ሱባኤያችን በረከት የሚያሰጥ ይሁን

በእንዳለ ደምስስ

በረከትን በመሻት በፍልሰታ ለማርያም ጾም ሱባኤ ለመያዝ በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስም በታነጸውና በቤተ ክርስቲያናችን ከሚታወቁ ታላላቅ ገዳማት ወደ አንዱ ለመሔድ ዝግጅት ሳደርግ ቆይቻለሁ፡፡ ወደ ንስሓ አባቴ ቀርቤ ንስሓ ገብቼና ቀኖናዬን ተቀብዬ፣ ከመሥሪያ ቤቴ ደግሞ ፈቃድ ቀኑ ሲደርስ በዋዜማው የሚያስፈልጉኝን የጸሎት መጻሕፍት፣ አልባሳት፣ በሶና ጥሬ ሽምብራ በቦርሳዬ ሸክፌ፣ የጸበል መቅጃ አነስተኛ ጀሪካን አንጠልጥዬ ልቤ ወደአሰበውና በየዓመቱ ወደምሔድበት ገዳም በሚኒባስ ተሳፈርኩ፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ገዳም ከአዲስ አበባ በስተደቡብ አቅጣጫ አንድ መቶ ኪ/ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ መኪናው ውስጥ እንደ እኔው ሱባኤ ለመግባት የተጣደፉ ወጣት ሴቶችና ጎረምሶች ተሳፍረዋል፣ ሾፌሩ የበኵረ መዘምራን ኪነ ጥበብን “አባታችን ሆይ” የሚለውን መዝሙር በስሱ ከፍቶ አብሮ እየዘመረ መኪናውን ያከንፈው ጀመር፡፡ እኛም በዝማሬ ተከተልነው፡፡

ገዳሙ በአጸድ ተሸፍኗል፣ በአካባቢው ከገዳማውያንና ሱባኤ ለመግባት ከሚጣደፉ ኦርቶዶክሳውያን በስተቀር በአቅራቢያው መኖሪያ ቤቶች እንኳን አይታዩም፡፡ ከመኪናችን ወረድን ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሔጄ ተሳለምኩ፡፡ ምእመናን ጓዛቸውን ተሸክመው እንደ እኔ በረከት ፍለጋ፣ በጾም በጸሎት ተወስነው ከአምላካቸው ከእግዚአብሔር ለመገናኘት፣ የልቦናቸውን መሻት ይፈጽምላቸው ዘንድ ለመማጸን ያለማቋረጥ ወደ ገዳሙ መጉረፋቸውን ቀጥለዋል፡፡

በበጎ አድራጊ ምእመናን እንደታነጹ የሚታወቁት የወንዶችና የሴቶች የሱባኤ መያዣ በአቶች(አዳራሾች) ከቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር ውጪ በስተ ምሥራቅና በስተ ምዕራብ ሽንጣቸውን አርዝመው ለመስተንግዶ በራቸውን ከፍተዋል፡፡ በበሮቹ መግቢያና መውጫዎች የሚገቡና የሚወጡ ምእመናን ግርግር አካባቢውን የገበያ ውሎ አስመስሎታል፡፡ ሁሉም ይጣደፋል፡፡ ግርግሩን እየታዘብኩ ለሱባኤ ወደ ገዳሙ መምጣቴን ለማሳወቅና ቦታ እንዲሰጠኝ ለመጠየቅ ወደ አስተናጋጆቹ ሔድኩ፡፡ ማንነቴን የሚገልጽ መታወቂያ በማቅረብ አስመዝግቤ ወደተመደብኩበት የወንዶች አዳራሽ አመራሁ፡፡

ገና ከቀኑ ስምንት ሰዓት ቢሆን ነው፡፡ አዳራሹ በመጋረጃ መሐል ለመሐል ተከፍሎ በርካታ ምእመናን እንዲያስተናግድ ተደርጎ ተዘጋጅቷል፡፡ ወለሉ ሙሉ ለሙሉ ምንጣፍ ተነጥፎበታል፣ ቀድመውኝ የመጡ ምእመናን የራሳቸውን ምንጣፍ ከዋናው ከምንጣፍ በላይ ደርበው አንጥፈዋል፡፡ አብዛኛው የአዳራሹ ሥፍራ ተይዟል፡፡ ቦታ ፍለጋ ዓይኖቼን አንከራተትኳቸው፡፡ ቢያንስ አምስት ሰው ሊያስተናግድ የሚችል ቦታ እንዳለ አስተዋልኩ፡፡ የሚመቸኝን ቦታ ከመረጥኩ በኋላ ጓዜን አስቀምጬ ምንጣፍ ዘረጋሁ፡፡

ራሴን ካረጋጋሁ በኋላ አዳራሹን ከላይ እስከ ታች በዐይኖቼ ቃኘሁት፡፡ አብዛኛው በአዳራሹ ቦታ ይዘው ያሉት ወጣቶች ናቸው፡፡ አልፎ አልፎ ግን በጎልማሳነት ዕድሜ ላይ ያሉ፣ በሕመም ምክንያት በአስታማሚ የሚረዱ ሰዎችም አብረውን አሉ፡፡ ከሁሉም ግን ትኩረቴን የሳበው  በስተቀኝ በኩል ግድግዳውን ተደግፈው ከአንድ ሱባኤ ከሚይዝ ሰው የማይጠበቅ ፌዝና ቀልድ ላይ ያተኮረ የወጣቶቹ ድርጊት ነው፡፡ ገና ከዋዜማው እንዲህ ከሆነ ጥቂት ሲቆይ ለጸሎትም እንኳን እንደምንቸገር መገመት አላዳገተኝም፡፡ እኔም አላርፍም እነሱን መከታታል ጀመርኩ፡፡ እየተቀላለዱ ይሳሳቃሉ፡፡

የልጆቹ ሁኔታ ስላላማረኝ ነጠላዬን መስቀልያ ለብሼ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ሔድኩ፡፡ አሁንም የቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር በጸበልተኛና ሱባኤ በሚገቡ ምእመናን ግርግር እንደተሞላ ነው፡፡ ያሰብኩትን ሱባኤ በሰላም አስጀምሮ በሰላም እንዲያስፈጽመኝ ተማጸንኩ፡፡ ጠዋት የጸበል መጠመቂያ ቦታውን በመፈለግ እንዳልደናገር ወደ አንድ ጸበልተኛ ጠጋ ብዬ “ጸበል መጠመቂያው የት ነው?” ብዬ ጠየቅሁት፡፡

በጣቱ ወደ ምሥራቅ አቅጣጫ እያመለከተኝ “በዚህ በኩል ነው፡፡ ቢያንስ አራት ወይም አምስት ደቂቃ ብቻ ቢወስድ ነው” አለኝ፡፡ በደንብ ሲያስተውለኝ እንግዳ መሆኔን በመረዳት “ለመጀመሪያ ጊዜ ነው የመጣኸው?” አለኝ፡፡

“አዎ፡፡” አልኩት፡፡

“ወንድሜ ራስህን በደንብ መጠበቅ አለብህ፡፡ በእግዚአብሔር ወይም በእመቤታችን እንዳታማርር፡፡ የሰው ፍላጎቱ ብዙ ነው፡፡ ለበረከት የሚመጣ እንዳለ ሁሉ ለስርቆትና ለክፉ ነገር የሚመጣም አለ፡፡ ጸበል ስትጠመቅ ያወለቅኸውን ልብስ ይዞብህ፣ ወይም ለብሶብህ የሚሔድም አይጠፋም፡፡ ንብረትህን በደንብ መጠበቅ አለብህ፡፡ እንዲህ ስልህ ለነፍሳቸው ያደሩ፣ ራሳቸውን ለእግዚአብሔር ያስገዙና ስለሌሎች የሚኖሩ የሉም እያልኩህ አይደለም፡፡ ሥፍራው ታላላቅ ተአምራት የሚከናወንበት የጽድቅ ሥፍራ ነው፡፡ ጠንክሮ መጸለይ ነው” አለኝ በትሕትና፡፡

“እሺ ወንድሜ፡፡ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡ የመጣሁት ከእመቤታችን በረከት ለማግኘት ነው፤ ለዚህም እግዚአብሔር ይረዳኛል” በማለት አመስግኜ ተሰናበትኩት፡፡

“ብዙ ኃጢአት ባለችበት የእግዚአብሔር ጸጋ ትበዛለች” የሚለው የቅዱስ ኤፍሬም የሰኞ ውዳሴ ማርያም ጸሎት ትዝ ብሎኝ እየተገረምኩ አንድ ጥግ ድንጋይ ላይ ተቀመጥኩ፡፡

የሰርክ መርሐ ግብር በጸሎትተጀምሮ የወንጌል ትምህርት እንዲሁም ምሕላ ተደረገ፡፡ ሱባኤው ተጀምሮ እስኪያልቅ ድረስ ምእመናን ሥነ ምግባር በተሞላበት ሁኔታ የመጡበትን ዓላማ አሳክተው እንዲመለሱ፣ የበረከቱ ተሳታፊም እንዲሆኑ በመምህራን ማሳሰቢያ ተሰጠ፡፡

የሰዓታት ጸሎት እስኪጀመር ድረስ ሁሉም ወደየበአቱ በማምራት በሶውን በጥብጦ፣ ቆሎውን፣ ሽምብራውን ቆርጥሞ የበረታ በጸሎት ሲጠመድ ሌላው ዕረፍት አደረገ፡፡ አንዳንዶች ከአሁኑ አርምሞ ጀምረዋል፡፡ አዳራሹ ውስጥ በቡድን ሆነው የመጡት ጓደኛማቾች ድምጻቸውን ይቀንሱ እንጂ መቀላለዳቸውን አላቋረጡም፡፡ በጸሎት ለተጠመደ ኅሊናን ይሰርቃሉ፡፡

ከሌሊቱ ዐራት ሰዓት ሲሆን የቤተ ክርስቲያኑ ደወል ተደወለ፡፡ አንዱ አንዱን እየቀሰቀሰ ተያይዘን ወደ ቤተ መቅደሱ አመራን፡፡ ካህናት አባቶች ሰዓታት ቆመዋል፡፡

ቤተ መቅደሱ የቻለውን ያህል ምእመናንን አስተናግዶ ሌላው ውጪ ሆኖ ብርዱን ተቋቁሞ ይጸልያል፡፡ ሰዓታት እንደ ተጠናቀቀ ንጋት ላይ ሊቀውንቱ የኪዳን ጸሎት፣ ስብሐተ ነግህ ቀጠሉ፡፡ ጨለማው ለብርሃን ሥፍራውን ሲለቅ ውዳሴ ማርያምና ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜ እንደ ቅደም ተከተላቸው ቀርበው የቅዳሴ ሰዓት እስኪደርስ ጸበል ለመጠመቅ እሽቅድድም በሚመስል ፍጥነት ተሯሯጥን፡፡

ጸበል መያዣ ባለ አምስት ሊትር ጀሪካን ይዤ ወደ ጸበሉ ስፍራ ሰዎችን ተከትዬ ሔድኩ፡፡ ግርግሩ ዕረፍት ይነሣል፡፡ እንደማንኛውም ሰው ወረፋ ያዝኩ ነገር ግን በጉልበታቸው የተመኩ ወጣቶች እየተጋፉ፣ የዕድሜ ባለጠጋ የሆኑትን አረጋውያንን እየገፉ ተጠምቀው ለመውጣት ይጣደፋሉ፡፡ ሰልፉ ተረበሸ፡፡ ችግሩ ከሚያስተናግዱ ወንድሞች በላይ ሆነ፡፡ በሴቶችም በኩል መጠነኛ ግርግሩ ቀጥሏል፡፡ በዚህ መካከል የሚወድቅ፣ ንብረቱ የሚዘረፍ ቁጥሩ በርካታ ነው፡፡ የምእመናን ቁጥር ከፍተኛ ቢሆንም እስከ ስድስት ሰዓት ሳይጠመቅ የተመለሰ አልነበረም፡፡

ከቅዳሴ በኋላ ዕረፍት የሚያደርጉ እንዳሉ ሁሉ ተፈትተው የተለቀቁ ይመስል ከበአታቸው እየወጡ በቡድን፣ በቡድን እየሆኑ በየጫካው ለፌዝና ለቀልድ ጊዜያቸውን የሰጡ ምእመናንም አሉ፡፡ ነገር ግን የመጡት ለሱባኤ ነው፡፡

እንዲህ እንዲህ እያልን ነሐሴ ፲፮ ቀን ድረስ ቆየን፡፡ የእመቤታችን ትንሣኤ ተበሠረ፡፡ ከቅዳሴ በኋላ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን “የእመቤታችንን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ ያክብሩት” ብላ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት እንደ ሠራች በስፋት አስተማሩ፡፡ የሱባኤውንም መጠናቀቅ አወጁ፡፡

ቤተ ክርስቲያኗ ከጥሉላት ምግቦች ተከልክሎ የቆየውን ምእመን የጾም መፍቻ ብላ ያዘጋጀችው ማዕድ በየአዳራሹና በድንኳኑ ታደለ፡፡ እኔ ካለሁበት አዳራሽ ውስጥ ካሉት ምእመናን መካከል “አንበላም እስከ ነሐሴ ፳፩ ቀን ጾማችንን እንቀጥላለን” በማለት የመለሱት ይበዛሉ፡፡ ግራ ተጋባሁ፡፡ የቀረበላቸውን ተቃምሰው ጓዛችውን ሸክፈው ወደወጡበት ቤታቸው ለመመለስ የሚጣደፉ ምእመናንም ቁጥር ብዙ ነው፡፡ እኔ ግን አንድ ቀን ዕረፍት አድርጌ በማግሥቱ ለመሔድ ስለወሰንኩ የቀረበልኝን ማዕድ በላሁ፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በመጣሱ ቅር ተሰኘሁ፡፡ ቤተ ክርስቲያን “የእመቤታችንን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ አክብሩ” እያለች ይህንን ተላልፈው የእመቤታችን ትንሣኤ በሚከበርበት ወቅት እጾማለሁ ማለት ምን ማለት እንደሆነ አልገባኝም፡፡ “ቤተ ክርስቲያን ሁለት ዓይነት ሥርዓት አላት እንዴ?” እያልኩ ከራሴ ጋር ሙግት ገጠምኩ፡፡ አንድ ነገር ወሰንኩ፡፡ አባቶችን ማማከር፡፡

ጥቂት ዕረፍት አድርጌ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ቅጥር በመግባት አባቶችን ፈለግሁ፡፡ ውዳሴ ማርያምና ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜን ላለፉት ቀናት በጣፋጭ አንደበታቸው ሲተረጉሙ የነበሩት አባት ከቤተ መቅደስ ሲወጡ አገኘኋቸው፡፡ ቀረብ ብዬ ሰላምታ ከሰጠኋቸው በኋላ ጥያቄዬን አቀረብኩ፡፡

በትኩረት እየቃኙኝ “ልጄ ቤተ ክርስቲያን የሠራችው ሥርዓት ማፋለስ ኃጢአት ነው፡፡ እውነት ነው ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችን ትንሣኤ እንደ ልጇ ትንሣኤ ያክብሩት ብላ ሥርዓት ሠርታለች፡፡ ነገር ግን ምእመናን ሲጥሱት እንመለከታለን፡፡ ከዚህ በፊትም በስፋት አስተምረናል፡፡ “የበለጠ በረከት ለማግኘት ነው” እያሉ የሚጾሙ ምእመናን ቁጥር በርካታ ነው፡፡ ይህ ትክክል አይደለም፡፡ አንዳንድ ምእመናን ቢነገራቸውም አይሰሙም፡፡ ግዝት አይደለም መጾም እንችላለን ይሉሃል፡፡ አንዳንድ አባቶችንም ስታነጋግር ምን ችግር አለው ይሉሃል፡፡ ይህ ትክክል አይደለም” አሉኝ ጥያቄው የእኔ ብቻ ሳይሆን የእሳቸውም ጥያቄ እንደሆነ በሚገልጽ ምላሽ፡፡

“ታዲያ ሥርዓት የሚሽሩትን ከገዳሙ ለምን አታስወጡም” አልኳቸው፡፡

ለጥቂት ሰከንዶች በመገረም እያዩኝ፡፡ “ልጄ እኔ የዚህ ሥልጣን የለኝም፡፡ በተቻለኝ አቅም ልጆቼን በሔዱበት ሁሉ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት እንዳይጥሱ አስተምራቸዋለሁ፡፡ ካለ እኔ ፈቃድም አያደርጉትም፡፡ አሁን አንተ የምትለኝን ገዳሙ የራሱ አስተዳደር አለውና እነሱን ጠይቅ” ብለው መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡ አስተዳደሩን ለማግኘት ያደረግሁት ጥረት ሳይሳከ ቀረ፡፡

ሁላችንም ምክንያት የምናደርገው ሌሎችን ነው፡፡ ለምን ብለን ግን አንጠይቅም፡፡ ፈቃጁ ማነው? ማን እንደሆነ አይታወቅም፡፡ አንዱ ወደ አንዱ ያሻግርሃል፡፡ በጣም ተበሳጨሁ፡፡ ወደ አዳራሹ ተመለስኩ፡፡ ብዙ ሰዎች ሱባኤያቸውን ቀጥለዋል፡፡ በመብላቴ እኔን እንደ ደካማና ኃጢአተኛ አድረገው የቆጠሩኝ መሰለኝ፡፡ ሕሊናዬ አላርፍ አለኝ፡፡

አዳራሹ ውስጥ ካሉት መካከል ለረጅም ሰዓት ቆሞ በመጸለይና በመስገድ መንፈሳዊ ቅናት ወደ ቀናሁበት ወንድም ጠጋ ብዬ ጥያቄዬን አቀረብኩለት፡፡ “ጾሙ አልተጠናቀቀም ወይ?” ነበር ጥያቄዬ፡፡

“በረከት ለማግኘት ስል እስከ እመቤታችን ዕረፍት መታሰቢያ ቀን ድረስ እቆያለሁ፡፡” አለኝ፡፡

“ለምን? ሥርዓት መጣስ አይሆንብህም?” አልኩት፡፡

“መብቴ እኮ ነው፡፡ ከመብላት አለመብላት ይሻላል፡፡” አለኝ፡፡

“እንዴት እንዴት አድርገህ ነው የምትተረጉመው? ቤተ ክርስቲያን የእመቤታችንን ትንሣኤ ከነሐሴ ፲፮-፳፩ ቀን እንደ በዓለ ሃምሳ ያክብሩት በማለት መደንገጓን ምነው ዘነጋህ? ለመሆኑ ሱባኤው እስከ ነሐሴ ፳፩ ቀን መቆየት የተጀመረው መቼ ነው?” አልኩት፡፡

“በቅርብ ይመስለኛል፡፡ ግን ምን ችግር አለው? ቀኖና ነው፡፡ ቀኖና ደግሞ ይሻራል፣ ይስተካከላል፡፡ አባታችን ይህንን ሲናገሩ ሰምቻለሁ” አለ በድፍረት፡፡

“ማናቸው አባትህ?” አልኩት ዐይን ዐይኑን እየተመለከትኩ፡፡

“ባሕታዊ እከሌ ናቸዋ” አለኝ፡፡

በጣም አዘንኩ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ተዘንግቶ፣ ቀድሞ አባቶች የሠሩትን ሥርዓት በባህታዊ ነኝ ባዮች ሲሻር ያሳዝናል፡፡

“ለመሆኑ ማነው የሚሽረውና፣ የሚያስተካክለው?” አልኩት እልህ እየተናነቀኝ፡፡

“ቤተ ክርስቲያን ናታ፡፡”

“የቤተ ክርስቲያን መብት ከሆነ አንድ ባሕታዊ ይህንን የመሻር ምን ሥልጣን አለው? ለምእመኖችዋ ውሳኔውን ማሳወቅ ያለባት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ እሷ ደግሞ አባቶች የሠሩትን ሥርዓት የምታጸና እንጂ የምታፈርስ አደለችም” አልኩት በንዴት፡፡

“አንተ እንደፈለግህ፡፡ እኔ ግን የባሕታዊ አባቴን ድምጽ እሰማለሁ፡፡ በቃ አትጨቅጭቀኝ!” በማለት ፊቱን አዞረብኝ፡፡

ለመሆኑ የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ሲጣስ አደብ የሚያስገዛው ማነው? ለማንስ አቤት እንበል? ሱባኤያችን በረከት የሚያሰጥ ይሆን ዘንድ ምን እናድርግ? ሱባኤ ሔጄ ይህንን ታዘብኩ፡፡ እናንተስ ምን ትላላችሁ?

“በዐዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለች” (ሲራ.፲፮፥፬)

የአንድ ሀገር ቋሚ ሀብቶቿ ልጆችዋ ናቸው፡፡ ሕዝብ ሀገር ወዳድና ጠንካራ ሲሆን አነዋወሩን ከመቀየር ጀምሮ የሀገሩን ታሪክ በወርቃማ ቀለም መጻፍ ይችላል፡፡ እንዲህ ያለው ተስፋ ብዙውን ጊዜ በአዳጊ ሀገሮች ለወጣቶች ይሰጣል፡፡ ይህ የሚሆነው በብዙ ሀገሮች ውስጥ ከፍተኛውን የነዋሪ ቁጥር ከሚይዙት ውስጥ ሕፃናትና ወጣቶች በመሆናቸው እና በአባቶች ፈንታ አገር የሚረከቡም ጭምር በመሆናቸው ነው፡፡

በሀገራችን ኢትዮጵያም ይህን ከፍተኛ ቁጥር የያዙት ሕፃናትና ወጣቶች ናቸው፡፡ እንደ ሌሎች አዳጊ ሀገራት ሁሉ የሀገሩቱ አስከፊ ገጽታ በመቀየሩ ረገድ ሰፊ ሚና ያላቸው እነዚህ ወጣቶች ናቸው፡፡

ቤተ ክርስቲያንም ሀገር ወዳድ፣ ታሪክ ሠሪና ታታሪ ትውልድ የማፍራት ሥራዋን ስትሠራ ኖራለች፡፡ የሀገራችንን ሕዝብ ከፊደል ቆጠራ እስከ ሥርዓተ መንግሥት ቀረጻ አስተምራና የሀገሪቱን ታሪክ በሕዝቡ ቋንቋና ፊደል ጽፋ ያቆየች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ በዚህ ትውልድም ውስጥ የለውጥ አርአያ የሚሆን ዜጋ ለመፍጠር በሚደረገው ጥረት ውስጥ የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ትገኛለች፡፡

ትውልድ መፍትሔ ፈላጊ ሊሆን የሚችለው አዋቂ የሆነ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ የዕውቀት ብርሃን የያዘ ትውልድ የድህነትና የበሽታ፣ የጦርነትና የርኃብ ጨለማ አያሰጋውም፡፡ የዕውቀት ብርሃን የችግር መፍቻ ቁልፍ ነውና፡፡ ቤተ ክርስቲያን ከማይነጥፍ ማሕፀኗ ልትወልደውና ልታሳድገው የምትሻው እንዲህ ያለውን ነው፡፡ ለዚህ ነው ጠቢቡ “ከሺህ ልጆች አንድ አዋቂ ልጅ ይሻላል፤ ክፉ ልጅም ከመውለድ ሳይወልዱ መሞት ይሻላል፤ አዋቂ በሆነ በአንድ ልጅ ሀገር ትጸናለችና” በማለት የገለጸው፡፡ (ሲራ.፲፮፥፬)፡፡

ሰው ሁሉ በሙያ ዘርፉ ተሰማርቶ እየሠራ ያለው ዕውቀት ቢኖረው ነው፡፡ ታዲያ ለምን ውጤታማ መሆን አልተቻለም? ብዙ መንፈሳውያን የሆኑና በዕውቀት የበሰሉ ባሉባት ኢትዮጵያ ለምን ሥጋዊ ችግሮች ሰለጠኑ? የሚሉ በርካታ ተመሳሳይ ጥያቄዎች በማኅበረሰባችን ዘንድ የመወያያ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ዕውቀቱም፣ ጉልበቱም፣ ገንዘቡም፣ ጊዜውም ተደምረው ለምን ለውጥ አላመጣም? የለውጡ መሠረት ምንድው? የቅዱሳት መጻሕፍት መጻፍ ቀዳሚ ዓላማ የለውጥን መንገድ መጠቆም ነውና ጠቢቡ በቅዱስ መጽሐፍ የሰጠንን ምክር እንመርምር፡፡ “በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለች” ብሎናልና፡፡

ዕውቀት ማለት በአንድ ዘርፍ ያለን ክህሎት አይደለም፡፡ ሁለቱን ዓይነት የዕውቀት ዘርፎች ይዞ መገኘት እንጂ፡፡ ዕውቀት ሁለት ዓይነት ነው፡፡ ዕውቀት ሥጋዊና ዕውቀት መንፈሳዊ፡፡ አዋቂነትም ሁለቱንም ዓይነት አጣምሮ መያዝ ነው፡፡ በአንድ ጎን ወይም ዘርፍ ማደግ ብቻውን የሰው ልጆችን ፍሬያማ አያደርግም፡፡ ለሀገር ለወገን ለቤተሰብና ለራስ መሆን የሚችል ዜጋ ለማፍራት በትክክል “በሁለት ወገን የተሣለ ሰይፍ” መሆን ያስፈልጋል፡፡ ይህ ነው በዕውቀት ሥጋዊ፣ በዕውቀት መንፈሳዊ፣ መታነጽ ማለት፡፡

ዕውቀት ሥጋዊ ከቤተሰብና ከአካባቢያዊ ሁኔታዎች ጀምረን በየደረጃው በትምህርት ማእከላትና በልዩ ልዩ መንገዶች የምናገኘው የተግባርና የቀለም ትምህርት ነው፡፡ ይህ ዕውቀት በተለይም በምድራዊ ኑሮአችን የሚኖረንን የግልና የማኅበር ሕይወት መልካም ለማድረግ ካለው ፋይዳ ባሻገር ለማኅበረሰባችንና ለሀገራችን ያለንን የምናካፍልበት የምድራዊ ኑሮ ክፍል ነው፡፡

ዕውቀት መንፈሳዊ የሰው ልጅ ከምድራዊ ኑሮው በኋላ ያለውን ሰማያዊ አነዋወር /አኗኗር/ የሚዋጅበት ዕውቀት ነው፡፡ ሁለቱም የዕውቀት ዓይነቶች ተፈላጊ ናቸው፡፡ ሰው የሁለት ነገር ውሕድ ፍጥረት ነው፡፡ የሥጋና የነፍስ፡፡ ሁለቱን ባሕርያት ማጣጣም ማዋደድና ማስታረቅ የመንፈሳውያን ሰዎች ዕውቀት መመዘኛ ነው፡፡ የሰው ልጅም ይህን ይይዝ ዘንድ ግድ ይለዋል፡፡

“ያልተገራ ፈረስ ገራገር ይሆናል፣ ያልተማረ ልጅም አውታታ ሆኖ ያድጋል፡፡ /ሲራ.፴፥፰/፡፡ ፈረስን መግራት ካልቻሉ ወይም አሥረው መያዝ ካልቻሉ አደጋ እንደሚያስከትል ሁሉ ከዕውቀት ሥጋዊ እና ከዕውቀት መንፈሳዊ ያልተማረ ልጅም አውታታ፣ ባተሌ፣ ባካና፣ ቀማኛ፣ ሥራ ፈት እየሆነ ያስቸግራል፡፡ ይህ ሁሉ የጨለማ ሥራ የሚሠራው ከዕውቀት ብርሃን የራቀ በመሆኑ ነው፡፡ ዕውቀት የሰው ልጅ ብርሃን ናትና፡፡

የሀገርን ሀብት የሚበዘብዝና የሚሠርቅ፣ ጉቦ የሚቀበል ዜጋ ምንም እንኳን በወረቀት ያስደገፋቸው የዕውቀቱ ማስረጃዎች /የምሥክር ወረቀቶች/ በዝተው የሥልጣንን እርከን እንዲቆናጠጥ ቢያስችሉትም ገና የዕውቀት ብርሃን ያልበራለት የእናት ጡት ነካሽ ነው፡፡ በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለች እንጂ አትፈርስም፣ ትለመልማለች እንጂ አትመዘበርም፡፡

አዋቂ የሆኑ የኢትዮጵያ ልጆች ሀገራቸው ከሰሜን ጫፍ እስከ ደቡብ፣ ከምዕራብ እስከ ምሥራቅ ያላትን የቀደመ ታሪክ የሚያውቁ፣ ኢትዮጵያንና የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ያላቸውን የታሪክ አንድነት ነጥለው የማያዩና በዚህም የሚኮሩ ናቸው፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ የኢትዮጵያ ታሪክ የሚሆነው በሰዎች ስምምነት አይደለም፤ በሺዎች ለሚቆጠሩ ዘመናት አብረው የተሻገሯቸው ዘመናት እንጂ፡፡ ለዚህም የኢትዮጵያ ታሪክ እውነተኛ ምንጮች የቤተ ክርስቲያናችን መዛግብት መሆናቸው ብቻውን ምሥክር ነው፡፡ ትውልዱን አዋቂ የሚያሰኘውም ዕድሜ ብቻ ሳይሆን እውነትንም ጭምር ከጠገቡት መዛግብት እውነቱን መረዳት ማወቅና ማሳወቅ ሲችል ነው፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ለኢትዮጵያ ሀገራችን ያበረከተቻቸውን አስተዋጽኦዎች ዘርዝሮ መጨረስ አይቻልም፡፡ በጥቅሉ ያየናቸው እንደሆነ ግን በርካታ ሥነ ጥበባት፣ ማኅበራዊ አንድነትን /በሕዝቦች ዘንድ ተዋሕዶና ተፋቅሮ የመኖር ባሕል/ ወዘተ… ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ይህ ሁሉ በአዋቂ ልጆቿ ትጋት የተገኘ ነው፡፡

በልዩ ልዩ ደረጃዎች የሚገኙ ኢትዮጵያውያንና የኢትዮጵያ ወዳጆች የሀገሪቱን ማንነት በግልጽ የተረዱ ሊሆኑ ይገባል፡፡ በዚህ ዕውቀት ላይ ተመሥርተው የሚሠሩት የአገር ግንባታ ሥራ ውጤታማ ብቻ ሳይሆን አኩሪ ታሪክም ይሆናልና፡፣ ኢትዮጵያ በአፍሪካ ቀንድ አካባቢ የምትገኝ ሀገር ብቻ አይደለችም፡፡ በሕዝቦቿ ዘንድ አኩሪ ታሪክ ያላት የነጻነት ምልክት፣ በቅዱሳት መጻሕፍት ውስጥ ተደጋግሞ ስሟ በበጎ የተጠቀሰ መንፈሳዊት ሀገርና የክርስትና ደሴትም ጭምር ናት፡፡ /መዝ.፷፯፥፴፩፤አሞ.፱፥፯/ አዋቂ ልጅ በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ ኢትዮጵያን የሚያውቃት ነው፡፡ ማንነቱን በትክክል መረዳት ያልቻለን ሰው እንዴት አዋቂ ልንለው እንችላለን?

በሁለት ወገን የተሳሉ ሰዎች ልበ ብርሃን በመሆናቸው አስተዋይነት ገንዘባቸው ነው፡፡ “አስተዋይነት ያልታከለበት ዕውቀት ለውድቀት” እንደሚባለው ከመውደቅ በፊት አስተዋይነትን ገንዘብ ልናደርግ ይገባል፡፡ አስተዋይነት አዋቂ ነን ከሚሉ ሰዎች መካከል በሁለት ወገን የተሳሉ ሰዎችን ለይታ የምታሳይ የመንፈሳውያን ሰዎች መለያ ናት፡፡

የባቢሎን ንጉሥ ናቡከደነጾር በከፈተው ት/ቤት እንዲማሩ የተመረጡ ተማሪዎች ከመስፈርቶቹ መካከል ብልሃተኝነት አንዱ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ተመርጠው ወደ ትምህርት ማእከሉ ከገቡ በርካታ ተማሪዎች መካከል በአስተዋይነት ተለይተው የወጡት በዕውቀትና በመንፈሳዊ ትጋት የበሰሉት ሠለስቱ ደቂቅ ነበሩ፡፡ /ዳን.፩፥፬/ የሦስቱ ሕፃናት በስደት አገር እየኖሩ ለሕዝባቸውና ለሀገራቸው ታሪክ መሥራት፣ ሕዝባቸውን መጽናትና በስደት አገር ሀራቸውን በበጎ ማስጠራት የቻሉት በአስተዋይነት ነው፡፡

የአስተዋዮች ጸሎት ሁልጊዜ በማስተዋል ይመላለሱ ዘንድ ነው፡፡ ዕውቀትና ጥበብን፣ ገንዘብንና ጉልበትን አስማምቶ ውጤት ማምጣት የሚቻለው በማስተዋል ነውና፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞን ወደ አባቱ የንግሥና ዙፋን ሲመጣ በጸሎቱ አስተዋይነት ገንዘብ እንዲያደረግ መለመኑ ለዚህ ነው፡፡ /፩ነገ.፫፥፱/፡፡ “በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለችና፡፡”

በጠቢቡ ሰሎሞን ዘመን አንድ እስራኤል ነበር፡፡ ጠቢቡ አዋቂ ልጅ ነበርና ለመጀመሪያ ጊዜ ለእግዚአብሔር ታቦት ማደሪያ ቤት /ቤተ መቅደስ/ አነጸ፡፡

አስተዋይነት ያለንን ዕውቀት በአግባቡ መጠቀም መቻል ነው፡፡ በየደረጃው የተማርናቸውን ትምህርቶች በአግባቡ በሥራ መተርጎም ከቻልን አስተዋይነታችን በውጤታማነታን ይገለጻል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ልጅነታችንን በቅዱሳን አሠረ ፍኖት የምንጓዝ መሆናችንን ለሕግጋተ እግዚአብሔር የምናረጋግጠው በምግባራችን ነው፡፡ ይህ ነው አዋቂ የሚያሰኝ ተግባር፡፡

ታማኝነት ሌላኛው የአዋቂዎች መገለጫ ነው፡፡ ሀገርን ለማጽናት የሕዝብን ኑሮ ለማሳደግ በሚደረገው ጥረት ውስጥ ታማኞችን ማግኘት ካልተቻለ ከንቱ ድካም እየተደከመ ነው፡፡ በቤተሰቡ መካከል ጠብን የሚዘራ ሰው ለሀገር ሰላም ያመጣል ማለት እንዴት ይቻላል? የእናቱን መሀረብ የሚፈታ፣ የአባቱን ኪስ የሚያወልቅ ልጅ ነገ በሚሠማራበት የሥራ መስክ በታማኝነት ያገለግላል ማለት ያስቸግራል፡፡ አዋቂነት ታማኝነት ነው፣ ሀገርን ማጽናትም ከታማኝነት ይጀምራል፡፡

የልጆችን ሰብእና እንዴት ወደዚህ ደረጃ እናምጣ? በልጅነት ዕድሜው ወላጆቹ የሚያወጡለት የትምህርት ቤት ክፍያ፣ ስለሚለብሰው ልብስና ስለ ሌሎች ተመሣሣይ ወጪዎቹ ኃላፊነት የማይሰማውና ግድየለሽ አድርጎ ልጆችን መቅረጽም በነገ ሕይወታቸው ንዝህላልና በአሠራር ዝርክርክነት የሚታወቁ ያደርጋቸዋል፡፡ ስለዚህ የታማኝነትና የኃላፊነት መልካም ሥነ ምግባራትን በልጆች ሥነ ልቡና ውስጥ ከልጅነት ዕድሜ ጀምሮ ማስረጽ አለብን፡፡ በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለችና፡፡ ወላጆች በእግዚአብሔር ፈቃድ ልጆችን ወደዚህ ምድር እንዳመጡ ሁሉ ለልጆቻቸው ሕይወት ስኬታማነት ሊጠበቡ ያስፈልጋል፡፡ አልሚም አጥፊም ትውልድን  ይፈጥራሉና፣ አዋቂም አጥፊም ልጅ ያስገኛሉና፡፡

ሀገርን የሚጠብቅ፣ የሚገነባና የሚያጸና ትውልድ መቅረጽ ካልተቻለ የሚያፈርስ፣ የሚሸጥና የግል ጥቅሙን የሚያስቀድም ዘር/ትውልድ/ ያስቀራሉና ታማኝነትን፣ ሀገር ወዳድነትንና የእምነት ጽናትን ከልጅነት ዕድሜ ጀምሮ ልጆችን ማስተማር አለብን፡፡

የልጆች በቅዱሳት መጻሕፍት ምክር፣ በወላጆች ተግሣጽ ማደግ የሚያስገኘው ጥቅም ብዙ ነው፡፡ ጠቢቡ “እናንት ልጆች የአባትን ተግሣጽ ስሙ፣ ማስተዋልንም ታውቁ ዘንድ አድምጡ” /ምሳ.፩፥፬/ በማለት ልጆች የወላጆቻቸውን ምክር ያደምጡ ዘንድ ይመክራል፡፡ ልጆችን በምክር በማሳደግ አስቀድሞ ወላጆች ታላቁን አደራ ተወጥተዋል ማለት ነው፡፡ ልጆች ከእግዚአብሔር እጅ የተቀበልናቸው የከበሩ ሥጦታዎች ናቸው፡፡ በመሆኑም ልጆችን መንከባከብና በሥነ ምግባር ማሳደግ የእግዚአብሔርን ሥጦታ መጠበቅ ነው፡፡ /መዝ.፩፻፮፥፫/፡፡ ከወላጆችም በላይ ግን ልጆች የታማኝነት፣ የትሕትናና የዐዋቂነት ሥነ ልቡና እያዳበሩ የሚያድጉ ከሆነ ተወዳጅና ተመራጭ ያደርጋቸዋል፡፡ በዚህም አብዝቶ ተጠቃሚዎች ልጆች ይሆናሉ፡፡ የልጆች ጥቅም የወላጆችም ጥቅም ነው፡፡ የልጆች መልካምነት ለወላጆች ኩራት ነው፡፡ ለልጆችም አስፈላጊና ጠቃሚ ነው፣ በወላጆች ዘንድ ተወዳጅ ያደርጋልና፡፡ /ምሳ.፬፥፫/፡፡ በዚህ ብቻ አይበቃም በሥነ ምግባር በሃይማኖት ተኮትኩተው በሚያድጉ ልጆች ቤተ ክርስቲያንም ሀገርም ተጠቃሚዎች ናቸው፡፡ “በአዋቂ ልጅ ሀገር ትጸናለች” እንደተባለ፡፡

በአጠቃላይ ሀገራችንም ቤተ ክርስቲያናችንም በርካታ “አዋቂዎች” የሚሹበት ዘመን ቢኖር ዛሬ ነው፡፡ አስተዋዮች ብቻ ሳይሆኑ በመንፈስ ቅዱስ ፀጋ የሚሠሩ የሃይማኖት ልጆችን በዕቅድና በሥርዓት ማሳደግ አለብን፡፡ ካለፈው ተምረው መጻኢውን የሚተነብዩ ለፈቃዳቸው፣ ለሐሳባቸውም እግዚአብሔርን በማስቀደም የሚሠሩ ልጆችን ማዘጋጀት የሚጀምረው ደግሞ በልጅነት ዕድሜአቸው ነው፡፡ እነዚህ ናቸው ሀገርን የሚያጸኑ፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚጠብቁ፡፡

ቤተ ክርስቲያን የምትፈልገው አዋቂ ልጅ መስቀሏን በገንዘብ የማይለውጠውን፣ ቅርሶቿን የማይሸጠውን፣ ሃይማኖቷን የማይክደውን ነው፡፡ በከፋ ፈተና ውስጥ እያለፈ እንኳን “የማመልከው አምላክ ያድነኛል፣ ባያድነኝ እንኳ እንዲህ ያለውን አላደርግም” የሚለውን ነው፡፡ /ዳን.፫፥፲፯/፡፡

ሀገራችን ብዙ ጠበብት፣ ብዙ አዋቂዎችን ትሻለች፡፡ ፊደል የቆጠሩ፣ እንግሊዝኛ የሚናገሩ ብቻ ሳይሆን ወደተሻለ የዕድገት ደረጃ የሚያሸጋግሯትን ቅን ልቡና ያላቸውን አዋቂዎች ትሻለች፡፡ ሀገራችን የታሪኳ መበረዝ፣ የዕድገቷ ኋላ ቀርነት፣ የድህነቷ መብዛት፣ የሕፃናቷ ሞት፣ የሥነ ምግባር ውድቀት፣ የጠላቶቿ መብዛት፣…. የሚያስቆጫቸው፣ የሚያቃጥላቸውና ለለውጥ የሚሠሩ አዋቂ ልጆች ያስፈልጓታል፡፡

“ሮም በአንድ ቀን አልተገነባችም” እንደሚባለው የኢትዮጰያን ዕድገት በአንድ ጀምበር አናመጣውም፡፡ ይልቁንም አዋቂ ልጅ መርሐ ግብር ነድፎ የድርሻውን ጠጠር ይወረውራል፡፡ ያኔ ኢትዮጵያን እንደ ጥንቱ ሁሉ ከታላላቅ ሀገሮች ተርታ የምናይበት ዘመን ይመጣል፡፡

አዋቂዎችን አያሳጣን፡፡ አሜን፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ጥር፲፭-፴፣ ፳፻፩ ዓ.ም

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!

በሀገር ውስጥና በውጭ የምትገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ምእመናት፣ እንዲሁም ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት በሙሉ!

የይቅርታ ባለቤት የሆነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ በሰላም አደረሳችሁ!!

“ወሣህሉኒ ለትውልደ ትውልድ ለእለ ይፈርሕዎ፣ ይቅርታው ለሚፈሩት ለልጅ ልጅ ነው” (ሉቃ.፩፥፶)፡፡

ይህ ኃይለ ቃል የቅዱስ መጽሐፍ ቀዋሚ ምሰሶ ሆኖ በብዙ ቦታ የሚገኝ ነው፣ ቃሉ እግዚአብሔር ለሚፈሩት የሚያጎናጽፋቸውን የምሕረት ቃል ኪዳን በውስጡ ይዞአል፤ ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የሆነችው ቅድስት ድንግል ማርያምም እግዚአብሔርን ባመሰገነችብት የምስጋና መዝሙር ይህንን ኃይለ ቃል ተናግራዋለች፡፡

በዚህ ኃይለ ቃል የእግዚአብሔር ይቅርታ ምን ጊዜም የከበረና እንደ ተስፋ ቃሉ የሚፈጸም መሆኑ፣ ያም ሊሆን የሚችለው ለሚፈሩት ሰዎች መሆኑ በሚገባ ተገልጿል፡፡ የእግዚአብሔር ይቅርታ አጭርና ቀጭን ሳይሆን ለልጅ ልጅ እንደሚሆንም ተብራርቷል፡፡

ይህ አባባል እውነት እንደሆነ ለመረዳት ከእኛ ከሰዎች የበለጠ ሌላ ምስክር ሊኖር አይችልም፡፡ ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “ሣህሉ ለእግዚአብሔር መልአ ምድረ፣ የእግዚአብሔር ይቅርታ ምድርን መላ” ብሎ እንዳስተማረን ይቅርታው በየጊዜው በዝቶ ባይደረግልን ኖሮ ውሎ ማደሩ የሚቻል አልነበረም፡፡ እግዚአብሔር በነገር ሁሉ ኃጢአትን፣ ክፋትን፣ ርኵሰትንና ክህደትን የሚጠላ አምላክ ነው፡፡ እኛ ደግሞ ከእነኚህ ክስተቶች ለአንድ ደቂቃ ስንኳ ጸድተን አናውቅም፣ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር በቅጣት ፈንታ ምሕረትንና ይቅርታውን እያበዛልን በምሕረቱ ተጠልለን እንኖራለን፡፡ ቅድስት ድንግል ማርያምን በመውደድ፣ አስተብቍዖቷን፣ ጸሎቷንና ልመናዋን በመሻት ይህንን ጾም በመጾም በመንፈስ ተሞልታ ያስተማረችንን ፈሪሐ እግዚአብሔር ገንዘብ በማድረግ መሆን አለበት፤ እንደ ተስፋ ቃሉም ለቃሉ በመታዘዝ መሆን አለበት፤ ቃሉ ይቅር እንድትባሉ ይቅር በሉ፣ ሰላምና አንድነትን አጽንታችሁ ያዙ ይለናል፡፡

ይህን ይቅርታ ለማግኘት የተጠየቅነው ዋናው ነገር እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ እግዚአብሔርን በእውነት የምንፈራ ከሆነ ይቅርታ ለመስጠትም ሆነ ለመቀበል ዳገት አያግደንም ነው፡፡ እግዚአብሔርን መፍራት ማለት በምሠራው ሥራ፣ በመንናገረው ቃል፣ በምናስበው ሐሳብና ምኞት ሁሉ እግዚአብሔር ያውቅብናል፣ ያየናል፣ ይፈርድብናል የሚል አስተሳሰብ በውስጣችን ኖሮ ክፉ ድርጊትን ከማድረግ እንድንቆጠብ መሆን ማለት ነው፡፡

ሰው ሁሉ እግዚአብሔርን ከእርሱ ውጪ እንዳለ ሳይሆን በአጠገቡና በመንፈሱ ውስጥ ሆኖ እንደሚያውቅበት ተገንዝቦ እግዚአብሔርን መፍራት አለበት፣ የሰላምና የአንድነት መሠረት ከፈሪሐ እግዚአብሐየር መነሣት ሲችል ዘላቂና ጠቃሚ ይሆናል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናትና ምእመናን!

ዘንድሮ የምጾመው ጾመ ማርያም ሀገራችንና ሕዝባችን በሰው ሠራሽና በተፈጥሮ አደጋ ውስጥ ተከበው ባሉበት ወቅት ነው፤ የተጋረጡብን ፈተናዎች እግዚአብሔርን ይዘን ካልሆነ በቀር ብቻችንን ሆነን የምንወጣቸው አይደሉም፤ በእግዚአብሔር ከለላነት እነዚህን ፈተናዎች ልናልፋቸው ከሆነ እሱን በመፍራት ከክፋታችን መመለስና ንስሓ መግባት አለብን፤ በነገው ዐለት የምንጅመረው የጾመ ማርያም ሱባኤም ዋናው ዓላማው በንስሓ ወደ እግዚአብሔር ለመመለስና እሱን በመፍራት ለእሱ ተገዢዎች ለመሆን ነው፡፡

ሁሉም እንደሚያውቀው ንስሓ በይቅርታና በዕርቅ መታጀብ ይገባዋል፤ ችግሮቻችን ምን ያህል ቢበዙም ለእግዚአብሔር ብለን ብንፈጽመው ይቅርታና ዕርቅ፣ በምናረጋግጠው ሰላምና አንድነት ተሸናፊዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ችግሮችን ለማሸነፍ ብሎም ለማስወገድ ከይቅርታና ዕርቅ፣ ከሰላምና አንድነት የተሻለ አማራጭ እንደሌለልሂቃኖቻችንም ሆኑ ሕዝቦቻችን በውል መገንዘብ አለባቸው፡፡

ኢትዮጵያ የምትባለው ሀገር የዚህ ትውልድ ሀገር ብቻ አይደለችም፤ ያለፉ አባቶች፣ የሚመጡ ትውልዶችም የኢትዮጵያ ባለቤቶች ናቸው፡፡ እኛ በክብ ጠረጴዛ ተገናኝተን ተወቃቅሰንና ተመካክረን ችግሮቻችንን በተሸንፎ ማሸነፍ ጥበብ ማረም ካቃተን ቢያንስ ኢትዮጵያን ባለችበት ሁናቴ ለባለመብቱ ለመጪው ትውልድ የማስተላለፍ ግዴታ እንዳለብን መዘንጋት የለብንም፤ ነገሮችን ሁሉ በትዕግሥት፣ በአርቆ አስተዋይነትና በሰላማዊ ሁኔታ ለማስተናገድ ያላሰለሰ ጥረት ማድረግ ይገባናል፤ በመሆኑም ኢትዮጵያ የገጠሟትን ፈተናዎች ሁሉ ተቋቁማ በአሸናፊነት መሻገር የምትችለው እግዚአብሔርን በመፍራት ለይቅርታና ለዕርቅ ስንዘጋጅ ነው፤ ስለዚህ ይህ ግንዛቤ ተወስዶ ለኢትዮጵያና ለኢትዮጵያውያን ቆመናል የሚሉ የፖለቲካ ተፎካካሪ ወገኖች ሁሉ አንድ ላይ ተገናኝተውና በክብ ጠረጴዛ ሆነው በመወያየት የሀገሪቱን አንድነት፣ ሰላምና ልማት እንዲያስቀጥሉ በዚህ አጋጣሚ በእግዚአብሔር ስም እንማፀናለን፡፡

በመጨረሻም፣

ሕዝበ ክርስቲያኑ የጾም ሱባኤ በኮረና ቫይረስ እንዳይጎዳ ጥንቃቄ በማድረግ የሱባኤውን ወቅት ስለ ሀገር ሰላምና አንድነት በኃዘን፣ በምህላ፣ በጸሎት፣ በንስሓና በፍቅር፣ የተቸገሩትንም በመርዳት እግዚአብሔርን በመፍራት እንዲያሳልፍ አባታዊና መንፈሳዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

                        እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ፣ ይቀድስ፤

                        ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም

ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሐምሌ ፴ ቀን ፳፻፲፪ ዓ.ም

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ

ውጣ ውረድ

በእንዳለ ደምስስ

ከአርሲ ነገሌ አምስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ከሚገኘው የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን መጠለያ ውስጥ ከአንድ መቶ ያልበለጥን ኦርቶዶክሳውያን ክርስቲያኖች ሰሞኑን “መንደራችንን ከክርስቲያኖች የማጽዳት ዘመቻ” በሚል በጽንፈኛ አክራሪ ሙስሊሞች በተከሠተ ወረራ መሰል ዘመቻ ተፈናቅለን ተጠልለናል፡፡ መኖሪያ ቤቶቻችን ተቃጥለዋል፣ ንብረቶቻችን ወድመዋል፣ ከጥቂት አባወራዎች በስተቀር አባቶቻችን ታርደዋል፡፡ በእግዚአብሔር ቸርነት የተረፍነው ቤት ንብረታችንን ጥለን ራሳችንን ለማዳን ቤተ ክርስቲያንን መጠጊያ አድርገናል፡፡

አባቴ በሰማዕትነት ካለፉት ውስጥ አንዱ ነው፡፡ እኔንና እናቴን ደብድበው ሲጥሉን፣ አባቴ እኛንና ቤት ንብረታችንን ለመከላከል ሲል ባደረገው ተጋድሎ እንደ በግ እጅና እግሩን አስረው በፊት ለፊታችን አርደውታል፣ ቤታችንን ከነከብቶቻንና ንብረቶቻችን ሁሉ እሳት ለቀውበታል፡፡

ሰፈሩ በለቅሶና በዋይታ ተሞልቶ ሁሉም ራሱን ለማዳን ማቄን ጨርቄን ሳይል ነፍሱን ለማዳን ይሯሯጣል፡፡ እንደምንም እናቴን ከወደቀችበት አንስቼ ወደ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ነፍሳችንን ለማዳን ሮጠን ከክርስቲያን ወገኖቻችን ጋር ተቀላቀልን፡፡

ተወልጄ ያደግሁት እዚያው መንደር ውስጥ ነው፡፡ የ፳፯ ዓመት ወጣት ስሆን ሰላማዊት ዋለልኝ እባላለሁ፡፡ እኔና ቤተሰቦቼ በመንደሩ በጣት ከሚቆጠሩ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች መካከል ነን፡፡ በርካታ የእስልምና እምነት ተከታዮች የሚገኙባት ሲሆን በየአራት ወይም አምስት መቶ ሜትሮች ከግዙፍና ዘመናዊ እስከ ቆርቆሮ ለበስ አነስተኛ መስጊዶች ከቁመታቸው ገዝፈው ይታዩባታል፡፡ ፺፭ በመቶ የሚሆነው የአካባቢው ነዋሪ የእስልምና ተከታይ ሲሆን፣ ወንዶቹን ነጭ ጀለቢያ ሴቶቹን ደግሞ ጥቁር ሂጃብ ለብሰው በየመንገዱ ማየት የተለመደ ትእይንት ነው፡፡

በአቅራቢያችን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት ተከታዮች የምንገለገልበት የፃድቁ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን ብቸኛው ነው፡፡ መላው ቤተሰባችን በእምነታችን በጣም ጠንካራ ከሚባሉት ውስጥ እንመደባለን፡፡ በተለይም አባቴ ይህ ቤተ ክርስቲያን በአያቴ ከፍተኛ ጥረት የተተከለ ነው ብሎ ስለሚያምን ልዩ ፍቅር አለው፡፡ ባለው ጊዜ ሁሉ ዘወትር ቤተ ክርስቲያን የጎደላትን በማሟላት ደከመኝ ሰለቸኝ የማይል ስለሆነ ከእናታችን ጀምሮ ቤተሰቡ ሁሉ የእርሱን ፍኖት ተከትለን አድገናል፡፡ በየቀኑ አስገዳጅ ችግር ካልገጠመን በስተቀር ቤተ ክርስቲያን ሄደን ሳንሳለምና የኪዳን ጸሎት ሳናደርስ አንውልም፡፡ የኪዳን ጸሎት ባይታጎልም የአገልጋይ እጥረት ስላለ በሰንበተ ክርስቲያንና በዓመት አራት ጊዜያት ከሚከበሩ የፃድቁ መታሰቢያ ክብረ በዓላት፣ በተጨማሪ የዘመን መለወጫ፣ የልደት፣ የትንሣኤ እና የደብረ ታቦር በዓላት ብቻ ይቀደስበታል፡፡

በቀድሞው ዘመን ክርስትና ከተስፋፋባቸው አካባቢዎች አንዱ የነበረ ቢሆንም ቀስ በቀስ ግን እስልምናው አይሎ ኦርቶዶክሳውያን አረጋውያን ዐረፍተ ዘመን እየገታቸው በማረፋቸው፣ የእስልምናው ተጽእኖ መቋቋም ተስኗቸው ወደ ከተማ የገቡ በርካቶች ናቸው፡፡ ክርስቲያን የነበሩ ልጃገረዶችንም በጠለፋም ይሁን በሀብት የበላይነትና በማስፈራራት በማስለም ስለሚያገቧቸው የክርስቲያኑ ቁጥር ተመናምኗል፡፡ በዚህም ምክንያት የአብዛኛው ነዋሪ መሠረት ክርስትና ቢሆንም ዛሬ ግን ተለውጧል፡፡

ለመስፋፋታቸው ዋነኛው ምክንያት ከአስገዳጅነታቸው በተጨማሪ የክርስቲያኖች ቸልተኝነት፣ ክርስቲያን ወንዶች በሥራ ምክንያት በሚያደርጉት እንቅስቃሴ የትዳር አጋሮቻቸውን ከከተማ ይዘው ስለሚመጡ የአካባቢው ተወላጅ የሆንን ልጃገረዶች ወደ ዩኒቨርሲቲ የመግባት ዕድል ካለገኘን ወይም ወደ ከተማ ካልኮበለልን በስተቀር ትዳር ሳንይዝ ዕድሜአችን እያለፈ በዕድላችን ስናማርር እንኖራለን፡፡

ሁለቱ ታላቅ እኅቴና ታናሼ በዚህ ምክንያት በሙስሊም ወጣቶች ገንዘብ ተደልለው ምድራዊ ሕይታቸውን ለማሳመር ሲሉ የእግዚአብሔር ልጅነታቸውን ክደው፣ የአባቴን ልፋትና መሠረታቸውን ጥለው ሰልመዋል፡፡ ሁለቱ ወንድሞቼም የከተማ ነጋዴ ስለሆኑ እንደ ሌሎቹ የአካባቢያችን ወጣቶች በከተማ ኑሯቸውን መሥርተው፣ በከተማው ያገኟቸውን ሴቶች አግብተው ይኖራሉ፡፡ አባቴ እኅቶቼን ለማስመለስ ያደረገው ጥረት ስላልተሳከለት በኀዘን እንደተኖር ነበር፡፡

በትምህርቴ እስከ ፲፪ኛ ክፍል ልድረስ እንጂ ውጤት ስላልመጣልኝ እቤት ቀርቻለሁ፡፡ የቤተሰቦቼን እጅ ከመጠበቅ እያልኩ ያልሞከርኩት ሥራ የለም፤ ግን አልተሳካልኝም፡፡ በቅርቡ ግን ሰፈራችን ከሚገኝ ጉልት ድንች፣ ቲማቲምና የመሳሰሉትን እየቸረቸርኩ ከራሴ አልፌ ለቤተሰቦቼ መርዳት ባልችልም ለራሴ መሆን አላቃተኝም፡፡ አንድ ነገር ግን ይጎድለኛል፤ በዚህም እጨነቃለሁ፡፡ ትዳር መያዝ አለመቻሌ፡፡

ራሴን ዕድለ ቢስ አድርጌ እቆጥረዋለሁ፡፡ ነፍሷን ይማርና አያቴ “አንዲት የገጠር ሴት ትዳር ይዛ ራሷን ካልተካች እንዴት ሴት ተብላ ትጠራለች?” እያለች ስትናገር የምሰማው ድምጽ ሁልጊዜ ዕረፍት ይነሳኛል፡፡

ያገቡም ያላገቡም ሙስሊም ወንዶች እኔን ከመጠየቅ ወደ ኋላ ያሉበት ጊዜ የለም፡፡ በተለያዩ መደለያዎችን ስጦታዎች እጅ እንድሰጥ ከማድረግ እስከ ዛቻና ማስፈራሪያ ይደርስብኛል፡፡ አንዳንዶቹ ሦስትና አራት ሚስት ያላቸው ናቸው መውጫ የሚከለክሉኝ፡፡ ነገር ግን በያዝኩት እውነተኛና ቀጥተኛ በሆነው በክርስትና መንገዴ ከማንም ጋር አልደራደርም፤ የትናንት፣ የዛሬም፣ የወደፊትም አቋሜ ነው፡፡ ከአካባቢው ልማድ አንጻር ዕድሜዬ እየገፋ እንደሆነ ይታወቀኛል፣ ነገር ግን እግዚአብሔር አምላኬን፣ የአምላኬን እናት ቅድስት ድንግል ማርያምን፣ ቅዱሳን ጻድቃን፣ ሰማዕታትን፣ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ትቼ ከምኮበልል ሞቴን እመርጣለሁ፡፡

ማግባት እንዳለብኝ ውስጤ ያስገድደኛል፡፡ ግን ማንን ላግባ? ፈላጊ እንደሌላት ጋለሞታ ራሴን እቆጥራለሁ፡፡ መልሼ ደግሞ እግዚአብሔር ለእኔ ያዘጋጀው ይኖራል፣ ለምን አጉረመርማለሁ እያልኩ ራሴን ለማጽናናት ጥረት አደርጋለሁ፡፡ ውስጤ ደስታ ርቆታል፡፡ በከፋኝ ሰዓት መሸሸጊዬ ፃድቁ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሔጄ ዕንባዬን እያፈሰስኩ እቆያለሁ፡፡

እኅቶቼን ጨምሮ የቅርብ ጓደኟቼ ብዙዎቹ “ደረቴ ይቅላ፣ የዚህ ዓለም ኑሮን ላጣጥማት” በሚል ፈሊጥ በተኩላዎች ተነጥቀው ጓደኛ የምለው የለኝም፡፡ በየቀኑ “እከሊት እኮ ሰለመች፣ እከሌን እኮ አገባችው” መባል የተለመደ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ቀስ በቀስ የክርስቲያኖች ቁጥር ተመናምኗል፡፡ ያም ቢሆን ግን በሰላም ተከባብሮ ከመኖር ውጪ አንዱ በአንዱ ላይ ተነሥቶ ግጭት ተከስቶ አያውቅም ነበር፡፡ ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ግን መልኩን ቀይሮ “ክርስቲያኖችን ከአካባቢው ማጽዳት” በሚል እንቅስቀሴያቸው በየጊዜው ግጭት ማስተናገድ የተለመደ ሆኗል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ ብንጠለልም አባቴን መርሳት አልቻልኩም፡፡ ሕይወቱ ቢያልፍ እንኳን አስከሬኑ የአውሬ ሲሳይ እንዳይሆን መቅበር አለብኝ በሚል ስሜት ተነሣሥቼ ግርግሩ ጋብ ሲል አመሻሽ ላይ ወደ ሰፈራችን ሮጥኩ፡፡ አካባቢው ምድረበዳ መስሏል፣ ያስፈራል፣ ቤት ንብረታችን ወድሞ ጭሱ ብቻ አልጠፋም፡፡ አባቴን ከታረደበት ለማንሣት አስከሬኑን ዞር እያልኩ ፈለግሁ፣ ማግኘት ግን አልቻልኩም፡፡ በታረደበት ቦታ የፈሰሰውን ደሙን ብቻ አገኘሁ፡፡ ቁጭ ብዬ አለቀስኩ፡፡

“ልጄ አታልቅሺ፡፡ አባትሽ የጀነት ሰው ነው፡፡ ልጆቻችን እምቢ ብለው አብረን በፍቅር ከኖርናቸው ሰዎች ለዩን፣ ምን እናድርግ ልጄ አቅም አጣን፣ እንደ እናንተው ዕንባችን እናፈስሳለን፡፡ በይ ደሙ እንዳይዞርብሽ ተነሺ” አሉ ጎረቤታችን ሐጂ ሙስጠፋ እነሣ ዘንድ በደከመ ጉልበታቸው እየጣሩ፡፡

“ሐጂ ተዉኝ፡፡ አባቴ ካረፈበት፣ ሰማዕትነት ከተቀበለበት ሆኜ ላልቅስ” ብዬ ሣሩ ላይ ተደፋሁ፡፡

“ልጄ እያደረግሽ ያለው ነገር በጎ አይደለም፣ እባክሽ ልጄ ካገኙሽ ይገድሉሻል፡፡ የአባትሽንና የሌሎችን ጎረቤቶቻችን አስከሬን የአካባቢው ሚሊሺያዎች አንስተው የት እንደወሰዷቸው እኛም አናቅንም፡፡ ለእናትሽ አንቺ እንኳን ትረፊላት” ብለው ካነሡኝ በኋላ  አብረውኝ አለቀሱ፡፡

ተስፋ ቆርጬ በመጣሁበት ፍጥነት እየሮጥኩ የቀረችኝ እናቴና ሌሎች ወደተጠለሉበት የጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በረርኩ፡፡

ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከተጠለልን ሦስተኛ ቀናችን ነው፡፡ ነፍስን ለማቆየት የሚበላ የሚቀመስ ባለመኖሩ የሕፃናት ዋይታ፣ የደካማ እናቶች ጣር፣ ከፍተኛ ድብደባ የደረሰባቸው፣ የተደፈሩ ወጣችና እናቶች ሥቃይ ያስጨንቃል፡፡ የትኛውን አጽናንተን የትኛውን እንተው? የሰቆቃ ዕንባ ከእናቶችና ሕፃናት እንደ ጎርፍ ይፈሳ’ል፣ ካህናቱ ነፍሳቸውን ለማትረፍ ሲሉ ጽላቱን ይዘው ሸሽተዋል፣ አንድም ጠያቂ ሆነ አጽናኝ አካል ብቅ አላለም፡፡

አመሻሽ ላይ ከዐሥር የሚበልጡ የአካባቢው ሚሊሺያዎችና ሦስት የአስተዳደር አካላት በአንድ አይሱዙ መኪና ምግብና ብርድ ልብስ ይዘው መጡ፡፡ በተፈጠረው ነገር ማዘናቸውን፣ ችግሩን የፈጠሩት ፀረ ሰላም ኃይሎች እንደሆኑ በመግለጽ አሰልቺ ዲስኩራቸውን ከደሰኮሩ በኋላ ለተጎዱት ሰዎች ነገ የጤና ባለሙያዎችን ይዘው እንደሚመጡና ለጊዜው ለሕፃናትና ለእናቶች እንዲሁም ለሌሎቻችን የሚሆኑ የታሸጉ ምግቦችን፣ የሚጠጣ ውኃ እና ብርድ ልብሶችን አከፋፍለው ሄዱ፡፡

እናቴ ጭካኔን በተላሞሉ ጎረምሶች በደረሰባት ድብደባ ከተጎዱት ሰዎች አንዷ ናት፡፡ እኔን ግን ከማንገላታት ያለፈ ብዙም ጉዳት አልደረሰብኝም፡፡ ብዙዎቹ የማውቃቸው ልጆች ተደፍረዋል፣ እኔን ግን አምላከ ተክለ ሃይማኖት ከልሎኛል፡፡ ለእናቴና ለእኔ የሚያስፈልገውን ምግብና ብርድ ልብስ ተቀብዬ እናቴን ለመንከባከብ ሞከርኩ፡፡ ረኃብና ጥማችንንም ካስታገሥን በኋላ የተጎዱትን ለመንከባከብ የተወሰንን ሰዎች ተሰባበስን ተሯሯጥን፡፡ ነገር ግን ከፍተኛ ሕክምና የሚያስፈልጋቸው ሰዎች ሁኔታ ከአቅማችን በላይ ሆነ፡፡ ያለን አማራጭ ነገ ይመጣሉ የተባሉትን የጤና ባለሙያዎች መጠበቅ ግዴታ ሆነብን፡፡

አባቴን አሰብኩት፡፡ እኛን ለማሳደግ የከፈለው መሥዋዕትነት፣ ለእምነቱ ያለው ጽናትና ለቤተሰቡ እንዲሁም ለሀገሩ ያለው ፍቅር በቀላሉ መግለጽ አይቻልም፡፡ “እባካችሁ አትግደሉኝ” እያለ እየለመናቸው ፊት ለፊቴ እንደ በግ አረዱት፡፡ ያሰማው የሲቃ ድምፅ እረፍት ነሳኝ፡፡ ምንም መፍጠር ሳልችል፣ ለአባቴ አለሁልህ ሳልለው በፊቴ ታረደ፡፡ ከማልቀስና ከማንባት በስተቀር ሐይወቱን ከግፈኞች እጅ ማዳን የምችልበት መሣሪያ አልነበረኝም፡፡

አንድ ቀን በጠዋት ከቤተ ከርስቲያን ስመለስ በአካባቢያችን በሀብቱ የሚታወቅ ጎልማሳ ጀለቢያውን ለብሶ፣ በረጅም ወፍራም መፋቂያ ጥርሱን እየፋቀ ፊት ለፊቴ ተደቅኖ ያዘኝ፡፡ ከዚህ በፊት በአካል ከማውቀውና ሌሎች ስለ ሀብቱ ሲያወሩለት መስማት ካልሆነ በስተቀር ምንም አይነት ግንኙነት የለንም፡፡ እጄን ለማስለቀቅ ሞከርኩ፡፡ አልተሳካልኝም፡፡

“ምንድነው የምትፈልገው?” በማለት በቁጣ ጠየቅሁት፡፡

“ረጋ በይ፣ ምን ያፈናጥርሻል? ሴት ልጅ አደብ ሲኖራት ነው የሚያምርባት፣ አደብ ግዢ” አለኝ፡፡

በንዴት ገፍትሬው ለመሔድ ጥረት ባደርግም በፈረጠመው ጡንቻው ይዞ አስቀረኝ፡፡

“ለምን አትለቀኝም፡፡ እኔና አንተን የሚያገኛኘን ምንም ነገር የለም” አልኩት እየተጠየፍኩት፡፡

እየሳቀ “ያገናኘናል እንጂ፡፡ እኅቶችሽ እንዴት ተንደላቀው እንደሚኖሩ አታውቂም? የአጎቶቼ ልጆች ናቸው ያገቧቸው” አለኝ፡፡

“እና?”

“እናማ እኔም አንቺን አገባለሁ” አለኝ ሳያመነታ፡፡

“ገድል ግባ፡፡ እኔና አንተ ምን ኅብረት አለን? ዞር በልልኝ ልሂድበት፡፡”

“እኔን ተራምደሽማ አትሔጂም፡፡ ለጥያቄዬ መልስ እፈልጋለሁ” አለ ቁጣው እያገረሸ፡፡

“አልችልም፡፡ ሂድና በገንዘብ የምትደልላትን ፈልግ፡፡ እኔ ክርስቲያን ነኝ” አልኩት ከራስ ፀጉሩ እስከ እግር ጥፈሩ በመጠየፍ እየተመለከትኩት፡፡

“እንደ ሦስቱም ሚስቶቼ ምንም ሳላጓድል ነው አንቀባርሬ ነው የማኖርሽ” አለ እየሳቀ፡፡

ያለኝን ኃይል አጠራቅሜ ገፍትሬው መንገዴን ቀጠልኩ፡፡ ባለበት እንደቆመ የፌዝ ሳቁ ብቻ ተከተለኝ፡፡

እቤት እንደተመለስኩ እያለቀስኩ ለአባትና እናቴ ነገርኳቸው፡፡ “እኛ ለአንቺ መሆን አያቅተንም፡፡ በክርስትና ሕይወትሽ ጠንክሪ፣ የእግዚአብሔርንም ጊዜ ጠብቂ፡፡ እንደ እኅቶችሽ እንዳናዝንብሽ ተጠንቀቂ” በማለት አባቴ አቅፎ አጽናናኝ፡፡

እናቴም “ዕድሜዬ ገፋ፣ ቆሜ ቀረሁ እያልሽ አትጨነቂ፤ እግዚአብሔር ምን እንዳዘጋጀልሽ አታውቂም፡፡ ልመናሽ ወደ እግዚአብሔር ይሁን፣ በገንዘብና ብልጭልጭ ነገር አትታለዪ፣ እኅቶችሽን አጥተናልና አንቺንም እንዳናጣ አደራሽን” አለችኝ፡፡

በዐራተኛው ቀን ጠዋት ከወረዳው የሕክምና ባለሙያዎች መጥተው ጎበኙን፡፡ ከፍተኛ ጉዳት የደረሰባቸውን እየለዩ ወደ መኪናዎቻቸው ወስደው በሆስፒታል ደረጃ ሕክምና እንደሚያስፈልጋቸው ከገለጹ በኋላ ለሌሎቹ አስፈላጊውን የመጀመሪያ ሕክምና ዕርዳታ አደረጉላቸው፡፡

ከነርሶቹ መካከል አንገቷ ላይ ወፈር ያለ ክር ያሰረችው ነርስ ሁላችንንም ሰብስባ “አሁን አካባቢው እየተረጋጋ ነው፡፡ ክፉ አድራጊዎች ለሰው ባይቻለው ከእግዚአብሔር ፍርድ አያመልጡም፡፡ ለዚህም ነው አካባቢውን የጦር ቀጠና አድርገው፣ የሚገድሉትን ገድለው፣ የሚዘርፉትን ዘርፈው በአይሱዙ መኪና ተጭነው ሲሔዱ ተገልብጦ ለወሬ ነጋሪ እንኳን ሳይተርፉ ጥልቅ ገደል ውስጥ ገብተው አልቀዋል፡፡ እናንተ ልትረጋጉ ይገባል፡፡ አይዟችሁ” በማለት አጽናናችን፡፡

ክፉን በክፉ መቃወም ተገቢ ባይሆንም ለደረሰብን የመንፈስና የአካል ስብራት ባይጠግንልም፣ በሰማዕትነት ያረፉ ቤተሰቦቻችንን በአካል ባይመለሱልንም ክፉ አድራጊዎቹ ሳይውል ሳያድር መቀሰፋቸው አስደሰተን፡፡

በአምስተኛው ቀን ከአርሲ ሀገረ ስብከት የተውጣጡ ልዑካን አልባሳትና ምግብ ይዘው በመምጣት እስከ አሁን ያልመጡት መላው አርሲ አለመረጋጋት እንደነበር በመግለጽ ቶሎ ባለመድረሳቸው ይቅርታ ጠየቁን፡፡ የወንጌል ትምህርት በመስጠት እያበረታቱን ለሦስት ቀናት አብረውን ቆይተው ተመለሱ፡፡

ለአሥራ አምስት ቀን ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከጠጠለልን በኋላ አካባቢው በመረጋጋቱ ወደመጣንበት እንድንመለስ ተደረገ፡፡ ያ ውጣ ውረድ የበዛበት፣ እንግልትና ሞት የበዛበት ሕይወት በእግዚአብሔር ቸርነት አልፏል፡፡ ከደቂቃዎች በኋላ ምን እንደሚፈጠር አናውቅም፣ ዛሬን በተጠንቀቅ፣ ነገን ደግሞ እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ ኑሮአችንን እንደገና “ሀ” ብለን ጀመርን፡፡

ቅዱስ መስቀል

በዲ/ን ዘክርስቶስ ፀጋዬ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተሰቅሎበት የነበረው መስቀል ያደርግ የነበረው ተአምራት በመቃወም አይሁድ እንደቀበሩት በአብዛኛዎቹ ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያናት ይተረካል፡፡ አይሁድ በሮማውያን ላይ እስከአመጹበት፣ ኢየሩሳሌም ከክርስትና በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ እስከጠፋችበት እስከ ፸ ዓ.ም ድረስ መስቀሉ በክርስቲያኖች እጅ ነበር፡፡ ይህም ቆስጠንጢኖስ ለኢየሩሳሌሙ ኤጲስ ቆጶስ ለአቡነ መቃርዮስ በጻፈው እና እነ አውሳብዮስ መዝግበው ባቆዩት የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ተገልጧል፡፡ ቀጣዮቹ ፫፻ ዓመታት ለክርስቲያኖች የመከራ ጊዜያት ነበሩ፡፡ በእነዚህ ጊዜያት የሮም ቄሣሮች ክርስቲያኖችን የሚያሳድዱባቸው ዓመታት ስለነበሩ መስቀሉን የመፈለግ ጉዳይ በልብ ይታሰብ እንጂ በተግባር ሊሞከር አልተቻለም፡፡

መስቀሉና ንግሥት ዕሌኒ

ጥንታውያን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ጸሐፊዎች መስቀሉን ከጠፋበት (ከተሰወረበት) ያገኘቸው ንግሥት ዕሌኒ መሆኗን ይገልጻሉ፡፡ ድርሳነ መስቀል ዘየካቲት እና ዘመጋቢት እንደተገለጸው እስከ ፫፻፲፰ ዓ.ም ተሰውሮ የነበረው መስቀል ያለበትን ይገልጽላት ዘንድ አስቀድማ እግዚአብሔርን በጸሎት ጠየቀች፡፡ ከዚያም በሮሜ ሀገር የሚኖሩ ሊቃውንትንና ጥበበኞችን ሰብስባ የክብር ባለቤት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበትን መሰቀል ዜና ንገሩኝ አለቻቸው፡፡ ሊቀ ጳጳሱ ቀራንዮ በሚባል ቦታ አዳምና ልጆቹን ለማዳን የክብር ባለቤት ጌታችን እንደ ተሰቀለ፣ በጎልጎታም እንደተቀበረ፣ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሳ፣ በዐርባ ቀንም በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ እንደ ዐረገ ተረከላት፡፡ ንግሥት ዕሌኒም ፈጽሞ ደስ አላት፣ የእግዚአብሔርን ፈቃድ እየጠየቀች ሰባት ዓመት ያህል ቆየች፡፡ ከሰባት ዓመት በኋላም ልጅዋ ቆስጠንጢኖስን በመንግሥቷ ዙፋን አስቀምጣ የክብር ባለቤት የኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል ትፍልግ ዘንድ ከሮም ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች፡፡ በ፫፻፳፭ ዓ.ም አየሩሳሌም ደርሳ አይሁድንም ሰብስባ የክብር ባለቤት የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል ያለበትን ንገሩኝ፣ አባቶቻችሁ ወዴት እንደቀበሩት አሳዩኝ አለቻቸው፡፡ እነርሱ ግን እኛ የሆነውን አናውቅም፣ አባቶቻችንም መስቀሉን በምድር ውስጥ አልቀበሩም፣ ነገር ግን ስማቸው ኪራኮስ እና አሚኖስ የሚባሉ ሁለት አረጋውያን በእኛ ዘንድ አሉ፡፡ እነርሱም ስለዚህ ጉዳይ ይነግሩሽ ዘንድ ጠይቂያቸው አሏት፡፡

ንግሥት ዕሌኒ ወደ ቤተልሔም ገብታ “የታላቁ ንጉሥ ሀገሩ ቤተልሔም ሆይ ሰላምታ ይገባሻል” እያለች የመስቀሉን ነገር ይገልጽላት ዘንድ ለሰባት ቀናት እያለቀሰች ወደ እግዚአብሔር በመስገድ ማለደች፤ ጸለየች፡፡  ከዚያም ወደ ዮርዳኖስ፣ ቆሮንቶስ፣ ደብረ ታቦር፣ ቀራንዮ፣ ጌቴ ሴማኒ ሔዳ ሰባት ቀን ጾመች፣ ጸለየች፣ በጎልጎታ ድንኳኖቿን ተክላ ከተመች፡፡ በጾምና በጸሎት ብዙ ዕንባ በማፍሰስ እስከ ዐርባ ቀን ቆየች፡፡

በመጨረሻም በአረጋዊው ኪራኮስ አመላካችነት፣ በዕጣን ጢስ ጠቋሚነት ክቡር መስቀሉን ፈልጎ ለማግኘት ቁፋሮው ከመስከረም ፲፯ እስከ መጋቢት ፲ ቀን ወደ ስድስት ወራት የሚጠጋ ጊዜ ፈጀ፡፡ በመጨረሻም መጋቢት ፲ ቀን መስቀሉ ከተቀበረበት ወጥቷል፡፡ በዚህም መሠረት የኢትዮጰያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ዕለቱን ታከብረዋለች፡፡

ቅዱስ መስቀሉና ኢትዮጵያ

ግማደ መስቀሉን ካገኙትና ከጠበቁት ሀገሮች ኢትየጵያ ሀገራችን አንዷ ናት፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መዛግብት እንደሚገልጹት ግማደ መስቀሉ ወደ ኢትዮጵያ ጉዞ የጀመረው በ፲፬ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ሲሆን፣ በግሸን አምባ የተቀመጠው ደግሞ በዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ዘመን መንግሥት ነው፡፡

በዐፄ ሰይፈ አርእድ ዘመነ መንግሥት በግብፅ ሡልጣን እና በኢትዮጵያ ንጉሥ መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት ለመፍታት አንድ የልኡካን ቡድን ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ ነበር፡፡ የልኡካን ቡድኑ መሪ የኢየሩሳሌሙ ፓትርያርክ አባ ዮሐንስ ነበሩ፡፡ ልኡካኑ ወደ ኢትዮጵያ ሲደርሱ የዐፄ ሰይፈ አርእድ ልጅ ዐፄ ዳዊት የኢትዮጵያ ንጉሥ ሆነው ነበር፡፡ ፓትርያርኩ በሁለቱ ሀገሮች መካከል የነበረውን ችግር በውይይትና በስምምነት ፈትተው አስማሟቸው፡፡ ዐፄ ዳዊት በነበራቸው ቀና መንፈስ አቡነ ዮሐንስ የኢየሩሳሌሙ ፓትርያርክ ዕሌኒ ንግሥት አስቆፍራ ካስወጣቸው ከጌታ መስቀል ክፋይ ለበረከት እንዲልኩላቸው ወርቅ፣ አልማዝ ሌላም የከበረ ማዕድን ገጸ በረከት አስጭነው ወደ ኢየሩሳሌም መልእክተኞችን ላኩ፡፡ መልእክተኞቹ ኢየሩሳሌም ደርሰው ገጸ በረከቱን ለፓትርያርኩ ከሰጡ በኋላ ፓትርያርኩ የጌታችንን ግማደ መስቀል የቀኙ ክፋይ ከሌሎች ንዋየ ቅድሳት ጋር ላኩላቸው፡፡

ግማደ መስቀሉ በግብፅ በኩል ወደ ኢትዮጵያ ለማስገባት በግብፅ ሡልጣን እና በንጉሥ ዳዊት መካከል ለኢትዮጰያውያን ተሳላሚዎችና ለነጋዴዎች ጥበቃ ማድረግን ጭምር የሚያካትት ስምምነት አካሔዱ፡፡ ግማደ መስቀሉን የያዙት የዐፄ ዳዊት መልእክተኛችም ያለ ችግር ወደ ኢትዮጵያ ጉዞአቸውን ቀጠሉ፡፡ ነገር ግን ዐፄ ዳዊት መልእክተኞቹን ለመቀበል ሲሔዱ መንገድ ላይ መሞታቸውን የጥቅምት ፱ ቀን ፲፬፻፬ ዓ.ም ታሪካቸው ይናገራል፡፡ ያን ጊዜ ግማደ መስቀሉ በሱዳን ስናር በሚባል ቦታ ነበር፡፡

ግማደ መስቀሉ ኢትዮጵያ የገባው መስከረም ፲ ቀን ሲሆን ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ግሸን አምባ ላይ ያስቀመጡት መስከረም ፳፩ ቀን በወሎ ክፍለ ሀገር ግሸን ደብረ ከርቤ ተራራ ላይ ነው፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የካቲት ፳፻፭ ዓ.ም

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎቻችን እንኳን በደህና መጣችሁልን!

የተወደዳችሁ በተለያዩ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የምትማሩ ኦርቶዶክሳውያን ወንድሞቻችንና እህቶቻችን፤ እንኳን ለ2012 ዓ.ም የትምህርት ክፍለ ጊዜአችሁ በሠላም አደረሳችሁ፤ እንኳንም በደህና መጣችሁልን!

ዘመኑ የሰላም፣ የጤና እና የውጤታማነት እንዲሆንላችሁ እየተመኘን መንፈሳዊ መልእክቶቻችንን በተለመዱት ሚዲያዎቻችን (ጉባኤ ቃና፣ ድረ ገጽ http://gibi.eotcmk.org/a/ (አማርኛ) http://gibi.eotcmk.org/ao/ (Afaan Oromoo) እና ፌስ ቡክ https://www.facebook.com/የግቢ-ጉባኤያት-አገልግሎት-ማስተባበሪያ-ገጽ-Gibi-Gubaeyat-Coordination-414397429324567/ ላይክ በማድረግ) እንድትከታተሉ ለመጠቆም እንወዳለን!

ማኅበረ ቅዱሳን፣ የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ
ጥቅምት 05 ቀን 2012 ዓ.ም

Barattootni Yaa’iiwwan Mooraa Baga Nagaan Nuuf Dhuftan!

Dhaabbilee ol’aanoo addaddaa keessaatti barachuuf kan dhuftan ijoolleen Ortodooksii hundi keessan baga bara barnootaa 2012’n isin gahe; baga nagaan nuuf dhuftan!!! Akkuma kanaan duraa ergaalee afuurawoo keenya karaa miidiyaalee keenyaa (Gubaa’ee Qaanaa, Websaayitii http://gibi.eotcmk.org/a/ (አማርኛ) http://gibi.eotcmk.org/ao/ (Afaan Oromoo) fi FB keenya https://www.facebook.com/የግቢ-ጉባኤያት-አገልግሎት-ማስተባበሪያ-ገጽ-Gibi-Gubaeyat-Coordination-414397429324567/ waan isiniif dabarsinuuf LIKE gochuudhaan akka nu hordoftan isin yaadachiisna!

Waldaa Qulqullootaa, Qindeessaa Tajaajila Yaa’iiwwan Mooraa

Onkololeessa 05, B.A 2012

የሕማማት ሣምንት ሐሙስ ስያሜዎች

በሰሙነ ሕማማት ውስጥ ማለትም ከሰኞ አስከ ቅዳሜ 6 ቀናት ያሉ ሲሆን በተለይ ዕለተ ሐሙስ በተለያዩ ስያሜዎች ትታወቃለች፡፡ የተወሰኑትንም ለማየት ያህል ፡-

ጸሎተ ሐሙስ፡- የዓለም መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋን የተዋሐደ አምላክ መሆኑን ለመግለጥና ለአርአያነት ጠላቶቹ መጥተው አስኪይዙት ድረስ ሲጸልይ ያደረበት ነውና ጸሎተ ሐሙስ ተባለ፡፡ማቴ 26 ፡1

ሕፅበተ እግር፡- ጌታችን በዚህ እለት የደቀ መዛሙርቱን እግር በፍጹም ትሕትና ዝቅ ብሎ አጥቧል፡፡ ይህም የሚያሳየው የዓለምን ሁሉ ኃጢአት ለማጠብ የመጣ መሆኑን ነው፡፡ ይህንኑ ለመዘከርም ዕለቱ ‹‹ሕፅበተ እግር›› ይባላል፡፡ ይህን ለማስታወስ ዛሬም ከቅዱስ ፓተርያርኩ ጀምሮ ካህናት ሊቃነ ካህናት የደብር አስተዳዳሪዎች፤ በዕለቱ የተገኙትን ምእመናንን እግራቸውን በወይንና በወይራ ቅጠል ያጥባሉ፡፡

የምስጢር ቀን፡- ከሰባቱ ምሥጢራት አንዱ በዚህ ዕለት ተመሥርቷል፡፡ ይኸውም ‹‹ሲበሉም ኢየሱስ እንጀራን አንሥቶ ባረከ ቈርሶም ለደቀ መዛሙርቱ ሰጠና ይህ ስለ እናንተ በመስቀል ላይ የሚቆረሰው ሥጋዬ ነው፤ እንካችሁ፥ ብሉ፡፡ ጽዋውንም አንስቶ አመሰገነ፣ ይህ ስለ እናንተ ነገ በመስቀል የሚፈርስ የሐዲስ ኪዳን ደሜ ነው፥ ከእርሱም ጠጡ›› (ማቴ.26፡26) በማለት እኛ ከእርሱ ጋር፣ እርሱም ከእኛ ጋር አንድ የምንሆንበትን ምሥጥር ከጠላት ዲያብሎስ ሰውሮ ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ቀን በመሆኑ የተሰጠ ሥያሜ ነው፡፡ ይህንኑ አብነት በማድረግም በዚህ ዕለት ክርስቲያን የሆነ ሁሉ በንስሐ ታጥቦ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል ይዘጋጃል፡፡

የሐዲስ ኪዳን ሐሙስ፡- ዕለቱ በዚህ ስያሜ የተጠራበት ምክንያት በዘመነ ኦሪት በእንስሳት ደም የሚቀርበው መሥዋዕት ማብቃቱን ገልጦ ለድኅነተ ዓለም ራሱን የተወደደ መሥዋዕት አድርጎ ያቀረበበት ዕለት በመሆኑ ነው፡፡ ‹‹ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን ሐዲስ ኪዳን ነው፤ ከእርሱ ጠጡ›› በማለቱ ይታወቃል፡፡ ሉቃ.22፡20

የነጻነት ሐሙስ፡- የሰው ልጅ ለኃጢአትና ለዲያብሎስ ባሪያ ሆኖ መኖር ማብቃቱ፣ ያጣውን ክብር መልሶ ማግኘቱ የተረጋገጠበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡ ጌታችን ስለ ሰው ልጅ ነጻነት ሲናገር ‹‹ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም ባርያ ጌታው የሚደርገውን አያውቅምና፡፡ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ›› (ዮሐ.15፡15) በማለት ከባርነት ወጥተን ልጆች የተባልንበት፣ ባርነት ርቆ ከእግዚአብሔር ጋር የተወዳጀንበት፣ ታርቀን አንድ የሆንበት፣  ፍቅር አንድነት ልጅነት የታወጀበት፣ ወደ ቀደመው ክብራችን የተመለሰንበት ዕለት በመሆኑ የነጻነት ቀን ይባላል፡፡

በአጠቃላይ ከዕለተ ሐሙስ በትሕትና ራስን ዝቅ ዝቅ በማድረግ ከትዕቢትም መጠበቅን፣ ፍቅርን፣ አንድነትን፣ በጎነትን፣ ለሰዎች ድኅነት መልካም ማድረግን፣ ትዕግስትን፣ በአገልግሎት ላይም በጾም በጸሎት እና በንሰሐ ሕይወትን መምራት፣ መተሳሰብንና ለሎችም መኖር እንዳለብን እንማራለን፡፡ ቀኑን አስበን ከቀኑም በረከትን እንድናገኝበት በዓሉንም ለሕይወት፣ ለድኅነት እና ለበረከት እንዲያደርግልን የእርሱ መልካም ፈቃድ ይሁንልን አሜን ፡፡

ምንጭ ፡- ስምዐ ተዋሕዶ ልዩ እትም ዘሰሙነ ሕማማት ከሚያዝያ 1-15 ቀን 2004 ዓ/ም

ሰሚ ያጣው የሕፃናት ጩኸት

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

ቀኑ ወረፋውን ለጨለማው ለመልቀቅ በማመናታት ላይ ያለ ይመስላል፡፡ የአዲስ አበባ ምድርም የፀሐይን ብርሃን በሰው ሠራሽ ብርሃን ለመተካት ፓውዛዎቿን ስልም ቁልጭ እያደረገች ነው፡፡ ሁሉም በየፊናው እየተሯሯጠ ነው፡፡ ጠዋት ሥራ የገባው ወደ ቤቱ ለመመለስ፣ ማታ የሚሠራው ደግሞ በአዲስ መንፈስ ለመሥራት ጥድፊያ ላይ ነው፡፡

ከዐዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ዋናው ግቢ ተነሥቼ በድካም የዛለ ሰውነቴን ለማሳረፍ ወደ ቤቴ እያመራሁ ነው፡፡ ስድስት ኪሎ ዩኒቨርሲቲ ፊት ለፊት ዋናውን አስፓልት አቋርጬ ቀጥታ በድባብ መናፈሻ አድርጌ የቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ግቢን ትቼ ወደ ታች ስታጠፍ በርቀት የሚስረቀረቅ የሕፃናት ኅብረ ድምፅ ሰማሁ፡፡ ምን እንደሚሉ አይሰማም፤ የድምፃቸው ጣዕመ ዜማ ግን ልብን ሰርስሮ ይገባል፡፡

Read more

በፍቅር መኖር

…በመ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ…

በክርስቲያናዊ ሕይወት ለመኖር የወሰነ ሰው ሰውን ሁሉ ሊወድ ይገባል፡፡ ፍቅር ሲባል ፍትወታዊ የጾታ ፍቅር ሳይሆን ሁሉንም ሰው ሳይለያዩ መውደድ ነው፡፡ ለዚህ ነው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሕግጋት ሁሉ ፍቅርን ያስበለጠው፡፡ (ዮሐ. 15፥12) ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ሲጠቅስ በሰዎችና በመላእክት ልሳን ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮኽ  ናስ ወይም እንደሚንሿሿ ጸናጽል ሆኛለሁ፤ ትንቢትም ቢኖረኝ ምሥጢርንም ሁሉና ዕውቀትን  ሁሉ ባውቅ ተራሮችንም እስካፈርስ ድረስ እምነት ቢኖረኝ ፍቅር ግን ከሌለኝ ከንቱ ነኝ፤ ድሆችን ልመግብ ያለኝን ሁሉ ባካፍል ሥጋዬንም ለእሳት መቃጠል፤ አሳልፌ ብሰጥ ፍቅር ግን ከሌለኝ ምንም አይጠቅመኝም፡፡ ፍቅር ይታገሣል፤ ቸርነትም ያደርጋል፤ ፍቅር አይቀናም፤ ፍቅር አይመካም፤ አይታበይም፤ የማይገባውን አያደርግም…(1ኛ ቆሮ. 13፥1) በማለት አስረድቷል፡፡

Read more