‹ትውልድ ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል ተመልከቱ› /ኤር 2፥31/

ዲ/ን ብርሃኑ አድማ
‹አንድ ምድራዊ ንጉሥ ወይም ጠቅላይ ሚኒስቴር ወይም ሌላ ታላቅ ባለሥልጣን ደብዳቤ ቢጽፍልን በደስታ አናነበውምን? በእርግጠኝነት በታላቅ ደስታ የማያነበውና በልዩ ትኩረት የማይመለከተው አይኖርም፡፡ ይሁን እንጂ ከምድራዊ ባለሥልጣን እንዲህ ያለ ደብዳቤ የተጻፈለት ሰው የለም፤/ለሥራ፣ ለሹመት፣…ካልሆነ በቀር/ ከሰማያዊው ንጉሥ ግን ያልተጻፈለት የለም፣ በምድራዊ ዋጋ የማይታመን ለሕይወት መድኃኒት የሆነ ደብዳቤ ተጽፎልን ነበር። ይሁን እንጂ ለአንድ ምድራዊ ንጉሥ ደብዳቤ የምንሰጠውን ያህል ክብርና ትኩረት እንኳን አልሰጠነውም፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ምን ማለት እንደሆነ አልገባንምና፡፡ ወንጌልን ስናነብ እኮ ክርስቶስ ራሱ እያነጋገረን እኛም ከእርሱ ጋር እየተነጋገርንና ወደ እርሱ እየጸለይን ነበር፡፡ አንድ አባት መጽሐፍ ቅዱስን አስመልክተው የተናገሩት ነበር፡፡ በርግጥም መጽሐፍ ቅዱስ ለእያንዳንዳችን የተጻፈና የተነገረ የእግዚአብሔር ቃል ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ ሳሙኤል ‹ባሪያህ ይሰማልና ተናገር›እንደ ኢሳይያስም ‹እኔ አለሁ› የሚል እግዚአብሔርን ሰምቶ ለመታዘዝ የተዘጋጀ ብዙም ያለ አይመስለኝም፡፡ /1ኛ ሳሙ 3፥10፣ ኢሳ 6፥8/

የእግዚአብሔር ቃል /መጽሐፍ ቅዱስ/
በመጽሐፍ ቅዱስ የተመዘገበው የእግዚአብሔር ቃል ፍጹም እውነትና ከእርሱ የተገኘ ቃል ነው፡፡ ይህም ማለት በጸሐፊዎቹ ሥጋዊ ዕውቀት ወይም አመለካከት ተጽእኖ ሥር የወደቀ አይደለም፡፡ የተጻፈው በመንፈስ     ቅዱስ መሪነት ወይም መንፈስ ቅዱስ በአደረባቸው አበው ብቻ ነውና ፡፡ «ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና..ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ» ተብሎ እንደጻፈ። ጸሐፊዎቹ በመንፈስ ቅዱስ የተመረጡ  /መንፈስ ቅዱስ ያደረባቸው/ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ /2ኛ ጴጥ 1፥21/ ቅዱስ ጳውሎስም ‹የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው መጻሕፍት› በማለት ይጠራቸዋል፡፡ /2ኛ ጢሞ 3፥16/ ስለዚህ መቼም ቢሆን ትክክል ናቸው፡፡

 
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹በምድር ላይ እንደተፈተነ ሰባት ጊዜ እንደተጣራ ብር የእግዚአብሔር ቃላት የነጹ ቃላት ናቸው› /መዝ1፥16/ ሲል እንደተናገረው ልንጠራጠረው ወይም ስህተት ሊኖርበት ይችላል ተብሎ የሚገመት ቃል የለም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ፍጹም፣ ጽሩይ ፣ንጹሕ ፣እውነተኛ ቃል ነውና፡፡ እግዚአብሔር ለሙሴ ‹ከወንድሞቻቸው መካከል እንደ አንተ ያለ ነቢይ አስነሣላቸዋለሁ፤ ቃሌንም በአፉ አደርጋለሁ፤ ያዘዝሁትንም ቃል ሁሉ ይነግራቸዋል፤ በስሜም  የሚናገረውን ቃሌን የማይሰማውን ሰው እኔ እበቀልለታለሁ› ሲል የተናገረው ቃል የነቢያቱ ወይም የሐዋርያቱ ሳይሆን የእግዚአብሔር ቃል ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ /ዘዳ18፥18-19/ ስለዚህም በመጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው ሁሉ የእግዚአብሔር ቃል ብቻ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ‹ቃሌን ሰምቶ የማይጠብቀው ቢኖር የምፈርድበት እኔ አይደለሁም!…እኔ ተናገርሁት ቃል እርሱ በመጨረሻው ቀን ይፈርድበታል፡፡› ያለን ቃሉ ንጹሕ የራሱ ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ /ዮሐ 12፥47-48/ የሰው ቃል ቢሆን ሊፈርድብን አይችልምና፡፡
ቃለ እግዚአብሔር ለሕይወታችን
ያለምንም ቅድመ ሁኔታና ያለ ተጨማሪ ዓላማ የእግዚአብሔርን ቃል የምንሰማው ለነፍሳችን ድኅነት ነው፡፡ ይህም ማለት ሰማዕያኑ /ሰሚዎቹ ወይም አንባቢዎች/ የእግዚአብሔርን ቃል የምናነብበት፣ የምንሰማበት ተቀዳሚ ዓላማ ድኅነት ብቻ መሆን አለበት ለማለት ነው፡፡ ‹አስቀድማችሁ ጽድቁንና መንግሥቱን ፈልጉ፤ ሌላው ሁሉ ይጨመርላችኋል› /ማቴ 6፥33/ መባላችንን መዘንጋት የለብንም፡፡ እኛ ለነፍሳችን ድኅነት ስንሰማው ከእግዚአብሔር የምንቀበለው እጅግ ይበዛል፡፡ ‹ይጨመርለችኋል› ያለን አምላካችን ይጨምርልን ዘንድ የታመነ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ጥቂቶቹን ጥቅሞች እንመልከትና እንዴት ማንበብና መማር እንዳለብን እንመልከት፡፡
ሀ/ ለሕይወተ ነፍስ፡- ‹ሲሳያ ለነፍስ ቃለ እግዚአብሔር ውእቱ፤ የነፍስ ምግቧ የእግዚአብሔር ቃል ነው› እንደተባለ ያለ እግዚአብሔር ቃል ለድኅነት የምትበቃ ነፍስ የለችም፡፡ ጌታ በወንጌል ‹እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ ቃሌን የሚጠብቅ ቢኖር ለዘለዓለም ሞትን  አያይም/ ዮሐ8፥51/ ያለው ድኅነት ነፍስን የሚያስገኝ ስለሆነ ነው፡፡ በዚሁ ምዕራፍ ላይ ‹ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል› ያለውም ያለ ቃለ እግዚአብሔር የእግዚአብሔር መሆን ስለማይቻል ነው፡፡ / ዮሐ 8፥47/ ቃሉን የሚሰሙ፤ እንደሰሙም የሚኖሩት ግን በሰላምና በሕይወት ይኖራሉ፡፡ ራሱ ጌታም ‹እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው፤ ሕይወትም ነው፡፡› ብሏልና፡፡ /ዮሐ 6፥63/ ቅዱስ ጳውሎስም ቅዱሳት መጻሕፍት ሰውን ለፍፁምነት የሚያበቁ፣ በጎ የሚያደርጉ፣ በተግሣጽ ልብን የሚያጸኑና በትምህርት እያነጹ በጽድቅ ላለው ምክር እንደሚጠቅሙ አስረግጦ ያስተምራል፡፡ /2ኛ ጢሞ 3፥16-17 ፣ ሮሜ 15፥3-4/ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትም ሕጉን /መጻሕፍትን/ በቀንም በሌሊትም የሚያነብ ሰው ቢኖር ቅጠሎቿ እንደማይረግፉና ፍሬዋን በየጊዜው እንደምትሰጥ በወንዝ ዳር እንደተተከለች ዛፍ ይሆናል፤ ይላል፡፡ /መዝ 1፥2-3/
ለ/ ለሕይወተ ሥጋ፡- ጌታችን በወንጌል ‹ሰው በእንጀራ ብቻ አይኖርም፤ በእግዚአብሔር ቃልም ጭምር ነው እንጂ› እንዳለ ቃለ እግዚአብሔር ለሥጋዊ ሕይወታችንም ይጠቅመናል፤ /ማቴ 4፥4/፡፡ ነቢየ እገዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹ቃልህ (ሕግህ) ለእግሬ መብራት ለመንገዴም ብርሃን ነው› እንዳለ ቅዱሳት መጻሕፍትን የሚያነቡ ሰዎች መንገዳቸው ሁሉ የተቃና ይሆንላቸዋል፡፡ /መዝ118፥105/ ሳምራዊቷ በእርሷ ተሰውሮ አምስት ባሎቿን ከገደለባት መንፈስ ርኩስ ነጻ የወጣችው የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት ነው፡፡ /ዮሐ4፥7-40/  መቶ አለቃው ‹ቃል ብቻ ተናገር ብላቴናዬም ይፈወሳል› በማለቱ እንደ እምነቱ ተደርጎለታል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ዓለሙ ሁሉ የተፈጠረው በእግዚአብሔር ቃል ነውና የእግዚአብሔር ቃል የጎደለብንን ሁሉ ይሞላል፡፡ ቅዱስ ዳዊት «የቃልህ ፍቺ ያበራል ፤ሕጻናትንም ጠቢባን /አስተዋዮች/ ያደርጋል፤ አፌን ከፈትሁ አለከለክሁም፤ ወደ ትእዛዝህ ናፍቄአለሁና» እያለ ናፍቆቱን የሚናገረው ከቃለ እግዚአብሔር የማይገኝ ዕውቀትና ጥበብ ስለሌለ ነው፡፡ /መዝ 118፥129-131/

እግዚአብሔር ይነግሮሙ ለሕዝቡ በመጽሐፍ /መዝ 86፥6/

ቅዱስ ዳዊት ‹እግዚአብሔር ለሕዝቡ በመጽሐፍ ይነግራቸዋል› ይላል፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር እንዲነግረው የፈለገ ሁሉ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ይጠበቅበታል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስም ‹ትውልድ ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል ተመልከቱ› የሚለን ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብና በማድመጥ እንድንጠቀም ነው፡፡ ለመሆኑ አንድ ሰው መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ አስቀድሞ መገንዘብ ያለበት ጉዳይ ምንድ ነው?  የሚለውን መረዳት ያፈልጋል፡፡

ሀ/ መጽሐፍ ቅዱስን በቤተ ክርስቲያን መንፈስ መረዳት

በመጀመሪያ ደረጃ መጽሐፍ ቅዱስን ከቤተ ክርስቲያን እንደተቀበልነው ወይም እነዳገኘነው መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ቤተክርስቲያን ስንልም ክርስቶስ መሠረቷ ጉልላቷ የሆነላት /1ኛ ቆሮ 3፥6፣ ዕብ 6፥1፣ ኤፌ 5፥22/ በምድርም፣ በገነትም፣ በብሔረ ብፁአንና በብሔረ ሕያዋን ያሉት የቅዱሳን ሰዎችና የማኅበረ መላእክት አንድነት ማለታችን ነው፡፡ ቅዱስ የሆነው ትውፊት ወይም ቅብብል እስከ ዘመነ ሊቃውን ካደረሳቸው በኋላ በቤተ ክርስቲያን ቀኖና ተወስነዋል፡፡ ስለዚህ አንድ አማኝ መጽሐፍ ቅዱስን እንደሌላ የፍልስፍና መጽሐፍ በፈለገው መንገድ ሊተነትነው አይችልምም፣ አይገባምም፡፡ ከቤተ ክርስቲን የተቀበለው ከሆነ በቤተ ክርስቲያን /በኅብረቱ በአንደነቱ መንፈስ/ ሆኖ መረዳት ይገባዋል፡፡ ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ «የሚተረጉምልኝ ሳይኖር ይህ እንዴት ይቻለኛል?» /ሐዋ 8፥31/ ያለው ራሱን በኅብረቱ ውስጥ አድርጎ ስለሚያኖርና የእነርሱንም ርዳታ ስለሚሻ ነበር፤ አገኘም፡፡ ሉቃስና ቀልዮጳ ‹በመንገድ ሲናገረን መጻሕፍትንም ሲከፍትልን /ሲተረጉምልን/ ልባችን ይቃጠል አልነበረምን?› የተባባሉት መጻሕፍትን መረዳት የሚቻለው በቤተ ክርስቲያን መንፈስ /ትምህርት፣ ትርጓሜና ሥርዓት መሠረት /ማንበብና ማጥናት ስንችል ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ /ሉቃ 24፥32/ ቅዱስ ጴጥሮስም «በመጽሐፍ ያለውን ትንቢት ሁሉ ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደው….» የሚለው ለዚህ ነው፡፡ /2ኛ ጴጥ 1፥20/ ያለ ትርጓሜ መንፈስ የምናነብ ከሆነ ከቤተ ክርስቲያን የመውጣት ዕድላችን ሰፊ ነውና እንጠበቅ፡፡

ለ/ በመታዘዝ ማንበብ፡-

መጻሕፍቱ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ተጽፈዋል ብሎ የሚያምን ሰው ሲማር የሚሰማው፤ ሲያነብም የሚያዳምጠው በመታዘዝ መንፈስ ነው፤ ቃሉ በሰው ቋንቋ  የተጻፈ የእግዚአብሔር ድምጽ ነውና፡፡ ስለዚህ አንድ አማኝ በሚያነብበት ጊዜ ራሱን አስገብቶ ከመጻሕፍቱ ባለቤት ከእግዚአብሔር በትሕትና መንፈስ በማድመጥ ያነብባል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ….›› ስለሚል መንገዱ ቢለያይም ነገሩ ሁልጊዜም ለእኛ ሁሉ ነው፡፡ /ዕብ1፥1/ ስለዚህ በመታዘዝ ማንበብ ማለት አንደኛ በማድነቅ/በተመስጦ/ ሁለተኘ ለራስ በማድመጥ ማንበብ ነው፡፡ ይህም ቅድስት ድንግል ማርያም ‹‹ይኩነኒ በከመ ትሌበኒ፣ እነደ ቃልህ ይሁንልኝ ›› እንዳለችው ቃሉን በእምነት በመቀበልና በመታዘዝ ማንበብ ነው፡፡

ሐ/ ለእኔ ብሎ ማንበብ፦

እውነት የመጽሐፍ ቅዱስ አንባቢ ለራሱ ብሎ ያነባል፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው በዝሙት የተከሰሰችውን ሴት ታሪክ ቢያነብ ያን ጊዜ እርሷን ወክሎ መናዘዝ፣ራሱን መክሰስ ይገባዋል፡፡ ‹‹በሰላም ሒጂ›› የሚለው ቃል ላይ ሲደርስም ክርስቶስ ለራሱ እንደተናገረው እየሰማ ሥርየተ ኃጢአት ማግኘትን እየተቀበለ ያነባል፡፡ /ንስሐ አያስፈልግም ማለት አይደለም/፡፡ ይህንኑ አለፍ ብሎም ‹‹ዳግመኛም ኃጢአት አትሥሪ›› የሚለውን አድምጦ ዳግም ኃጢአት ላለመሥራት እየታዘዘ ማንበብ አለበት፡፡ በዚህ መንገድ ካልሆነ የሌሎች ሰዎች ታሪክን የሚያነብ ይመስለውና ሳይጠቀም ይቀራል፡፡ ስለዚህ የአዳምን ታሪክ ሲያነብ የወደቀው፤ የእግዚአብሔርንም ድምጽ ለራሱ አድርጎ ይሰማል፡፡ ‹‹አዳም አዳም ወዴት ነህ›› የሚለውን ‹‹ እኔ ወዴት ነኝ›› እያለ ያነበዋል፡፡ እግዚአብሔር ለቃየል ‹‹ወንድምህ አቤል ወዴት ነው?›› ሲል የጠየቀው የእኔ ወንድሞች /ክርስቲያኖች፣ ደቂቀ አዳም…/ ወዴት ናቸው? እያለ ያነባል እንጂ አርቆ አያነብም፡፡ በዚህም የእግዚአብሔርን የምሕረት ድምጽ ይሰማል፡፡ ስለጠፋው በግ፣ ስለጠፋው ልጅ፣ ስለፈሪሳውያን ፣….. ስለሌሎችም ሲያነብ የሚያስበው ራሱን ነው፣ወይም እራሱን ከእነዚያ እንደ አንዱ በመቁጠር ያነባል፤ ያን ጊዜ በትክክል እግዚአብሔር ለእርሱ የሚለውን ይሰማል፡፡

ማጠቃለያ

በሊቃውንት ዘንድ ቅዱሳት መጻሕፍት ለማንበብ ከዚህ በላይ ግንዛቤና ዝግጅት የሚያስፈልገው ቢሆንም እኛ ለመጀመር ያህል እንኳን መጽሐፍ ቅዱሳችንን በዚህ መንገድ እንቅረበው፡፡ በዚያን ጊዜ ‹‹እኔ ስጸልይ ለእግዚአብሔር እየተናገርኩ ነው፡፡ መጻሕፍትን ሳነብ ደግሞ እግዚአብሔር ለእኔ የሚናገረውን እሰማለሁ›› ያሉት ሊቅ ሕይወትን ገንዘብ ማድረግ እንችላለን፡፡የአሁን ዘመን የእግዚአብሔርን ቃል የምንራብበትም ዘመን ነው፡፡ ‹‹ እነሆ በምድር ላይ ራብን የምሰድበት ዘመን ይመጣል? ይላል ጌታ እግዚአብሔር፡፡ እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ከመስማት እንጂ እንጀራን ከመራብና ውኃን ከመጠማት አይደለም፡፡ ከባሕርም እስከ ባሕር ድረስ፤ ከሰሜንም እስከ ምሥራቅ ድረስ ይቅበዘበዛሉ፤ የእግዚአብሔርን ቃል ለመሻት ይሯሯጣሉ፤ አያገኙትምም፡፡ በዚያ ቀን መልካሞች ደናግል ጎበዛዝትም በጥም ይዝላሉ››ተብሎ እንደተጻፈ ነፍሳት በርግጥም ተጠምተዋል፡፡/አሞ 8፥11-14/
ረሀብ የተፈጠረው ግን በመጻሕፍት ወይም በመምህራን አለመኖር አይደለም፡፡ በሰው ወይም በሰማዕያንና በአንባብያን አለመዘጋጀት ነው ማለት ይቻላል፡፡ ምእመናን ስንሰማም ሆነ ስናነብ መንፈሳችንን ከሥጋዊ ዓላማ ‹‹ የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንክ ይህንን ድንጋይ ዳቦ አድርግ›› በማለት ሰይጣን ከሚያቀርበው ፈተና ማለትም መንፈሳዊ ነገርን ለምድራዊ ጥቅም ከማዋል ርቀን በቤተ ክርስቲያን መንፈስ፣ ለእኔ እግዚአብሔር ምን ይለኛል? ቤተ ክርስቲያን ምን ትላለች? በማለት በመታዘዝ መንፈስ ተዘጋጅተን ከመጣን እግዚአብሔር ይናገረናል፡፡ ‹‹ የልብ መዘጋጀት ከሰው ነው የምላስ /የጸሎትና የዝግጅት/ መልስ ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው›› ተብሎ ተጽፎአልና /ምሳ 16፥1/
ስለዚህ ከስሜት፣ ከእልህ፣ ከመብለጥና ከመፎካከር ስሜት ወጥተን እናንብበው፤ ያን ጊዜ በግጥም ‹‹ የእግዚአብሔርን ቃል ተመልከቱ›› የሚለውን ትእዛዝ እንፈጽማለን፤ እግዚአብሔርም ምስጢሩን ይገልጽልናል፤ ለድኅነትም ያበቃናል፡፡
                                                
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም(ክፍል ሁለት)

ዲ/ን ዮሐንስ ልሳነወርቅ

ከክፍል አንድ የቀጠለ

በቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎች ላይ በሚያጠነጥነውና የሚያበራ ዐይን በሚል ርእስ ሰባስቲያን ብሩክ ካዘጋጀው  መጽሐፍ የተገኘው እንዲህ ተተርጉሞ ቀርቦአል። መልካም ንባብ

በዚህ ክፍል ውስጥ የምናየው ፈጣሪና ፍጡር፣/የተሰወረውና የተገለጠው/ሁለቱ ጊዜያትና ነጻ ፈቃድ በሚሉት ርእሶች ስር ቅዱስ ኤፍሬም በግጥም ያቀረበውን ትምህርት ነው።የቅዱስ ኤፍሬም መዝሙራት ከሚያጠነጥኑባቸው ርእሰ ጉዳዮች አንጻር ስያሜ ተሰጥቶአቸዋል። ለምሳሌ በእምነት ዙሪያ የጻፈውን -Faith ፣በቤተ ክርስቲያን ዙሪያ የጻፈውን -Church የሚል ሲሆን ፤በዚህ ጽሑፍም እነዚህ  በእያንዳንዱ መዝሙር ስር ተጠቅሰዋል።

1. ፈጣሪ-ፍጡር (Creator-Creation)

ቅዱስ ኤፍሬም በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለዉን ልዩነት ሁልጊዜ የተረዳ ነው። በእምነት ላይ ከዘመራቸው መዝሙሮች በአንዱ(Faith 69:11) በነዌና አልአዛር (ሉቃ.16፣26) ምሳሌ የተገለጸውን ቃል በማንፀባረቅ ስለ ነገረ ህላዌ(ontology) ያለውን ክፍተት እንደ ሰፊ ልዩነት በመውሰድ ይናገራል። በዚህ ሰፊ ልዩነት ውስጥ ፍጡር ፈጣሪዉን አይደርስበትም።(Faith)ይኽም ማለት የተፈጠረ ማንነት ስለ ፈጣሪ ማንነት ምንም ማለት አይችልም።

ቀድሞ እንዳየነው በፈጣሪና በፍጡር መካከል ያለው ጥርት ያለ  የልዩነት ቦታ የማመልከት ጉዳይ በአራተኛው መቶ ክ/ዘመን ክርክር ነበረበት። ቅ/ኤፍሬም  ሁሉንም የመልአካዊና የቁስ አካላዊ ማንነትን በአንድ ወገን (ፍጡር) ሲያስቀምጥ የፈጣሪ ቃል ከነገረ ህላዌ ልዩነት(ontological chasm) በሩቅ አቅጣጫ በአጽነዖት ያስቀምጠዋል።

ማንኛዉም ፍጡር ይኽንን ሰፊ ልዩነት በማለፍ ፈጣሪ ጋር መድረስ እንደማይችል ከማስተዋል ጋር በተያያዘ (ቅ/ኤፍሬም ከሌሎች ብዙ አባቶች ጋር የሚጋራው ሀሳብ) በሆነ ነገር ዕውቀት ያለው መረዳት ከዕውቀቱ አካል የግድ መብለጥ አለበት የሚለው ግንዛቤ ውጤት ነው።በዚህ መረዳት መሠረት በተመሳሳይ ጊዜ  እግዚአብሔርን ማወቅም መግለጽም ይቻላል የሚል የሰው መረዳት የማይያዘውን (uncontainable) እግዚአብሔርን መያዝ ይችላል እያለ ነው። ስለዚህም የእግዚአብሔርን ማንነት ለመመርመር መሞከር እጅግ አስፈሪ እንደሆነ እንዲህ ይገልጸዋል።

           ማንኛዉም መመርመር(ላልቶ ይነበብ) የሚችል ሰው
           የሚመረምረውን(ነገር) የያዘ (contains) ይሆናል።
           ፍጹም ዕውቀት ያለውን የሚይዝ (contains) ዕውቀት
           ሁሉን ዐዋቂ ከሆነው(ከእግዚአብሔር ) ይበልጣል።
           እርሱን(እግዚአብሔርን) በአጠቃላይ መለካት እንደሚችል አረጋግጧልና።
           ስለዚህም አብንና ወልድን የሚመረምር ሰው ከእነርሱ ይበልጣል!
           አመድና ትቢያ ሲሆን ራሱን ከፍ አድርጎ

አብና ወልድ መመርመር(ጠብቆ ይነበብ) አለባቸው የሚል የራቀ ፣የተወገዘም ይሁን። (Faith 9:16)
የአምላክን መሰወር ስለመመርመርና መጠየቅ (የማይጠየቀውን) የሚሰጠው ምላሽ ማስጠንቀቂያ ቅ/ኤፍሬም   ዝንባሌው ኢ-ምሁራዊ ነው ወደሚለው ሊመራን አይገባም። ከዚህ የራቀ ነው፣ እርሱ እንደሚያየው የሰው መረዳት በተፈጥሮ ውስጥ ብዙ አቅጣጫ(scope) ያለው ሲሆን ድርሻዉም የፈጣሪን እውነታ በከፊል ለመረዳት የሚያስችሉትን ዓይነቶችንና  ምሳሌዎችን ከተፈጥሮ መፈለግ ነው። አስነቃፊ የሚሆነው መረዳቱ የነገረ ህላዌን ልዩነት ማለፍ ሲፈልግ ብቻ ነው።አግባብነት ያለው የመረዳት ጥያቄ የሚያርፍበት ቦታ እግዚአብሔር ራሱን በፍጥረት(በተገለፁ ነገሮች) በገለፀበት ላይ ነው። ስለዚህም በእምነት መዝሙሮች ላይ ቅ/ኤፍሬም ሲገልፅ                                         

                         በቤተ ክርስቲያን የመረዳት ጥያቄ አለ፤
                         የተገለጸውን መመርመር
                         መረዳቱ ያልተፈቀዱ የተሰወሩ ነገሮችን
                         የመመርመር ዝንባሌ አልነበረውም።(Faith 8:9)

ይህም ቅ/ኤፍሬም ደጋግሞ በሚጠቀማቸው የተገለጠና የተሰወረ በሚሉ ቃላት መካከል ያለውን ሚዛናዊነት(tension) ወደሚያሳየው ቀጣይ ርእስ ይወስደናል።

 

2. የተሰወረውና የተገለጠው( The Hidden and The Revealed )

ቅዱስ ኤፍሬም ስውርና ክሱት(ግልጥ) የሚሉ ቃላትን ሲጠቀም ፈጽመው ከተለያዩ ሁለት እይታዎች አንዱን ይገልጻል። አብዛኛውን ጊዜ የሰው እይታ እያልን የምንጠራውን ራሱ እንዲገለጽ ካልፈቀደ በቀር እግዚአብሔር ስውር ነው የሚለውን ይተካል። የእግዚአብሔርን መሰወር ሰው ሊረዳው  የሚችለው እግዚአብሔር በተለያዩ  ሁኔታዎች ራሱን ሲገልጽ ብቻ  ነው።ለፍጡር ህላዌ የእነዚህ እግዚአብሔር ራሱን ለእያንዳንዱ  የመግለጽ ሁነቶች ሁሉ የእግዚአብሔርን መሰወር ወደ ሙሉ መገለጥ አያደርሱትም፤ መገለጡ ሁል ጊዜ በከፊል ነው። ይኽም ማለት ይህ የሰው እይታ በዋናነት እንደየራሱ ነው። እያንዳንዱ ሰው የእግዚአብሔርን መሰወር የሚያቀርበው በተለያዩ የመገለጥ መንገዶች ነው።
የእግዚአብሔር መሰወር ወደ ሙሉነት በቀረበ ሁኔታ ለሰውነት የተገለጠው በሥጋዌ ነው ማለት አስፈላጊ አይደለም፤ያኔም እንኳን የፈጣሪነት መሰወር እንደተጠበቀ ነበር።

                       ለተሰወረው ምሥጋና የማይሰጥ ማነው፡ ከሁሉም ይልቅ የተሰወረ
                       መገለጥን ይከፍት ዘንድ ማን መጣ፡ ከሁሉም ይልቅ የተከፈተ
                       እሱ በሰውነት ላይ ተቀምጦአልና ፤ ህሊናዎች ባይዙትም
                       ሌሎች አካላትም ዳሰሱት (Faith 19:7)
                     
         ወይም ሰፋ ባለ ሁኔታ
                       ጌታ፡ ወደ መገለጥ የመጣውን መሰወርህን 
                       ትኩር ብሎ ማየት ማን ይችላል?
                       አዎ መሰወርህ ወደ መገለጥና ወደ መታወቅ መጥቶአል
                       ምሥጢራዊ ህላዌህ ያለ ገደብ ወደ መገለጥ መጥቶአል
                        የሚፈራ (የሚደነቅ) ማንነትህ ወደ ያዙት እጆች መጥቶአል።
                        ጌታ ይህ ሁሉ በአንተ ሆኖአል ፤ ምክንያቱም ሰው ስለ ሆንክ
                        አንተን ስለላከ ምስጋና ለእሱ(ለአብ)
                        እንዲህ ቢሆንም ፈጽሞ የማይፈራህ ማነው
                        ምክንያቱም ምንም እንኳ
                        ሰው መሆንህ ዳግም ልደትህ የተገለጠ ቢሆንም
                        ከአብ የተወለድከው ልደት የማይደረስበት እንደሆነ ይቀራል።
                        የሚመረምሩትን ሁሉ አስቁሞአል። (Faith 51:2-3)

ከዚህ ሰውአዊና ግላዊ እይታ ጎን ለጎን ሌላ ፈጽሞ የተለየ እይታ አለ፤ ይኽም ቅዱስ ኤፍሬም እውነት እያለ የሚጠራው የፈጣሪ እርግጠኝነት ነው። እዚህ ላይ  መነሻው የሰው እግዚአብሔርን መረዳት አይደለም፤  በራሱ ህልው የሆነ (objectively exists) ግን በተሰወረና   ግላዊ በሆነ መንገድ የሚገለጥ የእግዚአብሔር  እውነተኛ ህላዌ ነው። ከዚህ አቅጣጫ ሲታይ ዓይነቶችና ምሳሌዎች እግዚአብሔር በሚታይ  ፍጥረት  ራስን የመግለፅ ቅጽበቶች አይደሉም ፤ይልቁንም አንድ ቀን የሚገለጥን ነገር የሚያመለክት መሰወር አላቸው፤ በተፈጥሮና በቅዱሳት መጻሕፍት ምሳሌዎች የተሰወረው በክርስቶስ ሥጋዌ ተገልጦአል፤ በ(ቤ/ክ) ምስጢራት የተሰወረ በፍርድ ጊዜ በመንግሥተ ሰማያት ይገለጣል።
ቅዱስ ኤፍሬም በግጥሙ ስለ ተሰወረውና ስለ ተገለጠው ያሉትን እነዚህን ሁለት እይታዎች ድንቅ በሆነ መንገድ ያስተሳስራቸዋል። በሁለቱም ጥጎች ፡ የተሰወረና የተገለጠ ፡እንዲጠበቅ የሚያደርገው ሚዛናዊነት በእግዚአብሔር  ርሑቅነት(transcendence) ና ቅሩብነት(immanence) መካከል ካለው መሳሳብ ሌላ አይደለም።

3. ሁለቱ ጊዜያት (The Two Times)

መደበኛው ጊዜ ቀጥታዊ ነው፤ እያንዳንዱ ነጥብም በጊዜ ውስጥ በፊትንና  በኋላን ያውቃል። በሌላ በኩል ምስጢራዊ ጊዜ በፊትንና በኋላን አያውቅም ዘልዓለማዊ አሁንን ብቻ። ለምሥጢራዊ ጊዜ ጠቃሚ የሆነው  በቀጥታዊ ጊዜ ቅደም ተከተል ላይ ያለው ልዩ ቦታ ሳይሆን ይዘቱ ነው። ይኽም ማለት በታሪካዊ ጊዜ በተለያዩ ወቅቶች የሚገኙ ፣ በነገረ ድሕነታዊ ይዘታቸው አንድነት ያላቸው ድርጊቶች ፡እንደ የክርስቶስ ሰው መሆን/መጠመቅ/መሰቀል/ወደ ሲኦል መውረድ(ነፍሳትን ለማውጣት)ና ትንሣኤ ፡በምስጢራዊ ጊዜ በአንድነት ይሄዳሉ፤ሊተኮርበት የሚቻል አጠቃላይ ነገረ ድሕነታዊ ይዘታቸው  ከእነዚህ ተከታታይ  ነጥቦች በቀጥታዊ ጊዜ በማንኛዉም(በአንዱ) ላይ በማተኮር በሚለው ውጤት። ለምሳሌ ምንም እንኳ በቀጥታዊ ጊዜ የክርስቶስ ጥምቀት ከሞቱ እና ከትንሣኤው በፊት ቢሆንም በሶሪያ ትውፊት እንደራስና ለሁሉም የክርስትና ጥምቀት ምንጭ መሆኑን ወደ መረዳት እንዴት እንደመጡ ይገልጻል።

በቅዱስ ኤፍሬም መዝሙራት የምስጢራዊ ጊዜ እሳቤ ከሌሎች ሁለት ነጥቦች አንጻርም ጠቃሚ ነው።
በመጀመሪያ  ደረጃ ቅ/ኤፍሬም ክርስቶስ ወደ ሙታን ዓለም ሲኦል የመውረድ አስፈላጊነቱን ስለተረዳበት መንገድ የሚያሳይ ስለሆነ። ነገር ግን በመሬት ላይ የክርስቶስ ሥግው ሕይወት ለታሪካዊ ጊዜና ቦታ መግቢያ ነው፡ የመጀመሪያው ክ/ዘመን ፍልስጥኤም፡ ወደ ሲኦል መውረድ ከምሥጢራዊ ጊዜ እና ቦታ ጋር ብቻ የተያያዘ ነው።ይኽ የክርስቶስ ወደ ሁለቱም ኃላፊና መጪ ጊዜ መግባት ነው፤በጂኦግራፊያዊ ቦታ የተከለለም አይደለም። ስዚህም ወደ ሲኦል መውረዱ በነገረ ድሕነት ሂደት ላይ ከጌታ የምድር ቆይታው ጋር እኩል ጠቀሜታ አለው፤ በዚያም እንዲህ ባይሆን ኖሮ ሊነሳ የሚችለው ውሱንነትን (የክርስቶስ ሥራ በታሪካዊ ጊዜና ጂኦግራፊያዊ ቦታ እንደተገደበ መረዳት) ያብራራል።

የክርስቶስ ወደ ሲኦል የመውረድ ዶግማዊ ዓላማ ሥጋዌ(የክርስቶስ ሰው መሆን) ሁሉንም ታሪካዊ ጊዜንና ጂኦግራፊያዊ ቦታን እነደለወጠ(effects) በግልጽ ለማሳየት ነው። ነገር ግን ይኽን ለማግኘት በምስጢራዊ ጊዜና በምስጢራዊ ቦታ  አንጻር ሊነገር ይገባዋል፤ በዚህም መሠረት መውረዱም ታሪካዊ በሚመስልና ግጥማዊ የጥንት ታሪክ በሆነ መንገድ ብቻ ሊገለጽ ይችላል፡ ቅዱስ ኤፍሬም በንጽቢን መዝሙሮቹ ሁለተኛ አጋማሽ ላይ በታላቅ ድራማዊ ውበት እንደገለጸው።

የቅዱስ ኤፍረምን አስተሳሰብ ለመረዳት የምስጢራዊ ጊዜ እሳቤ ጠቃሚ የሆነው ሁለተኛው ነጥብ የሚያጠነጥው በታሪካዊጊዜ የክርቲያኖች የጥምቀትና ቁርባን ምስጢራት ሱታፌና በፍርድ ቀን የእነሱ ሙሉ በሙሉ እውን መሆን ነው። ምክንያቱም የመንግሥተ ሰማያት ሕይወት ለምሥጢራዊ ጊዜ የተገባ ነው። በተለያየ መጠን በምድር ላይ በታሪካዊ ጊዜ ውስጥ ባለ በእያንዳንዱ ሊተገበር ይችላል።

4. ነጻ ፈቃድ (Free will)
በቅዱስ ኤፍሬም አስተሳሰብ ውስጥ ነጻ ፈቃድ እጅግ ጠቃሚ የሆነ ሚና ይጫወታል። በዚህ ርእስ ላይ ያተኮረ መዝሙር  ጌታ፡ትንሿን አካል ነፃ ፈቃድን በመስጠት ከሌሎች ሁሉም ከተፈጠሩ ነገሮች አገዘፍክ። (Heresies 11)የሚል መልስ አለው።

ቀድሞ እንዳየነው አዳም በራሱ ነጻ ፈቃድ ትእዛዛቱን ይጠብቅ ዘንድ መርጦ ቢሆን ኖሮ እግዚአብሔር ከፍ ባለ ሁኔታ  አዳምን ያከብረው ዘንድ በመካከለኛ ሁኔታ ፈጥሮታል ።

         
                  ፍትሓዊ የሆነው(እግዚአብሔር)፡ዘውዱን ለአዳም በከንቱ እንዲሰጠው አልወደደም
                  ምንም እንኳ በገነት ያለ ድካም ደስ ይሰኝ ዘንድ ቢፈቅድለትም
                  አዳም ቢፈልግ ሽልማቱን ማግኘት እንደሚችል እግዚአብሔር አውቆአል።
                  ፍትሓዊው ፡አዳምን ያከብረው ዘንድ ስለወደደ፤ ምንም እንኳ በልዑላዊ ሕላዌዎች ደረጃ
                  በጸጋ ታላቅ ቢሆንም ለሰው አግባብነት ላለው ለነጻ ፈቃድ አጠቃቀም
                  ክብሩ ያነሰ ነገር   አይደለም።(Paradise 12:18)   
አዳም ከገነት የተባረረው በተሳሳተ የነጻ ፈቃዱ አጠቃቀም ነው፤እንዲሁም ቅዱሳን የከበሩት በዚህ ስጦታ ትክክለኛ አጠቃቀም ነው።
                  ትእዛዛቱን ያስቀመጠ እርሱ(እግዚአብሔር) ምስጉን ነው
                  በእነዚያ(ትእዛዛቱ) ምክንያት ነጻ ፈቃድ ይከበር ዘንድ
                  ጽድቅን፣ስለነጻ ፈቃድ የሚጣሩ ምስክሮችን ያበዛ
                  እርሱ(እግዚአብሔር) ምስጉን ነው።(Heresies 11:4,end)
እርሱ ራሱን ባለ ማስከፋት ደስ እናሰኘው ዘንድ እኛን ማስገደድ በቻለ ነበር ፤ግና በምትኩ   በራሳችን ነጻ ፈቃድ በደስታወደ እርሱ እንቀርብ ዘንድ በሁሉም መንገድ ተቸገረ።(Faith 31:5)
የኖህ ትውልድ ስለ ነጻ ፈቃድ ትክክለኛ እና የተሳሳተ አጠቃቀም ለቅዱስ ኤፍሬም ቀዳሚ ምሳሌ ሆኖአል።
                   የኖህን ምሳሌ ውሰድ፤
                   በዘመኑ የነበሩትን ሁሉንንም መገሰፅ ይችላል፤
                   ፈልገው ቢሆን ኖሮ እነሱም እኩል ድል መንሳት ይችሉ ነበር፤
                   በእነሱ የነበረው የእኛ ነፃ ፈቃድ በኖህ ከነበረው ጋር አንድ ነውና።(Chrch 3:9)

የነፃ ፈቃድ ተግባር በሞራል ክልል የተገደበም አይደለም።ለተለያዩ የእግዚአብሔር ራስን የመግለፅ መንገዶች ምላሽ መስጠት ሙሉ በሙሉ እንደኛ ፍላጎት ነው።የእኛ የራሳችን ነፃ ፈቃድ የአንተ ደስታ መክፈቻ ነው።(Church 13:5)
 
ምንም እንኳ በራሳቸው ነጻ ፈቃድ ራሳቸውን ለሃጢአት ባሪያ ባደረጉት ውስጥ በግልጽ ባይታይም ነጻ ፈቃድ በእያንዳንዱ በእኩል መጠን ይገኛል።

ቅዱስ ኤፍሬም ይኽንን በሕክምናዊ ንጽጽር ይገልፀዋል።
                   የእኛ ነጻ ፈቃድ ማንነት በእያንዳንዳችን ውስጥ አንድ ዓይነት ነው።
                   የነጻ ፈቃድ ኃይል በአንዱ ውስጥ ደካማ ከሆነ በሁሉም ውስጥ ደካማ ነው
                   የነጻ ፈቃድ ኃይል በአንዱ ውስጥ ብርቱ ከሆነ በሁሉም ውስጥ አንድ  ነው።
                   የጣፋጭነት ተፈጥሮ ምንነት በጥሩ ጤንነት ላለ ለአንድ ሰው
                   ጣፋጭ ይመስለዋል።
                   ለታመመ ለሌላው ሰው ግን መራራ ይመስለዋል፤
                   ለነጻ ፈቃድም እንዲሁ
                   ከኃጢአተኞች ጋር ታማሚ ነው፤ ከጻድቃን ጋር ግን ጤነኛ ነው።
                   ማንኛዉም ሰው የጣፋጭነትን ጣዕም መቅመስ ቢፈልግ
                   በታማሚ ሰዎች አፍ ውስጥ አይቀምስም ወይም ለመቅመስ ሙከራ አያደርግም፤
                   ጣዕሞችን ለመለየት መቀመጫ የሚሆነው ጤነኛ አፍ ነው።
                   እንደገና ማንም የነጻ ፈቃድን ኃይል መለካት ቢፈልግ
                   በመጥፎ ተግባሮቻቸው በተዳደፉት ውስጥ መሞከር የለበትም
                   ንጹህ የሆነ ጤነኛ ሰው እሱን ለመቅመስ ማደሪያዉን ሊሰጥ ይገባዋል።
                   ሕመምተኛ ሰው የጣፋጭነት ጣዕም መራራ ነው ሊልህ የሚገባ ከሆነ
                   ሕመሙ ምን ያህል እንደጸና ተመልከት፤
                   ስለዚህም የደስታ ምንጭ የሆነውን ጣፋጭነትን አሳስቶአል፤
                  እንደገና ማንም የተዳደፈ ሰው የነጻ ፈቃድ ኃይል ደካማ ነው ሊልህ የሚገባ ከሆነ
                  የሰው ልጅ ገንዘብ ያደረገውን ኃብት ነጻ ፈቃድን ደሀ በማድረግ 
                  ተስፋዉን እንዴት እንደቆረጠው ተመልከት ። (Church 2:18-23)

 
ይቆየን!                                    

 

አሥሩ ትእዛዛት

  እመቤት ፈለገ
እግዚአብሔር አምላካችን እጅግ በጣም የሚወደን እና የሚያስብልን አባታችን ነው፡፡ እርሱ ደግሞ ሁሉንም የሚያውቅ ስለሆነ ለእኛ ምን እንደሚጠቅመን፤ምን እንደሚያስፈልገን፤ምን እንደሚጎዳን ሰለሚያውቅ አሥሩን ትእዛዛት ሰጠን፡፡

 እነዚህም፡-
          1.ከኔ በቀር ሌሎችን አማልክት አታምልክ
          2.የእግዚአብሔር አምላክህን ስም በከንቱ አትጥራ
          3.የሰንበትን ቀን አክብር
          4.አባትና እናትህን አክብር
          5.አትግደል
          6.አታመንዝር
          7.አትስረቅ
          8.በሐሰት አትመስክር
          9.የባልንጀራህን ቤት አትመኝ
         10.ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ የሚሉት ናቸው፡፡

 

እነዚህ ትዕዛዞች ሁሉም ሰው እንዲያደርጋቸው ርህሩህ አባታችን እግዚአብሔር አዞናል፡፡ እነዚህ ትዕዛዞችን ከፈጸምን እግዚአብሔር ይወደናል፤በረከትም ይሰጠናል፡፡
ልጆች እግዚአብሄርን እንወደዋለን አይደል? እግዚአብሄርን መውደዳችን የሚታወቀው ደግሞ አድርጉ ያለንን ስናደርግ፤ አታድርጉ ያለንን ደግሞ የማናደርግ ከሆነ ነው፡፡ይህን ካደረግን እግዚአብሔር በእኛ ደስ ይለዋል፤ ይባርከናል፤የሚያስፈልገንን ሁሉ ይሰጠናል፡፡ እነዚህ ትዕዛዛት ካልፈጸምን  ግን እግዚአብሔር ያዝንብናል፤ ከደጉ አምላካችንም እንለያያለን፡፡ ከአምላካችን ከተለየን ደግሞ ጥሩ ነገር አይኖረንም፡፡ ስለዚህ ልጆች እነዚህን ትእዛዛት ልንፈጽማቸው ስለሚገባ እያንዳዳቸውን በዝርዝር በሌላ ቀን እናያቸዋለን፡፡

በሌላ ቀን አሥሩን ትዛዛት በዝርዝር እስከምናያቸው ድረስ እናንተ በቃላችሁ ይዛችሁ ለእማማ፤ ለአባባ እና ለጓደኞቻችሁ ንገሯቸው፡፡
                                                                                  

በጎ ያልሆኑ ተጽእኖዎች በክርስትናችን

በማሞ አየነው
 
በተደጋጋሚ ከሚያጋጥሙኝ ክስተቶች አንዱ ይህ ነው፡፡ ከዚህ በፊት ከምተዋወቀው አንድ ልጅ ጋር ቁጭ ብለን እየተጨዋወትን ነው፡፡ ልጁን የማውቀው ሰ/ት/ቤት ውስጥ ታታሪ አገልጋይ በነበረበት ጊዜ ነበር፡፡ አሁን ከመንፈሳዊ አገልግሎቱ ራሱን አግልሏል፡፡ እንደድሮው ስለመንፈሳዊ ሕይወቱ የሚያወያየው ለአገልግሎት የሚጋብዘው፣ ሲደክም የሚያበረታው፣ ሲሰለች መንፈሱን የሚያድስለት፣ ጓደኛ የለውም፡፡
 
ከሚሳተፍባት አጥቢያ  ሰ/ት/ቤት መራቁን እንደ ትልቅ ምክንያት እያነሳ በተደጋጋሚ ነገረኝ ምክንያቱ አልተዋጠልኝም፤የራቀው ከአንድ አካባቢ እንጂ ቤተ ክርስቲያንና ሰ/ት/ቤት አሁን ካለበት አካባቢ እንዳለ አውቃለው፤ ከተለያየን በኋላ ስለጉዳዩ በደንብ አሰብኩበት፡፡ ይህ ችግር የብዙ ሰዎች ችግር እንደሆነ በተደጋጋሚ እናያለን፤ ራስን ከሚያገኛቸው ሁኔታዎች ጋር አስማምቶ ክርስቲያናዊ ሕይወትን በጊዜና በቦታ የመገደብ፣ ራስን ከሚያገኛቸው ሁኔታዎች ጋር አስማምቶ ክርስቲያናዊ ሕይወትንና አገልግሎትን የማስኬድ ችግር የብዙዎች ችግር ነው፡፡ ይህም አንድ ነገር እንዳለ ያመላክተናል።ይህም ክርስትናችን የቆመበት መሠረት በነፋስና በጎርፍ ተጠራርጎ ለመውደቅ ቅርብ መሆኑን ነው። ለዚህ ነው ጥቃቅን ምክንያቶች ግዙፍ የሚመስለንን ግን ያልሆነውን ክርስትናችንን አደጋ ላይ የሚጥሉት የሁሉም ነገር መነሻ መሠረቱ ነውና፡፡ ክርስትናም የራሱ መሠረት አለው፡፡ እስኪ በተረጋጋ መንፈስ ክርስትናችን የተገነባበትን እንመርምር፡፡ በክርስቲያናዊ ሕይወታችን ውስጥ ልብ ልንላቸው የሚገቡ ነገር ግን እንደዋዛ የምናያቸውን ነጥቦችን እንደሚከተለው እንመለከታለን፡-

ሀ.  በሌሎች ጫንቃ ያረፈ ክርስትና ነው ያለዎት?

ሁሌም ልብ ልንለው ከሚገቡ ነጥቦች አንዱ ክርስትናችን ማንን ተስፋ እንዳደረገና በማንስ ላይ ተስፋውን እንደጣለ መረዳት ነው፡፡ የብዙዎቻችንን መንፈሳዊ አይን ሸፍኖ ዋናውን ነጥብ እንዳናይና የሚያደርጉ ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ በአካባቢያዊና በአጥቢያ ላይ የተመሠረተ የአገልግሎተ ፍቅር፣ በማኅበራት ትክሻ ላይ የተንጠላጠለ ሱታፌ፣ ከጓደኝነትና ከመላመድ የመነጨ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ ዋናውን የክርስትና ዓላማ  እንዳንረዳ ከሚያደርጉን መሰናክሎች ጥቂቶቹ ናቸው፡፡ እነዚህ ነጥቦች ለክርስትናችን እንደ ግብዓት የሚታዩ እንጂ የአገልግሎታችንና የክርስቲያናዊ ሕይወታችን መሠረቶች ሊሆኑ አይገባም፡፡ ልብ ብሎ ራስን መመርመር የሚገባም ለዚሁ ነው፡፡
ግድግዳና ጣሪያ ብቻ ለቤት መሠረት ሊሆኑ እንደማይችሉ ሁሉ በሰው በማኅበር መሠባሰብ ላይ የተመሠረተ ክርስትናም ዘላቂነት የለውም፡፡ ብዙዎች ከሚያገለግሉበት አጥቢያ ሲርቁ፤ በክርስትና ከሚያውቋቸው ጓደኞቻቸው ሲለዩ ከቤተክርስቲን ለመራቅ ያስባሉ፡፡ ክርስትና እዚያና እዚህ ብቻ ያለ ይመስላቸዋል፤ ክርስቲያናዊ ሕይወት የእነ እገሌ ተሰጥዖ  ብቻ አድርገው ይወስዳሉ፤ ቀስ በቀስም ተስፋ የመቁረጥና የብቸኝነት ስሜት በልባችን ሰርጾ ይገባል፡፡ ከለመድነው አሰራርና አካሄድ የተለወጠ ነገር ባየን ቁጥር እየበረገግንና እየራቅን እንመጣለን። ስለዚህ በድሮው ክርስትናችን መቀጠል ይከብደናል፡፡ ዴማስ ከለመደው ከተማና ሁኔታ የተለየ ሁኔታ ስለገጠመው ነበር በተሰሎንቄ ተስቦ የቀረው /2ኛ ጢሞ/ ብዙዎች የተሰናከሉት የሰው ልጆችን ኑሮ በማየታቸውና ከለመዱት የአኗኗር ዘየ የተለየ ነገር ስለገጠማቸውና ስለተሸነፉለትም ነበር። /ኩፋ 6፥9 ዘፍ 6፥1/  የያዕቆብ ልጅ ዲናም ከክብር ያነሰችው የለመደችውን የአህዛብ አኗኗር መቋቋም አቅቷት ነበር፡፡ ዘፍ 34፥1 የብዙዎቻችንም ክርስትና እንዲሁ ለፈተና የተጋለጠ ነው፡፡ አካባቢን ከመለወጥ ይልቅ እኛው ተለውጠን ክርስትናችን ደብዛው የጠፋብን ብዙዎች ነን፡፡ የማኅበረ እስጢፋኖስ መበታተን ክርስትናን የበለጠ እንዲስፋፋ አደረገ እንጂ ክርስትናቸውን አላጠፋባቸውም፡፡ በጊዜና በቦታ ሳይወሰኑ አሐቲ የሆነችውን ቤተክርስቲያን ማገልገል የቤተክርስቲያንን የአገልግሎት ሁኔታ የመረዳትና የክርስትናንም ውል የመያዝ ምልክት ነው፡፡ ከመንፈሳዊ ሩጫችን ጎን ለጎን ልናስተውለውና ልንረዳው የሚገባን ቢኖር እያገለገልኩና እየሮጥኩ ያለሁት ከራሴ በሚመነጭ መንፈሳዊ ግፊት ነው ወይስ በስብሰባ ድምቀት ልምድ ስለሆነብኝ? ወይንም ከሰ/ት/ቤት ልጆች መራቅ ስላልፈለግሁ ነው የሚለውን መሠረታዊ ጥያቄ ነው፡፡

ለ. ከአፍአዊ አገልግሎትና ምስጢራት ከመሳተፍ የቱን ያስቀድማሉ?

በሚገባ አስተውለንና አጢነን ከሆነ ብዙ ጊዜ መንፈሳዊ ሩጫ ውስጥ የገቡ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ምስጢራት መሳተፍ ያቆማሉ፡፡ ከኪዳን፣ ከቅዳሴ፣ ከሥጋ ወደሙ የራቁ ነገር ግን ሩጫ የሚያበዙ፣ መረጋጋት የማይታይባቸው፣ በአፍአ (በውጭ) ያሉ ብዙ ጓደኞች አሉን፡፡ መንፈሳዊ በሆነ ኃይልና ዕውቀት ከማገልገል ይልቅ በስጋ ድካም ማገልገል የበለጠ ውጤት የሚስገኝ ስለሚመስላቸው ቅዳሴና ኪዳን ለነሱ ቦታ የላቸውም፤ እንደዚህ ዓይነት አገልጋዮች ይህን ከመሰለው እንቅስቃሴ ሲለዩ የክርስትና መስመር የተበጠሰ ይመስላቸዋል፡፡ የዚህ ሁሉ እንቅስቃሴ ዓላማ ሰውን ምስጢራት ወደ ማሳተፍ ማምጣት መሆኑን ይዘነጉታል፡፡
የማርታና የማርያምም ታሪክ የሚያስተላልፍልን መልእክት ይህንን ነው፡፡ ቃለ እግዚአብሔርን መስማት የሚቻለው ከቅዳሴው ምስጢር መሳተፍ ስንችል ነው፡፡ በቅዳሴ ቃለ እግዚአብሔርን ሰምተን ብቻ አንበተንም፤ ለሥጋ ወደሙ ያዘጋጀናል፡፡ ዋናው የክርስትና ግብም ይህን ምስጢር መሳተፍ ነው።   ጌታችንም ሐዋርያትን ካስተማረና አእምሮአቸውን ካዘጋጀ በኋላ በመጨረሳ ሰዓት የተናገራቸው  ታላቅ ነገር ቢኖር ምስጢራትን እንዲፈጽሙ ማድረግ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው በምሴተ ሐሙስ ሥጋውና ደሙን ያቀበላቸው፡፡ማቴ 26፥26 መንፈሳዊ አገልግሎት ላይ ያለን ሰዎችም ልናስተውለው የሚገባን ታላቅ ምስጢርም ይህ ነው፡፡ ዕውቀትን ከማጎልበት፣ ለሌሎች መዳን ደፋ ቀና ከማለት በተጨማሪ ምስጢራትን መሳተፍና መፈፀም ይገባናል፡፡ በምስጢራት መሳተፍ ያልለመደ አገልጋይ ክርስትና ሰ/ት/ቤት፣ ማኅበራት ጋር፣ ከጓደኞቹ ዘንድ ብቻ ያለ ስለሚመስለው ከነዚህ ሲርቅ ክርስትናው ከገደል አፋፍ ላይ ይቆማል፡፡ ከምንም ነገር በላይ በምስጢራት መሳተፍ መልመድ ከቤተክርስቲያን እንዳንርቅ የሚያስተሳስረን ሕቡር ገመድ ነው፡፡ ይህን የለመደ ሰው የትም ሄደ የት ከምስጢሩ አይርቅም፡፡ ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ማስተካከል የሚገባንም ከዚህ መሠረታዊ ነጥብ ጋር ነው፡፡

ሐ. እውን ሕይወትዎን እየመሩ ያሉት ለሰው ወይስ ለእግዚአብሔር?

ህገ እግዚአብሔርን እየፈጸ ምን ያለነው በእውነተኛ የእግዚአብሔር ፍቅር ተመክረን ነው ወይስ ከመንጋው ላለመለየትና ከነቀፌታ ለመራቅ ብለን ነው? ቤተ እግዚአብሔር የምንሄደው፣ የምናስቀድሰው፣ የምናገለግለው፣ … ከሰው ምላሽን ጠብቀን ከሆነ ጽድቃችን ከፈሪሳዊያን በምን ይለያል? ፈሪሳውያንና ጸሐፍት ህጉን የሚፈጽሙት ለጽድቅ ብለው ሳይሆን የሙሴን ህግ ይፈጽማሉ ለመባል ብቻ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን ‹‹ ጽድቃችው ከፈሪሳውያን ጽድቅ ካልበለጠ ….›› ብሎ ያስተማረ፡፡ እያንዳንዱ የሕይወታችን ጥቃቅን ነገር መመርመር ያለብንም ያደርጋሉ ይፈጽማሉ ለመባል ሳይሆን የጌታ ፍቅር ገብቶንና ደስ እያለን በፍጹም ተመስጦ መሆን ይገባል፡፡ ፍፁም በሆነ ፈቃድ ያለተርእዮ ህግን መፈጸም ግን ጽድቃችንን ከሰው ተጽእኖ የጸዳ ያደርገዋል፡፡ ጌታም በወንጌሉ ‹‹ ቀኝህ የሚያደርገውን ግራህ አይመልከት›› ያለው ለታይታና ለሆይ ሆይታ ተብሎ ጽድቅን መፈጸም እንደማይገባን ሲያስረዳን ነው፡፡ በዚህ መነሻነት ጽድቅን አለመፈጸም ከጓደኛ ሲለዩ’ ከሚያውቁት ማኅበረሰብ ሲወጡ ክርስትናችንን ፈተና ላይ ይጥላቸዋል፡፡ ህግ የተሰጠ ከእግዚአብሔር ስለሆነ መፈጸም ያለበት ስለእግዚአብሔርና ለእግዚአብሔር ተብሎ ብቻ ነው፡፡ መጽሐፍም ‹‹ የእግዚአብሔርን ለእግዚአብሔር ›› ይላል ለሰው’ ለጓደኛ’ለማህበረሰብ  ብሎ ህግን መፈጸም የእግዚአብሔርን ለሌላ እንደመስጠት ይቆጠራል። ነገሮችን ለእግዚአብሔር ብሎ መፈጸም ክርስትናችን በጊዜ፣ በቦታና በሁኔታ እንዳይወሰን ያደርጋል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር የሌለበት  ቦታ፣ ጊዜና ሁኔታ የለምና ነው፡፡ ስለዚህም የትም ሆን የት ከእግዚአብሔር እቅፍ መውጣት አንፈልግም፡፡ ከእግዚአብሔር መራቅ ለሰከንዶች እንኳን ሳናቋርጥ ከምንወስደው አየር እንደመለየት ነው፤ አየር ለመውሰድ ጊዜና ቦታን እንደማንመርጥ ሁሉ ከእግዚአብሔር ከአገልግሎት ላለመራቅም ጊዜና ቦታ መምረጥ አይገባም፡፡
ከላይ የተጠቀሱትን ነጥቦች በማስተዋል ክርስትናችንን በጎ ካልሆነ ተጽእኖ ማጽዳት አስፈላጊ ከመሆኑም በላይ መንፈሳዊ ሕይወታችን በጊዜና በቦታ እንዳይወሰን ለማድረግ ጠቃሚ ነው፡፡ እነዚህን ሀሳቦች እናስተውል ዘንድ አስተውለንም እንተገብራቸው ዘንድ መንፈስ ቅዱስ ልቦናችንን ያነቃቃል!!  አሜን።
                                                            
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

qanaze.jpg

ለባለ ትዳሮች የተዘጋጀ መርሐ ግብር

qanaze.jpg
Silestu Dekik.jpg

ሠለስቱ ደቂቅ

በአዜብ ገብሩ
እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች?ደህና ናችሁ ልጆች? ዛሬ ስለ ሦስቱ ህጻናት ታሪክ እንነግራችኋለሁን በደንብ ተከታተሉን እሺ፡፡
 

በአንድ ወቅት በባቢሎን ከተማ የሚኖር ናቡከደነፆር የሚባል ንጉሥ ነበር፡፡ይህም ንጉሥ ከወርቅ የተሰራ ትልቅ ጣኦት አሠርቶ አቆመ፡፡ ሕዝቡንም ሁሉ ሰበሰበና ለጣኦቱ እንዲሰግዱ አዘዘ፡፡ ለጣኦት ያልሰገደ ግን በእሳት ውስጥ ይጣላል ብሎ አዋጅ አስነገረ፡፡

Silestu Dekik.jpg
 
ከሕዝቡም መካከል ሚሳቅ፤ሲድራቅ እና አብደናጎም የተባሉት ህፃናት ግን ለጣኦቱ አንሰግድም አሉ፡፡ምክንያቱም እግዚአብሔርን ስለሚወዱ ለእርሱ ስለሚገዙ ነው፡፡ንጉሡ እነዚህን ህጻናት ለጣኦቱ አንሰግድም በማለታቸው በጣም ተቆጣ፡፡ካልሰገዱም ወደ እሳት እንደሚጣሉ ነገራቸው፡፡ህጻናቱም የሚያመልኩት አምላክ በሰማይ እንዳለና እርሱም ከእሳቱ እንደሚያድናቸው ነገሩት፡፡እንዲህም ሲሉ ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ ‹‹አንተ ከእኛ ጋር ነህና ክፉውን አንፈራም››። ንጉሡም በመለሱለት መልስ ይበልጥ ተቆጣ፡፡ እሳቱንም ይነድ ከነበርው ሰባት እጥፍ እንዲያነዱትና ወደ እሳቱ ውስጥ እንዲጥሏቸው አዘዘ፡፡
ሲድራቅ ሚሳቅና አብደናጎም ግን እሳቱ አላቃጠላቸውም ነበር፡፡ በእሳት ውስጥ ሆነው እግዚአሔርን በመዝሙር እያመሰግኑ ነበር፡፡ከእነርሱም ጋር ሌላ አራተኛ ሰው ይታይ ነበር፡፡ እርሱም ከእሳቱ ሊያድናቸው  ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከው መልአክ  ቅዱስ ገብርኤል ነበር፡፡ በእሳቱ ውስጥ ሆነው መዝሙር ሲዘምሩ ንጉሡ በጣም ተገረመ ከእሳቱ እንዲያወጧቸው አዘዘ። ከፀጉራቸው አንዲቷ እንኳን ሳትቃጠል በሰላም ከእሳቱ ወጡ፡፡ንጉሡም ባየው ተዓምር ተደንቆ የእነርሱን አምላክ አመለከ በፊታቸውም ለእግዚአብሔር ሰገደ።
አያችሁ ልጆች እነዚህ ሦስቱ ህጻናት  ጎበዞች ናቸው፤ አምላካቸው እንደሚያድናቸው በሁሉም ቦታ ቢሄዱ ከእነርሱ ጋር እንደሆነ ስለሚያምኑ እሳቱን አልፈሩም፡፡እግዚአባሔርም ስለእምነታቸው እሳቱን አቀዘቀዘው፡፡በሰላም ከእሳቱም አወጣቸው፡፡

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም(ክፍል አንድ)

ዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ

በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የረጅም ዘመን ሐዋርያዊ ጉዞ ላይ በጎ ተፅዕኖ ካላቸው የአራተኛው መ/ክ/ዘመን አባቶች መካከል አንዱ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም ነው፡፡ይህ አባት ምንም እንኳን በቋንቋ ውሱንነትና በቦታ ርቀት በርካቶች ሥራዎቹና ጽሑፎቹ የታወቁለት ባይሆንም ሕይወቱን በብሕትውና የመራ የትርጓሜ መጻሕፍትን ፣የቅኔ፣ የግጥምና የወግ ጽሑፍ በማዘጋጀት የኖረ ባለ በጎ ገድል አባት ነው፡፡

የቅዱስ ኤፍሬምን ሥራዎች በማሰባሰብ በመጽሐፍ መልክ ካወጡ ሰዎች አንዱ የሆነው (ዶ/ር ሰባስትያን ብሮክ) ’the Luminous Eye’’ በሚል ርዕስ ካዘጋጀው መጻሕፍ  ውስጥ ጎላ ጎላ ያሉትን ትምህርቶች እየተረጎምን ልናቀርብ ወደድን፡፡ ይህም ክፍል አንድ መግቢያ ሆኖ የቅዱስ ኤፍሬምን ሕይወትና ሥራዎች በአጭሩ የሚቀርብበት ነው፡፡
የቅዱስ ኤፍሬም ሕይወቱ
የቅዱስ ኤፍሬም ሀገረ ውላዱ ከዋክብትን ከሚያመልኩ ሰዎች መካከል ነው፡፡ አባቱም ክርስትናን የሚጠላ ካህነ ጣዖት ነበር፡፡ አንዳንድ ምንጮች ከቅዱስ ኤፍሬም ሕይወት በመነሳት ወላጆቹ ክርስቲያኖች እንደነበሩ ዘግበዋል፡፡ የሐምሌ አስራ አምስት ስንክሳር ግን የአባቱን ካህነ ጣዖትነት ያረጋግጣል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም የተወለደው  በ306 ዓ.ም ገደማ “በሜሶፖታሚያ” ውስጥ በምትገኝ “ንጽቢን” እንደሆነ ይታመናል።(ንጽቢን   በደቡባዊ ቱርክ እና በምዕራባዊ ሶርያ መካከል የምትገኝ ቦታ ናት፡፡) ይህቺም ቦታ ከ318ቱ ሊቃውንት አንዱ የነበረው የቅዱስ ያዕቆብ ሀገረ ሰብከቱ የነበረች ናት፡፡
ይህንን ታላቅ አባታችንን የእግዚአብሔር መንፈስ አመላክቶት ወደ ቅዱስ ያዕቆብ ሄዶ ትምህርተ ክርስትናን ተምሮ የተጠመቀ ሲሆን ከወላጆቹ ጋር የኖረው እስከ አሥር ዓመቱ ብቻ ነው፡፡ በትምህርተ ክርስትና አምኖ ከተጠመቀ በኋላ ግን በቅዱስ ያዕቆብ ዘንድ በብሕትውና ተወስኖ በመማርና በማስተማር በንጽቢን ለሚገኘው መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ሓላፊ እስክመሆን ደርሶ ነበር፡፡
በ393 ዓ.ም የንጽቢን ከተማ  በወራሪዎች እጅ ስትወድቅ ቅዱስ ኤፍሬም ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር በመሆን የሮም ግዛት ወደነበረችው ኤዴሳ (ታናሽ እስያ፣ዑር) ተሰደደ፡፡ ይህቸ ቦታ ቅዱስ ኤፍሬም ከመናፍቃን ጋር የተጋደለባት፣ በቤተክርስቲያን ትምህርት ላይ ያላቸውን አብዛኞቹን የክህደት ትምህርቶች የሞገተባትና  መጻሕፍቱን ያዘጋጀባት ናት፡፡አብዛኛዎቹን ትምህርቶቹንና መጻሕፍቱን ያዘጋጀው በዚች በኤዴሳ በሚገኘው ትምህርት ቤት ነው፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም ከመምህሩ ከቅዱስ ያዕቆብ ጋር በመሆን በአርዮስ ምክንያት በተካሄደው  የኒቅያው ጉባኤ    ( 325 ዓ.ም ) ላይ ተገኝቷል፡፡ በዚህም የአርዮስን ክህደትና ምክንያተ ውግዘት ተገንዝቧል፡፡
ከኒቅያ ጉባኤ መልስ መንፈሰ እግዚአብሔር በራዕይ በገለፀለት መሠረት ቅዱስ ኤፍሬም ከቅዱስ ባስልዮስ (ቁጥሩ ከ318ቱ ሊቃውንት ወገን ነው) ዘንድ ለመገናኘት ወደ ቂሣርያ ሄዷል፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም የዲቁና ክህነት ሠጥቶ ከሀገረ ስብከቱ ከፍሎ እንዲያስተምር ወስኖ በእርሱ ዘንድ አኑሮታል፡፤ በዚያም ቦታ ብዙ ተአምራትን አድርጓል መጻሕፍትንም ጽፏል፡፡
ቅዱስ ኤፍሬም በትውፊት እንደሚታወቀው ምንኩስናን በገቢር ገለጣት እንጂ ሥርዓተ ምንኩስናን መፈጸሙን በግልጽ የሚመለክት ማስረጃ አልተገኘም፡፡ እንዲያውም በሶርያውያን ክርስቲያኖች የሚዘወተረውን ራስን በአንድ ስፍራ ወስኖ በብሕትውናና በመምህርነት ቤተክርስቲያንን የማገልገል (Proto-monasticism) ሕይወት ይኖር እንደነበር ይታመናል፡፡ በትውፊት ቅዱስ ኤፍሬም ቅዱስ ባስልዮስን ለመጎብኘት ወደ ቀጰዶቅያ እንዲሁም አባ ቢሾይን ለመጎብኘት ወደ ግብጽ እንደተጓዘ የሚነገረውም ከዚህ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ ፍጹም በሆነ ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቱ ምሳሌ በሚሆነው ትምህርቱና የምናንኔ ሕይወቱ የሚታወቀው ቅዱስ ኤፍሬም ሐምሌ አስራ አምስት ቀን በ 370 ዓ.ም አርፏል፡፡በዚህ ሁሉ ትጋቱም ሶርያውያን ክርስቲያኖች ‹ጥዑመ ልሳን›፣ ‹መምህረ ዓለም›፣ ‹ዓምደ ቤተ ክርስቲያን› በማለት ይጠሩታል፣ያወድሱታል፣ያመሰግኑታል፡፡የቅዱስ አባታችን ረድኤትና በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡ አሜን!

የቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎች
ቅዱስ ኤፍሬም እንደሌሎች የ4ኛው  መ/ክ/ዘ አበው በርካታ ትምህርቶችንና መጻሕፍትን የጻፈና ያዘጋጃ አባት ነው፡፡ ይህንንም ስንክሳር እንዲህ ይገጸዋል፡፡

እጅግም ብዙ የሆኑ 14 ሺህ ድርሳናትንና ተግሳጻትን ደረሰ፤ ከእርሳቸውም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ውዳሴዋን ነው፡፡ ‹አቤቱ የጸጋህን ማዕበል ግታልኝ ‘ እስከሚል ድረስ ድርሳናትን ደርሶአል፡፡ (ስንክሳር ዘሐምሌ 15 ተመልከት)
በአሁኑ ዘመን የቅዱስ ኤፍሬም መጻሕፍትና ትምህርቶች እንደሌሎቹ የ4ኛው  መ/ክ/ዘ አበው ሥራዎች ጎልተው የታወቁ አይደሉም፡፡ ለዚህም ምክንያቶቹ ሁለት ናቸው፡፡
1. ቅዱስ ኤፍሬም አብዛኛዎቹን ትምህርቶችና መጻሕፍትን ያዘጋጀው በዘመኑ ብዙ ተጽእኖ በነበራቸው በግሪክ ወይም በላቲን ቋንቋዎች ሳይሆን በሱርስት በመሆኑ ነው፡፡ አንዳንድ ሊቃውንት ይህን እውነት እንደ መልካም ነገር ይጠቅሱታል፡፡ ወንጌል በግሪክ ከመጻፏ በፊት የተሰበከችው በሱርስት ነው( ጌታም ያስተማረው በዚሁ ቋንቋ ነው በማለት ይህም የሶርያ ክርስትና በግሪካዊው ፍልስፍና ያልተጠቃ (Little Hellenized) እንዲሆን ያደረገ ነው በማለት እንደመልካም ነገር ይጠቅሱታል።
 
2. ቅዱስ ኤፍሬም ትምህርተ ክርስትናን ከሌሎች አበው ለየት ባለ መልኩ በጥበባዊ ስልት (በግጥም፣በቅኔ፣በደብዳቤ፣በጥያቄና መልስ) በማዘጋጀቱና አብዛኞቻችን በዚህ ስልት ጠንከር ያለ ትምህርተ ክርስትና ይገኛል ብለን ስላላመንን ወይም ዝንባሌው ስለሌለን ነው፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ በዚህ ዘመን በርካታ መጻሕፍት የቅዱስ ኤፍሬም ናቸው እየተባሉ ሲሰራጩ እናስተውላለን። አብዛኛዎች ግን የእርሱ አይደሉም ፤በተለይ የመጀመሪያ ጽሕፈተ ቋንቋቸው ግሪክ የሆኑት።ስለዚህ መጻሕፍቱን ከመጠቀማችን በፊት የቅዱስ ኤፍሬም ድርሰቶች መሆናቸውን ማወቅ ይገባል፡፡
የቅዱስ ኤፍሬም የጽሑፍ ሥራዎች
እነዚህን ጽሑፎች ጠቅለል አድርጎ በአራት መክፈል ይቻላል፦
1. ቀጥተኛ ትርጓሜያት፡- ይህ ክፍል ከመጽሐፍ ቅዱስ አንዱን መጽሐፍ በመውሰድ የተጻፉ ትርጓሜያትን የሚያጠቃልል ነው፡፡ ምሳሌ – የኦሪት ዘፍጥረት፣ የኦሪት ዘፀአትና የግብረ ሐዋርያት ትርጓሜያትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
2. ጥበበባዊ (Artistic) ትምህርቶች (ትርጓሜያት)፦ በግጥም ወይም በሌላ ጥበባዊ መልክ የተጻፉ ትርጓሜያትን የሚያካትት ነው፡፡ ‹በእንተ ክርስቶስ› (በጥያቄና መልስ የቀረበው) ትምህርት ተጠቃሽ ነው፡፡ እንዲሁም ‹በነገረ ምጽአት ላይ ለፑከሊየስ የተጻፈው ደብዳቤም፡፡›
3. በቁጥር የተደረጉ ስብከቶች (Verse homilies)፦ አንድን ርዕስ በማንሳት የተሰጡ ስብከቶችን የምናገኝበት ክፍል ነው፡፡ ‹በእንተ እምነት› የተሰኘው ስብከቱ ተጠቃሽ ነው፡፡
4. የዜማ ወይም የቅዳሴ ድርሰቶች፡፡
ቅዱስ ኤፍሬምና የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን
የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያዘጋጀቻቸውን አብዛኛዎችን የትርጓሜ መጻሕፍት ያጠኑ ሊቃውንት መጻሕፍቱ የኤዴሳ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት የትርጓሜ ስልትና የምስጢር ፤ የዘይቤ አንድነት እንደሚስተዋልባቸው ያስረዳሉ፡፡ ከዚያ ውጪ በውዳሴ ማርያምና በአንቀፀ ብርሃን መካከል ያለው የአንድነት ጉዳይ ከትርጓሜ መጻሕፍት ወደ ጸሎት መጻሕፍትም ሊራመድ እንደሚችል ያስገነዝባል፡፡ ለዚህ ሃሣብ መቋጫ የስርግው ሐብለ ሥላሴን ንግግር እናቅርብ፡-
‹ኤፍሬም (ሶርያዊ)› የሶርያ ተወላጅ እርሱ የደረሳቸው መጻሕፍት ወደ ግእዝ ብዙዎቹ ተመልሰዋል፡፡ በተለይ ውዳሴ ማርያም በየዕለቱ በሕዝበ ክርስቲያን የሚጸለይ ጸሎት ነው፡፡
በመጽሐፈ አክሱም እርሱና አባ ሕርያቆስ የተባለው ቅዳሴ ማርያም የደረሰው ወደ አክሱም መጥተው ማይ ከርዋህ በሚባል ስፍራ ተገናኝተው ኤፍሬም ያሬድን ውዳሴ ማርያምን ሕርያቆስን ደግሞ ቅዳሴዋን እንዳስተማረው በሰያፍ መንገድ ይገለጻል፡፡ እዚህ ላይ ዋናው ቁም ነገር ቅዱስ ያሬድ በስድ ንባብም ሆነ በግጥም መልክ የደረሳቸው ድርሰቶች የሶሪያ ቤተክርስቲያን ባህል የተከተሉ መሆናቸውና የሶርያ ቤተክርስቲያን ለኢትዮጵያ መንፈሳዊ እድገት ከፍ ያለ አስተዋጽዖ እንዳደረገች የሚያሳይ ነው፡፡
  (አማርኛና የቤተ ክርስቲያን መዝገበ ቃላት ረቂቅ ኤፍሬም የሚለውን ተመልከት)፡፡
 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ይቆየን !

ታቦት

ትምህርት ሃይማኖት (የሃይማኖት ትምህርት) በሁለት ይከፈላል፡፡ ይኸውም፦
1ኛ፡- ዶግማ   2ኛ፡- ቀኖና በሚል ነው፡፡
ዶግማ፡- ቃሉ የግሪክ ሲሆን ፍችውም እምነት ማለት ነው፡፡

ቀኖና፡- ደግሞ ቃሉ የግሪክ ሲሆን ሥርዓት ማለት ነው፡፡ ከእነዚህ ከሁለቱ ዶግማ ወይም እምነት አይጨመርበትም፤ አይቀነስበትም፤ አይሻሻልም፤ ችግርና ፈተናም ቢመጣ እስከ ሞት ድረስ አጥብቀን የምንይዘው ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል ይህን ዓለም ካለመኖር ወደ መኖር አምጥቶ የፈጠረ፤ ቢመረምር እንጂ የማይመረመር ሁሉን ቻይ አምላክ፤ የሚሳነው ነገር የሌለ ፈጣሪ፤ የሰማይና የምድር ባለቤት የሠራዊት ጌታ ሕያው እግዚአብሔር ነው፡፡

እግዚአብሔር (ፈጣሪ) የአካል ሦስትነት አለው፡፡ በመለኮት፣ በመፍጠር፣ በሥልጣን፣ በአገዛዝ፣ በፈቃድ ግን አንድ ነው፡፡ በሦስትነቱ አብ፤ ወልድ፤ መንፈስ ቅዱስ ሲባል በአንድነቱ አንድ መለኮት አንድ እግዚአብሔር ይባላል፡፡ በአዳም ምክንያት ከመጣው የዘለዓለም ሞትና ከዲያብሎስ ባርነት ነጻ የወጣነው ከሦስቱ አካላት በአንደኛው አካል ማለትም በወልድ በኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ይህ ዶግማ ወይም እምነት ይባላል፡፡

ቀኖና ግን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው ያደጉ ክርስቲያኖች የሚመሩበት ሥርዓት ስለሆነ፤ በሃይማኖት አባቶች ወይም በቅዱስ ሲኖዶስ አማካኝነት እንደጊዜው ሁኔታ የሚሻሻል በመሆኑ የሚጨመርበት፤ የሚቀነስለት ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል እኛ ኦርቶዶክሳውያን የምንጠመቀው ሴት በሰማንያ ወንድ በአርባ ቀናችን ነው፡፡ የተወለዱ ሕጻናት ሴቷ ሰማንያ ወንዱም አርባ ቀን ሳይሞላቸው ቢታመሙና በሽታው አስጊ ከሆነ በ10፣ በ20፣ በ30…ቀናቸው መጠመቅ ይችላሉ ቀኖና ነውና፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የቀዳስያን ብዛት መነሻው አምስት ነው፡፡ ምናልባት ከአምስቱ አንዱ፤ ሁለቱ፤ ሦስቱ ቢታጡና ሌላም ተፈልጎ እስከ መጨረሻ የማይገኝ ከሆነ ከአቅም በላይም የሆነ ችግር ከገጠመ ሁለቱ ወይም አንዱ ብቻ ቀድሰው ማቁረብ ይችላሉ፡፡ ቀኖና ነውና፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ታቦት ሲከብር ቤተ ክርስቲያኑን የሚዞረው ሦስት ጊዜ ነው ችግር ካለ አንድ ጊዜ ብቻ ዑደት ተፈጽሞ ሊገባ ይችላል። ቀኖና ነውና፤ ስለቀኖና (ስለሥርዐት) ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ እንዲህ ሲል ጽፏል።

1. ‹‹ነገር ግን ሁሉን በአግባብና በሥርዐት አድርጉ፡፡›› 1ኛ ቆሮ. 14፥40፡፡
2. ‹‹ወንድሞች ሆይ በሠራንላቸው ሥርዐት ሳይሆን በተንኮል ከሚሄዱት ወንድሞች ሁሉ ትለዩ ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እናዝዛችኋለን፡፡ እኛን ልትመስሉ እንደሚገባችሁ እኛም በእናንተ መካከል ያለ ሥራ እንዳልኖርን ራሳችሁ ታውቃላችሁ›› 2ኛተሰ. 3፥6-7›› ቀኖና (ሥርዐት) የሚወሰነው በሃይማኖት አባቶች እንደሆነና ወንጌልን የሚስተምር ሰው ለሚያስተምራቸው ክርስቲያኖች በሃይማኖት አባቶች የተወሰነ ቀኖና ማስተማርና መሰጠት እንዳለበት መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ሲል ያስረዳል፡፡

በየከተማውም ሲሄዱ፥ ሐዋርያትና ቀሳውስት በኢየሩሳሌም ያዘዙትን /የወሰኑትን/ ሥርዐት አስተማሯቸው፡፡ አብያተ ክርስቲያናትም በሃይማኖት ጸኑ ዕለት ዕለትም ቁጥራቸው ይበዛ ነበር፡፡›› ይላል የሐዋ. 16፥4-5፡፡ በዚህ የእግዚአብሔር ቃል መሠረት ቅዱስ ጳውሎስ ደርቤንና ልስጥራን በተባሉ ቦታዎች ለነበሩ ክርስቲያኖች ወንጌልን ከሰበከ በኋላ ሐዋርያት የወሰኑትን ቀኖና (ሥርዐት) እነደሰጣቸው እንረዳለን፡፡ ስለዚህ ቀኖና ወይም ሥርዐት ቤተክርስቲያንን ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም፡፡ በመሆኑም ዶግማንና ቀኖናን ወይም እምነትንና ሥርዓትን ጎን ለጎን ይዞ መጓዝ ሐዋርያትን መከተል እንጂ ወደ ኋላ ተመልሶ አይሁድን መከተል አይደለም፡፡ እንግዲህ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን የሚቃወሙ ሰዎች ሁሉ፤ የሚቃወሙት በቀኖና (በሥርዐት) የሚመሩትን ክርስቲያኖች ሳይሆን የእግዚአብሔር ቃል የሆነ መጽሐፍ ቅዱስን በመሆኑ እንዳይሳሳቱ አደራ እንላለን፡፡

አሁን እንግዲህ የዶግማንና የቀኖናን ልዩነት ከተረዳን በቀጥታ ወደ ታቦቱ ጥያቄ እንሄዳለን፡፡

ጥያቄ፡-1 ዛሬ በእኛ ቤተክርስቲያን ያለው ታቦት ነው? ወይስ ጽላት በታቦትና በጽላት መካከል ልዩነት አለና፡፡

መልስ፡- ታቦት የጽላት ማደሪያ ነው፡፡ ዘዳ 40፥20፡፡ ጽላት ደግሞ ቅዱስ ቃሉ የተጻፈበት ሰሌዳ ማለት ነው፡፡ ዘዳ 34፥27-28፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሁለት ነገሮች ዛሬም በሐዲስ ኪዳን አሉ። ሆኖም ግን አሠራሩ ሙሉ በሙሉ በዘጸ 25፥10-18 ያለውን የሙሴን ሕግ የተከተለ አይደለም፡፡ ምክንያቱም፤

1ኛ፡- ታቦት እንደሙሴ ሕግ የሚዘጋጀው ከግራር እንጨት ሆኖ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፤ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል ቁመቱም አንድ ተኩል ይሁን ይልና በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፤ በዙሪያውም የወርቅ አክሊል አድርግለት ይላል፡፡ ደግሞም ታቦቱን የሚሸከሙት ከወርቅ በተሠሩ መሎጊያዎች አራት ሰዎች እንደሆኑ እንረዳለን፡፡ በአጠቃላይ የብሉይ ኪዳን የታቦት አሠራር እጅግ ከባድ በመሆኑ በሁሉም ዘንድ አይቻልም ነበር፡፡ ምናልባት አንዳንድ የቤተክርስቲያን ፍቅር የነበራቸው ነገሥታትና ዛሬም ፍቅረ ቤተክርስቲያን ያላቸው አንዳንድ ምዕመናን ይችሉት እንደሆነ ነው እንጂ፡፡

2ኛ፡- ጽላት፤ ጽላትም እንደሙሴ ሕግ ከሆነ መዘጋጀትና መጠረብ ያለበት ከከበረ ድንጋይ ነው፡፡ በአንድ ታቦት ውስጥም መቀመጥ ያለባቸው ሁለት ጽላቶች ናቸው፡፡ ዘዳ 34፥1፡፡ በአጠቃላይ እንደ ብሉይ ኪዳኑ ሕግና ሥርዐት ከባድ ነው፡፡ የብሉይ ኪዳኑ ሥርዐትም ለሐዲስ ኪዳኑ ሥርዓት ጥላ ሆኖ አልፏል፡፡ 2ኛ ቆሮ 3፥7-11 ፤ ቆላ 2፥17፤ ዕብ 10፥1፡፡

እንግዲህ እዚህ ላይ የሐዲስ ኪዳኑ ታቦትና ጽላት የብሉይ ኪዳኑን የታቦት አሰራርና ሥርዐት ጠንቅቆና ተከትሎ የማይሄድ ከሆነ፤ ይህ የብሉይ ኪዳኑን የታቦትና የጽላት አቀራረጽ ሥርዐት ጠንቅቆ ያልሄደ የሐዲስ ኪዳን ታቦትና ጽላት ከየት መጣ የሚል ጥያቄም ሳይነሳ አይቀርም፡፡

አንባብያን ሆይ በቀጥታ ወደ ጥያቄው ከመግባታችን በፊት በዚህ ጽሑፍ ዶግማ ላይ ስለዶግማና ቀኖና ማብራሪያ የሰጠነው ይህን ለመሰለው ጥያቄ እንዲጠቅም ነው፡፡ አሁን ወደ ሐዲስ ኪዳን ታቦትና ጽላት ስንሄድ ቁም ነገሩ እንደሚከተለው ነው፡፡

የሐዲስ ኪዳን የታቦትና የጽላት አቀራረጽም ሆነ አጠቃቀሙ የተወሰነውና የሚወሰነው በቀኖና ነው፡፡ ቀኖና ደግሞ እንደ ሁኔታው የሚሻሻል ነው፡፡ ሲቻል ይጨመርበታል ሳይቻል ደግሞ ይቀነስለታል፡፡ እንግዲህ በቤተክርስቲያናችን ቀኖና ካበረከታቸው ነገሮች አንዱ የሐዲስ ኪዳን የታቦትና የጽላት አቀራረጽንና አጠቃቀምን ነው፡፡

ስለዚህ በሐዲስ ኪዳን ታቦትን ለመቅረጽ የግራር እንጨት ባይገኝ በዘፍ 1፥31 ላይ ‹‹ እግዚአብሔርም የፈጠረውን (ያደረገውን) ሁሉ እጅግ መልካም እንደሆነ አየ›› ስለሚልና እግዚአብሔር የፈጠረውን ስለማይንቅ ከግራር ሌላ ከማይነቅዝ እንጨት መቅረጽ እንችላለን፡፡ ቁመቱ ወርዱና ዙሪያውም እንደችሎታችን ይሆናል፡፡ በውስጥና በውጭ ስለሚሆነው የወርቅ ክብርም እንደችሎታችን ይወሰናል፡፡ ከሌለንም ወርቁ ይቀራል ቀኖና ነውና፡፡

ስለጽላቱም እንደዚሁ ነው ከቻልን ከከበረ ድንጋይ፣ ከዕብነ በረድ መቅረጽ እንችላለን፤ ካልቻልን ጽላቱን ከማይነቅዝ እንጨት መቅረጽ እንችላለን፡፡ በሌላ በኩልም ከቻልን እንደ ብሉይ ኪዳኑ በአንድ ታቦት ሁለት ጽላት ማስቀመጥ እንችላለን፤ ካልቻን በአንድ ታቦት አንድ ጽላት ብቻ ይሆናል፡፡ በተጨማሪም የጽላቱን ማስቀመጫ ታቦት ባይኖረን ጽላቱን ታቦት ብለን በመጥራት በጽላቱ ብቻ መጠቀም እችላለን ቀኖና ነውና፡፡

በተጨማሪም በኤር 31፥31፤ 2ኛ ቆሮ 3፥1-3፤ በዕብ 8፥8-13፡፡ የእኛ አካልና ልቡና የእርሱ ታቦትና ጽላት አልሆነም ወይ? በሐዲስ ኪዳን ለምን ታቦትና ጽላት አስፈለገ? ለምንስ ይህ ሁሉ ተፈጠረ የሚሉ አሉ፡፡ የክርስቲያኖች  አካልና ልቡና በክርስቶስ ደም ታቦት፤ ጽላት፤ ቤተ መቅደስ መሆኑን እናምናለን፡፡ ቢሆንም በሐዲስ ኪዳን ታቦትና ጽላት ያስፈለገበት ምክንያት ስለአምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነትና ክብር ሲባል ነው፡፡ ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን ክብሩን የገለጠበት፤ ቃሉን ያሰማበት፣ ሙሴን እንደባልጀራ ያነጋገረበት፣ የክብሩ ዙፋን ሆኖ ጽላቱ በውስጡ ለታቦቱ ማደሪያ በመሆኑ፤ በሐዲስ ኪዳንም የሥጋውና የደሙ የክብር ዙፋን እንዲሆን ሲሆን ስለእኛ በዚህ ዓለም መከራ የተቀበለውን መድኅኔዓለም ክርስቶስን ለማክበር ሲባል ነው፡፡

ጥያቄ2፡- በዘዳ 31፣18፣32፣15፣134፣1-5፡፡2ኛዜና 5፣10 ያሉትን ጥቅሶች በመጥቀስ እግዚአብሔር ለሙሴ የሰጠው ሁለት ጽላቶችን ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን እነዚህን እልፍ አእላፋት ጽላቶች ከየት አመጣቻቸው? አራብታችሁ ቅረጹ የሚል አለ ወይ?

መልስ፡- በዘዳ 32፥19፡፡ ስንመለከት እግዚአብሔር ራሱ አዘጋጅቶ ለሙሴ የሰጠውን ሁለቱን ጽላቶች እሥራኤል ጣዖት ሲያመልኩ ስላገኛቸው ሙሴ ተበሳጭቶ ሰብሯቸዋል፡፡ነገር ግን ቸርነቱ ለዘለዓለም የሆነ እግዚአብሔር አምላክ  ለሙሴ የመጀመሪያዎቹን አስመስሎ እንዲሰራ ነገረው፤ ሙሴም አስመስሎ ሠራ፡፡ ዘዳ 34፥1-5 መሥራት ብቻ ሳይሆን ዐሥሩን የቃል ኪዳን ቃላትም በጽላቶቹ ላይ እንዲጽፍ ሙሉ ሥልጣን ከእግዚአብሔር ተሰጠው፡፡ ሙሴም ተፈቅዶለታልና አሥሩን ቃላት በጽላቶቹ ላይ ጻፈ፡፡ ዘዳ 34፥27-28 ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ጽላትንም ሆነ ታቦትን እያስመሰሉ ለመሥራት ሙሉ ሥልጣንን አግኝተናል፡፡ ይህን በተመለከተ አንዳንድ አባቶች እንዲህ ይላሉ፤

‹‹አዳም እንኳን በደለ አዳም ባይበድል ኖሮ አምላክ ሰው ሆኖ በቀራንዮ ስለእኛ የመሰቀሉን፤ ስለኛ የመሞቱን የፍቅር ምስጢር አናውቀውም ነበር፡፡››

እስራኤልም በጥጃ ምስል ጣኦት አምልከው እንኳን በደሉ እሥራኤል ባይበድሉ ሙሴ በእግዚአብሔር የተዘጋጁት ሁለቱ ጽላቶች’ የሰው ልጅም እግዚአብሔር የሠራቸውን የፊተኞቹን አስመስሎ ለመሥራት ስልጣን ባልኖረውም ቢሠራም ለምን ሠራህ ለሚለው መረጃ ባላቀረበም ነበር›› ይላሉ፡፡ ያም ሆነ ይህ ጽላትን አስመስለን፤ አባዝተን፤ አራብተን ለመሥራት መሠረታችን ሥልጣኑ ለኛ ለልጆቹ የተላለፈልን ከአባታችን ከሙሴ ነው፡፡››

ሙሴ የተሰበሩትን አስመስለህ ሁለት ጽላቶች ቅረጽ ከሚል በቀር ጽላቶችን አብዝታችሁ፤ አራብታችሁ ተጠቀሙ የሚል ቀጥተኛ ቃል አምጡ ለሚለው ግን ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን የጽላትም ሆነ የቤተ መቅደስ ሥርዐት፤ የመስዋዕቱ የዕጣኑ አገልግሎት፤ በኢየሩሳሌም ብቻ ስለነበረና፤ የሌላውም አገር ሕዝብ የሚከተለው የጣዖትን ሥርዓት እንጂ የሙሴን ሥርዐት ባለመሆኑ ጽላቱ ተባዝቶ ተራብቶ ለሌላው አገር ሕዝብ አልተሰጠም፡፡ እግዚአብሔርም ከኢየሩሳሌም ውጭ አልፈቀደም የተቀደሰውን ጣዖታውያኑ አሕዛብ ያረክሱታልና ስለዚህ ስግደቱም የቤተመቅደስ ሥርዐቱም በኢየሩሰሳሌም ብቻ ነበር። /ዮሐ 4፥18-24/

በኢየሩሳሌም ይኖሩ የነበሩ አሕዝቦችም ሠሎሞን ያሠራው ታላቁ ቤተ መቅደስና ሁለቱ ጽላቶች አንሰውናል፤ በርቀት የምንገኝ እኛ የመንገድ ድካም በዝቶብናልና፡፡ ስለዚህ በያለንበት ቤተ መቅደስ ሠርተን ጽላቱን አክብረን መገልገል እንፈልጋለንና ይፈቀድልን ብለው ሙሴም ከሁለቱ ጽላቶች በቀር ሌላ አልተፈቀደም ብሎ መልስ የሰጠበት ቦታ የለም፡፡

ያም ሆነ ይህ በሐዲስ ኪዳንም በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በአብ፤ በወልድ፤ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቀው ፤ሁለተኛ የድኅነት ልደት ተወልደው የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣን ሰጣቸው። ለክርስቲያኖችም ከፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ ድረስ እንደሚበዙና በአዲስ ኪዳን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ንጹሕ የሆነውን ቁርባን ከኢየሩሳሌም ውጭ በየቦታው ለእግዚአብሔር ማቅረብ እንደሚችሉ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡፡

1. ‹‹ ከፀሐይ መውጫ ጀምሮ እስከ መግቢያዋ ድረስ ስሜ በአሕዛብ ዘንድ ይከበራልና፤ በየስፍራው ለስሜ ዕጣን ያጥናሉ፤ ንጹሕንም ቁርባን ያቀርባሉ፤ ስሜ በአሕዛብ ዘንድ ታላቅ ይሆናልና ይላል ሁሉን የሚችል እግዚአብሔር›› ሚል 1፥11፡፡
2. ‹‹ ቤቴ ለአሕዛብ ሁሉ የጸሎት ቤት ትባላለች ተብሎ ተጽፎ የለምን? እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችኋት ብሎ አስተማራቸው›› ማር11፥17፤ ኢሳ 56 ፥ 7፤ ኤር 7፥11 ፡፡

ይህ ትንቢት በቀጥታ ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች መሆኑ ግልጥ ነው፡፡ ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን ቤተ መቅደስም ሆነ የዕጣን፤ የቁርባን አገልግሎት እንኳን ከፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ ድረስ ላሉ አሕዛብ በኢየሩሳሌም ከሚኖሩ የእግዚአብሔር ሕዝቦች በቀር ለእስራኤል ጎረቤት አገሮች እንኳ አልተፈቀደምና፡፡ ነቢዩ ሚልክያስ ንጹሕ ዕጣን ያለው በማቴ 2፥11፡፡ ወንጌል እንደተናገረው ከአሕዛብ ወገን የሆኑ ሰብአ ሰገል በቤተልሔም ዋሻ ለክርስቶስ ካቀረቡት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በዓለም ያለን ክርስቲያኖች በክርስቶስ ስም ለክርስቶስ የምናቀርበው ቅዱስ ዕጣን ነው፡፡

ንጹሕ ቁርባን የሚለውንም በማቴ 26፥26፤ ጌታ ኅብስቱን አንሥቶ ነገ የሚቆረሰው ሥጋዬ ይህ ነው፤ ወይኑንም አንሥቶ ነገ ስለብዙዎች ሀጢአት የሚፈሰው ደሜ ይህ ነው ብሎ ለሐዋርያት የሰጣቸው የክርስቶስ ሥጋና ደም ነው፡፡ ንጹሕ የተባለው እርሱ በባሕርዩ ንጹሕ ሆኖ የእኛን የኃጢአት እድፍ ስለሚያነጻ ነው፡፡

በብሉይ ኪዳን በኢየሩሳሌም ብቻ መሆን የሚገባቸው ቤተ መቅደሱ፤ ዕጣኑ፣ ቁርባኑ፣ በክርስቶስ ደም በአዲስ ሕይወት፣ በአዲስ ተፈጥሮ፤ በአዲስ ሥርዓት፣ ክርስቲያኖች ለሆንን ለዓለም ሕዝቦች በየሥፍራው (በያለንበት) እንድንጠቀምባቸው ከተፈቀዱልን በኢየሩሳሌም ይኖሩ የነበሩት ሁለቱ ጽላቶች ከፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ ተባዝተው በዓለም ያለን ክርስቲያኖች በያለንበት በየቤተ መቅደሳችን ለሥጋውና ለደሙ የክብር ዙፋንነት ብንገለገልባቸውና የአምላካችን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም ብናከብርባቸው ምን የሚጎዳ ነገር ተገኘ? የሚያስደነግጠውስ ምኑ ነው? ስህተቱስ የቱ ላይ ነው?
   
እንዲሁም ዐሠርቱ ትእዛዛት የተጻፉባቸው ሁለቱ ጽላቶች መባዛት መራባት የለባቸውም ከተባለ በጽላቶቹ ላይ የተጻፉት ዐሠርቱ ትእዛዛት መባዛት የለባቸውም፡፡ ከኢየሩሳሌምም መውጣት የለባቸውም ማለት አይደለም? ትእዛዛቱም ተከለከሉ ማለት ነውና፡፡

በጽላቶች ላይ የተጻፉት ትእዛዛት በእግዚአብሔር ፈቃድ በፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ ድረስ በሚገኙ ክርስቲያኖች እጅ ገብተዋል፡፡ ይህም ያስደስታል እንጂ አያሳዝንም፡፡ ይህ ከሆነ ለሥጋውና ለደሙ (ለክርስቶስ) ክብር ሲባል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚገኙ ጽላቶች ምን በደል አስከተሉ፥ እግዚአብሔር ለቀደሙ አባቶቻችን በታቦቱ አድሮ የሠራላቸውን ድንቅ ሥራ እያስታወስን እግዚአብሔርን ከማመስገን ውጭ ደግሞም ጌታ ስለ ጸሎት ሲያስተምረን ‹‹አባታችን ሆይ በሚለው ጸሎት ውስጥ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን›› በሉ ብሏል፡፡ በዚህ መሠረት በዮሐንስ ራዕይ 11፥19 ላይ ታቦቱን በሰማይ አሳይቶናል፡፡ ስለዚህ የሙሴ የቃል ኪዳኑ ታቦት በሰማይ እንዲገኝ፤ በሰማይ እንዲሆን፤ በሰማይ እንዲታይ ፈቃዱ ከሆነ፤ በምድርም እንዲሆን ፈቃድህ ይሁን ብለን ብንጠቀምበት ስህተቱ ምን ይሆን?

ጥያቄ3፡- የሰሎሞን ቤተ መቅደስ እስኪሠራ ድረስ በእርግጥ ታቦቱ ከቦታ ወደ ቦታ ይዘዋወር ነበር፤ ቤተ መቅደሱ ተሠርቶ ታቦቱ ወደ ቤተ መቅደሱ ከገባ በኋላ ግን ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው ስለመውጣታቸው መጽሐፍ ቅዱስ አይናገርም፡፡ ታዲያ ዛሬ ክርስቶስ ደሙን ካፈሰሰ በኋላ፤ በብሉይም ሆነ በሐዲስ ኪዳን መመሪያ ሳይኖር፤ ከየት አምጥታችሁ ነው ታቦትን በየጊዜው በማውጣት የክርስቲያኖች ህሊና ሁሉ ወደተሰቀለው ክርስቶስ መሆኑ ቀርቶ ወደ ታቦቱ የሆነው?

መልስ፡- በብሉይ ኪዳን እንኳን አይወጣም ነበር ማለት አንችልም ምክንያቱም በችግራቸው ጊዜ ለችግራቸው መፍትሔ ያገኙ ዘንድ ከነበረበት ከድንኳኑም ቢሆን ያወጡት ነበርና ለምሳሌ፦

1. በሙሴ ምትክ  የተመረጠ ኢያሱ ሕዝበ እስራኤልን እየመራ ወደ ምድረ ርስት ሲሄድ ድንገት የዮርዳኖስ ወንዝ ሞልቶ ባገኘው ጊዜ ወንዙን ከፍሎ አሕዛብን ለማሻገር ከእግዚአብሔር በተነገረው መሠረት ካህናቱ ታቦቱን ከነበረበት ቦታ ተሸክመው ወደ ወንዙ በመሄድ ታቦቱን የተሸከሙት ካህናት እግር ወንዙን ሲረግጥ ወንዙ ተከፍሎ ሕዝቡ ሁሉ በሰላም መሻገራቸውን እናገኛለን፡፡ ኢያሱ 3፥1-17፡፡
 
2. እስራኤል ምድረ ርስት በደረሱ ጊዜ ምድረ ርስት (ኢያሪካ) በጠላት እጅ በጽኑዕ ግንብ ታጥራ አገኟት፡፡ በዚህም ጊዜ ይህን የጠላት የግንብ አጥር ለማፍረስና ርስታቸውን በእጃቸው ለማድረግ እግዚአብሔር የገለጠላቸው ጥበብ ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው ሕዝቡም እየተከተሉ ሰባት ጊዜ ግንቡን እንዲዞሩት ነው፡፡ የታዘዙትን አደረጉ ግንቡም ፈረሰላቸው፡፡ ኢያሱ 6፥1-17፡፡

3. እስራኤል ጠላት በበረታባቸው ጊዜ ጠላትን ለማሸነፍ ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው ይወጡ ነበር፡፡ 1ሳሙ 5፥1-ፍ፡፡ ስለዚህ በብሉይ ኪዳን ካህናቱ ታቦቱን ከቦታ ወደ ቦታ ሲንቀሳቀሱ ካልሆነ በቀር ለሚፈልጉት ዓላማ ታቦቱን ካለት ቦታ ተሸክመው አያወጡትም ነበር ማለት አንችልም፡፡ ሰሎሞን ቤተ መቅደሱን ሠርቶ ካስገባው በኋላ ቢሆንም ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው እንዳያወጡ የሚል ሕግም የለም፡፡ እግዚአብሔር የሠራው ሥራ በብሉይ ኪዳን የተፈጸመው አገልግሎት ሁሉ ሙሉ በሙሉ በመጽሐፍ ቅዱስ አልተጻፈም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስም ያልተጻፈ ብዙ ነገር እንዳለ እናምናለን ከዚህ በመነሳት ነው እኛ በሐዲስ ኪዳን ታቦትን ተሸክመን የምናወጣው፤

በብሉይ ኪዳን በእግዚአብሔር ቸርነት (ትእዛዝ) ካህናቱ ታቦታቱን ተሸክመው እንዲወጡ ተደርጎ ካህናቱም ታቦታቱን ተሸክመው በመውጣት በታቦቱ ያደረ ኃይለ እግዚአብሔር ለሕዝበ እስራኤል ያደረገው ድንቅ ሥራ ለማሰብና እግዚአብሔርን ለማመስገን ነው፡፡ዛሬም ለሥጋና ለደሙ የክብር ዙፋን የሆነውን ቅዱስ ስሙም የተጻፈበትን ቅዱስ ታቦት በምናወጣበት ጊዜ በደሙ የባረከን መድኅነ ዓለም ክርስቶስ አሁንም የሥጋውና የደሙ ዙፋን በሆነው በታቦቱ ረቂቅ ኃይሎች በማስተላለፍ በረከቱን ያበዛልናል ብለን በማመን ነው፡፡

የተሰቀለው አምላክ መክበሩና መንገሡ ቀርቶ በየጊዜው ታቦት ወጣ እየተባለ ታቦቱ ብቻ ነገሠ ከበረ ሕዝቡም ወደ አምልኮ ባዕድ ኮበለለ ስለሚለው ግን አንድ ሕዝብ የንጉሡን ዙፋን ሲያከብርና ሲፈራ ንጉሡን ማክበሩና መፍራቱ እንደሆነ መዘንጋት የለበትም፡፡

እኛ የምናምነው ቅዱስ ስሙ የተጻፈበትን የክርስቶስ ሥጋና ደም የክብር ዙፋን የሆነውን ታቦት ማክበራችን በኪሩቤል ዙፋን የሚቀመጥ መድኅነ ዓለም ክርስቶስን ማክበራችን መሆኑን ነው፡፡ በታቦቱ ፊት መስገዳችንም በታቦቱ ለተጻፈው ለቅዱስ ስሙ ነው፡፡ በታቦት ፊት ለእግዚአብሔር ስም ይሰግዱ የነበሩ ኢያሱና የእስራኤል ሽማግሌዎች በረከት አገኙበት እንጂ አልተጎዱበትምና ነው፡፡ ኢያ 7፥6፣ ዘዳ 33፥10፡፡

በሐዲስ ኪዳንም ‹‹ድል ለነሣው ስውር መናን እሰጠዋለሁ፤ የብርሃን መጽሐፍንም እሰጠዋለሁ፤ በዚያ መጽሐፍ ውስጥ ላይ ከተቀበለው በቀር ማንም የሚያውቀው የሌለ አዲስ ስም ተጽፎበታል›› ራእ 217፡፡ ለዚህ ስም ደግሞ ጉልበት ሁሉ መንበርከክ እንደሚገባ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፤

‹‹ይህም በሰማይና በምድር በቀላያትና ከምድርም በታች ያለ ጉልበት ሁሉ ለኢየሱስ ክርስቶስ ስም ይሰግድ ዘንድ ነው። አንደበትም ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔር አብ ክብር ጌታ እንደሆነ ያምን ዘንድ ነው›› ፊልጵ 2፥10-11፡፡ በዚህ መሠረት ቅዱስ ስሙ በተጻፈበት ከነጭ ድንጋይ (ከዕምነ በረድ፣ከእንጨት) በተሠራው በጽላቱ ፊት ለቅዱስ ስሙ መስገድ ታላቅ የመንፈስ ጥበብ እንጂ ሞኝነት አይደለም፡፡ ምናልባት ስለታቦት፣ ስለጽላት ባለማወቅ ባጠቃቀሙ በኩል የሚሳሳቱ አባቶችን፤ እናቶችን ወንድሞችንና እህቶችን በተገቢው መንገድ ማስተማር ተገቢ ነው፡፡

ከዚህ በላይ ስለ ታቦት ከቤተ መቅደስ መውጣትና አለመውጣት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ከመሆኑም በተጨማሪ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሆኑ መታወቅ አለበት፡፡

ብዙዎች በሐዲስ ኪዳን ታቦትን ለመቃወም በኤር 3፥16፡፡ የተጻፈውን ጠቅሰው “በዚያ ዘመን ፦የ እስራኤል ቅዱስ እግዚአብሔር የቃል ኪዳኑ ታቦት እነኋት እያሉም በአፋቸውም አይጠሯትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሿትም።” ተብሏልና ታቦት አያስፈልግም በማለት ያስተምራሉ፡፡

እንደተባለው ታቦት ብሎ መጥራት ካላስፈለገ በኤርምያስ 31፥34፤ ደግሞ “እያንዳንዱ ሰው ባልንጀራውን፣ እያንዳንዱም ወንድሙን፦ እግዚአብሔርን ዕወቅ ብሎ አያስተምርም” ተብሎ ስለተጻፈ እንግዲህ ሰው ሁሉ በየዘመኑ እግዚአብሔርን እንዲያውቅ ማስተማር አያስፈልግም ማለት ነዋ! ደግሞም ጌታችን በማቴ 28፥19 “እንግዲህ ሂዱና በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ” ብሎ መናገሩ ስህተት መሆኑ ነዋ! በአጠቃላይ እንዲህ ነው ብሎ ከመናገር አስቀድሞ በመጽሐፍ የተጻፈው ነገር ለምንና እንዴት ባለ ሁኔታና ጊዜ መጻፉን ማጥናትና መልእክቱን (ምስጢሩን) መመርመር ይገባል እንላለን፡፡

በመጨረሻ ግን በኢትዮጵያ ኦርቶኮክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማርያም፣ የቅዱሳን፣የሰማዕታት፣ የመላዕክት ወዘተ…. ታቦት እየተባለ የተሰየመበት ምክንያቱና የዚህ ስያሜ ከየት ነው የመጣው ምንድን ነው የሚሉ ጥያቄዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ እርግጥ ነው፡፡

እንዲህ ተብሎ መሠየሙ በትንቢተ ኢሳይያስ 56፥46 በተገለጸው መሠረት የእግዚአብሔርን ሰንበቱን ለሚጠብቁ ደስ የሚያሰኘውንም ለሚመርጡ ቃል ኪዳኑንም ለሚይዙ ጃንደረቦች (ስለእግዚአብሔር መንግሥት ራሳቸውን ጃንደረባ ያደረጉ ቅዱሳን) ማቴ 19፥12 በእግዚአብሔር ቤትና በቅጥሩ የዘለዓለም መታሰቢያ እንደሚደረግላቸው የተገለጠ በመሆኑ ይህን አብነት በማድረግ ጌታ ሥጋው፣ ደሙ የሚከብርበት ሆኖ ለቅዱሳኑም መታሰቢያ ለማድረግ ነው፡፡ /መዝ 111፥7/ እንዲሁም የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነውና ምሳ 10፥7፡፡ በዚህ ምክንያት እንጂ በታቦታቱ የሚከብረው መድኃኒተ ዓለም ክርስቶስ መሆኑ ግልጽ ሊሆን ያስፈልጋል፡፡

እግዚአብሔር አስተዋይ ልቡና ይስጠን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
አሜን።

/ምንጭ፦ ሐመር መጽሔት ሚያዝያ 1985 ዓ.ም/

qana.jpg

ቃና ዘገሊላ

qana.jpg

የሃይማኖት አባቶች የቀድሞ የደርግ ባለሥልጣናትን ወክለው ይቅርታ አቀረቡ።

መ/ር መንግስተአብ አበጋዝ

የአራት የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች የቀድሞ የደርግ ባለሥልጣናትን የይቅርታ ጥያቄ ለኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት አቀረቡ።

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን፣ የኢትዮጵያ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን፣ የኢትዮጵያ ወንጌላዊት ቤተ ክርስቲያን መካነ ኢየሱስ እና የኢትዮጵያ እስልምና ጉዳዮች ጠቅላይ ምክር ቤት የሃይማኖት መሪዎች ቅዳሜ ታኅሳስ 9 ቀን 2003 ዓ.ም በኢንተርኮንቲኔንታል ሆቴል ተገኝተው በሰጡት የጋራ መግለጫ ይህን የታሪክ ጠባሳ በአገራዊ ይቅርታና ዕርቅ መጨረስ ከሁሉ በላይ ታላቅ መንፈሳዊ አንድምታ ይኖረዋል ብለዋል።
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ጉባኤውን ወክለው ባቀረቡት መግለጫ ላለፉት ሁለት ዓመታት ለጉዳዩ ስኬታማነት ሲሠሩ መቆየታቸውን ገልጸዋል። ከኢትዮጵያ ሕዝብና መንግሥት በሚያገኙት ይሁንታ ታኅሣሥ 21 ቀን 2003 ዓ.ም አጠቃላይ ሀገራዊ እርቅ እንደሚካሄድ ተናግረው፥ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ይህንኑ መንፈሳዊ ጥሪ ተቀብሎ በጎ ምላሽ እንደሚሰጠን በመተማመን ይህን የሰላምና የዕርቅ ሐሳብን ይዘን ቀርበናል በማለት አስረድተዋል።

«ብፁዓን ገባርያነ ሠላም፥ እስመ እሙንቱ ውሉደ እግዚአብሔር ይሰመዩ።
የሚያስታርቁ ብፁዓን ናቸው፥ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና»  ማቴ 5፥9