ዝክረ ግማደ መስቀሉ!
በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን (በ፫፻፳፯ ዓ.ም) የንጉሥ ቆስጠንጢኖስ እናት ቅድት እሌኒ መስቀሉን ለማግኘት ወደ ኢየሩሳሌም ሄደች፡፡ ቅድት ዕሌኒ መስከረም ዐሥራ ስድስት ቀን በታሪክ አዋቂው አረጋዊው ኪራኮስ አማካኝነት ዕጣን እንዲጤስ አድረጋ በዕጣኑም ጢስ አመልካችነት መስቀሉን ከተቀበረበት ቦታ ለማውጣት በመስከረም ፲፯ ቀን ቍፋሮ አስጀምራለች፡፡ ንግሥት እሌኒ ከመስከረም ፲፯ ቀን አስጀምራ እስከ መጋቢት ፲ ቀን ሌሊትና ቀን ለሰባት ወራት ያህል የጉድፍን ኮረብታ ቆፍረው ቆሻሻውንም ካስወገዱ በኋላ ሦስት መስቀሎች ተገኙ፡፡ የጌታም መስቀል ሙት በማስነሣቱ ተለይቶ ታውቋል፡፡ መስቀሉ የተገኘው መጋቢት ፲ ቀን ፫፻፳፮ ዓ.ም. ነበር፡፡ በተመሳሳይ መልኩ መስቀሉ ከተቀበረበት ተራራ ተቈፍሮ የወጣበት መጋቢት ፲ ቀንም በቤተ ክርስቲያን በደማቅ ሥርዓት ይከበራል፡፡ በተጨማሪም መስከረም ፲፯ ቀን ንግሥት ዕሌኒ ቅዳሴ ቤቱን ያከበረችበትን የመታሰቢያ በዓል ታቦት አውጥተው ዑደት በማድረግ በቤተ ክርስቲያን ያከብሩታል፡፡ ከሦስቱ መስቀሎች መካከል ጌታችን የተሰቀለበት መስቀል የተለየው ተአምራት በማድረጉና ብዙ ድውያንን በመፈወሱ ነው፡፡






