አገልግሎቴን አከብራለሁ!

በ፲፱፻፺፰ ዓ.ም. ማኅበረ ቅዱሳን ‹‹የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት መጻሕፍት ጥናትና ምርምር ማእከል›› በመክፈት ቅዱሳት መጻሕፍትን ማስተዋወቅ እና ከሚደርስባቸው ልዩ ልዩ ጉዳዮች አደጋዎች ተጠብቀው ለቀጣዩ ትውልድ እንዲተላላፉ ማድረግ ያቋቋመው የአገልግሎት ክፍል ለዛሬው የጥናትና ምርምር ማእከል መመሥረት ምክንያት ነው። ይህ ክፍል በተሻለ አደረጃጀትና የሰው ኃይል ተጠናክሮ ከኅዳር ወር ፳፻፩ ዓ.ም. ጀምሮ ‹‹የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል›› በሚል ስያሜ አገልግሎት መስጠት ጀመረ።

“የሕይወት ቀን” በግቢ ጉባኤያት

ወርቃማው የወጣትነት ዘመናችን በተስፋ፣ በመልካም ምኞትና በትጋት የተሞላ፣ ዕውቀትንና አቅምን ያማከለ ማንነታችን የሚታነጽበት፣ መንፈሳዊነታችን የሚገለጽበት የዕድሜ ክልል እንደመሆኑ የሕይወታችን መሠረት ነው፡፡ መንፈሳዊ ፍሬን አፍርተን ርስተ መንግሥተ ሰማያት ለምንወርስብትም የሕይወት ስንቅ የምንሰንቅበት የተጋድሎ ዘመን ስለመሆኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከልጅነታችን ጀምሮ አበክራ ታስተምረናለች፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤቶቿም ኮትኩታ አሳድጋ መንፈሳዊ ፍሬ ለማፍራት ታበቃናለች፡፡ ለዚህ የመሸጋገሪያ ዕድሜ በደረስንበት ጊዜም የሕይወታችን መርሕ የሆነው ትምህርተ ወንጌል እንዳይጓደልብን በዐውደ ምሕረቷ ላይ ጉባኤ ዘርግታ ሰማያዊ ኅብስትን አዘጋጅታ ትመግበናለች፡፡

ለዶክተር ዐቢይ አህመድ

የኀዘን መግለጫ

“ብንኖረም ብንሞትም ለእግዚአብሔር ነን”፤ሮሜ ፲፬፥፰

እሁድ መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. ከጠዋቱ ፪፡፵፰ ደቂቃ ከአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ተነስቶ ወደ ኬንያ ናይሮቢ በመጓዝ ላይ የነበረው ET ፫፻፪ የመንገዶኞች አውሮፕላን ከ፮ ደቂቃ በረራ በኋላ ከአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት ከምትገኘው ደብረዘይት ወድቆ መከስከሱ ይታወቃል፡፡በመሆኑም ፻፵፱ መንገደኞች ፰ የበረራ አስተናጋጆችን ጨምሮ በድምሩ ፻፶፯ ሰዎች በሙሉ የአደጋው ሰለባ ሆነዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ፲፯ ያህሉ ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ ሌሎቹ ደግሞ የ፴፫ ሀገራት ዜጎች መሆናቸው ታውቋል፡፡ በዚህ ድንገተኛ ክስተት ለተጎዱ መላው ወገኖቻችን፤ ኢትዮጵያውያንንና ቤተሰቦቻቸውን ጨምሮ እግዚአብሔር አምላክ ነፍሳቸውን በአጸደ ገነት ዕቅፍ ያሳርፍልን ፤ ለቤተሰቦቻቸውም መጽናናትን ይሰጥልን ዘንድ እንጸልያለን፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ  ማኅበረ ቅዱሳን

ከማኅበረ ቅዱሳን የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ፡፡

በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን፡፡

ጥር  17 ቀን  2011 ዓ.ም

እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ፡፡ / 1ኛ ጴጥ 4፤7/

በማንኛውም የሰው ልጅ ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችንና ግድያዎችን ሁሉ እናወግዛለን፡፡  በየቦታው የተከሰቱ ችግሮች እንዲቆሙም በድርጊቱ የሚሳተፉ አካላትን ሁሉ እንማጸናለን፤  እናሳስባለንም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን

የክርስትና ሃይማኖት ማእከላዊ ጉዳዩ ሰው ነው፡፡ አምላክ ሰው ሆነ፣፤ ሰውም አምላክ ሆነ፣ የሚለው የትምህርቱ አስኳል ዋና ነጥብም የሚያመለክተው የነገራችን ሁሉ ማእከል ሰው መሆኑን ነው፡፡ ይህም ለሰው ሲባል አምላክ እንኳ ራሱን ዝቅ አድርጎ በተዋሕዶ ሰው ሆኖ መገለጡንና በዚሀም ሰውን ከወደቀበት ማንሣቱን፤  ከዚያም በላይ ሰውን በተዋሕዶ ለአምላክነት ክብር ማብቃቱን የሚገልጽ ትምህርት ነው፡፡ ስለዚህ  ሀገራዊ ብቻ ሳይሆን ዐለምአቀፋዊ ሆነው በትልቁ የሚከበሩት የአምላካችን ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤና ዕርገት ሁሉ ማእከላዊ ነጥባቸው ሰው ነው፡፡ ሁሉም ነገሮች አምላክ ለሰው ሲባል ያደረጋቸው ናቸውና፡፡

ሌሎች አስተምህሮዎች ሁሉ አሁንም ሰውን ለማስረዳት ሲባል የተለያዩ አርእስት ይሰጣቸው እንጂ ማእከላዊ ነጥባቸው አንድ ነው፤ የሰው ድኅነትና ደኅንነት፡፡ የአንድ ሰው ጽድቁም ኃጢአቱም የሚለካው ለሰው በሚያደርገው ወይም በሰው ላይ በሚያደርገው ነው ማለት ይቻላል፡፡ ስለዚህም በምድር ላይ ከሰው በላይ የከበረና ጥንቃቄ ሊደረግለት የሚገባው ምንም ፍጥረት የለም፡፡ በምድር ላይ ጥንቃቄና ዕርምት የሚወሰድበት ነገር ሁሉ የመጨረሻ ዓላማው ሰውን ለመጥቀም ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ከሰው የሚጣላ ከአምላኩም ከአጠቃላይ ከፍጡራንም ሁሉ ጋር የሚጣላ ይሆናል፡፡ በሰው ላይ ያልተገባውን ድርጊት የሚፈጽም ሁሉ በፈጣሪው ላይ የሚያደርግ መሆኑን መዘንጋት የለበትም፤ ፈጣሪ ሰው መሆንን በተዋሕዶ ገንዘብ አድርጎ ሰው ሆኖ ተገልጧልና በሰው የሚደረግ ሁሉ በእርሱ ላይ የሚደረግ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡

የክርስትና ሃይማኖት መምህራንና ተቋማት ዋና ዐላማና ተልእኮም ሊመነጭ የሚችለው ከዚህ መሠረታዊ የሰው ክብርና ዋጋ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ስለዚህ በየትኛውም የዓለም ክፍል በማንኛውም ሰው ላይ የሚፈጸሙ መጥፎ ተግባራት ይልቁንም ከሕግ ማሕቀፍ የወጡትንና በሴራና በተንኮል የሚፈጸሙትን እንደ ማኅበር አብዝተን እናወግዛቸዋለን፤ እንጸየፋቸዋለንም፡፡ ይልቁንም በሀገራችን በኢትዮጵያ ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ የመጣው ንጹሐንን ሰለባ እያደረገ ያለው የተቀነባበረና የተነጣጠረ የሚመስለው ጥቃት በእጅጉ የሚያሳስብ መሆኑ ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡

Read more

እንኳን ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል፣ በሰላም አደረሰን/አደረሳችሁ

 

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡

                                                  በሀገር ውስጥና በመላው ዓለም ለምትገኙ ኢትዮጵያውያን በሙሉ፡-
ከሁሉ በማስቀደም፣ የዘመናት ባለቤት ልዑለ ባሕርይ እግዚአብሔር አምላክ፣ በረከት የምናገኝበትን ፆም በሰላም አስጀምሮ በሰላም በማስፈፀም፣እንኳን ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል፣ በሰላም አደረሰን/አደረሳችሁ! በማለት፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ስር ተዋቅሮ፣ የቅድስት ቤተክርስቲያንን አገልግሎት ለማገዝ፣ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያደረገ ያለው ማኀበራችሁ፣ ማኀበረ ቅዱሳን፣ መልካም ምኞቱን ይገልጻል፡፡

ውድ ምእመናን! የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት፡- የድኀነታችን ተሰፋ ቃል የተፈጸመበት፤ ዓመተ ኩነኔ ተደምስሶ፣ ዓመተ ምሕረት የታወጀበት ዕለት በመሆኑ፤ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ይህን በዓል በየዓመቱ በታላቅ መንፈሳዊ አገልግሎት፣ ደስታና ድምቀት ታከብረዋለች፡፡

እግዚአብሔር ጊዜን ለእኛ የፈጠረ እንጂ፣ለእርሱ ዘመን የማይቆጠርለትና ቦታ የማይወሰንለት አምላክ ሆኖ እያለ፤ እኛን ለማዳን ከእናታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍፁም አምላክ፣ ፍፁም ሰው ሆኖ የተወለደበትን ይህን ዕለት በየዓመቱ እየቆጠርን የምናከብረው፡- የቸርነቱን ስራ እያደነቅን፣ በልደቱ ብርሃንነት ከተገኘው በረከት ተካፋይ በመሆን፣ በመንፈሳዊ ሕይወታችን የበረታን እንሆን ዘንድ ነው፡፡

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲወለድ፡-ሰብአ ሰገል ልዩ ልዩ ገጸ በረከቶችን ይዘው፣ በቤተልሔም እንደተገኙ ሁሉ፣ እኛም ክርስቲያኖች በአንድ ልብና በጋራ በመሆን፣ በተሰጠን ጸጋ፣ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ልናግዝና ልንጠብቅ ይገባል፡፡እኛ ክርስቲያኖች በዓሉን፡- ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ለሰው ልጆች ድኀነትና ፍጹም ሰላም ሲል ወደ ምድር የመጣበትን በማሰብ የምናከብረው ስለሆነ፤ እያንዳንዳችን ከእግዚአብሔር በተሰጠን ሰላም እየተጠቀምንና እርስ በእርሳችን እየተዋደድን፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ብሎም ለሀገራችን ፍሬ ያለዉ ተግባር እንድንፈጽም እግዚአብሔር ይጠብቅብናል፡፡

ውድ ምእመናን! የእግዚአብሔር ልጆች በመሆናችን፣ በሕይወት ዘመናችን ሁሉ ትእዛዛቱን አክብረን በቤቱ ውስጥ መኖር የሚጠበቅብን ስለሆን፣ መዳናችን ዘለዓለማዊነት ያለው ይሆን ዘንድ፣ጌታችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሰማያዊቷ ኢየሩሳሌም የተመሰለችውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ስለመሠረተልን፣ በእርሷ መገልገልና ማገልገል፣ የመንፈሳዊ ሕይወታችን ብቸኛዉ መንገድ ስለሆነ፤ በፍጹም ትጋት ልንጠቀምበት ይገባል፡፡

ማኀበረ ቅዱሳንም፡-የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልጅ በመሆን አገልግሎቷን እየፈፀመ ያለው፣ሁላችንም ያገኘነውን የእግዚአብሔር ልጅነት በማጽናት የሰማያዊው መንግሥት ወራሾች እንሆን ዘንድ ነውና፤ ማኀበሩ፡- ኃይለ እግዚአብሔርን፣ የአባቶችን ጸሎትና ብራኬ አጋዥ በማድረግ እንዲሁም የአባላቱንና የምእመናንን ዐቅምና ድጋፍ በማስተባበር እየፈጸመ ያለው አገልግሎት፣ እግዚአብሔር እንደፈቀደ፣ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎች የምናፈራበትና በሥነ ምግባር ተኮትኩተው በማደግ ሀገራቸዉን በሥርዓት ማገልገል የሚችሉ ዜጋዎችን ማግኘት የምንችልበት ነው፡፡

በአጠቃላይም በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እየተፈጸመ ያለው አገልግሎት፡-
 በዘመኑ ከሚፈለገዉ የቅድስት ቤተክርስቲያን ዘመኑን የዋጀ የአገልግሎት ተደራሽነት፣
 መጠናከር ካለበት አሠራር እንዲሁም
 መፈታት ካሉባቸዉ ፈተናዎችና ችግሮች አኳያ ሲታይ፣ በጣም ትንሽና ከሁላችንም ገና ብዙ የሚጠበቅ ነገር ያለ መሆኑን የሚያሳይ ነዉ፡፡

ስለሆነም ኀምሳ ሎሚ ለአንድ ሰው ሸክም ነው፤ ለኀምሣ ሰው ግን ጌጡ ነው! እንደሚባለው፣ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሆነውን የማኀበሩን አገልግሎት፡ቀርበን በጉልበታችን፣ በጊዜአችንና በገንዘባችን እናግዝ፡፡ እግዚአብሔር በሰጠን ጸጋ እንደ እየአቅማችንና ተሰጥዎአችን በቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር ዉስጥ በቃለ ዐዋዲዉ መሠረት እየገባን፣ ድጋፍና ተሳትፎ እናድርግ፣ በማለት ማኀበሩ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

በመጨረሻም፡-በቅዱስ ወንጌሉ፣ «በነገር ሁሉ ደስ ልታሰኙ ለጌታ እንደሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን» ተብሎ እንደተጻፈ፣ በዓሉን ስናከብር፡- እግዚአብሔር ሰላምን በሃገራችን እንዲያጸናልን በመለመን፣ የተቸገሩ ወገኖችን በማሰብ እና በፍፁም መንፈሳዊ ሕይወት በመመላለስ፣በረከት የምናገኝበት ይሁንልን በማለት ማኀበሩ ምኞቱን ይገልጻል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በኢትዮጵያ ሱማሌ ክልል በተከሰተው ችግር ከማኅበረ ቅዱሳን የተሰጠ መግለጫ!

 

                                                               እንግዲያስ ሰላም የሚቆምበትን እርስ በርሳችንም የምንታነጽበትን እንከተል /ሮሜ  1419/

         በሀገራችን በኢትዮጵያ የሚካሔደውን የመንግሥት የአሠራር ለውጥ ተከትሎ ላለፉት ጥቂት ወራት በተለያዩ አካባቢዎች ግጭቶች መከሰታቸው የሚታወቅ ነው፡፡ በግጭቶችም ከሀብት ውድመት እስከ ክቡሩ የሰው ሕይወት ኅልፈት ድረስ መከሰቱ እና በዚህም መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ማዘኑና ለመፍትሔውም በሚችለው ሁሉ መረባረቡ የሚታወቅ ነው፡፡ ባለፉት ሁለት ቀናት በሶማሌ ክልል የተከሰተው ግን በተለይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን በተለየ ሁኔታ አደጋ ውስጥ መክተቱ ደግሞ የበለጠ አሳዝኖናል፡፡ ይልቁንም ደግሞ ግጭቱ ሆነ ተብሎ ሃይማኖትን መሠረት ያደረገ ሰፊ ጥፋት ለመቀስቀስ የታሰበ መምሰሉ በእጅጉ አሳስቦናል፡፡ ሆኖም ክርስቲያኖችም ሆኑ የሌላ እምነት ተከታዮች ነገሩን በጥንቃቄና ኃላፊነት በሚሰማው ሁኔታ እንደሚይዙት እምነታችን ታላቅ ነው፡፡

የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች እና አማኞች ላይ ልዩ ትኩረት አድረገው ግድያ መፈጸማቸው፣ አብያተ ክርስቲያንን ማቃጠላቸው እና የአማኞቹን ሀብት ንብረት መዝረፋቸውና ማቃጠላቸውም ቢሆን ለሟቹቹ የሰማዕትነትን ክብር ከማቀዳጀቱና ለቤተ ክርስቲያንም ጸጋና ኃይል ከማጎናጸፍ ያለፈ ዘላቂ ጉዳት ሊያስከትል አይችልም፡፡ ምክንያቱም ክርስቲያኖች “በእኔ ሳላችሁ ሰላም እንዲሆንላችሁ ይህን ተናግሬአችኋለሁ። በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ” /ዮሐ 16፥33 / በሚለው የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቃል አምነውና ታምነው የሚኖሩ የሰላም ሰዎች ናቸውና፡፡ ሰማዕትነቱም ቢሆን ለሟቾቹ ብቻ ሳይሆን መከራውን፣ ስቃዩንና ጭንቀቱ ሁሉ ለደረሰባቸው ሁሉ ነውና ሥርየተ ኃጢአትንና ጸጋ እግዚአብሔርን ያበዛላቸዋል እንጂ ቤተ ክርስቲያንን ሊያጠፋት አይችልም፡፡ እንዲያውም በዘመነ ሰማዕታት እንደሆነው በሌላ አካባቢ ያሉ ክርስቲያኖችን ሁሉ ለሰማዕትነት የሚያበቃ በዚያ ጉዳት የደረሰባቸውንም በመርዳት፤ አብያተ ክርስቲያኑንም የበለጠ አድርጎ በመሥራት የሰማዕትነቱ ተካፋይ የመሆን እድል ይሰጣቸዋል፡፡ በፍትሐ ነገሥታችን አንቀጸ ሰማዕታት ላይ እንደተገለጸውም በዚያ የተጎደቱን ለመርዳት የሚረባረቡ ሁሉ ቁጥራቸው ከሰማዕታት ስለሆነ በመንፈሳዊ ዐይን ለሚያዩት ሁሉ ጥቅም እንጂ ጉዳቱ እምብዛም ነው፡፡

ለክርስቲያኖች እንዲህ ያለ መንፈሳዊ ጠቀሜታ ቢኖረውም የሰው ሕይወት ክቡር ከመሆኑ የተነሣ ደግሞ በማናቸውም የሰው ልጆች ላይ ያለአግባብ የሚደርሰው ጥፋት በእጅጉ ያሳዝነናል፤ ያሳስበናልም፡፡ ስለዚህም ከመንግሥት ጀምሮ ኃላፊነት ያለባቸው አካላት ሁሉ ይህን የመሰለ ችግር እየሰፋና እየተበራከተ እንዳይሔድ ቅድመ ጥፋት የጥንቃቄና የሰዎችን ሁሉ የደኅንነት ዋስትና የሚያረጋግጡ እርምጃዎችን መውሰድ ይኖርባቸዋል፡፡ በዚህ ዐይነት ድርጊት የተሳተፉ አካላትንም ለሕግ በማቅረብ ለሰዎች ዋስተናን ለአጥፊዎችም ትምህርትን መስጠት ይኖርባቸዋል፡፡

ጥፋት አድራሾቹ “የሰላምንም መንገድ አያውቁም። በዓይኖቻቸው ፊት እግዚአብሔርን መፍራት የለም” /ሮሜ 3፥17-18 / ተብሎ በቅዱሱ ሐዋርያ የተነገረላቸው መሆናቸውን ለመረዳት አይቸግርም፡፡ ስለዚህም እነዚህ አካላት የየትኛውንም ሃይማኖት የማይወክሉና የራሳቸውን ሰላም አጥተው የሌሎቻችንም ለመውሰድ የተነሡ መሆናቸውን ተረድቶ የእነርሱ ጠባይን ላለመውሰድና ለበቀልና ለመሳሰሉት ተጨማሪ አደጋ አምጭ ነገሮች ተጋላጭ እንዳሆን መጠበቅም ክርስቲያናዊ ብቻ ሳይሆን የመልካም ዜግነት ግዴታችን መሆኑንም ለማስታወስ እንወድዳለን፡፡  በዚህ አጋጣሚ ጥፋቱ ከደረሰው በላይ እንዳይሆን ስትከላከሉና የመልካም ዜግነት ግዴታችሁን ስትወጡ ለነበራችሁ ክቡር የሱማሌ ክልል ህዝብ ከፍ ያለ አክብሮታችንን እናቀርብላችሀለን፡፡ አሁንም በየመጠለያውና በየቦታው ያሉ የጉዳት ሰለባዎችን በመደገፍና ከወደቁበት በማንሳት አርአያነታችሁን እንድምታሳዩንእናምናለን፡፡

በሶማሌ ክልልና በሌሎችም ሆናችሁ ይህ አደጋ የደረሰባችሁ ክርስቲያኖችም ነቢዩ ኢሳይያስ “በአንተ ታምናለችና በአንተ ለምትደገፍ ነፍስ ፈጽመህ በሰላም ትጠብቃታለህ” /ኢሳ 26 ፤ 3/ ሲል በተናገረው ቃለ መጽሐፍ ተማምናችሁ ብትጸኑ ለሰማዕትነት ክብር ከታጩት በቀር እግዚአብሔር እንደሚጠብቃችሁ የታመነ አምላክ ነውና አትረበሹ፡፡ ከዐለም የሆነው ሁሉ ስለመጥፋቱም አትጨነቁ፡፡ “ስለዚህ እላችኋለሁ፥ ስለ ነፍሳችሁ በምትበሉትና በምትጠጡት፥ ወይም ስለ ሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፤ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ አይበልጥምን?” /ማቴ 6 ፤ 25/ ሲል ያስተማረንን ጌታችንን አስታውሳችሁ እንድትጸኑ በፍጹም ፍቅርና ትሕትና ልናሳታውሳችሁ እንወድዳለን፡፡ እንደታዘዝነውም ለሚያሳድዷችሁና መከራውን ላመጡብን ሁሉ ከልብና ከእውነት እንጸልይላቸው፤ ጌታችንን አብነት አድረገንም በአንድነት አቤቱ  የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው ብለን በየዕለቱ እንጸልይላቸው፡፡ በየትም ዐለም ያለን ክርስቲያኖች ሁላችንም ከመቼዉም ጊዜ በላይ ስለቤተ ክርስቲያናችን፣ ስለሀገራችንና በስደትና በመከራ ላይ ስላሉት ሁሉ እግዚአብሔር በሃይማኖታቸው መጽናትን፤ በፍቅርም ይቅርታ ማድረግን በልቡናቸው ይጨምር ዘንድ በጥፋት ጎዳናም ያሉት ልቡና አግኝተው ይመለሱ ዘንድ ጊዜ ወስደን ሥራዬ ብለን ልንጸልይ ይገባናል፡፡ ከዚህም በሻገር ከሰማዕትነት ክብር እንካፈልና እኛንም ልንሸከመው ከማንችለው ፈተና እግዚአብሔር ይጠብቀን ዘንድ የተፈናቀሉትን ለማቋቋም፣ የተቸገሩትን ለመርዳት፣ የፈረሱ አብያተ ክርስቲያንን ለማሳነጽና የሰማዕታቱን ቤተ ሰቦች በዘላቂ ለመርዳት መነሣሣትና ኃላፊነታችንን በአግባቡ በፍጥነት ልንወጣ ይገባናል፡፡

ጉዳት በማድረስ ከምክር እስከ ገቢር የተሳተፋችሁትም በማወቅም ባለማወቅም ከፈጸማችሁት ጥፋት ትመለሱና የእግዚአብሔርንም ይቅርታ ተገኙ ዘንድ “ከክፉ ሽሽ መልካምንም አድርግ ሰላምን እሻ ተከተላትም” /መዝ 34፥14/  በሚለው ቃለ መጽሐፍ እንለምናችኋለን፡፡ የማትመለሱ ከሆነ ግን እርሱ የቁጣ ፊቱን ወደ እናንተ ባዞረ ጊዜም ሊያድናችሁ የሚችል ኃይል የለም፡፡ በነቢዩ ዳዊት “እግዚአብሔርን የምትረሱ እናንተ፥ ይህን አስተውሉ አለዚያ ግን ይነጥቃል የሚያድንም የለም” /መዝ 50 ፤ 22/ ተብሎ ተጽፏልና፡፡ ስለዚህም ይህን አምላካዊ ማስጠንቀቂያ አስባችሁ እንድትመለሱና ሀገራችን የሰላምና የፍቅር ሀገር እንድናደርጋት በእውነት እንማጸናችኋለን። ሁላችንም ልንጠቀም የምንችለው በሰላም፣ በፍቅርና በመተሳሰብ ብቻ ነውና በታላቁ ሐዋርያ በቅዱስ ጳውሎስ ቃል “እንግዲያስ ሰላም የሚቆምበትን እርስ በርሳችንም የምንታነጽበትን እንከተል በማለት ጥሪያችንን እናቀርብላችኋለን /ሮሜ  14፥19/።

እግዚአብሔር አምላካችን ሀገራችንን ሕዝቦቿን ሁሉ በጽኑ ሰላም ይጠብቅልን፤ አሜን፡፡

 ማኅበረ ቅዱሳን

 

 

 

 

 

 

   የአባቶች አንድነት ላይ የተሰጠ  የደስታ መግለጫ!

       

ቅዱስ ቂርቆስና ቅድስት ኢየሉጣ ከእቶነ እሳት በወጡበት በብሥራተ መልአክ በቅዱስ ገብርኤል የመታሰቢያ ዕለት የኢትዮጵያ አርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን  አባቶች  አንድ ሆነዋል፡፡በዚህም የምእመናን ተስፋ ለምልሟል፡፡የጥል ግድግዳ ፈርሷል፡፡ይህ ታላቅ መንፈሳዊ ተግባር የተፈጸመበት ዕለት ለቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ የደስታ ዕለት ነው፡፡ይህ ዕለት ሰይጣን ቤተ ክርስቲያንን ለመዋጋት ጥይቱን የጨረሰበት፤ዝናሩን አራግፎ ባዶ እጁን የቀረበት ነው፡፡ዕለቱ የሰይጣን ጥርሱ የረገፈበትና የቤተ ክርስቲያን ብርሃን ለዓለም የተገለጠበት በመሆኑ የቤተ ክርስቲያን የምስራች ቀን ነው፡፡

ለዚህ ዕለት ደርሶ የተገኘውን ዕርቅ አይቶ የማይደሰት ቢኖር ዲያብሎስ ብቻ ነው፡፡ዕርቁ እውን እንዲሆን መለያየት እንዲወገድ፤የተፈጠረው ክፍተት መፍትሔ እንዲያገኝ ያደረገ እግዚአብሔር ይመስገን በማለት በቅን ልቡና የተቀበላችሁ ቅዱሳን ፓትርያርኮቻችን የፈረሰውን አንድነት በዘመነ ፕትርክናቸሁ ለመጠገን ፤የተለያየውን አንድ ለማድረግ፤የሻከረውን ለማለስለስ ያበቃችሁ እግዚአብሔር ይመስገን !

ከቅዱሳን አባቶቻችንና ከቅዱስ ሲኖዶስ የተቀበላችሁትን አደራ ከዳር ለማድረስ አንድ ጊዜ  አሜሪካ ሌላ ጊዜ ኢትዮጵያ በመመላለስ የደከማችሁ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና  በየአገሩ የምትገኙ የዕርቀ ሰላም ኮሚቴ አባላት እንኳን የድካማችሁን ፍሬ ለማየትና “ዕርቅ የሚያደርጉ ብፁዓን ናቸው፤ እነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይባላሉና” (በማቴ፭፥፱) የተባለው ተፈጽሞ ለማየት አበቃችሁ!

ዕርቁ ለቤተ ክርስቲያን፤ ለምእመናን አንድነት እንዲሁም ለሀገር ሰላም የሚኖረውን ጠቀሜታ ከፍተኛ መሆኑን ተመልክተው ለተግባራዊነቱ የሚችሉትን ሁሉ ላደረጉት ለኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስተር ለክቡር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ከፍተኛ ምስጋና ይገባቸዋል፡፡ በመጨረሻም ዕርቁ ተግባራዊ እንዲሆን በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን ስትጠይቁ ለኖራችሁ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ፤መምህራን ፤ገዳማውያንና ምእመናን  እንኳን ይህን የአባቶችን የአንድነት ቀን ለማየት አበቃችሁ፤አበቃን በማለት ማኅበረ ቅዱሳን በራሱና በአባላቱ ስም ደስታውን ይገልጻል!

ይህ ደስታ የቤተ ክርስቲያን ታላቅ በዓል በመሆኑ ቤተ ክርስቲያናችን በምታደርግልን ጥሪ መሠረት ሁላችንም ምእመናን በአቀባበሉ ሥርዓት በመሳተፍ ፤የድርሻችንን እንድንወጣ ማኅበረ ቅዱሳን ጥሪያውን ያስተላልፋል፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!

ሐምሌ 20 ቀን 2010 ዓ.ም