቹ ተያይዞ ተገልጿል፡፡

በኢትዮጵያ አንድና ብቸኛ ወደ ሆነው የአቡነ ጴጥሮስ ገዳም በሚደረገው ጉዞ በሐዊረ ሕይወት ቁጥር አንድ ጉዞ ወቅት ተነስተው ላልተመለሱና አሁንም ለሚነሱ ጥያቄዎች ሰፋ ባለ ሁኔታ በአበው ሊቃውንት መልስ የሚሰጥበት የምክረ አበውን ዝግጅት በድጋሚ አካቷል፡፡ ባለፈው ከነበሩ መምህራንና ሊቃውንት በተጨማሪም ሌሎች በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙበት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በተለይም ይህ ጉዞ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ተረድተን መፍትሔ ፍለጋ ለመሄድ አቅጣጫ የሚሰጥ እንደሆነ አጽንኦት ተሰጥቶበታል፡፡

“ገዳሙ አንድና ብቸኛ መሆኑና ከአካባቢው ምእመናን በስተቀር በብዙው ኅብረተሰብ ዘንድ አይታወቅም በአሁኑ ጉዞ ወደ 3000 ምእመናን ይዘን እንጓዛለን ብለን እናስባለን” ያሉት ቀሲስ አንተነህ የሄዱት ምእመናን ለሌሎች ስለሚያስተላልፉ ገዳሙን በቀላሉ ማስተዋወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም ምዕመናን የራሳቸውን አስተዋጽኦ ለገዳሙ እንዲያበረክቱ ያደርጋል ሲሉ ሌላኛውን አላማ ተናግረዋል፡፡

ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሊቀ ጳጳስ ዘምሥራቅ ኢትዮጵያ የኢጣሊያ ጦር ሀገራችን ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት አርበኞችን በማስተባበር በጀግንነት ያዋጉ ሲሆን በጦርነቱ መሃል ተይዘው ስለሃይማኖታቸው በመመስከር የሀገራቸውን መሬትም ለፋሽስት እንዳትገዛ በመገዘት ሐምሌ 22 ቀን 1928 በሰማዕትነት ያረፉ አባት ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በ2001 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ ጽላት ተቀርጾላቸው እንዲሁም በስማቸው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በትውልድ ሀገራቸው ሰርታ ሰማዕተ ጽድቅ ዘኢትዮጵያ እያለች ታከብራቸዋልች፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለምዕመናን መንፈሳዊ ሕይወት መጠንከር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቁ የተለያዩ መንፈስዊ ጉዞዎችን እንደሚያዘጋጁ የገለፁት ቀሲስ አንተነህ በቅርብ ጊዜ የአዲስ አበባ ማዕከል ባዘጋጀው መንፈሳዊ ጉዞ ከ3000 በላይ ምእመናንን የማኅበረሩን አባላት ሌሎች ማኅበራችንና ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ይዞ ወደ ደብር ቅዱስ ደብር ጽጌ ማርያም ገዳም ያደረገውን የሐዊረ ሕይወት ቁጥር አንድ ጉዞን ተጠቃሽ አድርገዋል፡፡

አጭሩ ዘኪዮስ(ለሕፃናት)

ሰኔ11 ፣2003 ዓ.ም

አዜብ ገብሩ

ዘኪዮስ የሚባል አጭር ሀብታም ሰው ነበረ፡፡ ኢየሱሱ ክርስቶስን ለማየት በጣም ይፈልግ ነበር፡፡ ምክንያቱም ስለ እርሱ ብዙ ነገር ሲነገር ይሰማ ስለነበረ ነው፡፡ ጌታችን በዛሬው ዕለት ኢያሪኮ ወደምትባለው ከተማ ይገባል ብለው ሰዎች ሲያወሩ ዘኪዮስ ሰማ፡፡

ዘኪዮስም ይህን ሲሰማ ከቤቱ ጌታችንን ለማየት ወጣ፡፡ ከሩቅም ብዙ ሰዎች ተሰብስበው ሲመጡ  አየ፡፡ “ምንድን ነው ነገሩ?” ብሎ ጠየቀ ሰዎቹም ጌታችን እየመጣ እንደሆነ ነገሩት፡፡ ዘኪዮስም ጥቂት ካሰበ በኋላ እንዲህ አለ፡፡ “እኔ አጭር ነኝ ከዚህ ሁሉ ከተሰበሰበው ሰው ለይቼ ጌታችንን እንዴት ላየው እችላለሁ?” ከዛም ወደ ተሰበሰበው ሰው ተጠጋና አንድ የሾላ ዛፍ ላይ ወጣ፡፡ ልጆች ዛፉ በጣም ረዥም ስለሆነ ለመውጣት አስቸጋሪ ነበር፡፡

ዘኪዮስ ግን ጌታችንን ለማየት ካለው ፍላጎት የተነሳ በብዙ ጥረት ዛፉ ላይ ወጣ፡፡ የተሰበሰበው ሰው ዘኪዮስ ወዳለበት ዛፍ መጠጋት ጀመረ፡፡ ሕፃናት፣ ሴቶች፣ ወጣቶች ጌታችንን ከበውት ነበር፡፡ ጌታችንን በጣም ስለሚወዱት ከእርሱ አይለዩም ነበር፡፡ የተሰበሰበው ሰው የሾላውን ዛፍ ማለፍ ጀመረ፡፡ ጌታችን ግን ቆመ፡፡ ቀና ብሎም ዘኪዮስን ተመለከተው፡፡ “ዘኪዮስ ሆይ ና ውረድ” ብሎም ጠራው፡፡ ዘኪዮስም በደስታ ከዛፉ ላይ ወረደ ከዛም ጌታችን ለዘኪዮስ እንዲህ አለው “ዛሬ ወደቤትህ እገባለሁ፡፡ ከአንተ ጋርም ራት  እበላለሁ፡፡” ዘኪዮስም በደስታ ተቀበለው በቤቱም አስተናገደው፡፡

ልጆች ጌታችን እኛ ስለራሳችን ከምናስበው በላይ እርሱ ለእኛ እንደሚያስብልን ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡ ዘኪዮስ የፈለገው ጌታችንን ማየት ብቻ ነበር፡፡ ጌታችን ግን ከማየትም አልፎ ከእርሱ ጋር ራት እንደሚበላ ነገረው፡፡ ዘኪዮስ ካሰበው በላይ ጌታችን መልካም ነገርን አደረገለት፡፡ ሌላው ደግሞ ልጆች እንደዘኪዮስ እንግዳ ተቀባይ መሆን አለባችሁ፡፡ ዘኪዮስ ጌታችንን ደስ ብሎት እንዳስተናገደው እናንተም ወደቤታችሁ የመጣውን ሁሉ ትንሽ ትልቅ ሀብታም ድሃ ብላችሁ ሳትለዩ ሁሉንም በፍቅር ማስተናገድ አለባችሁ፡፡ በሉ እንግዲህ ልጆች በሌላ ጽሑፍ እስከምንገናኝ ደህና ሁኑ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የግቢ ጉባኤያትን ተማሪዎች መንፈሳዊ ሕይወት ለማሳደግ የሚያስችል የንሰሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ

በእንዳለ ደጀኔ

ሰኔ 10 ቀን 2003 ዓ.ም 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን መንፈሳዊ ህይወት ለማሳደግ የሚያስችል የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ፡፡
ከግንቦት 24 እስከ ግንቦት 26 ቀን 2003 ዓ.ም አዲስ አበባ ላይ በተካሔደው የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንሰሐ አባቶች ሴሚናር በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ ግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የንስሐ አባቶች ተወካዮች የተሳተፉ ሲሆን፥ በሴሚናሩም በቤተክርስቲያን ወቅታዊ ሁኔታ የንስሐ አባቶች ሚና፣ ለግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች መንፈሳዊ እድገት የንስሐ አባቶች ሚና፣ ሉአላዊነት ዘመናዊነት በተለይ ከአንቀጸ ንስሐ አንፃር፣ የግብጽ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ተሞክሮ ወጣቶችን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ከማዘጋጀት አንፃር እና የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ግቢ ጉባኤያትን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ከማዘጋጀት አንፃር የሚሉ ርዕሰ ጉዳዮችን መሠረት ያደረገ ነበር፡፡

ለመጀመሪያ ጊዜ በተዘጋጀው በዚህ የግቢ ጉባኤያት የንስሐ አባቶች ሴሚናር ቁጥራቸው 50 የሚደርሱ አባቶች መሳተፋቸው ታውቋል፡፡

በካህናቱ አቀባበል ላይ የተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም «እናንተን አባቶች እዚህ ድረስ እንድትመጡ ያስቸገርነው በግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች አገልግሎት ያላችሁ ድርሻ ታላቅ በመሆኑ ነው» ብለዋል፡፡

በሴሚናሩ ላይም ብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተገኝተው ቡራኬና ቃል ምዕዳን የሰጡ ሲሆን «ማኅበሩ የሚያደርገው የልጅነት ድርሻውን በማገዝ እናንተ ካህናት ትልቁን ድርሻ ትይዛላችሁ» ብለዋል፡፡

ለ3 ቀናት በተካሔደው በዚህ ሴሚናር «እጅግ በጣም ተደስተናል» ያሉት ተሳታፊ ካህናቱ «ቀጣዩን ትውልዱ በመቅረጽና ለሀገርና ለቤተክርስቲያን ብቁና በሥነ-ምግባር የታነፁ ለማድረግ የምንችልበትን ግንዛቤ አግኝተናል። ይህም ካህናት ባገኘነው ግንዛቤና ልምድ ተነሳስተን ውጤታማ ሥራዎችን እንሰራለን» ብለዋል፡፡

ሴሚናሩም ሊቃውንቱን እርስ በእርስ ያስተዋወቀና በመረጃም ረገድ ልምድ ለመለዋወጥ መነሳሳትን እንደፈጠረላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡

hohitebirhan.jpg

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የተሐድሶ እንቅስቃሴ አለን? ዓላማውና ስልቱስ ምንድን ነው?

ሰኔ 11 ቀን 2003 ዓ.ም

/ምንጭ፦ ስምዐ ጽድቅ ልዩ እትም ግንቦት 2003 ዓ.ም/

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን “መታደስ አለባት” የሚሉ ድምፆችን የሚያሰሙ አካላት አሳባቸውን በተለያዩ መንገዶች ማሰማት ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ እነዚህ አካላት በመጽሔቶች፣ በጋዜጦች፣ በመጻሕፍት፣ በበራሪ ወረቀቶች፣ በዓውደ ምሕረት ስብከቶችና በሚያገኟቸው አጋጣሚዎች ሁሉ ይኸን ጩኸታቸውን ማስተጋባቱን ተያይዘውታል፡፡ እንዲህ እያሉ ያሉትም “ኦርቶዶክሳውያን ነን” እያሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ በተለያየ ቦታና ሓላፊነት ላይ ካሉና እንጀራዋን ከሚበሉ፣ ጥቂቶች እንዲሁም ደግሞ በኅቡእና በግልጽ በተለያየ መልክና ቅርጽ ራሳቸውን አደራጅተው ቤተ ክርስቲያኗ ሳትወክላቸው እርሷን ወክለው፣ “እኛም ኦርቶዶክስ ነን” በሚል ካባ ራሳቸውን ደብቀው እምነቷንና ሥርዓቷን “ይህ ሳይሆን ሌላ ነበር” እያሉ ፕሮቴስታንታዊ ትምህርትና መንፈስ የተዋረሳቸው ሰዎች ናቸው፡፡

 
ተሐድሶ የሚባል ነገር አለን? እነዚህ አካላት በአንድ በኩል ተሐድሶ የሚባል ነገር እንደሌለና ተሐድሶ የሚባለው ጉዳይ የሆነ አካል (እነርሱ እንደሚሉት ማኅበረ ቅዱሳን) ስም ለማጥፋት ሲል የፈጠረው የፈጠራ ወሬ እንጂ በሕይወት የሌለ ምናባዊ ነገር እንደሆነ ያስወራሉ፣ ይናገራሉ፡፡ ግን በእውነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዶግማዋ፣ ቀኖናዋና ትውፊቷ መታደስ አለበት በማለት የሚሠራ የተሐድሶ እቅስቃሴ የለምን?

ይህን ጉዳይ እነርሱው በይፋ ካወጧቸው የኅትመት ውጤቶቻቸው ለመመልከትና ለመታዘብ ይረዳ ዘንድ ራሳቸው በተለያዩ መጻሕፍቶቻቸው፣ መጽሔቶቻቸውና ጋዜጦቻቸው ካወጧቸው መካከል የተወሰኑትን ብቻ እንመልከት፡-

hohitebirhan.jpg

“እንደ እውነቱ ከሆነ በወንጌል እውነት ከታደሱ በኋላ በየጊዜው እየተመዘዙ የወጡት ምእመናኖቿና አገልጋዮቿ በውስጧ ቆይተው የተሐድሶን ሥራ እንዲሠሩ ቢደረግ ኖሮ፣ በወንጌል ተሐድሶ ያገኙ ክርስቲያኖች ለዓመታት የጸለዩበትንና የጓጉለትን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተሐድሶ በቅርብ ጊዜ ሊያዩ ይችሉ እንደ ነበር የሚያምኑ ጥቂቶች አይደሉም፡፡” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት 2002፣ ገጽ 15)

 


“ተሐድሶ እንቅስቃሴ በመሆኑ፣ እንቅስቃሴም ውጤታማና ትርፋማ ይሆን ዘንድ ዓላማን፣ ሒደትንና ግብን የያዘ ድርጊት እየተከናወነበት ያለ ሊሆን ስለሚገባው፣ ያለፈውና እየሆነ ያለው ግብረ ተሐድሶ ተመዝግቦ ለአሁኑና ለሚመጣው ትውልድ በሥነ ጽሑፍ ዳብሮና አምሮ ሊቀርብለት ይገባዋል፡፡” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት2002፣ ገጽ 17) “በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ገብተን አረሞችን በገሀድ ካልነቀልን ተሐድሶን እንዴት ልናመጣ እንችላለን? መባሉ አይቀርም፡፡ ዳሩ ግን ስሕተቶችን ፊትለፊት ሳይቃወሙ ስሕተቶች እንዲታረሙ ማድረግ የሚቻልባቸው የተፈተኑ መንገዶች አሉ፡፡ ለምሳሌም …” (ኆኅተ ብርሃን፣መጋቢት 2002፣ ገጽ 19)

metkie.jpg


“ከ2000 ዘመናት በላይ ያስቆጠረች የእኛ ቤተ ክርስቲያንማ እንዴት አብልጦ ተሐድሶ (መታደስ) አያስፈልጋት?” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 15) “ቤተ ክርስቲያናችን በክፉ ሰዎች ሴራ ዓላማዋን ስታለች፣ የሐዋርያትንም ትምህርት ገፍታለች፣ ስለ ሆነም ይህን የሐዋርያት ትምህርት በክፉዎች ምክንያት በመጣሱ በድፍረት ተሳስተሻልና ታረሚ ልንላት፣ በድፍረትም በሥልጣንም ሕዝቡን ልናስተምር ይገባል፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 20) “ቤተ ክርስቲያናችን በየሀገሩ የተነሣውን የተሐድሶ የወንጌል እሳት በተለይ በሐረር፣ በባሕር ዳር፣ በአዲስ አበባ፣ በማርቆስ፣ በጎንደር፣ በሰሜን ሸዋ፣ በወሎ፣ በትግራይ፣ በባሌ ለማዳፈን ያን ሁሉ እልፍ አእላፍ ሠራዊት የቤተ ክርስቲያን አለኝታ ወጣት ወንጌል ባልገባቸው ምእመናንና ካህናት እያስደበደበች ለሌላ ድርጅት አሳልፋ ከመስጠት ይልቅ ስሕተቷን አርማ ልጆቿን በጉያዋ ብትይዝ ኖሮ ዛሬም ጭምር ጋብ ላላለው ፍጥጫ አትዳረግም ነበር፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 16) “ሕዝባችን በልማድና በባህል ሃይማኖትን መያዙና ይህን የያዘውን ሃይማኖት ለመጣልና ለማጣራትም በቂ እውቀት ስለሚጎድለው በራሱ አንብቦ መረዳት ስለማይችል …” (የሚያሳውቁት ሃይማኖትን ለማስጣል ነው ማለት ነው) (ይነጋል፣ 1997፣ ገጽ 144)

 


እነዚህ እነርሱው ከጻፏቸውና አሳትመው ካሰራጯቸው መካከል ለአብነት ያህል የተጠቀሱት በግልጽ የሚያሳዩን ነገር ቢኖር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እምነትና ትምህርት የሚቃወሙና ሊለወጥ ይገባል የሚሉ ራሳቸውን “ተሐድሶ” የሚል ስያሜ ሰጥተው በተለየ መልክና ቅርጽ በግልጽና በኅቡእ እየሠሩ ያሉ አካላት መኖራቸውን ነው፡፡ ራሳቸው እንዲህ በይፋ “እኛ አለን፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስ ቲያን ተሐድሶ ያስፈልጋታል” እያሉ እየተናገሩ “አይ፣ ተሐድሶ የሚባል ነገር የለም” ማለት እንዴት ይቻላል?

ዓላማቸው ምንድን ነው? ተሐድሶዎች ዋና ዓላማቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖናና ትውፊት በመለወጥ ፕሮቴስታንታዊ ይዘት እንዲኖረው ማድረግ ነው፡፡ ምእራባውያን ሚሲዮናውያን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አጥፍቶ ፕሮቴስታንታዊ ለማድረግ መሥራት ከጀመሩበት ከሃያኛው መቶ ዓመት መጀመሪያ አንሥቶ እስከ አሁን ድረስ ሦስት ስልቶችን ተጠቅመዋል፡፡ የመጀመሪያው እስከ 1950 ዓ.ም ድረስ የሠሩበት ስልት ሲሆን እርሱም የራሳቸውን አስተምህሮ ማስተማር ነበር፡፡

ከ1950 ዓመት ጀምሮ እስከ 1990 ዓ.ም ድረስ ደግሞ የሠሩት የራሳቸውን እምነት መሰበክ ሳይሆን በዋናነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በመንቀፍና በማጥላላት ምእመኑ እንዲኮበልል በማድረግ ነበር፡፡

ከ1990 ዓ.ም ጀምሮ እስከ አሁን እየሠሩበት ያለው ሦስተኛው ስልት ደግሞ "ኦርቶዶክስ ነኝ" ብሎ ውስጧ ገብቶ “ትታደስ” እያሉ በመጮኽ ቤተ ክርስቲያኗ እንዳለች እንድትለወጥ በማድረግ ምእመናኗን ከእነ ሕንፃዋና አስተዳደራዊ መዋቅሯ መረከብ ነው፡፡ የእነርሱ ምኞትና እቅድ የኢትዮጵያን ቤተክርስቲያን ወደ ሦስተኛው ሺሕ እንዳትሻገር ማድረግ ነበር፡፡ ነገር ግን እንዳሰቡት አልሆነም፡፡ በዚህም ብስጭታቸውን በተለያዩ ሚዲያዎች ገልጸዋል፡፡ ለምሳሌም ፓውልባሊስኪ (Paul Balisky) የተባለ “የዓለም አቀፍ ተልእኮ ማኅበር” የኢትዮጵያ ዳይሬክተር በ1992 ዓ.ም በወጣው “የክርስቲያን ሳይንስ ሞኒተር” በተባለ መጽሔት በሰጠው ቃለ መጠይቅ የደከሙት ድካምና ያወጡት ገንዘብ ሁሉ ወደ ጠበቁት ግብ እንዳላደረሳቸው፡-

“ይህ ሁሉ ጥረት ቢደረግም ወንጌላውያኑ አሁን በማደግ ላይና በመካከለኛ ኑሮ ላይ ያለውን የከተማውን ኅብረተሰብ መቀየር አልቻሉም፡፡ ምክንያቱም የተማረና ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ከፍተኛ ቅንዓት ያለው የወጣቶች ኃይል ማኅበረ ቅዱሳን የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በሃያ አንደኛው መ/ክ/ዘመን ዘልቃ መጓዝ ትችል ዘንድ እየተጋደለ ነውና፡፡” በማለት ከሃያ አንደኛው ክፍለ ዘመን በፊት የማጥፋት ሕልም እንደነበራቸው ገልጸዋል፡፡(The Christian Science Monitor, 8 June, 2000)

ስለሆነም ከዚያ በፊት ያደርጉት እንደነበረው በውጭ ሆኖ ምእመናንን ለመንጠቅ በመሥራት ብቻ ካሰቡት ቤተ ክርስቲያኒቱን ሙሉ በሙሉ የማጥፋት ግብ ለመድረስ ቀላል እንዳልሆነ ተረዱ፡፡ ስለዚህ አዲስ ስልት መቀየስ አስፈለጋቸው፡፡ ይህም “እናድሳለን”

በሚል ሽፋን ከውጭ ወደ ውስጥ ሠርጎ በመግባት ምእመኑን እስከ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑ የመረከብ ስልት ነው፡፡ ይህንም ኬንያ ውስጥ የሚታተመው “The Horn of Africa, Challe nge and opportunity” የተባለው መጽሔት “ዓላማው አዲስ ቤተ ክርስቲያን መመሥረት አይደለም፤ ቤተ ክርስቲያኗን (ኦርቶዶክስን) መለወጥ (ፕሮቴስታንት ማድረግ) እንጂ – The objective is not to set up a new church as such but to introduce reforms within the church” በማለት ገልጾ ነበር፡፡ (The Horn of Africa, Challenge and opportunity, p. 6)

ስለዚህ አዲሱ ስልት “የጥንቷ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ትክክል ነበረች – The ancient orthodox was the right Church” የሚል ነው፡፡ ይህም ማለት ቤተ ክርስቲያንን ከውጭ ከመቃወም ይልቅ ውስጥ ገብቶ ምእመን፣ ካህን፣ መነኩሴ፣ ሰባኪ … መስሎ ከፕሮቴ ስታንት እምነትና ባህል ውጭ ያለውን ነገር ሁሉ “ይህ የጥንቷ ቤተ ክርስቲያን ትምህርት አይደለም፣ ይህን እገሌ የጨመረው ወይም የቀነሰው ነው … ’ እያሉ ቤተ ክርስቲያኗ ኦርቶዶክሳዊ ዶግማዋ፣ ቀኖናዋና ትውፊቷ በሙሉ ጠፍቶ ሙሉ በሙሉ ፕሮቴስታንት እስክትሆን ድረስ መሥራት ነው፡፡

ይህን ስልታቸውንም በኅትመቶቻቸው በይፋ ገልጸዋል፡፡ ለምሳሌም በአንድ ስልታቸውን ይፋ ባደረጉበት መጽሔታቸው ላይ እንዲህ ብለዋል፡-

“ታዲያ እርሷን (የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን) የማዳኑ ሥራ ከየት ይጀምር? እዳር ሆኖ አንዳንድ ምርኮኛን ማፍለሱ የሚፈለገውን የኦተቤን ተሐድሶ ሊያመጣ ይችላልን? አገልግሎቱ ከየት ወደ የት ቢሄድ ይሻላል? ማለት ከውስጥ ወደ ውጭ ወይስ ከውጭ ወደ ውስጥ? በውስጧ እያሉ የወንጌል እውነት ለተገለጠላቸው አገልጋዮቿ እንደ ውጊያ ቀጠና እግዚአብሔር የሰጣቸውን ምሽግ በአሁኑ ጊዜ የማስለቀቅና የጠላትን ወረዳ ከጥቃት ነጻ የማድረግ ሥራ እየተሠራ ያለው በሁለት ወገን ነው፤ … ” ይልና ቀጥሎም ወደ ግባቸው ለመድረስ መደረግ አለበት ያሉትን እንዲህ ዘርዝረዋል፡-

ውስጥ ያሉት እግዚአብሔር በሰጣቸው የውጊያ ቀጣና ውስጥ ሆነው በታማኝነት በእግዚአብሔር ቃል ምስክርነትና በጸሎት ውጊያውን መቀጠል አለባቸው፡፡ በውስጥ ላለው ለዚሁ ውጊያ በወንጌል የታደሱ ክርስቲያኖች ሁሉ እንደ ሙሴ እጃቸውን ወደ ላይ በማንሣት ታላቁን ርዳታ ማድረግና በደጀንነት መቆም ይገባቸዋል፡፡

እነዚህ በወንጌል ተሐደሶ አግኝተናል የሚሉ ሁሉ በውጭ ሆነው ወደ ውስጥ የሚያደ ርጉትን ውጊያ መቀጠላቸው እንደ ተጠበቀ ሆኖ ለውስጠኛው ውጊያ የሚያገለግል ትጥቅ ያላቸውን ወደ ውስጥ ማስገባትና የውስጠኛውን የውጊያ መስመር ማጠናከር ይጠበቅባቸዋል፡፡


“ … በዚህ የተቀናጀ ስልት መንፈሳዊው ጦርነት ቢቀጥል በውስጥ የተሰለፈው ሠራዊት (በተሐድሶ ስም የሚሠራው የፕሮቴስታንት ክንፍ) እያጠቃ ወደ ውጪ ሲገሰግስ፣በውጭ ያለውም (በግልጽ ፕሮቴስታንት ሆኖ የሚሠራው) ከበባውን አጠናክሮ ወደ ውስጥ ሲገፋ እግዚአብሔር በወሰነው ቀን የውስጡና የውጪው ሠራዊት ሲገናኙ በውስጧ የመሸገው ጠላት መሸነፉን በሚመለከት በአንድነት የድል ዝማሬ ሊያቀርቡ ይችላሉ፡፡”
(ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት 2002 ዓ.ም)

ይህ ሁሉ የሚያሳየው

ሀ) በቤተ ክርስቲያኒቷ ላይ በይፋ የተቀናጀ ጦርነት ያወጁባት መሆኑን፣

ለ) የጦርነቱ አንዱ ስልት ውስጥ ሆኖ በውስጥ አርበኝነት መሥራትና መዋጋት መሆኑን፣

ሐ) የጦርነቱ ዓላማ ጠላት የተባለችውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማፍረስ መሆን ነው፡፡


የተሐድሶው ዘመቻ ዘዴዎች ምንድን ናቸው?

ተሐድሶዎች ያሰቡትን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን እንዳለች ፕሮቴስታንታዊ አድርጎ ለውጦ ለመረከብ ያላቸውን ምኞትና ዓላማ እውን ለማድረግ የተለያዩ ዘዴዎችን ይጠቀማሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል ሁለቱ የሚከተሉት ናቸው፡፡

ሀ) የሐሰት ውንጀላዎችን መፍጠርና ማሰራጨት ሌባ ሲሰርቅ የሚያየውን ወይም መስረቁን ያወቀበትን ሰው ይወዳል ብሎ ማሰብ ከባድ ነው፡፡ እንደዚሁም እነዚህ በውጫቸው የቤተ ክርስቲያንን ለምድ የለበሱ፣ በውስጣቸው ግን ኦርቶዶክሳዊ የሆነውን እምነትና ባህል አጥፍቶ የምእራባውያን ባህል ተሸካሚ ለማድረግ የሚሠሩ ክፉ ሠራተኞች (ፊል.3÷2) ዓላማቸውንና ስልታቸውን የሚያውቅባቸውን ማንኛውንም ግለሰብም ሆነ ማኅበር አምርረው ይጠሉታል፣ ይፈሩታልም፡፡፡ በእነ ማርቲን ሉተር በአውሮፓ ተካሒዶ ምእራባውያንን ወደ እምነት አልባነትና ክህደት ማድረሱን ዛሬ በተግባር ያስመሰከረውን ተሐድሶ (ፕሮቴስታንት) በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንም ላይ እውን በማድረግ ይሁዳ ስለ ሠላሳ ብሩ ሲል ጌታውንና አምላኩን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመሸጥ ከጸሐፍትና ከፈሪሳውያን ጋር “አሳልፌ እንድሰጣችሁ ምን ትሰጡኛላችሁ?” (ማቴ.!1÷05) ብሎ ጌታውን ለሽያጭ እንዳቀረበ፣ እነዚህም ስንቅና ተስፋ የሚሰጧቸውንና ስልት ነድፈው ከርቀት እያሳዩ የሚያሠሯቸውን የላኪዎቻቸውንና የጌቶቻቸውን ምኞት ለማሳካት እንቅፋት ይሆኑብናል የሚሏቸውን ሁሉ ማሩን አምርረው ወተቱን አጥቁረው በማሳየት ስማቸውን በማጥፋት እንዲጠሉ ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡

ከዚህ ተግባራቸው ለምሳሌ ያህል ብንጠቅስ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው ሕገ ደምብ መሠረት በአባቶች ቡራኬና ፈቃድ የተመሠረተውንና በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ሆኖ ዓቅሙ በፈቀደ መጠን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘርፈ ብዙ አገልግሎት በመስጠት ላይ የሚገኘውንና ይህን ለቤተ ክርስቲያናችን እጅግ አደገኛ የሆነ የተሐድሶ እንቅስቃሴ ምንነት በማጋለጥ ለሕዝብ የሚያስረዳውን ማኅበረ ቅዱሳንን ስሙን በኅትመቶቻቸውና በልዩ ልዩ መንገድ ማጥፋትና ሰይጣናዊ አስመስሎ መሳል አንዱ ስልታቸው ነው፡፡ ለአብነት ያህልም የሚከ ተሉትን እንመልከት፡-


“ማቅ (ማኅበረ ቅዱሳን) ያለ እኔ ቤተ ክርስቲያን፣ ሀገርና መንግሥት የለም ብሎ በጭፍን የሚያስብ ስለሆነ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሌላ መንፈሳዊ ማኅበርም ሆነ ጉባኤ ለማየት ዓይኑ የተሸፈነ ነው፡፡ ራሱን የቅዳሴ፣ የቅኔና የመጻሕፍት ማስመስከሪያ ቤተ መምህራን አድርጎ በማየቱ በእርሱ እጅ ፈቃድ ያላገኙ ሰባክያንና መዘምራን ቢፈጠሩ የተለመደው የኮሚኒስቶች ፍልስፍና (የሀሰት ስም የማጥፋት ቅስቀሳውን) ያወርድባቸዋል፡፡”
(መጥቅእ፣ ኅዳር 2002፣ ገጽ 1፣ርእሰ አንቀጽ)

እንግዲህ ይህን የሚለው አካል በግልጥ ቤተ ክርስቲያኒቱ ተሐድሶ ያስፈልጋታል እያለ በዚሁ ጋዜጣ የገለጸው የተሐድሶ ድርጅት ነው፡፡ ልዩነቱ የዓላማ መሆኑን ራሳቸው ተናግረው ሲያበቁ እንደገና መልሰው ተሐድሶ መባልን የሐሰት ስም ማጥፋት ዘመቻ ነው ይላሉ፡፡ አንባቢዎቻቸው ይህን እንኳን ማገናዘብ አይችሉም ብለው ይሆን?

“የማኅበረ ቅዱሳን ትምህርት እግዚአብሔር ፍጹም ጨካኝ ስለሆነ ስለማይሰማንና በርኅራሄ ከእርሱ የተሻሉ ቅዱሳን በፊቱ ቆመው እንዲለምኑልን የእነርሱ ልመና ግድ ብሎት ስለሚምረን በአማላጅነት እንመን ይላል፡፡” (ይነጋል፣ 1997 ዓ.ም. ገጽ 123) “ማኅበረ ቅዱሳን የተባለው ይህ የሰይጣን ማኅበር አሁን ወደ ነፍሰ ገዳይነት ሊገባ ራሱን እያዘጋጀ ነው፡፡” (ይነጋል፣ 1997 ዓ.ም.ገጽ 127) ይህ የስም ማጥፋት ዘመቻ በሀገር ውስጥ ባሉ ሚዲያዎች ብቻ የተወሰነ ሳይሆን ዋናው የተሐድሶ ዘመቻ አርቃቂዎችና ስልት ነዳፊዎች በሆኑት በምእራባውያን ፓስተሮችም በብዛትና በዓይነት የሚሠራ ሥራ ነው፡፡ ለምሳሌ ያህልም ዊሊያም ብላክ የተባለው አሜሪካዊ ፓስተር አናሲሞስ በተባለው የጦማር መድረኩ ላይ የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን እንዴት ማፈራረስ እንደሚቻልና በአሁኑ ወቅትም የእርሱና መሰል ድርጅቶች ቤተ ክርስቲያንን እንዴት እየተዋጓት እንደሆነ “Struggle for the soul of the Ethiopian orthodox Church” በተሰኘው ጽሑፉ ላይ በሰፊው ገልጧል፡፡ የፕሮቴስታንት ጉዳይ አስፈጻሚ የሆነው የተሐድሶ አንቅስቃሴ ምን ማለት መሆኑን ለዓላማቸው መሳካት እንቅፋት ሆኖብናል ያለውን ነገር ሲናገር ገልጾታል፤ እንዲህ ሲል፡-

“Working against both the ongoing creep of Western values and the attempts by Reformists to restore the church, a reactionary movement called Mahebere Kidusan and led by members of the hierarchy and priests and others, are seeking to fend off any changes and to preserve aspects of the Church which they feel are crucial to their identity and Ethiopia’s place in the world. …

በሀገሪቱ ውስጥ እየተንሰራፋና ሥር እየሰደደ ያለውን ምእራባዊ ባህልና በተሐድሶ አራማጆች ቤተ ክርስቲያኒቷን ለማደስ የሚደረገውን ጥረት ሁለቱንም የሚቃወምና ለዚህም እየሠራ ያለ አድኃሪ የሆነ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባል እንቅስቃሴ አለ፡፡ ይህ ማኅበርም ቤተ ክርስቲያንን ለመለወጥ የሚደረገውን ማንኛውንም ነገር ለመከላከልና ለራሳቸው ማንነትና ኢትዮጵያ በዓለም ስላላት ቦታ አስፈላጊ ነው የሚሉትን የቤተ ክርስቲያኒቷን ገጽታ ለመጠበቅ ይፈልጋሉ፡፡”

http://www.Compassdirect.org/english/country.ethiopia/11092/ተሐድሶዎች ቤተክርስቲያናቸውን የሚወዱትንና ለእምነታቸውና ለሥርዓታቸው ተቆርቋሪ የሆኑትን ምእመናን፣ ካህናት፣ መነኮሳት … ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳን የሚባል ነገር መኖሩን ከነ ጭራሹ ያልሰሙ ሰዎች ቢሆኑም እንኳ “ማኅበረ ቅዱሳን (ማቅ)” ናቸው የሚል ታርጋ በመለጠፍ ለማሸማቀቅ ይሞክራሉ፡፡ በዚህም የተሐድሶ ጉዳይ የሌለና የሆኑ ቡድኖች ጠብና ሽኩቻ ብቻ ተደርጎ እንዲታይ ይጥራሉ፡፡ እጅግ በጣም ብዙ የሆኑ ለማመን የሚከብዱ የበሬ ወለደ ዓይነት የስም ማጥፋት ወሬዎችን በማኅበሩ ላይ በማሰራጨት ላይ ናቸው፡፡ ለምሳሌም በቅርቡ “የማኅበረ ቅዱሳን የሃያ አምስት ዓመት ስትራቴጂ ነው” በሚል ስም አንድን ሕፃን እንኳ ሊያሳምን በማይችል መልኩ ራሳቸው የፈጠሩትን አሉባልታ የማኅበሩ አስመስለው በሐሰት ማኅተም አትመው በኢንተርኔት አሰራጭተዋል፡፡ እንዲህ ዓይነት የፈጠራ ክሶችንና ስም ማጥፋቶችን ደህና አድርገው ተያይዘዋቸዋል፡፡

ለ) የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደርና መዋቅር መቆጣጠር ተሐድሶዎች ቤተ ክርስቲያኒቷን ለመለወጥና ለዓላማቸው ማስፈጸሚያ የተመቸች ለማድረግ ይረዳቸው ዘንድ ለመቆጣጠር የሚመኙት አንዱ ነገር የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደርና መዋቅር መያዝ ነው፡፡ ይህን ማድረግ ከቻሉ በቤተ ክርስቲያኒቱ አንደበት በመናገር፣ ቤተክርስቲያን ያልሆነችውን ናት፣ የሆነችውን ደግሞ አይደለችም በማለት ያሰቡትን የተሐድሶ ዓላማ ከግብ ለማድረስ ይረዳቸዋል፡፡

ወደዚህ ግብ ለመድረስም በተለያዩ ጊዜያትና ስልቶች ከመሪጌቶች፣ከቀሳውስት፣ ከመነኮሳት፣ ከዲያቆናትና ከሌሎችም መካከል በተለያየ ጥቅማ ጥቅምና ድለላ የማረኳቸውንና ያሰለጠኗቸውን ሰዎች በአስተዳደር መዋቅሩ ውስጥ ለማስገባትና ቦታውን ለመያዝ ደፋ ቀና በማለት ላይ ናቸው፡፡ በዚህም የተወሰነ ርቀት መጓዝ ችለዋል፡፡ ይህም በስልታቸው እንደ ገለጹት “መንፈሳዊ ቀውስ የደረሰበትን አስተዳደር ማረምና ማስተካከል” (ኆኅተ ብርሃን፣ መጋቢት2000፣ ገጽ 16) በሚል ሽፋን የሚካሔድ ነው፡፡

ይህን ጉዳይ እስከ የት ድረስ መግፋትና ማድረስ እንደሚፈልጉ ሲገልጹም እንዲህ ብለዋል፡-

“ማቅ (ማኅበረ ቅዱሳን) ወደደም ጠላም ቤተ ክርስቲያኒቱ በእውነት በሚወዷትና የወንጌልን እውነት በሚያገለግሉ መምህራንና ሊቃውንት ይህንም እውነት ተቀብለው አምላካቸውን በንጹሕ ልብ ሆነው በሚያመልኩ፣ በተለይም መጪው ዘመን በትካሻቸው ላይ የወደቀባቸው ከመንፈሳዊ ኮሌጆቻችን እየተመረቁ የሚወጡ የወንጌል አርበኞችና ቤተ ክርስቲያንን ይጠብቁ ዘንድ እግዚአብሔር ጳጳሳት አድርጎ የሾማቸው አባቶች በሚወስዱት የማያዳግም እርምጃ ቤተ ክርስቲያናችን ተሐድሶን ታደርጋለች፡፡” (መጥቅእ፣ ኅዳር 2000፣ ገጽ 2) ጳጳሳት ሳይቀሩ የማያዳግም እርምጃ መውሰዳቸውና ቤተ ክርስቲያኒቱን ማደሳቸው የማይቀር መሆኑን በግልጽ ተናግረዋል፡፡ ስለሆነም ይህን ሕልማቸውን እውን ለማድረግ የቤተ ክርስቲያኗን የአስተዳደር መዋቅር፣ እስከ ጵጵስና ደረጃ ያለውንም መቆጣጠር ዋና ስልታቸው ነው፡፡

ዛሬ የመነኮሱበት የማይታወቅ ሰዎች የአባቶቻችንን ቆብ አጥልቀው መስቀሉን ጨብጠው ቀሚሱን አጥልቀው ካባውን ደርበው፣ ያልሆኑትን መስለው፣ ሌሎችም የነበሩ፣ ዛሬ ግን ያልሆኑ፣ ዓላማቸውን እንደ ይሁዳ ለውጠው የክፋቱ ተባባሪ ሆነው ያሉ ሁሉ በቤተ ክርስቲያኗ ስም ሲጫወቱ ዝም እየተባሉ ስለሆነ እነዚህ ሰዎች የነገዪቱ ጳጳሳት የማይሆኑበት እድል አይኖርም ብሎ ማሰብ አይቻልም፡፡

ይልቁንም አሁን ሃይማኖታቸው በግልጽ ፕሮቴስታንት (ተሐድሶ) የሆኑና ብዙ ጉድ ያለባቸው፣ የምግባር ድቀት ያንገላታቸው፣ የሃይማኖት አባት ሆነው ምእመናንን ለማስተ ማርና ለመምራት ቀርቶ ተነሳሒ ለመሆን እንኳ የከበዳቸው ሰዎች ዓይናቸውን በጨው ታጥበው ጵጵስና ለመሾም የሲኖዶስ ስብሰባ በመጣ ቁጥር አፋፍ ላይ እየደረሱ እየተ መለሱ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ እንዲሁ ከቀጠለ እነዚህ ሰዎች አንድ ቀን የጳጳሳትን አስኬማ ደፍተው፣ በትረ ሙሴ ጨብጠው፣ “አቡነ” እገሌ ተብለው ላለመምጣታቸው ምን ዋስትና አለ? “ሞኝ ቢቃጡት የመቱት አይመስለውም” እንደሚባለው እንደ እነዚህ ዓይነት ሰዎችን ለጵጵስና እጩ አድርጎ እስከማቅረብ ደረጃስ እንዴት ሊደረስ ቻለ?

ማንነታቸው ተጣርቶ በንስሐ የሚመለሱት ቀኖና ሊሰጣቸው፣ የማይመለሱት ደግሞ ሊለዩ (ሊወገዙ) ሲገባቸው የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ሆነው በቤተ ክርስቲኒያቱ ህልውና ላይ ወሳኝ አካላት ሊሆኑ መታሰቡ በራሱ የሚያሳየው ከባድ ነገር አለ፡፡

እነዚህን ሰዎች በአድባራትና በገዳማት ዕልቅናና በተለያየ ሓላፊነት ከመሾም ጀምሮ ግልጽ የሆነ የአደባባይ ጉዳቸውን ዝም ከማለትና አልፎ አልፎም ከማበረታታት ጀምሮ በቤተ ክርስቲኒያቱ አስተዳደር ውስጥ እንዳሻቸው እንዲናኙበት የሚፈቅድና የሚመች የተሐድሶ ሰንሰለት አለማለት ይሆን?

እውነተኛ የቤተ ክርስቲያን ልጆችና አባቶች እንደ እንጀራ ልጆች እየተቆጠሩና እየተገፉ እነዚህ ተሐድሶዎች ደግሞ ባለሟሎች መስለው ከዚያም አልፎ ለጵጵስና ታጭተው ማየትና መስማት በእጅጉ ያማል፣ ልብንም ያደማል፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሰዎች አናት ላይ ወጥተው የጵጵስና መዓርግ ጨብጠው ከመጡ በኋላ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ሊያመጡ ያሰቡትን ስልታዊ አደጋ መገመት ውኃን የመጠጣት ያህል ቀላል ነው፡፡

ስለሆነም እነርሱ ያሰቡት ከባድ ትርምስ ሳይመጣ ‹ሳይቃጠል በቅጠል› እንዲሉ በጊዜ ከጸሎት ጀምሮ ማንኛውም ሊደረግ የሚገባውን የመከላከል ሥራ ከወዲሁ መፈጸም ይገባል፡፡ ቁጭ ብሎ የሰቀሉትን ቆሞ ማውረድ ያቅታልና፡፡ ይህም “እነ እገሌ ምን እየሠሩ ነው?” በሚለው ያልጠቀመን ፈሊጥ ሳይሆን “እኔ ምን አደረግሁ?

አሁንስ ምን ማድረግ አለብኝ?” በሚል ሊሆን ይገባል፡፡ የቤተ ክርስቲያን አምላክ እግዚአብሔር በቤቱ የተሰገሰጉ ይሁዳዎችን የሚያጋልጥበትንና ከመንጋው የሚለይበትን ዘመን ያቅርብልን፣ አሜን፡፡

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን አረፉ።

ከባህር ዳር ማእከል

ሰኔ 9 ቀን 2003 ዓ.ም

መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁንበባህር ዳር ከተማ በሚገኘው ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳምን ከ40 ዓመት በላይ በአስተዳዳሪነት ያገለገሉት መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ፋንታሁን በጠና ከታመሙ በኋላ በተወለዱ በ80 ዓመታቸው ግንቦት 30 ቀን 2003 ዓ.ም ከምሽቱ 2፡00 ሰዓት አርፈዋል። 

ሥርዓተ ቀብራቸው ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ፣ ብፁዕ አቡነ ኤልያስና ብፁዕ አቡነ ቶማስ፣ ብፁዕ አቡነ ማርቆስ እንዲሁም ወዳጅ ዘመድና ቤተሰቦቻቸው በተገኙበት በፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም በዕለተ ሐሙስ ሰኔ 2 ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ 5፡30 ተፈጽሟል፡፡

 
መልአከ ገነት ኃይለ ማርያም ከአባታቸው መምህር ፋንታሁን ጥሩነህ እና ከእናታቸው ወ/ሮ ውዴ አካሌ በምዕራብ ጎጃም ዞን በሜጫ ወረዳ በደብር መድኃኒት ማርያም ልዩ ስሟ ደረመኔ በተባለ ቦታ የተወለዱ ሲሆን እድሜያቸው ለትምህርት እንደደረሰ አባታቸው ተተኪ አገልጋዮችን ለማፍራት ባላቸው ልዩ ፍላጎት የተነሣ መንፈሣዊ ትምህርት ቤት በመግባት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በትጋት በመማር እንዲሁ ደግሞ ወንበር ዘርግተው በማስተማር፣ ተተኪ ካህናትንና መምህራንን በማፍራት፣ ለከፍተኛ ማዕረግ የበቁ ጳጳሳትን በማፍራት፣ ከ300 በላይ መነኮሳትን አመንኩሰዋል። ከመነኮሱት ውስጥም ለፓትርያርክነት ማዕረግ የበቁ ያሉበት ሲሆን ፈለገ ገነት ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳምን ለ43 ዓመታት በማስተዳደር፣ በቤተ ክርስቲያኒቷ የተለያዩ የልማት ሥራዎች ላይ በመሣተፍ፣ ችግረኞችን በመርዳት፣ የተጣሉትን በማስታረቅ፣ ያዘኑትን በአባታዊ ምክር የሚያረጋጉ አባት እንደነበሩ አጭር የሕይወት ታሪካቸው ያስረዳል።