«በህልምም ተረድቶ ወደገሊላ ሀገር ሄደ፤……. ናዝሬት ወደምትባልም ከተማ መጥቶ ኖረ»

ሕዳር 6 ቀን እመቤታችን ጌታን ይዛ ከግብጽ /ከስደት/ ወደ ኢየሩሳሌም መመለሷ ይታሰባል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቀጥሎ ካለው የማቴዎስ ወንጌል ምንባብ በመነሳት ይህንን አስመልክቶ በማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜው ላይ ያስተማረውን ትምህርት እናቀርባለን፡፡
«ሄሮድስም ከሞተ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በግብጽ ለዮሴፍ በህልም ታይቶ የሕፃኑን ነፍስ የፈለጉት ሞተዋልና ተነሳ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ አለው፡፡ ዮሴፍም ተነስቶ ሕፃኑንና እናቱን በመያዝ ወደ እስራኤል ምድር ተመለሰ፤ ነገር ግን አርኬላዎስ በአባቱ ፈንታ በይሁዳ መንገሱን በሰማ ጊዜ ወደዚያ መሄድ ፈራ፤ በህልምም ተረድቶ ወደገሊላ ሀገር ሄደ፤ በነቢያት ናዝራዊ ይባላል የተባለው ይፈጸም ዘንድ ናዝሬት ወደምትባል ከተማ መጥቶ ኖረ» /ማቴ. 2-19-23/፡፡

ዮሴፍ የሕፃናቱ ገዳይ መሞቱን ሰምቶ ከስደት ተመልሶ ወደ ሀገሩ ተመልሶ መጣ፡፡ ነገር ግን ገና እግሩ ሀገሩን እንደረገጠ በድጋሚ የቀደመውን አደጋ ቅሪት /ተረፍ/ አገኘ፤ የክፉው ገዢ ልጅ ንጉስ ሆኗል፡፡

ሄሮድስ በንጉስነት የሚመራትን ሀገር /እስራኤልን/ ለሦስት ከፋፍሎ ሦስቱ ልጆቹ በእርሱ ስር ሆነው በሀገረ ገዢነት እንዲመሯት አድርጎ ነበር፡፡ እርሱ ከሞተ በኋላ ቆይተው እነዚህ ልጆቹ መንግስቱን ለሦስት ተካፍለውታል፡፡ የበላይ ንጉስም አልነበረም፡፡ አሁን ግን ሄሮድስ ገና መሞቱ ስለሆነ መንግስቱ ገና አልተከፋፈለምና ልጁ አርኬላዎስ ለጥቂቱ ለጊዜው መንግስቱን ተቀብሎ ንጉስ ሆነ፡፡

ዮሴፍ በአርኬላዎስ ምክንያት ይሁዳ መቀመጥ ከፈራ /ቤተልሔም የምትገኘው በይሁዳ ነው/ በወንድሙ በሄሮድስ አንቲጳስ ምክንያት ናዝሬት መቀመጥን ለምን አልፈራም? /ናዝሬት የምትገኘው የሄሮድስ አርኬላዎስ ወንድም ሄሮድስ በአንቲጳስ በሚገዛት በገሊላ ነው/ ይህ በቂ ምክንያት አይሆንም?

ቦታውን በመቀየር ጉዳዩ እንዲሸፈን፣ እንዲረሳ ለማድረግ ነው፡፡ ምክንያቱም ጥቃቱ / ግድያው/ ሙሉ በሙሉ የተካሄደው «በቤተልሔምና በአውራጃዋ» ነው /ማቴ. 2-6/፡፡ ስለዚህ ግድያው ከተፈፀመ በኋላ ወጣቱ አርኬላዎስ የሚያስበው ሁሉም እንደተፈፀመ እና እርሱም /ጌታም/ ከብዙዎቹ ሕፃናት ጋር አብሮ እንደተገደለ ነው፡፡

ስለዚህ ዮሴፍ ወደ ናዝሬት መጣ፡፡ በአንድ በኩል አደጋውን ለማስቀረት፤ በሌላ በኩል ደግሞ በቀድሞ /native/ ቦታው ለመኖር፡፡ ተጨማሪ ድፍረት እንዲሆነውም በጉዳዩ ላይ ከመልአኩ ምክር ተሰጠው፡፡ «በህልምም ተረድቶ ወደ ገሊላ ሀገር ሄደ»

ታዲያ ቅዱስ ሉቃስ ወደ ናዝሬት የሄዱት እንዲህ ባለ መልኩ ነው ለምን አላለም? ምክንያቱም ከጌታችን ልደት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሄዱ ከነገረን በኋላ እንዲህ ይላል፡፡ «በዚያም በእግዚአብሔር ሕግ የተጻፈውን ሁሉ ከፈጸሙ በኋላ ወደ ገሊላ ከተማቸው ወደ ናዝሬት ተመለሱ » /ሉቃ. 2-39/ ወደ ናዝሬት የሄዱት ከግብጽ ሲመለሱ መሆኑን አይነግረንምን?

ቅዱስ ሉቃስ እየተናገረ ያለው ወደ ግብጽ ከመውረዳቸው በፊት ካለው ጊዜ ነው፡፡ ምንም ነገር ከህጉ ውጭ እንዳይፈጸም ከጌታችን ልደት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ሄደው ሕጉ የሚያዘውን ሁሉ ፈጽመዋል፡፡

«እንደ ሙሴ ህግ የመንጻታቸው /ማለትም 40 ቀን/ በተፈጸመ ጊዜ በጌታ ሕግ የበኩር ልጅ ወንድ ልጅ ሁሉ ለጌታ የተቀደሰ ይባላል ተብሎ እንደተጻፈ፣ በጌታ ፊት ሊያቆሙት በጌታም ሕግ ሁለት ዋልያ ወይም ሁለት የርግብ ጫጩቶች እንደተባለ መስዋዕት ሊያቀርቡ ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዱት» /ሉቃ.2-21-24/ «ሁሉንም እንደህጋቸው ከፈፀሙ በኋላ ወደ ገሊላ ከተማቸው ወደ ናዝሬት ተመለሱ፡፡ /ሉቃ.1-39/ ጌታ «ኦሪትና ነቢያትን ልፈጽማቸው እንጂ ልሽራቸው አልመጣሁም» /ማቴ.5-17/ እዳለው፡፡ ይህ ከመደረጉ /ሕጉ ከመፈጸሙ/ በፊት ወደ ግብጽ እንዲወርዱ አልሆነም፡፡ ይህ እስኪሆን ተጠበቀ ከዚያ ወደ ናዝሬት ሄዱ፤ ከዚያ በኋላ ወደ ግብጽ እንዲወርዱ፡፡

ግብጽ ደርሰው ከመጡ በኋላ ግን ቅዱስ ማቴዎስ እንደተናገረ መልአኩ ወደ ናዝሬት እንዲወርዱ ያዘቸዋል፡፡ መጀመሪያ ወደ ናዝሬት የሄዱት ግን ትዕዛዝ ተሰጥቷቸው ሳይሆን ቅዱስ ሉቃስ እንዳለው የመኖሪያ ቦታቸው /ከተማቸው/ ስለነበረ ነው፡፡ ምክንያቱም ወደ ቤተልሔም የሄዱት ለሕዝብ ቆጠራው እንጂ እዚያ ለመቆየት አይደለም፡፡ ስለዚህ ቤተልሔም የሄዱበትን ምክንያት ሲፈጽሙ ወደ ናዝሬት ተመለሱ፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ወደ ናዝሬት የሄዱበትን ሌላም ምክንያት ይነግረናል፤ ትንቢት፡፡ «በነቢያት ልጄ ናዝራዊ ይባላል የተባለው ይፈጸም ዘንድ ናዝሬት ወደምትባል ከተማ መጥቶ ኖረ» /ማቴ.2-23/

ይህንን የተናገረው የትኛው ነቢይ ነው» አትጓጉ አትጨነቁም፡፡ ምክንያቱም ከትንቢት ጽሑፎች ብዙዎች ጠፍተው ነበርና፡፡ ይህንንም በመጽሐፈ ዜና መዋዕል ከተመዘገበው ታሪክ ማወቅ እንችላለን፡፡
«የቀረው ፊተኛውና ኋለኛው የሰሎሞን ነገር በነቢዩ በናታን ታሪክ በአኪያ ትንቢት ስለ ናባጥም ልጆች ስለ ኢዮርብዓም ባየው በባለ ራእዩ በኢዩኤል ራእይ የተጻፈ አይደለምን?» እነዚህ ሁሉ ተጽፈዋል የተባሉት ትንቢቶች ግን ዛሬ በእኛ ዘንድ አልደረሱም፡፡

ምክንያቱም አይሁድ ስለ መጻሕፍቱ ቸልተኛ ስለነበሩና በተደጋጋሚ ከአምልኮተ እግዚአብሔር ይወጡ ስለነበር አንዳንዶቹ ጠፍተው ነበር፡፡ ሌሎቹንም ራሳቸው አቃጥለዋቸው ቀዳደዋቸው ነበር፡፡ ሁለተኛው መቃጠላቸው እንደተፈፀመ ነቢዩ ኤርምያስ በትንቢት መጽሐፍ ይነግናል፤

«ንጉሱም /ሴዴቅያስም/ ክርታሱን /የነቢዩ የኤርምያስን ትንቢት የያዘ/ያወጣ ዘንድ ይሁዳን ላከ፤ እርሱም ከጸሐፊው ከኤሊሳማ ክፍል ወሰደው፡፡ ይሁዳም በንጉሱ አጠገብ በቆሙት አለቆች ሁሉ ፊት አነበበው፡፡ ንጉስም በክረምት በሚቀመጥበት ቤት ተቀምጦ ነበር፤ ከፊቱም እሳት ይነድድ ነበር፡፡ ይሁዳም ሦስትና አራት ዐምድ በአነበበ ቁጥር ንጉሱ በብርዕ መቁረጫ ቀደደው፡፡ ክርታሱንም በምድር ውስጥ ባለው እሳት ፈጽሞ እስኪቃጠል ድረስ በምድጃ ውስጥ ወደ አለው እሳት ጣለው፡፡» /ኤር.30-23/

የመጀመሪያውን /መጥፋታቸውን/ በተመለከተ ደግሞ የመጽሐፈ ነገሥት ፀሐፊ የኦሪት ዘዳግም መጽሐፍ አንድ ቦታ ተቀብሮ ተደብቆ ቆይቶ በችግር መገኘቱን ይነግረናል፡፡ «ታላቁ ካህን ኬልቅያስ ፀሐፊውን ሳፋንን የጠፋውን «የሕጉን መጽሐፍ በእግዚአብሔር ቤት አግኝቻለሁ» አለው»፡፡ /2ኛ ነገ.12-8/

ምንም ቀኝ ገዥ ባልነበረበት ጊዜ መጽሐፎቻቸው መጠበቅ እንዲህ ከከበዳቸው በግዞት ስር በነበሩባቸው ዘመናትማ የበለጠ ጥፋት ይኖራል፡፡

አንድ ነቢይ ይህንን ትንቢት በእርግጠኝነት እንደተናገረው ለማወቅ ግን ሐዋርያቱ በተለያየ ቦታ እርሱን ናዝራዊ ብለው መጥራታቸው ማስረጃ ነው፡፡

«ጴጥሮስም «ወርቅና ብር የለኝም፤ ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ፤ እነሆ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነስተህ ሂድ» አለው» /ሐዋ.3-6/

«እንግዲህ እናንተ ሁላችሁ የእስራኤልም ወገን ሁሉ በናዝሬቱ በኢየሱስ ስም ይህ ሰው እንደዳነና በፊታችሁ በእውነት እንደቆመ እወቁ» /ሐዋ.4-10/

ታዲያ ይህ ስለ ቤተልሔም የተነገረው ትንቢት ላይ ጥላ ማጥላት አይሆንምን? ሊባል ይችላል፡፡ ምክንያቱም ነቢዩ ሚኪያስ ክርስቶስ /መሲሕ/ ከቤተልሔም እንዲወጣ ተናግሯል፡፡ በፍጹም ምክንያቱም መጀመሪያ ነቢዩ ያለው «በቤተልሔም ይኖራል» ሳይሆን ከቤተልሔም ይወጣል» ነው፡፡
ጌታችን በናዝሬት መኖሩ ናዝራዊም መባሉ የሚያስተምረን ታላቅ ነገር አለ፡፡ ይህች ቦታ /ናዝሬት/ በጣም ዝቅተኛ ግምት የሚሰጣት ቦታ ነበረች፡፡ ለምሳሌ ናትናኤል «በውኑ ከናዝሬት ደግ ሰው ይወጣልን?» ብሎ ጠይቋል /ዮሐ. 1/ እንዲሁም የናዝሬት ከተማ ብቻ ሳትሆን አጠቃላይ የገሊላ አውራጃ የተናቀ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው ፈሪሳውያኑ «ከገሊላ ነቢይ እንደማይነሳ መርምርና እይ» /ዮሐ. 6-52/ ያሉት፡፡ እርሱ ግን ከእነዚህ ቦታዎች ወጣ መባልን አያፍርበትም ደቀ መዛሙርቱንም የመረጠው ከገሊላ ነው፡፡ ይህም ጽድቅን ገንዘብ ካደረግን /ከሰራን/ አፍአዊ /ውጫዊ/ የሆነ የክብርና የሞገስ ምንጭ እንደማያስፈልገን ለማሳየት ነው፡፡ በዚሁ ምክንያት ለራሱ ቤት እንኳን እንዲኖረው አልፈለገም፤ «የሰው ልጅ ግን አንገቱን የሚያስገባበት የለውም» ብሏል፤ ሄሮድስም በእርሱ ላይ ሴራ ሲጎነጉንበት ተሰዷል፤ ልደቱ በከብቶች በረት ሲሆን የተኛውም በግርግም ነው፤ እናቱ እንድትሆን የመረጠውም በዚህ ምድር መስፈርት ዝቅ ያለችውን ትንሽ ብላቴና ነው፤ ይህ ሁሉ እንዲህ ያሉ ነገሮችን እንደ መዋረድ እንዳንቆጥርና እያስተማረንና ራሳችንን ለመልካም ምግባር ብቻ እንድንሰጥ ግድ እያለን ነው፡፡

ስለዚህ በእነዚሁ ሁሉ ነገሮች «እኔ ለዓለሙ ሁሉ ባይተዋር እንድትሆኑ ሳዛችሁ እናንተ በተቃራኒው በሀገራችሁ፤ በወንዛችሁ በዘራችሁ፣ በአባቶቻችሁ የምትኮሩት ለምንድን ነው?» እያለን ነው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ምንም ምግባር ሳይኖራቸው በአባቶቻቸው ይመኩ የነበሩትን እንዲህ ብሏቸዋል «አብርሃም አባት አለን በማለት የምትድኑ አይምስላችሁ» /ማቴ.3-9/ ቅዱስ ጳውሎስም እንዲህ ይላል «ከእስራኤል የተወለደ ሁሉ እስራኤላዊ አይደለም፤ ከአብርሃም ዘርም ስለሆኑ ሁሉም ልጆች አይደሉም» /ሮሜ. 8-6-8/

እስኪ ንገሩኝ የሳሙኤል ልጆች እነርሱ የአባታቸውን የመልካም ምግባር ሕይወት ወራሾች ሳይሆኑ፤ በአባታቸው መልካምነት /ታላቅነት/ ምን ተጠቀሙ? የሙሴስ ልጆች የእርሱን ፍጹምነት ሳይደግሙ በእርሱ መልካምነት ብቻ ምን ተጠቀሙ? እነርሱ /የሙሴ ልጆች/ መንግስቱን አልወረሱም፤ ነገር ግን መሪ የነበረው ሙሴ አባታቸው ሁኖ ሳለ መንግስቱ የተላለፈው በምግባሩ የሙሴ ልጅ ለሆነው ለሌላው /ለኢያሱ/ ነው፡፡

ጢሞቲዎስስ የተወለደው ከግሪካዊ አባት መሆኑ /ዕብራዊ አለመሆኑ/ ምን ጎዳው) ወይም የኖህ ልጅ /ከነአን/ ባርያ ሆነ እንጂ በአባቱ መልካም ምግባር ምን ተጠቀመ? ኤሳውስ ቢሆን የያቆብ ልጅ አልነበረምን? አባቱስ በእርሱ ጎን አልነበረምን? አዎ አባቱ እርሱ በረከቱን እንዲቀበል ፈልጎ ነበር፤ እርሱ ለዚህ ብሎ አባቱ ያዘዘውን ሁሉ አድርጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ክፉ ስለነበረ እነዚህ ሁሉ ነገሮች አልጠቀሙትም፤ ቀድሞ የተወለደ  ቢሆንም፤ አባቱም በዚህ ረገድ ያሉትን ነገሮች ለማድረግ ከእርሱ ጋር ቢሆንም ፣ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ስላልነበር፣ ሁሉን ነገር አጣ፡፡

ስለ ሰዎች ብቻ ለምን እናገራለሁ አይሁድ የእግዚአብሔር ሕዝቦች /ልጆች/ ነበሩ፤ በዚህ ታላቅ ልደት ግን ምንም አልተጠቀሙም፡፡ እንግዲህ አንድ ሰው የእግዚአብሔር ልጅ ሁኖ ለዚህ የተከበረ ልደት የሚገባ መልካምነት ከሌላው የበለጠ የሚቀጣ ከሆነ ለምን የቅርብ እና የሩቅ አባቶቻችሁን እና አያቶቻችሁን ትቆጥራላችሁ»

ይህ የሚሆነው በብሉይ ኪዳን ብቻ ሳይሆን በሐዲስ ኪዳንም ነው፡፡ ያመኑና የተጠመቁ ሰዎች የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው፤ ነገር ግን ከእነዚህ መካከል ወደ እግዚአብሔር መንግስት የማይገቡ አሉ፡፡ እንግዲህ የእግዚአብሔር ልጅ መሆን እንኳን ያለ ምግባር ብቻውን የማይጠቅም ከሆነ፤ እንዴት ከሰዎች መወለድ ሊጠቅም ሊያኩራራ ይችላል? ስለዚህ ከታላላቅ ሰዎች በመወለድ በሃብት፣ በዘር፣ በሀገር ራሳችንን አናኩራራ፤ ይልቁንም እንዲህ የሚያደርጉትን እንገስጻቸው፡፡ በድሕነትና /ድሀ በመሆንና/ እነዚህን ነገሮች በማጣትም አንዘን፤ እነዚህ ነገሮች በእግዚአብሔር መንግስት አይጠቅሙንምና፤ ይልቁንም የመልካም ምግባር ባለሀብቶች ለመሆን እንጣር፤ . . . .

ምንጭ /Saint Jhon Chrysostome, homily 9 on the Gospel of St. Mathew/

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጉባኤው ባለ 26 ነጥብ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ አሳለፈ

ለቤተክርስቲያን ልማት የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ተሸለሙ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ 28ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ባለ 26 ነጥብ የጋራ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ በማቅረብ ተጠናቀቀ፡፡

ከጥቅምት 6-11 ቀን 2002 ዓ.ም ሲካሔድ የሰነበተው ይህ ስብሰባ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳዉሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት የዓለም ሃይማኖቶች የክብር ፕሬዚዳንት በሀገር ውስጥና በወጪ ሀገር የሚገኙ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የየአህጉረ ስብከቱ የሥራ ሓላፊዎች፣ የምእመናንና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በተገኙበት ነው፡፡

ጉባኤውን በጸሎት የከፈቱት ቅዱስነታቸው፤ የቤተክርስቲያን ዓላማ ሰላም በመሆኑ በሥልጡንና ሰላማዊ በሆነ መንገድ ጉባኤውን ማካሔድ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ «ሰላማዊ በሆነ መንገድ የሚካሔድ ውይይት የጎደለን ይሞላል የተጣመመን ያቃናል» ያሉት ቅዱስነታቸው «ቤተክርስቲያናችንን በልማቱ ለማሳደግ ጠንክሮ መሥራት ያስፈልጋል» በማለት ጉባኤውን አስጀምረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በ2001 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተክህነቱና በየአህጉረ ስብከቶች የተከናወኑትን ዐበይት ጉዳዮች የተመለከተውን ዘገባ በንባብ አሰምተዋል፡፡

ዘገባውን ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ በሐዋርያት ሥራ በጻፈው መልእክት /ም.5-42/ የጀመሩት ሥራ አስኪያጁ፤ ለቤተክርስቲያን የደም ሥር፣ ለምእመናን የጀርባ አጥንት የሆነው ስብከተ ወንጌልን በስፋትና በአግባቡ እንዲሰበክ፤ ምእመናን በእምነታቸው እንዲጸኑ፣ በሥነ ምግባር እንዲጎለብቱ፣ ከባዕድ ሃይማኖት ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን እንዲጠብቁ፣ ሰበካ ጉባኤያት እንዲስፋፉና እንዲጠናከሩ፣ የልማትና የምግባረ ሠናይ ሥራዎች እንዲሠሩ፣ ድህነትና ድንቁርና ከሕዝባችን ጫንቃ እንዲወርዱ ለማድረግ ሁሉም ጥረት ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው ዐቢይ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ዓመታዊ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዚህ ሁኔታ ሲካሔድ ሃያ ስምንተኛ ዓመቱን መያዙን የተናገሩት ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ «ጉባኤው ከወጣኒነት ወደ ፍጹምነት መሸጋገር እንደሚኖርበት የሁላችንም እምነት ነው፡፡» ብለዋል፡፡ ስለሆነም መለኪያው ከማእከል እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የሚቀርበው ዘገባና ውጤት ተኮር ሥራ ተሠርቶ ሲገኝ ብቻ መሆኑን አመልክተው፤ ይህ ካልሆነ ግን በየዓመቱ የሚደረገው ስብሰባ ልማዳዊ እንዳይሆን በብርቱ ማጤን እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

በመቀጠልም ሥራ አስኪያጁ ለግምገማና ለውይይት እንዲያመች ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ ከመንበረ ፓትርያርከ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ ከየአህጉረ ስብከቱ ጽ/ቤቶች በ2001 ዓ.ም የተከናወነውን የሥራ ክንውን ዘገባ አቅርበዋል፡፡

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤትን በተመለከተው ዘገባ ቅዱስ ፓትርያርኩ በሀገር ውስጥና በውጪ ሐዋርያዊ አገልግሎትና ልዩ ልዩ የሥራ ክንውኖችን ማድርጋቸውን አመልክቷል፡፡ ከነዚህ  ውስጥ ሐምሌ 22 ቀን 2000 ዓ.ም የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን የቅዱስ ላሊበላን ታሪካዊ መካናት እንዲጎበኙ መደረጉና በኋላም ከቅዱስ አባታችን ጋር ተወያይተው ለቤተክርስቲያናችን አድናቆት መቸራቸው ገልጸዋል፡፡ ነሔሴ 29 ቀን 2000 ዓ.ም ቅዱስ አባታችን የሀገሪቱ ፕሬዚዳንትና ልዩ ልዩ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር እንግዶች በተገኙበት ከጣሊያን መጥቶ አክሱም በቀድሞ ቦታው በተተከለው የአክሱም ሐውልት ሥነ ሥርዓት ላይ በክብር መገኘታቸው ተጠቅሷል፡፡

በመስከረም 13 ቀን 2001 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በናዝሬት ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን የተሠራውን ሕንፃ መመረቃቸው፣ መስከረም 24 ቀን 2001 ዓ.ም በምዕራብ ሸዋ አምቦ በጃን መንግሥት የተሠራውን ትምህርት ቤት ምረቃ ወቅት መገኘታቸውና መስከረም 16 ቀን 2001 ዓ.ም የሚከበረውን የመስቀል ደመራ በዓል በበለጠ ተጠናክሮ እንዲውል ጉዳዩ ለሚመለከተው አመራር መስጠታቸው በዘገባው ተመልክቷል፡፡

በቅዱስነታቸው ሰብሳቢነት የተመራው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ የተለያዩ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ እንዲያስተላልፍ ሁኔታዎች መመቻቸታቸው፣ በቅዱስነታቸው መመሪያ ሰጪነት ሸንኮራ ዮሐንስን ጨምሮ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙና አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናትና ቅዳሴ ቤት ተገኝተው እንዲከበር መደረጉ ተጠቅሷል፡፡

ልዑል አክሊለ ብርሃን መኮንን ኃይለ ሥላሴ የተባሉ በጎ አድራጊ ለቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ የሚውል አንድ ሚሊዮን፣ ለአክሱም ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተመጻሕፍት ወቤተመዘክር የሚውል አምስት መቶ ሺሕ ብር እርዳታ ሲለግሱ ቅዱስነታቸው በመገኘት ርዳታው ለተሰጣቸው ማስረከባቸው በልዩ ጽ/ቤቱ የተሠሩ ዐበይት ጉዳዮች መሆናቸው በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡

በውጪ ሀገርም በቅዱስነታቸው የተመረጡ ልዑካን ከኅዳር 5-16 ቀን 2001 ዓ.ም ድረስ ቦነስአይረስ በተካሔደው ዓለም አቀፍ ጉባኤ ላይ መሳተፍ፣ ከስብሰባው መልስም በሶርያ በመገኘት ከፕሬዝዳንቱ ዶ/ር በሽር አል አሳድ ጋር ስለ ዓለም ሰላም ጉዳይ መወያየታቸው፣ ከሶርያም ወደ ሊባኖስ በመጓዝ በቤሩት በሚገኙ ምእመናን የተገነባውን ቤተ ሳይዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በመገኘት ሕንፃውን ባርከው ቅዳሴ ቤት መክበሩ፤ እንዲሁም ወደ ግብጽ በማምራት ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ጋር በሁለቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መወያየታቸው በውጪው ዓለም ካከናወኑት ዐበይት ጉዳዮች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

ስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ በተመለከተ ዋና ሥራ አስኪያጁ ባቀረቡት ዘገባ፤ በዋናው መሥሪያ ቤት ያሉትን ሰባክያነ ወንጌልንና በሰዋሰው ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ፣ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በአዲስ አበባ የሚገኙትን ጨምሮ በማስተባበር በ26 አህጉረ ስብከት የስብከተ ወንጌል ሥምሪት መደረጉን አስታውቀዋል፡፡

ስበከተ ወንጌልን ይበልጥ ለማስፋፋት እንዲረዳ በደቡብ ኦሞ፣ በሽሬ፣ በደቡብ፣ በሰሜንና በምዕራብ ወሎ፣ በሶማሌ፣ በወላይታና በዳውሮ፣ በጉራጌ፣ በምሥራቅ ሐረርጌ፣ በአዲግራት፣ አክሱም፣ በአፋርና በምሥራቅ ጎጃም አህጉረ ስብከት 1ሺሕ228 ያህል ሰባክያነ ወንጌል መመደባቸውንም ሥራ አስኪያጁ አብራርተዋል፡፡

ገቢና ወጪን አስመልክቶ ከቁልቢ ንዋየ ቅድሳት ማደራጃ ከስብከተ ወንጌል ጉባኤ አንድ በመቶ አስተዋጽኦና ከመጽሔት ሽያጭ 238¸616.77 ገቢ ሲሆን ጠቅላላ ወጪው ደግሞ 238¸325.52 መሆኑን ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ አመልክተዋል፡፡

በሊቃውንት ጉባኤ በኩል በ2001 ዓ.ም ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ ከአምስት የቤተክርስቲያናችን ክፍሎች፣ ከተወካዮች ምክር ቤት እና ከልዩ ልዩ ድርጅቶች፣ ከአራት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትና አምስት ግለሰቦች የተዘጋጁ በድምሩ 192 የሆኑ በጥልቅ ታይተው እንዲታረሙ የተላኩትን ታላላቅ መጻሕፍት፣ መለስተኛ ጽሑፎችንና ጥያቄዎች ተመ ልክቶ ከአስተያየት ጋር ወደ በላይ አካል መመለሱን እንዲሁም ተጠቃሎ እንዲታተም የተጀመረውን የግእዝ መጽሐፍ ቅዱስ እያመሳከረ በመጀመሪያ የማጣራት ሥራ ላይ እንደ ሚገኝም ሥራ አስኪያጁ አስረድተዋል፡፡

ትምህርትና ማሠልጠኛን በተመለከተ ለ22 አህጉረ ስብከት አብነት ትምህርት ቤቶች አንድ ሚሊዮን 69 ሺሕ ብር፣ ለ14 አህጉረ ስብከት ንባብና ቅዳሴ ቤት 260 ሺሕ ብር፣ ለ21 አህጉረ ስብከት ካህናት ማሰልጠኛ 750 ሺሕ ብር በድምሩ 2 ሚሊዮን 79 ሺሕ ብር መላኩን ገልጸዋል፡፡

በጀትና ሒሳብን አስመልክተው ባቀረቡት ዘገባ ከቤተክርስቲያኒቱ የገቢ ርዕሶች 48 ሚሊዮን 631 ሺሕ 40 ብር ለማስገባት ታቅዶ 45 ሚሊዮን 711 ሺሕ 685 ብር ብቻ እንደተገኘና ከዚህም ውስጥ 39 ሚሊዮን 566 ሺሕ 487 ብር ወጪ ሆኖ በሥራ ላይ እንደዋለ አስረድ ተዋል፡፡

ጠቅላይ ቤተክህነቱ በስድስት መምሪያዎች እና በ10 የጠቅላይ ቤተክህነቱ ድርጅቶች፣ አራት አህጉረ ስብከቶችና የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሒሳብ ተመርምሮ 387 ሚሊዮን 431 ሺሕ 782 ብር ገቢ፣ 344 ሚሊዮን 674 ሺሕ 313 ወጪ ሲሆን አራት ሺሕ 496 ብር ጉድለት መገኘቱን ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ በዘገባቸው አመልክተዋል፡፡

በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ በኩል በ 2001 ዓ.ም ያሬዳዊ ዜማ የካሴትና የመጽሔት ሥርጭትን በተመለከተ ወጥ የሆነ ያሬዳዊ መዝሙር እንዲዘመር ጥረትና እንቅስቃሴ መደረጉን፣ ሐምሌ 5 ቀን 2000 ዓ.ም የተከበረውን የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ 16ኛ ዓመት በዓለ ሲመት ወጣቶችን የማስተባበር ሥራ መሠራቱን፣ ከነሐሴ 1-16 ቀን 2000 ዓ.ም ድረስ በጾመ ፍልሰታ ለማርያም ሱባኤ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በየአብያተ ክርስቲያናቱ በመገኘት ተገቢውን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲሰጡ በመምሪያው በኩል ትእዛዝ መተላለፉን ዘገባው አመልክቷል፡፡

በተጨማሪም ማደራጃ መምሪያው መስከረም 1 ቀን 2001 ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓልን አስመልክቶ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የእንኳን አደረሰዎ በዓል ላይ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት አገልግሎት እንዲሰጡ መመሪያ ማስተላለፉንና፣ የመስቀል ደመራ በዓል በደማቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዐት እንዲከበር የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትን በማሠልጠን የሚጠበቀውን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲያበረክቱ ማድረጉን ሥራ አስኪያጁ ጠቁመዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን በኩል ደግሞ በዋናው ማዕከል አማካኝነት ብቻ ለ22 ሕዝባዊ ጉባኤያት፣ በዐሥር የተለያዩ የወረዳ ከተሞች ሐዋርያዊ ጉዞ መደረጉን፣ ስብከተ ወንጌል ካልደረሰባቸው ጠረፋማ አህጉረ ስብከት ለተውጣጡ 40 ወጣቶችና በዝዋይና በጅማ ካህናት ማሠልጠኛ 135 ልዑካን ሥልጠና መስጠቱን፣ ትምህርተ ሃይማኖት እና መንፈሳዊ መልእክት የያዙ 325 ሺሕ የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 225 ሺሕ ሐመር መጽሔትና ሰባት ሺሕ ልዩ እትም ሐመረ ተዋሕዶ በ2001 ዓ.ም ማኅበሩ ማሰራጨቱን ሥራ አስኪያጁ በዘገባቸው ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም ማኅበሩ ልዩ ልዩ የቤተክርስቲያን ትምህርት የያዙ ዘጠኝ መጻሕፍትን በአማርኛና ኦሮምኛ ቋንቋዎች አሳትሞ ከ 57 ሺሕ ቅጂዎች በላይ ማሠራጨቱን፣ በድምፅና በምስል ልዩ ልዩ ወቅታዊነት ያላቸውን ጽሑፎች በአማርኛና በእንግሊዚኛ ቋንቋዎች በዌብሳይቱ /መካነ ድሩ/ ማስተላለፉን፣ በሀገር ውስጥ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተከታታይ ትምህርትና ሥልጠና መስጠቱ፣ ለአብነት ትምህርት ቤቶች 300 ደቀመዛሙርት የመሠረታዊ ትምህርትና የስብከት ዘዴ፣ በአፍሪካ፤ በግብጽ፣ በኬንያና በአውሮፓ 11 ከተሞች መምህራንን ልኮ ሐዋርያዊ አገልግሎት መስጠቱን የሥራ አስኪያጁ ዘገባ አመልክቷል፡፡

እንዲሁም ለአብነት ትምህርት ቤቶች ደቀመዛሙርት፣ ለንዋየ ቅድሳትና ለአህጉረ ስብከት ድጋፍ፣ ለቅኔ ትምህርት ማስተዋወቅ፣ በተለያዩ አህጉረ ስብከት ርክክብ ለተደረገባቸው ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያና ገና እየተሠሩ ላሉ ፕሮጀክቶች፣ ለአብያተ ክርስቲያናት በነፃ ለተሠሩ የአሠራር ንድፎች /ዲዛይኖች/ በጠቅላላ ከብር 2 ሚሊዮን 760 ሺሕ 186 በላይ ወጪ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡

በቅርሳ ቅርስ ምዝገባና ጥበቃ በኩልም በበጀት ዓመቱ ብዙ ጥረት መደረጉን በዘገባቸው ያመለከቱት ሥራ አስኪያጁ በቅርሳቅርስ ቀላጤዎች ተሰርቀው የነበሩ መጻሕፍትንና ንዋየ ቅድሳትን ለማስመለስ በተደረገ ጥረት 22 ጥንታውያን መጻሕፍትን፣ 10 የተለያዩ ንዋያተ ቅዱሳትንና ሁለት ጽላቶችን ለማስመለስ መቻሉን አስረድተዋል፡፡

ግምታቸው 223 ሺሕ 780 ብር የሆኑ ባለሥዕል የብራና ተአምረ ኢየሱስ፣ አንድ የብራና ተአምረ ማርያምና አንድ ድርሳነ ሚካኤል መጽሐፍ በፖሊስ ጣቢያ በኤግዚቢት ተይዘው በምርመራ ላይ ስለሆኑ ቅርሶቹ ወደቦታቸው እንዲመለሱም ክትትል እየተደረገ መሆኑን ዘገባው አመልክቷል፡፡

ዋና ሥራ አስኪያጁ የዋናውንና የየአህጉረ ስብከቶቹን የሥራ እንቅስቃሴ በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን በመ ምሪያዎች፣ በድርጅቶችና በ45 አህጉረ ስብከት አሉ ያሏቸውንም ችግሮች ገልጸዋል፡፡

ካጋጠሙ ችግሮች መካከል በጠቅላይ ቤተክህነቱ ያለው የገንዘብ ወጪ ጫና፣ ከየአህጉረ ስብከቱ ለሚዘዋወሩ ሠራተኞች ደሞዝ ከጠቅላይ ቤተክህነት መከፈሉ፣ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚመረቁ ደቀ መዛሙርት የሚመደበው አዲስ በጀትና የተቋማቱ የውስጥ ገቢ አለመፍጠር፣ ከበጀት ውጪ የሚቀርበው የገንዘብ ጥያቄና ከበቂ በላይ ሠራተኞች እያሉ ተጨማሪ ሠራተኞች ያለ ሥራ መመደብና መቅጠር ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በተጨማሪም ወደ ውጪ ሀገርና ሀገር ውስጥም ለአገልግሎት የሚመደቡና የሚላኩትም ወጪያቸው ከዚያው እንዲሸፈን አለመደ ረጉ ይገኙበታል፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤን የ 27 ዓመት ጉዞን የሚያሳይ ዐውደ ርእይ የቀረበ ሲሆን ዐውደ ርእዩም በቅዱስ ፓትርያርኩና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ተባርኮ ተከፍቷል፡፡ ዓውደ ርእዩ ከጥቅምት 6-15 ቀን 2002 ዓ.ም ለዘጠኝ ቀናት ለሕዝብ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡ ዓውደ ርእዩን የተመለከቱት ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት የቤተክርስቲያኒቱን ታላቅ ጉባኤ የሚያመለክት በመሆኑ ተጨማሪ የመጎብኛ ጊዜያት እንዲሰጡ ጠይቀዋል፡፡

በስብሰባው ማጠናቀቂያ ላይ ከቤተክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ጎን ለጎን አገልግሎቷን ለማቀላጠፍ በልማቱ ዘርፍ የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ሀገረ ስብከቶችና አብያተ ክርስቲያናት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ ለተመረጡት አብያተ ክርስቲያናት ሽልማት የሰጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እንደተናገሩት፤ ቤተ ክርስቲያን በልማቱ ዘርፍ በማሳተፍ ለሀገር ዕድገት የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ነው፡፡

ይህንንም አስተዋጽኦ የበለጠ አጠናክራ እንደምትቀጥል ቅዱስነታቸው ተናግረዋል፡፡ በሠሩት የልማት ሥራ ለሽልማት የበቁት አብያተ ክርስቲያናት የተመረጡት ከመላው ሀገሪቱ ሲሆን አህጉረ ስብከቶቹና የሰበካ ጉባኤ አባላቱ ልማቱን የበለጠ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጄኔሬተር፣ የውኃ ¬ምፕና ኮሚፒዩተር መሸለማቸው ታውቋል፡፡

ለሽልማት ከበቁት ውስጥ የባሌ፣ የሰሜን ሸዋ፣ የምሥራቅ ሸዋና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ይገኙበታል፡፡

ጉባኤው ሲጠናቀቅም የጉባኤውን ሒደት በቅደም ተከተል እንዲካሔድ የተሰየመው የቃለ ጉባኤ አርቃቂ ኮሚቴ ባለ 26 ነጥብ ያለው የጋራ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ አቅርቧል፡፡

ኮሚቴው ባቀረበው የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ እንዳመለከተው ቅዱስነታቸው በጉባኤው መክፈቻ ላይ የሰጡት የሥራ መመሪያና በተለይ በሀገራችን ሊከናወን ስለሚገባው ልማታዊ ሥራ፣ ለዚህ ተግባራዊነትም ሊኖር ስለሚገባው ሰላም አስመልክቶ ያስተላለፉት መልእክት ጉባኤው በአድናቆትና ከልብ እንደተቀበለውና ለተግባራዊነቱም እንደሚሠራ ገልጸዋል፡፡

ቅዱስነታቸው በተገኙበት ከየካቲት 9-10 ቀን 2001 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ የስብከተ ወንጌል አስተባባሪነት የተካሔደው ዓውደ ጥናት ጠቃሚ ትምህርት የተገኘበት፣ ነፃና ግልጽ በሆነ መንገድ ውይይት የተደረገበትና ተሳታፊዎቹን የበለጠ ለሥራ ያተጋ በመሆኑ ሊበረታታ የሚገባው ጉዳይ መሆኑን የአቋም መግለጫው አመልክቶ መምሪያው በ2002 ዓ.ም ያቀረበው ዕቅድ ተግባራዊ እንዲሆን ጉባኤው መጠየቁን አመልክቷል፡፡

ከጣና ቂርቆስ ገዳም ወደ ፈረንሳይ ተወስዶ በሪስ ሙዚየም ለብዙ ዓመታት የቆየው ቅዱስ መስቀል በቅዱስ ፓትርያርኩ ጥረት ግንቦት 28 ቀን 2001 ዓ.ም መመለሱን ጉባኤው አድንቆና ምስጋና አቅርቦ በቀጣይም በባዕድ ሀገር የሚገኙ ቅርሶችን ወደ ሀገር ቤት ለማስመለስ የሚደረገው ጥረት እንዲጠናከር ጠይቋል፡፡

በአንዳንድ አህጉረ ስብከት ያለው የአብነት ትምህርት ቤት መዳከም ምክንያቱ የአብነት ትምህርት ቤቶች በብዛት የሚገኙት በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል መሆኑን የጠቆመው የአቋም መግለጫው ለነዚህም በቂ በጀት አለመመደቡ ይልቁንም በአብዛኛው አህጉረ ስብከት ትምህርት ቤቶች አለመኖራቸው ባሉበትም ቢሆን የሚ ሰጠው ትምህርት ወቅታዊና ዘመናው በሆነ መልኩ ሊካሔድ አለመቻሉን ጉባኤው ግንዛቤ መውሰዱን አመል ክቷል፡፡

ለዚህም በምክንያት የሚጠቀሰው ትምህርትና ማሠልጠኛ መምሪያ በበቂ የሰውና የገንዘብ ኃይል ያልተደራጀ መሆኑ ግንዛቤ መያዙን ኮሚቴው አመልክቶ፤ በዚህ መሠረታዊ በሆነ የቤተክርስቲያን ጉዳይ ላይ ቅዱስ ሲኖዶስ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ጉባኤው ማሳሰቡን አስረድቷል፡፡

የነገይቱን ቤተክርስቲያን የሚረከቡና ዛሬም የቤተክርስቲያን ውበት የሆኑት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ወጣቶችን በመንከባከብ፣ በማስተማርና ከጠላት ወረራ እንደጠበቁ ለማድረግ፣ ከአባቶች የተማሩትን ንጹሕ ትምህርት ለፍሬ እንዲያበቁ በየአጥቢያ ቤተክርስቲያኑ የሚገኙትን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሁሉ ለማስተማር ያሉትን እያጠናከርን ባልተቋቋመባቸው አብያተ ክርስቲያናትም ለማቋቋም ጥረቱ እንደሚቀጥል የአቋም መግለጫው አመልክቷል፡፡

በበጀት ዓመቱም በተከናወኑ የልማት ሥራዎች በማኅበረ ቅዱሳን በኩል በየአህጉረ ስብከቱ በሚገኙ ወረዳዎችና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ለልማት ሥራ የሚውል የገንዘብ ድጋፍ መደረጉን በጥንታዊ ትምህርት ቤቶችና በሐዋርያዊ አገልግሎት ተዛማጅ ሥራዎች እንደተከናወኑ ከዘገባው መገንዘቡን በአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ ተጠቁሟል፡፡

በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያን ባደረገው እገዛ ጉባኤው እያመሰገነ ወደፊትም ማእከላዊ አሠራርን በጠበቀ መልኩ ማኅበሩ እገዛውን እንዲቀጥል ጉባኤው ማሳሰቡን መግለጫው አስረድቷል፡፡

ኮሚቴው ባቀረበው ባለ 26 ነጥብ የአቋም መግለጫ ሕጋዊ ባልሆኑና ባልተፈቀደላቸው ሰባክያን በየመንደሩም ሆነ በየአብያተ ክርስቲያናቱ የሚካሔዱ ስብከቶች ማዕከላዊ አሠራርን ያልተከተሉ መሆናቸውን፣ በውጪው ዓለም ባለው መለያየት ጉባኤው እንደሚያዝንና በተለይ በሰሜን ምዕራብና ካሊፎርኒያ ሀገረ ስብከት የቀረበው ዘገባ አባቶችን ለማቀራረብ እየተደረገ ያለውን ጥረት እንደሚያደንቁና ጉባኤውም ሰላም እንዲገኝ ሙሉ ድጋፍ እንዳለው በአቋም መግለጫው ተገልጿል፡፡

ማኅበሩ የደብረ ጽጌ ገዳም የአብነት ትምህርት ቤትን በ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ለማደስና ለማስፋፋት ስምምነት ተፈራረመ

በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ፍቺ ሀገረ ስብከት የሚገኘው ደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም አንድነት ገዳም የአብነት ትምህርት ቤትን ለማጠናከር በማኅበረ ቅዱሳንና በሀገር ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የአንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ብር የፕሮጀክት ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ጥቅምት 1 ቀን 2002 ዓ.ም ወደ ስፈራው በተደረገው ሐዋርያዊ ጉዞ ወቅት በማኅበረ ቅዱሳን የፍቺ ማዕከልና የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቆስጦስ የተከናወነው ይኸው የፕሮጀክት ስምምነት አንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ብር የሚፈጅ ሲሆን፤ ፕሮጀክቱ ከ3-4 ዓመታት ባለው ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል፡፡

በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ወቅት በማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ አገልግሎት ልማት ዋና ክፍል የቅስቀሳና ገቢ አሰባሰብ ሓላፊ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት እንደገለጹት፤ ይኸው የስምምነት ሰነድ የተዘጋጀው ማኅበሩ በነዚህ ዓመታት በአቅም እጥረትና በእርጅና ምክንያት ሳይታደስ በመፈራረስ ላይ የሚገኘውን የአብነት ትምህርት ቤት ለማጠናከር፣ ሦስት አዲስ ቤት ለመገንባት እና ሰባት የጥገና ማስፋፋት ለማካሄድ ነው፡፡

የፕሮጀክቱ አጠቃላይ ወጪ የማኅበሩን የሞያ አገልግሎት እንደማያካትት የገለጹት ወ/ሮ ዓለምፀሐይ፤ እግዚአብሔር ፈቅዶ ፕሮጀክቱን በወቅቱ ለማጠናቀቅ ጥረት እንደሚደረግ አስታወቀዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቆስጦስ በዚህ ወቅት እንደ ተናገሩት የቤተክርስቲያኒቱ የነገ ተስፋ የሚፈሩበት ይህ የአብነት ት/ቤት ፈርሶ ቢቀር ከፍተኛ ሐዘን ይሰማቸው እንደነበር ጠቅሰው፤ ማኅበሩ ይህን በማሰብ ያከናወነው ተግባር የሚያሰመሰግነው መሆኑን ተናግርዋል፡፡

ለፕሮጀክቱ ተግባራዊነት በዋናነት በሓላፊነት እንደሚንቀሳቀሱና ለግንባታውም ባላቸው አቅም በገንዘብ እንደሚራዱ የጠቀሱት ብፁዕነታቸው፤ ምእመናን በሥራው እገዛ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ወደ ማኅበረ ምእመናን እያደገ እንደሚገኝም ገልጸዋል ከፕሮጀክቱ ስምምነቱ በተጨማሪም ማኅበሩ ከምእመናን ያሰባሰበውን 13 ሺሕ 200 ብር ግምት ያላቸው 108 መንፈሳ ውያን መጻሕፍት፣ መጽሔትና ጋዜጦች ለገዳሙ  የአብነት ት/ቤት በስ ጦታ አበርክተዋል፡፡

ከዛሬ 50 ዓመታት በፊት የተቋቋሙ ይኸው የአብነት ት/ቤት የተመሠረተው በብፁዕ አቡነ ባስልዮስ መሆኑ በፕሮጀክት ስምምነቱ ወቅት ተጠቁሟል፡፡

በእንግድነት የተገኙት የታዕካ ነገሥት ባዕታ ለማርያም ገዳም እና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ስምኦን እና የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ በበኩላቸው ባስተላለፉት መልእክት፣ ነገ የቅድስት ቤተክርስቲያንን አገልጋይ መፍለቂያ የሚሆኑት የአብነት ት/ቤቶ ችን ለማጠናከር እየተደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ እነርሱም በየግላቸው የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንደሚያደረጉ ቃል ገብተዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ዳንኤል ተስፋዬ በበኩላቸው ማኅበሩ ገዳማትና አድባራትን በመደገፍ እንዲሁም የአብነት ት/ቤቶችን ከማጠናከር በተጨማሪ በርካታ ማኅበራዊና መንፈሳዊ አገልግሎቶችን እየሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በርካታ የአብነት ት/ቤቶች እየተዳከሙ እንደሚገኙ የገለጹት ዋና ጸሐፊው ይህን ችግር ለመቅረፍ ማኅበሩ በጎ አድራጊ ግለሰቦችንና ማኅበራትን እንዲሁም ምእመናንን በማስተባበር ፕሮጀክት ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

በዚህ መንፈሳዊ ጉብኝት እና የፕሮጀክት ስምምነት ወቅት ከ300 በላይ የበጎ አድራጊ ግለሰቦች እና የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች የተገኙ ሲሆን የአብነት ት/ቤቶችን ለማጠናከር በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከማኅበረ ቅዱሳን ጎን እንደሚቆሙ ቃል ገብተዋል፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መጠናከር የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት መሠረት ነው

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስተያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት፣ አገልጋዮቿን መዝግባ ይዛ ሥምሪት እና ምደባ ለመስጠት፣ ችሎታቸውንና ኑሮአቸውን ለማሻሻል፣ ምእመናንን ለማብዛትና በመንፈሳዊ እውቀት ጎልምሰው፣ በምግባርና በሃይማኖት ጸንተው እንዲኖሩ ለማድረግ፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደር ለማሻሻልና በሚያስፈልጋት ማንኛውም ጉዳይ ራሷን ለማስቻል ከአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ጀምሮ እስከ መንበረ ፓትርያርክ ድረስ በየደረጃው የሚቋቋም የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መዋቅርና አሠራር በቃለ ዓዋዲው መሠረት ዘርግታ ትገኛለች፡፡
የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች በሕዝብ በሚመረጡ ካህናት፣ ምእመናን እና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ተሳትፎ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋትና አስፈላጊ የሆነውን አቅም ለማጐልበት የሚመክርባቸው፣ የሥራ ክንዋኔዎችና ችግሮች እየቀረቡ የሚገመገሙባቸውና ልምዶች የሚወስዱባቸው፣ ቀጣይ አቅጣጫዎችም እግዚአብሔር ቢፈቅድ በሚል የሚታይባቸው በመሆናቸው፤ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መዋቅር ለቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት መስፋፋት ወሳኝነት ያለው ነው፡፡

ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን በዓለም ላይ በሚገኙ በአኀት አብያተ ክርስቲያናትም በእንግሊዘኛው አጠራር /ሪሽ ካውንስል/ በሚል ስያሜ እየተሠራበት የሚገኝ ዘመናዊ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅር ነው፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ /ሪሽ ካውንስል/ መዋቅርና አሠራር ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጦች በምእመናን ላይ የሚያስከትሉትን ተጽዕኖና መልካም አጋጣሚ ባገናዘበ ሁኔታ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስፋፋትና ለዚህም የሚያስፈልገውን ዐቅም መፍጠርና ማጠናከር፣ የምእመናን ችግር መፍቻ እንዲሆኑ ለማድረግ አብያተ ክርስቲያናት፡- አካባቢያዊ እና የምእመናንን አኗኗር ሁኔታዎች እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን ማድረግ የሚገባትን ዘመኑን የዋጀ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ /ሪሽ ካውንስል/ መዋቅርና አሠራር ለመዘርጋት ተጨባጭና ነባራዊ ሁኔታዎችን የተከተሉ የሕግና የመዋቅር ማሻሻያዎችን ያደርጋሉ፡፡ የአሠራር ስልቶችን በየጊዜው ያዳብራሉ፡፡

ከዚህ አኳያም በ1991 ዓ.ም ለሦስተኛ ጊዜ ተሻሽሎ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰበካ መንፈሳዊ ደንብ /ቃለ ዓዋዲ/ አንቀጽ 61  /2/ /ሀ/ ላይ የሰበካ ጉባኤ የሚኖረውን የምእመናን ድርሻ በተመለከተ፡- «የሰበካ ምእመናን በገንዘብ አስተዋጽኦ፣ በአስተዳደር፣ በትምህርት፣ በልማትና በማኅበራዊ ኑሮ አገልግሎት በጠቅላላው በሀብት፣ በዕውቀትና በጉልበት በመረዳት በሰበካው ልዩ ልዩ የክፍል ሥራዎች ውስጥ በመሳተፍ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል ክርስቲያናዊ ግዴታቸው ነው፡፡» በማለት በተደነገገው መሠረት ምእመናን ለቤተ ክርስቲያናቸው የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት ሲሰጡ ለሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓላማ መሳካት ትልቅ ድርሻ ያለው ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ደንብ /ቃለ ዓዋዲ/ መሠረት በአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የሚከተሉት ክፍሎች ይኖራሉ፡-

ሀ/ የስብከተ ወንጌል ክፍል
ለ/ የመንፈሳዊ ትምህርት ክፍል
ሐ/ የካህናት አገልግሎት ክፍል
መ/ የሰንበት ት/ቤት ክፍል
ሠ/ የእቅድና ልማት ክፍል
ረ/ የምግባረ ሠናይ /በጐ አድራገት/ ክፍል
ሰ/ የሕግና ሥነ ሥርዓት ክፍል
ሸ/ የንብረት፣ የዕቃ ግምጃ ቤትና የታሪካዊ ቅርስ ክፍል
ቀ/ የሒሳብ ክፍል
በ/ የገንዘብ ቤት
ተ/ የቁጥጥር ክፍል
ቸ/ የሕንፃ ሥራ፣ እድሳትና ጥገና ክፍል
ኀ/ የስታቲስቲክስ ክፍል

በሚል የተዋቀሩ የሥራ ክፍሎች ያሉት ሆኖ ምእመናን በችሎታቸው በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መሳተፍ እንዲችሉ የሚያደርግ ሲሆን ዳር ቁመን የምንመለከተው ወይም እገሌ ይሠራዋል፤ በሚል ልንሸሸው የማይገባ፣ ተሳታፊ በመሆን በረከት የምናገኝበት እና የቤተ ክርስቲያን ችግር የሚቀረፍበት መዋቅር ነው፡፡

በመሆኑም በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ደንብ መሠረት የሚጠበቅብንን  የድርሻችንን ካልተወጣንና ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅመውን በወቅቱ ካላደረግን ደንቡና መዋቅሩ ብቻውን ትርጉም ሊኖረው ስለማይችል በተሰጠን ጸጋ ልናገለግል ይገባል፡፡ እግዚአብሔርም ከእኛ ብዙ ይጠብቃል፡፡ የተቀበልነው መክሊት ነውና በተሰጠን መጠን ይፈለግብናል /ማቴ. 25-14-30/፡፡

በጉባኤ ደረጃ ያለውን ኃላፊነት ስንመለከት የአጥቢያ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፤ የአጥቢያው ካህናት፣ ምእመናን እና የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች የሚሳተፉበት በዓመት ሁለት ጊዜ የሚካሄድ ጠቅላላ ጉባኤ ያለው ሲሆን፤ የወረዳ፣ የሀገረ ስብከት እና የመንበረ ¬ፓትርያርክ ሰበካ ጉባኤዎችም በየደረጃቸው በዓመት አንድ ጊዜ በመሰብሰብ አፈጻጸማቸውን በማቅረብ ውይይት የሚያደርጉባቸው የሰበካ መንፈሳዊ ጠቅላላ ጉባኤዎች የሏቸው ስለሆነ፤ እኒህ በተለያየ ደረጃ የሚደረጉት ጠቅላላ ጉባኤዎች የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ ለማድረግ ቅድመ ዝግጅት እና ከጉባኤዎቹ በኋላም ቢሆን ክትትል ማድረግን የሚሹ ናቸው፡፡

በዚህም መሠረት የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎችን በማጠናከር የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት ከቀደምት ተሞክሮዎች አንፃር

ምእመናን፣ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማገዝ በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ድርሻ ስላላቸው፡- በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በመምረጥና በመመረጥ ቢሳተፉና የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያቸውን በገንዘባቸው፤ በሙያቸው እና በጉልበታቸው ቢያገለግሉና ሌሎች ምዕመናንን የቤተ ክርስተያንን ችግር ለመቅረፍ የሰበካ ጉባኤ ተሳትፎ ወሳኝ እንደሆነ አጽንኦት ቢሰጡ፤

በቃለ ዓዋዲው የተገለጸው እንደተጠበቀ ሆኖ በየደረጃው ለሚገኙ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች ችግር ፈቺ  የሆነ፣ ዘመኑን የሚዋጅ ስትራተጂክ እቅድ እንዲወጣላቸው እና ከጉባኤዎቹ ስብሰባ በፊትና በኋላ አፈጻጸሙ ጽኑ ክትትል የሚደረግበት ሁኔታ ቢጠናከር፤

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያት የእስካሁን አፈጻጸም ምን እንደሚመስል እና በቀጣይ መሻሻል የሚገባቸው አሠራሮች ምን እንደሆኑ የሚያወያዩ ጥናት በየደረጃው እንዲቀርብ ቢደረግ፤

የሰበካ መንፈሳዊ አጠቃላይ ጉባኤያት የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ ለማድረግ ጉባኤዎቹ ሪፖርቶች ማዳመጥ ብቻ ሳይሆን ችግር ፈቺ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የጠነከረ ውይይት ሊያደርጉ ስለሚችሉበት ሁኔታ በሁሉም ደረጃዎች ወጥነት እንዲኖረው ቢደረግ፤

በሰበካ መንፈሳዊ ጠቅላላ ጉባያት የሚወሰኑ ጉዳዮች ጊዜ በማይወሰድ ሁኔታ ታች በየደረጃው ለሚገኙ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያት ለአፈጻጸም እና ለግንዛቤ እንዲደርሱ አሠራሩ የተጠናከረ እንዲሆን ቢደረግ፤ እና በአንዳንድ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች የሚፈጠሩ አለመግባባቶችን አጣርቶ የመፍትሔ እና የውሳኔ ሐሳብ የሚያቀርብ ትጉህ እና ለችግሮች ገለልተኛ የሆነ ምእመናን የሚሳተፉበት አሠራር መዋቅራዊ እንዲሆን ቢደረግ፤

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤን ዓላማና ተግባር ለማሳካት አስተዋጽኦ ስለሚኖረው፤ ያልፈጸምነውን አጉልተን በማየት፣ ቅድመ ዝግጅት እና ተሳትፎ በማድረግ የሚጠበቅብንን ልንወጣ ይገባል፡

እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን – ራዕ. 2.10

በዲ. ኤፍሬም ውበት

 
 
ክርስትና በእምነት እያደጉ እና እየጠነከሩ ዘወትር የሚጎለብቱበት ሕይወት ነው፡፡ በመሆኑም አንድ ክርስቲያን ከትናንት ዛሬ ከአምና ዘንድሮ አድጎና ጠንክሮ መገኘት አለበት፡፡ «ንቁ በሃይማኖት ቁሙ ጎልምሱ ጠንክሩ» እንደተባለ በጊዜውም /በተመቸ ጊዜ/ ያለጊዜውም/ባልተመቸ ጊዜም/ በእምነት ጸንቶ ለመገኘትና እስከ ሞት ድረስ ለመታመን የግድ በእምነት አድጎና ጠንክሮ መገኘት ያስፈልጋል፡፡ /1ቆሮ.6.13ጠ14/፡፡ እምነትን በምግባርና በትሩፋት ለመግለጽም ራስን በመካድ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ይገባል፡፡ ለዚህም መከራን እየታገሱ ራስን ከዓለም መለየት ይገባል፡፡ በዚህ ዓይነት ፈቃደ ሥጋውን ለፈቃደ ነፍሱ በማስገዛት በእምነቱ የጠነከረ ሰው ከማናቸውም ነገር ይልቅ መንግሥቱንና ጽድቁን ያስቀድማል፡፡ /ማቴ.6.13/፡፡ ይህም ማለት ሃይማኖትን ከምግባር አዋሕዶ ልጅነቱን አጽንቶ ጽድቅ የሚገኝበትን ሀገር መንግሥተ ሰማያትን ተስፋ አድርጎ ይኖራል ማለት ነው፡፡ በዚህም የመንፈስን ፍሬ የሚያፈራ በአፀደ ቤተ ክርስቲያን የተተከለ የሃይማኖት ተክል ይሆናል፡፡ /ገላ.5:22/፡፡ ተክልነቱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደተተከለች ፍሬዋን በየጊዜው እንደምትሰጥ፣ ቅጠልዋም እንደማይረግፍ ዛፍ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱም ሰው በክፋዎች ምክር አይሄድም፡፡ በኃጢአተኞችም መንገድ አይቆምም፡፡ በዋዘኞችም ወንበር አይቀመጥም፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለዋል፡፡ ሕጉንም በቀንና በሌሊት ያስባል፡፡ /መዝ.1.3/፡፡

 

ቅዱስ ጳዉሎስ የተሰሎንቄ ምእመናን በእምነት አድገውና ጠንክረው በማየቱ «በጸሎታችን ጊዜ ስለ እናንተ ስናስብ የእምነታችሁን ሥራ የፍቅራችሁንም ድካም በጌታችንም በኢየሱስ ክርስቶስ ያለውን የተስፋችሁን መጽናት በአምላካችንና በአባታችን ፊት ሳናቋርጥ እያሰብን እግዚአብሔርን ሁልጊዜ በሁላችሁ ምክንያት እናመሰግናለን፡፡» በማለት ስለእነርሱ እግዚአብሔርን አመስግኗል፡፡ /1ተሰ.1.2ጠ3/፡፡ ከጥንት ጀምሮ በእምነታቸው ጠንካሮች የነበሩ ሰዎች በጉዟቸው ሁሉ እግዚአብሔርን ደስ አሰኝተዋል፡፡ እግዚአብሔርም ደስ የተሰኘባቸው በእምነታቸው ጸንተው በጎ ሥራ በመሥራታቸውና ዓለምን ድል በማድረጋቸው ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳዉሎስ በዕብራውያን መልእክቱ እንደዘረዘረው፡

 

•    አቤል ከቃየል ይልቅ የሚበልጥ መሥዋዕትን ያቀረበው፣
•    አብርሃም ከዘመዶቹ ተለይቶ ከሀገሩ የወጣው፤ አንድ ልጁን ይስሐቅንም ለመሠዋት ፈቀደኛ የሆነው፣
•    ሙሴ የግብጽን ብዙ ገንዘብ የናቀውና ከወገኖቹ ጋር መከራ መቀበልን የመረጠው፤ የፈርኦን የልጅ ልጅ እንዳይባል እምቢ ያለው፣
•    የኢያሪኮ ግንብ በእስራኤላውያን ጩኸት የፈረሰው፣
•    ጌዴዎንና ባርቅ፣ሶምሶንና ዮፍታሔ ጠላቶቻቸውን ድል ያደረጉት፣
•    ብላቴናው ዳዊት ኃይለኛውን ጎልያድን ያሸነፈው፣
•    ሠለስቱ ደቂቅ ወደ እቶነ እሳት ቢጣሉም ከመቃጠል የዳኑት በእምነት ነው፡፡ /ዕብ.11.1ጠ4/፡፡

 

በአዲስ ኪዳንም ቅዱሳን ሐዋርያት ሁሉን ትተው እስከ መጨረሻው የተከተሉት በእምነት ነው፡፡ /ማቴ.19.27/ ከእነርሱም ሌላ በሰው ዘንድ ያልተጠበቁ፣ በእርሱ ዘንድ ግን የታወቁ ጥቂት ሰዎች የእምነታቸው ጽኑነት ተመስክሮላቸዋል፡፡ ለምሳሌ ከነናዊቷ ሴት «አንቺ ሴት እምነትሽ ታላቅ ነው እንደ ወደድሽ ይሁንልሽ» ተብላለች፡፡ /ማቴ. 15.28/፡፡ በእምነት የጸኑ ሰዎች የቤተክርስቲያንን ሥርዓት፣ ትውፊት ለመጠበቅ መልካሙን ገድል ይጋደላሉ፡፡ /2ጢሞ.4.7/፡፡

አንድ ክርስቲያን በክርስትና ሕይወት እስከ ሞት ድረስ ታምኖ የመንግሥቱ ወራሽ ለመሆን ሊያከናውናቸው ከሚገቡ መንፈሳዊ ተግባራት ጥቂቶችን እንመለከታለን፡፡

 

1. የእግዚአብሔር ስጦታዎች ሁሉ ለበጎ መሆናቸውን ማመን

 

በማናቸውም ጊዜ እግዚአብሔር ሁሉን የሚሰጥ አምላከ መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ ሌላው ቀርቶ ለእኛ ክፉ የሚመስሉን ነገሮችን እንኳን ለበጎ መሆናቸው ማመን አለብን፡፡ /ሮሜ.8.28/፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ክፉውን ወደ በጎ ሊለውጥ የሚችል ኃያል አምላክ ነውና፡፡ ብላቴናው ዮሴፍ ባሪያ አድርገው የሸጡትን ወንድሞቹን «እናንተ ክፉ ነገር አሰባችሁብኝ እግዚአብሔር ግን ዛሬ እንደ ሆነው ብዙ ሕዝብ እንዲድን ለማድረግ ለመልካም አሰበው፡፡» ያላቸው ለዚህ ነው፡፡ /ዘፍ.50.20/፡፡ አበ ብዙኃን አብርሃም እግዚአብሔር «ልጅህን ሠዋልኝ» ያለው ለበጎ እንደሆነ ያውቅ ነበር፡፡ ማወቅም ብቻ ሳይሆን እንደተባለው ልጁን ቢሠዋ እንኳን ከሞት አስነሥቶ በእርሱ በኩል ዘሩን እንደሚያበዛለት ያምን ነበር፡፡ /ዕብ.11.17/፡፡ ኢዮብም ነገር ሁሉ ለበጎ እንደሆነ አውቆ «እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔርም ነሣ የእግዚአብሔር ስም የተባረከ ይሁን» ብሏል፡፡ /ኢዮ.1.21/፡፡

 

2. የእግዚአብሔርን ቃል ኪዳኖች ማመን

 

ብዙ ሰዎች እግዚአብሔር የሰጣቸው ተስፋ ደርሶ ቃሉ የሚፈፀም አይመስላቸውም፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል ያለጥርጥር ይፈጸማል፡፡ ለአዳምና ለሔዋን የተሰጠው ተስፋ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ተፈጽሟል፡፡ /ዘፍ.3.15/፡፡ ለኤልያስ የተሰጠው ተስፋ ምንድን ነው) የተሰጠው ተስፋ በሰራፕታዊቷ ሴት መጋቢነት ሲፈጸም ታይቷል፡፡ እንዲሁም በነቢዩ በኢዩኤል አንደበት የተነገረው ተስፋ የበዓለ ሃምሣ ዕለት ለቅዱሳን ሐዋርያት በመሰጠቱ ተፈጽሟል፡፡ /ኢዩ.2.28፤ ሐዋ.2.16/፡፡ በዚህ ዓይነት እግዚአብሔር ለሕዝቡ የገባውን ቃል ኪዳን እንደማይሽርና ከአፉ የወጣውን ቃል እንደማይለውጥ ማመን ይገባል፡፡/መዝ.88.34/፡፡ በቤተ ክርስቲያን በምንሰበሰብበት ጊዜ ሁለት ወይም ሦስት በስሜ በሚሰበሰቡት በዚያ እኔ በመካከላቸው እሆናለሁ ባለው መሠረት በመካከላችን እንደሚገኝ የታመነ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ቤተ ክርስቲያን ከውስጥም ሆነ ከውጭ መከራ በሚበዛባት ጊዜ መከራ የሚያስነሣባትና የሚያጸናባት ዲያብሎስ መሆኑን አውቀን «የገሃነም ደጆችም አይችሉአትም» በሚለው ቃል ኪዳን መጽናት ይገባል፡፡ /ማቴ.16.18/፡፡ መናፍቃን ከእውነት መንገድ ለማውጣት በሚከራከሩን ጊዜም «ወደረኞቻችሁ ሁሉ ሊቃወሙና ሊከራከሩ የማይችሉትን አፍና ጥበብ እሰጣችኋለሁ»የሚለውን ቃል ኪዳን በማሰብ መታመን ያስፈልጋል /ሉቃ.21.15/፡፡

 

3. በችግር ጊዜ የእግዚአብሔርን ቸርነትና ፈቃድ ተስፋ ማድረግ

 

በመንፈሳዊ ጎዳና ስንጓዝ በየአቅጣጫው የሚከበንን መከራ አይተን ተስፋ መቁረጥ ሳይሆን ወደ እግዚአብሔር ተመልክተን አዳኝነቱን ተስፋ ማድረግ አለብን፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ወገኖቹ እስራኤል ቀይ ባሕርን ከኋላ ደግሞ የፈርኦንን ሠራዊት ተመልክተው ተስፋ በቆረጡ ጊዜ «ቁሙ፣ ዛሬ ለእናንተ የሚያደርጋትን የእግዚአብሔርን ማዳን እዩ፡፡» ያላቸው ለዚህ ነው፡፡ /ዘዳ.14.13ጠ14/፡፡

ብላቴናው ዳዊት የተመለከተው በአካሉ ግዙፍ ወደሆነው ወደ ጎልያድ ሳይሆን ወደ እግዚአብሔር አዳኝነት ነው፡፡ /1ሳሙ.17.46/፡፡በአጠቃላይ ዓለም ድብልቅልቅ ቢል ተስፋ መቁረጥ አይገባም፡፡ ምክንያቱም «እግዚአብሔር በወጀብና በዓውሎ ነፋስ መካከል መንገድ አለውና»/ናሆ.1.3/፡፡

 

4. የቅዱሳንን ገድል ማሰብ

 

ቅዱሳን አንድ ጊዜ ስለተሰጣቸው ሃይማኖት እሰከ መጨረሻው ተጋድለዋል፡፡ /2ጢሞ.4.7/፡፡ በሰይፍ ተመትተዋል፣ በእሳት ተቃጥለዋል፣ ለአናብስት ተሰጥተዋል፣ ወደ ጥልቅ ባሕር ተጥለዋል፣ ይህም የሚያሳየን የእምነታቸውን ጥንካሬ ነው፡፡ በመሆኑም የቅዱሳንን ገድል በምናስብበት ጊዜ ከእነርሱ የምንማረው እምነታቸውን፣ ሥርዓታቸውንና ትውፊታቸውን ለመጠበቅ መጽናታቸውን ነው፡፡ መማርም ብቻ ሳይሆን በተሰጣቸው ቃል ኪዳንም እንጠቀማለን፡፡ እስራኤል ዘሥጋ «እናንተ ጽድቅን የምተከተሉ እግዚአብሔርንም የምትሹ ስሙኝጠ ከእርሱ የተቆረጣችሁበትን ድንጋይ ከእርሱም የተቆፈራችሁበትን ጉድጓድ ተመልከቱ፣ ወደ አባታችሁ ወደ አብርሃም ወደ ወለደቻችሁም ወደ ሣራ ተመልከቱ፡፡ አንድ ብቻውን በሆነ ጊዜ ጠራሁት፣ ባረኩትም፣ አበዛሁትም፡፡» የተባለለት ለዚህ ነው፡፡ /ኢሳ.51.1/፡፡

ቅዱስ ጳውሎስም «የእግዚአብሔርን ቃል የተናገሩአችሁን ዋኖቻችሁን አስቡ የኑሮአቸውንም ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነታቸው ምሰሉአቸው» ብሏል /ዕብ.13.7/፡፡ በአጠቃላይ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር መሆኑንና ሥራችንን ሁሉ እንደሚከናውንልን፣ ከሁሉም በላይ እንደሚወደን ማመን ያስፈልጋል፡፡ /ዘፍ.15.21፤1.22፤ መሳ.16.3/፡፡ ምክንያቱም አንድ ልጁን እንኳን አልከለከለንምና /ዮሐ.3.16/፡፡ የእግዚአብሔር ፍቅር በእኛ ዘንድ ተገለጠ፣ በእርሱም በኩል በሕይወት እንኖር ዘንድ እግዚአብሔር አንድ ልጁን ወደ ዓለም ልኮታልና፡፡ /1ዮሐ.4.9/፡፡ እርሱም በትምህርቱ «ከእንግዲሀ ወዲህ ባሮች አልላችሁም ወደጆች ግን ብያችኋለሁ» ብሎናልና፡፡ /ዮሐ.15.15/፡፡ በመጨረሻም ስለማናቸውም ነገር እንደምንጸልይ ሁሉ ስለ እምነታችንም ጽናት ልንጸልይ ይገባል፡፡ እንዲህ ከሆነ እምነታችን ዕለት ዕለት እያደገ እየጠነከረ ይሄዳል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ እስከ ሞት ድረስ እንዳንታመን በእምነትና በምግባር እንዳንጸና የሚያደርጉን ፈተናዎች አሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ ጥቂቶቹ፡

 

1. የራስን ክብር መሻት

 

ብዙ ሰዎች የእግዚአብሔርን ክብር ትተው የራሳቸውን ምድራዊ ክብር ሲፈልጉ እምነታቸው ደክሞባቸዋል፡፡ ዲያብሎስ ከክብሩ የተዋረደው፣ ሄሮድስ ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ለመግደል ያሳደደው፣ ፈሪሳውያን እርስ በርሳቸው ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ «እነሆ ዓለሙ ሁሉ በኋላው ተከትሎት ሄዷል፡፡» በማለት ይቃወሙት የነበረው የራስን ክብር በመሻት ነው፡፡ /ማቴ.2.17፤ ዮሐ.12.19/፡፡ ይሁን እንጂ ምድራዊ ክብር ፈጥኖ እንደ ሣር ይጠወልጋል፣ እንደ አበባም ይረግፋል፡፡ /ኢሳ.40.6፤1ጴጥ.1.24/፡፡ ስለሆነም እንደ ቅዱስ ጳውሎስ «ነፍሴን/ሰውነቴን/ በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጥራለሁ» ማለት ይገባል፡፡

 

2. እምነትንና ዕውቀትን መደባለቅ

 

የሰው ልጅ አእምሮው ውሱን፣ ዕውቀቱም የተገደበ ስለሆነ ነገረ ሃይማኖትን ከአቅሙ በላይ ለመተንተን ይከብደዋል፡፡ ስለሆነም የረቀቀውን የእግዚአብሔርን አሠራር ስፋቱንና ጥልቀቱን በሥጋዊ ዕውቀቱ እመረምራለሁ ሲል ከተሳሳተ ሀሳብ ላይ ደርሶ ይሰናከላል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ላይ እንደምናየው በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩት ግኖስቲኮች ከሃይማኖት ተሳስተው የወደቁት፣ ሃይማኖትንና ዕውቀትን በመደባለቅ ለመጓዝ ባደረጉት ሙከራ ነው፡፡ ሥጋዊውን ዓለም ልንመረምር እንችላለን እንጂ የመንፈስ ቅዱስን ሥራ ልንመረምር አንችልም፡፡ በመሆኑም ሊቃውንት በእምነት ተራቅቀው ብዙ የሃይማኖትን ምሥጢር ባወቁ ቁጥር የሚያውቁት ገና አለማወቃቸውን ነው፡፡ ስለሆነም ውሱን የሆነ ዕውቀታችንን በትህትናና በትዕግሥት እግዚአብሔርን ከማገልገል ጋር ልንጠቀምበት ይገባል፡፡

 

3. ክፉ ባልንጀርነት

 

ከመናፍቃን ጋር በመወዳጀት የእነርሱን ስብከትና መዝሙር መስማት እምነትን ያደክማል፡፡ ምክንያቱም የመዝሙሩ መሣሪያና ስሜት ለሥጋዊ ሀሳብና ፈቃድ መጥፎ ጎን መነሣሣት ይፈጥራልና፡፡ ሃይማኖታዊ ሳይሆን ስሜታዊ ያደርጋል፡፡ የዜማው ስልተ አልባ መሆንና ከዘፈን ጋር ተመሳሳይ በመሆኑ ዓለማዊነት ጠባይ የለበትም መንፈሳዊ ነው ለማለት ያዳግታል፡፡ ለዚህም ነው «ክፉ ባልንጀርነት መልካሙን አመል ያጠፋዋል» የተባለው /1ቆሮ.15.33/፡፡ በሃይማኖት በሥርዓት ከማይመስል ጋር ለመመሳሰል መሞከር፣ አብሮ ማደርም ሆነ መዋል መልካሙን እምነት ያጠፋዋል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም በመልእክቱ «በቤታችሁ አትቀበሉት ሰላምም አትበሉት ሰላምም የሚለው ሰው በክፉ ሥራው ይካፈላልና፡፡» ብሏል፡፡ /2ዮሐ.1.10 – 12/፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም «ከማያምን ጋር በማይመች አካሄድ አትጠመዱ፡፡» ብሏል፡፡ ስለሆነም ብርሃን ከጨለማ ጋር ምንም አንድነት ስለሌለው መለየት ያስፈልጋል፡፡ /2ቆሮ. 6.14-16/፡፡

 

4. ክፉ ወሬ

 

ምእመናን ስለ ሃይማኖታቸው መስማት የሚገባቸው ቤተ ክርስቲያናቸው የምትነግራቸውን መሆን አለበት፡፡ ምክንያቱም «ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው» እንዲሉ በወሬ የተፈቱ ብዙዎች ናቸውና፡፡ እስራኤል ዘሥጋ ምድረ ርስትን ከመውረስ የደከሙትና በእግዚአብሔር ላይ የነበራቸውም ተስፋ የጠወለገው፣ ዐሥሩ ሰላዮች ያወሩትን እምነት የጎደለው ወሬ እውነት ነው ብለው በመቀበላቸው ነበር፡፡ /ዘኁ.13. 28/፡፡ በአዲስ ኪዳንም ጌታችን ሞትን ድል አድርጎ በተነሣ ጊዜ አይሁድ «ደቀ መዛሙርቱ በሌሊት መጥተው ከመቃብር ሰርቀው ወሰዱት» ብለው አስወርተው ነበር፡፡ ይህም ወሬ መግደላዊት ማርያምን አሳምኗት ስለነበረ ከአንዴም ሦስት ጊዜ ጌታን ከመቃብር ወስደውታል እስከ ማለት ደርሳለች፡፡ /ዮሐ. 20.2-13፤15/፡፡ ጥንትም አዳምና ሔዋን ከእግዚአብሔር የተጣሉት የሰይጣንን ወሬ እውነት ነው ብለው በመቀበላቸው ነበር፡፡ /ዘፍ.3.4/፡፡ ምክንያቱም የሐሰት ወሬ ከዲያብሎስ ነው፤ የሐሰት አባት እርሱ ነውና፡፡ /ዮሐ.8.44/፡፡ በእምነት መድከም በመጀመሪያ ሥርዓትን ትውፊትን ያስንቀናል፡፡ በሃይማኖት ለሚኖር ሰው ይህ ደግሞ አግባብ አይደለም፡፡ እንግዲህ ይህንን ሁሉ አውቀን በጊዜውም አለጊዜውም በሃይማኖት በምግባር ጸንተን ልንገኝ ይገባል፡፡ በእምነታችን እንድንጸና ምክንያት ሳናበዛ እምነታችንን ከሚያዳክሙ እኩይ ተግባራት በመራቅ እምነትን የሚያጠናክሩትን በጎ ተግባራት ሁሉ መያዝ አለብን፡፡ «በዓመፀኞች ስሕተት ተስባችሁ ከራሳችሁ ጽናት እንዳትወድቁ ተጠንቀቁ» እንደተባለ በማንም ሳንወሰድ የቅዱሳን አባቶቻችንን ሃይማኖት ከምግባር አስተባብረን ልንይዝ ይገባናል፡፡ /2ጴጥ.3.17/፡፡

 

5. ሥጋዊ መከራን መፍራት

 

ሥጋዊ መከራን መፍራት እምነትን ያደክማል፡፡ ይህም ለዘለዓለም ሞት አሳልፎ ይሰጣል፡፡ /ራዕ.21.7/፡፡ እግዚአብሔር ግን የፍርሃትን መንፈስ አላሳደረብንም /2ጢሞ.1.7/፡፡ ለሥጋ ፍላጎት መገዛት ማለትም ለዝሙት፣ ለገንዘብና ለሥልጣን ወዘተ መገዛትም እምነትን ያዳክማል፡፡ /1ነገ.11.1፤ ማቴ.19.22፤ ዮሐ.5.4-9፤ ዕብ.4.4፤ 2ጴጥ.2.15፤3ዮሐ.10፤ ራዕ.2.14/፡፡ ምድራዊ ችግርም ሲያዩት የሚያልፍ ስለማይመስል እምነትን ያዳክማል፡፡ ጌዴዎን «ጌታዬ ሆይጠ እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ከሆነ ይህ ነገር ሁሉ ለምን ደረሰብን)» ያለው በምድራዊ ችግር ብዛት እምነቱ ደክሞ ስለነበር ነው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም የማዕበሉን ኃይል አይተው «ጌታ ሆይ ስንጠፋ አይገድህምን)» ያሉ ለዚህ ነው፡፡ /ማር.4.35/፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ልንጠነቀቅ የሚገባው ሰይጣን እንዳያታልለን ነው፡፡ ምክንያቱም ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው የብርሃን መልአክ እስከሚመስል ድረስ ራሱን ይለውጣልና፡፡ /2ቆሮ.11.14/፡፡ እንዳለ፡፡ ምትሐታዊ የሆኑ ድንቅ ምልክቶችንም ያደርጋልና፡፡ /2ተሰ.2.3-9/፡፡ ሌላው ደግሞ ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ካለው ነገር የምንጠራጠርበት ምንም ዓይነት ነገር መኖር የለበትም፡፡ ምክንያቱም ዛሬ በዓይነ ሥጋ ብቻ በመመልከት ጥቃቅን መስለው በሚታዩን ነገሮች መጠራጠር ከጀመርን ነገ ደግሞ የእግዚአብሔርን አዳኝነት እስከ መጠራጠር እንደርሳለንና ነው፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የእመቤታችንን ስደት ስናስብ የተሰደዱትን በማሰብ ይሁን

ለክርስቲያን ዓመታት፣ ወራትና ቀናት በሙሉ የተቀደሱ ናቸው፡፡ እያንዳንዱ ቀን በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በቅዱሳን መልካም ምግባር ተቀድሷል፡፡ ለዚህም ነው ቤተክርስቲያን በአንድ ዓመት ውስጥ የሚገኙ 365 ቀናት በቅዱሳን ስም ተሰይመው የሚዘከሩት፡፡
ምእመናን ቤተክርስቲያናቸው በሠራችላቸው ሥርዓት መሠረት በፍቅር በደስታ ከሚዘከሩት ዕለታት ደግሞ ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 6 ቀን የሚዘከረው የእመቤታትን ቅድስት ድንግል ማርያምና የልጇ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስደት አንዱ ነው፡፡

የእመቤታችን ስደት የመጀመሪያው የአዲስ ኪዳን ስደት ነው፡፡ ወንጌላዊው ማቴዎስ እንደሚለው፤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደበት ጊዜ ሰብአ ሰገል የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው? እያሉ በመጠየቅ ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ነበር፡፡ በዚያ ዘመን ምድረ እስራኤልን ይገዛ የነበረው ሄሮድስ የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ የሚለውን ቃል ሰምቶ፤ ከኔ ሌላ ንጉሥ ማን አለ? በማለት በአማካሪዎቹ ግፊት ከአንድ ዓመት ተኩል እስከ ሁለት ዓመት የሚሆን ዕድሜ ያላቸውን ሕፃናት እንዲገደሉ አደረገ፡፡
 
በዚያን ጊዜ «እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሣ፤ እናቱንና ሕፃኑን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሽ፤ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ አለው»፤ እርሱም ተነሥቶ ሕፃኑንና እናቱን በሌሊት ያዘና ከጌታ ዘንድ በነቢይ ልጄን ከግብጽ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብጽ ሔደ፡፡ ሄሮድስ እስኪሞት ድረስም በዚያ ኖረ፡፡ /ማቴ 2-13-15/ ተብሎ እንደተጻፈ ሁሉ፤ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይዛ፣ ዮሴፍና ሰሎሜን አስከትላ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር በግብጽ አውራጃዎች ስደተኛ በመሆን ኖራለች፡፡

ነቢያት ስለጌታ ትንቢት በመናገራቸው፣ እመቤታችን የጌታ እናት በመሆኗ፣ ሐዋርያት ስለጌታ በማስተማራቸው ተሰደዋል፡፡

የጌታ አገልጋይም እናትም የሆነችው የእመቤታችን ስደት ግን. . . ከሁሉ የሚለይ ነው፡፡ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስና የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ስደት ልዩ የሚያደርገው: –

1.    ሕግን በመተላፉ ከገነት ተሰዶ የነበረውን አዳምን ለመካስ የተደረገ በመሆኑ
2.    በግብጽ ነግሦ የነበረውን አምልኮት ጣኦት ለማሳደድ የተደረገ ስለሆነ የጌታችንና የእናቱ ስደት ልዩ ነው፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከናዝሬት ወደ ግብጽ ስትሰደድ የቀን ሐሩር የሌሊት ቁር አግኝቷታል፡፡ እሾህ እየወጋት እንቀፋት እየመታት ተጉዛለች /ተሰዳለች/፤ በስደቷም ረሃብና ጥም፣ ችግርና መከራ ደርሶባታል፡፡ በበረሃው ወንበዴዎችን ባየች ጊዜም በስደት ከሄሮድስ ጭካኔ ከሀገር ያወጣሁትን ልጄን ይገድልብኛል ብላ መሪር እንባ አልቅሳለች፡፡

በስደቷ ወቅት በደረሰባት ረሐብና ጥም የተነሣ ወደ መንደር ገብታ ብትለምን በችግር ምክንያት የሰው ፊት ማየት ከእሳት የበለጠ ወላፈኑ ስለሚያቃጥል የሰው ፊት ገርፏታል፡፡ የትእማን ቤተሰቦች ዘብተውባታል፡፡

«ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም የመጣው ሸክማችንን ሊሸከም ነውና ውኃውን ለፍጥረታት የሚሰጥ እርሱ እየጠማው፤ እንስሳትን የሚመግብ እየራበው ምድርን በልምላሜ የሚያለብስ፣ ተራቁቶ የኛን ከገነት መሰደድ የመጣብንን ዕዳ ሊክስልን ከእናቱ ጋር ተሰደደ፤ ድንግል ማርያምም የአምላክ እናት ሆና መከራን ቀመሰች፡፡ ጌታን አዝላ በረሐብ አለንጋ ተገረፈች፡፡

በመጨረሻ ግን ያ ሁሉ የመከራና የስቃይ ስደት ሲያበቃ «አንቺ ሱላማጢስ ሆይ ተመለሽ» ሲል በመኃልየ ማኀልይ ዘሰሎሞን ተነግሮ የነበረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ከዚያ ሁሉ መከራና ስደት ልጇን ይዛ ወደ ናዝሬት ተመልሳለች፡፡

የእመቤታችንን ስደት ስናስብ «ሲነቅፏችሁና ሲያሳድዷችሁ በእኔም ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲነግሩባችሁ ብፁዓን ናችሁ፡፡ ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ ሐሴትም አድርጉ፡፡ ከእናንተም በፊት የነበሩትን ነብያት እንዲሁ አሳድደዋቸዋልና» /ማቴ 5-11/ የሚለውን የስደት ዋጋ ጭምር እያሰብን መሆን ይገባል፡፡

ይህንንም የእመቤታችንን ስደት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 6 ድረስ በማኅሌትና በመዝሙር ትዘክራለች፡፡ ካህናቱም በዕለተ ሰንበት ከምሽት ጀምረው በማኅሌትና በመዝሙር ምስለ ፍቁር ወልዳን /የልጇ እና የእርሷ/ ሥዕል ይዘው ቤተክርስቲያኑን ይዞራሉ፡፡

ይህም የእመቤታችንን ስደት ለማጠየቅ ነው፡፡ ሌሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የደረሰባቸውን መከራ ለማስታወስ የፍቃድ ጾም ይጾማሉ፡፡

እኛ ክርስቲያኖች በቅድስት ቤተክርስቲያን ተገኝተን በመንፈስ የሩቁን አቅርበን የእመቤታችንን ስደት በእምነት እያየን በማኅሌተ ጽጌ ድርሰታችን በዜማ «መልካሟ ርግብ ማርያም ሆይ ንጹሕ፣ ፀአዳ ፣ቀይህና ብሩህ የሚሆን ልጅሽን ታቅፈሽ ርኅሩኅ የሆነ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤልን አስከትለሽ ከሐዘናችንና ከችግራችን ታረጋጊን ዘንድ ፈጥነሽ ድረሽልን» ልንላት ያስፈልጋል፡፡

በቅዳሴያችንም «ድንግል ሆይ ርጉም በሆነ ሄሮድስ ዘመን ከልጅሽ ጋር ከሀገር ሀገር ስትሸሺ ከአንቺ ጋር መሰደዱን አሳስቢ፤ ድንግል ሆይ ከዓይንሸ የፈሰሰውንና በተወደደ ልጅሽ ፊት የወረደውን መሪር እንባ አሳስቢ፡፡ ድንግል ሆይ ረሐቡንና ጥሙን፣ ችግሩንና ሐዘኑን፣ ከእርሱ ጋር የደረሰብሽንም ጭንቅ ሁሉ አሳስቢ እንላለን፡፡

በዚህ መታሰቢያ ወቅት እመቤታችን ከልጇ ጋር መሰደዷን ማስታወስ ብቻ ሳይሆን እኛም በመንፈስ አብረን ከእመቤታችን ጋር መሰደድ ይገባናል፡፡ የመሰደድ ዋጋው ብፅእና ነውና፡፡ ነገር ግን ወዴት እንደምንሰደድ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ዛሬ ብዙዎች ከጽድቅ ወደ ኃጢአት፣ ከብርሃን ወደ ጨለማ፣ ከእውነት ወደ ሐሰት፣ ከፍቅር ወደ ጸብ ተሰደዋል፡፡ የኛ ስደት ግን መሆን ያለበት ከኃጢአት ወደ ጽድቅ፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከሞተ ወደ ሕይወት፣ ከሐሰት ወደ እውነት፣ ከጥላቻና ክስ ወደ ፍቅርና መተሳሰብ፣ ከክህደት ወደ እምነት መሰደድ ያስፈልጋል፡፡ ከማሳደድ ይልቅ መሰደድ ይሻላልና፡፡

ዛሬ ብዙዎች ለሥጋ ተድላ በኃጢአት እየተሰደዱ ነው፡፡ እነዚህን ወገኖቻችን ከኃጢአት ስደት እንዲመለሱ በማስተ ማር፣ በመምከርና በመገሰጽ ጭምር ልንመልሳቸው ያስፈለጋል፡፡ መምህራንም ለኃጢአት የተሰደዱትን ወገኖች የንስሐ ፍሬ እንዲያፈሩ ሕይወት የሆነውን ወንጌል ሊያስተምሯቸው ይገባል፡፡

በተለያዩ የዓለም ክፍላት በችግርና በተለያዩ ምክንያቶች ከሀገር የተሰደዱትን በጸሎት ማሰብ በሚያስፈልጉ ድጋፎች ሁሉ መርዳት የክርስቲያን የዘወትር ምግባሩ ቢሆንም በተለይ በዚህ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስደት መታሰቢያ ጊዜ በልዩ ሁኔታ በችግር የተሰደዱትን ልናስባቸው ያስፈልጋል፡፡

የእመቤታችንን ስደት ስናስብ በኃጢአትና በመከራ የተሰደዱትን በማሰብ ይሁን፡፡

 
ወስብሐት ለእግዚአብሔ

ኢይብቁል ብክሙ መሪር ሥርው

/መራራ ሥር አይብቀልባችሁ/ /ዕብ.12፡15/  
ዘገብርኤሏ

የአብርሃም ልጆች ነን የሚሉ ነገር ግን የአብርሃምን ሥራ የማይሠሩና የነቢዩ ዳዊት ልጆች ነን የሚሉ የእርሱን ፈለግ የማይከተሉ ዕብራውያንን ቅዱሱ ጳዉሎስ «መራራ ሥር አይብቀልባችሁ» ሲል መከራቸው፡፡ ዕብራውያን በእግዚአብሔር እናምናለን፤ የእሱ ልጆች ነን እያሉ ይመጻደቁ ስለነበሩ መልካም ሥራ በመሥራት ወደ እግዚአብሔር እንዳይቀርቡ የከለከላቸውን መራራውን ሥር እንዲያስወግዱ አሳሰባቸው፡፡ ሁሉን የሚያይና የሚያውቅ አምላከ ሰማይ ወምድር ኢየሱስ ክርስቶስ እነዚህን ውጫቸውን ያሳመሩ ነገር ግን ውስጣቸውን በኃጢአት ያሳደፉትንና በመራራ ሥር የተመሰለው ኃጢአት በውስጣቸው የበቀለባቸውን ጸሐፍትና ፈሪሳውያንን ሲገስጽ «እናንተ ግብዞች ጻፎች፤ ፈሪሳዉያን በውስጡ ቅድሚያና ስስት ሞልቶ ሳለ የጽዋውንና የወጭቱን ውጭ ስለምታጠሩ ወዮላችሁ፡፡» ብሏቸውል፡፡ /ማቴ.23፡25/

ኃጢአትን በሐልዮ ጸንሶ በነቢብ መውለድ፣ በነቢብ ወልዶም በገቢር ማሳደግ መራራ ሥር ነው፡፡ /ማቴ.24፡16/ ይህም ማለት ኃጢአትን ማሰብ አስቦም ሥራ ላይ ማዋል በአጠቃላይ በኃጢአት መውደቅ በሰው ልቡና ውስጥ የሚበቅል መራራ ሥር ነው፡፡ በዚህም «ሐሞትና እሬትም የሚያበቅል ሥር አይሁንባችሁ» /ዘዳ.18፡19/ የተባለውም የሰው ልጅ በመራራ ሥር፣ በሐሞትና በእሬት የተመሰለውን ኃጢአት ከሕይወቱ ካላራቀ መራራ ገሀነመ ዕሳት እጣ ፈንታው ይሆናል፡፡
ከላይ የጠቀስናቸው ሐሳቦች በሙሉ መራራ ሥር የተባለው ኃጢአት መሆኑን የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡ ስለሆነም እስኪ በሕይወታችን ውስጥ ሊነቀሉ የሚገባቸው ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለዩንን መራራ ሥሮች በዝርዝር እንመልከት፡፡

1.ዝሙት

ዝሙት አእምሮን የሚያጐድል፣ ሰላምን የሚነሣ፣ ጤንነትን የሚያሳጣ፣ ሕይወትን የሚያበላሽ፣ ጸጋ እግዚአብሔርን የሚያሳጣ /የሚገፍፍ/ በሰው ልቦና ውስጥ የሚበቅልና መነቀል ያለበት መራራ ሥር ነው፡፡ ብዙ ታላላቅ አባቶች ክብራቸውን ያጡት በዝሙት እንደሆነ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ለምሳሌ፡- እስራኤላዊያን ከሞአብ ልጆች ጋር በማመንዘራቸው ብኤልፌጐር የሚባል ጣዖት እንዲያመልኩ አደረጓቸው፡፡ ከዚህም የተነሣ እግዚአብሔርን በማስቆጣታቸው 24 ሺሕ ሕዝብ በአንድ ቀን ተቀስፏል፡፡ /ዘፍ.22፡37፣ ዘኁ.27፡1/ «ኃጢአትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል» እንደተባለው፡፡ /ምሳ.22፡1ዐ/
ዝሙት፣ ሴሰኝነትና አመንዝራነት ቅድስናን ከሚያሳጡ ታላላቅ ኃጢአቶች ውስጥ የሚቆጠሩ ናቸው፡፡
የሰው ልጅ በእነዚህ ኃጢአቶች እንዳይወድቅ እግዚአብሔር አምላክ ሁሉን አዋቂ ነውና አንድ ለአንድ በመወሰን ጸንቶ እንዲኖር ጋብቻን ባርኮ ቀድሶ ሰጥቶታል፡፡ «መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር፤ መኝታውም ንጹሕ ይሁን፣ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል፡፡» እንዲል፡፡ /ዕብ.13፡4፣ 1ቆሮ.7፡1/ ዝሙት ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለይ መራራ ሥር ነው የተባለውም ለዚህ ነው፡፡ ሶምሶንም ጸጋውን እንዲገፈፍ ያደረገው ይህው በውስጡ የበቀለው መራራ ሥር ነው፡፡ /መሳ.17፡1/ ይህ ታላቅ ሰው ለእግዚአብሔር የተለየ ናዝራዊ ቢሆንም አንድ ናዝራዊ ማድረግ የሌለበትን የዝሙትን ተግባር ፈጽሞ በመገኘቱ ከክብሩ ተዋርዷል ኀይሉ ተነፍጎታል፡፡ /ዘኁ.6፡1/ ዛሬም ትእዛዛተ እግዚአብሔርን በመጣስና ዝሙት በመሥራት ከክብር እየተዋረድን ያለን ሰዎች ራሳችንን ልንመረምርና መራራውን ሥር በንስሐ በጣጥሰን በመጣል ወደ እግዚአብሔር ልንቀርብ ይገባል፡፡ ለሶምሶን እግዚአብሔር አምላክ ታላላቅ ውለታዎችን ቢውልለትም፤ እሱን ያስጨነቀው አምላክ ያደረገለት ውለታ ሳይሆን ከደሊላ በዝሙት የመውደቅ መንፈስ አእምሮውን አሳጥቶት ነበር፡፡ /መሳ.16፡17/ ይህች ሴት ቃሏን አጣፍጣ የዚህን የተመረጠ ሰው ሕይወት እንዳጠመደችው ዛሬም የብዙዎቹን ሕይወት በዝሙት የሚያጠምዱ እርኩስ መንፈስ ያደረባቸው መራራ ሥር የበቀለባቸው እንዳሉ ማስተዋል ይገባል፡፡
ከክብራችን እንዳንዋረድ የቅዱሳን አባቶቻችንን ፈለግ በመከተል ሥጋችንን ለነፍሳችን አስገዝተን መኖር ያስፈልጋል፡፡ ዓይኖቻችን ወደ ቅዱስ ሥጋውና ወደ ቅዱስ ደሙ የሚመለከቱ መሆን አለባቸው፡፡ «ልጄ ሆይ ወደ ጋለሞታ ሴት ልብህ አይባዝን በጐዳናዋ አትሳት፡፡ ወግታ የጣለቻቸው ብዙ ናቸውና፡፡» /ምሳ.7፡24/ በዝሙት ተወግተው ከወደቁት ወገኖች እንዳንደመር በየትኛውም ቦታ ጥንቃቄ ልናደርግ ያስፈልጋል፡፡

2.ትዕቢት

 ሳጥናኤልን ያህል ታላቅ መልአክ ከክብሩ ያዋረደው ሌላው መራራ ሥር ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢት በመራራ ሥር የተመሰለውም ከኔ በላይ ማን አለ በማለት የማይገባውን ይገባኛል እያሰኘ ሌላውን የመናቅ፤ ራስን ከፍ ከፍ የማድረግ መራራ መንፈስ ስለሚያበቅል ነው፡፡ «አንተ የንጋት ልጅ አጥቢያ ኮከብ ሆይ አንተ ወደ ሰማይ ዐርጋለሁ፣ ዙፋኔንም ከሰማይ ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አደርጋለሁ አልህ፡፡ ነገር ግን ወደ ሲኦል ወደ ጉድጓድም ጥልቅ ትወርዳለህ፡፡» /ኢሳ.14፡12-16/ ብሎ የተናገረለት ሳጥናኤል በትዕቢቱ ምክንያት ነው፡፡ «ትዕቢተኛ የሆነውና ልቡ የሚሳሳው ከእኔ ጋር አይተባበርም፡፡» /መዝ.3፡5/ ተብለ የተነገረውን የእግዚአብሔርን ቃል ልናስብ ይገባል፡፡
ይሁን እንጂ ትናንት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ ቅዱስ ሥጋውንና ቅዱስ ደሙን እየበላና እየጠጣ አድጎ በትዕቢት ምክንያት የበላበትን ወጭት ሰባሪ የሆነ ብዙ ነው፡፡ ክርስቲያን ነኝ እያለ በሀብቱ በጉልበቱ በእውቀቱ፣ በወገኑ የሚኩራራና የሚታበይም አለ፡፡ ይሁን እንጂ ሀብታሙ በደሃው ላይ፣ የተማረው ባልተማረውላይ አሠሪ በሠራተኛው ላይ የሚታበይ ከሆነ ክርስቲያን ነው ሊባል ከቶ አይችልም፡፡ እውነተኛ የእግዚአብሔር ልጆች መገለጫ፤ ያለው የሌለውን መርዳት፣ የተማረውም ላልተማረው ደሃ ተበደለ ፍርድ ተጓደለ ማለት፣ ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ሲባል ራስን ዝቅ ማድረግ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን የማገልገል ጸጋ ቢሰጠንም በቸርነቱ መሆኑን ማወቅ ይኖርብናል እንጂ ልንታበይ አይገባም፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የምናገለግል ሁሉ የምናቀርበው የአገልግሎት መስዋዕት በእግዚአብሔር ቸርነት መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል፡፡ ልክ «… የታዘዛችሁትን ሁሉ ባደረጋችሁ ጊዜ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን ልናደርገው የሚገባንን አድርገናል በሉ፡፡» እንደተባለ፡፡ /ሉቃ.17፡1ዐ/
ስለዚህ ፈሪሃ እግዚአብሔር ሊኖረን እንጂ ልንታበይ አይገባም፡፡ «እግዚአብሔርን መፍራት ባለጠግነት ክብር ሕይወትም ነው፡፡» /ምሳ.22፡4/ እንዳለ ጠቢቡ በምሳሌው፡፡

 3. ማስመሰል

መመሳሰልና መስሎ መታየት፣ ለመመሳሰል መጣር የብዙዎች ችግር ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንዳች ፍሬ ባገኝባት ብሎ ወደ አንዲት ዛፍ ሲጠጋ ፍሬ ያፈራች መስላ እንጂ አፍርታ ባለመገኘቷ ምክንያት ለዘላለሙ ፍሬ አይገኝብሽ ብሎ ረገማት፤ ወዲያውም ደረቀች፡፡ /ማቴ.21፡18/
ከዚህ ኀይለ ቃልም የምንረዳው በመስሎ መኖርና ሆኖ አለመገኘት የሚያመጣውን ርግማን ነው፡፡ ማስመሰል መራራ ሥር ነውና ሊነቀል ይገባዋል፡፡ ዛሬም ብዙ ሰው በአፉ የሃይማኖት ሰው ይመስላል፣ እውነታው ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ብዙዎች ቤተ ክርስቲያን የሚሔዱ ጾም የሚጾሙ፣ ነገር ግን ከኃጢያት ያልተለዩ፣ በንስሐ መመለስን ችላ የሚሉ፣ ታቦት ሲነግሥ እልል ስለተባለ ብቻ እልል የሚሉ ከዚያ ሲወጡ ግን ኃጢአት ለመሥራት የሚጣደፉና በልባቸው የሸፈቱ ሰዎች የማስመሰሉን መራራ ሥር ከውስጣቸው በንስሐ ነቅለው መጣል አለባቸው፡፡ ሆኖ መገኘት እንጂ መስሎ መታየት አያድንምና፡፡ «ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል፣ ልቡ ግን ከኔ በጣም የራቀ ነው፡፡ የሰውም ሥርዓት የሆነ ትምህርት እያስተማሩ በከንቱ ያመልኩኛል፡፡» /ኢሳ.29፡13፣ ማቴ.5፡8/ እንደተባለው ዛሬም የብዙ ሰው አምልኮ የዚህ ትንቢት መፈጸሚያ ይመስላል፡፡ ስለዚህ ጥዋት ቤተ ክርስቲያን፤ ከሰዓት ቤተ ጣኦት በመሔድ ጊዜን በከንቱ ከማሳለፍ መቆጠብ ያሻል፡፡ ክርስቲያን ነኝ እያለ ጨሌውን፣ የዐውደ ነገሥቱን ጥንቆላ ማመን፣ መናፍስትን መጥራትና የመሳሰሉትን እየፈጸሙ መገኘት በልብ መሸፈት ነውና ልንመለስ ይገባል፡፡ «በሰማያት ያለው የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ ጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይ፤ የሚሉኝ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡ አይደሉም፡፡» /ማቴ.7፡21/ ተብሏልና፡፡
 መስለው ለመኖር የሞከሩ ብዙ ሰዎች ሲጎዱ እንጂ ሲጠቀሙ አላይንም፡፡ ግያዝ ከኤልሳዕ ጋር መስሎ ሲኖር ልቡ ግን ወደ ገንዘብ ሸፍቶ ስለነበር በለምጽ ተመታ፡፡ /2ኛ ነገ.5፡2ዐ/ የይሁዳንም ታሪክ ስንመለከት ከሐዋርያት ጋር ተመሳስሎ እየኖረ ልቡናው በፍቅረ ንዋይ ተነድፎ እንደነበር ነው፡፡ እናም እነዚህንና የመሳሰሉትን የፍቅረ ንዋይ፣ የስስት፣ የእምነት ጎደሎነት ወዘተ መራራ ሥሮች በቶሎ በንስሐ መነቃቀል ያስፈልጋል፡፡
 ካህኑም፣ ዲያቆኑም፣ ሰባኪውም፣ ዘማሪውም በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ነኝ የሚል ሁሉም አገልግሎቱ ዋጋ የሚያገኘው ከእግዚአብሔር መሆኑን ከልብ በማጤንና ራሱን በመመርመር የጐደለውን ሊያስተካክል ይገባል፡፡ እያንዳንዷ ሥራችን የምትበጠርበት ጊዜ ይመጣልና፡፡ «መጻሕፍትም ተከፈቱ፤ ሌላ መጽሐፍም ተከፈተ፣ እርሱም የሕይወት መጽሐፍ ነው፡፡ ሙታንም በመጻሕፍት ተጽፎ እንደነበረ እንደሥራቸው መጠን ተከፈሉ፡፡ … እያንዳንዱ እንደሥራው መጠን ተከፈለ፡፡» እንዲል፡፡ /ራእ.2ዐ፡12/
 ስለዚህ መልካም ዋጋ ለማግኘት መልካም ሥራ ለመሥራት መጣር ይገባል፡፡ «አምላካችሁ እግዚአብሔርን ተከተሉ እርሱንም ፍሩ ትእዛዙንም ጠብቁ ቃሉንም ስሙ እርሱንም አምልኩ ከእርሱም ጋር ተጣበቁ» /ዘዳ.13፡4/ ስለተባልን ለመልካም ሥራ እሺ እንድንል ያስፈልጋል፡፡ «እሺ ብትሉ፣ ለእኔም ብትታዘዙ፣ የምድርን በረከት ትበላላችሁ፤ እምቢ ብትሉ ግን ብታምጹ ሰይፍ ይበላችኋል፤ የእግዚአብሔር አፍ ይህንን ተናግሯል» ተብሏልና፡፡ /ኢሳ.1፡19/

4. ዓላማ ቢስነት

ዓላማ የሌለው ሰው ከየት ተነሥቶ ወዴት መሔድ እንዳለበት የማያውቅ፣ ካሰበበት የማይደርስ ነው፡፡ ማንም ወደነዳው የሚነዳ፣ በጭፍን የሚጓዝ ሰው ዓላማ ቢስ ሊባል ይችላል፡፡ ዓላማ የሌለው ሰው በጀመረውና በተሠማራበት ተግባር ላይ ጸንቶ አይቆይም፡፡ በተለይ ክርስቲያን ዓላማ ከሌለው በትንሽ ነገር የሚፈተን፣ ሥጋዊ ፍላጐቱ ካልተሟላለት የማያገለግል፣ የሚያማርር፣ በሆነ ባልሆነው የሚያኰርፍ፣ መንፈሳዊነትን ያዝ፣ ለቀቅ የሚያደርግ የጸሎቱ፣ የጾሙ ዋጋ ዛሬውኑ እንዲከፈለው የሚፈልግ ይሆናል፡፡ የሚያገለግልበትንም ዓላማ ያልተገነዘበ ሰው በየደቂቃው እንዲመሰገን ይፈልጋል፡፡ ሰዎች ዓላማቸውን እንዲስቱ በልባቸው ውስጥ የማዘናጋትን ተግባር የሚፈጽም ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ስለሆነ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል፡፡ ቅዱሳን አባቶች በተለያዩ ፈተናዎች ውስጥ ቢያልፉም ዓላማን የመሳት መራራ ሥር በውስጣቸው አልበቀለም፡፡ በሁሉም ጸንተው በመቆማቸው ለክብር አክሊል በቅተዋል፡፡
 ሙሴ እስራኤልን በምድረ በዳ ይመራ በነበረበት ወቅት የተለያዩ ፈተናዎች ቢያጋጥሙትም ከዓላማው አልተዘናጋም፡፡ ይልቁንም ያህዌህ ንሲ /እግዚአብሔር ዓላማዬ ነው አለ እንጂ፡፡ /ዘዳ. 12፡15/
 ዮሴፍ ጽኑ ዓላማ ስለነበረው የተዘጋጀለትን የዝሙት ግብዣ እምቢ አለ፡፡ /ዘፍ. 39/
 ሶስና ልትሸከመው የማትችል የሚመስል ፈተና ቢያጋጥማት ንጽሕናዋን ክብሯን ጠብቃ፣ ለአምላኳ ታምና መኖርን ዓላማዋ ስላደረገች የመጣባትን ፈተና በጽናት፣ በታማኝነት፣ በንጽሕና በቅድስና ልታልፍ ችላለች፡፡ /መጽሐፈ ሶስና/
 ኢዮብ ዓላማው እግዚአብሔር ስለነበር ይፈራረቅበት የነበረውን መከራ፣ ሥቃይና ችግር ሊያልፍ ችሏል፡፡ ወርቅ በእሳት እንደሚፈተን ሁሉ ተፈትኖ፣ ነጥሮ ታላቅነቱን አስመስክሯል፡፡ /ኢዮ.2፡10/ በአንጻሩ ደግሞ ዓላማቸውን የሚያስት መራራ ሥር በውስጣቸው በመብቀሉ ምክንያት የተጐዱ ከክብራቸው ያነሡ ጥቂቶች አይደሉም፡፡
 ለምሳሌ ሳኦልን ብንመለከት እግዚአብሔር አምላክ ከሕዝበ እስራኤል ላይ ንጉሥ እንዲሆን ቢሾመውም የቅንዓት መንፈስ በውስጡ ስለበቀለ እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር ሲሠራ እናያለን፡፡ /1ኛሳሙ. 11፡9፣15፡35/
ዛሬም ትናንት የቤተ ክርስቲያን ልጆች የነበርን፣ እግዚአብሔር ከፍ ስላደረገን፣ ስለሾመን ዓላማችንን የዘነጋን አንታጣምና ራሳችንን ልንመረምር ይገባል፡፡ ከዓላማችን እንድንስት የሚያዘናጉ ነገሮች በርካቶች ናቸው፡፡ ሰው ለገንዘብ፣ ለሥልጣን፣ ለሓላፊ ጠፊ ሀብት ብሎ ዓላማውን ይስታል፡፡ ይሁዳ ምንም እንኳን ከሐዋርያት አንዱ ሆኖ ቢቆጠርም ዓላማው መንግሥተ ሰማያትን መውረስ ሳይሆን ገንዘብን ማሳደድ ስለነበረ አምላኩን እስከ መሸጥ ደረሰ፡፡ «እንጀራዬን የበላ በእኔ ላይ ተረከዙን አነሣ፡፡» ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመበት፡፡ /መዝ.4ዐ፡9/ ይሄው ዛሬ የነፍሰ ገዳዮችና የክፉዎች ተምሳሌት ሆኖ ይነገራል፡፡ ስለዚህ «ከመልካም ሽቱ መልካም ስም ይሻላል፡፡» እንደተባለ ስማችን በክፉ እንዳይጠራ በዓላማችን እንጽና፡፡ /መክ. 7፡1/ ዓላማችን መንግሥቱን ለመውረስ፣ ስሙን ለመቀደስ ይሁን፡፡ እንደ ዴማስ ወደ ዓለም የሚመለስ መራራ ሐሳብ በውስጣችን እንዳይበቅል ጥንቃቄ እናድርግ፡፡ /2ኛጢሞ. 4፡9/

5. የጥርጥር መንፈስ

«የሚጠራጠር ሰው በነፋስ የተገፋና የተነቃነቀ የባህርን ማዕበል ይመስላል፡፡ ሁለት ሐሳብ ላለው፣ በመንገድም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች የሚያገኝ አይምስለው፡፡» /ያዕ. 1፡6/ በማለት እንደተነገረው ተጠራጣሪ ሰው ከጌታ አንዳች ነገር አያገኝም፡፡
 በአሁኑ ወቅት ከጽናታችን እንድንናወጥ የሚያደርጉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን የተጠራበትን ዓላማ ጠንቅቆ የማያውቅ ክርስቲያን በጥርጥር ነፋስ ተነቅሎ ይገነደሳል፡፡ ስለዚህ ጊዜው ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሻው በመሆኑ በማስተዋል መራመድ ያስፈልጋል፡፡
 ቅዱሳን ሐዋርያት በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት ይመጣ ዘንድ ስላለው ክህደትና ሐሳዊ መሲህ «… የሚፈጥንን ጥፋት በራሳቸው ላይ እየተሳቡ የሚያጠፉ ኑፋቄን አሾልከው ያገባሉ፤ … በእነርሱም ጠንቅ የእውነት መንገድ ይሰደባል፡፡» /2ጴጥ.2፡1/ በማለት ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም የክርስቶስን አምላክነት የሚጠራጠርና የሚያጠራጥር፣ በቅዱሳን ላይ አፉን የሚከፍት ሐሳዊ መሲህ ቢነሣ የሚያስደንቅ መሆን የለበትም፡፡ ለምን ቢሉ ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ግድ ነውና፡፡ ዮሐንስም ስለዚህ ነገር «አውሬው ታላቅ ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው … እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም፣ በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ፡፡» ብሎ ጽፏል፡፡ /ራእ.13/
ስለዚህ በልባችን የሚበቅለውን የጥርጥር መንፈስ ከውስጣችን ነቅለን ልንጥል ያስፈልጋል፡፡ «ከራሳችሁ ጽናት እንዳትወድቁ ተጠንቀቁ፡፡ /2ጴጥ.3፡17/ እንደተባልነው ጥንቃቄ ልናደርግ ያስፈልጋል፡፡
በአጠቃላይ መራራ ሥር ኃጢአትና ክርስቲያናዊ ምግባር በአንድ ሰውነት ላይ ሊበቅሉ የማይገባቸው እንክርዳድና ፍሬ ናቸው፡፡ በመሆኑም በንስሐ መከር መለየት ይኖርብናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም የመራራ ሥራ ፍሬዎችን የሥጋ ሥራ በማለት ገልጿቸዋል፡፡ «አስቀድሜ እንዳልኩ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም ብሏል፡፡ ገላ. 5፡21» ስለዚህ ክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲያብብ የክፋት ሥራ የሆኑ ኃጢአቶችን በንስሐ እና በተጋድሎ በተለይም ዝሙት፣ ትዕቢት፣ ማስመሰል፣ ዓላማ ቢስነትና የጥርጥር መንፈስ የመሰሉ መራራ ስሮች በጥንቃቄ መንቀልና ማራቅ ያስፈልገናል፡፡ መራራ ሥሮችን ነቅለን የመንፈስ ፍሬያትን በሰውነታችን እናበቅል ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

                                                    

                                                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ዘመነ ጽጌ

 
 
ከገነት የተሰደደውን አዳምን ወደ ቀደመ ክብሩና መንበሩ ከዚያም ወደ ሚበልጥ ክብር ለመመለስ የተወለደው ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ገና ከህፃንንቱ ጀምሮ ስደትን እና መከራን ተቀብሏል፡፡
ጌታ ሲወለድ ሰብአ ሰገል «የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ? በምሥራቅ ኮከቡን አይተን ልንስግድለት መጥተናል» እያሉ በኮከብ እየተመሩ በመጡ ጊዜ በይሁዳ፣ በገሊላና በሰማርያ የሮማውያን ተወካይ የነበረው ንጉሥ ሄሮድስ የጌታችን ንግሥና ምድራዊ ንግሥና መስሎት መንግስቴን ሊቀማኝ ነው ብሎ ደነገጠ፡፡ ፊሪሳውያን «መሲህ ተወልዶ ከሮማውያን አገዛዝ ነጻ ያወጣናል፡፡» ብለው ያምኑ እንደነበር ስለሚያውቅም ይህ የተፈጸመ መስሎት ጭንቀቱ በረታ፡፡ የተወለደውን ሕፃንም ለመግደል ተነሳ፡፡
 
ስለዚህም ሰብአ ሰገልን አስጠርቶ «ሂዱ ሕፃኑን ፈልጉ ፤ ባገኛችሁትም ጊዜ እኔም እንድሰግድለት ወደ እኔ ተመልሳችሁ ያለበትን ንገሩኝ» በማለት በሽንገላ ተናገራቸው፡፡

ጠቢባኑም ከሄሮድስ ከተለዩ በኋላ በኮከቡ እየተመሩ ጉዞአቸውን ቀጥለው ጌታችንን ከእናቱ ጋር አገኙት ፤ ተንበርክከው ሰገዱለት፤ ወርቅ ፣ ዕጣን፣ ከርቤ እጅ መንሻ አቀረቡለት፡፡

የእግዚአብሔር መልአክ ወደ ሄሮድስ እንዳይመለሱ፤ ነገር ግን መንገድ ቀይረው ወደ ሀገራቸው እንዲሄዱ በነገራቸው መሠረት በሌላ መንገድ ወደ መጡበት ተደብቀው ተመለሱ፡፡

«እነርሱም ከሄዱ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ «ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነስ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሸ፤ እስክነግርህም በዚያ ተቀመጥ አለው፡፡ » /ማቴ. 2 13  14/

ዮሴፍም ተነሣ፤ በዕድሜዋ በጣም ልጅ የነበረችው እመቤታችን ገና የተወለደውን ሕፃን አቅፋ የምትቀመጥበት አህያም ተዘጋጀ፡፡ ጉዞአቸውን ጀመሩ፡፡ ከእስራኤል ወደ ግብጽ በእግር ለመሔድ የሲናን በረሃ ማለፍ የግድ ነው፡፡ በዚያን ዘመን ከእስራኤል ወደ ግብጽ የሚወስዱ ሦስት የተለያዩ መንገዶች ነበሩ፡፡ በሽፍቶች ላለመጠቃት መንገደኞች በቡድን በቡድን ሆነው በእነዚህ መንገዶች ይሔዱ ነበር፡፡

እነርሱ ግን ንጉሥ ሔሮድስ ተከታትሎ ሊይዛቸው ስለሚችል በእነዚህ መንገዶች መሔድ እንደሌለባቸው ግልጽ ነው፡፡ ስለዚህም በእግዚአብሔር መልአክ እየተመሩ ባልታወቁ መንገዶች መሔድ ነበረባቸው፡፡ ለበርካታ ቀናትና ሳምንታት ሸለቆዎችን በመውረድና ኮረብታዎችን እየወጡ ጉዛአቸውን ቀጠሉ፡፡ ሽማግሌው አናጢ ዮሴፍ ከፊት ሁኖ አህያዋን ባልተስተካከለውና ማለቂያ የሌለው በሚመስለው የበረሃ መንገድ ላይ ይመራ ነበር። ሰሎሜም ስንቃቸውን ይዛ ከኋላ ትከተል ነበር፡፡ በጣም አስቸጋሪ እና አስጨናቂ ጉዞ ነበር፡፡ ቀን ቀን የሚያቃጥለውን የፀሐይ ሐሩር ሌሊት ሌሊት ደግሞ የበረሀውን ውርጭ /ብርድ/ መታገል ነበረባቸው ምግባቸውንም በተአምራት ያገኙ ነበር፡፡

በመጨረሻም በመጽሐፈ ስንክሳር እንደተመዘገበው ግንቦት 24 ቀን ግብጽ ደረሱ፡፡ በግብጽም ባሉ የተለያዩ ከተሞች ተዘዋወሩ፣ ጌታም በተለያዩ ቦታዎች በርካታ ተአምራትን አደረገ፡፡ አንዳንድ ሰዎች ተቀብለው ሲያስተናግዷቸው ሌሎች ደግሞ አሳደዋቸዋል፤ መከራንም አጽንተውባቸዋል፡፡ በዚሁ ስድታቸው ወቅት ጌታ እና እመቤታችን ወደ ኢትዮጵያም መጥው ሀገራችንን ባርከዋል።

ለሦስት ዓመት ተኩል ያህል በስደት ከቆዩ በኋላ ሄሮድስ ሞተ። ሄሮድስም ከሞተ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በግብጽ ለዮሴፍ በሕልም ታይቶ «የሕፃኑን ነፍስ የፈለጉት ሞተዋልና ተነሣ፤ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ አለው፡፡ እርሱም ተነስቶ ሕጻኑንና እናቱን ይዞ ወደ እስራኤል ሀገር ገባ» ማቴ 2-19-21/

ቅዱስ ዮሴፍ ይህንን «.. ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ..» የሚለውን የመልአኩን ቃል የሰማው ቁስቋም በምትባል በግብጽ ባለች ቦታ ነው፡፡

በኋላ በዚህች ቦታ ላይ የእመቤታችን ቤተክርስቲያን ተሰርቶ ቅዳሴ ቤቱ ኅዳር 6 ቀን  ከብሯል። ሃያ ሦስተኛው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ቴዎፈሎስ /384-412 ዓ.ም/ ደግሞ በጌታ እና በእመቤታችን ስደት ወቅት የሆነውን ነገር እንዲገለጥለት ለብዙ ጊዜ ጸሎት ካደረገ በኋላ ህዳር 6 ቀን እመቤታችን ተገልጣለት በጉዞው ወቅት የሆነውን ነገር ሁሉ ነግራዋለች፡፡ ስለዚህ ኅዳር 6 ቀን በሁሉም ምሥራቃውያን አብያተ ክርስቲያናት የእመቤታችን ከስደት የመመለሷ ነገር የሚታሰብበት ሁኗል፡፡

በሀገራችን መስከረም 25 ቀን ዘመነ ክረምት አልፎ መስከረም 26 ቀን ዘመነ ጽጌ ይጀምራል፡፡ ጽጌ ማለት አበባ ማለት ሲሆን ዘመነ ጽጌ ማለት የአበባ ዘመን ማለት ነው፡፡ ዘመኑ አበቦች የሚያብቡበትና ሜዳዎችንና ተራሮችን የሚያስጌጡበት ዘመን ነው፡፡ ፍሬ የተባለ ጌታን ያስገኘች እመቤታችን በአበባ ትመሰላለችና ዘመኑ የጌታንና የእመቤታችንን ነገር በአበባና በፍሬ ለመመሰል የተመቸ ነው፡፡

ስለዚህም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከመስከረም 26 ቀን ጀምሮ እስከ ኅዳር 6 ቀን ድረስ የጌታን እና የእመቤታችን ስደት ታስባለች፡፡

በዚህ ዘመን ቅዱስ ያሬድ እና አባ ጽጌ ድንግል ባዘጋጇቸው ድርሰቶች የጌታችን እና የእመቤታችን ስደት በማኅሌት ይታሰባል፤ ምስጋና እና ልመና ይቀርባል። እነዚህን ለየሳምንቱ በሚዘጋጁት ትምህርቶች እናቀርባቸዋለን፡፡

ከዚህም በተጨማሪ ስደቱን ለማሰብና በረከት ለማገኘት በርካታ ክርስቲያኖች ዘመኑን በጾም ያሳልፉታል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜው /Homilies on the Gospel of Saint Mathew/ ይህንን ስደት አስመልክቶ ያስተማረውን ትምህርት ከዚህ ቀጥለን አቅርበናል፡፡

ሰብአ ሰገልም ከሄዱ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በህልም ለዮሴፍ ተገልጾ፡- ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሳና ሕፃኑን ከእናቱ ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ እስክነግርህም ድረስ በዚህ ተቀመጥ አለው እርሱም  ተነስቶ  ሕፃኑና እናቱን ያዘና ከጌታ ዘንድ በነቢይ ልጄን  ከግብፅ ጠራሁት የተባለው ይፈጸም ዘንድ ወደ ግብፅ ሄደ። ሄሮድስም እስኪሞት ድረስ በዚያ ኖረ።

ከዚህ በኋላ ሄሮድስ ሰብአ ሰገል እንደተሳለቁበት ባወቀ ጊዜ እጅግ ተቆጥቶ /ጌታን ለማስገደል በማሰብ / ጌታ በተወለደባት ከተማ በቤተልሔምና በአውራጃዋ የነበሩትን ሕጻናትን አስገደለ፡፡ /ማቴ. 1.13-18/

እዚህ ላይ ሕፃኑን በተመለከተና ሰብአ ሰገልን በተመለከተ ልንጠይቃቸው የሚገቡ ነገሮች አሉ፡፡ ለምን ሰብአ ሰገልም፣ ሕፃኑም /ጌታም/ በዚያው አልቆዩም? ለምን እነርሱ እንደ ተሳዳጅ /fugitive/ በድብቅ ወደ ፋርስ፣ እርሱም ከእናቱ ጋር ወደ ግብፅ ሄዱ?

ከዚህ ሌላ ምን መደረግ ነበረበት? ጌታ በሄሮድስ እጅ መውደቅና ከዚያ አለመገደል ነበረበት? እንዲህ ቢያደርግም ኖሮ ሥጋን መዋሃዱ ግልጽ አይሆንም ነበር፡፡ የክርስቶስ የማዳን ሥራም አይታመንም ነበር፡፡

ሥጋን መዋሃዱን የሚያሳዩ ይህን የመሳሰሉ በርካታ ነገሮች ተደርገው፣ ሥጋን ለበሰ /ተዋሃደ/ መባሉ ተረት /ውሸት/ ነው የሚሉ ካሉ ሁሉን ነገር እንደ አምላክነቱ ብቻ ቢያደርገውማ ከእነዚህ የሚበልጡ ብዙዎች በተሳሳቱ ነበር፡፡

ሰብአ ሰገልንም በፍጥነት የላካቸው አንደኛ ለፋርስ ሰዎች መምሀራን እንዲሆኑ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ጌታን ለማስገደል ላሰበው ሄሮድስ እየሞከረ ያለው የማይቻል ነገርን መሆኑን አስረድቶ የሄሮድስን እብደት ለማቆምና ንዴቱን አስታግሶ ከከንቱ ድካሙ እንዲያርፍ ለማድረግ ነበር፡፡

ምክንያቱም አምላካችን ጠላቶቹን በግልጽ እና በኃይል ማስገዛት ብቻ ሳይሆን በቀላል እና ትንሽ በሚመስሉ ነገሮች ማሳመንም፣ ያውቅበታል፡፡

ለምሳሌ ግብጻውያንን በግልጽ /በኃይል/ ንብረታቸውን ለእስራኤል እንዲያስረክቡ ማድረግ ሲችል እርሱ ግን በጥበብ ያለ ጦርነት ይህንን እንዲያደርጉ አድርጎአቸል፡፡ ይህም አድራጎቱ ከሌሎቹ ተአምራት ባልተናነሰ ሁኔታ በጠላቶቹ ዘንድ የሚፈራ አድርጎታል፡፡

ለምሳሌ ፍልስጤማውያን ታቦተ ጽዮንን ማርከው በመውሰዳቸው በተቀጠቀጡ ጊዜ የሀገራቸውን ጠቢባን ከእግዚአብሔር ጋር ለመዋጋት እንዳይሞክሩ በነገሯቸው ጊዜ ከሌሎች ተአምራት ጋር ይህንን እግዚአብሔር በሥውር የሠራውንም ሥራ አንስተውታል፡፡ በግልጽ ከተደረጉት የተለየ አድርገው አላዩትም፡፡ 1ኛ ሳሙ. 6-6

በዚህ ጊዜም የተደረገው ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ደም የጠማውን ነፍሰ ገዳይ ሊያስደንቅ የሚችል ነገር ነበር፡፡ ሄሮድስ ሊያስብ የሚገባው እንዲህ ነበር፡፡ ሰብአ ሰገል እንደካዱት፣ እንደተናቀና መሳቂያ መሳለቂያ እንደሆነ ባወቀ ጊዜ መደንገጥ ትንፋሹ መቆም ነበረበት፡፡ እነዚህ ሁሉ ነገሮች ካላሻሉት /ካላስተካከሉት/ ግን እርሱን ከጥፋቱ ለመመለስ እነዚህን ሁሉ ነገሮች ያደረገ እግዚአብሔር በእርሱ ጥፋት ሊጠየቅ አይችልም፡፡ ሄሮድስ ከዚህ በኋላ የሆኑትን ነገሮች ሁሉ ያደረገው የእብደቱ ብዛት እነዚህ ሁሉ እውነተኛ ግልጽ ነገሮች እንዲያሳምኑት ስላላደረገ ነው፡፡ ስለዚህ ከጥፋቱ መመለስ አልቻለም፡፡ በክፋቱ ስለ ቀጠለበትም ስለ ሞኝነቱ የከፋ ቅጣት ተቀብሏል፡፡

ሕፃኑ ለምን ወደ ግብጽ ሄደ? የመጀመሪያውን ምክንያት ወንጌላዊው ራሱ በግልጽ ይነግረናል፤ «ልጄን ከግብጽ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብጽ ሄደ» /ማቴ. 1-15/

ከዚህም በተጨማሪ በዚህ ድርጊት ለዓለም መልካም ተስፋ ተሰብኳል፡፡ በዚያን ጊዜ በዓለም ካለው ቦታ ሁሉ በከፋ ሁኔታ ባቢሎን /ፋርስ/ እና ግብጽ በእምነተ ቢስነት /በአምላክ አልባነት/ ነበልባል ተቃጥለው ነበር፡፡ እርሱም ከመጀመሪያው ሁለቱንም እንደሚያስተካክል ምልክት ሰጥቶ ሰዎችን ማዳኑ /ስጦታዎቹ/ ለዓለሙ በሙሉ እንደሆኑ አውቀው በተስፋ እንዲጠብቁ አደረጋቸው፡፡ ለዚህም ወደ አንዱ /ባቢሎን፣ ፋርስ/ ሰብአ ሰገልን ላከ፣ ሌላውን /ግብጽን/ ራሱ ከእናቱ ጋር ጎበኘ፡፡

ከዚህም ሌላ በዚህ የምንማረው ሌላ ትምህርት አለ፤ ከፍ ያለ ጽናት ሊኖረን እንደሚገባ፡፡ ይህ ምን ዓይነት ነው? ክፉ ሃሳብ /ተንኮል/ እና ክፉ ድርጊት ገና በመጠቅለያ ካለበት ጊዜ ጀምሮ በእርሱ ላይ እንደሆነ ተመልከቱ፡፡ በልደቱ ጊዜ መጀመሪያ ክፉ ነፍሰ ገዳይ፣ ተነሳበት ከዚያም ስደት እና ሀገርን ትቶ መሄድ ተከተለ፡፡ ያለ ምንም ጥፋትና በደል ከቤቷ እንኳን ርቃ ተጉዛ የማታውቀው እናቱ ወደ አረመኔዎች /barbarians/ ሃገር ተሰደደች፡፡ አስጨናቂና አስቸጋሪ የሆነ ረጅም ጉዞ እንድታደርግ ታዘዘች፡፡ ይህንን የሰማ ሰው መንፈሳዊ አገልግሎት ሲፈጽም አስጨናቂ ችግሮችና ህመሞች ቢደርሱበትና ህመሞች ቢያጋጥሙት መሸበር የለበትም፡፡

«የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ ስለፈጸምኩ መሸለም መከበርና ታዋቂ መሆን ሲገባኝ ለምን ይህ ሆነ?» ማለትም የለበትም፤ ነገር ግን ሁላችንም ይህንን እንደ ምሳሌ ወስደን ሁሉን ነገር በደስታ መቀበል አለብን፡፡ መንፈሳዊ ነገሮች ባሉበት ሁሉ ተቃዋሚ እንደማይጠፋ እና የመንፈሳዊ ነገሮች ሂደትም ይህ መሆኑንም መረዳት አለብን፡፡

ቢያንስ ይህ ነገር የሆነው በሕፃኑና በእናቱ ብቻ ላይ ሳይሆን በሰብአ ሰገልም ላይ መሆኑን እናስተውል፡፡ እነርሱም እንደ ተሳዳጅ /fugitive/ ሆነው በምስጢር እንዲሸሹ ሆነዋል፡፡

ሌላም አስደናቂ ነገር ተመልከቱ፡፡ የእግዚአብሔር ሐገር፣ የተስፋ ምድር የተባለችው ፍልስጤም በጌታ ላይ የተንኮል መረብ /ሤራ/ ስትዘረጋ የኀጢአትና የጣኦት አምልኮ ሀገር የሆነችው ግብጽ ደግሞ ተቀብላ አዳነችው፡፡

ጌታችን በእግረ ሥጋ በተመላለሰባቸው ዘመናት ያደረጋቸው አብዛኞቹ  ነገሮች ወደፊት ሊመጡ ላላቸው ነገሮች ትንቢት ናቸው፡፡

ዮሴፍ ጌታንና እናቱን ይዞ ወደ ግብጽ እንዲሄድ በመልአክ ታዘዘ፡፡ ግብጽ በሥፋት ጣኦት የሚመለክባት ሀገር ነበረች፡፡ ይህም በኋላ ክርስትና በአምልኮት ባዕድ ወደ ነበሩ ህዝቦች /አሕዛብ/ ዘንድ ለመውሰዷ ትንቢት /ምልክት/ነው፡፡ እመቤታችን ጌታን ይዛ ወደማታውቀው ሀገር ስትሰደድ ቤተልሄም /ይሁዳ/ ሄሮድስ ባስገደላቸው ሕፃናት በሰማዕታት ደም ተጥለቅልቃለች፤ የሄሮድስ ጭፍጨፋና ሕፃናቱን መግደሉ ወደፊት ክርስቲያኖች በአይሁድ እጅ ለሚቀበሉት ሰማዕትነት ምሳሌ ነው፡፡

መልአኩ ተገልጦ የተነጋገረው ከእመቤታችን ጋር ሳይሆን ከዮሴፍ ጋር ነበር፡፡ ምን አለው? «ተነሳ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ..» የእመቤታችን በግብረ መንፈስ ቅዱስ መጽነስ ሲነግረው ያለው «እጮኛህን ማርያምን ለመውሰድ አትፍራ» ነበር፡፡ አሁን ግን እጮኛህን አላለውም «የሕፃኑን እናት» አለው እንጂ፡፡ ምክንያቱም እመቤታችን ጌታችንን ከወለደች እና በጌታ ልደት ጊዜ የሆኑትን ነገሮች /ኮከቡን፣ ሰብአ ሰገልን/ ካየ በኋላ ሁሉን ነገር ተረድቶ ተረጋግጦ ነበር፡፡ በቂ ነገር ዓይቶ፣ ባየው ነገር ተረጋግቶ ነበር፡፡ ስለዚህ መልአኩ አሁን በግልጽ ይናገራል «ልጅህን» ወይም «እጮኛህን» አላለም፡፡ «ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ ግብጽ ሂድ አለው» እንጂ፡፡ የስደቱንም ምክንያት አብሮ ይነግረዋል፤ «ሄርድስ የሕፃኑን ነፍስ ይፈልጋልና፡፡»

ዮሴፍ ይህንን ሲሰማ ቅር አልተሰኘም፤ «ይህን ነገር ለመረዳት ይከብዳል፤ ሕዝቦቹን ያድናቸዋል አላለከኝም ነበር? አሁን ደግሞ ራሱን እንኳን ማዳን አይችልምን? እኛም ከቤታችን ወጥተን ርቀን ለብዙ ጊዜ መሰደድ አለብን አሁን ያለት ነገሮች ከተሰጠው ተስፋ /ቃል/ ጋር ተቃራኒ ናቸው፡፡» አላለም ጻድቅ እና እውነተኛ አማኝ ነበርና፡፡

ምንም እንኳን መልአኩ መመለሻውን ግልጽ ሳያደርግ እስከምነግርህ ድረስ በዚያው ተቀመጥ ቢለውም ስለሚመለሱበት ጊዜ አልተጨነቀም፤ አልጠየቀምም፡፡ ዮሴፍ ፍርሃትም እንኳን አላሳየም፡፡ ሁሉንም ነገር በደሰታ ተቀበለ እንጂ፡፡

ሰውን ወዳጅ የሆነው እግዚአብሔር መከራንና ደስታን በሰዎች ሕይወት ላይ ያመጣል፡፡ በችግር ወይም በደስታ ብቻ አያኖርም፡፡ ነገር ግን ሁለቱንም ችግርን /ሀዘንን/ እና ደስታን /ሃሴትን/ እያፈራረቀ ያመጣል፡፡ አሁንም ያደረገው ይህንኑ ነገር ነው፡፡ ዮሴፍ ድንግልን ጸንሳ ባያት ጊዜ ተጨነቀ፤ ተረበሸ፤ ታወከ፡፡ በዚህ መሃል ግን መልአኩ ተገልጦ ፍርሃቱን አስወገደለት፡፡ ሕፃኑን ተወልዶ ባየ ጊዜም ከፍ ያለ ደስታ ተደሰተ፡፡ ደስታው ብዙም ሳይቆይ አደጋ መጣ፤ በሰብአ ሰገል መምጣት ከተማው ተረበሸ ንጉሡም ከእብደቱና ከክፋቱ የተነሳ የተወለደውን ሕፃን ሊገድል ተነሳ፡፡ ይህ ጭንቀት ደግሞ በደስታ ተተካ ኮከቡና የሰብአ ሰገል ለጌታ መስገድ እጅግ አስደሳች ነበሩ፡፡ ከዚህ ደስታ በኋላም ጭንቀትና ፍርሃት መጣ፡፡ መልአኩ «ንጉሥ ሄሮድስ የሕፃኑን ነፍስ ይፈልጋል፡፡» ብሎ ነገረው፡፡

በዚህ ጊዜ ጌታችን በሕዝብ ፊት ተዓምራት ለማድረግ ጊዜው ገና ነውና መሰደድ አስፈለገው፡፡ ምክንያቱም ገና በልጅነቱ ተአምራትን በአደባባይ /በሕዝብ ፊት/ ቢያደረግ፣ ሥጋን እንደተወሃደ አይታመንም ነበር፡፡

በአንድ ጊዜ ሁሉን ማድረግ ሲችል ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን በማኅጸን ያደረው፣ እንደ ሕፃናት ጡትን እየጠባ፣ በጥቂት በጥቂቱ ያደገው፣ ሥራውን እስኪጀምርም ሠላውን ዘመን በዝምታ /በስውር ተዓምራት/ ያሳለፈው፡- የተዋህዶን ነገር እንረዳ ዘንድ ነው፡፡

አይሁድ ትንቢቱን በተመለከተ ጥያቄ ቢያነሱ እና ልጄን ከግብጽ ጠራሁት የተባለው ስለ እኛ ነው ቢሉን ይህ የትንቢት አካሄድ /መንገድ/ ነው እንላቸዋለን፡፡ ብዙ ጊዜ ስለተወሰኑ ሰዎች የተናገረው የሚፈጸመው በሌሎች ነው፡፡ ያዕቆብ ሊሞት ሲል ልጆችን ሰብስቦ በኋለኛው ዘመን ምን እንደሚደርስባቸው ሲነገራቸው እንዲህ ብሎ ነበር፡-

ስምኦንና ሌዊ ወንድማማች ናቸው፤

ሰይፎቻቸው የአመጽ መሣሪያ ናቸው፡፡

ከምክራቸው ነፍሴ አትግባ፡፡

ከጉባኤያቸውም ጋር ክብሬ አትተባበር

በቁጣቸው ሰውን ገድለዋልና

በገዛ ፈቃዳቸው በሬን አስነክሰዋልና፡፡

በያዕቆብ እከፍላቸዋለሁ፡፡ በእስራኤልም እበትናቸዋለሁ፡፡ ዘፍ. 49-7

ይህ ግን በእነርሱ አልተደረገም በልጆቻቸው እንጂ፡፡ በዘፍ. 9-25 ላይ ተጽፎ እንደሚገኘውም ኖህ እንዲህ ብሎ ነበር፡- «ከነአን ርጉም ይሁን ለወንድሞቹም የባሪያዎች ባሪያ ይሁን» ይህ የተፈጸመው በከንአን ሳይሆን በእርሱ ዘሮች ነው፡፡

ይህ መቼ እና እንዴት እንደሆነ በመጽሐፈ ኢያሱ እና በመጽሐፈ ዜና መዋዕል፤ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ እንዲህም ሆነ በዮርዳኖስ ማዶ በተራራማው በቆላውም በታላቁ ባሕር ዳርና ሊባኖስ ፊት ለፊት የነበሩ ነገሥታት ሁሉ ኬጢያዊ፣ አሞራዊም፣ ከነአናዊም፣ ኢያቡሳዊም፣ ይህን በሰሙ ጊዜ ኢያሱንና እስራኤልን ሊወጉ ወጡ፡፡

በዚያም ቀን ኢያሱ ለማኅበሩ በመረጠው ሥፍራ እስከ ዛሬ ድረስ፣ ለእግዚአብሔር መሠዊያ እንጨት ቆራጮች ውኃም ቀጂዎች አደረጋቸው፡፡ /ኢያ. 9-1-27/

1ኛ ዜና.8-7 ሰሎሞንም ኬጤያውያንንም፣ አምራውያንንም፣ ፌርዜያውያንንም ኢያቡሳውያንንም የቀሩትን ከእስራኤል ወገን ያልሆኑትን ሕዝብ ሁሉ… ገባሮች አድርጎ መለመላቸው፡፡

ይስሐቅ «ለወንድሞችህ ጌታ ሁን፡፡ የእናትህም ልጆች ይስገዱልህ»፡፡ ብሎ ያዕቆብን የመረቀው ምርቃት የተፈፀመው በእርሱ ሳይሆን በልጆቹ ነው፡፡ ዘፍ. 27-19

ስለዚህ እርሱ ባይወለድ ኖሮ፣ ትንቢቱ ፍጻሜውን አያገኝም ነበር፡፡ ወንጌላዊውም ያለውን አስተውሉ፡- «ይፈፀም ዘንድ፡፡» ይህም እርሱ ባይመጣ አይፈፀምም ነበር ማለት ነው፡፡

በዚህኛውም ጊዜ የተደረገው /የሆነው/ ከዚህ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ነገር ነው፡፡ መጀመሪያ ለእስራኤል የተነገረው ነገር በኋላ በጌታ ተፈጽሟል፡፡ ደግሞስ የእግዚአብሔር እውነተኛ ልጅ ሊባል የሚችለው የትኛው ነው? ጥጃን ያመለከና ለቤልሆር ልጆቹን የሰዋ? ወይስ በባሕሪው ልጅ የሆነና የወለደው አባቱ «የምወደው ልጄ» ብሎ የሚያመሰግነው?

ከዚህም ሌላ /ግብጽ መሄዳቸው/ እመቤታችን ከፍ ያለ ክብር ያላት እንደሆነች እንዲታወቅ ተደርጓል፡፡ ህዝቡ የሚመኩበትን ከእግዚአብሔር ያገኙትን ስጦታ እርሷም ለራሷ አግኝታለችና፡፡ ማለትም፣ እነርሱ ከግብጽ በመውጣታቸው /ከስደት በመመለሳቸው/ ይመኩና ይኮሩ ነበር፡፡ ይህንኑ የሚመኩበትን ነገር ለእመቤታችንም ስጣት፡፡

ያዕቆብና ህዝበ እስራኤል ወደ ግብጽ በመሄዳቸውና ከዚያም በመመለሳቸው የእርሱን ግብጽ ሄዶ መመለስ ምሳሌ እየፈጸሙ ነበር፡፡ እነርሱ ግብጽ የሄዱት በረሃብ /በድርቅ/ የመጣ መሞትን ለማምለጥ ነበር፡፡ እርሱ ደግሞ በተንኮል መሞትን ለማምለጥ ነው፡፡

እነሱ /ህዝበ እስራኤል/ ግብጽ መሄዳቸው ከረሃቡ /ከድርቁ/ ተርፈዋል፡፡ እርሱ ግን እዚያ በመሄዱ በኪዳተ እግሩ /በእግሩ በመርገጥ/ ምድሪቱን ቀድሷታል፡፡

በዚህ ራሱን ዝቅ በማድረጉ መሀልም ግን የአምላክነቱ ማሳያዎች /ምልክቶች/ ተገልጸዋል፡፡ ሰብአ ሰገልና እርሱን ለማምለክ በኮከብ እየተመሩ መጡ፤ አውግስጦስ ቄሳርም የሕዝብ ቆጠራ አዋጅ በማወጅ ልደቱ ቤተልሔም እንዲሆን አገለገለ፤ በግብጽም በርካታ ተዓምራት ተደርገዋል፡፡

አሁን ወደ ግብጽ ብንሄድ በረሃው ከማንኛውም የአትክልት ስፍራ የተሻለ ሥፍራ ያማረ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎች በመላእክት አምሳል ያመሰግኑበታል የሰማእታት ብሔር፣ የደናግል በአት፣ የሰይጣን አገዛዝ ድል የተመታበትና የክርስቶስ መንግስት ደምቆ የሚያበራበት ቦታ ነው፡፡

በትምህርተ ሃይማኖታቸው /doctrine/ ካላቸው ትክክለኛነት በተጨማሪ፣ በህይወታቸውም ያላቸውን ቁርጠኝነት ያሳያሉ፡፡ ያላቸውን ሁሉ ትተው ራሳቸውን ከዓለም ካገለሉና ለዓለሙ በሙሉ ከተሰቀሉ በኋላ በድጋሚ የተቸገሩትን ይረዱ ዘንድ የጉልበት ሥራ ይሠራሉ፡፡

ስለሚጾሙና ብዙ ጊዜ በተመስጦ ስለሚያሳልፉ፤ ቀናቱን /ጊዜን/ ሥራ በመፍታት /ቦዝነው/ ማሳለፍ ተገቢ ነው ብለው አያስቡም፡፡ ስለዚህም ቀኑን በጸሎት ሌሊቱንም በዝማሬና በትጋት ያሳልፉታል፡፡ ከዚህም የሐዋርያውን አሰር ይከተላሉ፡፡

«ከማንም ብር ወይም ወርቅ አላስፈለገኝም እነዚህ እጆቼ በሚያስፈልገኝ ነገር ለእኔና ከእኔ ጋር ላሉት እንዳገለገሉ እናንተ ታውቃላችሁ፡፡ እንዲህ እየደከማችሁ ድውያንን ልትረዱና፣ «እርሱ ራሱ ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብጽዕ ነው» የሚለው የጌታን የኢየሱስን ቃል ልታስቡ ይገባችሁ ዘንድ አሳየኋችሁ፤» ሐዋ. 10-34 ይህንን የሐዋርያውን ቃል ሲሰሙ በበረሃ ያሉት የግብጽ መነኮሳት እንዲህ ይላሉ፡- «እርሱ /ሐዋርያው/ በእግዚአብሔር ቃል እንዲመግባቸው ብዙዎች እየጠበቁት የእጅ ሥራ ይሠራ ከነበረ፣ መኖሪያችንን በገዳም፣ በዱር፣ በበረሃ ያደረግን፣ የከተማ ጾር /ፈተና/ የቀረልን እኛማ ከጸሎታችንና ከተመስጦአችን የተረፈንን ጊዜ ለተመሳሳይ ሥራ ልናውለው ምን ያህል ይገባናል)!»

እኛም ራሳችንን እንመርምር ሀብታምም ድሃም የሆንን እነዚህ መነኮሳት ከሰውነት /እጅና፣ እግር/ በስተቀር ምንም የሌላቸው ሲሆኑ የተቸገሩትን ለመርዳት እንዲህ ከወጡና ከወረዱ የተረፈንን እንኳን ለእነዚህ ሰዎች /ችግረኞች፣ ድውያን/ የማንሰጥ እኛ ለዚህ አድራጎታችን ምን ምክንያት፣ ምን ማስተባበያ ማቅረብ እንችላለን፡፡

ታላቁን አባት ቅዱስ እንጦንስን እናስታውስ፡፡ ይህ ሰው የተወለደው ፈርኦን በተወለደበት ሀገር ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ ምክንያት እነርሱን አልመሰለም፡፡ የነበረው ሰማያዊ ራእይ ስለጠበቀው እግዚአብሔር በሚወደው መልኩ ህይወቱን አሳልፏል፡፡ ከጽድቁ የተነሳ ከእርሱ በኋላ የሚመጡ መነኮሳት ምን ዓይነት እንደሚሆኑ እግዚአብሔር አሳይቶታል፡፡

ጻድቁ እንጦንስን ታሪክ ማንበብና ማድነቅ ብቻ ሳይሆን በሕይወት መተርጎምም ያስፈልጋል፡፡ ስለዚህ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን አለመበርታት ቦታን፣ አለመማርን፣ የአባቶችን መርገም… ምክንያት አናድርግ፡፡

ነገሮችን በማስተዋል ስንመለከት እነዚህ ሁሉ ነገሮች ለእኛ መሰናክል መሆን አይችሉም፡፡ አብርሃም ጣኦት አምላኪ አባት ነበረው /ኢያ. 24-2/ ነገር ግን የአባቱን ክፋት አልወረሰም፣ የሕዝቅኤልም አባት አካዝ ኀጢአተኛ ሰው ነበር፡፡ ሕዝቅያስ ግን የእግዚአብሔር ወዳጅ ነበር፡፡

ዮሴፍም በግብጽ ሆኖ ራሱን በትምህርት አስጊጧል፡፡ ሦስቱ ሕፃናትም በባቢሎን ቤተመንግስት ሆነው ታላቅ ራስን መግዛት አሳይተውናል፡፡ ሙሴም በግብጽ ነበር፣ ቅዱስ ጳውሎስም በዓለም ነበር፤ ነገር ግን እነዚህን ሁሉ ያሉበት ቦታና ሁኔታ ከጽድቅ ጉዞአቸው አላደናቀፋቸውም፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን

ማኅበረ ቅዱሳን ማን ነው? ክፍል ሦስት

በልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት

ይህ ዘርፍ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚሰጣቸው መንፈሳዊ አገልግሎቶች በተጨማሪ የተለያዩ ማኅበራዊ እና ኢኮኖ ሚያዊ ሥራዎች የሚሠራበት ዘርፍ ነው፡፡ በዚህም ለቅዱሳት መካናት፣ ለአብነት ትምህርት ቤቶች መምህራን እና ተማሪዎች፣ ለምእመናን ብሎም ለጠቅላላው ኅብረተሰብ አቅም በፈቀደ መጠን ዘላቂ የልማት ሥራዎችን በማከናወን ረገድ በገንዘብ፣ በዓይነት፣ በዕውቀት እንዲሁም በጉልበት እገዛ እያደረገ ይገኛል፡፡ ከእነዚህም መካከል ለአብነት ትምህርት ቤቶች መምህራን እና ተማሪዎች ድጎማ፣ ለገዳማት፣ አድባራት እና የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ጊዜያዊ ርዳታ፣ የዘላቂ ገቢ ቋሚ የልማት ፕሮጀክት ቀረፃና ትግበራ፣ ጉዳት ለደረሰባቸው አብያተ ክርስቲያናት የአስቸኳይ ጊዜ ድጋፍ የማድረግ፣ ኤች.አይ.ቪ/ ኤድስን የመከላከልና የመቆጣጠር ሥራዎችን ያከናውናል፡፡ በቀጣይም የተለያዩ ማኅበራዊ ችግሮችን በመፍታት ዙርያ ለመሥራት በዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡ እንዲሁም በትምህርት መስክ በአዲስ አበባ ሦስት ቦታዎች ላይ፣ በአዋሳ፣ በደብረ ብርሃንና፣ በባሕርዳር፣ ሃገረ ማርያም ወዘተ የራሱን መደበኛ ት/ቤት በመክፈት ሕፃናት በመንፈሳዊና በዘመናዊ ዕውቀታቸው ዳብረው እንዲወጡ እያደረገ ይገኛል፡፡

ሀ. አብነት ት/ቤቶችን ከመደገፍ አንጻር

አብነት ትምህርት ቤት የቤተ ክርስቲያን ትምህርት፣ ሥርዓት፣ ታሪክና ትውፊት ከትውልድ ወደ ትውልድ ማስተላለፍ የሚቻልበት ብቸኛ መድረክ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓቷን፣ ትውፊቷንና ትምህርቷን በየዘመኑ የሚቀበል ትውልድ እንዳታጣ የአብነት ት/ቤቶች ከፍተኛ አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ የአብነት ት/ቤቶች በተለያየ የተፈጥሮ እና ሰው ሠራሽ ችግር ምክንያት የከፋ አደጋ ላይ ይገኛሉ፡፡ በተለይም ጥንታውያን የሆኑት የአብነት ት/ቤቶች እና ሊቃውንቶቻቸው ቀደም ሲል የነበረው የመሬት ባለቤትነታቸውን በማጣታቸው እና የአካባቢው ምእመንም ቀደም ሲል ያደርግላቸው የነበረውን ድጋፍ በኑሮው ጫና ምክንያት በማቆሙ፣ መምህራኑ ወንበራቸውን አጥፈው ለመሰደድ፤ ተማሪዎቻቸውም ለመበታተን ተዳርገዋል፡፡ የነዚህ ለመላው አብያተ ክርስቲያናት የአገልጋይ ምንጭ የሆኑ የአብነት ትምህርት ቤቶች ችግር ምክንያት፤ በደቡብ በምሥራቅ እና በምዕራቡ ላሉት አብያተ ክርስቲያናት የካህናት እጦት መንስኤ በመሆን አብያተ ክርስቲያናቱ እንዲዘጉ አድርጓል፡፡ ማኅበሩ ይህንን ችግር በመረዳት፤ የአብነት ት/ቤቶች መምህራንን እና ተማሪዎችን በመደጎም፣ ጥንታውያን የሆኑት የቀድሞ ይዞታቸው ተጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ ለማድረግ እና በደቡብ፣ በምሥራቅ እና በምዕ ራቡ የሀገሪቱ ክፍል ደግሞ የአካባቢውን ልጆች በማስተማር አገልጋይ ካህናትን በማፍራት የበኩሉን ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ ድጎማው በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር የሚገኙ በጎ አድራጊዎችን በማስተባበር በወር ከአንድ መቶ እስከ ሦስት መቶ ሃምሳ ብር፣ ለስልሳ ሦስት መምህራን ድጎማ እንዲሁም አራት መቶ ሃያ ስምንት ለሚሆኑ ተማሪዎች ደግሞ በወር በሁለት መንገድ የሚፈጸም ነው፡፡ የመጀመሪያው ለመምህራኑና ለተማሪዎቹ የምግብ፣ የአልባሳት፣ የመጻሕፍትና ከሠላሳ እስከ መቶ ሃያ ብር ይደጉማል፡፡ በዚህም ለአብነት ደመወዝ /ለመምህራኑ/ ድጎማ ሲሆን፤ ሁለተኛው የአብነት ት/ቤቶች ራሳቸውን እንዲችሉ ዘላቂ የልማት ፕሮጀክቶችን መቅረፅና ተግባራዊ ማድረግና ለመምህራን እና ተማሪዎች ድጎማ ያደርጋል፡፡ በዓመት እስከ ዘጠኝ መቶ ሺሕ ብር፣ እንዲሁም የገንዘብ ድጎማ ለማይደረግላቸው አንዳንድ የአብነት ት/ቤቶች በጊዜያዊነት ለልብስ፣ ለምግብ፣ ለመጻሕፍት እና ሌሎች ወጪዎች እስከ ስልሳ ሺሕ ብር በዓመት ያወጣል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በተመረጡ የአብ ነት ት/ቤቶች ተማሪዎቹ ከአብነት ትምህርቱ ጎን ለጎን ትምህርተ ሃይማኖት፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትና የስ ብከት ዘዴ እንዲማሩ በማድረግ ለተሻለ አገልግሎት አቅም እንዲኖራቸው በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡

ለ. ገዳማትና አድባራትን ከመደገፍ አንጻር

ማኅበሩ ከአብነት ት/ቤቶች በተጨማሪ ችግር ላለባቸው አድባራትና ገዳማት ጊዜያዊ ርዳታ በማድረግ እና ዘላቂ መፍትሔዎችን በማመቻቸት የገዳማቱንና አድባራቱን ችግር በመጠኑም ቢሆን እየፈታ ይገኛል፡፡ በጊዜያዊ ርዳታ የተለያዩ የመባዕ /ጧፍ፣ ነዕጣን፣ ዘቢብና ሻማ/፣ የተለያዩ ንዋየ ቅድሳት /ልብሰ ተክህኖ፣ መጎናጸፊያ ወዘተ/፣ የዘወትር ልብስ፣ የምግብ እህልና ሌሎችን ርዳታዎችን እያደረገ ይገኛል፡፡ በዓመት በአማካይ ለሠላሳ ቅዱሳት መካናት የልብሰ ተክህኖ ድጋፍ፣ ለሁለት መቶ ቅዱሳት መካናት የመባዕ፣  እንዲሁም የምግብ፣ የአልባሳት እና ለሌሎች ድጋፎች በዓመት እስከ ዘጠና ሺሕ ብር ወጪ ያደርግላቸውል፡፡ በ1995 ዓ.ም በሁለት የአብነት መምህራን የተጀ መረው ድጎማ ዛሬ ቁጥሩን ከፍ በማድረግ ስልሳ ለሚሆኑ ለተመረጡ አብነት ት/ቤቶች ድጎማ ያደርጋል።

በሌላ በኩል ደግሞ ገዳማትና አድባራት ያሉባቸውን ችግሮች በዘላቂነት ለመፍታት ማኅበሩ የተለያዩ የልማትና ማኅበራዊ ፕሮጀክቶችን አጥንቶ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ ቅዱሳት መካናቱ ያላቸውን ነባራዊ ሁኔታ፣ ያላቸውን የተፈጥሮ ሀብት እና የሰው ኃይል መሠረት በማድረግ የአነስተኛ መስኖና አትክልት ልማት፣ የወተት ላም ርባታ፣ ዘመናዊ ንብ ርባታ፣ የከብት ማድለብ፣ ወፍጮ ቤት፣ ሽመና፣ የጥበበ ዕድ ፕሮጀክቶች የሚከራይ ቤት ግንባታ፣ የአብነት ተማሪዎች መኖሪያ ቤት እና የመሳሰሉትን በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም ቅዱሳት መካናቱን ወደ ቀደመው የልማት አውታርነታቸው ለመመለስ፣ የአካባቢውን ኅብረተሰብ የምርቶቻቸው ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከማ ድረግ በተጨማሪ ለአካባቢው አርሶ አደሮችም ሠርቶ ማሳያ እንዲሆኑ አስችሏል፡፡

እስከ 2000 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ በተለያዩ አህጉረ ስብከቶች ከአንድ መቶ ሃያ በላይ የተጠኑ የልማት ፕሮጀክቶች ያሉ ሲሆን ከእነዚህ ፕሮጀክቶች መካከል እስከ 2000 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ በጠቅላላው ከሁለት ሚሊዮን ብር በላይ የፈጁ ሃያ ሦስት የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ገዳማቱ ተረክበዋቸው ሥራ ጀምረዋል፡፡ በ2001 ዓ.ም ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ የሚፈጁ ሃያ ስድስት ከአለፈው የቀጠሉ ፕሮጀክቶች እና ሰባት አዳዲስ ፕሮጀክቶችን ለመተግበር ከተለያዩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገር በጎ አድራጊዎች የገንዘብ እርዳታ ማሰባሰብ ሥራ በመሠራት ላይ ይገኛል፡፡  የእነዚህ ፕሮጀክቶች የእያንዳንዳቸው ጠቅላላ ወጪ ከ35,000 እስከ 350,000 ብር የሚደርስ ሲሆን እንደ ፕሮጀክቱ ዓይነት ሊለያይ ይችላል፡፡ በዚህም የአምስት ዓመት ጉዞ በአብነት ትምህርቱ፣ በገዳማትና አድባ ራት ድጋፍ ከሃያ ሚሊዮን ብር በላይ በዘላቂና ጊዜያዊ ፕሮጀክቶች ላይ ወጪ ተደርጓል፡፡

ሐ. ጉዳት ለደረሰባቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ድጋፍ ማድረግ

ማኅበሩ በተለያዩ ሰው ሠራሽም ሆኑ ተፈጥሮአዊ ምክንያቶች ችግር ከደረሰባቸው ገዳማትና አድባራት ባሻገር በችግር ውስጥ ያሉ ምእመናንንም በመታደግ እንቅስቃሴ ያደርጋል፡፡ በመስከረምና ጥቅምት 1999 ዓ.ም በአክራሪ እስልምና እንቅስቃሴ ጉዳት ለደረሰባቸው የጅማ፣ ኢሉባቦር እና የምዕራብ ወለጋ አህጉረ ስብከት ምእመናንን እና አባላትን በማስተባበር የመልሶ ማቋቋም ሥራ ሠርቷል፡፡ በዚህም ለተፈናቀሉት የኅብረተሰብ ክፍሎች የምግብ ርዳታ ጤፍ፣ በቆሎና ማሽላ በጠቅላላው ለዘጠኝ መቶ ሃያ ስድስት አባወራ አምስት መቶ አሥራ አንድ ኩንታል ገዝቶ አከፋፍሏል፡፡ በኢሊባቦር ለተቃጠሉ ቤቶችም መልሶ ግንባታ ለሃምሳ አንድ አባወራ ለእያንዳንዳቸው አርባ ቆርቆሮና ሚስማር ሰጥቷል፡፡ በኢሊባቡር እና በምዕራብ ወለጋ ለተቃጠሉ ሦስት አብያተ ክርስቲያናት ማሠሪያ ሁለት መቶ ሃምሳ ቆርቆሮ፣ ሦስት መቶ ኩንታል ሲሚንቶ እና አንድ መቶ ሺሕ ብር አስረክቧል፡፡ በአካባቢው ያሉ አብያተ ክርስቲያናትንና ሰንበት ት/ቤቶችን ለማጠናከር ለአሥር አብያተ ክርስቲያናት ሙሉ አልባሳትና አንድ መቶ ዘጠና ሁለት መጽሐፍ ቅዱስ ገዝቶ ያከፋፈለ ሲሆን ለአምስት መምህራንና ለሁለት አብያተ ክርስቲያናት ካህናትና ዲያቆናት የአንድ ዓመት ደመወዝ መድቧል፡፡ የሁለት መምህራንን ቅጥርም አካሒዷል፡፡ በጅማ አካባቢ ያሉትን አብያተ ክርስ ቲያናትና ምእመናን በደረሰው ጉዳት ወላጆቻቸውን ያጡ ልጆችን ለመርዳት ሁለት የኤሌክትሪክ እና ሁለት በናፍጣ የሚሠሩ ወፍጮዎችን ገዝቶ ያስተከለ ሲሆን እንዲሁም ስድስት ክፍል ያለው መጸዳጃ ቤት በማሠራት ለገዳሙ አስረክቧል፡፡ በምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ላሉ ሠላሳ ሁለት ካህናት ሥልጠና ሰጥቷል፡፡

በ2000 ዓ.ም ደብረ ወገግ አሰቦት ገዳም ላይ ለደረሰው የቃጠሎ አደጋ የመልሶ ማቋቋም ሥራ ተሠርቷል፡፡ ለገዳሙ መናንያንም በየወሩ ለቀለብ የሚሆን ስምንት ሺሕ ብር ድጎማ ያደርጋል፡፡ ከዚህ ሌላም በገዳሙ የበቀሉ አላስፈላጊ እፅዋትን ለማስወገጃ ከስልሳ ሺሕ ብር በላይ ወጪ ተደርጓል፡፡ በያዝነው በ2001 ዓ.ም «አንድ መጽሐፍ ይለግሱ» የተሰኘ ፕሮጀክት በመቅረጽ ከአባላትና ከምእመናን ከሶስት ሺሕ አምስት መቶ በላይ መጻሕፍትን በማሰባሰብ ለተለያዩ የአብነት ት/ቤቶችና ሰንበት ት/ቤቶች የማሠራጨት ሥራ ተሠርቷል፡፡

መ. ኤች አይ ቪ/ኤድስን የመከላከልና የመቆጣጠር ሥራ

ማኅበሩ ኤች አይ ቪ/ኤድስን በመከላከልና በመቆጣጠር ረገድም ከተለያዩ አካላት ጋር በመሆን እየሠራ ይገኛል፡፡ የተለያዩ መገናኛ ብዙኃንን በመጠቀም ለማኅበረሰቡ ግንዛቤ እያስጨበጠ ይገኛል፡፡ የቤተ ክርስቲ ያን ትምህርትን መሠረት ያደረጉ የመከላከያ እና የመቆጣጠሪያ ዘዴዎች ላይ ያተኮሩ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ ከስዊድን የሕፃናት አድን ድርጅት፣ ከዓለም ባንክ፣ ከአክሽን ኤይድ እና ቪ.ኤስ.ኦ. ከተባሉ ዓለም አቀፍ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ጋር በመተባበር የተለያዩ ሥራዎችንም ሲሠራ ቆይቷል፡፡ ከተሠሩትም ሥራዎች መካከል ተከታታይ ጽሑፎች በ«ስምዐ ጽድቅ» ጋዜጣ እና «ሐመር» መጽሔት በማውጣት፣ አርባ የሚሆኑ ፀረ ኤች.አይ.ቪ/ ኤድስ ክበባትን ማቋቋም፣ ለዘጠኝ መቶ ዘጠና ሦስት ካህናትና ካውንስለሮች ሥልጠና በመስጠት፣ ለስድስት መቶ አምስት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና ሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች የአቻ ለአቻ የምክር አገልግሎት በመስጠት፣ ውይይቶችና በሃያ አምስት አህጉረ ስብከት ላይ በኤች አይ ቪ/ኤድስ ዙሪያ የዳሰሳ ጥናቶች ማድረግ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በ2001 ዓ.ም ከጥቅምት ወር ጀምሮ ከብሔራዊ የኤች አይ ቪ/ ኤድስ መቆጣጠሪያና መከላከያ ጽ/ቤት በተገኘ ከአምስት መቶ ሺሕ ብር በላይ በሆነ ገንዘብ ጠበልን ከፀረ ኤች አይ ቪ መድኃኒት ጋር አስማምቶ መጠቀም ላይ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ እየተሠራ ይገኛል፡፡

በዚህ ዘርፍ ማኅበሩ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለምእመናን ብሎም ለጠቅላላው ኅብረተሰብ አቅም በፈቀደ መጠን በገንዘብ፣ በዓይነት፣ በዕውቀት እንዲሁም በጉልበት እገዛ እያደረገ ይገኛል፡፡

ሠ. የሙያ አገልግሎት

የማኅበሩ አባላት በገቡት ቃል መሠረት የተለያየ ሙያ ያላቸው አባላት ማኅበሩንና ቤተ ክርስቲያንን በሙያቸው፣ በዕውቀታቸው፣ በገንዘቸው፣ በጉልበታቸው እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡ በተለይም በምህንድስና እና ጥበበ ዕድ ክፍል ባለሙያዎች ለተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት የዲዛይን፣ የቅየሳ፣ የሱፐርቪዥን ወዘተ ሥራ በመሥራት በሚሊዮን የሚቆጠር ብር ለቤተ ክርስቲያን እያዳኑ እና የቤተ ክርስቲያን ትውፊት እንዲጠበቅ አስተዋጽኦ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ ለአብነት ያህል ከ1995 ዓ.ም ወዲህ ከተሠሩትና በዋነኛነት ከሚጠቀሱት ውስጥ ለስምንት የመኖሪያ ቤት ፕሮጀክቶች ዲዛይንና የዋጋ ዝርዝር፣ ለሰባ አምስት አብያተ ክርስቲያናት ሕንፃ ዲዛይን፣ ከሠላሳ በላይ ለሆኑ አብያተ ክርስቲያናት የጥገና ዲዛይን፤ እንዲሁም ከሠላሳ በላይ ለተለያዩ አዳዲስ ፕሮጀክቶች ዲዛይኖችን ሠርተው አስረክበዋል፡፡ ይህም ቤተ ክርስቲያን ልታወጣ የነበረውን ከሰባት ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆን ገንዘብ እንዳታወጣና ወጭ እንድትቆጥብ አድርጓታል፡፡ የሕግ ባለሙያዎቹም የሕግ ምክር አገልግሎት ለሚፈልጉ የቤተ ክርስቲያን አካላት የምክር አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ እንዲ ሁም የተለያዩ የሒሳብና የአስተዳደር ማንዋሎች ተሠርተዋል፡፡ ለቱሪዝም ቅርስ ጥበቃና ክብካቤ የሚረዳ ስትራቴጂክ ዕቅድ በማዘጋጀት ለጠቅላይ ቤተ ክህነት አስረክቧል፡፡ «ቅርስና ቱሪዝም በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን» በሚል ርዕስ ከቅርስና ቱሪዝም ጋር ግንኙነት ላላቸው ባለሙያዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ሰጥቷል፡፡ የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎች በማዘጋጀት ባለድርሻ አካላት ባሉበት አቅርቦ ውይይቶች እንዲካሔዱ አድርጓል፡፡ በማኅበራዊና ምጣኔ ሀብት ክፍል ለአብነት ትምህርት ተማሪዎችና ገዳማዊያን ያሉባቸውን የጤና ችግሮች ላይ መፍትሔና ቅድመ ትምህርት ተሰጥቷል፡፡ በተጨማሪም ከተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት የሚመጡ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን የመገምገምና የማበልጸግ ሥራዎች ተሠርተዋል፡፡

ማኅበሩ አገልግሎቱ እየሰፋ በመጣ ቁጥር በየቦታው በተበታተነ ሁኔታ የሚከራያቸው ቤቶች ለቢሮ አገልግ ሎት አስቸጋሪ በመሆናቸው ቀደም ሲል በጽሕፈት ቤትነት ተከራይቶ ይጠቀምበት የነበረውነ ቦታ በአባላት ልዩ መዋጮና በበጎ አድራጊዎች ርዳታ በ1.3 ሚሊዮን ብር በመግዛት የሕንፃ ግንባታው ሥራ ተጀምሯል፡፡ እስከ ሚያዝያ 2001 ዓ.ም መጨረሻም የመሠረቱንና እስከ አራተኛው ፎቅ ወለል ያለውን ሥራ አጠናቆአል፡፡

ረ. አቡነ ጎርጎርዮስ አፀደ ሕፃናትና አንደኛ ደረጃ ት/ቤት

ማኅበሩ በአሁኑ ጊዜ የቤተ ክርስቲያንን ማንነት የሚያውቁና በግብረ ገብ ትምህርት የታነፁ ሕፃናት ቁጥር  ትንሽ መሆኑን በመገንዘብ ትምህርት ቤት ከፍቷል፡፡ ትምህርት ቤቱ ሰባት ቅርንጫፎች ያሉት ሲሆን፤ ሦስቱ በአዲስ አበባ፣ አንድ በአዋሳ፣ አንድ በባሕርዳር፣ አንድ በሀገረ ማርያም እና አንድ በደብረ ብርሃን ይገኛሉ፡፡ ትምህርት ቤቱ በ2001 ዓ.ም የትምህርት ዘመን በሰባቱ ቅርንጫፎች ከአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ተማሪዎች በላይ ተቀብሎ ከአፀደ ሕፃናት እስከ አምስተኛ ክፍል እያስተማረ ይገኛል፡፡ ትምህርት ቤቱ ከሃያ ለሚበልጡ ሕፃናትም የነፃ የትምህርት ዕድል ሰጥቷል፡፡

ሰ. የልማት ተቋማት

ማኅበሩ «ሐመር» መጽሔት፤ «ስምዐ ጽድቅ» ጋዜጣ፤ መጻሕፍት እና ሌሎችም የኅትመት ውጤቶቹን አሳትሞ በማሠራጨት እንዲሁም ሌሎች የማኅበሩን አገልግሎት ለመደገፍ የሚያስችሉ የልማት ሥራዎችን የሚያከናውን በልማት ተቋማት አስተዳደር ቦርድ የሚመሩ የራሱ የልማት ተቋማት አሉት፡፡ የልማት ተቋማቱ በ18 ማዕከላት /አዲስ አበባን ጨምሮ/ የሚገኙ የማኅበሩን የኅትመት ውጤቶችና ንዋያተ ቅድሳት ማቅረቢያዎች ሲኖሩት በዓይነታቸውም የሚከተሉትን ያካትታሉ፡፡ የካህናት አልባሳት፣ የሞካሽ ሥራ፣ የቆብ እና ጃንጥላ ሥራ ኢንዱስትሪ፣ ንዋያተ ቅድሳት መሸጫ ሱቆች /በቁጥር ሦስት/፣ ምግብ ቤት /በቁጥር ሁለት/፣ ሐመርና ስምዐ ጽድቅ ማከፋፈያዎች /በቁጥር ዐሥራ ዘጠኝ/፣ የመብዐ /የተቀመመ ዕጣን፣ የተለቀመ ነዕጣን፣ ጧፍ፣ ዘቢብ፣ ሻማ/ ማምረቻ ኢንዱስትሪን እንዲሁም የትምህርት ማዕከል በሥሩ ያቅፋል፡፡ ከእነዚህ ገቢ ማስገኛ ተቋማት የሚገኘው ገንዘብ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ለስብከተ ወንጌል ማጠናከሪያ የአብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማትን ለመደገፍ የሚውል ነው፡፡

 ማኅበረ ቅዱሳን ሥርዐተ ቤተክርስቲያን ከማስጠበቅና ቤተክርስቲያንን ከአሕዛብና ከመናፍቃን ከመከላከል አንጻር ምን ሥራ ሠራ?

ማኅበረ ቅዱሳን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው የሥራ መመሪያ መሠረት ካከናወናቸው ሥራዎች በተጨማሪ የቅሰጣ ዓላማቸውን በቤተክርስቲያን ላይ ለመጫን በውስጥም በውጪም ከሚንቀሳቀሱ የመናፍቃንና ቤተክርስቲያንን እናድሳለን ብለው እስከተነሱት እኩዮች ሥራቸውን እየተከታተለ በቅዱስ ሲኖዶስና በምእመናን በመረጃ ላይ የተደገፈ ሪፖርት ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡ አሁንም እያቀረበ ነው፡፡ ወደፊትም ያቀርባል፡፡ ከዚህም ሌላ በእስልምና ስም የሚንቀሳቀሱ አንዳንድ አክራሪዎች በቤተክርስቲያን ላይ እያደረሱ ያሉትን የጥፋት ዘመቻ ለማስታገስና ምእመናን እንዲረጋጉ ለማድረግ አክራሪዎቹ በቤተክርስቲያን ላይ ላነሱት ጥያቄ ማብራሪያ ያለው መልስ ሲሰጥ ቆይቷል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን እስልምናን በተመ ለከተ የሠራቸው ሥራዎችን በሚከተ ለው መንገድ ማጠቃለል ይቻላል፡፡

1. ከመጀመሪያው ጀምሮ ምእመናን አክራሪውንና ነባሩን ሰላማዊውን እስልምና ነጥለው እንዲመለከቱ ከፍተኛውን ድርሻ ተወጥቷል፡፡

2.. ለሚያነሷቸው ታሪካዊና ዶግማዊ ጥያቄዎች በተጻፉት ጽሑፎች መጠንና ቁጥር ጋር ሊነጻጸር ቀርቶ እዚህ ግባ   የሚባል ባይሆንም መጠነኛ ምላሾችን ሰጥቷል፡፡

3. ተቻችሎና ተከባብሮ ስለመኖር ከየትኛውም አካል በፊት እና በከፍተኛ ሽፋን ሠርቷል፡፡

4. ስለ አክራሪ እስልምና እና ስለ ትንኮሳው እጅግ አነሥተኛ እና ክስተት ተኰር የሆኑ መረጃዎችን በመስጠት ችግሩ ሲያጋጥም ለመንግሥት ማመልከት እንደሚገባ አቅጣጫ ለማሳየት ሞክሯል፡፡

 የፕሮቴስታንትና የተሐድሶ መናፍቃንን ሴራ በማጋለጥ ረገድ

ከላይ ለመግለጽ እንደሞርነው ማኅበረ ቅዱሳን የፕሮቴስታንትና የተሐድሶ መናፍቃንን ሴራ በማጋለጥ ረገድ ቤተክርስቲያንንና ምእመናን እንዲጠነቀቁ እንዲሁም የመናፍቃኑን ማንነት እንዲያውቁ በማድረጉ ረገድ በጣም ብዙ ሥራዎች ሠርቷል፤ እየሠራም ነው፡፡ ከነዚህም ውስጥ «የዘመቻ ፊሊጶስን» የመናፍቃን ባለብዙ በጀት ሰፊ እንቅስቃሴ ቀድሞ መረጃ ለቤተክርስቲያንና ለምእመናን በመስጠት ሴራው እንዲከሽፍ ምእመናንም እንዲጠበቁ አድርጓል፡፡ በዚህም የመናፍቃኑ ሴራ በታሰበበት ሁኔታ ሳይሔድ ተኮላሽቷል፡፡

ሌላው እግራቸውን በቤተክርስቲያን ታዛ ልባቸውን በመናፍቃኑ አዳራሽ አድርገው በቤተክርስቲያን ውስጥ በመሽሎክሎክ የሚሠሩ ተሐድሶ መናፍቃንን ማንነት መረጃ በማቅረብና በማጋለጥ ከድብቅ ዓላማቸው እንዲገቱና እንዲወገዙ አድርጓል፡፡ በዚህ መረጃም ምእመናን ማንነታቸውን እንዲለዩና እንዲጠነቀቁም ተደርጓል፡፡ /በአሁኑ ጊዜ ደግሞ የነዚህ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ በገሃድ በቤተክርስቲያኒቱ ሰርገው በመግባትና ለተልዕኮ ባስቀመጧቸው የውስጥ ሰዎች አማካኝነት ተጠናክረው እየሠሩ ነው፡፡ የነዚህንም ማንነት መረጃዎቻችንን አጠናክረን ስንጨርስ ለቅዱስ ሲኖዶስና ለምእመናን የምናሳውቅ መሆኑን በዚህ አጋጣሚ እንገልጻለን፡፡/

በተጨማሪም ላይችሉት የተቀበሉትን የምንኩስና ሕይወት ትተው በመናፍቃኑ አዳራሽ በድብቅ ጉባኤ ያደረጉትን ግለሰቦች ማንነት በማጋለጥ ለምእመናንና ለቤተክርስቲያን አባቶች ለማቅረብ የተደረገውና መናፍቃኑ የቤተክርስቲያንን የዋሀንን ለማሳሳት አስመስለው ከሚያሳትሟቸው የሕትመት ውጤቶችና የድምፅ መልእክቶች ምንነትና ማንነት በማጋለጥ ማኅበረ ቅዱሳን መረጃ ሲሰጥ ቆይቷል፤ አሁንም ወደፊትም ይሰጣል፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ በዐለት ላይ የተመሠረተ ማኅበር ነውና ቤተክርስቲያን የሰጠችውን ሓላፊነት በብቃት ይወጣል፡፡

በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ አጽድቆ በሰጠው መመሪያና ደንብ መሠረት ማኅበሩ በዓይን የሚታይ፣ በእጅ የሚዳሰስ ለውጥ ያመጣ ሥራ ሠርቶ አሳይቷል፡፡ በማሳየት ላይም ነው፡፡ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ወደፊትም ያሳያል፡፡ ነገር ግን በውስጥ ያሉ ሥራቸው ያልታወቀባቸው የመሰላቸው የመናፍቃኑ ዐርበኞች ማኅበሩን ሳያውቁት አልያም ለማወቅ ባለመፈለግ ጥቅመኛ አድረገው የሚያስወሩት አሉባልታ ከእውነት የራቀ መሆኑን ማንም የሚገነዘበው ሐቅ መሆኑን ሊረዱት ያስፈልጋል፡፡

እነዚህ እኩያን የቤተክርስቲያን ጠላቶች ማኅበረ ቅዱሳን ባሉት አባላትና በበጎ አድራጊ ምእመናን ድጋፍ በጉልበት በዕውቀትና በገንዘብ ቤተ ክርስቲያን ያለባትን ክፍተት እያጠና ይሞላል እንጂ ከቤተክርስቲያን ዜሮ አምስት ሣንቲም በጀት እንደ ማይመደብለት እያወቁ አለማወቃቸው ነው፡፡ በጀት ከመምሪያቸው በመመደብ ማኅበሩን ያንቀሳቀሱት ይመስል ቤተክርስቲያን ይሠሩልኛል ብላ ያስቀመጠቻቸው አንዳንድ በሓላፊነት ቦታ ላይ ያሉ የመናፍቃኑ ተላላኪዎች ግን ማኅበሩ ሒሳቡን ኦዲት እንደማያደርግና እንደማያስደርግ ጊዜያዊ ትርፍ የሚያገኙ መስሏቸው አሉባልታ በመንዛት ማኅበሩን ያልሆነ ስም ለማሰጠት ሲጣጣሩ እየተሰማና እየታየን ነው፡፡ እውነቱ ግን ይኼ አይደለም፡፡ ማኅበሩ ሲኖዶሱ ባጸደቀለት ግልጽ መመሪያን መሠረት በሚያገለግሉ ባለሙያ አባላቶቹ በየጊዜው ሒሳቡን እያሰላና እያስመረመረ ነው ሥራውን በጥራት እየሠራ የሚገኘው፡፡ ይኼንን አሠራር ለማወቅ ለሚፈልግ ማንኛውም አካል ሁሉ ማኅበሩን ቀርቦ ማየት፤ በማኅበሩም በተለያዩ አህጉረ ስብከት የተሠሩትን ሥራዎች መመርመር ይችላል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን አሠራሩ ግልጽ አገልግሎቱም የሚታይ ነው፡፡ እነዚህ የማኅበሩን አገልግሎት ለማሳጣት ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ የሚለፍፉት አንዳንድ የመምሪያ ሓላፊዎች ባልሆነ ነገር ላይ ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን ከሚያባክኑ ይልቅ ቤተክርስቲያኒቱ የመደበችላቸውን በጀት በአግባቡ ባለመጠቀማቸው ምክንያት በየጊዜው በየጠቅላላ መንፈሳዊ ሰበካ ጉባኤ ላይ በሪፖርት ላይ ከመወቀስ ቢድኑ መልካም ይሆን ነበር፡፡

ስለ ማኅበረ ቅዱሳን ለማወቅ ለሚፈልጉ ሁሉ ስለ ማኅበሩ አሠራር ብዙ ማለት ይቻል ነበር፤ ነገር ግን ምእመናን ከአሳሳቾች ትጠበቁ ዘንድ ስለማኅበሩ አገልግሎት ከብዙ በጥቂቱ ይኽን እውነታ እንድታውቁ እንወዳለን፡፡

                                                           ወስብሐት ለእግዚአብሔር

«ማኅበረ ቅዱሳን ለሁሉም ግልጽ አሠራር አለው» ክፍል ሁለት

ስምዐ ጽድቅ፦ አንዳንዶች ማኅበረ ቅዱሳን የተወሰነ ብሔር ስብስብ ነው የሚል አስተያየት አላቸው፤ ማኅበሩ ለዚህ ዓይነት አስተያየት የሚሰጠው መልስ ምንድነው?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ፡-  በመሠረቱ ማኅበረ ቅዱሳን የክርስቲያኖች የአገልግሎት ማኅበር ነው፡፡ የክርስቲያኖች አገልግሎት ደግሞ «ሑሩ ወመሐሩ፤ ወደ ዓለም ሁሉ ሒዱና አስተምሩ» ማር.16÷15 በሚለው የክርስቶስ ቃል ላይ የተመሠረተ በመሆኑ አገልግሎቱ ለሀገርም፣ ለአህጉርም ብቻ አይደለም ለዓለም ሁሉ ነው፡፡ ስለዚህ ለማገልገልም ለመገልገልም በቋንቋ ወይም በቀለም ወይም በጾታ… ላይ የተመሠረተ የወገንተኛነት አካሔድ ከሃይማኖታችን መሠረታዊ ሐሳብ ጋር የሚጋጭ ነው፡፡ ስለዚህ ማኅበራችን ማገልገልም መገልገልም የሚፈልጉ የትኞቹንም  ወገኖች ከልብና በእውነት የማገልገል ፍላጎት አለው፡፡ ከአፍሪካ የተለያዩ ሀገሮች የመጡ ወንድሞቻችንን ለጥ ምቀት እንዳበቃን ሁሉ ከአውሮ­ ከአሜሪካ  የመጡና በዚያውም ያሉ በቋንቋና በዜግነት ኢትዮጵያዊ ያልሆኑ ሰዎችን ሁሉ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነትና መድኃኒትነት አምነው ለጥምቀት  በቅተዋል፡፡ ስለዚህ ማኅበሩ እጅግ ሊታሰብ በማይችል ጠባብነት ታጥሮ የአንድ የተወሰነ ወገን ስብስብ ሆኖ የሚሠራ ነው የሚለው ሐሜት ካለማወቅ ወይም ደግሞ ሌላ ዓላማ ካለው ወገን የሚመጣ ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ማኅበሩ ከተለያዩ ብሔረሰብ ለተውጣጡ ምእመናን ሥልጠና በመስጠት በተለያዩ ቋንቋዎች ወንጌል ለሁሉም እንዲደረስ በትምህርትና ሐዋርያ ዋና ክፍሉ አማካኝነት ከፍተኛ ጥረት እያደረገ ነው፡፡ አባላቱም ዕድሉን አግኝተው ወደ ከፍተኛ ተቋማት በመግባት በማኅበሩ አገልግሎት የታቀፉ ሁሉ ወይም የማኅበሩን አገልግሎት ተረድተው አባል ለመሆን ፈቃደኛ ሆነው የቀረቡ ሁሉ ናቸው፡፡ የአባልነት መመዘኛም የቤተክርስቲያን ልጅ በመሆን የሰበካ ጉባኤ ወይም ሰንበት ት/ቤት አባል መሆን ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የ­ለቲካ አቋምን በተመለከተስ?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ- ከላይ ለመጥቀስ እንደሞከርኩት የእኛ ማኅበር ሃይማኖታዊ አገልግሎት ለመስጠት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ስር የተቋቋመ የአገልግሎት ማኅበር ነው፡፡ ስለዚህ ማኅበሩ እንደ ተቋም የሚሰጠውም አገልግሎት ሃይማኖታዊ ነው፡፡ ለየትኛውም የፖለቲካ ዓይነትና አደረጃጀት የሚያግዝ /የሚሠራ/ እንዲሆን መቼም ቢሆን ፍላጐቱ የለንም፡፡ በማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ አምስት እንደተቀመጠው «ማኅበሩ በማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ምንም ዓይነት ጣልቃ ገብነት አይኖረውም»  ይላል፡፡ የዚህን አንቀጽ ይዘት ተግባራዊ ለማድረግ እንዲቻል በማኅበሩ ያሉ የተወሰኑ አካላት በሓላፊነት ላይ እያሉ የማንኛውም የፖለቲካ አባል እንዳይሆኑ በ1998 ዓ.ም የሥራ አመራር ጉባኤያችን ወስኗል፡፡ በውሳኔውም መሠረት የሥራ አመራር ጉባኤ አባላት፣ የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ አባላት፣ የማኅበሩ መደበኛ መምህራን፣ የኤዲቶሪያል ቦርድ ጽ/ቤት አባላት፣ የኦዲትና ኤንስፔክሽን አገልግሎት ጽ/ቤት አባላት፣ ጋዜጠኞች፣ የማዕከላት ሰብሳቢዎች በሓላፊነት ላይ ያሉ መደበኛ አገልጋዮች የማንኛውም የፖለቲካ ­ፓርቲ አባል አይሆኑም፡፡

ይህ ማለት ግን ­ለፖለቲከኞች በማኅበሩ የማገልገል ዕድል አይኖራቸውም ማለት አይደለም፡፡ ለፖለቲካ ዓላማቸው ማኅበሩን መጠቀም ግን አይችሉም፡፡ ስለዚህ የትኛውንም የማኅበሩን አባል በግሉ የ«ሀ» ወይም የ«ለ» ­ፓርቲ ደጋፊ፣ አባል ወይም አመራር እንዲሆን ወይም እዳይሆን ምንም ዓይነት ተቋማዊ ተጽዕኖ በማኅበሩ የሚፈጠርበት ዕድል የለም፡፡ ይህ ግን ሀገርን በመገንባት ረገድ ለአጠቃላዩ ማኅበረሰብ ትርጉም ያለው ልማታዊ ተግባራትን የማከናውን ዓላማና እንቅስቃሴ የለውም ማለት አይደለም፡፡ እንደሚታወቀው ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ ያላት የሀገራዊ ልማት ተሳትፎ ከፍተኛ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ቀጣይነት እንዲኖረው ክርስቲያን ምሁራንና ወጣቶች ባላቸው አቅም ሁሉ ይሳተፋሉ፡፡ የልማት ተሳትፎአቸው ለሀገርና ለትውልድ እንዲጠቅም፣ ቤተክርስቲያንም ያላትን ድርሻ እድትወጣ በማሰብ ነው፡፡ ብዙዎቹ ልማታዊ ተግባሮቻችን ደግሞ በቀጥታ የቤተክርስቲያናችንን ጥቅም የሚያስጠብቁ በመሆናቸው እንቅስቃሴያችን ለሌላ ትርጉም በሚጋለጥ መልኩ የሚደረግ ነው የሚል እምነት የለንም፡፡  

በእርግጥ እንደተባለው በሀገር ውስጥም በውጪም በ­ፖለቲካ ወገንተኝነት ማኅበሩን ለማማት የሚፈለጉ ወገኖች እንዳሉ እናውቃለን፡፡ በጣም የሚገርመው ግን የሚሰጡት አስተያየቶች የተዘበራረቁ መሆናቸው በራሳቸው መሠረት የሌላቸው አስተያየቶች መሆናቸውን ያመለክታሉ፡፡ በሀገር ውስጥ ያለው ማኅበሩ የ«ሀ» ፖርቲ ደጋፊ ነው ሲል በውጪ ሀገር ያሉ አንዳንድ ወገኖች ደግሞ የ«ለ» ፖርቲ ደጋፊ ነው እያሉ ተጨባጭነት የሌለውና ምናልባትም የማኅበራችን አባላት በሆኑ የአንዳንድ ግለሰቦች ተሳትፎን መነሻ አድርጐ የሚሰጥ ሚዛናዊ ያልሆነ ድምዳሜ ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን ማኅበራችን ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መተዳደሪያ ደንብ ላይ ተመርኩዞ አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁሉ ባለው የፖለቲካ ሥርዓት ከሚቋቋመው መንግሥት ጋር መሥራት ሃይማኖታዊም ሕገ መንግሥታዊም ግዴታው ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ማኅበሩ እንደተቋም የትኛውንም የፖለቲካ አስተሳሰብ /Ideology/ በመደገፍ ወይም በመቃውም ከፖርቲዎች ጋር ግንኙነት ስለሌለው /ስለማይኖረው/ ለማንም ስጋት ወይም ዕድል ልንሆን አንችልም፡፡ በዚህ ደረጃ ፈርጆን የሚነሣ አካል ካለ ግን ለመፈረጅ ያበቁትን የመረጃ ምንጮች እንዲመረምር በዚሁ አጋጣሚ ሳልጠቁም አላልፍም፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ማኅበሩ አክራሪ ነው ስለሚባለውስ?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ፡- እኛ «አክራሪ» የሚለውን ቃል በጥንቃቄ ነው የምንመረምረው?  አክራሪ ማለት የሃይማኖቱን ሕግ አክብሮ የሚኖር ተግቶ የሚጾም፣ የሚጸልይ በሃይማኖቱ ላይ ለሚነሡ ጥያቄዎች መልስ የሚሰጥ፣ ታሪኩን፣ ቤተክርስቲያኑን የሚወድ፣ ለሃይማኖቱ የሚቀና የማይዋሽ ወይም ወደ ከፍተኛ ሥነ ምግባራዊ ሕይወት ራሱንም የሃይማኖት ወገኑን ሁሉ ለማድረስ የሚተጋ ከሆነ የማኅበራችንን አባላት ሊገልጽ ይችላል፡፡ ሰዎች ምናልባት በልማድ በዚህ ብያኔ ለመጥራት ፈልገው ከሆነ ችግር ላይኖረው ይችላል፡፡ ነገር ግን በዚህ ሁኔታ የሚመላለሱትን ክርስቲያኖች «አክራሪ» ተብ ለው ከሚጠሩ አጥባቂ፣ ዐቃቤ ሃይማኖት ቢባሉ የተሻለ ነው፡፡

በሌላ በኩል ግን «አክራሪ» የሚለው የሚያሰቃይ፣ የሚገድል፣ የሚያስገድድ፣ የሚሳደብ፣ የሌላውን ሳይነኩ የራሳቸውን አምልኮ እየፈጸሙ ያሉትን የሚረብሸ፣.. ወዘተ ለማለት የተቀመጠ ብያኔ ከሆነ በወንጌል የሚያምኑ፤ አምነውም የሚያስተምሩ ክርስቲያኖች ሊያደርጉት አይችሉም፡፡ ምክንያቱም ከላዩ የተጠቀሱት ተግባራት ከክርስትና ሃይማኖት አስተምህሮ ጋር ተጣጥመው አይሔዱም፡፡ ማኅበራችንም ስብከተ ወጌልን በመላው ሀገሪቱ  እና ዓለማት የማስፋፋት ዓላማ ይዞ የሚሠራ በመሆኑ ለፍቅርና ለመከባበር ትልቅ ቦታ አለው፡፡

ምናልባት በማስጨነቅ ወይም በማስገደድ ሃይማኖታችንን ለማስጣል የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሲኖሩ ቅሬታችንን መግለጻችንና በሃይማኖታችን ላይ በኅትመት ወይም በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ አማካኝነት የሚሰጡ አስተያየትና ጥያቄዎች ሲኖሩ መልስና የአጸፋ አስተያየቶችን መስጠታችን በዚህ ደረጃ አስ ፈርጆን ከሆነ ሚዛናዊ ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡ እነዚህን የምናደርገው በሃይማኖታችን ላይ ጥያቄ ያነሣውን ወይም አስተያየት የሰጠውን አካል ለመተቸት ወይም ለመሳደብ ተፈልጐ ሳይሆን እነዚህ አካላት ካሠራጯቸው መልእክቶች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንን ሐሳብ እንዳይበረዝ፣ ሃይማኖታችን መልስና አስተያየት የሌለው መስሎ ለምእመናን እንዳይታሰብ ለመጠበቅ የሚደረጉና ለጠየቁን መልስ እንድንሰጥ በሃይማኖታችንም የታዘዘውን መንፈሳዊ ተግባር ለመፈጸም ነው፡፡

መከራ የደረሰባቸውና የሚደርስባቸው ክርስቲያኖች ሲኖሩ ቅሬታችንን መግለጻችን ተገቢ ይመስ ለኛል፡፡ ምክንያቱም ለሀገር ሰላምም የሚበጀው ችግሮች መኖራቸውን ጠቁሞ ሕዝብም መንግሥትም መፍትሔ እየሰጣቸው ሲሔዱ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ስሜታዊ በሆነ መልክና ከጀርባው ሌላ ዓላማ ያለው እንቅስቃሴን በክርስቲያኖች ስም ማካሔድን በጽኑ የምንቃወመው ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተክርስቲያን ያለውን ተቆርቋሪነት ከግምት አስገብቶ የተለያዩ አካላት በስሜት የሚያካሒዷቸው ግልጽና ሥውር እንቅስቃሴዎችን ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳን ሳይሆን አይቀርም የሚሉ አካላት እንደሚኖሩ እናምናለን፡፡ ሌላው ቀርቶ በዓውደ ምሕረት ቆሞ ያለ ሕግና ሥርዓት የሚያስተ ምሩ መምህራንን ሁሉ የማኅበረ ቅዱሳን መምህራን ናቸው የሚሉም እንዳሉ እናውቃለን፡፡ ነገር ግን በጭፍን የሚሰጡ እነዚህን የሚመስሉ አስተያየቶች ተገቢ አይደሉም፡፡ ምክንያቱም እነዚህ አካላት ማኅበሩ ያሰማራቸው መሆን አለመሆኑን ማጣራትም ወይም ሆኖም ከተገኘ ማኅበሩ ባለው አሠራር ርምጃ እንዲወስድ ማሳሰብ የተሻለ መንገድ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ዓይነት አቋም ላይ ያለን ማኅበር አክራሪ የሚሉት አካላት ካሉ ያን ለማለት መነሻ ያደረጓቸውን ጭብጦች ማጤን ይኖርባቸዋል እላለሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ማኅበረ ቅዱሳን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ጋር ያለው ግንኙነት የሻከረ ነው፤ ማኅበሩም ለመምሪያው ለመታዘዝ ፈቃደኛ አይደለም የሚሉ አስተያየቶችም አሉ፡፡ እርስዎ እንደ ሰብሳቢ ምን ይላሉ?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ፡- ማኅበረ ቅዱሳን ሕገ ቤተክርስቲያን የቤተ ክርስቲያኒቱም ደንብና መመሪያዎች እንዲጠበቁ በጸኑ የሚሠራ ማኅበር ነው፡፡ ይህ ዋነኛ አጀንዳ ያለው አካል የማደራጃ መምሪያውን አሠራር ጠብቆ አይንቀሳቀስም ከተባለ ­ራዶክስ /መጣረስ/ ይፈጥራል፡፡ ማኅበሩ በመምሪያው የአሠራር ሥርዓት ላይ ችግር የመፍጠር ፍላጐትም ሥልጣንም የለውም ነገር ግን መምሪያውን ከሚመሩት ግለሰብ ዓላማና አቅም ላይ ግን ጥያቄ አለው፡፡ መከሩ ብዙ ሠራተኞቹ ግን ጥቂት በሆኑበት ቤተክርስቲያን ውስጥ ለአገልግሎት የተሰማሩ ማኅበራት እና ሰንበት ት/ቤቶችን በመምራት ረገድ የሚከተሉት የራሳቸው ፖሊሲ  እንደተመሪ /ባለድርሻ/ ምቹ አይደለም፡፡ ማኅበሩ ላይ አሉ የሚሏቸውን ችግሮች በውይይትና በክርስቲያናዊ የምክክር ሥርዓት ከመፈጸም ይልቅ በግልጽና በስውር የማኅበሩን ስም ማጥፋትን ሥራዬ ብለው ይዘዋል፡፡ የተለያዩ አካላትም በማኅበሩ ላይ የተዛባ አመለካከት እንዲኖራቸው ያላ ሠለሰ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ማኅበሩ ችግር አለበት፤ ለመምሪያውም አይታዘዝም… ወዘተ የሚለውን የራሳቸውን ሓሳብ መነሻ አድርገው የሚጽፏቸውን ደብዳቤዎች ምስክር እያደረጉ መናፍቃን ደግሞ በመጻሕፍት አሳትመው ሲሰድቡን እያየን ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን እያየን ማኅበረ ቅዱሳንን ከሚጠሉ መናፍቃን ጋር እርሳቸው ተመጋግበው እየሠሩ ነው ላለማለት ዋስትና አይሰጥም፡፡ የማኅበሩ አሠራር ችግር አለበት ብለው ቢያስቡ እንኳን ከሠሯቸው በጐ ተግባራት፣ የወጣት ምሁራን ክርስቲያኖች እንቅስቃሴን አስፈላጊነትና አሁን ቤተክርስቲያን ከአጽራረ ቤተ ክርስተያን በኩል እየደረሰበት ካለው ፈተና አንጻር በስብከተ ወንጌል ረገድ ያለውን ርምጃ በመመልከት ችግሮቹን ከሚመለከታቸው ከተለያዩ አካላት ጋር ተግባብቶ በመፍታት ግልጽ አሠራር ማስፈን ይገባቸው ነበር፡፡ ያንን አላደረጉም፡፡ ስለዚህ በአንዳንድ ማኅበሩ የአሠራር ችግሮች እንዳሉበት ለመምሪያውም እንደማይታዘዝ አድርጐ በማናፈስ ሺሕዎች የተሰለፉለትን ቤተክርስቲያን የመጠበቅ ተልእኮ ማነቆ እንዲያጋጥመው እያደረጉ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በግለሰቡ ተልእኮ ላይ ማኅበሩ ጥርጣሬ እንዲያድርበት ሆኗል፡፡ ማኅበሩ ለ17 ዓመታት ከተለያዩ መምሪያ ሓላፊዎች ጋር በምክክር ሠርቷል፡፡ ውጤትም ማስመዝገብ ችሏል፡፡ እኛ ጥያቄያችን ዛሬ እርሳቸው ያገኙት አዲስ ነገር ምንድነው የሚል ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የመምሪያው ዋነኛ ጥያቄ የማኅበሩን ገንዘብና ንብረት ኦዲት በመደረጉ ጉዳይ ነው፡፡ ማኅበሩ በዚህ ላይ ያለው አቋም  ምን ስልሆነ ነው ችግሮች የተፈጠሩት?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ- ማኅበራችን ለአገልግሎት የሚያስፈልገውን ከፍተኛ ገንዘብ በሀገር ውስጥና ከውጪ ሀገር ካሉ ከማኅበሩ አባላት የሚያገኘው በማኅበሩ የውስጥ ኦዲተሮች የሚሠሩት ሪፖርት ተአማኒነት ስላለውና የሚታዩ ውጤታማ ክንውኖችን መሠረት አድርጐ ነው፡፡ የኦዲት ሪፖርቱ የማይታመንና ግልጽነት የጎደለው ከሆነና ሥራችንም በጎና ውጤታማ ባይሆን ለቀጣዩ ተግባሮቻችን የሚሆን የገንዘብ መዋጮን መሰብሰብ ባልቻልን ነበር፡፡ ስለዚህ አባላቱ መዝናናት ሳያምራቸው በመጠን እየኖሩ ለቤተ ክርስቲያን ከሚከፈሉት ዓሥራት በኩራት ተጨማሪ ለማኅበሩ አገልግሎት  የሚሰጡትን ገንዘብ፣ ጊዜና ንብረት በአግባቡ መያዝ የእያንዳንዱ አባል ሓላፊነት ያለባቸው አካላት ሁሉ ግዴታ ነው፡፡ ለዚህ ዋስትና የሚሰጠው ደግሞ የኦዲት ሥራው ነው፡፡ ስለዚህ የኦዲት ሥራን ለማኅበራችን ደኅንነት እንደ አንድ ግብ የምናስብ ነን፡፡ ቅዱስ ጳዉሎስ «ስለዚህ ለጋስ ስጦታ ማንም እንዳይነቅፋችሁ ተጠንቀቁ» ያለውን ቃሉን ሁሌ እናስባለን፡፡ ስለዚህ በየጊዜው የኦዲት ሥራዎች የውስጥ ኦዲተሮቻችን ይደረጋሉ፡፡ ያንን አለማድረጋችን ከማደራጃ መምሪያው ይልቅ የሚጐዳው ማኅበሩን ስለሆነ ስለነገሩን ሳይሆን ስለሚያስፈልገን መቼም ቢሆን እናደርገዋለን፡፡ ማኅበሩ በጠቅላላ ጉባኤው የቤተክርስቲያን መምሪያ ሓላፊዎች ባሉበት የሂሳብ ሪፖርት ያቀርባል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም ሆነ የሚመለከተው አካል የሂሳብ ሪፖርቱ አላረካኝም በውጪ ኦዲተር ይቀርብ ብሎን አያውቅም፡፡ ጥያቄው ከቀረበ ምንግዜም ማድረግ ይቻላል፡፡

አሁን ግን የተሻለ አደረጃጀትና ሰፊ አገልግሎት በሀገር ውስጥና በውጪም መስጠት ስንጀምር መምሪያው በማኅበሩ አገልግሎት የማይደሰቱ ግለሰቦች እና አካላት ጉዳይ አስፈጻሚ ሆኖ መገኘቱ በእጅጉ ያሳስበናል፡፡ ከምንም በላይ ደግሞ የመመሪያ ሓላፊው የእኛን ስም ለማጥፋት በመ ጠመዳቸውና ጊዜያቸውን ለዚያ እየሠው በመሆኑ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሰ/ት/ቤቶች ከመምሪያው የሚፈልጉትን ያህል ድጋፍ ለማግኘታቸው ከፍተኛ ጥርጣሬ አለን፡፡ ከሁሉ በላይ ሊያሰጨንቀን የሚገባ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት እንጂ ሌላ አልነበርም በእኛ በኩል ግን የሚጠበቅብንን በማድረግ መልካም ግንኙነት እንዲኖረን ሁሌም እንሻለን፡፡ ችግራችንም ከመዋቅሩ /ከመምሪያው/ ጋር ሳይሆን ከመምሪያው ሓላፊ ጋር መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡