የኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠርና አጠቃቀሙ ክፍል 2

 መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም.

ዲ/ን ኃ/ኢየሱስ ቢያ

 

መጥቅዕ እና አበቅቴ ከየት መጣ ቢሉ

  1.  የፀሐይና የጨረቃ ቀን አቆጣጠር ልዩነት ነው፡፡ አንድ ዓመት በፀሐይ 365 ቀን ከ15 ኬክሮስ ሲሆን በጨረቃ 354 ቀን ከ22 ኬክሮስ ነው፡፡ ስለዚህ የሁለቱ ልዩነት 365 – 354 = ይህ ልዩነት አበቅጽ ተባለ፡፡

  2.  ሁለተኛው የቅዱስ ዲሜጥሮስ ሱባኤ ውጤት ነው፡፡ በዓላትና አጽዋማት የሚውሉበት ቀን በጥንተ ዕለቱ እንዲውል ለማድረግ ይመኝ ነበርና ከሌሊቱ 23 ሱባኤ ከቀኑ 7 ሱባኤ ገብቷል፡፡ ይህንን 23×7=161 ይሆናል፡፡ 161 ሲካፈል ለ30= 5 ይደርስና 11 ይተርፋል ይህን ቀሪ አበቅቴ አለው፡፡ 7 x7 = 49 ይሆናል፡፡ 49 ለ 30 ሲካፈል 1 ጊዜ ደርሶ 19 ይቀራል ይህን ቀሪ መጥቅህ አለው፡፡

– ዓመተ ዓለሙን

– ወንጌላዊውን

– ዕለቱን

– ወንበሩን

– አበቅቴውን

– መጥቁን

– መባጃ ሐመሩን

– አጽዋማትን

በዓላትን ለይቶ ለማወቅ ሒሳባዊ ሰሌቱ እንዲሚከተለው ነው፡፡ 

1. ዓመተ ዓለሙን ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ኩነኔ ሲደመር ዓመተ ምሕረት እኩል ይሆናል ዓመተ ዓለም፡፡ ምሳሌ 5500 + 2006= 7500 ዓመተ ዓለም ይባላል

2. ወንጌላዊውን ለማግኘት ስሌቱ፡- ዓመተ ዓለሙን ለአራት ማካፈል ማለትም ሰባት ሺህ አምስት መቶ ስድስት ለአራት ሲካፈል ለአንድ ወንጌላዊ አንድ ሺህ ስምንት መቶ ሰባ ስድስት ደርሶ ሁለት ይተርፋል፡፡ ዘመኑ ዘመነ ማርቆስ ይባላል፡፡
ዓመተ ዓለሙ ለ4 ተካፍሎ፡-

– ቢቀር ማቴዎስ

– ቢቀር ማርቆስ

– ቢቀር ሉቃስ

እኩል ሲካፈል ዮሐንስ ይሆናል፡፡

3. ዕለቱን/መስከረም 1 ቀንን ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ዓለም ሲደመር መጠነራብዒት /ለአንድ ወንጌላዊ የደረሰውን/ ሲካፈል ለሰባት ለምሳሌ ሰባት ሺህ አምስት መቶ ስድስት ሲደመር አንድ ሺህ ስምንት መቶ ሰባ ስድስት እኩል ይሆናል ዘጠኝ ሺህ ሦስት መቶ ሰማንያ ሁለት፡፡ ይህን ለሰባት ሲያካፍሉት ዘጠኝ ሺህ ሦስት መቶ ሰማንያ ሁለት ለሰባት ሲካፈል አንድ መቶ ሰላሳ አራት ደርሶ ሁለት ይቀራል፡፡

ዓመተ ዓለሙና መጠነ ራብዒት ተደምሮ ለሰባት ተካፍሎ

1. ቢቀር ማክሰኞ

2. ቢቀር ረቡዕ

3. ቢቀር ሐሙስ

4. ቢቀር ዓርብ

5. ቢቀር ቅዳሜ

6. ቢቀር እሑድ

እኩል ሲካፈል ሰኞ ይሆናል፡፡ ስለዚህ የዘንድሮው ቀሪ 2 ስለሆነ ዕለቱ ረቡዕ ነው፡፡

4. ተረፈ ዘመኑን /ወንበሩን/ ለማግኘት ስሌቱ ዓመተ ዓለሙ ለሰባት ተካፍሎ ቀሪው ተረፈ ዘመን/ ወንበር ይባላል፡፡ ከቀሪው ላይ ስለተጀመረ ተቆጠረ ስላልተፈጸመ ታተተ/ ተቀነሰ ብሎ አንድ መቀነስ ቀሪው ወንበር ይባላል፡፡
ለምሳሌ፡- 7506፥7=395 ደርሶ 1 ይቀራል 1-1=0 ዘንድሮ ወንበሩ ዜሮ ሆነ ማለት ነው፡፡

5. አበቅቴን ለማግኘት ስሌቱ ወንበር ሲባዛ በጥንት አበቅቴ /11/ ሲካፈል ለሰላሳ ቀሪው አበቅቴ ይባላል፡፡ የዘንድሮ ወንበሩ ዜሮ ስለሆነ በአሥራ አንድ ሲባዛ ውጤቱ ዜሮ በመሆኑ አበቅቴ ዜሮ/አልቦ/ ነው፡፡

6. መጥቅዕን ለማግኘት ስሌቱ ወንበር ሲባዛ በጥንተ መጥቅዕ /19/ ሲካፈል ለሰላሳ ቀሪው መጥቅዕ ይባላል፡፡ የዘንድሮ ወንበሩ ዜሮ/አልቦ ስለሆነ በአሥራ ዘጠኝ ሲባዛ ውጤቱ ዜሮ/አልቦ በመሆኑ መጥቅዕ ዜሮ/አልቦ ነው፡፡
እዚህ ላይ ስትደርስ አዋጁን ተመልከት

አዋጁ/መመሪያው – መጥቅዕ ከ14 በላይ ከሆነ በመስከረም ይውላል የመስከረም ማግስት/ሳኒታ የካቲት ነው፡፡

– 14 ራሱ መጥቅዕ መሆን አይችልም፡፡

– መጥቅዕ ከ14 በታች ከሆነ በጥቅምት ይውላል የጥቅምት ማግስት/ሳኒታ ጥር ነው፡፡

– መጥቅዕ ሲደመር አበቅቴ ሁል ጊዜ 30 ነው፡፡

– መጥቅዕ አልቦ ዜሮ ሲሆን መስከረም 30 የዋለበት የቀኑ ተውሳክ መባጃ ሐመር ይሆናል፡፡

7. መባጃ ሐመርን ለማግኘት ስሌቱ የዕለት ተውሳክ ሲደመር መጥቅዕ ሲካፈል ለሰላሳ ይሆናል፡፡ ለ30 መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል፡፡
ስለዚህ ዘንድሮ መጥቅዕ አልቦ ስለሆነ መስከረም ሰላሳ የዋለበት ዕለት ሐሙሰ ነው፡፡ የሐሙስ ተውሳክ 3 ነው፡፡ ሦስት ከዜሮ ጋር ተደምሮ ለ30 መካፈል ስለማይችል እንዳለ ይወሰዳል፡፡ ስለዚህ መባጃ ሐመሩ 3 ነው፡፡ ከዚህ በኋላ የአጽዋማትና የበዓላትን ተውሳክ እየደመርክ አውጣ፡፡

8. ጾምን ለማግኘት ስሌቱ መባጃ ሐመር ሲደመር የጾም ተውሳክ ሲካፈል ለሰላሳ ይሆናል /ለ30 መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወሰዳል/

9. በዓልን ለማግኘት ስሌቱ መባጃ ሐመር ሲደመር የበዓል ተውሳክ ሲካፈል ለሰላሳ ይሆናል፡፡ /ለ30 መካፈል ካልቻለ እንዳለ ይወስዳል

በዚህ መሠረት የ2006 ዓ.ም. አጽዋማትና በዓላትን አውጣ

1. ጾመ ነነዌ = 3 + 0=3 የካቲት 3 ቀን ሰኞ ይውላል፡፡

2. ዐቢይ ጾም = 3 + 14 = 17 የካቲት 17 ቀን ሰኞ ይውላል፡፡

3. ደብረ ዘይት = 3 + 11= 14 መጋቢት 14 ቀን እሑድ ይውላል፡፡

4. ሆሣዕና = 3 + 2= 5 ሚያዚያ 5 ቀን እሑድ ይውላል፡፡

5. ስቅለት = 3 + 7= 10 ሚያዚያ 10 ቀን ዓርብ ይውላል፡፡

6. ትንሣኤ = 3 + 9= 12 ሚያዚያ 12 ቀን እሑድ ይውላል፡፡

7. ርክበ ካህናት = 3 + 3= 6 ግንቦት 3 ቀን ረቡዕ ይውላል፡፡

8. ዕርገት = 3 + 18= 21 ግንቦት 21 ቀን ሐሙስ ይውላል፡፡

9. ጰራቅሊጦስ = 3 + 28= 31 – 30 = 1 ሰኔ 1 ቀን እሑድ ይውላል፡፡

10. ጾመ ሐዋርያት = 3 + 29= 32 – 30= 2 ሰኔ 2 ቀን ሰኞ ይውላል፡፡

11. ጾመ ድኅነት = 3 + 1= 4 ሰኔ 4 ቀን ረቡዕ ይውላል፡፡

ሃሌ ሉያ ባዘ ንዜከር ሐሰበተ ሕጉ

ወትዕዛዛትሁ ለእግዚእነ ወአምላክነ ወመድኀኒነ ኢየሱስ ክርስቶስ

ሐሳበ ነቢያት ወሐዋርያት

ሐሳበ ጻድቃን ወሰማዕታት

ሐሳበ ደናግል ወመነኮሳት

ሐሳበ ኄራን መላእክት እንዘ ሀሎነ በዘመነ ቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ ቡሩክ ያበጽሐነ እስከ ዘመነ ቅዱስ ሉቃስ ፍስሐ ዘናዊ በሰላመ እግዚአብሔር አሜን፡፡

በሃምሳ ምዕት ወበ ሃምሳቱ ምዕት ኮነ ዓመተ ኩነኔ ዓመተ ፍዳ፡፡ /5500/

በሰብአ ምዕት ወበሃምስቱ ምዕት ወስድስቱ ኮነ ዓመተ ዓለም /7506/

በእስራ ምዕት ወስድስቱ /2006/ ኮነ ዓመተ ምሕረት ዮም ሠረቀ ለነ ሠርቀ ወርህ መስከረም ቡሩክ ያብጽሐነ እስከ ወርኃ ጥቅምት በሰላመ እግዚአብሔር አሜን፡፡

ረቡዑ ሠረቀ ዕለት /ዕለቱ ረቡዕ/

አሚሩ ሠረቀ መዓልት /ቀኑ አንድ/

ሰኑዩ ሠርቀ ሌሊት /ሌሊቱ ሁለት/

ስድሱ ሠርቀ ወርኅ /በጨረቃ ስድስት ሆነ ማለት ነው/

ስብሐት በል ቀጥሎም አቡነ ዘበሰማያት በል

 

የሌሊት አቆጣጠር ስሌቱ

– አበቅቴ ሲደመር ህፀፅ ሲደመር መዓልት እኩል ይሆናል ሌሊት፡፡

የጨረቃ አቆጣጠር ስሌቱ

– አበቅቴ ሲደመር ህፀፅ ሲደመር መዓልት ሲደመር ጨረቃ እኩል ይሆናል የጨረቃ ሌሊት፡፡

አበቅቴ የተረፈ ዘመን ቁጥር ነው፤ ህፀፅ ጨረቃ ጠፍ ሆና የምታድርበት ሌሊት ነው፡፡ አንድ ጊዜ 29/30 ስለምትሆን የሁለት ወር ህፀፅ አንድ ነው፡፡ መዓልት ከ1-30 ያለው የወሩ ቀን የደረሰበት ዕለት ነው፡፡ የጨረቃ ህፀፅ ሁል ጊዜ 4 ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር