መንፈሳውያን በዓላት እና አሉታዊ አስተሳሰቦች – ክፍል አንድ

ketera1

በዳዊት አብርሃም

የካቲት ፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዓል ‹‹አብዐለ-  አከበረ፤ አስከበረ›› ከሚለው ግስ የወጣ ሲኾን ትርጕሙም የደስታ፣ የዕረፍት ቀን፤ ያለፈ ነገር የሚታሰብበት፤ ሕዝብ የበዓሉን ምሥጢር እያሰበ ደስ ብሎት፣ ለብሶ፣ አጊጦ የሚዘምርበት፤ ዕልል የሚልበት ማለት ነው (ኪ.ወ.ክ. ገጽ ፪፸፰-፪፸፱)፡፡ ከዚህ መዝገበ ቃላዊ ፍቺ በርከት ያሉ ጽንሰ ሐሳባዊ ትርጕሞችን የምናገኝ ሲኾን የተወሰነቱን እንደሚከተለው እንመልከት፤

በዓላት የሚከበሩ ናቸው

በዓላት ምእመናን ከዘወትር ሥራዎቻቸው አርፈው በምትኩ መንፈሳዊ ተግባራትን በማከናወን የሚያከብሯቸው ናቸው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ስለ በዓላት አከባበር በተሠራው ቀኖና በበዓላት ወቅት የማይፈጸም መንፈሳዊ ሥራ ስግደት ነው፡፡ ስግደት ሥጋን የሚያደክም ስለኾነ በበዓላት ወቅት አይሰገድም፡፡ ሌሎች መንፈሳዊ ሥራዎች ግን በበዓላት እንዲፈጸሙ ይፈቀዳል፡፡ ተግባረ ሥጋን በበዓላት መተው አስፈላጊ የሚኾንበት ምክንያት መንፈሳዊ ሥራ ለመሥራት እንዲቻል ነው፡፡

በዓላት የደስታ ዕለታት ናቸው

‹‹በዓል የሚያደርጉ ሰዎች የደስታና የምስጋና ቃል አሰሙ›› (መዝ.፵፩፥፭) እንደ ተባለው፤ በዓል የሚያዝኑበት፣ የሚያለቅሱበት፣ ከምግብ የሚከለከሉበት ወይም የሚጾሙበት ዕለት ሳይኾን ደስ የሚሰኙበት፣ በደስታ ውስጥም ኾነው እግዚአብሔርን የሚያመሰግኑበት ቀን ነው፡፡ ሐዋርያው ያዕቆብ ‹‹ደስ ያለው ይዘምር›› (ያዕ. ፭፥፲፬) እንዳለው የደስታ ቀን በኾነው በበዓል ስብሐተ እግዚአብሔር በስፋት ይቀርባል፡፡

በዓላት የዕረፍት ቀናት ናቸው

ሌሎች ቀናት የሥራ ቀናት ናቸው፡፡ በዓላት ግን ከእነዚህ ከብዙዎቹ ቀናት ተለይተው ሰው ከሥራው (ከተግባረ ሥጋው) የሚያርፍባቸው ዕለታት ናቸው፡፡ የበዓላት ጥንት የኾነችው ቀዳሚት ሰንበት እግዚአብሔር ሥነ ፍጥረትን ፈጥሮ ያረፈባት በመኾኑ እግዚአብሔር ሰዎች እንዲያርፉባት፤ በዕረፍትም ኾነው እንዲያከብሯት አዝዟል (ዘፍ. ፪፥፩-፫)፡፡ ኾኖም ማረፍ ማለት እጅና እግርን አጣጥፎ መዋል ማለት አይደለም፡፡ በዓላት ከተግባረ ሥጋ የሚታረፍባቸው ዕለታት ቢኾኑም በበዓላት ወቅት መንፈሳዊ ሥራ መሥራት ተገቢና አስፈላጊ መኾኑ ‹‹ክርስቲያኖች እንደ አይሁድ በዕለተ ቀዳሚት ሥራ ፈትተው መዋል አይገባቸውም፡፡ ይልቁንም ለክርስቲያን እንደሚገባ ሥራ ሊሠሩ ይገባቸዋል፤›› ተብሎ በፍትሐ ነገሥት ታዝዟል፡፡

በዓላት የመታሰቢያ ዕለታት ናቸው

እግዚአብሔር አምላክ አስቀድሞ ከሥራው ያረፈባትን የሰንበት ዕለት እንድናስባት አዝዞናል፡፡ ተአምራት ያደረገባቸውን፣ እስራኤል ዘሥጋን በግብጽ ባርነት ነጻ ያወጣበትንና የመሳሰሉትን ዅሉ በበዓላት እንዲታሰቡ አዝዟል (መዝ. ፻፲፥፬)፡፡ በሐዲስ ኪዳንም ‹‹ይህን ለመታሰቢያዬ አድርጉት›› በማለት አዝዟል (ሉቃ. ፳፪፥፱)፡፡ የፈጣሪን ሥራም ብቻ ሳይኾን ቅዱሳን ጻድቃንንና ሥራዎቻቸውን መዘከር የበዓላት አንዱ ገጽታ ነው፡፡ ‹‹የጻድቅ መታሰቢያ ለዘላለም ይኖራል›› ተብሎ መጻፉም ስለዚህ ነው (መዝ. ፻፲፯፥፳፬)፡፡

የበዓላት አከባበር

በዓላት በልዩ ልዩ መንገዶች ይከበራሉ፡፡ በበዓላት የሚከናወኑ መንፈሳዊና ሕዝባዊ ክንዋኔዎች አሉ፡፡ የተወሰኑ በዓላትን ሕዝብ ወደ ዐደባባይ በመውጣት በጋራ ያከብራቸዋል፡፡ አከባበሩም በዋናነት በጋራ ኾኖ የሚፈጸመውን ሥርዓተ አምልኮና የምስጋና ሥርዓት የሚያመለክት ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን እስራኤል ዘሥጋ በዓላትን ሊያከብሩ ወደ ዐደባባይ ሲወጡ ይዘምሩ ነበር፡፡ ይዘምሩዋቸው ከነበሩ ዝማሬያት መካከልም በመዝሙረ ዳዊት ከመዝሙር ፻፲፱ እስከ ፻፴፫ ያሉት የመዝሙር ክፍሎች ይገኙባዋል (የመጽሐፍ ቅዱስ መዝገበ ቃላት ገጽ ፴፩)፡፡ ክቡር ዳዊትም በታቦቱ ፊት በቤተ መቅደስ ምስጋና የሚያቀርቡ ካህናትን መድቦ ነበር (፩ኛ ዜ.መ. ፲፮፥፬)፡፡

በአገራችን ኢትዮጵያ በዐደባባይ ከሚከበሩ በዓላት መካከል ቤተ ክርስቲያን የምታውቃቸው ሁለት ዋና ዋና በዓላት የሚገኙ ሲኾን እነዚህም በዓለ መስቀልና በዓለ ጥምቀት ናቸው፡፡ ከዐደባባይ በዓላት መካከል በዓለ መስቀል በዩኔስኮ ከማይዳሰሱ የዓለም ቅርሶች ተርታ ለመመዝገብ የበቃ ታላቅ በዓል ሲኾን ጥምቀትም በዐደባባይ በዓልነቱ ከአማንያኑ በተጨማሪ የብዙዎችን በተለይም የውጪ ቱሪስቶችን በመሳብ ተወዳዳሪ የሌለው ታላቅ በዓል ነው፡፡ ከወር በፊት በድምቀት ያከበርነው በዓለ ጥምቀት ቤተ ክርስቲያናችን ታቦታትን በማውጣት የምታከብረው ዐቢይ በዓል ነው፡፡ ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው የሦስት ዓመት ከሦስት ወር የማስተማር ሥራውን የጀመረው በጥምቀት ነው፡፡ በየዓመቱ የጥምቀት በዓል የሚከበረውም ይህን ምሥጢር ለመዘከርና ለመመስከር ነው፡፡

ጌታችን ያሳየውን ትሕትና እና ለእኛ አርአያ መኾኑን ለመመስከር፣ ለጥምቀት ኀይልን ለመስጠት እንደዚሁም ውኃን ለመቀደስ ቤተ ክርስቲያን በዓለ ጥምቀቱን በየዓመቱ ታከብራለች፡፡ በየዓመቱ ውኃ ዳር ሔዶ ማክበር በየዓመቱ መጠመቅ ተብሎ እንዳይተረጐምና ሰዎችን እንዳያሳስትም ታስተምራለች፡፡ ይህንኑ ትምህርት ለማስገንዘብም ‹‹የጠበሉን መረጨት አይተው በቀድሞ ዘመን ወደ አገራችን መጥተው የነበሩ ኢየሱሳውያን፣ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ታጠምቃለች ብለው አጥላልተው ጽፈዋል፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ይህን የምትፈጽመው ጌታችን ለኛ ብሎ ያሳየውን ትሕትና ለመመስከር፣ የጌታን በረከተ ጥምቀት ለምእመናን ለማሳተፍ እንጂ የተጠመቁትን ምእመናን እየደመለሰች በየዓመቱ አታጠምቅም፤›› ሲሉ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ ጽፈዋል (የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ታሪክ ገጽ ፻፳፫)፡፡

የጥምቀት በዓል አከባበር ሥርዓት ከሌሎቹ በዓላት የተለየ ነው፡፡ ታቦታቱ ከመንበረ ክብራቸው ወጥተው በበዓሉ ዋዜማ በሕዝብ ታጅበው ወደ ወንዝ ዳር ይወርዳሉ፡፡ በዚያ ዳስ ተጥሎ፣ ከተራም ተከትሮ ሌሊቱን መዘምራኑ በማኅሌት ካህናቱ በሰዓታት እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ ያድራሉ፡፡ ይህም ጌታ ከገሊላ ወደ ዮርዳኖስ የመሔዱ ምሳሌ ነው፡፡ ሲነጋም ጸሎተ ቅዳሴው ተጠናቅቆ ወደ ወንዙ በመሔድ ጸሎተ አኮቴት ተደርሶ፣ ዐራቱ ወንጌላት ከተነበቡ በኋላ ውኃው ተባርኮ ለተሰበሰበው ሕዝብ ይረጫል፣ ወንዝም ሲሆን ሰዎች እየገቡ ሊጠመቁ ይችላሉ፡፡ በግብጽ ቤተ ክርስቲያንም፣ ከ6ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በፊት ዓባይ ወንዝ ወርደው በድምቀት ያከብሩት ነበር፡፡ ከዐረቦች መግባት በኋላ ግን ከሊፋዎቹ (ሡልጣኖቹ) ስለከለከሏቸው በቤተ ክርስቲያን ብቻ ለማክበር ተገድደዋል (The Coptic encyclopedia P.1103)፡፡

ከበዓለ መስቀል እና በዓለ ጥምቀት በተጨማሪ ‹‹አሸንዳ›› (‹‹አሸንድዬ››) በመባል የሚታወቀውና በሰሜን ኢትዮጵያ የሚከበረው የዐደባባይ በዓልም ሙሉ በሙሉ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የሚከናወን በዓል ባይኾንም ሕዝቡ በአለባበሱ፣ በአዘማመሩና በሚያደርጋቸው ሌሎች ክዋኔዎች በዓሉ እንደ ሌሎች ሕዝባዊ ባህሎች አረማዊ ወግን ያልተከተለ መኾኑን የሚያመለክቱ ናቸው፡፡

የበዓላት ፋይዳ

በዓላት በቀዳሚነት የሚከበሩት መንፈሳዊ ዓላማ ይዘው ነው፡፡ ኾኖም በዓላት በሕዝብ የሚከበሩ እንደ መኾናቸው ሌሎች ጥቅሞችም አሏቸው፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ሰው መሥራት ብቻ ሳይኾን ማረፍም አለበትና በዓላት ለማረፍና ለመዝናናት ጠቀሜታ አላቸው፡፡ በዅሉም ሀገራት ያሉ ሃይማኖታዊ በዓላት ግብይትን በማሳለጥና የገንዘብ ዝውውርን በማፋጠን ለአገር ኢኮኖሚ ማደግ አስተዋጽኦ እንዳላቸው የመስኩ ባለሙያዎች ያስረዳሉ፡፡ ሌላው የበዓላት ጥቅም ደግሞ ማኅበራዊ ግንኙነትን ማዳበር ነው፡፡ በበዓላት ሰዎች ይገናኛሉ፤ ስጦታዎችን ይለዋወጣሉ፤ ይገባበዛሉ፡፡ በዚህም ማኅበራዊ ግንኙነታቸውን ያዳብራሉ፡፡ በበዓላት ወቅት ችግረኞች ርዳታ ያገኛሉ፡፡

ከዚህም በላይ በዓላት ለባህል ግንባታ ለመልካም ዕሴት መፈጠር ምክንያት ኾነው ሊያገለግሉ ይችላሉ፡፡ በዓላት የቱሪስት መስሕቦችም ናቸው፡፡ እንደ በዓለ መስቀል በዓለም አቀፍ ደረጃ ዕውቅና ያገኙ፣ እንደ ጥምቀት ብዙ ሕዝብን የሚያሳትፉ በዓላት የአገር ውስጥ ቱሪዝምን ከመፍጠራቸውም ባሻገር የውጪ አገር ሰዎች ብዙ ኪሎ ሜትሮችን አቋርጠው መጥተው እንዲጐበኙ ዕድል ይፈጥራሉ፡፡ በዚህም አገር የውጪ ምንዛሪ ታገኛለች፡፡ ከዅሉም በላይ በዓላት የአገርን ገጽታ ይገነባሉ፡፡ በተለይ ኢትዮጵያን በመሰለች ስሟ በድርቅና በረኀብ ለምትነሣ አገር በዓላት መጥፎ ገጽታንና ክፉ ስምን የሚቀይሩ ፍቱን መድኀኒቶች ናቸው፡፡

ስለ በዓላት አሉታዊ አስተሳሰቦች

የቤተ ክርስቲያን በዓላት የተጠቀሱትና ሌሎች ያልተጠቀሱ በርካታ ጥቅሞች እንዳሏቸው የታወቀ ቢኾንም አንዳንድ ወገኖች ግን በማወቅም ይኹን ባለማወቅ በዓላትን የሚዘልፉና የሚያንቋሽሹ ወይም የበዓላቱን ዓላማ የሚቃረኑ ሐሳቦችን ያዛምታሉ፡፡ በዚህ ጽሑፍ ከእነዚህ የተቃርኖ ሐሳቦች መካከል ጥቂቶቹን በመጥቀስና የሐሳቦቹን ድክመት በማሳየት ምላሽ እንሰጥባቸዋለን፤

ይቆየን

ክብረ በዓላት በመጽሐፍ ቅዱስ

timket

በዲያቆን ዘአማኑኤል አንተነህ

የካቲት ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በዓል ማለት ‹‹አብዐለ – አከበረ›› ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጕሙም ‹‹መታሰቢያ ማድረግ፣ ማክበር›› ማለት ነው፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም በመዝገበ ቃላታቸው ‹‹በዓል (ላት) በቁሙ፣ የደስታ፣ የዕረፍት ቀን፤ በዓመት፣ በወር፣ በሳምንት የሚከበር፤ ያለፈ ነገር የሚታሰብበት፤ ሕዝብ የበዓሉን ምሥጢር እያሰበ ደስ ብሎት እና ለብሶ፣ አጊጦ የሚዘፍንበት የሚዘምርበት፤ ዕልል የሚልበት፤ ሽብሸባ፣ ጭብጨባ የሚያደርግበት፤ ሲያረግድ እስክስታ ሲወርድ ባንገቱ የሚቀጭበት እንደ ጥጃ የሚፈነጭበት ነው›› በማለት የበዓልን ትርጕም ገልጸውታል፡፡ በአጠቃላይ በዓል ማለት ማሰብ፣ መዘከር፣ ማስታወስ የሚል ትርጕም አለው፡፡

የበዓላት ዑደት

እግዚአብሔር አምላካችን ‹‹ይህም ቀን መታሰቢያ ይኹናችሁ፤ ለእግዚአብሔርም በዓል ታደርጉታላችሁ፡፡ ለልጅ ልጃችሁ ሥርዓት ኾኖ ለዘለዓለም ታደርጉታላችሁ፤›› በማለት በዓል ዘለዓለማዊ መታሰቢያ እንደ ኾነ ተናግሯል /ዘፀ.፲፪፥፲፬-፲፯፤ ዘሌ.፳፫፥፪-፬/፡፡ ስለዚህም በዓላት በዓመታት፣ በወራት እና በሳምንታት ዑደት እየተመላለሱ ይከበራሉ፡፡ በየዓመቱ ከምናከብራቸው መንፈሳውያን በዓላት መካከል በዓለ ልደት፣ በዓለ ጥምቀት፣ በዓለ ትንሣኤ ይጠቀሳሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በየዓመቱ የልደት በዓልን የምታከብረው ክርስቶስ በየዓመቱ የሚወለድ ኾኖ አይደለም፤ የልደቱን መታሰቢያ ለማሰብ ነው እንጂ፡፡ ጥምቀትን ስታከብርም የወንጌልን አስተምህሮ ተከትላ፣ ምሥጢር አስተካክላ፣ ወቅቱን ‹‹ዘመነ አስተርእዮ›› ብላ ሰይማ የክርስቶስን መገለጥ በማስተማር በዓሉን ታስበዋለች፡፡ የጥምቀት በዓልን እኛ ምእመናን ስናከብርም ዅልጊዜ እንጠመቃለን ማለት አይደለም፤ በዓሉን የምናከብረው ክርስቶስ መጠመቁን ለመዘከር፤ ከበረከቱም ለመሳተፍ ነው፡፡ በዓለ ትንሣኤን የምናከብረውም የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ በማሰብ፣ የእኛንም ትንሣኤ ተስፋ በማድረግ ነው እንጂ ጌታችን በየዓመቱ ከሙታን ይነሣል በማለት አይደለም፡፡ ሌሎችን በዓላትም እንደዚሁ፡፡

በዓላትን በማክበራችን ምን ጥቅም እናገኛለን?

፩. በረከት

‹‹አምላክህ እግዚአብሔር በፍሬህ ዅሉ በእጅህም ሥራ ዅሉ ይባርክሃልና እግዚአብሔር በመረጠው ስፍራ ለአምላክህ ለእግዚአብሔር ሰባት ቀን በዓል ታደርጋለህ፤ አንተም ፈጽሞ ደስ ይልሃል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ዘዳ.፲፮፥፲፭/ በዓል ማክበር በረከትን ያሰጣል፡፡

፪. ፍጹም ደስታ

በዓል ስናከብር መንፈሳዊ ደስታ ይሰማናል፡፡ በበዓላት ወቅት እርስበርስ በመጠራራት ቤተሰብ ከሩቅም ከቅርብም ይሰባሰባል፤ ዕለቱ የደስታ ቀን ነውና፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ሙሴም ‹‹አንተም፣ ወንድ ልጅህና ሴት ልጅህ፣ ወንድ ባሪያህ እና ሴት ባሪያህ፣ በአገርህም ደጅ ውስጥ ያለ ሌዋዊ እና መጻተኛ፣ ድሃ አደግ እና መበለትም በበዓል ደስ ይበላችሁ፤›› በማለት በበዓል ቀን በዓሉን በማክበር መደሰት እንደሚገባ ይናገራል /ዘዳ.፲፮፥፲፬/፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትም በመዝሙሩ ‹‹በዓል የሚያደርጉ ሰዎች የደስታ እና የምስጋና ቃል አሰሙ፤›› ይላል /መዝ.፵፪፥፬/፡፡ ነቢዩ ዕዝራ ደግሞ ‹‹እግዚአብሔር ደስ አሰኝቷቸዋልና የቂጣውን በዓል ሰባት ቀን በደስታ አደረጉ፤›› ሲል የእስራኤላውያንን በበዓል ቀን መደሰት አስረድቶናል /ዕዝ.፮፥፳፪፤ ፪ኛ ዜና መዋዕል ፴፥፳፫-፳፭/፡፡ በአገራችን አባባልም ‹‹አብሮ የበላን ቅዱስ ዮሐንስ አይሽረውም›› እንደሚባለው በዓመት በዓል ሕዝበ ክርስቲያኑ እርስበርስ እየተጠራራ አብሮ በመብላት በመጠጣት ይጫወታል፤ ይደሰታል፡፡

የበዓላት ክብር እኩል ነውን?

በዓላት በክብር ይለያያሉ፤ ለምሳሌ የእመቤታችን በዓል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየወሩ በ፳፩ ቀን ይከበራል፡፡ መስከረም ፳፩፣ ኅዳር ፳፩፣ እና ጥር ፳፩ ቀን ደግሞ የእመቤታችን ዐበይት በዓላት ናቸው፡፡ እንደዚሁም የቅዱስ ሚካኤል በዓል ወር በገባ በ፲፪ኛው ቀን ይከበራል፡፡ ኾኖም ግን የቅዱስ ሚካኤል ዐቢይ በዓል የሚከበረው በየዓመቱ በኅዳር ፲፪ እና ሰኔ ፲፪ ቀን ነው፡፡ የቅዱስ ገብርኤል ደግሞ በየወሩ በ፲፱ ቀን በዓሉ ቢታሰብም ታኅሣሥ እና ሐምሌ ፲፱ ቀን ዐቢይ በዓሉ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በወር ውስጥ የሚገኙትን እያንዳንዱን ቀናት በቅዱሳን ስም ብትሰይምም በዓላትን በዐቢይነትና ታቦታትን በማውጣት የምታከብራቸው በዓመት አንድ ወይም ሁለት ጊዜ ነው፡፡ ከዚህ ሥርዓትም በዓላት በአከባር የተለያዩ መኾቸውንና ልዩ የበዓል ቀኖችም እንዳሉ እንረዳለን፡፡ በመጽሐፈ ዜና መዋዕል ካልዕ ምዕራፍ ፴፥፳፮ ላይ ‹‹በኢየሩሳሌም ታላቅ ደስታ ኾነ፤ ከእስራኤል ንጉሥ ከዳዊት ልጅ ከሰሎሞን ዘመን ጀምሮ እንደዚህ ያለ በዓል በኢየሩሳሌም አልተደረገም ነበር፤›› ተብሎ የተጻፈው ኃይለ ቃል ለዚህ ማረጋገጫችን ነው፡፡

በዓላትን አለማክበር ምንን ያመጣል?

፩. ረድኤተ እግዚአብሔርን ያርቃል

በሰቆቃወ ኤርምያስ ምዕራፍ ፩፥፬ ላይ ‹‹ዳሌጥ፣ ወደ ዓመት በዓልም የሚመጣ የለምና የጽዮን መንገዶች አለቀሱ፡፡ በሮችዋ ዅሉ ፈርሰዋል፡፡ ካህናቶችዋም እየጮኹ ያለቅሳሉ፤ ደናግሎችዋም ተጨነቁ፡፡ እርስዋም በምሬት አለች፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ በዓላትን በማክበራችን ከእግዚአብሔር በረከትን እንደምንቀበል ዅሉ ባለማክበራችን ደግሞ ረድኤተ እግዚአብሔር ከእኛ ይርቃል፡፡

፪. ቅጣትን ያስከትላል

በመጽሐፈ ሳሙኤል ካልዕ እንደ ተገለጸው የእግዚአብሔር ታቦት ወደ ዳዊት ከተማ በገባ ጊዜ ነቢዩ ዳዊት በደስታ ምስጋና ያቀርብ ነበር፡፡ ሚስቱ ሜልኮል ግን ሲዘምር ባየችው ጊዜ ንጉሥ ኾኖ ሳለ ራሱን አዋረደ በሚል ሐሳብ ባለቤቷ ንጉሥ ዳዊትን ናቀችው፡፡ ዳዊትም ሜልኮልን ‹‹በእግዚአብሔር ፊት ዘፍኛለሁ፤ በእግዚአብሔር ሕዝብ በእስራኤል ላይ አለቃ እኾን ዘንድ ከአባትሽ እና ከቤቱ ዅሉ ይልቅ የመረጠኝ እግዚአብሔር የተባረከ ይኹን፡፡ ስለዚህም በእግዚአብሔር ፊት እዘምራለሁ፤›› በማለት ለእግዚአብሔር ምስጋና ማቅረብ እንደሚያስከብርና ከፍ ከፍ እንደሚደርግ ተናግሯል፡፡ እግዚአብሔርም ለአምላኩ የዘመረውን ዳዊትን በመናቋ ልጅ እንዳትወልድ የሜልኮልን ማኅፀን ዘግቶታል /፪ኛ ሳሙ. ፮፥፲፮-፳፫/፡፡ ከዚህ ታሪክ በዓሉን ብቻ ሳይኾን በዓሉን የሚያከብሩ ሰዎችንም ማክበር እንደሚገባን እንማራለን፡፡ ‹‹ዕልልታን የሚያውቅ ሕዝብ ምስጉን ነው፤›› እንዳለ ቅዱስ ዳዊት /መዝ.፹፱፥፲፭/፡፡

በክብረ በዓላት ምን ዓይነት ልብስ መልበስ አለብን?

ሰው ወደ ሰርግ ሲጠራ ከቤቱ ያለውን፣ የተሻለውን ልብስ መርጦ እንዲለብስ መንፈሳውያን በዓላት የቤተ ክርስቲያን የክብሯ መግለጫ ቀናት እንደ መኾናቸው መጠን እኛ ክርስቲያኖችም በእነዚህ ቀናት የምንለብሰው ልብስ የተለየ መኾን ይገባዋል፡፡ የሌሊት ልብስ ለብሶ ወደ ቤተ ክርስቲያን መሔድ እንደማይገባ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡ በገዳማውያን አባቶች ዘንድ ለቅዱስ ቍርባን መቀበያ የሚኾን ልብስ ከሌሎች አልባሳት ተለይቶ ውኀ፣ ጭስ፣ አቧራ ከማይደርስበት ቦታ ይቀመጣል፡፡ አባቶች ይህንን ልብስ የሚለብሱት ለቅዱስ ቍርባን ብቻ ነው፡፡ በገጠሩ የአገራችን ክፍልም ልጆች ልብስ የሚገዛላቸው በአብዛኛው በጥምቀት ወቅት ነው፡፡ ይህም ለበዓሉ የሚሰጠውን ልዩ ክብር ያስረዳናል፡፡ እናቶቻችንም ‹‹ለጥምቀት ያልኾነ ቀሚስ ይበጣጠስ›› እያሉ በበዓለ ጥምቀት ያላቸውን አዲስ ቀሚስ አውጥተው ይለብሳሉ፡፡

በዓመት በዓል ቀን እንስሳት የሚታረዱት ለምንድን ነው?

በዓል ሲደርስ ገበያው ይደምቃል፤ ቤታችን ያምርበታል፡፡ እንበላቸው ዘንድ የተፈቀዱ እንስሳት ይታረዳሉ፡፡ በተለይም በገጠሩ የሀገራችን ክፍል ለፋሲካ፣ ለልደት እየተባለ በግ ተቀጥቅጦ  ይቀመጥና ጊዜው ሲደርስ ይታረዳል፡፡ በበዓላት ቀን የከብት፣ የበግ፣ የፍየል መሥዋዕት ይቀርብ እንደ ነበር መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳል፡፡ መጽሐፈ ዕዝራ ፫፥፬ ‹‹እንደ ተጻፈውም የዳስ በዓል አደረጉ፤ እንደ ሥርዓቱም ለዕለቱ የተገባውን የየዕለቱን የሚቃጠል መሥዋዕት በቍጥር አቀረቡ፤›› ይላል፡፡ ዛሬም በበዓላት ቀን በየቤተ ክርስቲያኑ እና በየቤቱ የሚታረደው ይህንኑ አብነት በማድረግ ነው፡፡ (በተጨማሪም ዘሌ.፳፫፥፴፯፤ ሕዝ.፵፮፥፲፩ ይመልከቱ)፡፡

በአጠቃላይ በዓላትን ከሥጋዊ ሥራ ተከልክሎ ማክበር እንደሚገባ ቅዱሳት መጻሕፍት ይናገራሉ፡፡ ‹‹በመጀመሪያው ቀን የተቀደሰ ጉባኤ ይኹንላችሁ፤ የተግባር ሥራ ዅሉ አትሥሩበት፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ /ዘሌ.፳፫፥፯/፡፡ የበዓላት አከባበርም እንደ እንግዳ ደራሽ እንደ ውኃ ፈሳሽ በኾነ ባህል ሳይኾን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በጠበቀ፤ የበዓሉን መንፈሳዊ ታሪክ በተመረኮዘ መንገድ የተሰጠን ትእዛዝ ነው፡፡ ዮሴፍ ወልደ ኮሪዮን በዜና አይሁድ መጽሐፉ እንደ ጠቀሰው አይሁድ በዕለተ ሰንበት ወደ መጸዳጃ ቤት እንኳን አይሔዱም ነበር፡፡ እኛ ግን እንደ አይሁዳውያን በተጋነነ መንገድ ሳይኾን ሰውነትን ከሚያደክም ሥጋዊ ሥራ ተከልክለን በዓላትን እንድናከብር በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡

አገራችን ኢትዮጵያ አስቀድማ በሕገ ልቦና እግዚአብሔርን ስታመልክ የኖረች በኋላም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕፀ መስቀሉ የቀደሳት፣ በኪደተ እግሩ የባረካት አገር ናት፡፡ ኢትዮጵያውያን ምእመናን ከጥንት ጊዜ ጀምሮ መጽሐፍ ቅዱስን መሠረት አድርገው መንፈሳውያን በዓላትን በሥርዓት ሲያከብሩ ኖረዋል፡፡ አሁን አሁን ግን በብዙዎቻችን ዘንድ እንደሚስተዋለው የበዓላት አከባበር ሥርዓት እየተጣሰ ይገኛል፡፡ በበዓላት ቀን ሥራ መሥራት እየተለመደ መጥቷል፡፡ ይህ ልማድ ሊስተካከልና ሊቀረፍ ይገባል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም እንደ በዓለ ጥምቀት ባሉ የዐደባባይ በዓላት ወቅት የሚታየው የሥጋዊ ገበያ ግርግር ክርስቲያናዊ የበዓላት አከባበር ሥርዓትን እንዳያጠፋብን ልንጠነቀቅ ያስፈልጋል፡፡

በአገራችን ብሂል ‹‹በዓል ሽሮ የከበረ፣ ጦም ገድፎ የወፈረ የለም›› እንደሚባለው በዓላትን መሻር ከሚሰጠው ትርፍ ይልቅ የሚያመጣው መቅሠፍት ይብሳልና በዓላትን ለሥጋዊ ጉዳይ መጠቀሚያ ከማድረግ ይልቅ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን መሠረት አድርገን በአግባቡ ማክበር ይገባናል፡፡ አንድ ክርስቲያን መንፈሳውያን በዓላትን በሥርዓት ሲያከብር የሚመለከቱ አካላት ‹‹ሃይማኖቱ እንዴት ደስ ይላል? እኛም እንደ እርሱ በኾንን›› በማለት እርሱንም ሃይማኖቱንም ያደንቃሉ፤ መንፈሳዊ ቅናትንም ይቀናሉ፡፡ ስለዚህም የጥንቱን ሥርዓት ጠንቅቀን፣ መልኩን ሳንለውጥ፣ ሥርዓቱንም ሳናፋልስ በዓላትን ማክበር ይገባናል፡፡ በዓላትን በሥርዓቱ አክብረን በረከትን እናገኝባቸው ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ኢትዮ አሜሪካውያን ሕፃናት መዓርገ ዲቁና ተቀበሉ

usa

ጥር ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን ሰሜን አሜሪካ ማእከል ዋሺንግተን ስቴት በአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል ለመዓርገ ዲቁና የሚያበቃ የአብነት ትምህርታቸውን ለሁለት ዓመታት ሲከታተሉ የቆዩ ኢትዮ አሜሪካውያን ሕፃናት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዋሺንግተን እና ካሊፎርኒያ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከብፁዕ አቡነ ፋኑኤል መዓርገ ዲቁና ተቀበሉ፡፡

ሕፃናቱ መዓርገ ዲቁና የተቀበሉት በዓለ ጥምቀት በሲያትል ከተማ በተከበረበት ጥር ፲፬ ቀን እና የእመቤታችን በዓለ ዕረፍት በሲያትል ደብረ ሰላም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በተዘከረበት ጥር ፳፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ነው፡፡

ዲያቆናት

ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል ከዲያቆናቱ ጋር

በተያያዘ ዜና ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል በማኅበረ ቅዱሳን አሜሪካ ማእከል ከሲያትል ንዑስ ማእከል በቀረበላቸው ጥሪ መሠረት የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ማሠልጠኛ ማእከል ባትል ከተማ ቅርንጫፍ ትምህርት ቤትን ጐብኝተዋል፡፡ ለተመራቂ ተማሪዎችም የአንገት መስቀል አበርክተውላቸዋል፡፡

በዕለቱ የአካባቢው ማኅበረ ካህናትና የተማሪዎቹ ወላጆች ለብፁዕነታቸው ደማቅ አቀባበል ያደረጉላቸው ሲኾን የትምህርት ቤቱ የአብነት መምህር በግእዝ እና አማርኛ ቋንቋዎች መወድስ ቅኔ፤ ተማሪዎቹም የቃል ትምህርትና ምስባክ አቅርበዋል፡፡

uu

በመርሐ ግብሩ ላይ የትምህርትና ሥልጠና ማእከሉ በሲያትል ንዑስ ማእከል ውስጥ በሲያትል፣ በቤልቪዉ እና በባትል፤ እንደዚሁም በሰሜን አሜሪካ ግዛቶች ባሉ ሦስት ከተማዎች በድምሩ በስድስት ትምህርት ቤቶች ከ፪፻ በላይ ተማሪዎችን በማስተማር ላይ እንደሚገኝ፤ በዚሁ ትልቅ ድካምና ጥረት በሚጠይቀው አገልግሎት ውስጥ ከማኅበሩ አባላት በተጨማሪ በአካባቢው የሚገኙ መምህራን፣ ካህናትና ዲያቆናት እንደዚሁም ሰባክያነ ወንጌል እና ወላጆች የሚያደርጉት አስተዋጽዖ የጎላ መኾኑ ለብፁዕነታቸው ሪፖርት ተደርጓል፡፡

በተጨማሪም በአሜሪካ ማእከል የአቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል አማካይነት በውጭው ዓለም ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ተተኪ አገልጋይና ምእመናንን ለማፍራት ማኅበረ ቅዱሳን እያበረከተ ስለሚገኘው አተዋጽዖ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡

u

ብፁዕነታቸውም ‹‹በአባቶችሽ ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ›› በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ ማኅበረ ቅዱሳን ከመነሻው ጀምሮ ዓላማውና ተልእኮው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ተተኪዎችን ማፍራትና ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት መኾኑን እንደሚያውቁ ገልጸው አሁንም ማኅበሩ በማከናወን ላይ የሚገኘውን መንፈሳዊ አገልግሎት አድንቀዋል፡፡

በማእከሉ በተመለከቱት መልካም ተግባር በከፍተኛ ኹኔታ መደሰታቸውንና ይህ ሥራም ቤተ ክርስቲያን በዚህ ዘመን እየገጠማት ባለው ፈርጀ ብዙ ፈተና የተወሰነውን አገልግሎት ሊቀርፍ የሚችል ተግባር መኾኑን ጠቅሰው ማኅበረ ቅዱሳንን፣ የማእከሉ መምህራንን፣ ወላጆችን እና ተማሪዎችን በአጠቃላይ ዅሉንም ባለ ድርሻ አካላት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤል አመስግነዋል፡፡

በመጨረሻም በብፁዕነታቸው ቃለ ምዕዳን እና ጸሎተ ቡራኬ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ኾኗል፡፡

ምንጭ፡- በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል

ታላቅ የምሥራች ለኦርቶዶክሳውያን ምእመናን!

app-01

በማኅበረ ቅዱሳን የኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አገልግሎት ክፍል የተሠራው ‹‹ተዋሕዶ›› የተሰኘው የስልክ አፕሊኬሽን አንድሮይድ (Android) የተባለውን የቴክኖሎጂ ውጤት ለሚጠቀሙ ዘመናዊ ስልኮች እና የኪስ ኮምፒውተሮች አመቺ በኾነ መልኩ እንደገና ተሻሽሎ ቀረበ፡፡

ይህ አፕሊኬሽን በ፳፻፮ ዓ.ም ለመጀመሪያ ጊዜ ተዘጋጅቶ የነበረ ሲኾን፣ ክፍሉ ከተጠቃሚዎቹ የደረሱትን አስተያየቶች በማካተት ልዩ ልዩ ማሻሻያዎችን አድርጎ ለሁለተኛ ጊዜ እንዲቀርብ አድርጓል፡፡

አፕሊኬሽኑ በውስጡም የጸሎት መጻሕፍትን፣ ወቅታዊ የኾኑ መንፈሳዊ ትምህርቶችን፣ ዜናዎችን እና ልዩ ልዩ መረጃዎችን፤ ያሬዳውያን መዝሙሮችን፣ መንፈሳዊ የኪነ ጥበብ ዝግጅቶችን፤ እንደዚሁም የየዕለቱ ምንባባትን እና የሬዲዮ ሥርጭቶችን፤ የቀን መቍጠሪያዎችን፣ የበዓላትና አጽዋማት ማውጫዎችን፤ በተጨማሪም በሰሜን አሜሪካ፣ በካናዳ እና በአውሮፓ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የሚከናወኑ መርሐ ግብራትንና ሌሎችንም አርእስተ ጉዳዮች አካቷል፡፡

በልዩ ልዩ የመገናኛ መንገዶችና ገጾች ላይ በሃይማኖት ስም የሚጻፉ የኑፋቄ ትምህርቶች በስፋት በሚለቀቁበት በዚህ ዘመን ይህ የቴክኖሎጂ ውጤት መዘጋጀቱ ለምእመናን ታላቅ የምሥራች ነው፡፡

ስለዚህም አንድሮይድ (Android) የተሰኘውን የቴክኖሎጂ ውጤት መጠቀም የሚችል ዘመናዊ ስልክ ወይም የኪስ ኮምፒዩተር ያላችሁ ምእመናን ዅሉ ከጎግል ፕለይ (Google Play) ውስጥ ተዋሕዶ (Tewahedo) የሚለውን ቃል በመፈለግ በዚህ አፕሊኬሽን እንድትጠቀሙና ኦርቶዶክሳዊ ይዘት ባለው ቃለ እግዚአብሔር ነፍሳችሁን እንድታጠግቡ፣ አእምሯችሁንም በመንፈሳዊ ዕውቀት እንድታጎለብቱ ስንል መንፈሳዊ ግብዣችንን እናቀርባለን፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ አገልግሎት ክፍል ይኼንኑ አፕሊኬሽን አይ ኦ ኤስ (IOS)ን ለሚጠቀሙ የእጅ ስልኮች እና የኪስ ኮምፒውተሮች ከአሁን በፊት ማቅረቡ የሚታወስ ነው፡፡

ታላቁ የቅኔ ጉባኤ ቤት በእሳት ወደመ

chegodie

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጥር ፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በምዕራብ ጐጃም ሀገረ ስብከት በቋሪት ወረዳ ቤተ ክህነት ልዩ ስሙ ፈንገጣ በሚባል ቀበሌ በጨጎዴ ሐና የተቋቋመው፤ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በርካታ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትን ሲያፈራ የኖረውና እስከ አሁን ድረስም ሊቃውንትን የመተካት ተልእኮውን በመወጣት ላይ የሚገኘው የሊቀ ሊቃውንት ያሬድ ሽፈራው የቅኔ ምስክር ጉባኤ ቤት ጥር ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ረፋድ ላይ ድንገት በደረሰ የእሳት ቃጠሎ ወደመ፡፡

100_0718

የጉባኤ ቤቱ መምህር ሊቀ ሊቃውንት ያሬድ ሽፈራው ከከፊል ደቀ መዛሙርታቸው ጋር (ጉባኤ ቤቱ በእሳት ከመቃጠሉ በፊት)

በቦታው የተገኙ የዓይን እማኞች እንደሚያስረዱት በአካባቢው ያለው የአየር ጠባይዕ ነፋሻ ከመኾኑ፣ ጉባኤ ቤቱ ከእንጨትና ከሣር ከመሠራቱ ባሻገር ደቀ መዛሙርቱ ለክብረ በዓል በወጡበትና የአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን ወደ ቤተ ክርስቲያን በሔዱበት ሰዓት ቃጠሎው መከሠቱ ጉዳቱን የከፋ አድርጎታል፡፡

ድንገት በደረሰው በዚህ የእሳት ቃጠሎ ሁለት መቶ ሃያ አምስት የደቀ መዛሙርት መኖሪያ ጎጆዎች፣ ልዩ ልዩ መጻሕፍት፣ ምግብ እና አልባሳት በአጠቃላይ ከሰባት መቶ ስልሳ ሦስት ሺሕ አምስት መቶ ብር በላይ የሚገመት ንብረት መውደሙን የፍኖተ ሰላም ማእከል የላከልን ዘገባ ያመላክታል፡፡

ከማእከሉ ያገኘነው መረጃ እንደሚያሳየው ጉባኤ ቤቱ ከአምስት መቶ እስከ ስድስት መቶ የሚደርሱ ደቀ መዛሙርት ይማሩበት የነበረ ሲኾን በአሁኑ ሰዓትም በከፊል ከቃጠሎው በተረፈው የጉባኤ ቤቱ ማኅበር ቤት ተጠልለው ይገኛሉ፡፡

chegodie

የእሳት ቃጠሎው ያደረሰው ጉዳት በከፊል

የቋሪት ወረዳ ማእከል ከቦታው ያገኘውን መረጃ መሠረት አድርጎ ለዝግጅት ክፍላችን እንደ ገለጸው እሳቱ የተነሣው ከጉባኤ ቤቱ አጥር አካባቢ ሲኾን፣ እሳቱ በምን ምክንያትና በማን አማካይነት እንደ ተለኮሰ ለማረጋገጥ መንሥኤው በፖሊስ በመጣራት ላይ ይገኛል፡፡

ለደቀ መዛሙርቱ ምግብ፣ መጠለያና አልባሳት ድጋፍ ለማሟላት ምን ማድረግ እንደሚገባም የምዕራብ ጐጃም ሀገረ ስብከት ከፍኖተ ሰላም ማእከልና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመኾን ውይይት በማካሔድ ላይ እንደሚገኝ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ሥዩማን ቀሲስ አያና በላቸው ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡

በመጨረሻም ጉባኤ ቤቱን ወደ ነበረበት ህልውና ለመመለስ፤ ደቀ መዛሙርቱን ከመበተንና የጉባኤውን ወንበርም ከመታጠፍ ለመታደግ እንችል ዘንድ ‹‹መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፋችሁ አይለየን?›› ሲሉ ሊቀ ሊቃውንት ያሬድ ሽፈራው በጉባኤ ቤቱ ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡

በዚህ ታሪካዊ ጉባኤ ቤት ላይ በደረሰው ጉዳት ለጉባኤ ቤቱ መምህር ሊቀ ሊቃውንት ያሬድ ሽፈራው፣ ለደቀ መዛሙርቱና ለአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን መጽናናትን ይመኛል፡፡

በሐዊረ ሕይወቱ መደሰታቸውን ተሳታፊዎች ተናገሩ

በዝግጅት ክፍሉ

ታኅሣሥ ፳፯ ቀን ፳፻፱ .

img_0298

ዓለም ገና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ማርያም ገዳም

img_0351

፲፩ኛው የማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት በዓለም ገና ደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስ እና ቅድስት ድንግል ማርያም ገዳም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን፣ አባቶች ካህናትና ዐሥራ አንድ ሺሕ የሚኾኑ ምእመናን በተገኙበት ታኅሣሥ ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም መካሔዱ የሚታወስ ነው፡፡

img_0325

በሐዊረ ሕይወቱ ጠዋትና ከሰዓት በኋላ በተከናወነው መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ በማኅበሩ ሰባክያነ ወንጌል መ/ር ምትኩ አበራና መ/ር ያረጋል አበጋዝ ልቡናን የሚገዛና ድካመ ነፍስን የሚጠግን ሰፊ ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

img_0296

ምክረ አበው አቅራቢ አባቶች

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ለ ‹‹ምክረ አበው›› በተጋበዙት በቆሞስ አባ ሳሙኤል በሰዋስወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የብሉያትና ሐዲሳት ትርጓሜ መምህር፤ በአባ ገብረ ኪዳን በደቡብ ጎንደር እስቴ መካነ ኢየሱስ ደብር የአባ ኤስድሮስ ጉባኤ ቤት የሐዲሳት ትርጓሜ መምህርና የብሉያት ደቀ መዝሙር፤ በመጋቤ ሐዲስ ሮዳስ ታደሰ በአዲስ አበባ የምሥራቀ ፀሐይ ቀበና መድኀኔ ዓለም ደብር የሐዲሳት ትርጓሜ መምህር እና የስብከተ ወንጌል ክፍል ሓላፊ የብዙ ምእመናንን ጥያቄ የሚመልስ ትምህርት ቀርቧል፡፡

img_0333

የማኅበሩ መዘምራን ወረብና መዝሙር ሲያቀርቡ

በማኅበሩ ዘማርያንና በሊቀ መዘምራን ዲ/ን ቴዎድሮስ ዮሴፍ የቀረበው ያሬዳዊ ወረብና መዝሙርም የጉባኤው ክፍል ነበር፡፡

የሐዊረ ሕይወቱ ዐቢይ ኰሚቴ ሰብሳቢ አቶ ኤርምያስ ዓለሙ ለዝግጅት ክፍላችን እንዳስታወቁት ትኬት በመግዛት የመጡ ስምንት ሺሕ፤ ለልዩ ልዩ አገልግሎት ለመስጠት የተመደቡ አንድ ሺሕ፤ ከዓለም ገና እና ከአካባቢው የመጡ ደግሞ በግምት ሁለት ሺሕ፤ በድምሩ ዐሥራ አንድ ሺሕ የሚኾኑ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ የታደሙ ሲኾን በሐዊረ ሕይወቱ መደሰታቸውንም ተሳታፊዎች ተናግረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ቃለ ምዕዳን በሰጡበት ወቅት ‹‹ይህ ጉባኤ በዚህ ቦታ መዘጋጀቱ ለገዳሙ ብቻ ሳይኾን አጠቃላይ ለሀገረ ስብከታችን ትልቅ ዕድል ነው፤ በዚህ አካባቢ የሚገኙ ምእመናንም በመርሐ ግብሩ ትልቅ ተስፋ አግኝተዋል፤›› ካሉ በኋላ ‹‹ይህንን ጉባኤ በዚህ ቦታ በማካሔድ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስደሰቱ ማኅበሩን አመስግነዋለሁ፤›› በማለት የማኅበሩን አገልግሎት አበረታተዋል፡፡

ብ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ እና ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ከከፊል የጉባኤው ተሳታፊዎች ጋር

ከመርሐ ግብሩ ተሳታፊዎች መካከል አንዳንዶቹ በሐዊረ ሕይወቱ በመሳተፋቸው በርካታ መንፈሳዊ ቁም ነገር ማግኘታቸውን፣ በትምህርቱ ነፍሳቸው መርካቷንና አእምሯቸውም መደሰቱን ጠቅሰው ይህን ዅሉ ምእመን በአንድ ድንኳን ሥር አሰባስቦ፤ ቍርስ እና ምሳ መግቦ ቃለ እግዚአብሔር እንዲማር በማድረጉ ማኅበረ ቅዱሳንን አድንቀዋል፡፡ አያይዘውም ‹‹መርሐ ግብሩ ከዓመት ሁለት ጊዜ ብቻ ሳይኾን በየወሩ ቢካሔድልን?›› የሚል አስተያየት ሰጥተዋል፡፡

ed

የጉባኤው ተሳታፊ አባቶችና ወንድሞች በከፊል

የዓለም ገና እና የአካባቢው ማኅበረ ካህናትና ምእመናንም ሐዊረ ሕይወቱ በአካባቢያቸው በመካሔዱ ካገኙት መንፈሳዊ ትምህርት ባሻገር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቀ መንፈሳዊ ጉባኤ የማዘጋጀት ልምድን ከማኅበረ ቅዱሳን መማራቸውንም ተናግረዋል፡፡

በዕለቱ በማኅበሩ ሰብሳቢ በአቶ ታምሩ ለጋ የማኅበሩ መልእክት የቀረበ ሲኾን በመልእክቱም ማኅበሩ በሚያበረክተው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በመሳተፍ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በጋራ ለመደገፍና አገልግሎቷን በሚፈለገው ደረጃ ለማሳደግ መላው ሕዝበ ክርስቲያን የበኩሉን እገዛ ያደርግ ዘንድ ሰብሳቢው ጥሪያቸውን በቤተ ክርስቲያን ስም አስተላልፈዋል፡፡

wo

የጉባኤው ተሳታፊ እናቶችና እኅቶች በከፊል

እንደዚሁም የማኅበሩ የስድስት ዓመት ስልታዊ ዕቅድ የትኩረት አቅጣጫዎችን የስልታዊ ዕቅዱ ክንውንና ትግበራ ጽ/ቤት ሓላፊ አቶ ፋንታኹን ዋቄ አቅርበው ለዕቅዱ መሳካትም ምእመናን በሚቻላቸው ዓቅም ዅሉ የድርሻቸውን አስተዋፅዖ እንዲያበርክቱ አሳስበዋል፡፡

በመቀጠልም ሐዊረ ሕይወቱ በተሳካ ኹኔታ እንዲከናወን ድጋፍና ትብብር ያደረጉ የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስንና የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞችን፤ የሰበታ አዋስ ወረዳ ቤተ ክህነትና ወረዳ ማእከሉን፤ የደብረ ናዝሬት ኢየሱስ ክርስቶስና ቅድስት ማርያም ገዳም ሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤትን፣ ማኅበረ ካናትንና ምእመናንን፤ ከፌዴራል መንግሥት ጀምሮ በየደረጃው እስከ ከተማ አስተዳደሩ ድረስ የሚገኙ የመንግሥት አካላትን ማኅበሩ በእግዚአብሔር ስም አመስግኗል፡፡

11

መርሐ ግብሩ በጸሎት ሲፈጸም

በመጨረሻም ፲፩ኛው የማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ቃለ ምዕዳንና ጸሎተ ቡራኬ ተፈጽሟል፡፡

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ የእሳት ቃጠሎ ደረሰበት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

sebeta

የተቃጠለው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ወለልና የሕንጻው ቍሳቍስ በከፊል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሰበታ ወረዳ ቤተ ክህነት የሚገኘውና በጥር ወር ፳፻፮ ዓ.ም የተመሠረተው የሰበታ ዋታ ምዕራፈ ቅዱሳን አቡነ አረጋዊ እና በዓታ ለማርያም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከጠዋቱ ፪ ሰዓት ከ፴ ደቂቃ አካባቢ የእሳት ቃጠሎ ደረሰበት፡፡

ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ በቆርቆሮና በኮምፖርሳቶ ከመታነጹ በተጨማሪ ቃጠሎው የደረሰው ካህናቱ አገልግሎታቸውን ፈጽመው ከቤተ ክርስቲያን ከወጡ በኋላ መኾኑ ጉዳቱን የከፋ አድርጎታል፡፡

የቃጠሎው መንሥኤ እስካሁን በግልጽ እንዳልታወቀና በቃጠሎውም ከጽላቶቹ በስተቀር ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ሙሉ በሙሉ እንደ ወደመ የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ መልአከ ሕይወት ሐዋዝ ተስፋ ለማኅበረ ቅዱሳን ሚድያ ክፍል አስታውቀዋል፡፡ እንደ አስተዳዳሪው ገለጻ ከአምስት መቶ ሺሕ ሰማንያ ብር በላይ የሚገመቱ ንዋያተ ቅድሳት በቃጠሎው ወድመዋል፡፡

sebeta-copy

በቃጠሎው የወደሙ ንዋያተ ቅደሳት በከፊል

የማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች ቦታው ድረስ በመሔድ እንደ ተመለከትነው ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ረፋድ ላይ ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በደብሩ ተገኝተው ማኅበረ ካህናቱንና ሕዝበ ክርስቲያኑን አጽናንተዋል፤ የደብሩን ይዞታ የሚያስከብርና ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን የሚያስገነባ የልማት ኰሚቴም አስመርጠዋል፡፡ እንደዚሁም የሰበታ ወረዳ ቤተ ክህነት ሠራተኞች፣ የየአድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ካህናትና ማኅበረ ምእመናን ለሕንጻው ማሠሪያና ለንዋያተ ቅድሳት መግዣ የሚኾን ገንዘብ በማሰባሰብ ለልማት ኰሚቴው አበርክተዋል፡፡

አቡነ ሳዊሮስ

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ

ብፁዕነታቸው በዕለቱ ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ የልማት ኰሚቴው ከሐሜት በጸዳ መልኩ የማያድግምና ዘላቂ የኾነ ሥራ መሥራት እንደሚጠበቅበት ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም ለሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ግንባታ ብቻ ሳይኾን ለሃይማኖታችን መጠበቅና ለምእመናን አንድነትም ዘብ መቆም ይገባዋል ብለዋል፡፡

‹‹ይህ ዅሉ የደረሰው በእኛ ኀጢአት ነው›› ያሉት ብፁዕነታቸው የደብሩ አገልጋይ ካህናትና የአካባቢው ምእመናን ጥላቻንና መለያየትን በማስወገድ፤ ከኀጢአት በመራቅ፤ በፍቅር፣ በሰላምና በአንድነት በመኾን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በቅንነት እንዲያገለግሉ አባታዊ መልእክት አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ በቃለ ምዕዳናቸው ማጠቃለያም በደብሩ ላይ የደረሰውን የእሳት ቃጠሎ ከማጥፋት ጀምሮ መቃኞ ቤት በመሥራትና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ ድጋፍና ትብብር ያደረጉትን ምእመናንና በአካባቢው የሚኖሩ የእስልምና እምነት ተከታዮችን አመስግነዋል፡፡

መቃኞ

በአካባቢው ነዋሪዎች ትብብር የታነጸው መቃኞ ቤት

በቤተ ክርስቲያኑ ላይ የደረሰውን የቃጠሎ አደጋ ሰበካ ጉባኤው ለፖሊስ ሪፖርት እንዳደረገና በቃጠሎው ዕለትም የሰበታ ወረዳ ኮማንድ ፖስት፣ የጸጥታ ዘርፍ ሠራተኞችና ሌሎችም የመንግሥት ባለሥልጣናት እንደ ተገኙ የተናገሩት አስተዳዳሪው የቃጠሎው መንሥኤ እስኪጣራ ድረስም የደብሩ ሰሞነኛ ካህናትና የጥበቃ ሠራተኞች በሕግ ከለላ ሥር ይገኛሉ ብለዋል፡፡

አማንያንም ኾኑ ኢአማንያን የአካባቢው ነዋሪዎች በጋራ በመረባረብ ለታቦተ ሕጉ መቀመጫ የሚኾን ጊዜያዊ መቃኞ ቤት ማነጻቸውን ያስታወቁት የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ እንደ ገና ታድሶ አገልግሎት ይሰጥ ዘንድም የመላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፍና ርዳታ አይለየን ሲሉ በቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪያቸውን ያቀርባሉ፡፡

ትውልዱን ከሱስ ለመታደግ የቤተ ክርስቲያን ሚና

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አማካይነት በተዘጋጀው የዐውደ ጥናት ጉባኤ ታኅሣሥ ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በማኅበሩ ሕንጻ ፫ኛ ፎቅ አዳራሽ በቀረበው ጥናታዊ ጽሑፍ ከሱስ የነጻ ትውልድ ለመፍጠር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሚና ከፍተኛ መኾኑ ተገለጸ፡፡

ዶ/ር

ዶክተር ጃራ ሰማ ጥናታዊ ጽሑፍ አቅራቢ

በጉባኤው ‹‹ከሱስ የነጻ ትውልድ ለመፍጠር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሚና›› በሚል ርእስ ጥናታዊ ጽሑፋቸውን ያቀረቡት የሕክምና እና የማኅበራዊ ሳይንስ ባለሙያው ዶክተር ጃራ ሰማ የአልኮል መጠጦች፣ አደንዛዥ ዕፀዋት፣ አሽሽ፣ ትንባሆ፣ ሻይ፣ ቡና፣ የለስላሳ መጠጦች፣ ልዩ ልዩ መድኀኒቶችና የመሳሰሉት ልምዶች፤ እንደዚሁም የኢንተርኔት አገልግሎት፤ በተመሳሳይ መልኩ ሰዶማዊነት፣ ወደ ዝሙት ተግባር የሚወስዱ ፊልሞችን በዓይን ማየትና በድምፅ መስማት፣ እንደዚሁም ራስን ለፍትወተ ሥጋ ማነሣሣት በተደጋጋሚና በብዛት ከተወሰዱ ወይም ከተተገበሩ ሱስ ሊያስይዙ እንደሚችሉ ጠቁመዋል፡፡

ከዚሁ ዅሉ ጋርም ሳውና ባዝ፣ ስቲም ባዝና ሞሮኮ ባዝን ጨምሮ ሌሎች የመታሻ ሥፍራዎችና ጂም ቤቶችም ሱስን ሊያስይዙ የሚችሉ የምቾትና የድሎት አገልግሎቶች መኾናቸውን ጥናት አቅራቢው አስረድተዋል፡፡ ሱስ በድርጊት በመፈጸምና በመቅመስ ብቻ ሳይኾን በማየት፣ በመስማት፣ በመዳሰስ ወይም በመንካት እንደሚፈጸም ያስረዱት ጥናት አቅራቢው በማሽተት ከሚፈጸሙ ሱስ አምጪ ተግባራት መካከልም ቤንዚን፣ ትምባሆ፣ ሲጋራና ማስቲሽ የማሽተት ሱስን እንደ ምሳሌ አድርገው አቅርበዋል፡፡

ሱስ የሰውን ልጅ አእምሮውንና አካሉን በአግባቡ የማይጠቀም፤ የፈዘዘ፣ የደነዘዘ እንዲኾን ያደርጋል ያሉት ባለሙያው ሱሰኝነት ትዳር እንዲፈርስ፣ ቤተሰብ እንዲበተን፣ ክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲላላ፣ የማይታመን ራእይ አየን የሚሉ የሐሰት ባሕታውያን እንዲበዙ፣ ሽብርተኝነት እንዲስፋፋ፣ ወዘተ. በማድረግ ከግለሰብ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያንና በአገር ላይ የሚያደርሰው ሃይማኖታዊ፣ ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ምጣኔ ሀብታዊ ጉዳት ከፍተኛ መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡

የአእምሮ መታወክ፣ ጭንቀትና ውጥረት፣ የአስተዳደግ ችግር፣ የጓደኛ ተፅዕኖ፣ ቤተሰባዊ ግጭት፣ ሴሰኝነት፣ በኑሮ የሚያጋጥም ዕዳና ኪሳራ፣ ሥራ አጥነት፣ ወዘተ የመሳሰሉት አጋጣሚዎች ለሱስ የሚዳርጉ መሠረታዊ ጫናዎች መኾናቸውን ያመላከተው የዶ/ር ጃራ ጥናት ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ፣ የግብረ ገብ ትምህርቶችን በመማርና ሥልጠናዎችን በመውሰድ አመለካከትን መለወጥ (የእይታ አድማስን ማስፋት)፤ እንደዚሁም ማኅበራዊ ግንኙነትን ማሳመርና ሓላፊነትን ማሳደግ ከሱስ የማምለጫ መንገዶች መኾናቸውን ያስረዳል፡፡

tinat

የጥናቱ ታዳሚዎች በከፊል

የሰው ልጅ ከአምላኩ ውጪ በእርሱ ላይ አንዳች ኃይል ሊሠለጥንበት የማይችል በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ከፍጡራን ዅሉ የላቀ ክቡር ፍጥረት መኾኑን በጥናታቸው ያስታወሱት ዶ/ር ጃራ ሰማ የሰው ልጅ ክብሩን አዋርዶ ይሠለጥንባቸው ዘንድ የተሰጡት ፍጥረታት በእርሱ ላይ እንዲሠለጥኑ ከፈቀደ በምድር በኀጢአት አረንቋ ወድቆ እንደሚኖር፤ በዚህም ራሱን እንደሚበድልና የፈጠረውን አምላክም እንደሚያሳዝን ገልጸው ትውልዱ የተፈጠረለትን ዓላማ በመረዳት ወደ ሱስ ከሚወስዱ ነገሮች ራሱን መጠበቅ እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡

ምእመናንን ከልጅነታቸው ጀምሮ በሰንበት ት/ቤት፣ በማኅበር፣ በዐውደ ምሕረት፣ በኅትመት ውጤቶችና በሌላም ልዩ ልዩ መንገድ ግብረ ገብነትን በማስተማር፤ ወደ ሱስ የገቡትንም በሱባዔ፣ በቀኖና፣ በንስሐ፣ በጠበልና በሥጋ ወደሙ አማካይነት ፈውስን እንዲያገኙና በመንፈሳዊውም ኾነ በዓለማዊው ሕይወታቸው ጤናማ ኾነው እንዲኖሩ በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ያበረከተችው ሚና ከፍተኛ መኾኑን የጠቀሱት ጥናት አቅራቢው ችግሩን በዘላቂነት ለመከላከል የተዘጋጀ መዋቅራዊ አደረጃጀት ባለመኖሩ፣ ካህናት ከሕክምና ባለሙያዎች ጋር ተቀናጅተው ባለመሥራታቸው፣ ሱሰኞች ከሱስ ከወጡ በኋላ የሚቋቋሙበት ተቋም ባለመመሥረቱ፣ በጉዳዩ ላይ በቂ ጥናትና ምርምር ባለመደረጉ፣ የሚድያ ሽፋን ባለማግኘቱና በጀት ባለመመደቡ የተነሣ ቤተ ክርስቲያናችን ሓላፊነቷን በአግባቡ እንዳትወጣ ካደረጓት ምክንያቶች መኾነቻውን በጥናታቸው ዳሰዋል፡፡

ዶ/ር ጃራ ሰማ በጥናታቸው ማጠቃለያም ‹‹ምእመናን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው ብቻ ሳይኾን በማኅበራዊ ኑሯቸውም ከሌሎች ጋር ተስማምተው በፍቅር፣ በቅንነት፣ በሰላምና በአንድነት እንዲኖሩ የማስቻል ከማንም በላይ ከአምላክ ዘንድ የተሰጣት መንጋዋን ከጥፋት የመጠበቅ ከፍተኛ ሓላፊነት እንዳለባት ቤተ ክርስቲያናችን ተገንዝባ የአሠራር ችግሮችን በመቅረፍ ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ትኩረት ሰጥታ መሥራት ይገባታል›› ብለዋል፡፡

የአዳዲስ አማንያኑ ቍጥር ወደ ሰማንያ አምስት ሺሕ አደገ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ታኅሣሥ ፳ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

img_0090

በማኅበረ ቅዱሳን አስተባባሪነት በተከናወነው የጥምቀት መርሐ ግብር ከመስከረም እስከ ታኅሣሥ ወር ፳፻፱ ዓ.ም ባለው የአገልግሎት ዘመን በመተከል ሀገረ ስብከት በአምስት ወረዳዎች ውስጥ በሚገኙ ዐሥር የጥምቀት ቦታዎች ስድስት ሺሕ ስምንት መቶ ሃያ አንድ፤ በጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት በዐርባ ምንጭ አካባቢ ሁለት ሺሕ አንድ መቶ ሠላሳ ሰባት፤ በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት በጂንካ አካባቢ አንድ ሺሕ ስልሳ አንድ፤ በሸካ ቤንች ማጂ ሀገረ ስብከት በማጂ ወረዳ ሦስት ሺሕ ስድስት መቶ ሰማንያ ስድስት፤ በድምሩ ዐሥራ ሦስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስት በልዩ ልዩ ጠረፋማ አካባቢዎች የሚኖሩ አዳዲስ አማንያን የሥላሴ ልጅነትን አግኝተዋል፡፡

ይህም ከአሁን በፊት ማኅበሩ ካስጠመቃቸው ሰባ ሁለት ሺሕ አማንያን ጋር ሲደመር የአዳዲስ አማንያኑን ቍጥር ወደ ሰማንያ አምስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስት እንደሚያደርሰው በማኅበሩ የስብከተ ወንጌል ትግበራ ባለሙያ ቀሲስ ይግዛው መኮንን ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡ ከዐሥራ ሦስት ሺሕ ሰባት መቶ አምስቱ አዳዲስ አማንያን መካከልም ከፊሎቹ ታኅሣሥ ፱፣ ፲፮ እና ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም የተጠመቁ ናቸው፡፡

metekel-2

የመተከል ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሰላም ብርሃን ዓለም ጥምቀቱ በተፈጸመበት ዕለት በድባጤ ወረዳ ቤተ ክህነት አልባሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ተገኝተው ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ ‹‹ዛሬ ወላጆች ከልጆቻችሁ ጋር ተጠምቃችኋል፡፡ ከዚህ በኋላ ልጆችን ስትወልዱ ወንዶችን በዐርባ፤ ሴቶችን ደግሞ በሰማንያ ቀናቸው ወደ ቤተ ክርስቲያን በማምጣት ማስጠመቅ አለባችሁ፤›› በማለት ተጠማቂዎቹን አስተምረዋል፡፡ በማያያዝም ተጠማቂዎቹ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተው፣ ከኀጢአት ተለይተው መኖር እንደሚገባቸው፤ ከዚህም ባሻገር ያልተጠመቁ ዘመዶቻቸውንና ጎረቤቶቻቸውን አስተምረው ወደ ክርስትና ሃይማኖት መመለስ፤ የተጠመቁትንም በሃይማኖትና በምግባር እንዲጸኑ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው ሥራ አስኪያጁ ተጠማቂዎቹን መክረዋል፡፡

በመተከል ሀገረ ስብከት በተካሔደው የጥምቀት መርሐ ግብር ከልዑካኑ ጋር አብረው የተሳተፉት የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ንጉሤ መብራቱ አዳዲስ አማንያንን ማስጠመቅ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚሰጠው አገልግሎት ውስጥ ዐቢዩና ዋነኛው ተግባር መኾኑን አስታውሰው ለአገልግሎቱ ውጤታማነትና ለተጠማቂዎቹ ቍጥር መጨመርም የማኅበሩ አባላትና የበጎ አድራጊ ምእመናን ተሳትፎ ከፍተኛ አስተዋጽዖ እንዳለው ተናግረዋል፡፡

metekel-3

የማኅበረ ቅዱሳን የግልገል በለስ ማእከል ሰብሳቢ አቶ አሰፋ ደሳለኝ እና ጸሐፊው አቶ ደግ አረገ አለነ በበኩላቸው ማእከሉ ከመተከል ሀገረ ስብከት ጋር ኾኖ ሰባክያንን በመመደብ፣ ቅኝት በማድረግና በመሳሰሉት ተግባራት አገልግሎቱን በማስተባበር የሚጠበቅበትን ድርሻ መወጣቱን ጠቅሰው ማእከሉ ያለበት የሰው ኃይል፣ የመምህራንና የገንዘብ እጥረት፣ እንደዚሁም የጥምቀት መርሐ ግብሩ የሚፈጽምባቸው ቦታዎች ርቀትና ለአገልግሎት ምቹ አለመኾን አዳዲስ አማንያንን የማስጠመቁን ተልእኮ ከሚፈታተኑ ችግሮች መካከል ዋነኞቹ መኾናቸውን ጠቁመዋል፡፡

በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በመስጠት ላይ ከሚገኙ ሰባክያነ ወንጌል መካከል ዲያቆን ቶማስ ጐሹ እና ወንድም ፈጠነ ገብሬ ተጠማቅያኑ ቀደምት አባቶቻቸው ለዚህ ክብር ሳይበቁ በማለፋቸው እንደሚቈጩና የክርስትና ጥምቀትን ለማግኘት ሲሉም ከሌሊቱ ሰባት ሰዓት ጀምረው በእግራቸው እንደ ተጓዙ ገልጸው የጉሙዝ ብሔረሰብ አባላት የቃለ እግዚአብሔር ጥማት እንዳለባቸውና ‹‹ልጆቻችንን የቄስ ትምህርት አስተምሩልን?›› እያሉ እንደሚጠይቋቸውም አስረድተዋል፡፡

ወደ ፊትም ሰንበት ት/ቤቶችን በየቦታው በማቋቋም ተጠማቅያኑ በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ለማድረግ ዕቅድ ቢኖራቸውም ነገር ግን ሰባክያነ ወንጌል በብዛት አለመመደባቸው፣ ቢመደቡም የሚከፈላቸው የድጎማ ገንዘብ አነስተኛ መኾኑ፣ ሞተሮቻቸው ሲበላሹባቸው የሚያስጠግኑበት በጀት አለመኖሩ፣ እንደዚሁም የአካባቢው መናፍቃን ተጽዕኖ መበራከቱ ‹‹አገልግሎታችንን በአግባቡ እንዳንወጣ አድርጎናልና መፍትሔ እንፈልጋለን›› ሲሉ የድጋፍ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡

metekel-2

ከተጠማቅያን የጉሙዝ ብሔረሰብ አባላት መካከል አንደኛው ለዚህ ታላቅ ክብር ስላበቃቸው እግዚአብሔርን ካመሰገኑ በኋላ ‹‹አጥምቃችሁን መመለስ ብቻ ሳይኾን ለወደ ፊትም አስተማሪ፣ መካሪ ካህን አጥተን ወደ ሌላ ቤተ እምነት እንዳንወሰድ እየመጣችሁ በመምከር፣ በማስተማርና በማበረታታት በሃይማኖታችን እንድንጸና ድጋፍ አድርጉልን፤›› ሲሉ የድረሱል ድምፃቸውን ያሰማሉ፡፡ ሌላኛው ተጠማቂ ወንድምም እንደዚሁ ራሳቸውን ጨምሮ ዐሥራ አራት የቤተሰቡ አባላት በሙሉ በአንድ ቀን መጠመቃቸውን አውስተው ‹‹ያልተጠመቁ ዘመዶቼና ወዳጆቼንም ተምረው የሥላሴን ልጅነት እንዲያገኙ አደርጋለሁ›› ብለዋል፡፡

የማኅበሩ ጋዜጠኞችም በመተከል ሀገረ ስብከት ልዩ ልዩ ቦታዎች ታኅሣሥ ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በተካሔደው የጥምቀት መርሐ ግብር በተሳተፍንበት ወቅት በድባጤ ወረዳ ቤተ ክህነት በአልባሳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የአዊ ብሔረሰብ ተወላጆች ተጠማቂ የጉሙዝ ብሔረሰብ ተወላጆችን ክርስትና በማንሣት በሚያስፈልጋቸው መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጉዳይ ዅሉ ከጎናቸው እንደማይለዩ ቃል በመግባት ዝምድናቸውን ሲያጠናክሩና አንድነታቸውን ሲያጸኑ ተመልክተናል፡፡

img_0143በግል መኪኖቻቸው ልዑካኑን በመያዝ በጉዞው የተሳተፉ ወንድሞችም ከአሁን በፊት ብዙ ቦታዎችን እንደሚያውቁ፤ ነገር ግን እንደዚህ ዓይነት አስቸጋሪ መንገድ እንዳላጋጠማቸውና መንገዱም ከጠበቁት በላይ ለመኪናዎቻቸው አስቸጋሪ እንደ ነበረ ገልጸው ማኅበሩ የሚሰጠውን አገልግሎት በመመልከት በመንፈሳዊ ቅናት ተነሳሥተው ብዙ ውጣ ውረዶችን በመቋቋም ተልእኳቸውን ተወጥተው መመለሳቸውን ተናግረዋል፡፡ ባለ መኪኖቹ ‹‹መንፈሳዊ ጉዞው ወደ ፊት የሚጠበቅብንን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ለመወጣት እንድንዘጋጅ አድርጎናል›› ሲሉም ቃል ገብተዋል፡፡

የጥምቀት መርሐ ግብሩን ለማስተባበር በየጠራፋማ አካባቢዎች ተሰማርተው ለነበሩ የማኅበረ ቅዱሳን ልዑካንም የማኅበሩ ሥራ አመራርና ሥራ አስፈጻሚ አባላት፣ የልዩ ልዩ ዋና ክፍሎች አገልጋዮችና ተጋባዥ እንግዶች በተገኙበት በማኅበሩ ሕንጻ ፮ኛ ፎቅ አዳራሽ የእንኳን ደኅና መጣችሁ አቀባበል ተደርጎላቸዋል፡፡

በዕለቱ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በምቹ ኹኔታዎች የሚፈጸም ተግባር ሳይኾን ፈተና የበዛበት ተልእኮ መኾኑን ገልጸው ልዩ ልዩ ፈተናዎችም ማኅበሩ መንፈሳዊ ተልእኮውን በአግባቡ እንዲወጣ ስላደረጉት በሺሕ የሚቈጠሩ ኢአማንያን የሥላሴ ልጅነትን እንዲያገኙ ለማድረግ መቻሉን አስረድተዋል፡፡

metekel

‹‹በጠረፋማ የኢትዮጵያ አካባቢዎች በልዩ ልዩ ቋንቋ ወንጌልን የሚሰብኩ መምህራን የሕይወት መጻሕፍት ናቸውና ዅላችንም ልንማርባቸው ይገባል፤›› ያሉት ዋና ጸሐፊው በጸሎት፣ በስብከት፣ በማስተባበር፣ በገንዘብ ድጋፍ፣ በጉልበት ሥራና በመሳሰሉት ተግባራት በመሳተፍ ለአማንያኑ መጠመቅ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ያበረከቱ የቤተ ክርስቲያን አባቶችን፣ መምህራንና ካህናትን፣ እንደዚሁም በጎ አድራጊ ምእመናንን በማኅበሩ ስም አመስግነዋል፡፡

ከሥራ አመራር አባላት መካከል አንደኛው ከፈጸምነው ተልእኮ ይልቅ ገና ያልሠራነው ብዙ ተግባር እንደሚበልጥ በመገንዘብና ምእመናንን ከቤታቸው ለማስወጣት ተግተው የሚሠሩ አካላት በየቦታው እንደሚገኙ በመረዳት ወደ ፊት ለሚጠበቅብን ዘርፈ ብዙ ሥራ መዘጋጀት ተገቢ መኾኑን አስረድተዋል፡፡

አያይዘውም በጥምቀት መርሐ ግብሩ የተሳተፉ መምህራን፣ ጋዜጠኞች፣ የካሜራ ባለሙያዎች፣ ሹፌሮችና ሌሎችም የልዑካኑ አባላት በአገልግሎቱ መሳተፋቸው ምስጋና ለማግኘት ሳይኾን እናት ቤተ ክርስቲያናቸውን በተሰማሩበት የሥራ ዘርፍ ለማገልገል እና ክርስቲያናዊ ግዴታቸውን ለመወጣት መኾኑን ሊረዱት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

metekel

ተጠማቂዎቹ እንዳይበተኑና በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ ለማድረግ በጠረፋማ አካባቢዎች አብያተ ክርስቲያናትን ማሳነጽ፣ በየቋንቋው የሚሰብኩ መምህራንና ካህናትን ቍጥር ማሳደግ፣ የትምህርተ ሃይማኖት መማሪያ መጻሕፍትን በየቋንቋው ማዘጋጀት፣ አዳሪ ት/ቤቶችንና ሰንበት ት/ቤቶችን በየቦታው ማቋቋም፣ የስብከት ኬላዎችን ማስፋፋትና ለተጠማቅያኑ አስፈላጊውን ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ድጋፍ ማድረግ ለወደፊቱ በማኅበሩ ሊሠሩ የታቀዱ ተግባራት መኾናቸውን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ምክትል ሓላፊ አቶ ሰይፈ አበበ ጠቅሰው ይህንን ዕቅድ ከግብ ለማድረስም የበጎ አድራጊ ምእመናን ተሳትፎ እንዳይለያቸው በማኅበሩ ስም መንፈሳዊ ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

ሰማንያ አምስት ሺሕ ኢአማንያንን የቤተ ክርስቲያን ልጆች እንዲኾኑ ማድረግ ታላቅ ተልእኮ ቢኾንም ከዚህ የበለጠ መትጋት ከኹላችንም የሚጠበቅ ተግባር ነው፡፡ መላው ሕዝበ ክርስቲያን በአንድነት ኾነን ተባብረን ከሠራን ከዚህ በላይ ቍጥር ያላቸው ኢአማንያንን ለማስጠመቅና ተዋሕዶ ሃይማኖታችንን ይበልጥ ለማስፋፋት እንደሚቻል ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ስለዚህም በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም (መርሐ ግብር) ለሚሠሩ ልዩ ልዩ ፕሮጀክቶች መሳካት የበጎ አድራጊ ምእመናን ድጋፍ እንዳይለየን ሲል ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያን ስም ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡

ከሃያ አምስት በላይ የግብጽ ምእመናን በቦምብ ፍንዳታ ሕይወታቸው ዐለፈ

news

ታኅሣሥ ፫ ቀን ፳፻፱ .

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በግብጽ ካይሮ ከተማ እሑድ ታኅሣሥ ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ረፋድ ላይ ከቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል አጠገብ በሚገኘው የቅዱስ ጴጥሮስና ቅዱስ ጳውሎስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በደረሰ የቦምብ ፍንዳታ ከሃያ አምስት በላይ የግብጽ ምእመናን ሕይወታቸው ዐለፈ፡፡

ፍንዳታው የደረሰው በሴቶች መቆሚያ በኩል መኾኑን ከግብጽ አካባቢያዊ የመረጃ አውታሮች ለመረዳት ተችሏል፡፡

በጥቃቱ ዐርባ ዘጠኝ ሰዎች መቍሰላቸውንና ከእነዚህ መካከልም አብዛኞቹ ሴቶች መኾናቸውን የግብጽ ጤና ጥበቃ ሚኒስትር አሕመድ ኢማድ ተናግረዋል፡፡ እንደ ጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ መግለጫ ከቍስለኞቹ መካከል ሦስቱ አሳሳቢ ደረጃ ላይ ይገኛሉ፡፡

egypt-7

ጕዳቱ ለደረሰባቸውና ሕክምና ላይ ለሚገኙት ቍስለኞች የደም ልገሳ እንዲደርግላቸው በማኅበራዊ ሚድያዎች አማካይነት የግብጽ ሆስፒታሎች ጥሪ ማቅረባቸውም ታውቋል፡፡

በፍንዳታው ምክንያት በግብጻውያን ምእመናን ላይ ለደረሰው ሞትና ጉዳት አገሪቱ የሦስት ቀን ኀዘን እንደምታውጅ የግብጽ ፕሬዚዳንት አብደል ፈታሕ አል ሲሲ አስታውቀዋል፡፡

ለድርጊቱ ሓላፊነቱን የወሰደ አካል ግን እስካሁን ድረስ አልተገኘም፡፡

fun-5

በፍንዳታው ሕይወታቸው ያለፈ ምእመናን ሥርዓተ ቀብርም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዎድሮስ ካልዕ መሪነት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት እና ብዙ ሺሕ የግብጽ ምእመናን በተገኙበት ታኅሣሥ ፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በግብጽ ቅድስት ማርያም እና ቅዱስ አትናቴዎስ ቤተ ክርስቲያን ተፈጽሟል፡፡

ምንጭ፡

Orthodoxy Cognate PAGE – Media Network

http://www.dailynewsegypt.com

http://english.ahram.org.eg