ወርኀ ጳጉሜን

የዘመናት ባለቤት ቅዱስ እግዚአብሔር ከሥነ ፍጥረት ጀምሮ ጨለማንና ብርሃንን እያፈራረቀ፣ ቀናትን በቀናት እየተካ፣ ሳምንታት፣ ወራት፣ ዓመታት፣…  በማፈራረቅ ከዘመን ዘመን እንሸጋገራለን፡፡ አንዱ ሲያልፍ ሌላው እየተተካ እንደ በደላችን ሳይሆን እንደ አምላካችን እግዚአብሔር ቸርነት መሸጋገራችንን ቅዱስ ዳዊት “በቸርነትህ ዓመታትን ታቀዳጃለህ፣ ምድረ በዳዎችም ጠልን ይጠግባሉ” በማለት ገልጾታል /መዝ.፷፬፥፲፩/፡፡

እንደ ቅድስት ኢትዮጵያ የዘመን ቀመር ፲፫ ወራት ይፈራረቃሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አንዱ የጳጉሜን ወር (አምስቱን ቀናት ወይም ስድስት ቀናት በአራት ዓመት) ፲፫ኛው ወር አድርጋ ትቆጥረዋለች፡፡

የጳጉሜን ትርጒም አስመልክቶ ደስታ ተክለ ወልድ ዐዲስ የአማርኛ መዝገበ ቃላት በሚለው መጽሐፋቸው “ጳጉሜን የወር ስም፣ ዐሥራ ሦስተኛ ወር፣ ተረፈ ዓመት፣ በነሐሴ መጨረሻ በሦስት ዓመት አምስት አምስት፤ በዐራት ዓመት አንድ ጊዜ ደግሞ ስድስት የሚሆን ሲሆን፤ ትርጓሜውም ጭማሪ ማለት ነው፡፡” (ገጽ ፲፪፻፳፰) በማለት ይፈቱታል፡፡

በዚህ ወር ጳጉሜን ሦስት ቀን ቤተ ክርስቲያን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል በዓለ ሢመትን ታከብራለች፡፡

እንዲሁም በዚህች ዕለት ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል በእርሱ ስም ከደሴት ላይ የተሠራችውን ቤተ ክርስቲያን ዓሣ አንበሪ ሊገለባብጣት፣ ሕዝቡንም ሊያጠፋቸው ሲል በቅዱስ ሩፋኤል ጸሎት፣ ምልጃና ተራዳኢነት በእግዚአብሔርም ቸርነት እንደተረፉ በድርሳነ ሩፋኤል ተጽፎ እናገኛለን፡፡ ስለሆነም ይህ ወር የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል በዓል የሚከበርበት መሆኑን ያስታውሰናል፡፡

በወርኀ ጳጉሜን ሰዎች የፈቃድ ጾም ይጾማሉ፣ ጠበል ይጠመቃሉ፡፡ ጾሙን የሚጾሙበት ምክንያት በዮዲት ጾም እስራኤላውያን ከጦርነት፣ ከመከራ የዳኑበትን ምክንያት በማድረግ ጾመውታልና ዛሬ ደግሞ የሚጾሙት አዲሱን ዓመት የሰላም እንዲያደርግላቸው ነው፡፡ ዮዲት ከ፮፻፭ እስከ ፭፻፷፪ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በባቢሎን በከለዳውያን የነገሠው ናቡከደነፆር የተባለው ኃያል ንጉሥ በነበረበት ዘመን የተገኘችና ሕዝበ እስራኤልን በቅኝ እንዳይገዛ ቅድስቲቱን ከተማ ኢየሩሳሌምና ቤተ መቅደሱንም እንዳያጠፋ ትልቅ ተጋድሎ የፈጸመች እስራኤላዊት ሴት ነች፡፡

እግዚአብሔር በቸርነቱ መፍትሔ ይሰጣቸው ዘንድ በጾም፣ በጸሎት፣ በልቅሶም ልመናዋን አቀረበች፡፡ እግዚአብሔርም የመፍትሔውን አቅጣጫ አመለከታት፡፡ ለጦርነት የወጣውንም የናቡከደነፆር ቢትወደድ የሆነውን ሆሎፎርኒስን ሰይፈ አንስታ አንገቱን ቆረጠች፡፡ ሕዝቦችዋንና ቅድስቲቱንም ከተማ ከጥፋት ታደገች፡፡

ዛሬም ምእመናን የዮዲትን ጾምና ጸሎት ሰምቶ ኢየሩሳሌምንና ሕዝቦችዋን ከጥፋትና ከመከራ እንደዳናቸው ያለፈ በደላቸውን ደምስሶላቸው አዲሱን ዘመን የደስታና የተድላ፣ የድልና የስኬት፣ የቅድስናና የበረከት ያደርግላቸው ዘንድ የፈቃድ ጾም ይጾማሉ፡፡

በዚህ የጳጉሜን ወር አምስቱንም /ስድስቱንም/ ዕለታት ምእመናን ጠበል ይጠመቃሉ፡፡ ጠበል መጠመቁ ሃይማኖታዊም፤ መጽሐፍ ቅዱሳዊም ነው፡፡ ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በድንግል ማርያም፣ በጻድቃን፣ በሰማዕታት፣ በመላእክት፣ በአጠቃላይ በቅዱሳን እና በእግዚአብሔር ስም በፈለቀ ጠበል ላይ ጥምቀትን ያከናውናሉ፡፡

በገጠሩ የሀገራችን ክፍልም በአዲስ ዓመት ዋዜማ ሌሊት ምእመናን አቅራቢያቸው ወደሚገኘው ወንዝ ወርደው ይጠመቃሉ፡፡

ይህ የጳጉሜን ጠበል የመጠመቁ ሃይማኖታዊ ምክንያትን ስንመለከት፡-

የመጀመሪያው ከበሽታ ለመዳን ምእመናን ይጠመቃሉ፡፡  ሰዎች በሥጋዊ ሕመም ሲያዙ ጠበል ተጠምቀው ከሕመማቸው ይፈወሳሉ፡፡ ከብሉይ ኪዳን ታሪክ ብናስታውስ ንዕማን በዮርዳኖስ ጠበል ተጠምቆ ከበሽታቸው ተፈውሷል፡፡ (፩.ነገ.፭፥፩)፡፡ ኢዮብም እንዲሁ በዮርዳኖስ ተጠምቆ እንደተፈወሰ መምህራን በትርጓሜ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡

ሁለተኛው ቅዱስ ዮሐንስ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሓ ግቡ፤ ተራራው ይስተካከል፤ ጎድጓዳው ይሙላ፤ የእግዚአብሔርን መንገድ ጥረጉ፤ ልባችሁን ከኃጢአት ከጣዖት አጽዱ፤ ሰውነታችሁን ለክርስቶስ ማደሪያነት አሰናዱ” እያለ ያስተምርና የንስሓ ጥምቀት ያጠምቅ ነበር፡፡ ዛሬም ይህን ለማስታወስ ምእመናን በጳጉሜን ወር ይጠመቃሉ፡፡

ሦስተኛው በንጹሕ ሰውነት አዲስ ዓመትን ለመቀበል ሲሉ ይጠመቃሉ፡፡ የእግዚአብሔርን በዓል ሰውነትን ታጥቦ፣ ንጹሕ ልብስ ለብሶ ማክበር ተገቢ ነው፡፡ ይኸውም ለበዓሉና ለበዓሉ ባለቤት ያለንን ክብር ያስረዳል፡፡ ሥርዓቱም በብሉይ ኪዳን ሲደረግ የነበረ ነው፡፡ ሊቀ ነቢያት ሙሴ ከእግዚአብሔር የተቀበለውን እንመልከት፡፡ “ውረድ ዛሬና ነገ ራሳቸውን ያነጹ፤ ልብሳቸውንም ያጥቡ ዘንድ ሕዝቡን እዘዛቸው፡፡ በሦስተኛውም ቀን ሕዝቡ ሁሉ ሲያዩ እግዚአብሔር በሲና ተራራ ላይ ይወርዳልና ለሦስተኛው ቀን ተዘጋጅተው ይጠብቁ” (ዘፀ. ፲፱፥፲-፲፩) እንዲል፡፡

ምእመናን ዓመቱን ሙሉ የተለያየ ኃጢአትን ሲሠራ የቆየ ሰውነትን ለመገሰጽ፣ በደልን እያሰቡ በዕንባና በዋይታ፣ በንስሓ፣ እየጾሙ፣ እየጸለዩና እየሰገዱ አምላካቸውን ይማጸናሉ፡፡ አዲሱን ዓመት በአዲስ ማንነትና ስሜት እንዲሁም ባለፈው ዓመት ያላሳኩትናን ያልሠሯቸውን ሥራዎች ለማሳካት ዕቅድ የሚያወጡበት ወር ነው፣ ጳጉሜን፡፡

ስለዚህ የበደልነውን ክሰን፣ ከንስሓ የራቀውን ማንነታችንን ገልጠን በአባቶቻችን ፊት ቀርበን፣ ንስሓ ገብተን አዲሱን ዓመት እንቀበል ዘንድ ከሁላችን ይጠበቃል፡፡ ዘመን ያረጀው ዓመት በአዲስ ሲተካ እኛም ደግሞ በኃጢአት ያደፈውን ሰውነታችን አንጽተን መቅረብ ይጠበቅብናል፡፡ ይህንን እንድናደርግ እግዚአብሔር አምላካችን በቸርነቱ ይርዳን፡፡

 

 

“በልቅሶ የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ”(መዝ.፩፻፳፭:፭)

በመምህር ፍቃዱ ሳህሌ

ክፍል ሁለት

የተከበራችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች፡- በክፍል አንድ ዝግጅታችን ቅዱስ ዳዊት “በልቅሶ የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ” በማለት የተናገረበትን ምክንያት በተብራራበት ጽሑፋችን ስላለፈው ዘመን መናገሩን ገልጸን ቀሪውን በክፍል ሁለት እንደምናቀርብ በገባነው ቃል መሠረት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡-

ለ. ስለ ጊዜው ተናግሮታል፡-

ስለ ጊዜው ተናግሮታል ስንል ቅዱስ ዳዊት በነበረባቸው ዘመናት ስለተፈጠረው ክስተት የተናገረውን የሚያመላክት ነው፡፡ በአንደበቱም ሆነ በድርጊቱ ምንም የበደለው ነገር ባይኖርም ንጉሡ ሳዖል በቅንዓት ሰይጣናዊ ተነሣስቶ ቅዱስ ዳዊትን ብዙ ጊዜ አሳዶታል፡፡ እግዚአብሔር አዳነው እንጂ ሁለት ጊዜ ጦር ወርውሮበታል፣ ለዚያውም እርሱን እያገለገለ ባለበት ሰዓት፡፡ ዱር ለዱር፣ ገደል ለገደል በተሰደደበት ወቅት ውሎውና አዳሩ በልቅሶ ነበር፡፡ እግዚአብሔር እጁ ላይ የጣለለት ቢሆንም ክፉን በክፉ ሊቃወም፣ የሚያሳድደውን ሳዖልን ሊገድለው አልፈለገም፡፡ ኃዳጌ በቀልነቱ ንጽሕናውና ፍቅሩ፣ ቅንነቱና ደግነቱ እንዲሁም እግዚአብሔርን መፍራቱ ከልቅሶው ውስጥ የተሸከመው ፍሬ/ዘር/ ነበርና፡፡

ቅዱስ ዳዊት የገዛ ልጁ አቤሴሎም በተነሣበት ወቅት ተመሣሣይ የመከራ ሕይወትን ከመንፈሳዊነቱ ጋር አስተናግዷል፡፡ በሁለቱም የመከራ ጣሮች ላይ ቅዱስ ዳዊትን ያቆየው በእግዚአብሔር ቸርነት የተዘጋጀ የበረከት ነዶ ነው፡፡ ያንን ተሸክሞ ወደ ኢየሩሳሌም በምስጋናና በደስታ ተመልሶ የነገሠው፡፡

በዚህ የነቢዩ ዳዊት ሕይወት ላለፈ፣ እያለፈ ላለና ለሚያልፍ ክርስቲያን ሁሉ ታሪኩ የሚናገረው ለማን ነው? የመጀመሪያው ለሰዎች መልካም እያደረገላቸው ቤተ ክርስቲያንም በቅንነት እያገለገለ የሚገኝ ሰው እንደ ሳዖል በሥልጣን ኮርቻ ላይ በተፈናጠጡ እኩያን ሰዎች መከራ ሊደርስበት እንደሚችል ስገነዝበን ሲሆን ክፉ ላደረጉብኝ ክፉ ላድርግባቸው ሳይልና መልካምነቱን ሳያዛባ ለሚያገለግል ሁሉ ምላሹ መንፈሳዊ ደስታን መጎናጸፍ መሆኑን ይጠቁመናል፡፡

ሁለተኛው ጉዳይ እንደ አቤሴሎም በሥጋ፣ በመንፈሳዊ ልጆቹ፣ ወንድሞቹ፣ እኅቶቹ፣ እናቶቹ፣ አባቶቹና ወገኖቹ ከሚኖሩበት ቤት፣ ከሚሠራበት ድርጅት፣ ከተቀመጠበት መንበር፣ ከሚገለገልባትና የሚያገለግልባት ቤተ ክርስቲያኑ ስደት የገጠመው የዘመኑ ዳዊት ቅዱስ ዳዊትን ተሸክሞ እያለቀሰ መከራን ከተቀበለና ከጸና እሴተ ቅዱስ ዳዊትን ተሸክሞ በደስታ እየተፍለቀለቀ ዛሬም በዚህ ነገም በወዲያኛው ዓለም በመንግሥተ ሰማያት እንዲያርፍ የሚያስገነዝበን ነጥብ ነው፡፡ በአንጻሩም ግብረ አቤሴሎምን፣ ግብረ ሳዖልን ለሚሠሩ ሥልጣናቸውንና አጋጣሚዎችን ተገን በማድረግ እውነተኛችን ለሚያሳድዱ ሰዎችም ለሕይወት የሚሆነን ተግሣጽ ነው፡፡ መልእክቱም ፍጻሜአቸውን ከእነ ሳዖል ፍጻሜ ተለይተውና ለንስሓ በሚሆን ዕንባ ታጅበው ወደ እግዚአብሔር እንዲጮኹ የሚያነቃ የጥሪ ደወል ነው፡፡ አለበለዚያ በቁማቸውም እንደ ሳዖል መንፈሰ እግዚአብሔር ተለይቷቸው መንፈሰ እርኩስ እያሰቃያቸው እንደሚኖሩ ሲያስረዳን /፩ሳሙ.፲፮፤፲፬/ አሟሟታቸውም እንደሚከፋና ፍጻሜያቸውም እንደማያምር ፍንትው አድርጎ የሚያሳይ ማነጻጸሪያ ነው፡፡ በዚህ ጉዞ ውስጥ ራስን ማየትና ማስተካክል ደግሞ ከእያንዳንዳችን የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡

ሐ. ስለ ፍጻሜው ዘመን ተናግሮታል፡-

በዚህ ንዑስ ክፍል የምናየው ከቅዱስ ዳዊት ዕረፍት በኋላ በተለይ ስለ አዲስ ኪዳን ዘመን የተናገረውን የሚያጠቃልል ነው፡፡ ከቅዱስ ዳዊት ዕረፍት በኋላ በነቢያት አባቶቻችንና ሕዝበ እግዚአብሔር ላይ የደረሰባቸው የመከራ ሕይወትና በአጸፋው ያገኙት ደስታ በይዘቱ በ”ሀ” እና “ለ” ካየናቸው ተመሳሳይ ታሪኮች ጋር የተሰናሰለ በመሆኑ የእነርሱን ትተን ስለ አዲስ ኪዳን የተነገረውን ብቻ በአጭሩ እንቃኛለን፡፡

ከአዳም ጀምሮ የነበረው የሰው ልጅ በሙሉ በአዳም በደል ምክንያት ምንም ጻድቅ እንኳን ቢሆን ገነት መግባት ሳይችል ቀርቷል፡፡ የእግዚአብሔርን ቸርነት እየጠበቀ ተስፋ ደኅንነትን ተሸክሞ በሕገ ልቡናና ሕገ ኦሪት እየተመላለሰ ወደ ሲዖል እያለቀሰ ይወርድ ነበር፡፡ በሲዖልም ዲያብሎስ መከራ እያጸናባቸው በልቅሶና በስቃይ ረጅም ዘመናትን ኖረዋል፡፡ በክህነታቸው፣ በዕጣናቸው፣ በመሥዋዕታቸው ፍጹም ድኅነትን ማምጣት ባይችሉም እያለቀሱ የተሠማሩበት የብሉይ ኪዳን የአገልግሎት ሕይወት ነዶ አዲስ ኪዳንን ተሸክመው በደስታ እንዲመለሱ አድርጓቸዋል፡፡ አዳምና ሔዋን እያለቀሱ ትተዋት የወጡበትን ገነት ደስ ብሏቸው ተመለስው ገብተውበታል፡፡ “በልቀሶ የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ” እንደተባለ በአዳም በደል ተይዘው በልዩ ልዩ ጸዋትወ መከራ እያለቀሱ የቅድስና ሕይወትን በተጋድሎ የዞሩ አበውና እመው ተስፋ ድኅነት ተሸክመው በደስታ ዐርፈዋል፡፡

የቀጠሮው ዘመን በደረሰ ጊዜ ሰው የሆነው ወልደ እግዚአብሔር ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንኑ እውነታ በተጨባጭ በመከራ ውስጥ በማለፍ ያሳየን ሲሆን “ዛሬን የሚያዝኑ ብፁዓን ናቸው፣ መጽናናትን ያገኛሉና” /ማቴ.፭፤፬/ በሚልና በመሳሰሉት የሕይወት ቃሎች በዚህ ምድር ላይ በልቅሶ የሚዘሩ ማለትም እንደ ቃሉ የሚጋደሉና ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉ ምእመናን የደስታን ፍሬ እንደሚያጭዱ አስተምሯል፡፡

ሕይወቱን ሕይወታቸው አድርገውና መከራ መስቀሉን ተሸክመው በልቅሶ የዘሩ ጻድቃን ሰማዕታት በገነት በደስታ ተሰብስበዋል፣ ብዙዎችንም በአርአያነታቸውና በቃልኪዳናቸው ሰብስበዋል፡፡ በገድል የሚታሰሩበትን እንጨት ተሸክመው ጸብአ አጋንንቱን፣ ግርማ ሌሊቱን፣ ድምፀ አራዊቱን ታግሰው ከእኩያት ፍትወታተ ኃጣውእ፣ ከዓላውያን ነገሥታት ከሰይጣን ጋር ታግለው ከፈጣሪያችን ለሁላችንም የሚተርፍ የቃልኪዳን ነዶዎችን ተቀብለው በደስታ ዐርፈዋል፡፡

ለሁላችንም መድኃኔዓለም ክርስቶስም ያሳየንና ያስተማረን በዚሁ የልቅሶ ሕይወት ውስጥ በማለፍ የደስታ ባለቤት መሆንን ነው፡፡ በኋላ በገሃነም ላለማልቀስ ዛሬ በንስሓ ማልቀስ እንደሚገባ በቅዱሳን አባቶቻችን ሕይወት ከተማርን ዘንድ በደስታ የሕይወት ፍሬ ለመስበክስ በተሰጠን ዘመን መከራ መስቀሉን ተሸክመን እናገልግል፡፡ መስቀሉን ሳይሸከሙ የሕይወት ባለቤት መሆን እንደማይቻል እግዚአብሔር በቅዱኑ ነግናል፡፡ ስለ ክርስርስቶስ መከራ ባየንባቸው፣ ባለቀስንባቸው ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተ ክርስቲያን በታመምንባቸው ዘመናት ፈንታ አምላካችን በዚሁ ጊዜ ያበቃል የማይባል ተድላ ደስታ ይሰጠናል፡፡ /መዝ.፹፱፥፲፬‐፲፭/ ከላይ ባየናቸው በ፫ቱም ሂደቶች ውስጥ የምንማረው ተጨማሪው ቁም ነገር ያለውን የሀገርና የቤተ ክርስቲያንን ታሪክ በማስታወስ ደካማውን በማሻሻል ከጠንካራው ጎን ደግሞ በመማር እምነትና ሥርዓትን፣ ታሪክንና ትውፊትን እንድንጠብቅና የአባቶቻችንና የእናቶቻችን የቀደመ ሕይወት እንዳንረሳ ነው፡፡ /ዘዳ.፴፪፤፯/ ስለዚህ ቅዱስ ዳዊት ስላለፈው ማወቅና መናገር እንደሚገባ ሲያጠይቅ ስላለፈው ተናግሮታልና፡፡ ስለ ጊዜውም አጠቃላይ የዓለም፣ የሀገርና የቤተ ክርስቲያን ጉዞ ቀርቦ መረዳትና በልቅሶ ለራስ፣ ለቤተሰብ፣ ለሀገርና ለቤተ ክርስቲን የሚጠቅሙ መልካም ዘርን መዝራት እንደሚገባና መራራ በሆነው ጉዞ ውስጥ ከማለፍ ባሻገር ያለውን ጣፋጭ ደስታ ማጣጣም እንደሚቻል ሊያመለክተን ስለ ጊዜውም ተናገረው፡፡

ለጊዜው ትውልድ ስላለፈው የልቅሶና የተጋድሎ ኑሮ ሰለተገኘው አስደሳች ሕይወት በጊዜው እሱም አባቶቹንና እናቹን መስሎ እንዲኖር በቃልም በሕይወትም ምሳሌ ልንሆን እንደሚገባ ያስረዳናል፡፡

በዚህ ሁሉ ውጣ ውረድ ውስጥ ነገን በተስፋ ከመጠበቅ በዘለለ ለነገው የተሻለና ታሪክ ተረካቢ ትውልድ መፍጠር ለነገዋ የበለጸገች ሀገር መገነትና ለነገዋ መልካም አስተዳደር የሰፈነበት፣ በልማት አድጋ መንጋዎቿን በሁሉም ዘርፍ የምትመግብ ቤተ ክርስቲያን መታየት ዛሬ ሁላችምን መከራውንና ፈተናውን ሳንሰቀቅና ሳናፈገፍግ ማገልገልና መታገል እንደሚገባ መርሳት የለብንም፡፡ ቅዱስ ዳዊት ስለሚመጣው ዘመን በመናገር ብቻ የኖረ አባት ሳይሆን በጊዜው ከእርሱ በኋላ ለሚሆነው ነገር በጾምና በጸሎት በሚችለው ሁሉ ሠርቶ አሳይቶናል፡፡ ስለ ልጁ ስለ ሰሎሞን ለሚሠራውም ቤተ መቅደስ፣ ስለ ቤተ መንግሥቱ አስተዳደርና ስለመሳሰለው ሁሉ አስፈላጊውን ሁሉ በማድረግ አርአያ ሆኖናል፡፡

እነዚህን ሁሉ ነገሮች ስንቅ አድርገን በአዲሱ ዓመት የአሮጌውን ዘመን አሮጌ ሕይወት አርቀን መልካም የሆነውን ምርኩዝ አድርገን በአዲስ ርዕይና መንፈስ ለመሥራት እንነሣ፡፡ አዲስ ዓመት አዲስ መሆንን ይሻልና፡፡ በዓመቱ መተርጎም በማይችሉ ያማሩ ዕቅዶች አዲስ ዓመትን እየተቀበልን ደግሞ በዕቅድነት እያሸጋገሩ መኖር ራስን ማሞኘት ነው፡፡ ዘመኑ ስለ ድሎቻችን የመጨረሻም ሊሆን እንደሚችል አንርሳ፡፡ እንደ ቤት ተከራይ ድንገት ውጡ/ልቀቁ/ ልንባልና ልንጠራ እንደምንችል እንዴት ልንዘነጋ እንችላለን፡፡ /ኢዮ.፰፥፱/ ስለዚህ ዘመን እንደ ሞላ ውኃ /ወንዝ/ ሳያቋርጥ እየፈሰሰ ዝም ብለን የምናይ ወይም ልቅሶንና መከራን ሸሽተን ለጊዜያዊ ደስታ ብለን ብቻ የምንሯሯጥ መሆን የለብንም፡፡ ቅዱስ ይስሐቅ “ንስሓ ያልገባሁበትን ዕለት እንደኖርኩባት አልቆጥራትም” እንዳለ በልቅሶና በመከራ ዘለዓለማዊው ደስታ ለማግኘት ያልተጋንበት ዘመን እንዳይሆን እንጠንቀቅ፡፡ መጽናናትና ደስታን ልቅሶና መከራ እንደሚቀድሙትም እናስታውስ /ኢሳ.፷፩፥፩‐፫/ ሰው የሚዘራውን ነው የሚያጭደውና፡፡ /ገላ.፮፤፯‐፲/ ቅዱስ ዳዊት እንደነገረን ደግሞ በደስታ የሚያጭዱት በፈንጠዚያ /በመቀማጠል/ የዘሩት አይደለም፡፡ ክርስቶስ እንዳስተማረን ነውና አለዘር በተለያየ መንገድ በዘህች ምድር ላይ ዘሩ በኋላም በተለያየ መንገድ አዝመራቸውን ሰበሰቡ፡፡ /ሉቃ.፲፮፥፲፱‐ፍጻሜ/ ቅዱስ ጳውሎስም “…በውርደት ይዘራል፣ በክብር ይነሣል፣ በድካም ይዘራል፣ በኃሉም ይነሣል፣ …” /፩ቆሮ.፲፭፥፵፪‐፪፫/ በማለት ስለ ትንሣኤ ሙታን ያስተማረን ትምህርት ይህንኑ የሚያጸናልን ነው፡፡ በመከራዎቻችን ውስጥ ጸንተንና ቀቢጸ ተስፋን አስወግደን ዘር ሃይማኖታችንን ተሸክመን በመልካም ምግባራት ተሰማርተን ነዶ ቃለ ሕይወትን ለመስማት አምላካችን ይርዳን፡፡ አሜን፡፡

በለቅሶ የሚዘሩ በደስታ ይሰበስባሉ (መዝ.፩፻፳፭:፭)

በመምህር ፍቃዱ ሳህሌ

ክፍል አንድ                                      

ይህ የቅዱስ ደዊት መዝሙር የመዓርግ መዝሙሮች ከሚባሉት መካከል የሚመደብ ነው፡፡ እስራኤላውያን በእግረ ሥጋ ወደ ኢየሩሳሌም፣ በእግረ ሕሊና/ነፍስ/ ደግሞ ወደ እግዚአብሔር ሲወጡ ይዘምሯቸው ስለነበር ይህን ስያሜ አግኝተዋል፡፡ “አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ” ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጠው በዚህ ኃይለ ቃል ውስጥ የምናገኛቸው ቁም ነገሮች እግዚአብሔር በምናውቀውና በምንረዳው በዕለት ተዕለት ተግባራቸው ምሳሌነት ገልጦልናል፡፡ ዛሬም በእግረ ሥጋ ብቻ ለምንመላለሰውና አንዱንም ላልያዝነው ሰዎች የሚያስተምረን ቁም ነገር አለ፡፡

ሁላችንም እንደምናውቀው የፀደዩን ክፍለ ዘመን /ወቅት/ ተከትሎ የሚመጣው የክረምት ወቅት ከሰኔ ፳፭ እስከ መስከረም ፳፭ ነው፡፡ ይህ ወቅት በርካታ ተፈጥሯዊ ክስተቶች የሚስተናገዱበት ከመሆኑም በላይ የሰብዓዊ ፍጥረት የኑሮ መሠረት የሆነው የግብርና ሥራ ሌት ተቀን የሚከናወንበት ጊዜ ነው፡፡ አሮጌው ዓመት ፋይሉን ዘግቶ ለአዲስ ዓመት የሚያስረክብበት የርክክብ ጊዜ ነው፡፡ በጥቅሉ ክረምት ሁለት እጁ መብረቅ፣ ነጎድጓድ፣ ዝናብና ነፋስ የሚበረታበት ላዩ ውኃ ታቹ ውኃ /ጭቃማና ድጥ/ የሚሆንበት፣ ተራራውና ሸንተረሩ በጉም ተጨፍኖ የሚከርምበት፣ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት በደመና ተጋርደው የሚቆዩበት፣ ውኃዎች የሚደፈርሱበት፣ ጎርፍ መሬትን የሚሸረሽርበት፣ ማዕበል ከፍ ከፍ የሚልበት ሲሆን፤ አንድ እጁ ማለትም የክረምቱ ጫፍ መስከረም ደግሞ ሰማዩ ወለል የሚልበት፣ ጨለማው ተወግዶ ፀሐይ፣ ጨረቃና ከዋክብት መግቦታቸውን በጠራ ሰማይ ላይ የሚቀጥሉበት፣ ውኆች ከድፍርስነታቸው የሚጠሩበት፣ ምድር በልምላሜና በአበቦች የምታጌጥበት፣ አእዋፍ በዝማሬ የሚደምቁበት፣ የአበቦች መዐዛ የሚያውድበት፣ ቆሻሻውና ደለሉ ተወግዶ ያረገረገው መሬት የሚጠብቅበትና ክረምት ያልተመቻቸው ወይን በለስና እምቧጮ የመሳሰሉት ዕፅዋት የሚለመልሙበት እንዲሁም በልቅሶ የዘሩ ሰዎች ያማረ ቡቃያን ከመልካሙ አበባ ጋር በማየት ደስታን መጥገብ የሚጀምሩበት ጊዜ ነው፡፡

ለመሆኑ እነዚህን ሁሉ አስደናቂ ትእይንቶች ይህ ክፍለ ዘመን /ክረምት/ ምን ሊያስተምረን ይችላል? ከላይ ለማየት እንደሞከርነው ሁሉ እግዚአብሔር በተፈጥሮ መስተጋብር ውስጥ ብዙ ነገር የሚያሳየን አንድ ቀን እንድንማርበትም ነው፡፡ ይህም በሥጋና በነፍስ ውጤታማ ለመሆን የሚረዳ ለአእምሮ የቀረበ /የተረዳ/ ጉዳይ ነው፡፡ የክረምት ሰፋ ያለ  የመጀመሪያው ንዑስ ክፍል የሁላችንንም የጨለመ፣ የደፈረሰና የተሸረሸረ ውጣ ውረድ የበዛበትና ያረገረገ /ላላ/ ሥጋዊና መንፈሳዊ ሕይወት የሚጠቁም ነው፡፡  በብልሹ አሠራር በዘረኝነት፣ በሙስና እና በሕገወጥነት ዳኝነት የተመረዘውን ሥጋዊና መንፈሳዊ አስተዳደርም ሆነ በእነዚሁ ጠንቅ የተሽመደመደውን የግልና የጋራ ክርስቲያናዊ ሕይወት የሚጠቁም መልእክት የያዘ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በሁለተኛ ንዑስ ክፍል ደግሞ ከጠቀስነው የተበላሸ ሕይወት ወዴትና እንዴት መሸጋገር እንደሚገባን ያሳየናል፡፡

በዓመቱ ውስጥ በሥጋ ፍሬዎች /በኃጢአት/ በመመላለስ ያዳጎስነውን ቡራቡሬ ወይም ጥቁር ፋይል እንዴት ለአዲስ ዓመት ማስረከብ እንዳለብንም ያመለክተናል፡፡ ተፈጥሮ እንኳን አዲሱን ዓመት አስተካክላና አስወባ ለሚኖሩባት ፍጥረታት ካቀረበች እኛ ደግሞ ምን ያህል ሰውነታችንን አስተካክለን ለአዲሱ ዕቅድ ሥራና ሕይወት ማዘጋጀት ይገባን ይሆን? በኃጢአት የጨለመ ሰውነታችንን በንስሓ ብርሃን አብርተን የተዝረከረከና የደፈረሰ ሥነ ምግባራችንን በቁርጠኝነት አጥርተን የዘረኝነት ደለል አስወግደን የውስጥ ጎርፍ የናደውን ሕይወት በሃይማኖትና በምግባር አድሰን ሰውነታችንና ቤተ ክርስቲያናችን በቅድስና መዓዛ እንድታውድ ልንነሣ ይገባል፡፡ ያልረጋ /የላላ/ መንፈሳዊ ሕይወታችንና የቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር እግዚአብሔር ጠብቆ የጠወለጉ የፍቅርና የሰላም ዛፎች አብበው እንዲታዩ ወርኃ ክረምትን አብነት አድረገን እንትጋ፡፡

ካለፉት ዓመታ በቅብብሎሽ መጥቶ በ፳፻፲፫ ዓ.ም ደግሞ የዕዳ ደብዳቤዎች ተደርቶ የተከማቸውን ፋይላችን የኃጢአት ቆሻሻ ደለል እንደተሸከመ እንዳሸጋገር ብርቱ ጥረት ማድረግ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ያለውን ሁሉ የሚመለከት ወቅታዊ ተግባር ነው፡፡ ለዚህም ነው በልቅሶና በመከራ መከፈል ያለበትን መሥዋዕትነት ሁሉ መክፈል ይጠበቅብናል፡፡ የመንፈስ ፍሬዎች በደስታ መሰብሰብና በዚህም ሆነ በወዲያኛው ዓለም ሁላችንም በገነት መንግሥተ ሰማያት መሰብሰብ የምንችለው ያኔ ነው፡፡

ነቢዩ ዳዊት በኃይለ ቃሉ ውስጥ በቀጥታ በልቅሶ የሚዘሩ ሲል፡-

፩ኛ. ከላይ በዘረዘርናቸው አስቸጋሪ የክረምት ተፈጥሯዊ ክስተት ውስጥ ራስን አሳልፎ በመስጠት መከራውን ሳይሰቀቁ አርሶ አደሮች የሚቀበሉትን የውዴታ ግዴታ ስቃይ መግለጽ ነው፡፡

፪ኛ. የከረመው እህል ከጎተራ አልቆ /ተሟጦ/ መሶቡ ጎድሎ እያለ በመጨከን ዘር ቋጥሮ ለመሬት አደራ የሚሰጥበትንና አንጀትን አሥሮ እየተራቡ የሚሠራበትን እልህ አስጨራሽ ጉዞ የሚያሳይ ነው፡፡ ገበሬው በዚህ ወቅት ከእርሻ ጀምሮ የሚታወቁትንና ከተፈጥሮ ጋር የሚያደርጋቸውን ግብግብ ነው፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን እንደተናገረው ልቅሶ በማለት የጠራው ይህንን ወቅት ነው፡፡ /መክ.፫፤፬/ አርሶ አደሩ ይህንን መሥዋዕትነት ወድዶ ፈቅዶ የሚቀበለው በመከራ ጊዜ የሚያገኘውን እጥፍ ድርብ ምርት /ደስታ/ በማስብ ነው፡፡ በኋላ ተስፋ ስለሚያደርገው ጥጋቡ በክረምት ይራባል፣ ደስ እያለው ፍሬውን ሊሰበስብ በታላቅ መከራ ውስጥ ይዘራል፡፡ ከዚህ ተጨባጭ ክስተት መማር ካልቻልን በእውነት ከምን ልንማር እንችላልን፡፡

ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት ይህን አጠቃሎ ሲያስቀምጠው “በሄዱ ጊዜ ዘራቸውን ተሸክመው እያለቀሱ ተሠማሩ በተመለሱ ጊዜ ነዶዋቸውን ተሸክመው ደስ እያለቸው ይመጣሉ” ይላል፡፡ /መዝ.፩፻፭፤፮/፡፡ በኋላ ስለሚመጣውና ስለ ዘለዓለማዊው ደስታ ዛሬ በጊዜያዊው ዓለም ውሰጥ የሃይማኖትንና የምግባርን ዘር በልቅሶና በፈተና እንዝራ፤ ሁላችንም በምናውቀው በዚህ እውነት ውስጥ እግዚአብሔር የሚያስተምረን ብዙ ነገር በቅዱስ ዳዊት አድሮ በርእሰ ጉዳያችን ያነሣነውን ኃይለ ቃል ስለ ሦስት ነገር ተናግሮታል፡፡ እነዚህ በተራ በተራ እያነሣን እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

ሀ. ስላለፈው ዘመን ተናግሮታል፡-

ነቢዩ ዳዊት ከእርሱ ዘመን በፊት ስለነበረው የእስራኤላውያን መንፈሳዊ ሕይወት የተናገረውን የሚያመለክት ነው፡፡ ሁለቱን ዐበይት ክንውኖች መነሻ አድርገን የተናገረውን እንመልከት፡-

፩ኛ. የግብፅ የባርነት ሕይወት፡- ዮሴፍ ወልደ ያዕቆብ ወንድሞቹ የሸጡት፣ ግብፅም ይባስ ብሎ የጲጢፋራ ሚስት በሐሰት ከሳው ወደ ወኅኒ ቤት የወረደው በዕንባና በታላቅ ልቅሶ ሲሆን የልቅሶ አዝመራውን የሰበሰበው ግን በቤተ መንግሥት በደስታ ነበር፡፡ /ዘፍ.፴፯፤፴፱፤ ፵፥፵፩/፡፡ አባቱ ያዕቆብና ቤተሰቡ ሁሉ ወደ ግብፅ እህል ፍለጋ የወረዱት በረሃብና በመከራ በታላቅ ልቅሶም ነው፡፡ በባዕድ ምድር የተወሰኑት አንጻራዊ የዕረፍት ዓመታት ቢኖሩም ዮሴፍን የማያውቅ ሌላ ፈርኦን ከተነሣበት ጊዜ ጀምሮ የነበረው የግብፅ ኑሮዋቸው የልቅሶና የሰቆቃ ሲሆን ኪዳነ አብርሃም፣ ይስሐቅ ያዕቆብን ያልዘነጋው አምላከችን እግዚአብሔር በጸናች እጁ፣ በተዘረጋች ክንዱ ከግብፅ የመለሳቸው /ያወጣቸው/ ደግሞ በታላቅ ደስታ ነው፡፡ በልቅሶና በመከራ ውስጥ የዘሩት ዕንባና የተቀበሉት ግፍ የደስታ ፍሬ ሲያሳፍሳቸው እንመለከታለን፡፡ በዘር የተመሰለ ተስፋ /ኪዳን/ አበውን ተሸክመውና እግዚአብሔር እንደማይተዋቸው ተማምነው እያለቀሱ ግብፅ ወረዱ፡፡

የአባቶቻቸው አምላክም አብሮአቸው በረድኤት ግብፅ ወረደ፡፡ በተመለሱ ጊዜም በነዶ የተመሰለ ተአምራት ተደርጎላቸውና ነፃነት ተጎናጽፈው ጭቃ፣ ጡብ፣ ድንጋይና የመሳሰሉትን ያለ ርኅራሄ እያሰቃየ ላሰቃዩአቸው የነበሩ ግብፃውያንን በተራቸው መሸከም የማችሉት ውኃ አሸክመው “ንሴብሖ፣ እናመስግነው” እያሉ በደስታ ወደ ምድራቸው ከነዓን ተሰበሰቡ፡፡ ባለቅኔው “አይተርፍ ግፍዕ ለዘዕድሜሁ ጎንድየ፤ አስራኤል ለፈርኦን እስመ አጸርዎ ማየ፤ የግፍ ጊዜ ቢረዝም አይቀርም እስራኤል ፈርኦንን ውኃ አሸክመውታልና” ያለውን ይህን ታሪክ ጠቅልሎ አስውቦ ያቀረበበት ምሥጢር ነው፡፡ ታሪኩ በዮሴፍ ዓይነት ሕይወት በሐሰተኛ ወንድሞቻቸውና እኅቶቻቸው ለመከራና ለሰቆቃ የተሸጡ፣ እየተሸጡ ያሉና የሚሸጡ አልፎ ተርፎም ታሪክ ተዘግቶባቸው እንኳን ሊሠሩት አስበውትም የማያውቁት ጉዳይ የመከራ እንጀራ እንዲበሉ የተፈረደባቸው ወገኖቻችን አንድ ቀን የእውነት አምላክ በደስታ እንደሚያወጣቸው ያስተምረናል፡፡

ትጋታቸውን፣ የለውጥ ርእያቸውን፣ ቅን አስተሳሰባቸውን እና ንጽሕናቸውን የማያውቁ፣ ሊያውቁ የማይወዱና እያወቁም ሰይጣናዊ ቅንዓት በልቡናቸውን ያነጹ ናቸው፡፡ አሰሪዎች አለቆች በሚፈጥሩት መሰናክል በግድ ተጠልፈው የወደቁ ብዙ ወገኖቻችን ልቅሶና ዋይታ ወደ አሸናፊ እግዚአብሔርም በተስፋ ደጅ የሚጠኑትን ልጆቹን ዕንባ የሚያብስበትንና ጠላቶቻቸውን የሚያደቅበት ጊዜ አለው፡፡ /መዝ.፻፵፮፤፲/፡፡ የዘገየ ቢመስለንም እንኳን በተሰጣቸው ጊዜ ከክፋታቸው እስኪመለሱ ወይም ኃጢአታቸውን ፈጽመው እስኪሠሯት ድረስ እየጠበቀችው እንደሆነ መሆኑን አውቆ በትዕግሥት መጽናት ከዮሴፍና ከእስራኤላውያን የምንማረው ቁም ነገር ነው፡፡

፪ኛ. የባቢሎን የምርኮ ሕይወት ማርና ወተት የምታፈሰውን ተስፋይቱን ምድር ከነዓንን ከወረሰ በኋላ ዘወትር እንዲያስታውሱትና እንዳይረሱት የተናገራቸውን የአባቶቻቸውን መከራና የእግዚአብሔርን ድንቅ ሥራ፣ የተሰጣቸውንም ትእዛዝ ዘንግተው ፈጣሪያቸውን በማሳዘናቸው እስራኤላውያን ሌላ የመከራ ዘመን ገጠማቸው፡፡ ነቢዩ ኤርምያስ ደጋግሞ ቢያስጠነቅቃቸውም ሊሰሙ ባለመፈለጋቸውና በነቢዩም ላይ በክፋት በመነሣታቸው ባቢሎናውያን ጓዝ፣ ትብትብ አሸክመው ምድራቸውን አጥፍተው እነርሱን በመማረክ ባቢሎን አወረዷቸው፡፡ ዘር ተስፋ ሚጠትን /መመለስን/ ተሸክመው እያለቀሱ ወረዱ፡፡ በታላቅ ግዞት ቀንበር ሥር ወድቀው በሰቆቃ ሰባ ዓመታትን ከኖሩ በኋላ የአባቶቻቸው አምላክ እግዚአብሔር አስቀድሞ “በልቅሶ ወጡ፣ እኔም በመጽናናት አመጣቸዋለሁ” /ኤር.፴፩፥፱/ በማለት እንዳናገረው በደስታ ሰበሰባቸው፡፡

እዚህ ላይ ልናስተውለው የሚገባው የብዙዎቻችን ድክመት ያለፈውን የመከራም ሆነ የደስታ ጊዜ መዘንጋትና ካለፈው ጥሩም ሆነ መጥፎ ድርጊት መማር አለመቻላችን ነው፡፡ ክረምት ላይ በጋን፣ በጋም ላይ ክረምትን እንረሳለን፣ ወይም አናስብም፡፡ በክረምት እያፈሰሰ ያስቸገረን የቤት ጣሪያ /ቆርቆሮ/ የምናስታውሰው ሌላኛው ክርምት ሲመጣ ነው፡፡ በበጋ ችግራችንን ሁሉ ረስተን በሌላ ጉዳይ ላይ እንጠመዳለን፡፡ በተደላደልንበት ወቅት የተቸገርንበትን፣ በጠገብንበት ወቅት የተራብንበትን፣ ባለ ሥራ በሆንበት ሰዓት ሥራ አጥ የነበርንበትን፣ በሣቅንበት ጊዜ ያለቀስንበትን … ማሰብ ካልቻልን በሌላ የመከራ ድግስ ዋዜማ መሆናችንንና በተስፋ ለመጽናትም እንደምንቸገር ያስረዳናል፡፡ አንዳንዶቻችን ለሌሎች ወገኖቻችን የማንራረውና በሚያለቅስ ዐይናቸው በርበሬ፣ በቁስላቸውም ውስጥ እንጨት የምንጨምረው የራሳችም ያለፈውን የመከራ ጉዞአችንን መለስ ብለን ለማየት ባለመፈለጋችን ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች ተጠራቅመው ወደተለየና ወደ ባሰ የመከራ አዘቅት ያወርዱናል፡፡ የእግዚአብሔር ምሕረትና ይቅርታ ግን ከሰው ግፍና ኃጢአት ይልቅ ሊነገር በማይችል መጠን ስለሚበልጥ በመከራቸው ውስጥ ሆነው በእምነት የፀፀት ዕንባቸውን ለሚረጩትና የተስፋ እጃቸውን ለሚዘረጉት ሁሉ እርሱም የቸርነት እጁን ልኮ ያወጣቸዋል፡፡ ከባቢሎን ምርኮኞች ሕይወት ያየነው ይህንን ነው፡፡

በኃጢአታቸው ምክንያት እያለቀሱ ቢወርዱም ነዶ ሚጠትን /ነፃነትን/ ተሸክመው ደስ እያላቸው ወደ ምድራቸው ተመልሰዋል፡፡ አባት የሚወደውን ልጁን እንደሚቀጣ ተቆጥቶ ቢቀጣም አምላካችን የልጆቹን የመከራ ዕንባ እያየ የሚጨክን ልብ /ባሕሪ/ የለውም፡፡ የደረሰውን መከራ እያበላለጡ ብቻ ሳይሆን ይበልጡንም ፈጣሪያችንን በደልነው፣ አሳዘንነው እያሉ በመጸጸት የሚያለቅሱ ምእመናን የእግዚአብሔርን የይቅርታ ድምጽ ለመስማትና በምሕረት እጆቹም ለመዳሰስ የቀረቡ ናቸው፡፡ “አልቦ ካልዕ ሕሊና ለአዳም ዘእንበለ ብካይ ላዕለ ኃጠአቱ፤ ለአዳም ስለ ኃጢአቱ ከማልቀስ በስተቀር ሌላ ሐሳብ የለውም” ተብሎ ለአዳም እንደተነገረ በመከራችን ውስጥ ኃጢአታችንን እያሰብን ወደ አምላካችን ልናንጋጥጥ ያስፈልጋል፡፡

ይቆየን፡፡

“አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም” (መዝ. ፻፴፩፥፰)

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

እግዚአብሔር አምላካችን አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም ከልጅ ልጅህ ተወልጄ ስደትህን በስደቴ፣ ሞትህን በሞቴ አጥፍቼ፤ የቀደመ ክብርህን መልሼ ያጣኸውን ርስት፣ ገነትን (መንግሥተ ሰማያትን) አወርስለሁበማለት ለአባታችን አዳም የገባው ቃል ኪዳን ፍጻሜው በደረሰ ጊዜ ለእግዚአብሔር ወልድ ማደሪያነት የተመረጠች፣ ለአዳም እና ለዘሩ መዳን ምክንያት የኾነች “የልጅ ልጅ” የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች፡፡ ፲፭ ዓመት ሲኾናት በቅዱስ ገብርኤል ብሥራት የእግዚአብሔር ወልድ ኢየሱስ ክርስቶስ ማደሪያ ኾነች (ገላ. ፬፥፬)፡፡ ልጇን በወለደች ወቅት የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ?”  የሚለውን የሰብአ ሰገልን ዜና የሰማው “ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኵሉ፤ ሞት ለማናቸውም ሰው የተገባ ነው፡፡ የማርያም ሞት ግን ዅሉን ያስደንቃል ሄሮድስ ሕፃኑን ለመግደል ፈለገ፡፡ እመቤታችንም ልጇ ኢየሱስ ክርስቶስን ለማዳን ወደ ግብጽ ይዛው ተሰደደች (ማቴ. ፪፥፲፪)፡፡ የስደቱ ዘመን አልቆ ወደ ኢየሩሳሌም ከተመለሱ በኋላም ኢየሱስ ክርስቶስ ፴ ዓመት ሲኾነው ስለ መንግሥተ ሰማያትና ስለ ሰው ልጆች ነጻነት ይሰብክ ጀመር፡፡ ከዚህ በኋላ የአዳምና የዘሩን ሞት ለማጥፋት በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሞተ፤ በሦስተኛው ቀን ተነሥቶ፣ ባርነትን አስወግዶ ለሰው ልጅ ነጻነትን ዐወጀ፡፡

በዚህ ዅሉ የድኅነት ጉዞ ውስጥ ያልተለየችና ምክንያተ ድኂን የኾነችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በተወለደች በ፷፬ ዓመቷ ጥር ፳፩ ቀን ዐርፋለች፡፡ ይህን የእመቤታችን ሞት የሚያስደንቅ መኾኑን ታላቁ የቤተ ክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድ በማለት ገልጾታል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት የእመቤታችንን የከበረ ሥጋዋን ገንዘውና ከፍነው ለማሳረፍ ወደ ጌቴሴማኒ መካነ ዕረፍት (የመቃብር ቦታ) ይዘው ሲሔዱ አይሁድ በቅናት መንፈስ ተነሣሥተው ቀድሞ ልጇን በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተነሣ፤ በዐርባኛው ቀን ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡እንደገናም ተመልሶ ይህን ዓለም ለማሳለፍ ይመጣል እያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ፡፡ አሁን ደግሞ እርሷንም እንደ ልጇ ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሲያውኩን ሊኖሩ አይደለምን? ! ተሰብሰቡና በእሳት እናቃጥላት” ብለው ተማከሩ፡፡

ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም የከበረ ሥጋዋን የተሸከሙበትን አጎበር (የአልጋ ሸንኮር) በድፍረት ያዘ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በእሳት ሰይፍ ሁለት እጆቹን ቆረጣቸው፡፡ እጆቹ ተንጠልጥለው ከቆዩ በኋላ በእውነት የአምላክ እናት ናት ብሎ ስለ አመነ እጆቹ ተመልሰው እንደ ነበሩ ኾነዉለታል፡፡ ከዚህ በኋላ መልአከ እግዚአብሔር የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ  ከሐዋርያው ዮሐንስ ጋር ነጥቆ ወስዶ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጠው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ ከጥቂት ወደ ሐዋርያት በተመለሰ ጊዜም የእመቤታችን የከበረ ሥጋ በገነት መኖሩን ነገራቸው፡፡ ሐዋርያትም የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አግኝተው  ለመቅበር በነበራቸው ምኞትና ጉጉት ዮሐንስ አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን? ብንጠየቅስ ምን እንመልሳለን?”  በማለት በነሐሴ አንድ ቀን ሱባኤ ጀምረው ሲጾሙና ሲጸልዩ ከሰነበቱ በኋላ በሁለተኛው ሱባዔ መጨረሻ (ነሐሴ ፲፬ ቀን) ጌታችን የእመቤታችንን ትኩስ የከበረ ሥጋ አምጥቶ ሰጥቷቸው በታላቅ ዝማሬና ውዳሴ በጌቴሴማኒ ቀብረዋታል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የእመቤታችን የቀብር ሥነ ሥርዐት ሲፈጸም አልነበረምና ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ እመቤታችን በተቀበረች በሦስተኛው ቀን  እንደ ልጇ ተነሥታ ስታርግ አገኛት፡፡ በዚህ ጊዜ ቀድሞ የልጅሽን፣አሁን ደግሞ የአንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ” ብሎ ቢያዝን እመቤታችን ከእርሱ በቀር ሌሎች ሐዋርያት ትንሣኤዋን እንዳላዩ ነግራ አጽናናችው፡፡ ወደ ምድር ወርዶ የኾነውን ዅሉ ለሐዋርያት እንዲነግራቸው አዝዛው፣ ለምልክት ይኾነው ዘንድም የተገነዘችበትን ሰበኗን ሰጥታው ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡ ቅዱስ ቶማስም ሐዋርያት ወደ አሉበት ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ የእመቤታችን ነገር እነዴት ኾነ?”  ብሎ ቢጠይቃቸው፤ እመቤታችንን እኮ ቀበርናት ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ደብቆ ምሥጢሩን አይደረግም! ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር  እንደምን ይኾናል?”  አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “አንተ መጠራጠር ልማድህ ነው፡፡ ቀድሞ የጌታን ትንሣኤ ተጠራጠርክ አሁንም አታምንም?” ብሎ የእመቤታችን መካነ መቃብር ሊያሳዩት ይዘውት ሔዱ፡፡ መቃብሩን ቢከፍቱ የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አጡት፤ ደነገጡም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሥታ ዐርጋለች ብሎ  የኾነውን ዅሉ ተረከላቸውና የሰጠችውን ሰበኗን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ማረጓን አምነው ሰበኗን ለበረከት ተከፋፍለው ወደየአህጉረ ስብከታቸው ሔዱ፡፡ በዚያም ሕሙማንን ሲፈውሱበትና ገቢረ ተአምር ሲያደርጉበት ኖረዋል፡፡

በዓመቱ ቶማስ ትንሣኤዋን አይቶ እንዴት እኛ ይቅርብን?” ብለው ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምሮ ሱባኤ ገብተው ነሐሴ ፲፮ ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ልመናቸውን ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ (ረዳት) ቄስ፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገባሬ ሠናይ (ዋና) ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ አቍርቧቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ እመቤታችንን ሐዋርያት በግልጽ እያዩዋት ከጌታችን ጋር በክብር በይባቤና በዝማሬ ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ትንሣኤ ጊዜያዊና ዘለዓለማዊ በመባል ይታወቃል፡፡ ጊዜያዊ ትንሣኤ የሚባለው የእግዚአብሔር ከሃሊነት የሚገለጽበት ተአምራዊ ሥራ ኾኖ በተወሰኑ ሰዎች ላይ የሚፈጸምና ዳግም ሞትን የሚያስከትል ነው፡፡ ለምሳሌ ኤልያስ ያስነሣውን ወልደ መበለት (፩ኛነገ. ፲፯፥፰-፳፬)፤ ዐፅመ ኤልሳዕ ያስነሣውን ሰው (፪ኛነገ. ፲፫፥፳-፳፩)፤ ወለተ ኢያኢሮስን (ማቴ. ፱፥፰-፳፮)፤ በዕለተ ስቅለት ከመቃብር ወጥተው በቅድስት ከተማ የታዩ ሙታንን (ማቴ. ፳፯፥፶፪-፶፫)፤ በቅዱስ ጴጥሮስ ጸሎትና ምልጃ የተነሣችዋን ጣቢታን (ሐዋ. ፱፥፴፮-፵፩)፤ እንደዚሁም ትንሣኤ አልዓዛርን መጥቀስ ይቻላል (ዮሐ. ፲፩፥፵፫-፵፬)፡፡ እነዚህ ዅሉ ለጊዜው ከሞት ቢነሡም ተመልሰው ዐርፈዋል፡፡ ወደፊትም ትንሣኤ ዘጉባኤ ይጠብቃቸዋል፡፡

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት በትንቢቱ ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅድስከ፤አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፤ አንተና የመቅደስህ ታቦትም (መዝ. ፻፴፩፥፰) በማለት አስቀድሞ የክርስቶስን ትንሣኤ ከገለጸ በኋላ ቀጥሎ የመቅደሱ ታቦት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ከሞት እንደምትነሣ ተናግሯል (ማቴ. ፭፥፴፭፤ ገላ. ፬፥፳፮፤ ዕብ. ፲፪፥፳፪፤ ራእ.፫፥፲፪)፡፡ የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ የክብርና የሕይወት ትንሣኤ ሲኾን ሁለተኛ ሞትን አያስከትልም፤ ትንሣኤ ዘጉባኤንም አይጠብቅም፡፡ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤያችን በኵር ኾኖ በሞተ በሦስተኛው  ቀን ተነሥቷል፡፡ እመቤታችንም በልጇ ሥልጣን፤  እንደ ልጇ ትንሣኤ በሦስተኛው ቀን ተነሥታ ትንሣኤ ዘጉባኤን ሳትጠብቅ በክብር ዐርጋለች፡፡

እንደዚህ ያለውን ትንሣኤ ከእርሷ በቀር ሌሎች ቅዱሳን ወይም ነቢያትና ሐዋርያት አላገኙትም፡፡ በዚህም ኹኔታ የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ ከማናቸውም ትንሣኤ ልዩ ኾኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህም ትንሣኤ ዘለዓለማዊ፣ ከዳግም ሞተ ሥጋ ነጻ የኾነ ትንሣኤ ነው፡፡ ዕርገቷም በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው ከእነ ሄኖክና ኤልያስ ዕርገት የተለየ ነው፡፡ ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ፤ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም ተብሎ እንደ ተጸፈ (ዕብ. ፲፩፥፭)፣ ሄኖክ ወደ ሰማይ ያረገው በምድር ሳለ እግዚአብሔርን በእምነቱና በመልካም ሥራው ስላስደስተና በሥራውም ቅዱስ ኾኖ ስለ ተገኘ ነው፡፡ ኾኖም ግን ወደፊትም ገና ሞት ይጠብቀዋል፤ ሞቶም ትንሣኤ ዘጉባኤ ያስፈልገዋል፡፡ ነቢዩ ኤልያስም በእሳት ሠረገላም ቢነጠቅም (፪ኛ ነገ. ፪፥፲) ወደፊት ሞት ይጠብቀዋል፤ ትንሣኤ ዘጉባኤም ያስፈልገዋል፡፡ የእመቤታችን ትንሣኤ ግን ሞት የሌለበት ዘለዓለማዊ ትንሣኤ ነው፡፡

በአጠቃላይ ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ በድርሰቱ በቃልዋ የታመነች፣ በሥራዋም የተወደደች ቅድስት ድንግል ማርያምን መላእክት እያመሰገኗትና በመንፈሳዊ ደስታ እያጀቧት ወደ ሰማይ አሳረጓት ሲል እንደ ገለጸው፣ በመጽሐፈ ስንክሳርም እንደ ተመዘገበው ቅዱስ ዳዊት በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋ፣ ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች(መዝ.፵፬፥፱) በማለት የተናገረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ አባቷ ዳዊት በበገና፣ ነቢዩ ዕዝራ በመሰንቆው እያመሰገኗት፤ በቅዱሳን መላእክት፣ በቅዱሳን ነቢያትና ጻድቃን ዝማሬ በብሩህ ደመና ወደ ሰማይ ዐርጋ በክብር ተቀምጣለች፡፡

እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ዐረገች፤ በሰማይም ከልጇ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች” እንዳለ ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ፡፡ በዚያም ሥፍራ ሁለተኛ ሞት ወይም ኀዘን፣ ጩኸትና፣ ስቃይ የለም፡፡ የቀደመው ሥርዐት አልፏልና (ራእ. ፳፩፥፬-፭)፡፡ ስለዚህም የእመቤታችን ዕረፍቷ፣ ትንሣኤዋና ዕርገቷ በሚታሰብበት በጾመ ፍልሰታ ሳምንታት ምእመናንን ከአካባቢያቸው ራቅ ብለው በተለያዩ ገዳማትና አድባራት በመሔድ አለዚያም በየአጥቢያቸው በመሰባሰብ እመቤታችን በተለያዩ ጊዜያት ሞቷንና ትንሣኤዋን ለሐዋርያት የገለጸችበትን ኹኔታ ያስባሉ፡፡ በጾም በጸሎት ተወስነው የልጇን ቸርነት የድንግልን አማላጅነት በእምነት ኾነው ይማጸናሉ፡፡ እንደዚሁም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነሐሴ ፲፮ ቀን እናቱን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ተራዳዒ ካህን፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ ሐዋርያትንም እመቤታችንንም ማቍረቡን በማሰብና ድኅት ሥጋ ድኅነተ ነፍስ ለማግኘት ቅዱስ ሥጋውን፣ ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ሱባዔው ሲፈጸምም በእውነት ተነሥታለች እያሉ በደስታ የጾሙን ወቅት ይፈጽማሉ፡፡ የእመቤታችን አማላጅነት፣ የትንሣኤያችን በኵር የኾነው የአምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነት ከዅላችን ጋር ይኹን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

“ሠናይ ውእቱ ለነ ሀልዎ ዝየ” (ማቴ.፲፯፥፬)

በዲ/ን ዐቢይ ሙሉቀን

የቃሉ ተናጋሪ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ነው። ቃሉን የተናገረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን ሊገልጥላቸው ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን፣ ከሐዋርያት ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ወደ ተራራው ባወጣቸው ጊዜ ነው፡፡ ሙሴና ኤልያስ ከክርስቶስ ጋር ሲነጋገሩ ሰምቶ “በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው፣ ብትፈቅድስ ሦስት ሰቀላዎች እንሥራ አንድ ላንተ፣ አንድ ለሙሴ፣ አንድ ለኤልያስ” በማለት ተናገረ።

በዚህ ጽሑፍ ክርስቶስ ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን፣ ከሐዋርያት ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ብቻ ወስዶ ብርሃነ መለኮቱን ለመግለጥ የፈቀደበትን ምክንያት፣ ደብረ ታቦር የምን ምሳሌ እንደሆነ፣ በዚህ እንኑር የሚለው ቃል ምንን እንደሚያመለክት፣ እናያለን።

ሀ. ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን ማሳየት ለምን አስፈለገው?

አንደኛ፡-  “እውነት እውነት እላችኋለሁ የሰውን ልጅ በመንግሥቱ ሲመጣ እስኪያዩት ድረስ እዚህ ቆመው ካሉት ሞትን የማይቀምሱ አሉ” (ማቴ.፲፮፥፳፰) ብሏቸው ነበርና ከዚያ ጋር ለማያያዝ።

ሁለተኛ፡- እሞታለሁ ብሎ ቢናገር ቅዱስ ጴጥሮስ አይሁንብህ (ማቴ.፲፮፣፳፩-፳፫) እያለ ተናግሮ ነበርና የሚላችሁን ስሙ ለማለት።

ሦስተኛ፡- በቂሣርያ ሰብስቦ “የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?” ባላቸው ጊዜ “ከነቢያት አንዱ ነው” (ማቴ.፲፮፣፣፲፫-፲፬) ብለውት ነበርና የነቢያት ጌታ መሆኑን እንዲረዱት ነው።

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ፣ ወልደ አምላክ መሆኑን ሙሴና ኤልያስም መስክረዋል። ሙሴ እኔ ባሕር ብከፍል፣ ጠላት ብገድል፣ መና ባወርድ፣ ደመና ብጋርድ በአንተ ዕርዳታ ነው። ነገር ግን ይህም ሆኖ እስራኤልን ማዳን አልቻልኩም፤ እስራኤልን ማዳን የምትችል አንተን የሙሴ አምላክ የሙሴ ጌታ ነህ ይበሉህ እንጂ ለምን ሙሴ ይሉሃል ብሎ መስክሯል። ኤልያስም ሰማይ ብለጉም፣ እሳት ባዘንም በአንተ ቸርነት እንጂ እኔማ እንዴት ይቻለኛል? ይህም ሆኖ እስራኤልን ከኃጢአታቸው መልሼ ማዳን አልቻልኩም። ይህን ሁሉ ማድረግ የምትችል አንተን የኤልያስ ጌታ ሊሉህ ይገባል እንጂ እንዴት ኤልያስ ነህ ይሉሃል ሲሉ ተሰምተዋል። እንዲሁም በባሕርይ አባቱ ለማስመስከር ነው። ሐዲስ ኪዳን የአምላክ መገለጥ ወይም ዘመነ አስተርእዮ ነው የሚባለውም ለዚህ ነው። ግራ ሲጋቡ የነበሩ ሐዋርያትም አምላክነቱን ተረድተዋልና።

ለ. ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን ከሐዋርያት ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ብቻ ወሰዳቸው?

ይህን ጉዳይ ስንመለከት ሁሉም የየራሳቸው ምክንያት አላቸው። በመጀመሪያ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመረጣቸው ከብሉይ ኪዳንም፣ ከሐዲስ ኪዳንም፣ ከደናግልም፣ ከሕጋውያንም ነው። ሁሉም መንግሥተ ሰማያትን መውረስ እንደሚችሉ ሲያስረዳ ነው። ይህም በብሉይ ኪዳን ምእመናንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን ምእመናን፣ እንዲሁም በድንግልና በኖሩትም ሆነ በጋብቻ ሕይወት በኖሩት ትምክህት እንዳይኖር፣ መንግሥተ ሰማያት በሃይማኖት ጸንቶ፣ መልካም ምግባር ሠርቶ የኖረ ሁሉ የሚወርሳት እንደሆነች ለማስረዳት ነው።

ሌላው ደግሞ ሙሴ በመዋዕለ ዘመኑ ክብርህን አሳየኝ ባለው ጊዜ እኔን አይቶ መቋቋም የሚቻለው የለም (ዘፀ.፴፫፥፲፯-፳፫) ብሎት ነበርና የተመኘውን ሊያሳካለት፣ እንዲሁም በባሕርይው የማይመረመር መሆኑንም ሲገልጽለት ነው። ኤልያስንም ምስክር ትሆነኛለህ ተብሎ ስለነበር። ከዚህም በመነሣት የለመኑትን የማይነሣ፣ የነገሩትን የማይረሳ አምላክ መሆኑን እንድንረዳ፣ እንዲሁም የማያደርገውን የማይናገር የተናገረውንም የማያስቀር እውነተኛ አምላክ መሆኑን እንረዳ ዘንድ መረጣቸው።

ሐዋርያት የተመረጡበትን ምክንያት ሊቃውንቱ በሁለት መንገድ ገልጸውታል። የመጀመሪያው ሦስቱም እንሾማለን ብለው ያስቡ ስለነበር እርሱ ንጉሥነቱ ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ እንዳልሆነ፣ ንግሥናው ሰማያዊ መሆኑን አስረድቶ የእነርሱንም ሹመት ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ እንዳልሆነ ሊያስረዳቸው። ሌላው ደግሞ እጅግ አብዝተው ይወዱት ስለነበር የፍቅራቸው ዋጋ እንዲሆንላቸው ነው። ሹመት ይመኙ እንደነበር ያዕቆብና ዮሐንስ እናታቸውን ልከው ያስጠየቁ ሲሆን ጴጥሮስ ደግሞ እሞታለሁ ቢለው አትሙትብኝ ብሎ መጠየቁ እርሱ ከሞተ ማን ይሾመኛል ብሎ ነው ብለው መተርጉማኑ ተርጉመውታል። ፍቅራቸውን ግን እኔ የምጠጣውን ጽዋዕ ትጠጣላችሁ ወይ ሲባሉ አዎን ማለታቸው ቢወዱት ነውና፤ ጴጥሮስም አትሙትብኝ ማለቱ ቢወደው ነውና የፍቅራቸው መገለጫ ይሆናቸው ዘንድ ብርሃነ መለኮቱን ገለጠላቸው። በዚህ ምክንያት ከሌሎች ሐዋርያት ተለይተው ብርሃነ መለኮቱን እንዲያዩ ተመርጠዋል።

ሐ. ቅዱስ ጴጥሮስ የሙሴንና የኤልያስን ምስክርነት ከሰማ በኋላ ለክርስቶስ፣ ለሙሴና ለኤልያስ ቤት እንሥራ  ማለቱ ለምንድነው?

ብንታመም እየፈወስከን፣ ብንሞት እያስነሣኸን፣ ብንራብ ባርከህ እያበላኸን፣ ሙሴም የጥንት ሥራውን እየሠራ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላት እየገደለ፣ መና እያወረደ፣ ደመና እየጋረደ፣ ኤልያስም ሰማይ እየለጎመ፣ ዝናም እያዘነመ በዚህ እንኑር በማለት ተናግሯል። ቅዱስ ጴጥሮስ ለክርስቶስ፣ ለሙሴና ለኤልያስ ቤት እንሥራ ሲል ለራሱና ለሌሎች ሐዋርያት እንሥራ አላለም። ከዚህና ከሌላውም አገላለጹ የምንረዳው መሠረታዊ ነጥብ አለ። እርሱም፡-

የክርስቶስን፣ የሙሴንና የኤልያስን ተግባር መመስከር ሲሆን፤ እውነተኛ ምስክርነትን እንማራለን። በብሉይ ኪዳን ሲተገብሩት የኖሩትን፣ እንዲሁም ክርስቶስ ሁሉን የሚችል አምላክ መሆኑን አስረድቷል። ከዚህ በተጨማሪ ለራሱ አለመጠየቁ አስቀድሞ የነበረውን የዓሣ ማጥመጃ መረብና አንድ አህያ ትተህ ተከተለኝ ተብሏልና፣ እንዲሁም ብር ወይም ወርቅ አትያዙ ተብሏልና ምድራዊ ገንዘብ፣ ቤት ንብረት ማፍራት እንደሌለባቸው የተማሩትን መሠረታዊ ትምህርት ያስታውሰናል። ሌላው ደግሞ ለራስ አለማለትን ሌላውን ማስቀደም እንዳለብን ያስተምረናል።

መ. ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት የሚባለው ለምንድንነው?

በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱ እንደተገለጠባት ቤተ ክርስቲያንም ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አዕማደ ምሥጢራት፣ ነገረ እግዚአብሔር ይገለጥባታል። ቅዱስ ጴጥሮስ በደብረ ታቦር እንኑር ማለቱ ዛሬም በቤተ ክርስቲያን መኖር እንዳለብን ያስረዳናል። ደብረ ታቦር በክርስቶስ ሰብሳቢነት ነቢያትና ሐዋርያት የተገናኙበት የተቀደሰ ተራራ ነው። ቤተ ክርስቲያንም “በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋልና፤ የሕንጻው ማዕዘን ራስ ድንጋይም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው” (ኤፌ.፪፥፳) በማለት ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ እንደገለጸው የብሉይ ኪዳን ምእመናንና የሐዲስ ኪዳን ምእመናን ኅብረት፣ አንድነት ናት።

በደብረ ታቦር በአጸደ ሥጋ ያሉ ሐዋርያትና በአጸደ ነፍስ ያሉት ምእመናን እንደተገናኙ ቤተ ክርስቲያንም በአጸደ ሥጋ ያሉ ምእመናን እና በአጸደ ነፍስ ያሉ ምእመናን አንድነት ናት። በደብረ ታቦት ስውራን እና ሕያዋን እንደተገናኙበት ቤተ ክርስቲያን የእነዚህ ሁሉ ኅብረት አንድነት ናት። በድንግልና የኖሩት ኤልያስና ዮሐንስ በጋብቻ ከኖሩት ሙሴና ጴጥሮስ ጋር አንድ ሆነው ብርሃነ መለኮቱን እንደተመለከቱበት ቤተ ክርስቲያንም በድንግልና ያሉትም፣ በጋብቻ ሕይወት የሚኖሩትም ምእመናን በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምነው ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን የሚሳተፉባት እነዚህን ሁሉ አንድ የምታደርግ የአንድነት ቦታ ናት።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ልዩ የሆነ ምሥጢር እንድንረዳው ድክመታችንንም እንኳን ልዩ በሆነው ጥበቡ ሰውሮ ደካማ ነህ ሳይል በልዩ ጥበቡ ሊያስተምረን እንደ ሐዋርያቱ እንደ ነቢያቱ ምሥጢሩን ሊገልጽልን፣ አምላክነቱን ሊያስረዳን፣ ሹመታችን ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ እንዳልሆነ ሊያስተምረን ዕለት ዕለት ይጠራናል። ቤተ ክርስቲያን ምድራዊ ሹመት የምንለምንባት ሳትሆን ሰማያዊ ሹመት የምንለምንባት ቅድስት ቦታ ናት። በቅድስና ኑረን ሰማያዊውን ርስት መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ የሚያስችል ሥራ የምንሠራባት የቅድስና ሥፍራ ናት።

እኛም ምንም እንኳን ደካማና ለቤቱ የማንመች ብንሆንም፣ በኃጢአት የረከስን፣ ምድራዊ ሹመትና ሀብት በቀላሉ የሚያታልለን ብንሆንም በጥበብ ያስተምረን ዘንድ ዕለት ዕለት ይጠራናልና ጥሪውን አክብረን እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው ልንል ይገባል። ይልቁንም ሰላም በጠፋበት ዘመን፣ እርስ በእርስ መስማማት በሌለበት ዘመን፣ ወንድም ወንድሙን በሚያርድበት ዘመን፣ የተበላሸ ርእዮተ ዓለም እንደ ወጀብ እየናጠን ባለንበት ዘመን፣ የተሻለ ብቻ ሳይሆን ምርጫ የሌለው መኖሪያችንን ቤተ ክርስቲያን ልናደርግ ይገባል። ምንም እንኳን በክርስትና ሕይወት እንድንፈጽማቸው የምንታዘዛቸው ሁሉ በፈቃዳችን ልንፈጽማቸው የሚገቡ ቢሆኑም አሁን ካለው ውስብስብ ችግር አንጻር ግን ቢበርደንም፣ ቢርበንም፣ ቢጠማንም፣ ብንቸገርም፣ በቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ተጠልለን መኖር ግድ ይለናል። ግድ ይለናል ሲባል ግን እግዚአብሔር አምላካችን አስፈቅዶና አስወድዶ የሚገዛ አምላክ እንጂ አስገድዶ የሚገዛ አምላክ እንዳልሆነ ልብ ማለት ያስፈልጋል። ከክፉ የሚሰውረንን አምላክ ወደንና ፈቅደን ልንገዛለት፣ እንዲሁም ወደንና ፈቅደን ወደ ቤተ ክርስቲያን በመምጣት በቤተ ክርስቲያን ልንኖር ይገባል።

ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ የሕክምና ማእከልና የጤና ጣቢያ ናት። በሽተኛ በዝቷል ተብሎ የሕክምና ማእከላት ይስፋፋሉ እንጂ አይዘጉም። እንዲሁ እኛ ሰዎች ምንም ኃጢአተኞችና ደካሞች ብንሆንም፣ ዘመኑም የከፋ ቢሆንም፣ በሽታውም ቢበረታ የሕክምና ቦታችን ናትና የበለጠ ልናስፋፋት፣ የበለጠ ድጅ ልንጸናት እንጂ ልንሸሻት አይገባምና ሁሌም እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው ልንል ያስፈልጋል። በቤቱ ኖረን ንስሓ ገብተን ሥጋውን ደሙን ተቀብለን የስሙ ቀዳሾች የመንግሥቱ ወራሾች እንድንሆን እግዚአብሔር አምላካችን ይፍቀድልን አሜን።

ሱባኤያችን በረከት የሚያሰጥ ይሁን

በእንዳለ ደምስስ

በረከትን በመሻት በፍልሰታ ለማርያም ጾም ሱባኤ ለመያዝ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም በታነጸውና በቤተ ክርስቲያናችን ከሚታወቁ ታላላቅ ገዳማት ወደ አንዱ ለመሔድ ዝግጅት ሳደርግ ቆይቻለሁ፡፡ ወደ ንስሓ አባቴ ቀርቤ ንስሓ ገብቼና ቀኖናዬን ተቀብዬ፣ ከመሥሪያ ቤቴ ደግሞ ፈቃድ ቀኑ ሲደርስ በዋዜማው የሚያስፈልጉኝን የጸሎት መጻሕፍት፣ አልባሳት፣ በሶና ጥሬ ሽምብራ በቦርሳዬ ሸክፌ፣ የጸበል መቅጃ አነስተኛ ጀሪካን አንጠልጥዬ ልቤ ወደአሰበውና በየዓመቱ ወደምሔድበት ገዳም በሚኒባስ ተሳፈርኩ፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ገዳም ከአዲስ አበባ በስተደቡብ አቅጣጫ አንድ መቶ ኪ/ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ መኪናው ውስጥ እንደ እኔው ሱባኤ ለመግባት የተጣደፉ ወጣት ሴቶችና ጎረምሶች ተሳፍረዋል፣ ሾፌሩ የበኵረ መዘምራን ኪነ ጥበብን “አባታችን ሆይ” የሚለውን መዝሙር በስሱ ከፍቶ አብሮ እየዘመረ መኪናውን ያከንፈው ጀመር፡፡ እኛም በዝማሬ ተከተልነው፡፡

ገዳሙ በአጸድ ተሸፍኗል፣ በአካባቢው ከገዳማውያንና ሱባኤ ለመግባት ከሚጣደፉ ኦርቶዶክሳውያን በስተቀር በአቅራቢያው መኖሪያ ቤቶች እንኳን አይታዩም፡፡ ከመኪናችን ወረድን ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሔጄ ተሳለምኩ፡፡ ምእመናን ጓዛቸውን ተሸክመው እንደ እኔ በረከት ፍለጋ፣ በጾም በጸሎት ተወስነው ከአምላካቸው ከእግዚአብሔር ለመገናኘት፣ የልቦናቸውን መሻት ይፈጽምላቸው ዘንድ ለመማጸን ያለማቋረጥ ወደ ገዳሙ መጉረፋቸውን ቀጥለዋል፡፡

በበጎ አድራጊ ምእመናን እንደታነጹ የሚታወቁት የወንዶችና የሴቶች የሱባኤ መያዣ በአቶች(አዳራሾች) ከቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ውጪ በስተ ምሥራቅና በስተ ምዕራብ ሽንጣቸውን አርዝመው ለመስተንግዶ በራቸውን ከፍተዋል፡፡ በበሮቹ መግቢያና መውጫዎች የሚገቡና የሚወጡ ምእመናን ግርግር አካባቢውን የገበያ ውሎ አስመስሎታል፡፡ ሁሉም ይጣደፋል፡፡ ግርግሩን እየታዘብኩ ለሱባኤ ወደ ገዳሙ መምጣቴን ለማሳወቅና ቦታ እንዲሰጠኝ ለመጠየቅ ወደ አስተናጋጆቹ ሔድኩ፡፡ ማንነቴን የሚገልጽ መታወቂያ በማቅረብ አስመዝግቤ ወደተመደብኩበት የወንዶች አዳራሽ አመራሁ፡፡

ገና ከቀኑ ስምንት ሰዓት ቢሆን ነው፡፡ አዳራሹ በመጋረጃ መሐል ለመሐል ተከፍሎ በርካታ ምእመናን እንዲያስተናግድ ተደርጎ ተዘጋጅቷል፡፡ ወለሉ ሙሉ ለሙሉ ምንጣፍ ተነጥፎበታል፣ ቀድመውኝ የመጡ ምእመናን የራሳቸውን ምንጣፍ ከዋናው ከምንጣፍ በላይ ደርበው አንጥፈዋል፡፡ አብዛኛው የአዳራሹ ሥፍራ ተይዟል፡፡ ቦታ ፍለጋ ዓይኖቼን አንከራተትኳቸው፡፡ ቢያንስ አምስት ሰው ሊያስተናግድ የሚችል ቦታ እንዳለ አስተዋልኩ፡፡ የሚመቸኝን ቦታ ከመረጥኩ በኋላ ጓዜን አስቀምጬ ምንጣፍ ዘረጋሁ፡፡

ራሴን ካረጋጋሁ በኋላ አዳራሹን ከላይ እስከ ታች በዐይኖቼ ቃኘሁት፡፡ አብዛኛው በአዳራሹ ቦታ ይዘው ያሉት ወጣቶች ናቸው፡፡ አልፎ አልፎ ግን በጎልማሳነት ዕድሜ ላይ ያሉ፣ በሕመም ምክንያት በአስታማሚ የሚረዱ ሰዎችም አብረውን አሉ፡፡ ከሁሉም ግን ትኩረቴን የሳበው  በስተቀኝ በኩል ግድግዳውን ተደግፈው ከአንድ ሱባኤ ከሚይዝ ሰው የማይጠበቅ ፌዝና ቀልድ ላይ ያተኮረ የወጣቶቹ ድርጊት ነው፡፡ ገና ከዋዜማው እንዲህ ከሆነ ጥቂት ሲቆይ ለጸሎትም እንኳን እንደምንቸገር መገመት አላዳገተኝም፡፡ እኔም አላርፍም እነሱን መከታታል ጀመርኩ፡፡ እየተቀላለዱ ይሳሳቃሉ፡፡

የልጆቹ ሁኔታ ስላላማረኝ ነጠላዬን መስቀልያ ለብሼ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሔድኩ፡፡ አሁንም የቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር በጸበልተኛና ሱባኤ በሚገቡ ምእመናን ግርግር እንደተሞላ ነው፡፡ ያሰብኩትን ሱባኤ በሰላም አስጀምሮ በሰላም እንዲያስፈጽመኝ ተማጸንኩ፡፡ ጠዋት የጸበል መጠመቂያ ቦታውን በመፈለግ እንዳልደናገር ወደ አንድ ጸበልተኛ ጠጋ ብዬ “ጸበል መጠመቂያው የት ነው?” ብዬ ጠየቅሁት፡፡

በጣቱ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ እያመለከተኝ “በዚህ በኩል ነው፡፡ ቢያንስ አራት ወይም አምስት ደቂቃ ብቻ ቢወስድ ነው” አለኝ፡፡ በደንብ ሲያስተውለኝ እንግዳ መሆኔን በመረዳት “ለመጀመሪያ ጊዜ ነው የመጣኸው?” አለኝ፡፡

“አዎ፡፡” አልኩት፡፡

“ወንድሜ ራስህን በደንብ መጠበቅ አለብህ፡፡ በእግዚአብሔር ወይም በእመቤታችን እንዳታማርር፡፡ የሰው ፍላጎቱ ብዙ ነው፡፡ ለበረከት የሚመጣ እንዳለ ሁሉ ለስርቆትና ለክፉ ነገር የሚመጣም አለ፡፡ ጸበል ስትጠመቅ ያወለቅኸውን ልብስ ይዞብህ፣ ወይም ለብሶብህ የሚሔድም አይጠፋም፡፡ ንብረትህን በደንብ መጠበቅ አለብህ፡፡ እንዲህ ስልህ ለነፍሳቸው ያደሩ፣ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ያስገዙና ስለሌሎች የሚኖሩ የሉም እያልኩህ አይደለም፡፡ ሥፍራው ታላላቅ ተአምራት የሚከናወንበት የጽድቅ ሥፍራ ነው፡፡ ጠንክሮ መጸለይ ነው” አለኝ በትሕትና፡፡

“እሺ ወንድሜ፡፡ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡ የመጣሁት ከእመቤታችን በረከት ለማግኘት ነው፤ ለዚህም እግዚአብሔር ይረዳኛል” በማለት አመስግኜ ተሰናበትኩት፡፡

“ብዙ ኃጢአት ባለችበት የእግዚአብሔር ጸጋ ትበዛለች” የሚለው የቅዱስ ኤፍሬም የሰኞ ውዳሴ ማርያም ጸሎት ትዝ ብሎኝ እየተገረምኩ አንድ ጥግ ድንጋይ ላይ ተቀመጥኩ፡፡

የሰርክ መርሐ ግብር በጸሎትተጀምሮ የወንጌል ትምህርት እንዲሁም ምሕላ ተደረገ፡፡ ሱባኤው ተጀምሮ እስኪያልቅ ድረስ ምእመናን ሥነ ምግባር በተሞላበት ሁኔታ የመጡበትን ዓላማ አሳክተው እንዲመለሱ፣ የበረከቱ ተሳታፊም እንዲሆኑ በመምህራን ማሳሰቢያ ተሰጠ፡፡

የሰዓታት ጸሎት እስኪጀመር ድረስ ሁሉም ወደየበአቱ በማምራት በሶውን በጥብጦ፣ ቆሎውን፣ ሽምብራውን ቆርጥሞ የበረታ በጸሎት ሲጠመድ ሌላው ዕረፍት አደረገ፡፡ አንዳንዶች ከአሁኑ አርምሞ ጀምረዋል፡፡ አዳራሹ ውስጥ በቡድን ሆነው የመጡት ጓደኛማቾች ድምጻቸውን ይቀንሱ እንጂ መቀላለዳቸውን አላቋረጡም፡፡ በጸሎት ለተጠመደ ኅሊናን ይሰርቃሉ፡፡

ከሌሊቱ ዐራት ሰዓት ሲሆን የቤተ ክርስቲያኑ ደወል ተደወለ፡፡ አንዱ አንዱን እየቀሰቀሰ ተያይዘን ወደ ቤተ መቅደሱ አመራን፡፡ ካህናት አባቶች ሰዓታት ቆመዋል፡፡

ቤተ መቅደሱ የቻለውን ያህል ምእመናንን አስተናግዶ ሌላው ውጪ ሆኖ ብርዱን ተቋቁሞ ይጸልያል፡፡ ሰዓታት እንደ ተጠናቀቀ ንጋት ላይ ሊቀውንቱ የኪዳን ጸሎት፣ ስብሐተ ነግህ ቀጠሉ፡፡ ጨለማው ለብርሃን ሥፍራውን ሲለቅ ውዳሴ ማርያምና ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜ እንደ ቅደም ተከተላቸው ቀርበው የቅዳሴ ሰዓት እስኪደርስ ጸበል ለመጠመቅ እሽቅድድም በሚመስል ፍጥነት ተሯሯጥን፡፡

ጸበል መያዣ ባለ አምስት ሊትር ጀሪካን ይዤ ወደ ጸበሉ ስፍራ ሰዎችን ተከትዬ ሔድኩ፡፡ ግርግሩ ዕረፍት ይነሣል፡፡ እንደማንኛውም ሰው ወረፋ ያዝኩ ነገር ግን በጉልበታቸው የተመኩ ወጣቶች እየተጋፉ፣ የዕድሜ ባለጠጋ የሆኑትን አረጋውያንን እየገፉ ተጠምቀው ለመውጣት ይጣደፋሉ፡፡ ሰልፉ ተረበሸ፡፡ ችግሩ ከሚያስተናግዱ ወንድሞች በላይ ሆነ፡፡ በሴቶችም በኩል መጠነኛ ግርግሩ ቀጥሏል፡፡ በዚህ መካከል የሚወድቅ፣ ንብረቱ የሚዘረፍ ቁጥሩ በርካታ ነው፡፡ የምእመናን ቁጥር ከፍተኛ ቢሆንም እስከ ስድስት ሰዓት ሳይጠመቅ የተመለሰ አልነበረም፡፡

ከቅዳሴ በኋላ ዕረፍት የሚያደርጉ እንዳሉ ሁሉ ተፈትተው የተለቀቁ ይመስል ከበአታቸው እየወጡ በቡድን፣ በቡድን እየሆኑ በየጫካው ለፌዝና ለቀልድ ጊዜያቸውን የሰጡ ምእመናንም አሉ፡፡ ነገር ግን የመጡት ለሱባኤ ነው፡፡

እንዲህ እንዲህ እያልን ነሐሴ ፲፮ ቀን ድረስ ቆየን፡፡ የእመቤታችን ትንሣኤ ተበሠረ፡፡ ከቅዳሴ በኋላ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን “የእመቤታችንን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ ያክብሩት” ብላ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት እንደ ሠራች በስፋት አስተማሩ፡፡ የሱባኤውንም መጠናቀቅ አወጁ፡፡

ቤተ ክርስቲያኗ ከጥሉላት ምግቦች ተከልክሎ የቆየውን ምእመን የጾም መፍቻ ብላ ያዘጋጀችው ማዕድ በየአዳራሹና በድንኳኑ ታደለ፡፡ እኔ ካለሁበት አዳራሽ ውስጥ ካሉት ምእመናን መካከል “አንበላም እስከ ነሐሴ ፳፩ ቀን ጾማችንን እንቀጥላለን” በማለት የመለሱት ይበዛሉ፡፡ ግራ ተጋባሁ፡፡ የቀረበላቸውን ተቃምሰው ጓዛችውን ሸክፈው ወደወጡበት ቤታቸው ለመመለስ የሚጣደፉ ምእመናንም ቁጥር ብዙ ነው፡፡ እኔ ግን አንድ ቀን ዕረፍት አድርጌ በማግሥቱ ለመሔድ ስለወሰንኩ የቀረበልኝን ማዕድ በላሁ፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በመጣሱ ቅር ተሰኘሁ፡፡ ቤተ ክርስቲያን “የእመቤታችንን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ አክብሩ” እያለች ይህንን ተላልፈው የእመቤታችን ትንሣኤ በሚከበርበት ወቅት እጾማለሁ ማለት ምን ማለት እንደሆነ አልገባኝም፡፡ “ቤተ ክርስቲያን ሁለት ዓይነት ሥርዓት አላት እንዴ?” እያልኩ ከራሴ ጋር ሙግት ገጠምኩ፡፡ አንድ ነገር ወሰንኩ፡፡ አባቶችን ማማከር፡፡

ጥቂት ዕረፍት አድርጌ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር በመግባት አባቶችን ፈለግሁ፡፡ ውዳሴ ማርያምና ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜን ላለፉት ቀናት በጣፋጭ አንደበታቸው ሲተረጉሙ የነበሩት አባት ከቤተ መቅደስ ሲወጡ አገኘኋቸው፡፡ ቀረብ ብዬ ሰላምታ ከሰጠኋቸው በኋላ ጥያቄዬን አቀረብኩ፡፡

በትኩረት እየቃኙኝ “ልጄ ቤተ ክርስቲያን የሠራችው ሥርዓት ማፋለስ ኃጢአት ነው፡፡ እውነት ነው ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ ያክብሩት ብላ ሥርዓት ሠርታለች፡፡ ነገር ግን ምእመናን ሲጥሱት እንመለከታለን፡፡ ከዚህ በፊትም በስፋት አስተምረናል፡፡ “የበለጠ በረከት ለማግኘት ነው” እያሉ የሚጾሙ ምእመናን ቁጥር በርካታ ነው፡፡ ይህ ትክክል አይደለም፡፡ አንዳንድ ምእመናን ቢነገራቸውም አይሰሙም፡፡ ግዝት አይደለም መጾም እንችላለን ይሉሃል፡፡ አንዳንድ አባቶችንም ስታነጋግር ምን ችግር አለው ይሉሃል፡፡ ይህ ትክክል አይደለም” አሉኝ ጥያቄው የእኔ ብቻ ሳይሆን የእሳቸውም ጥያቄ እንደሆነ በሚገልጽ ምላሽ፡፡

“ታዲያ ሥርዓት የሚሽሩትን ከገዳሙ ለምን አታስወጡም” አልኳቸው፡፡

ለጥቂት ሰከንዶች በመገረም እያዩኝ፡፡ “ልጄ እኔ የዚህ ሥልጣን የለኝም፡፡ በተቻለኝ አቅም ልጆቼን በሔዱበት ሁሉ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት እንዳይጥሱ አስተምራቸዋለሁ፡፡ ካለ እኔ ፈቃድም አያደርጉትም፡፡ አሁን አንተ የምትለኝን ገዳሙ የራሱ አስተዳደር አለውና እነሱን ጠይቅ” ብለው መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ አስተዳደሩን ለማግኘት ያደረግሁት ጥረት ሳይሳከ ቀረ፡፡

ሁላችንም ምክንያት የምናደርገው ሌሎችን ነው፡፡ ለምን ብለን ግን አንጠይቅም፡፡ ፈቃጁ ማነው? ማን እንደሆነ አይታወቅም፡፡ አንዱ ወደ አንዱ ያሻግርሃል፡፡ በጣም ተበሳጨሁ፡፡ ወደ አዳራሹ ተመለስኩ፡፡ ብዙ ሰዎች ሱባኤያቸውን ቀጥለዋል፡፡ በመብላቴ እኔን እንደ ደካማና ኃጢአተኛ አድረገው የቆጠሩኝ መሰለኝ፡፡ ሕሊናዬ አላርፍ አለኝ፡፡

አዳራሹ ውስጥ ካሉት መካከል ለረጅም ሰዓት ቆሞ በመጸለይና በመስገድ መንፈሳዊ ቅናት ወደ ቀናሁበት ወንድም ጠጋ ብዬ ጥያቄዬን አቀረብኩለት፡፡ “ጾሙ አልተጠናቀቀም ወይ?” ነበር ጥያቄዬ፡፡

“በረከት ለማግኘት ስል እስከ እመቤታችን ዕረፍት መታሰቢያ ቀን ድረስ እቆያለሁ፡፡” አለኝ፡፡

“ለምን? ሥርዓት መጣስ አይሆንብህም?” አልኩት፡፡

“መብቴ እኮ ነው፡፡ ከመብላት አለመብላት ይሻላል፡፡” አለኝ፡፡

“እንዴት እንዴት አድርገህ ነው የምትተረጉመው? ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችንን ትንሣኤ ከነሐሴ ፲፮-፳፩ ቀን እንደ በዓለ ሃምሳ ያክብሩት በማለት መደንገጓን ምነው ዘነጋህ? ለመሆኑ ሱባኤው እስከ ነሐሴ ፳፩ ቀን መቆየት የተጀመረው መቼ ነው?” አልኩት፡፡

“በቅርብ ይመስለኛል፡፡ ግን ምን ችግር አለው? ቀኖና ነው፡፡ ቀኖና ደግሞ ይሻራል፣ ይስተካከላል፡፡ አባታችን ይህንን ሲናገሩ ሰምቻለሁ” አለ በድፍረት፡፡

“ማናቸው አባትህ?” አልኩት ዐይን ዐይኑን እየተመለከትኩ፡፡

“ባሕታዊ እከሌ ናቸዋ” አለኝ፡፡

በጣም አዘንኩ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ተዘንግቶ፣ ቀድሞ አባቶች የሠሩትን ሥርዓት በባህታዊ ነኝ ባዮች ሲሻር ያሳዝናል፡፡

“ለመሆኑ ማነው የሚሽረውና፣ የሚያስተካክለው?” አልኩት እልህ እየተናነቀኝ፡፡

“ቤተ ክርስቲያን ናታ፡፡”

“የቤተ ክርስቲያን መብት ከሆነ አንድ ባሕታዊ ይህንን የመሻር ምን ሥልጣን አለው? ለምእመኖችዋ ውሳኔውን ማሳወቅ ያለባት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ እሷ ደግሞ አባቶች የሠሩትን ሥርዓት የምታጸና እንጂ የምታፈርስ አደለችም” አልኩት በንዴት፡፡

“አንተ እንደፈለግህ፡፡ እኔ ግን የባሕታዊ አባቴን ድምጽ እሰማለሁ፡፡ በቃ አትጨቅጭቀኝ!” በማለት ፊቱን አዞረብኝ፡፡

ለመሆኑ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሲጣስ አደብ የሚያስገዛው ማነው? ለማንስ አቤት እንበል? ሱባኤያችን በረከት የሚያሰጥ ይሆን ዘንድ ምን እናድርግ? ሱባኤ ሔጄ ይህንን ታዘብኩ፡፡ እናንተስ ምን ትላላችሁ?

“በዐዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለች” (ሲራ.፲፮፥፬)

የአንድ ሀገር ቋሚ ሀብቶቿ ልጆችዋ ናቸው፡፡ ሕዝብ ሀገር ወዳድና ጠንካራ ሲሆን አነዋወሩን ከመቀየር ጀምሮ የሀገሩን ታሪክ በወርቃማ ቀለም መጻፍ ይችላል፡፡ እንዲህ ያለው ተስፋ ብዙውን ጊዜ በአዳጊ ሀገሮች ለወጣቶች ይሰጣል፡፡ ይህ የሚሆነው በብዙ ሀገሮች ውስጥ ከፍተኛውን የነዋሪ ቁጥር ከሚይዙት ውስጥ ሕፃናትና ወጣቶች በመሆናቸው እና በአባቶች ፈንታ አገር የሚረከቡም ጭምር በመሆናቸው ነው፡፡

በሀገራችን ኢትዮጵያም ይህን ከፍተኛ ቁጥር የያዙት ሕፃናትና ወጣቶች ናቸው፡፡ እንደ ሌሎች አዳጊ ሀገራት ሁሉ የሀገሩቱ አስከፊ ገጽታ በመቀየሩ ረገድ ሰፊ ሚና ያላቸው እነዚህ ወጣቶች ናቸው፡፡

ቤተ ክርስቲያንም ሀገር ወዳድ፣ ታሪክ ሠሪና ታታሪ ትውልድ የማፍራት ሥራዋን ስትሠራ ኖራለች፡፡ የሀገራችንን ሕዝብ ከፊደል ቆጠራ እስከ ሥርዓተ መንግሥት ቀረጻ አስተምራና የሀገሪቱን ታሪክ በሕዝቡ ቋንቋና ፊደል ጽፋ ያቆየች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ በዚህ ትውልድም ውስጥ የለውጥ አርአያ የሚሆን ዜጋ ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ውስጥ የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ትገኛለች፡፡

ትውልድ መፍትሔ ፈላጊ ሊሆን የሚችለው አዋቂ የሆነ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ የዕውቀት ብርሃን የያዘ ትውልድ የድህነትና የበሽታ፣ የጦርነትና የርኃብ ጨለማ አያሰጋውም፡፡ የዕውቀት ብርሃን የችግር መፍቻ ቁልፍ ነውና፡፡ ቤተ ክርስቲያን ከማይነጥፍ ማሕፀኗ ልትወልደውና ልታሳድገው የምትሻው እንዲህ ያለውን ነው፡፡ ለዚህ ነው ጠቢቡ “ከሺህ ልጆች አንድ አዋቂ ልጅ ይሻላል፤ ክፉ ልጅም ከመውለድ ሳይወልዱ መሞት ይሻላል፤ አዋቂ በሆነ በአንድ ልጅ ሀገር ትጸናለችና” በማለት የገለጸው፡፡ (ሲራ.፲፮፥፬)፡፡

ሰው ሁሉ በሙያ ዘርፉ ተሰማርቶ እየሠራ ያለው ዕውቀት ቢኖረው ነው፡፡ ታዲያ ለምን ውጤታማ መሆን አልተቻለም? ብዙ መንፈሳውያን የሆኑና በዕውቀት የበሰሉ ባሉባት ኢትዮጵያ ለምን ሥጋዊ ችግሮች ሰለጠኑ? የሚሉ በርካታ ተመሳሳይ ጥያቄዎች በማኅበረሰባችን ዘንድ የመወያያ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ዕውቀቱም፣ ጉልበቱም፣ ገንዘቡም፣ ጊዜውም ተደምረው ለምን ለውጥ አላመጣም? የለውጡ መሠረት ምንድው? የቅዱሳት መጻሕፍት መጻፍ ቀዳሚ ዓላማ የለውጥን መንገድ መጠቆም ነውና ጠቢቡ በቅዱስ መጽሐፍ የሰጠንን ምክር እንመርምር፡፡ “በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለች” ብሎናልና፡፡

ዕውቀት ማለት በአንድ ዘርፍ ያለን ክህሎት አይደለም፡፡ ሁለቱን ዓይነት የዕውቀት ዘርፎች ይዞ መገኘት እንጂ፡፡ ዕውቀት ሁለት ዓይነት ነው፡፡ ዕውቀት ሥጋዊና ዕውቀት መንፈሳዊ፡፡ አዋቂነትም ሁለቱንም ዓይነት አጣምሮ መያዝ ነው፡፡ በአንድ ጎን ወይም ዘርፍ ማደግ ብቻውን የሰው ልጆችን ፍሬያማ አያደርግም፡፡ ለሀገር ለወገን ለቤተሰብና ለራስ መሆን የሚችል ዜጋ ለማፍራት በትክክል “በሁለት ወገን የተሣለ ሰይፍ” መሆን ያስፈልጋል፡፡ ይህ ነው በዕውቀት ሥጋዊ፣ በዕውቀት መንፈሳዊ፣ መታነጽ ማለት፡፡

ዕውቀት ሥጋዊ ከቤተሰብና ከአካባቢያዊ ሁኔታዎች ጀምረን በየደረጃው በትምህርት ማእከላትና በልዩ ልዩ መንገዶች የምናገኘው የተግባርና የቀለም ትምህርት ነው፡፡ ይህ ዕውቀት በተለይም በምድራዊ ኑሮአችን የሚኖረንን የግልና የማኅበር ሕይወት መልካም ለማድረግ ካለው ፋይዳ ባሻገር ለማኅበረሰባችንና ለሀገራችን ያለንን የምናካፍልበት የምድራዊ ኑሮ ክፍል ነው፡፡

ዕውቀት መንፈሳዊ የሰው ልጅ ከምድራዊ ኑሮው በኋላ ያለውን ሰማያዊ አነዋወር /አኗኗር/ የሚዋጅበት ዕውቀት ነው፡፡ ሁለቱም የዕውቀት ዓይነቶች ተፈላጊ ናቸው፡፡ ሰው የሁለት ነገር ውሕድ ፍጥረት ነው፡፡ የሥጋና የነፍስ፡፡ ሁለቱን ባሕርያት ማጣጣም ማዋደድና ማስታረቅ የመንፈሳውያን ሰዎች ዕውቀት መመዘኛ ነው፡፡ የሰው ልጅም ይህን ይይዝ ዘንድ ግድ ይለዋል፡፡

“ያልተገራ ፈረስ ገራገር ይሆናል፣ ያልተማረ ልጅም አውታታ ሆኖ ያድጋል፡፡ /ሲራ.፴፥፰/፡፡ ፈረስን መግራት ካልቻሉ ወይም አሥረው መያዝ ካልቻሉ አደጋ እንደሚያስከትል ሁሉ ከዕውቀት ሥጋዊ እና ከዕውቀት መንፈሳዊ ያልተማረ ልጅም አውታታ፣ ባተሌ፣ ባካና፣ ቀማኛ፣ ሥራ ፈት እየሆነ ያስቸግራል፡፡ ይህ ሁሉ የጨለማ ሥራ የሚሠራው ከዕውቀት ብርሃን የራቀ በመሆኑ ነው፡፡ ዕውቀት የሰው ልጅ ብርሃን ናትና፡፡

የሀገርን ሀብት የሚበዘብዝና የሚሠርቅ፣ ጉቦ የሚቀበል ዜጋ ምንም እንኳን በወረቀት ያስደገፋቸው የዕውቀቱ ማስረጃዎች /የምሥክር ወረቀቶች/ በዝተው የሥልጣንን እርከን እንዲቆናጠጥ ቢያስችሉትም ገና የዕውቀት ብርሃን ያልበራለት የእናት ጡት ነካሽ ነው፡፡ በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለች እንጂ አትፈርስም፣ ትለመልማለች እንጂ አትመዘበርም፡፡

አዋቂ የሆኑ የኢትዮጵያ ልጆች ሀገራቸው ከሰሜን ጫፍ እስከ ደቡብ፣ ከምዕራብ እስከ ምሥራቅ ያላትን የቀደመ ታሪክ የሚያውቁ፣ ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያላቸውን የታሪክ አንድነት ነጥለው የማያዩና በዚህም የሚኮሩ ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የኢትዮጵያ ታሪክ የሚሆነው በሰዎች ስምምነት አይደለም፤ በሺዎች ለሚቆጠሩ ዘመናት አብረው የተሻገሯቸው ዘመናት እንጂ፡፡ ለዚህም የኢትዮጵያ ታሪክ እውነተኛ ምንጮች የቤተ ክርስቲያናችን መዛግብት መሆናቸው ብቻውን ምሥክር ነው፡፡ ትውልዱን አዋቂ የሚያሰኘውም ዕድሜ ብቻ ሳይሆን እውነትንም ጭምር ከጠገቡት መዛግብት እውነቱን መረዳት ማወቅና ማሳወቅ ሲችል ነው፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለኢትዮጵያ ሀገራችን ያበረከተቻቸውን አስተዋጽኦዎች ዘርዝሮ መጨረስ አይቻልም፡፡ በጥቅሉ ያየናቸው እንደሆነ ግን በርካታ ሥነ ጥበባት፣ ማኅበራዊ አንድነትን /በሕዝቦች ዘንድ ተዋሕዶና ተፋቅሮ የመኖር ባሕል/ ወዘተ… ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ይህ ሁሉ በአዋቂ ልጆቿ ትጋት የተገኘ ነው፡፡

በልዩ ልዩ ደረጃዎች የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና የኢትዮጵያ ወዳጆች የሀገሪቱን ማንነት በግልጽ የተረዱ ሊሆኑ ይገባል፡፡ በዚህ ዕውቀት ላይ ተመሥርተው የሚሠሩት የአገር ግንባታ ሥራ ውጤታማ ብቻ ሳይሆን አኩሪ ታሪክም ይሆናልና፡፣ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ የምትገኝ ሀገር ብቻ አይደለችም፡፡ በሕዝቦቿ ዘንድ አኩሪ ታሪክ ያላት የነጻነት ምልክት፣ በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ተደጋግሞ ስሟ በበጎ የተጠቀሰ መንፈሳዊት ሀገርና የክርስትና ደሴትም ጭምር ናት፡፡ /መዝ.፷፯፥፴፩፤አሞ.፱፥፯/ አዋቂ ልጅ በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ ኢትዮጵያን የሚያውቃት ነው፡፡ ማንነቱን በትክክል መረዳት ያልቻለን ሰው እንዴት አዋቂ ልንለው እንችላለን?

በሁለት ወገን የተሳሉ ሰዎች ልበ ብርሃን በመሆናቸው አስተዋይነት ገንዘባቸው ነው፡፡ “አስተዋይነት ያልታከለበት ዕውቀት ለውድቀት” እንደሚባለው ከመውደቅ በፊት አስተዋይነትን ገንዘብ ልናደርግ ይገባል፡፡ አስተዋይነት አዋቂ ነን ከሚሉ ሰዎች መካከል በሁለት ወገን የተሳሉ ሰዎችን ለይታ የምታሳይ የመንፈሳውያን ሰዎች መለያ ናት፡፡

የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነጾር በከፈተው ት/ቤት እንዲማሩ የተመረጡ ተማሪዎች ከመስፈርቶቹ መካከል ብልሃተኝነት አንዱ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ተመርጠው ወደ ትምህርት ማእከሉ ከገቡ በርካታ ተማሪዎች መካከል በአስተዋይነት ተለይተው የወጡት በዕውቀትና በመንፈሳዊ ትጋት የበሰሉት ሠለስቱ ደቂቅ ነበሩ፡፡ /ዳን.፩፥፬/ የሦስቱ ሕፃናት በስደት አገር እየኖሩ ለሕዝባቸውና ለሀገራቸው ታሪክ መሥራት፣ ሕዝባቸውን መጽናትና በስደት አገር ሀራቸውን በበጎ ማስጠራት የቻሉት በአስተዋይነት ነው፡፡

የአስተዋዮች ጸሎት ሁልጊዜ በማስተዋል ይመላለሱ ዘንድ ነው፡፡ ዕውቀትና ጥበብን፣ ገንዘብንና ጉልበትን አስማምቶ ውጤት ማምጣት የሚቻለው በማስተዋል ነውና፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ወደ አባቱ የንግሥና ዙፋን ሲመጣ በጸሎቱ አስተዋይነት ገንዘብ እንዲያደረግ መለመኑ ለዚህ ነው፡፡ /፩ነገ.፫፥፱/፡፡ “በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለችና፡፡”

በጠቢቡ ሰሎሞን ዘመን አንድ እስራኤል ነበር፡፡ ጠቢቡ አዋቂ ልጅ ነበርና ለመጀመሪያ ጊዜ ለእግዚአብሔር ታቦት ማደሪያ ቤት /ቤተ መቅደስ/ አነጸ፡፡

አስተዋይነት ያለንን ዕውቀት በአግባቡ መጠቀም መቻል ነው፡፡ በየደረጃው የተማርናቸውን ትምህርቶች በአግባቡ በሥራ መተርጎም ከቻልን አስተዋይነታችን በውጤታማነታን ይገለጻል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ልጅነታችንን በቅዱሳን አሠረ ፍኖት የምንጓዝ መሆናችንን ለሕግጋተ እግዚአብሔር የምናረጋግጠው በምግባራችን ነው፡፡ ይህ ነው አዋቂ የሚያሰኝ ተግባር፡፡

ታማኝነት ሌላኛው የአዋቂዎች መገለጫ ነው፡፡ ሀገርን ለማጽናት የሕዝብን ኑሮ ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ታማኞችን ማግኘት ካልተቻለ ከንቱ ድካም እየተደከመ ነው፡፡ በቤተሰቡ መካከል ጠብን የሚዘራ ሰው ለሀገር ሰላም ያመጣል ማለት እንዴት ይቻላል? የእናቱን መሀረብ የሚፈታ፣ የአባቱን ኪስ የሚያወልቅ ልጅ ነገ በሚሠማራበት የሥራ መስክ በታማኝነት ያገለግላል ማለት ያስቸግራል፡፡ አዋቂነት ታማኝነት ነው፣ ሀገርን ማጽናትም ከታማኝነት ይጀምራል፡፡

የልጆችን ሰብእና እንዴት ወደዚህ ደረጃ እናምጣ? በልጅነት ዕድሜው ወላጆቹ የሚያወጡለት የትምህርት ቤት ክፍያ፣ ስለሚለብሰው ልብስና ስለ ሌሎች ተመሣሣይ ወጪዎቹ ኃላፊነት የማይሰማውና ግድየለሽ አድርጎ ልጆችን መቅረጽም በነገ ሕይወታቸው ንዝህላልና በአሠራር ዝርክርክነት የሚታወቁ ያደርጋቸዋል፡፡ ስለዚህ የታማኝነትና የኃላፊነት መልካም ሥነ ምግባራትን በልጆች ሥነ ልቡና ውስጥ ከልጅነት ዕድሜ ጀምሮ ማስረጽ አለብን፡፡ በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለችና፡፡ ወላጆች በእግዚአብሔር ፈቃድ ልጆችን ወደዚህ ምድር እንዳመጡ ሁሉ ለልጆቻቸው ሕይወት ስኬታማነት ሊጠበቡ ያስፈልጋል፡፡ አልሚም አጥፊም ትውልድን  ይፈጥራሉና፣ አዋቂም አጥፊም ልጅ ያስገኛሉና፡፡

ሀገርን የሚጠብቅ፣ የሚገነባና የሚያጸና ትውልድ መቅረጽ ካልተቻለ የሚያፈርስ፣ የሚሸጥና የግል ጥቅሙን የሚያስቀድም ዘር/ትውልድ/ ያስቀራሉና ታማኝነትን፣ ሀገር ወዳድነትንና የእምነት ጽናትን ከልጅነት ዕድሜ ጀምሮ ልጆችን ማስተማር አለብን፡፡

የልጆች በቅዱሳት መጻሕፍት ምክር፣ በወላጆች ተግሣጽ ማደግ የሚያስገኘው ጥቅም ብዙ ነው፡፡ ጠቢቡ “እናንት ልጆች የአባትን ተግሣጽ ስሙ፣ ማስተዋልንም ታውቁ ዘንድ አድምጡ” /ምሳ.፩፥፬/ በማለት ልጆች የወላጆቻቸውን ምክር ያደምጡ ዘንድ ይመክራል፡፡ ልጆችን በምክር በማሳደግ አስቀድሞ ወላጆች ታላቁን አደራ ተወጥተዋል ማለት ነው፡፡ ልጆች ከእግዚአብሔር እጅ የተቀበልናቸው የከበሩ ሥጦታዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም ልጆችን መንከባከብና በሥነ ምግባር ማሳደግ የእግዚአብሔርን ሥጦታ መጠበቅ ነው፡፡ /መዝ.፩፻፮፥፫/፡፡ ከወላጆችም በላይ ግን ልጆች የታማኝነት፣ የትሕትናና የዐዋቂነት ሥነ ልቡና እያዳበሩ የሚያድጉ ከሆነ ተወዳጅና ተመራጭ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህም አብዝቶ ተጠቃሚዎች ልጆች ይሆናሉ፡፡ የልጆች ጥቅም የወላጆችም ጥቅም ነው፡፡ የልጆች መልካምነት ለወላጆች ኩራት ነው፡፡ ለልጆችም አስፈላጊና ጠቃሚ ነው፣ በወላጆች ዘንድ ተወዳጅ ያደርጋልና፡፡ /ምሳ.፬፥፫/፡፡ በዚህ ብቻ አይበቃም በሥነ ምግባር በሃይማኖት ተኮትኩተው በሚያድጉ ልጆች ቤተ ክርስቲያንም ሀገርም ተጠቃሚዎች ናቸው፡፡ “በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለች” እንደተባለ፡፡

በአጠቃላይ ሀገራችንም ቤተ ክርስቲያናችንም በርካታ “አዋቂዎች” የሚሹበት ዘመን ቢኖር ዛሬ ነው፡፡ አስተዋዮች ብቻ ሳይሆኑ በመንፈስ ቅዱስ ፀጋ የሚሠሩ የሃይማኖት ልጆችን በዕቅድና በሥርዓት ማሳደግ አለብን፡፡ ካለፈው ተምረው መጻኢውን የሚተነብዩ ለፈቃዳቸው፣ ለሐሳባቸውም እግዚአብሔርን በማስቀደም የሚሠሩ ልጆችን ማዘጋጀት የሚጀምረው ደግሞ በልጅነት ዕድሜአቸው ነው፡፡ እነዚህ ናቸው ሀገርን የሚያጸኑ፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚጠብቁ፡፡

ቤተ ክርስቲያን የምትፈልገው አዋቂ ልጅ መስቀሏን በገንዘብ የማይለውጠውን፣ ቅርሶቿን የማይሸጠውን፣ ሃይማኖቷን የማይክደውን ነው፡፡ በከፋ ፈተና ውስጥ እያለፈ እንኳን “የማመልከው አምላክ ያድነኛል፣ ባያድነኝ እንኳ እንዲህ ያለውን አላደርግም” የሚለውን ነው፡፡ /ዳን.፫፥፲፯/፡፡

ሀገራችን ብዙ ጠበብት፣ ብዙ አዋቂዎችን ትሻለች፡፡ ፊደል የቆጠሩ፣ እንግሊዝኛ የሚናገሩ ብቻ ሳይሆን ወደተሻለ የዕድገት ደረጃ የሚያሸጋግሯትን ቅን ልቡና ያላቸውን አዋቂዎች ትሻለች፡፡ ሀገራችን የታሪኳ መበረዝ፣ የዕድገቷ ኋላ ቀርነት፣ የድህነቷ መብዛት፣ የሕፃናቷ ሞት፣ የሥነ ምግባር ውድቀት፣ የጠላቶቿ መብዛት፣…. የሚያስቆጫቸው፣ የሚያቃጥላቸውና ለለውጥ የሚሠሩ አዋቂ ልጆች ያስፈልጓታል፡፡

“ሮም በአንድ ቀን አልተገነባችም” እንደሚባለው የኢትዮጰያን ዕድገት በአንድ ጀምበር አናመጣውም፡፡ ይልቁንም አዋቂ ልጅ መርሐ ግብር ነድፎ የድርሻውን ጠጠር ይወረውራል፡፡ ያኔ ኢትዮጵያን እንደ ጥንቱ ሁሉ ከታላላቅ ሀገሮች ተርታ የምናይበት ዘመን ይመጣል፡፡

አዋቂዎችን አያሳጣን፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ጥር፲፭-፴፣ ፳፻፩ ዓ.ም

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

በሀገር ውስጥና በውጭ የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት፣ እንዲሁም ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ!

የይቅርታ ባለቤት የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ!!

“ወሣህሉኒ ለትውልደ ትውልድ ለእለ ይፈርሕዎ፣ ይቅርታው ለሚፈሩት ለልጅ ልጅ ነው” (ሉቃ.፩፥፶)፡፡

ይህ ኃይለ ቃል የቅዱስ መጽሐፍ ቀዋሚ ምሰሶ ሆኖ በብዙ ቦታ የሚገኝ ነው፣ ቃሉ እግዚአብሔር ለሚፈሩት የሚያጎናጽፋቸውን የምሕረት ቃል ኪዳን በውስጡ ይዞአል፤ ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያምም እግዚአብሔርን ባመሰገነችብት የምስጋና መዝሙር ይህንን ኃይለ ቃል ተናግራዋለች፡፡

በዚህ ኃይለ ቃል የእግዚአብሔር ይቅርታ ምን ጊዜም የከበረና እንደ ተስፋ ቃሉ የሚፈጸም መሆኑ፣ ያም ሊሆን የሚችለው ለሚፈሩት ሰዎች መሆኑ በሚገባ ተገልጿል፡፡ የእግዚአብሔር ይቅርታ አጭርና ቀጭን ሳይሆን ለልጅ ልጅ እንደሚሆንም ተብራርቷል፡፡

ይህ አባባል እውነት እንደሆነ ለመረዳት ከእኛ ከሰዎች የበለጠ ሌላ ምስክር ሊኖር አይችልም፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ሣህሉ ለእግዚአብሔር መልአ ምድረ፣ የእግዚአብሔር ይቅርታ ምድርን መላ” ብሎ እንዳስተማረን ይቅርታው በየጊዜው በዝቶ ባይደረግልን ኖሮ ውሎ ማደሩ የሚቻል አልነበረም፡፡ እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ኃጢአትን፣ ክፋትን፣ ርኵሰትንና ክህደትን የሚጠላ አምላክ ነው፡፡ እኛ ደግሞ ከእነኚህ ክስተቶች ለአንድ ደቂቃ ስንኳ ጸድተን አናውቅም፣ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር በቅጣት ፈንታ ምሕረትንና ይቅርታውን እያበዛልን በምሕረቱ ተጠልለን እንኖራለን፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምን በመውደድ፣ አስተብቍዖቷን፣ ጸሎቷንና ልመናዋን በመሻት ይህንን ጾም በመጾም በመንፈስ ተሞልታ ያስተማረችንን ፈሪሐ እግዚአብሔር ገንዘብ በማድረግ መሆን አለበት፤ እንደ ተስፋ ቃሉም ለቃሉ በመታዘዝ መሆን አለበት፤ ቃሉ ይቅር እንድትባሉ ይቅር በሉ፣ ሰላምና አንድነትን አጽንታችሁ ያዙ ይለናል፡፡

ይህን ይቅርታ ለማግኘት የተጠየቅነው ዋናው ነገር እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ እግዚአብሔርን በእውነት የምንፈራ ከሆነ ይቅርታ ለመስጠትም ሆነ ለመቀበል ዳገት አያግደንም ነው፡፡ እግዚአብሔርን መፍራት ማለት በምሠራው ሥራ፣ በመንናገረው ቃል፣ በምናስበው ሐሳብና ምኞት ሁሉ እግዚአብሔር ያውቅብናል፣ ያየናል፣ ይፈርድብናል የሚል አስተሳሰብ በውስጣችን ኖሮ ክፉ ድርጊትን ከማድረግ እንድንቆጠብ መሆን ማለት ነው፡፡

ሰው ሁሉ እግዚአብሔርን ከእርሱ ውጪ እንዳለ ሳይሆን በአጠገቡና በመንፈሱ ውስጥ ሆኖ እንደሚያውቅበት ተገንዝቦ እግዚአብሔርን መፍራት አለበት፣ የሰላምና የአንድነት መሠረት ከፈሪሐ እግዚአብሐየር መነሣት ሲችል ዘላቂና ጠቃሚ ይሆናል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናትና ምእመናን!

ዘንድሮ የምጾመው ጾመ ማርያም ሀገራችንና ሕዝባችን በሰው ሠራሽና በተፈጥሮ አደጋ ውስጥ ተከበው ባሉበት ወቅት ነው፤ የተጋረጡብን ፈተናዎች እግዚአብሔርን ይዘን ካልሆነ በቀር ብቻችንን ሆነን የምንወጣቸው አይደሉም፤ በእግዚአብሔር ከለላነት እነዚህን ፈተናዎች ልናልፋቸው ከሆነ እሱን በመፍራት ከክፋታችን መመለስና ንስሓ መግባት አለብን፤ በነገው ዐለት የምንጅመረው የጾመ ማርያም ሱባኤም ዋናው ዓላማው በንስሓ ወደ እግዚአብሔር ለመመለስና እሱን በመፍራት ለእሱ ተገዢዎች ለመሆን ነው፡፡

ሁሉም እንደሚያውቀው ንስሓ በይቅርታና በዕርቅ መታጀብ ይገባዋል፤ ችግሮቻችን ምን ያህል ቢበዙም ለእግዚአብሔር ብለን ብንፈጽመው ይቅርታና ዕርቅ፣ በምናረጋግጠው ሰላምና አንድነት ተሸናፊዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ችግሮችን ለማሸነፍ ብሎም ለማስወገድ ከይቅርታና ዕርቅ፣ ከሰላምና አንድነት የተሻለ አማራጭ እንደሌለልሂቃኖቻችንም ሆኑ ሕዝቦቻችን በውል መገንዘብ አለባቸው፡፡

ኢትዮጵያ የምትባለው ሀገር የዚህ ትውልድ ሀገር ብቻ አይደለችም፤ ያለፉ አባቶች፣ የሚመጡ ትውልዶችም የኢትዮጵያ ባለቤቶች ናቸው፡፡ እኛ በክብ ጠረጴዛ ተገናኝተን ተወቃቅሰንና ተመካክረን ችግሮቻችንን በተሸንፎ ማሸነፍ ጥበብ ማረም ካቃተን ቢያንስ ኢትዮጵያን ባለችበት ሁናቴ ለባለመብቱ ለመጪው ትውልድ የማስተላለፍ ግዴታ እንዳለብን መዘንጋት የለብንም፤ ነገሮችን ሁሉ በትዕግሥት፣ በአርቆ አስተዋይነትና በሰላማዊ ሁኔታ ለማስተናገድ ያላሰለሰ ጥረት ማድረግ ይገባናል፤ በመሆኑም ኢትዮጵያ የገጠሟትን ፈተናዎች ሁሉ ተቋቁማ በአሸናፊነት መሻገር የምትችለው እግዚአብሔርን በመፍራት ለይቅርታና ለዕርቅ ስንዘጋጅ ነው፤ ስለዚህ ይህ ግንዛቤ ተወስዶ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ቆመናል የሚሉ የፖለቲካ ተፎካካሪ ወገኖች ሁሉ አንድ ላይ ተገናኝተውና በክብ ጠረጴዛ ሆነው በመወያየት የሀገሪቱን አንድነት፣ ሰላምና ልማት እንዲያስቀጥሉ በዚህ አጋጣሚ በእግዚአብሔር ስም እንማፀናለን፡፡

በመጨረሻም፣

ሕዝበ ክርስቲያኑ የጾም ሱባኤ በኮረና ቫይረስ እንዳይጎዳ ጥንቃቄ በማድረግ የሱባኤውን ወቅት ስለ ሀገር ሰላምና አንድነት በኃዘን፣ በምህላ፣ በጸሎት፣ በንስሓና በፍቅር፣ የተቸገሩትንም በመርዳት እግዚአብሔርን በመፍራት እንዲያሳልፍ አባታዊና መንፈሳዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

                        እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፣ ይቀድስ፤

                        ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሐምሌ ፴ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

ውጣ ውረድ

በእንዳለ ደምስስ

ከአርሲ ነገሌ አምስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን መጠለያ ውስጥ ከአንድ መቶ ያልበለጥን ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ሰሞኑን “መንደራችንን ከክርስቲያኖች የማጽዳት ዘመቻ” በሚል በጽንፈኛ አክራሪ ሙስሊሞች በተከሠተ ወረራ መሰል ዘመቻ ተፈናቅለን ተጠልለናል፡፡ መኖሪያ ቤቶቻችን ተቃጥለዋል፣ ንብረቶቻችን ወድመዋል፣ ከጥቂት አባወራዎች በስተቀር አባቶቻችን ታርደዋል፡፡ በእግዚአብሔር ቸርነት የተረፍነው ቤት ንብረታችንን ጥለን ራሳችንን ለማዳን ቤተ ክርስቲያንን መጠጊያ አድርገናል፡፡

አባቴ በሰማዕትነት ካለፉት ውስጥ አንዱ ነው፡፡ እኔንና እናቴን ደብድበው ሲጥሉን፣ አባቴ እኛንና ቤት ንብረታችንን ለመከላከል ሲል ባደረገው ተጋድሎ እንደ በግ እጅና እግሩን አስረው በፊት ለፊታችን አርደውታል፣ ቤታችንን ከነከብቶቻንና ንብረቶቻችን ሁሉ እሳት ለቀውበታል፡፡

ሰፈሩ በለቅሶና በዋይታ ተሞልቶ ሁሉም ራሱን ለማዳን ማቄን ጨርቄን ሳይል ነፍሱን ለማዳን ይሯሯጣል፡፡ እንደምንም እናቴን ከወደቀችበት አንስቼ ወደ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ነፍሳችንን ለማዳን ሮጠን ከክርስቲያን ወገኖቻችን ጋር ተቀላቀልን፡፡

ተወልጄ ያደግሁት እዚያው መንደር ውስጥ ነው፡፡ የ፳፯ ዓመት ወጣት ስሆን ሰላማዊት ዋለልኝ እባላለሁ፡፡ እኔና ቤተሰቦቼ በመንደሩ በጣት ከሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች መካከል ነን፡፡ በርካታ የእስልምና እምነት ተከታዮች የሚገኙባት ሲሆን በየአራት ወይም አምስት መቶ ሜትሮች ከግዙፍና ዘመናዊ እስከ ቆርቆሮ ለበስ አነስተኛ መስጊዶች ከቁመታቸው ገዝፈው ይታዩባታል፡፡ ፺፭ በመቶ የሚሆነው የአካባቢው ነዋሪ የእስልምና ተከታይ ሲሆን፣ ወንዶቹን ነጭ ጀለቢያ ሴቶቹን ደግሞ ጥቁር ሂጃብ ለብሰው በየመንገዱ ማየት የተለመደ ትእይንት ነው፡፡

በአቅራቢያችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት ተከታዮች የምንገለገልበት የፃድቁ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ብቸኛው ነው፡፡ መላው ቤተሰባችን በእምነታችን በጣም ጠንካራ ከሚባሉት ውስጥ እንመደባለን፡፡ በተለይም አባቴ ይህ ቤተ ክርስቲያን በአያቴ ከፍተኛ ጥረት የተተከለ ነው ብሎ ስለሚያምን ልዩ ፍቅር አለው፡፡ ባለው ጊዜ ሁሉ ዘወትር ቤተ ክርስቲያን የጎደላትን በማሟላት ደከመኝ ሰለቸኝ የማይል ስለሆነ ከእናታችን ጀምሮ ቤተሰቡ ሁሉ የእርሱን ፍኖት ተከትለን አድገናል፡፡ በየቀኑ አስገዳጅ ችግር ካልገጠመን በስተቀር ቤተ ክርስቲያን ሄደን ሳንሳለምና የኪዳን ጸሎት ሳናደርስ አንውልም፡፡ የኪዳን ጸሎት ባይታጎልም የአገልጋይ እጥረት ስላለ በሰንበተ ክርስቲያንና በዓመት አራት ጊዜያት ከሚከበሩ የፃድቁ መታሰቢያ ክብረ በዓላት፣ በተጨማሪ የዘመን መለወጫ፣ የልደት፣ የትንሣኤ እና የደብረ ታቦር በዓላት ብቻ ይቀደስበታል፡፡

በቀድሞው ዘመን ክርስትና ከተስፋፋባቸው አካባቢዎች አንዱ የነበረ ቢሆንም ቀስ በቀስ ግን እስልምናው አይሎ ኦርቶዶክሳውያን አረጋውያን ዐረፍተ ዘመን እየገታቸው በማረፋቸው፣ የእስልምናው ተጽእኖ መቋቋም ተስኗቸው ወደ ከተማ የገቡ በርካቶች ናቸው፡፡ ክርስቲያን የነበሩ ልጃገረዶችንም በጠለፋም ይሁን በሀብት የበላይነትና በማስፈራራት በማስለም ስለሚያገቧቸው የክርስቲያኑ ቁጥር ተመናምኗል፡፡ በዚህም ምክንያት የአብዛኛው ነዋሪ መሠረት ክርስትና ቢሆንም ዛሬ ግን ተለውጧል፡፡

ለመስፋፋታቸው ዋነኛው ምክንያት ከአስገዳጅነታቸው በተጨማሪ የክርስቲያኖች ቸልተኝነት፣ ክርስቲያን ወንዶች በሥራ ምክንያት በሚያደርጉት እንቅስቃሴ የትዳር አጋሮቻቸውን ከከተማ ይዘው ስለሚመጡ የአካባቢው ተወላጅ የሆንን ልጃገረዶች ወደ ዩኒቨርሲቲ የመግባት ዕድል ካለገኘን ወይም ወደ ከተማ ካልኮበለልን በስተቀር ትዳር ሳንይዝ ዕድሜአችን እያለፈ በዕድላችን ስናማርር እንኖራለን፡፡

ሁለቱ ታላቅ እኅቴና ታናሼ በዚህ ምክንያት በሙስሊም ወጣቶች ገንዘብ ተደልለው ምድራዊ ሕይታቸውን ለማሳመር ሲሉ የእግዚአብሔር ልጅነታቸውን ክደው፣ የአባቴን ልፋትና መሠረታቸውን ጥለው ሰልመዋል፡፡ ሁለቱ ወንድሞቼም የከተማ ነጋዴ ስለሆኑ እንደ ሌሎቹ የአካባቢያችን ወጣቶች በከተማ ኑሯቸውን መሥርተው፣ በከተማው ያገኟቸውን ሴቶች አግብተው ይኖራሉ፡፡ አባቴ እኅቶቼን ለማስመለስ ያደረገው ጥረት ስላልተሳከለት በኀዘን እንደተኖር ነበር፡፡

በትምህርቴ እስከ ፲፪ኛ ክፍል ልድረስ እንጂ ውጤት ስላልመጣልኝ እቤት ቀርቻለሁ፡፡ የቤተሰቦቼን እጅ ከመጠበቅ እያልኩ ያልሞከርኩት ሥራ የለም፤ ግን አልተሳካልኝም፡፡ በቅርቡ ግን ሰፈራችን ከሚገኝ ጉልት ድንች፣ ቲማቲምና የመሳሰሉትን እየቸረቸርኩ ከራሴ አልፌ ለቤተሰቦቼ መርዳት ባልችልም ለራሴ መሆን አላቃተኝም፡፡ አንድ ነገር ግን ይጎድለኛል፤ በዚህም እጨነቃለሁ፡፡ ትዳር መያዝ አለመቻሌ፡፡

ራሴን ዕድለ ቢስ አድርጌ እቆጥረዋለሁ፡፡ ነፍሷን ይማርና አያቴ “አንዲት የገጠር ሴት ትዳር ይዛ ራሷን ካልተካች እንዴት ሴት ተብላ ትጠራለች?” እያለች ስትናገር የምሰማው ድምጽ ሁልጊዜ ዕረፍት ይነሳኛል፡፡

ያገቡም ያላገቡም ሙስሊም ወንዶች እኔን ከመጠየቅ ወደ ኋላ ያሉበት ጊዜ የለም፡፡ በተለያዩ መደለያዎችን ስጦታዎች እጅ እንድሰጥ ከማድረግ እስከ ዛቻና ማስፈራሪያ ይደርስብኛል፡፡ አንዳንዶቹ ሦስትና አራት ሚስት ያላቸው ናቸው መውጫ የሚከለክሉኝ፡፡ ነገር ግን በያዝኩት እውነተኛና ቀጥተኛ በሆነው በክርስትና መንገዴ ከማንም ጋር አልደራደርም፤ የትናንት፣ የዛሬም፣ የወደፊትም አቋሜ ነው፡፡ ከአካባቢው ልማድ አንጻር ዕድሜዬ እየገፋ እንደሆነ ይታወቀኛል፣ ነገር ግን እግዚአብሔር አምላኬን፣ የአምላኬን እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ ቅዱሳን ጻድቃን፣ ሰማዕታትን፣ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ትቼ ከምኮበልል ሞቴን እመርጣለሁ፡፡

ማግባት እንዳለብኝ ውስጤ ያስገድደኛል፡፡ ግን ማንን ላግባ? ፈላጊ እንደሌላት ጋለሞታ ራሴን እቆጥራለሁ፡፡ መልሼ ደግሞ እግዚአብሔር ለእኔ ያዘጋጀው ይኖራል፣ ለምን አጉረመርማለሁ እያልኩ ራሴን ለማጽናናት ጥረት አደርጋለሁ፡፡ ውስጤ ደስታ ርቆታል፡፡ በከፋኝ ሰዓት መሸሸጊዬ ፃድቁ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሔጄ ዕንባዬን እያፈሰስኩ እቆያለሁ፡፡

እኅቶቼን ጨምሮ የቅርብ ጓደኟቼ ብዙዎቹ “ደረቴ ይቅላ፣ የዚህ ዓለም ኑሮን ላጣጥማት” በሚል ፈሊጥ በተኩላዎች ተነጥቀው ጓደኛ የምለው የለኝም፡፡ በየቀኑ “እከሊት እኮ ሰለመች፣ እከሌን እኮ አገባችው” መባል የተለመደ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ቀስ በቀስ የክርስቲያኖች ቁጥር ተመናምኗል፡፡ ያም ቢሆን ግን በሰላም ተከባብሮ ከመኖር ውጪ አንዱ በአንዱ ላይ ተነሥቶ ግጭት ተከስቶ አያውቅም ነበር፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን መልኩን ቀይሮ “ክርስቲያኖችን ከአካባቢው ማጽዳት” በሚል እንቅስቀሴያቸው በየጊዜው ግጭት ማስተናገድ የተለመደ ሆኗል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ብንጠለልም አባቴን መርሳት አልቻልኩም፡፡ ሕይወቱ ቢያልፍ እንኳን አስከሬኑ የአውሬ ሲሳይ እንዳይሆን መቅበር አለብኝ በሚል ስሜት ተነሣሥቼ ግርግሩ ጋብ ሲል አመሻሽ ላይ ወደ ሰፈራችን ሮጥኩ፡፡ አካባቢው ምድረበዳ መስሏል፣ ያስፈራል፣ ቤት ንብረታችን ወድሞ ጭሱ ብቻ አልጠፋም፡፡ አባቴን ከታረደበት ለማንሣት አስከሬኑን ዞር እያልኩ ፈለግሁ፣ ማግኘት ግን አልቻልኩም፡፡ በታረደበት ቦታ የፈሰሰውን ደሙን ብቻ አገኘሁ፡፡ ቁጭ ብዬ አለቀስኩ፡፡

“ልጄ አታልቅሺ፡፡ አባትሽ የጀነት ሰው ነው፡፡ ልጆቻችን እምቢ ብለው አብረን በፍቅር ከኖርናቸው ሰዎች ለዩን፣ ምን እናድርግ ልጄ አቅም አጣን፣ እንደ እናንተው ዕንባችን እናፈስሳለን፡፡ በይ ደሙ እንዳይዞርብሽ ተነሺ” አሉ ጎረቤታችን ሐጂ ሙስጠፋ እነሣ ዘንድ በደከመ ጉልበታቸው እየጣሩ፡፡

“ሐጂ ተዉኝ፡፡ አባቴ ካረፈበት፣ ሰማዕትነት ከተቀበለበት ሆኜ ላልቅስ” ብዬ ሣሩ ላይ ተደፋሁ፡፡

“ልጄ እያደረግሽ ያለው ነገር በጎ አይደለም፣ እባክሽ ልጄ ካገኙሽ ይገድሉሻል፡፡ የአባትሽንና የሌሎችን ጎረቤቶቻችን አስከሬን የአካባቢው ሚሊሺያዎች አንስተው የት እንደወሰዷቸው እኛም አናቅንም፡፡ ለእናትሽ አንቺ እንኳን ትረፊላት” ብለው ካነሡኝ በኋላ  አብረውኝ አለቀሱ፡፡

ተስፋ ቆርጬ በመጣሁበት ፍጥነት እየሮጥኩ የቀረችኝ እናቴና ሌሎች ወደተጠለሉበት የጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በረርኩ፡፡

ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከተጠለልን ሦስተኛ ቀናችን ነው፡፡ ነፍስን ለማቆየት የሚበላ የሚቀመስ ባለመኖሩ የሕፃናት ዋይታ፣ የደካማ እናቶች ጣር፣ ከፍተኛ ድብደባ የደረሰባቸው፣ የተደፈሩ ወጣችና እናቶች ሥቃይ ያስጨንቃል፡፡ የትኛውን አጽናንተን የትኛውን እንተው? የሰቆቃ ዕንባ ከእናቶችና ሕፃናት እንደ ጎርፍ ይፈሳ’ል፣ ካህናቱ ነፍሳቸውን ለማትረፍ ሲሉ ጽላቱን ይዘው ሸሽተዋል፣ አንድም ጠያቂ ሆነ አጽናኝ አካል ብቅ አላለም፡፡

አመሻሽ ላይ ከዐሥር የሚበልጡ የአካባቢው ሚሊሺያዎችና ሦስት የአስተዳደር አካላት በአንድ አይሱዙ መኪና ምግብና ብርድ ልብስ ይዘው መጡ፡፡ በተፈጠረው ነገር ማዘናቸውን፣ ችግሩን የፈጠሩት ፀረ ሰላም ኃይሎች እንደሆኑ በመግለጽ አሰልቺ ዲስኩራቸውን ከደሰኮሩ በኋላ ለተጎዱት ሰዎች ነገ የጤና ባለሙያዎችን ይዘው እንደሚመጡና ለጊዜው ለሕፃናትና ለእናቶች እንዲሁም ለሌሎቻችን የሚሆኑ የታሸጉ ምግቦችን፣ የሚጠጣ ውኃ እና ብርድ ልብሶችን አከፋፍለው ሄዱ፡፡

እናቴ ጭካኔን በተላሞሉ ጎረምሶች በደረሰባት ድብደባ ከተጎዱት ሰዎች አንዷ ናት፡፡ እኔን ግን ከማንገላታት ያለፈ ብዙም ጉዳት አልደረሰብኝም፡፡ ብዙዎቹ የማውቃቸው ልጆች ተደፍረዋል፣ እኔን ግን አምላከ ተክለ ሃይማኖት ከልሎኛል፡፡ ለእናቴና ለእኔ የሚያስፈልገውን ምግብና ብርድ ልብስ ተቀብዬ እናቴን ለመንከባከብ ሞከርኩ፡፡ ረኃብና ጥማችንንም ካስታገሥን በኋላ የተጎዱትን ለመንከባከብ የተወሰንን ሰዎች ተሰባበስን ተሯሯጥን፡፡ ነገር ግን ከፍተኛ ሕክምና የሚያስፈልጋቸው ሰዎች ሁኔታ ከአቅማችን በላይ ሆነ፡፡ ያለን አማራጭ ነገ ይመጣሉ የተባሉትን የጤና ባለሙያዎች መጠበቅ ግዴታ ሆነብን፡፡

አባቴን አሰብኩት፡፡ እኛን ለማሳደግ የከፈለው መሥዋዕትነት፣ ለእምነቱ ያለው ጽናትና ለቤተሰቡ እንዲሁም ለሀገሩ ያለው ፍቅር በቀላሉ መግለጽ አይቻልም፡፡ “እባካችሁ አትግደሉኝ” እያለ እየለመናቸው ፊት ለፊቴ እንደ በግ አረዱት፡፡ ያሰማው የሲቃ ድምፅ እረፍት ነሳኝ፡፡ ምንም መፍጠር ሳልችል፣ ለአባቴ አለሁልህ ሳልለው በፊቴ ታረደ፡፡ ከማልቀስና ከማንባት በስተቀር ሐይወቱን ከግፈኞች እጅ ማዳን የምችልበት መሣሪያ አልነበረኝም፡፡

አንድ ቀን በጠዋት ከቤተ ከርስቲያን ስመለስ በአካባቢያችን በሀብቱ የሚታወቅ ጎልማሳ ጀለቢያውን ለብሶ፣ በረጅም ወፍራም መፋቂያ ጥርሱን እየፋቀ ፊት ለፊቴ ተደቅኖ ያዘኝ፡፡ ከዚህ በፊት በአካል ከማውቀውና ሌሎች ስለ ሀብቱ ሲያወሩለት መስማት ካልሆነ በስተቀር ምንም አይነት ግንኙነት የለንም፡፡ እጄን ለማስለቀቅ ሞከርኩ፡፡ አልተሳካልኝም፡፡

“ምንድነው የምትፈልገው?” በማለት በቁጣ ጠየቅሁት፡፡

“ረጋ በይ፣ ምን ያፈናጥርሻል? ሴት ልጅ አደብ ሲኖራት ነው የሚያምርባት፣ አደብ ግዢ” አለኝ፡፡

በንዴት ገፍትሬው ለመሔድ ጥረት ባደርግም በፈረጠመው ጡንቻው ይዞ አስቀረኝ፡፡

“ለምን አትለቀኝም፡፡ እኔና አንተን የሚያገኛኘን ምንም ነገር የለም” አልኩት እየተጠየፍኩት፡፡

እየሳቀ “ያገናኘናል እንጂ፡፡ እኅቶችሽ እንዴት ተንደላቀው እንደሚኖሩ አታውቂም? የአጎቶቼ ልጆች ናቸው ያገቧቸው” አለኝ፡፡

“እና?”

“እናማ እኔም አንቺን አገባለሁ” አለኝ ሳያመነታ፡፡

“ገድል ግባ፡፡ እኔና አንተ ምን ኅብረት አለን? ዞር በልልኝ ልሂድበት፡፡”

“እኔን ተራምደሽማ አትሔጂም፡፡ ለጥያቄዬ መልስ እፈልጋለሁ” አለ ቁጣው እያገረሸ፡፡

“አልችልም፡፡ ሂድና በገንዘብ የምትደልላትን ፈልግ፡፡ እኔ ክርስቲያን ነኝ” አልኩት ከራስ ፀጉሩ እስከ እግር ጥፈሩ በመጠየፍ እየተመለከትኩት፡፡

“እንደ ሦስቱም ሚስቶቼ ምንም ሳላጓድል ነው አንቀባርሬ ነው የማኖርሽ” አለ እየሳቀ፡፡

ያለኝን ኃይል አጠራቅሜ ገፍትሬው መንገዴን ቀጠልኩ፡፡ ባለበት እንደቆመ የፌዝ ሳቁ ብቻ ተከተለኝ፡፡

እቤት እንደተመለስኩ እያለቀስኩ ለአባትና እናቴ ነገርኳቸው፡፡ “እኛ ለአንቺ መሆን አያቅተንም፡፡ በክርስትና ሕይወትሽ ጠንክሪ፣ የእግዚአብሔርንም ጊዜ ጠብቂ፡፡ እንደ እኅቶችሽ እንዳናዝንብሽ ተጠንቀቂ” በማለት አባቴ አቅፎ አጽናናኝ፡፡

እናቴም “ዕድሜዬ ገፋ፣ ቆሜ ቀረሁ እያልሽ አትጨነቂ፤ እግዚአብሔር ምን እንዳዘጋጀልሽ አታውቂም፡፡ ልመናሽ ወደ እግዚአብሔር ይሁን፣ በገንዘብና ብልጭልጭ ነገር አትታለዪ፣ እኅቶችሽን አጥተናልና አንቺንም እንዳናጣ አደራሽን” አለችኝ፡፡

በዐራተኛው ቀን ጠዋት ከወረዳው የሕክምና ባለሙያዎች መጥተው ጎበኙን፡፡ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸውን እየለዩ ወደ መኪናዎቻቸው ወስደው በሆስፒታል ደረጃ ሕክምና እንደሚያስፈልጋቸው ከገለጹ በኋላ ለሌሎቹ አስፈላጊውን የመጀመሪያ ሕክምና ዕርዳታ አደረጉላቸው፡፡

ከነርሶቹ መካከል አንገቷ ላይ ወፈር ያለ ክር ያሰረችው ነርስ ሁላችንንም ሰብስባ “አሁን አካባቢው እየተረጋጋ ነው፡፡ ክፉ አድራጊዎች ለሰው ባይቻለው ከእግዚአብሔር ፍርድ አያመልጡም፡፡ ለዚህም ነው አካባቢውን የጦር ቀጠና አድርገው፣ የሚገድሉትን ገድለው፣ የሚዘርፉትን ዘርፈው በአይሱዙ መኪና ተጭነው ሲሔዱ ተገልብጦ ለወሬ ነጋሪ እንኳን ሳይተርፉ ጥልቅ ገደል ውስጥ ገብተው አልቀዋል፡፡ እናንተ ልትረጋጉ ይገባል፡፡ አይዟችሁ” በማለት አጽናናችን፡፡

ክፉን በክፉ መቃወም ተገቢ ባይሆንም ለደረሰብን የመንፈስና የአካል ስብራት ባይጠግንልም፣ በሰማዕትነት ያረፉ ቤተሰቦቻችንን በአካል ባይመለሱልንም ክፉ አድራጊዎቹ ሳይውል ሳያድር መቀሰፋቸው አስደሰተን፡፡

በአምስተኛው ቀን ከአርሲ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ ልዑካን አልባሳትና ምግብ ይዘው በመምጣት እስከ አሁን ያልመጡት መላው አርሲ አለመረጋጋት እንደነበር በመግለጽ ቶሎ ባለመድረሳቸው ይቅርታ ጠየቁን፡፡ የወንጌል ትምህርት በመስጠት እያበረታቱን ለሦስት ቀናት አብረውን ቆይተው ተመለሱ፡፡

ለአሥራ አምስት ቀን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከጠጠለልን በኋላ አካባቢው በመረጋጋቱ ወደመጣንበት እንድንመለስ ተደረገ፡፡ ያ ውጣ ውረድ የበዛበት፣ እንግልትና ሞት የበዛበት ሕይወት በእግዚአብሔር ቸርነት አልፏል፡፡ ከደቂቃዎች በኋላ ምን እንደሚፈጠር አናውቅም፣ ዛሬን በተጠንቀቅ፣ ነገን ደግሞ እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ ኑሮአችንን እንደገና “ሀ” ብለን ጀመርን፡፡

ቅዱስ መስቀል

በዲ/ን ዘክርስቶስ ፀጋዬ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሰቅሎበት የነበረው መስቀል ያደርግ የነበረው ተአምራት በመቃወም አይሁድ እንደቀበሩት በአብዛኛዎቹ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ይተረካል፡፡ አይሁድ በሮማውያን ላይ እስከአመጹበት፣ ኢየሩሳሌም ከክርስትና በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ እስከጠፋችበት እስከ ፸ ዓ.ም ድረስ መስቀሉ በክርስቲያኖች እጅ ነበር፡፡ ይህም ቆስጠንጢኖስ ለኢየሩሳሌሙ ኤጲስ ቆጶስ ለአቡነ መቃርዮስ በጻፈው እና እነ አውሳብዮስ መዝግበው ባቆዩት የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ተገልጧል፡፡ ቀጣዮቹ ፫፻ ዓመታት ለክርስቲያኖች የመከራ ጊዜያት ነበሩ፡፡ በእነዚህ ጊዜያት የሮም ቄሣሮች ክርስቲያኖችን የሚያሳድዱባቸው ዓመታት ስለነበሩ መስቀሉን የመፈለግ ጉዳይ በልብ ይታሰብ እንጂ በተግባር ሊሞከር አልተቻለም፡፡

መስቀሉና ንግሥት ዕሌኒ

ጥንታውያን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች መስቀሉን ከጠፋበት (ከተሰወረበት) ያገኘቸው ንግሥት ዕሌኒ መሆኗን ይገልጻሉ፡፡ ድርሳነ መስቀል ዘየካቲት እና ዘመጋቢት እንደተገለጸው እስከ ፫፻፲፰ ዓ.ም ተሰውሮ የነበረው መስቀል ያለበትን ይገልጽላት ዘንድ አስቀድማ እግዚአብሔርን በጸሎት ጠየቀች፡፡ ከዚያም በሮሜ ሀገር የሚኖሩ ሊቃውንትንና ጥበበኞችን ሰብስባ የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበትን መሰቀል ዜና ንገሩኝ አለቻቸው፡፡ ሊቀ ጳጳሱ ቀራንዮ በሚባል ቦታ አዳምና ልጆቹን ለማዳን የክብር ባለቤት ጌታችን እንደ ተሰቀለ፣ በጎልጎታም እንደተቀበረ፣ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሳ፣ በዐርባ ቀንም በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ እንደ ዐረገ ተረከላት፡፡ ንግሥት ዕሌኒም ፈጽሞ ደስ አላት፣ የእግዚአብሔርን ፈቃድ እየጠየቀች ሰባት ዓመት ያህል ቆየች፡፡ ከሰባት ዓመት በኋላም ልጅዋ ቆስጠንጢኖስን በመንግሥቷ ዙፋን አስቀምጣ የክብር ባለቤት የኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል ትፍልግ ዘንድ ከሮም ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች፡፡ በ፫፻፳፭ ዓ.ም አየሩሳሌም ደርሳ አይሁድንም ሰብስባ የክብር ባለቤት የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ያለበትን ንገሩኝ፣ አባቶቻችሁ ወዴት እንደቀበሩት አሳዩኝ አለቻቸው፡፡ እነርሱ ግን እኛ የሆነውን አናውቅም፣ አባቶቻችንም መስቀሉን በምድር ውስጥ አልቀበሩም፣ ነገር ግን ስማቸው ኪራኮስ እና አሚኖስ የሚባሉ ሁለት አረጋውያን በእኛ ዘንድ አሉ፡፡ እነርሱም ስለዚህ ጉዳይ ይነግሩሽ ዘንድ ጠይቂያቸው አሏት፡፡

ንግሥት ዕሌኒ ወደ ቤተልሔም ገብታ “የታላቁ ንጉሥ ሀገሩ ቤተልሔም ሆይ ሰላምታ ይገባሻል” እያለች የመስቀሉን ነገር ይገልጽላት ዘንድ ለሰባት ቀናት እያለቀሰች ወደ እግዚአብሔር በመስገድ ማለደች፤ ጸለየች፡፡  ከዚያም ወደ ዮርዳኖስ፣ ቆሮንቶስ፣ ደብረ ታቦር፣ ቀራንዮ፣ ጌቴ ሴማኒ ሔዳ ሰባት ቀን ጾመች፣ ጸለየች፣ በጎልጎታ ድንኳኖቿን ተክላ ከተመች፡፡ በጾምና በጸሎት ብዙ ዕንባ በማፍሰስ እስከ ዐርባ ቀን ቆየች፡፡

በመጨረሻም በአረጋዊው ኪራኮስ አመላካችነት፣ በዕጣን ጢስ ጠቋሚነት ክቡር መስቀሉን ፈልጎ ለማግኘት ቁፋሮው ከመስከረም ፲፯ እስከ መጋቢት ፲ ቀን ወደ ስድስት ወራት የሚጠጋ ጊዜ ፈጀ፡፡ በመጨረሻም መጋቢት ፲ ቀን መስቀሉ ከተቀበረበት ወጥቷል፡፡ በዚህም መሠረት የኢትዮጰያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ዕለቱን ታከብረዋለች፡፡

ቅዱስ መስቀሉና ኢትዮጵያ

ግማደ መስቀሉን ካገኙትና ከጠበቁት ሀገሮች ኢትየጵያ ሀገራችን አንዷ ናት፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መዛግብት እንደሚገልጹት ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮጵያ ጉዞ የጀመረው በ፲፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ሲሆን፣ በግሸን አምባ የተቀመጠው ደግሞ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመን መንግሥት ነው፡፡

በዐፄ ሰይፈ አርእድ ዘመነ መንግሥት በግብፅ ሡልጣን እና በኢትዮጵያ ንጉሥ መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት አንድ የልኡካን ቡድን ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ነበር፡፡ የልኡካን ቡድኑ መሪ የኢየሩሳሌሙ ፓትርያርክ አባ ዮሐንስ ነበሩ፡፡ ልኡካኑ ወደ ኢትዮጵያ ሲደርሱ የዐፄ ሰይፈ አርእድ ልጅ ዐፄ ዳዊት የኢትዮጵያ ንጉሥ ሆነው ነበር፡፡ ፓትርያርኩ በሁለቱ ሀገሮች መካከል የነበረውን ችግር በውይይትና በስምምነት ፈትተው አስማሟቸው፡፡ ዐፄ ዳዊት በነበራቸው ቀና መንፈስ አቡነ ዮሐንስ የኢየሩሳሌሙ ፓትርያርክ ዕሌኒ ንግሥት አስቆፍራ ካስወጣቸው ከጌታ መስቀል ክፋይ ለበረከት እንዲልኩላቸው ወርቅ፣ አልማዝ ሌላም የከበረ ማዕድን ገጸ በረከት አስጭነው ወደ ኢየሩሳሌም መልእክተኞችን ላኩ፡፡ መልእክተኞቹ ኢየሩሳሌም ደርሰው ገጸ በረከቱን ለፓትርያርኩ ከሰጡ በኋላ ፓትርያርኩ የጌታችንን ግማደ መስቀል የቀኙ ክፋይ ከሌሎች ንዋየ ቅድሳት ጋር ላኩላቸው፡፡

ግማደ መስቀሉ በግብፅ በኩል ወደ ኢትዮጵያ ለማስገባት በግብፅ ሡልጣን እና በንጉሥ ዳዊት መካከል ለኢትዮጰያውያን ተሳላሚዎችና ለነጋዴዎች ጥበቃ ማድረግን ጭምር የሚያካትት ስምምነት አካሔዱ፡፡ ግማደ መስቀሉን የያዙት የዐፄ ዳዊት መልእክተኛችም ያለ ችግር ወደ ኢትዮጵያ ጉዞአቸውን ቀጠሉ፡፡ ነገር ግን ዐፄ ዳዊት መልእክተኞቹን ለመቀበል ሲሔዱ መንገድ ላይ መሞታቸውን የጥቅምት ፱ ቀን ፲፬፻፬ ዓ.ም ታሪካቸው ይናገራል፡፡ ያን ጊዜ ግማደ መስቀሉ በሱዳን ስናር በሚባል ቦታ ነበር፡፡

ግማደ መስቀሉ ኢትዮጵያ የገባው መስከረም ፲ ቀን ሲሆን ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ግሸን አምባ ላይ ያስቀመጡት መስከረም ፳፩ ቀን በወሎ ክፍለ ሀገር ግሸን ደብረ ከርቤ ተራራ ላይ ነው፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የካቲት ፳፻፭ ዓ.ም

ወስብሐት ለእግዚአብሔር