ታላቁ ጾም(ለሕፃናት)

መጋቢት 11 ቀን 2005 ዓ.ም.


ቤካ ፋንታ

ልጆች እንኳን ለጌታችን ጾመ ሁዳዴ በሰላም አደረሳችሁ? ልጆች ዛሬ ስለ ጾም እንማራለን፡፡

ልጆችዬ በዚህ ወቅት የምንጾመው ጾም ብዙ ስሞች አሉት፡፡ እነርሱም፡- ዐቢይ ጾም ሁዳዴ የጌታ ጾምም ይባላል፡፡ የምንጾመውም ለሃምሳ አምስት ቀናት ያህል ነው፡፡

ይህንን ጾም እንድንጾም ያስተማረን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ቆሮንቶስ ወደ ሚባል ትልቅ ገዳም ደረሰና ምግብ ሳይበላ፣ ውኃ ሳይጠጣ፣ አርባ ቀንና አርባ ሌሊት ጾመ፡፡ ልጆችዬ ጾም ማለት ውኃ ሳንጠጣ፣ ምግብ ሳንበላ እስከ ዘጠኝ ሰዓት መቆየት ማለት ነው፡፡ በተጨማሪም ሥጋ፣ ቅቤ፣ ወተት፣ እንቁላል…. የመሳሰሉ ምግቦችን የጾሙ ቀናት እስኪያልቅ ድረስ አይበላም፡፡

ጌታችን በገዳም ውስጥ ሆኖ ለአርባ ቀናት ሲጾም ከእርሱ ጋር ማንም አልነበረም፡፡ ረሀቡን ችሎ፣ ውኃ ጥሙን ችሎ ከጾመ በኋላ ጠላታችን ሰይጣን ሊፈትነው ወደ አምላካችን መጣ፡፡

 

ወደ አምላካችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ቀርቦ በምግብ ሲፈትነው ፈጣሪያችን ክርስቶስ ድል አደረገው፡፡ ከዚያ ለሁለተኛ ጊዜ መጥቶ ለምን ፈተነው? ሲፈትነው ትእቢተኛነት ጥሩ እንዳልሆነ ነግሮት እንደገና አሸነፈው፡፡ በመጨረሻም ሰይጣን በዓለም ውስጥ ያለውን ገንዘብ፣ ወርቅ፣ ጌጣጌጥ ሁሉ እያሳየው “እኔን ብታመልከኝ ለእኔም ብትሰግድልኝ የምታየውን ሁሉ ወርቁን፣ አልማዙን፣ ብሩን… እሰጥሃለሁ” አለው፡፡ ጌታችንም ሰይጣንን እንዲህ አለው “ሂድ፥ አንተ ሰይጣን ለእግዚአብሔር ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ ተብሎ ተጽፎአል” ብሎ ሦስት ጊዜ አሸነፈው፡፡ ከዚያ ሰይጣን ተሸንፎ ሄደ፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ 40 ቀንና 40 ሌሊት ጾሞ ሰይጣንን ስላሸነፈ እኛም በየዓመቱ ሰይጣን እንዳያሸንፈን እንጾማለን፡፡

ልጆችዬ ከአምላካችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ምን ተማራችሁ? እኔ የተማርኩትን ልንገራችሁና እናንተ ደግሞ የተማራችሁትን ትነግሩኛላችሁ፡፡

  1. ጾምን በአግባቡ መጾም እንዳለብኝ ተምሬአለሁ፡፡

  2. ወደ ቅዱሳት ገዳማት በመሄድ በዚያ መጸለይ፣ መጾም፣ እግዚአብሔርን ማመስገን እንደሚገባኝ ተምሬአለሁ፡፡

  3. ከጾምኩኝና ክፉ ነገር ካላደረኩኝ ሰይጣንን ማሸነፍ እንደምችል እግዚአብሔር አስተምሮኛል፡፡

ልጆችዬ መልካም የጾም ጊዜ ይሁንላችሁ፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ከጾሙ በረከትን ያድለን አሜን፡፡