ማኅበረ ቅዱሳን በኦሮምኛ ቋንቋ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር ሊጀምር ነው

ጥቅምት 23 ቀን 2008 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የአፋን ኦሮሞ ሚዲያ ፕሮጀክት ክፍል ከኅዳር 12 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ በኦሮምኛ ቋንቋ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር እንደሚጀምር የኅትመትና ኤልክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍል ም/ክትል ሓላፊ አቶ አክሊሉ ለገሠ ገለጹ፡፡

በNilesat, OBS /Oromiya broadcast Service/ ለሠላሳ ደቂቃ ዘወትር እሑድ ከረፋዱ 4፡30-5፡00 ሰዓት እንዲሁም በድጋሚ ረቡዕ ከጠዋቱ 12፡30-1፡00 ሰዓት የሚሠራጨው መርሐ ግብር የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊትን ጠብቆ የሚዘጋጅ ሲሆን፣ የኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ ለሆኑ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ስለ እምነታቸው እንዲያውቁ እና ጸንተው እንዲኖሩ፣ እንዲሁም ከእምነታቸው ለወጡ ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲመለሱ ለማድረግ ታስቦ መጀመሩን ምክትል ሓላፊው አስታውቀዋል፡፡

የኦሮሞ ማኅበረሰብን ከቤተ ክርስቲያን ለመነጠል በርካታ መጻሕፍት ታትመው እየወጡ በመሆናቸው የማኅበረ ቅዱሳን የአፋን አሮሞ ሚዲያ ፕሮጀክት ክፍል ይህንን ለመከላከል ምእመናን ለማስተማር፣ እምነታቸውን ጠብቀው ጸንተው እንዲኖሩ ለማድረግ ፕሮጀክቱ መቀረጹንም ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በኦሮምኛ ቋንቋ ምእመናንን የሚያንጹ በርካታ በትምህርተ ሃይማኖት፣ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ላይ ያተኮሩ መጻሕፍትን፣ የጸሎት መጻሕፍትንና መጽሔት በማሳተም፣ በኦሮምኛ ድረ ገጽ ጭምር ሲያሠራጭ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ በቅርቡም Dangaa Lubbuu/ የነፍስ ምግብ/ የተሰኘ መጽሔት በማሳተም ለምእመናን በማዳረስ ላይ ይገኛል፡፡

በቴሌቪዥንና በሬድዮ የሚተላለፉ መርሐ ግብሮችን በካናዳ ለማዳረስ በስልክ አገልግሎት መስጠት ጀመረ

ጥቅምት 17 ቀን 2008 ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን በቴሌቪዥንና በሬድዮ የሚሰጠውን አገልግሎት በማስፋፋት የሚያስተላልፋቸውን ዝግጅቶች በስልክ አማካይነት በካናዳ ለሚገኙ ምእመናን ማሠራጨት ጀመረ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማስፋፋት የኅትመትና የኤሌክትሮኒክስ መገናኛ ብዙሃንን በመጠቀም ምእመናን ስለእምነታቸውና ስለ ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲያውቁ፣ በሃይማኖት እንዲጸኑ መረጃ በመስጠትና በማስተማር ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህም በቴሌቪዥንና በሬድዮ የሚያሰራጫቸውን መርሐ ግብሮች በሰሜን አሜሪካ፣ በጀርመን እና በእንግሊዝ /UK/ በስልክ አማካይነት በማዳረስ ላይ ነው፡፡

ማኅበሩ በሰሜን አሜሪካ እና በአውሮፓ ብቻ ሳይወሰን ቁጥሩን ወደ ዐራት በማሳደግ በቴሌቪዥንና በሬድዮ የሚተላለፉት ዝግጅቶችን በቅርቡ በስልክ አማካይነት በካናዳ ማሠራጨቱን ቀጥሏል፡፡

በካናዳ የሚገኙ ምእመናን የስልክ አገልግሎቱን (604) 670 9698 በመደወል በቀላሉ ማግኘት እንደሚችሉም መረጃው ያመለክታል፡፡

የጥቅምት 2008 ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጸሎት ተጀመረ

ጥቅምት 11 ቀን 2008 ዓ.ም

sami.02.07በዓመት ሁለት ጊዜ የሚካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ጥቅምት 11 ቀን 2008 ዓ.ም ከቀኑ 10፡00 ሰዓት ጀምሮ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በጸሎት ተጀመረ፡፡

ምልዓተ ጉባኤው አስፈላጊና ወሳኝ በሆኑ ጉዳዮች ላይ በመወያየት ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጠቃሚ ውሳኔዎችን እንደሚያሳልፍ ይጠበቃል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቪዥንና የሬድዮ ሥርጭት በአውሮፓ በስልከ አገልግሎት መስጠት ጀመረ

መስከረም 4 ቀን 2008 ዓ.ም

01awropaማኅበረ ቅዱሳን በኢቢኤስ ቴሌቪዥን እንዲሁም በሬድዮ አያሰራጨ የሚገኘውን መንፈሳዊ መርሐ ግብር በአውሮፓም ምእመናን ባሉበት ሆነው በቀላሉ በስልክ ሥርጭቱን መከታተል እንዲችሉ ማድረጉን የአውሮፓ ማእከል አስታወቀ፡፡

በዚህም መሠረት በጀርመን የሚገኙ ምእመናን በ0699-432-98-11 ፣በእንግሊዝ /UK/ 033-032-63-60 በመደወል  መከታተል እንደሚችሉ ከማእከሉ የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

በሰሜን አሜሪካም በተመሳሳይ ሁኔታ የቴሌቪዥንና የስልክ አገልግሎት መጀመሩን መዘገባችን ይታወሳል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቪዥን እና የሬዲዮ ሥርጭት በስልክ የሚከታተሉበት አገልግሎት ተጀመረ

ነሐሴ 30 ቀን 2007 ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን እየተዘጋጀ በቴሌቪዥን እና በሬዲዮ የሚሰራጨው መርሐ ግብር በሰሜን አሜሪካ ለሚኖሩ ምእመናን በቀላሉ በተመቻቸው ጊዜ ስልክ ደውለው የሚከታተሉበት አገልግሎት ተጀመረ።

ምእመናን 605-475-8172 ስልክ ቁጥር በመጠቀም በተመቻቸው ጊዜ መርሐ ግብሩን መከታተል እንደሚችሉ በማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል አስታውቋል።

በአሁኑ ወቅት የስልክ አገልግሎቱ የሚሠራው በሰሜን አሜሪካ ለሚኖሩ ምእመናን ብቻ ሲሆን በቅርቡ በሌሎችም የዓለም ክፍሎች ተመሳሳይ አገልግሎት እንዲኖር ማኅበረ ቅዱሳን በመሥራት ላይ ይገኛል።

 

የማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቪዥን እና የሬዲዮ ሥርጭት በስልክ የሚከታተሉበት አገልግሎት ተጀመረ

ነሐሴ 30 ቀን 2007 ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን እየተዘጋጀ በቴሌቪዥን እና በሬዲዮ የሚሰራጨው መርሐ ግብር በሰሜን አሜሪካ ለሚኖሩ ምእመናን በቀላሉ በተመቻቸው ጊዜ ስልክ ደውለው የሚከታተሉበት አገልግሎት ተጀመረ።

ምእመናን 605-475-8172 ስልክ ቁጥር በመጠቀም በተመቻቸው ጊዜ መርሐ ግብሩን መከታተል እንደሚችሉ በማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል አስታውቋል።

በአሁኑ ወቅት የስልክ አገልግሎቱ የሚሠራው በሰሜን አሜሪካ ለሚኖሩ ምእመናን ብቻ ሲሆን በቅርቡ በሌሎችም የዓለም ክፍሎች ተመሳሳይ አገልግሎት እንዲኖር ማኅበረ ቅዱሳን በመሥራት ላይ ይገኛል::

የማኅበረ ቅዱሳን ንዋያተ ቅድሳት ማምረቻ ክፍል ቃጠሎ ደረሰበት

ነሐሴ 21 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

01 kateloበማኅበረ ቅዱሳን የልማት ተቋማት አስተዳደር የንዋያተ ቅድሳት ማምረቻ ክፍል ነሐሴ 18 ቀን 2007 ዓ.ም ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ጀምሮ ምክንያቱ ባልታወቀ ሁኔታ ቃጠሎ እንደደረሰበት የልማት ተቋማት አስተዳደር ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ኃይሉ ፍስሐ ገለጹ፡፡

መረጃው ከምሽቱ 1፡00 ሰዓት እንደደረሳቸው የገለጹት አቶ ኃይሉ በማምረቻ ክፍሉ ተከስቶ የነበረውን ቃጠሎ በአካባቢው ሕዝብና በአዲስ አበባ ከተማ አራዳ ወረዳ የእሳት አደጋ ማጥፊያና መቆጣጠሪያ ክፍል አባላት ርብርብ ወደ ሌሎች ክፍሎች ሳይዛመት በቁጥጥር ሥር እንዲውል መደረጉን ተናግረዋል፡፡

በቃጠሎው 12 የልብስ ስፌት ማሽኖች፤ 2 ዘመናዊ የኤሌክትሪክ ካውያዎች፤ 1 መዘምዘሚያ ማሽን፤ 1 ቁልፍ መትከያ ማሽን፤ በዝግጅት ላይ የነበሩና ያልተጠናቀቁ፤ ለስፌት የሚያገለግሉ የግሪክ ጨርቆች፤ የካህናት፤ የዘማርያንና የሰባኪያን አልባሳት፤ ለአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤት ተማሪዎች የተዘጋጁ አልባሳት፤ የግሪክ ጣቃ ጨርቆች፤ የማምረቻ ክፍሉ በሮች፤ መስኮቶችና ኮርኒስን ጨምሮ ሙሉ ለሙሉ ወድመዋል፡፡ ግምታቸውንም ለጊዜው ማወቅ እንዳልተቻለ ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡

02kateloበዕለቱ ቀኑን ሙሉ መብራት ጠፍቶ ስለነበር ምንም ዓይነት ሥራ አገልጋዮቹ እንዳለከናወኑ የገለጹት ዳይሬክተሩ ቃጠሎው የተከሰተው አገልጋዮቹ ከወጡ በኋላ በመሆኑ የአደጋው መንስኤ እሰካሁን አለመታወቁን ተናግረዋል፡፡ አደጋው የተከሰተበት ምክንያት ፖሊስ የቴክኒክ ምርመራ በማካሔድ ላይ ስለሚገኝ ምርመራው እንደተተናቀቀ የሚታወቅ ይሆናል ብለዋል፡፡

ወደፊት ጥንቃቄ የተሞላበት ሥራ ለማከናወን ጥረት እንደሚደረግ የገለጹት አቶ ኃይሉ ከኢንሹራንሽ ጋር በተያያዘም ወደፊት የሚሠሩ ሥራዎች እንደሚኖሩ ጠቁመዋል፡፡ በቃጠሎው ከፍተኛ ጉዳት ሳይደርስ በቁጥጥር ሥር እንዲውል ላደረጉ አካላት ለአራዳ ክፍለ ከተማ የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መቆጣጠሪያ ጣቢያ፣ ለአካባቢው ምእመናንና ፖሊስ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

በንዋያተ ቅዱሳት ማምረቻ ውስጥ የአልባሳት፤ የመባ /ዕጣን፤ ጧፍ፤ ዘቢብ/ ዝግጅት፤ የተማሪዎች አልባሳት፤ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚውሉና በእንጨት የሚዘጋጁ ንዋያተ ቅድሳት እንዲሁም የብረታ ብረት ሥራዎች ይሉ፡፡

የጥናት መድረክ

ሥነ ተዋልዶ ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ አንጻር 

01Tinat ena Miremer

የላይ ቤት የአቋቋም ደቀ መዛሙርት ተመረቁ

ሐምሌ 30 ቀን 2007 ዓ.ም

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ /ጎንደር ማእከል/

01 kehaበጎንደር ከተማ በደብረ ስብሐት ቀሐ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ሐምሌ 26 ቀን 2007 ዓ.ም 61 የላይ ቤት የአቋቋም ደቀ መዛሙርት ተመረቁ፡፡

የደብረ ስብሐት ቀሐ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ዋና አስተዳዳሪ መልአከ ስብሐት ቀሲስ ሞገስ አለሙ ለተመራቂ ደቀ መዛሙርት ባስተላለፉት መልእክት ልጄ ሆይ አደራህን ጠብቅ 2ኛ. ጢሞ.1፡-14 በሚል ኃይለ ቃል አባትክን መስለህ፣የአባቾችህን ጉባኤ ቤት ጠብቅ በማለት ተመራቂ ደቀ መዛሙርት በተማሩት ትምህርት ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲገለግሉ እና አደራቸውን መጠበቅ እንደሚገባቸው ገልጸዋል፡፡

መልአከ ስብሐት ቀጥለውም ቦታው ቀደምት ነው ነገር ግን ለእነዚህ የአብነት ተማሪዎች የምግብ፣የመጠለያ፣የአልባሳት ችግር እንዳለ ሆኖ በጋራ ሆነው የሚማሩበት የመማሪያ ቤት እንኳን የላቸውም፤ በመሆኑም ሁሉም አካል ይህ የላይ ቤት አቋቋም እንዳይጠፋ የበኩላችንን አስተዋጽኦ እናድርግ ብለዋል፡፡

ተመራቂ ደቀ መዛሙርቱም ከቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ከመልአከ ስብሐት ቀሲስ ሞገስ አለሙ መስቀል እና የምሥክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡

02kehaበምርቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ መምህር ዳንኤል ኃይሉ የደብረ ፀሐይ ቁስቋም ማርያም ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር ቅኔ፣ መሪጌታ ድረስ ቦለድ በቀሐ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን የድጓ መምህር ሰሎሞን ምቅናይ እና የድጓ ዜማ፤ የማኅበረ ቅዱሳን ጎንደር ማእከል የመዝሙር ክፍል አባላት እና የደብረ ስብሐት ቀሐ ኢየሱስ ሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎች ያሬዳዊ ወረብ አቅርበዋል፡፡

የደብረ ስብሐት ቀሐ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ከጎንደር ካሉት ቀዳሚ አድባራት የሚጠቀስ ሲሆን፤ በ1355 ዓ.ም የተተከለ ነው፡፡

የታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም መንፈሳዊ ት/ቤት ያሠለጠናቸውን ደቀመዛሙርት አስመረቀ

ሐምሌ 27 ቀን 2007 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

06temerakiየዳግማዊ ምኒልክ መታሰቢያ ታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም የመምህራንና ቀሳውስት ማሠልጠኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ያሠለጠናቸውን ደቀመዛሙርት ሐምሌ 25 ቀን 2007 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ አስመረቀ፡፡

27 ደቀመዛሙርት በአብነት ትምህርት በዲፕሎማ የተመረቁ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ በብሉይ ኪዳን 5፤ በሐዲስ ኪዳን 8፤ በድጓ 1፤ በቅኔ 1፤ በቅዳሴ 11፤ በአቋቋም 1 የተመረቁ ናቸው፡፡ 10 በመደበኛ /በአዳሪነት/፤ ቀሪዎቹ 17 ደቀመዛሙርት ደግሞ በማታው የትምህርት ክፍለ ጊዜ ትምህርታቸውን የተከታተሉ ናቸው፡፡ ከአብነት ትምህርት በተጨማሪ በሥነ መለኮት ትምህርት ቅዳሜ እና እሁድ ትምህርታቸውን የተከታተሉ 38 ደቀመዛሙርትም በሠርተፊኬት ተመርቀዋል፡፡

02temerakiበጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ በተከናወነው የምረቃ መርሐ ግብር ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የገዳሙ የበላይ ሓላፊዎች፤ የገዳሙ ሊቃውንት እና ደቀመዛሙርቱ በተገኙበት ቅዱስነታቸው በዲፕሎማ እና በሠርተፊኬት ለተመረቁ ደቀመዛሙርት የምሥክር ወረቀት ሰጥተዋል፡፡

ቅዱስነታቸው ለተመራቂ ደቀመዛሙርት የምሥክር ወረቀት ከሰጡ በኋላ ባስተላለፉት አባታዊ መመሪያ “ቤተ ክርስቲያናችን ጥንታዊት፤ ታሪካዊት እንደመሆኗ መጠን ሀገራችን ሰፊ፤ ሕዝባችንም ብዙ ነው፡፡ ስለዚህ በተማራችሁት ትምህርት መሠረት በሕዝበ ክርስቲያኑ ዘንድ ያለውን የትምህርት ጥም የምትቀርፉ ባለአደራዎች ናችሁ፡፡ አደራዋን ጠብቃችሁ የጎደለውን አሟልታችሁ፤ የጠፉትን መልሳችሁ፤ ያሉትንም አጽንታችሁ ቸግሩን እንድታስወግዱ ያስፈልጋል€ ብለዋል፡፡

የዳግማዊ ምኒልክ መታሰቢያ ታዕካ ነገሥት በአታ ለማርያም ገዳም የመምህራንና ቀሳውስት ማሠልጠኛ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት በ1925 ዓ.ም የተመሠረተ ሲሆን፤ 82 ዓመታትን አስቆጥሯል፤ በእነዚህ ዓመታትም በርካታ ደቀመዛሙርትን አፍርቷል፡፡ በአሁኑ ወቅት 300 ደቀመዛሙርት ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ሲሆኑ ከእነዚህ ውስጥ ልብስና ቀለብ እየተሰጣቸው በመደበኛነት/አዳሪነት/ በመማር ላይ ያሉ 70 ደቀመዛሙርት ብቻ ናቸው፡፡ ከ70ዎቹ መደበኛ ደቀመዛሙርት መካከልም ሦስቱ መነኮሳይያት እናቶች እንደሆኑ በቀረበው ሪፖርት ላይ ተገልጿል፡፡

05temerakiበዚሁ የምረቃ መርሐ ግብር ላይ ገዳሙን በታማኝነት እና በቅንነት ለ50 ዓመታት ያገለገሉት የእድሜ ባለጸጋው አባት መጋቤ ሀብታት አባ እስጢፋኖስ ወልደ ኢየሱስ ከገዳሙ የተበረከተላቸውን ካባና የምሥክር ወረቀት ከቅዱስ ፓትርያርኩ እጅ ተቀብለዋል፡፡