Aba Entones Gedam.JPG

በዓለማችን የመጀመሪያ የሆነው የአባ እንጦንስ ገዳም በዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር እድሳት ተደረገለት

ገዳሙ አንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመታትን አስቆጥሯል

በሻምበል ጥላሁን

በዓለም የመጀመሪያው የምንኩስናና የገዳማውያን ኑሮ መሥራች የሆነው የአባ እንጦንስ ገዳም በግብፅ መንግሥት በዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር ወጪ እድሳት ተደርጎለት ለአገልግሎት መዘጋጀቱን ቢቢሲ የካቲት 4 ቀን 2002 ዓ.ም ዘገበ፡፡ በግብፅ የሚገኘው የቅዱስ እንጦንስ ገዳም ከአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ዓመት በላይ ዕድሜ ያለው ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡

Aba Entones Gedam.JPG 

በግብፅ የሚገኘው የአባ እንጦንስ ገዳም 

ገዳሙ ከዕድሜ ብዛት በእርጅና ከደረሰበት ጉዳት ተጠግኖ ለቱሪስት ኢንዱስትሪው ተጨማሪ አቅም እንዲፈጥር የግብፅ መንግሥት ከዐሥራ አራት ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጪ እንዳደረገ ዘገባው ጠቁሞ፤ ገዳሙ መንፈሳዊ እሴቱና ታሪካዊ ዳራው እንዳይጠፋ ለማደስ ከስምንት ዓመት በላይ እንደፈጀም የዜና ምንጩ አስታውቋል፡፡

የቢቢሲ ዘገባ እንዳመለከተው፤ የገዳሙ መታደስ የሀገሪቱን የቱሪስት ኢንዱስትሪ ከማስፋፋቱም በላይ ከፍተኛ የኢኮኖሚ አቅም ለመገንባትም እንደሚያስችል አመልክቷል፡፡

በግብፅ ስዊዝ ከተማ የሚገኘው የአባ እንጦንስ ገዳም መታደስ፣ አገልግሎት ላይ መዋልና ለቱሪስት መስህብነት ክፍት መሆኑ፤ ሀገሪቱ የቀድሞ ታሪኳንና ቅርሷን ለመጠበቅ የምታደርገውን ጥረት እንደሚያሳይ ዛሒ ሐዋስ የተባሉት የግብፅ ዋና የቅሪተ አካል ተመራማሪ መናገራቸውንም የዜና ምንጩ አስታውቋል፡፡

ገዳሙ ቅዱስ እንጦንስ በሦስተኛው መቶ ከፍለ ዘመን በቀይ ባሕር አካባቢ በሚገኘው ተራራማና በረሐማ አካባቢ ለጸሎት የመነኑበት ቦታ ነው፡፡

በመልሶ ግንባታው ወቅት በገዳሙ የሚኙት ሁለት አብያተ ክርስቲያናትና ሁለት ማማዎች በጥንቃቄ መንፈሳዊና ታሪካዊ ይዘታቸው ሳይቀየር መሠራታቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡

የቅዱስ እንጦንስ ገዳም በግብፅ ኦርቶዶክሶችም ሆነ በአምስቱ ኦሪየንታል አኀት አብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ታዋቂ ነው፡፡

በገና እንደርድር

 በመ/ር መንግስተአብ አበጋዝ
ለግማሽ ምእተ ዓመት ያህል በገና ለደረደሩት መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ እሑድ የካቲት 14 ቀን 2002 ዓ.ም ልዩ ነበር፡፡ ስለዚህ በገናቸውን አንሥተው መጋቤ ስብሐት «ማን ይመራመር ማን ይመራመር ያንተን ሥራ ያንተን ግብር ማን ይመራመር …» እያሉ ያመሰግናሉ፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ለስድስት ወር ያሠለጠናቸው አርባ ስድስት የበገና ደርዳሪዎችን በሩሲያ ባሕል ማእከል የፑሽኪን አዳራሽ ተመልክተዋልና፡፡

«ለረዥም ዘመን ብቸኝነት ይሰማኝ  ነበር» ያሉት መጋቤ ስብሐት ዓለሙ፡፡ «አሁን በዝተናል» በማለት የበገና ማሠልጠኛዎችም ሆኑ ተማሪዎቹ እየጨመሩ መምጣታቸው ሀገራዊ እሴቱንም ሆነ ሃይማኖታዊ ሥርዓቱን ጠብቆ ለማየቆት ጠቃሚ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መመሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የተቋቋመው የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤት በአብነት ትምህርትና በዜማ መሣሪያዎች እያሠለጠነ ማስመረቅ ከጀመረ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ እንደ ት/ቤቱ ሥራ አስኪያጅ አቶ አዲስ ተፈራ ገለጻ የዛሬውን ጨምሮ አሥራ አራት ዙር አሠልጥኖ አስመርቋል፡፡

ሥራ አስኪያጁ የአብነት ትምህርትና የዜማ መሣሪያዎች ሥልጠና እሴቶቹን ከመጠበቅ ባሻገር የሚያስገኙትን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጠቀሜታዎች ሲዘረዝሩ «ለምስጋና፣ ለተመስጦ፣ ጭንቀትንና ርኩስ መንፈስን ለማራቅ፣ ለትምህርት፣ እንዲሁም የሀገርን ቅርስ ከነሙሉ ታሪኩና ጥቅሙ ለማስተዋወቅ፣ ትውፊትን ለትውልድ ለማውረስና በገና ከነበረው ጥቅም አንጻር ቀጣይ አገልግሎት እንዲኖረው ማድረግ ይቆይ የማይባል አገልግሎት ነው፡፡» ይላሉ፡፡

ወጣት ሚልካ ሐጎስ በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የአምስት ኪሎ ኢንጂነሪንግ የ4ኛ ዓመት ተማሪ ናት፡፡ ከትምህርቷ በተጓዳኝ ትምህርተ ቤተ ክርስቲያን የምትከታተል የግቢ ጉባኤ ተማሪ ናት፡፡ በዚህ ሁሉ የጊዜ ጥበት ግን በአቡነ ጎርጎርዮስ ት/ቤት የሚሰጠውን የዜማ መሣሪያ ሥልጠና ወስዳ በበገና መደርደር ተመርቃለች፡፡ ሚልካ ጊዜዋን አጣጥማ በሳምንት ሁለት ቀን ለሁለት ሰዓት ተከታትላ በስድስት ወር ያጠናቀቀችውን ሥልጠና እንዴት ትገልጠዋለች)

«ጊዜአችንን በአግባቡ የምንጠቀም ከሆነ ሕልምን እውን ማድረግ እንችላለን፡፡ ጊዜዬን ተጠቅሜ በገና ተምሬአለው፡፡ ይህ ለእኔ መንፈሳዊ ሕይወት እጅግ አጋዤ ነው፡፡ ጊዜ መድቤ ደግሞ የአብነት ትምህርቱንና ተጨማሪ የዜማ መሣሪያዎችን ለመማር አስባለሁ፡፡ እድሜዬን ሁሉ አገልጋይ ሆንኩ ማለት አይደል፡፡ በእውነት በገና መደርደር መታደል ነው፡፡» ብላለች፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም ትምህርት ቤቱን ከፍቶ ኑና በገና እንደርድር ይላል፡፡

ከጋምቤላ ክልል የመጡ ሠልጣኞች ተመረቁ

በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል አስተባባሪነት ከጋምቤላ ክልል የአኝዋክና የኑዌር ብሔረሰብ ተወላጅ ሠልጣኞች ተመረቁ፡፡ በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ሓላፊ ዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል እንደተናገሩት በክልሉ ከ1997 ዓ.ም ወዲህ ሠልጣኞች መጥተው ሲሠለጥኑ የአሁኑ የመጀመሪያ ጊዜ ነው፡፡

ሓላፊው የሥልጠናውን ዓላማ ሲያስረዱ በአብዛኛው የጠረፋማ ቦታዎች የሚገኙ ብሔር ብሔረሰቦች በቋንቋቸው የሚያስተምራቸው ባለማግኘታቸው ተቸግረው ቆይተዋል፡፡ ይህንን ለማቃለል ከማኅበረሰቡ የተገኙ ወጣቶችን በማስተማር ወደ ትውልድ ቀዬአቸው ተመልሰው ሕዝቡን እንዲያስተምሩና እንዲያስጠምቁ ለማድረግ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ላሬ፣ ኝንኛንግ፣ ፒኝዶ፣ አበቦ፣ ጆር፣ ኢታንግ እና ጋምቤላ ዙሪያ ከሚባሉ ሰባት ወረዳዎች የመጡት ሠልጣኞች በቁጥር ዐሥራ ስድስት ሲሆኑ ሥልጠናው ዐሥራ አምስት ቀን እንደወሰደ ሓላፊው ተናግረዋል፡፡

ሥልጠናውን ለመሥጠት ከሰላሳ አምስት ሺሕ ብር በላይ ወጪ እንዳስፈለገ የጠቀሱት ሓላፊው ወደፊትም በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኙ በጎ አድራጊዎች ይህንን መሰል መንፈሳዊ አገልግሎት ለማከናወን የእርዳታ እጃቸውን ከዘረጉ በርካታ የጠረፋማ አካባቢ ወገኖችን ለማስተማር እንደሚቻል አስረድተዋል፡፡

በአፍ መፍቻ ቋንቋ ተምሮ ማስተማር ውጤቱ ከፍተኛ በመሆኑም የክርስትናው እምነት ባልተዳረሰባቸው አካባቢዎች በቋንቋቸው በማስተማር ልንደርስላቸው ይገባል ብለዋል፡፡

ሠልጣኞቹ ሥነፍጥረት፣ ትምህርተ ሃይማኖት፣ የቤተክርስቲያን ታሪክ፣ ነገረ ቅዱሳን፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ ሥርዓተ ቤተክርስቲያንና የስብከት ዘዴ በሚሉ ርእሶች ትምህርት እንደተሰጣቸው እና ወደ ክልላቸው ሔደው ምን መሥራት እንደሚገባቸው ምክክር እንደተደረገም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ለገዳሙ ካህናትና ዲያቆናት መሠረታዊ የኮምፒውተር አጠቃቀም ሥልጠና ተሰጣቸው

በይበረሁ ይጥና
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የምስካየ ኅዙናን መድኃኔዓለም ገዳም የተምሮ ማስተማር ሰንበት ትምህርት ቤት ለስምንት ወራት በመሠረታዊ የኮምፒውተር ትምህርት ያሠለጠናቸውን አሥራ አምስት ካህናትና ዲያቆናት ጥር 30 ቀን 2002 ዓ. ም. አስመረቀ፡፡

የገዳሙ አስተዳዳሪ ቆሞስ መልአከ ፀሐይ አባ ገብረ ሥላሴ  በምረቃው መርሐ ግብር እንደተናገሩት፤ የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮችን በዘመናዊ ቴክኖሎጂ የታገዘ ትምህርት ማስተማር ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት ለመስጠት ያስችላል፡፡ ትምህርቱን ያገኙት አባቶችም ሆኑ ዲያቆናት በኮምፒውተር ትምህርት መሠልጠናቸው የመረጃ ሥርዓትና ተዛማጅ ሥራዎች በዘመናዊ መልክ ለማከናወን እንደሚያግዛቸውም ተናግረዋል፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቱ ሥልጠናውን አዘጋጅቶ አባቶች፣ ዲያቆናትና የሰንበት ትምህርት ቤቱ ወጣቶች በአንድነት እንዲሠለጥኑ ማድረጉ ቤተ ክርስቲያንን በልማት ለማሳደግ ያለውን ርእይ እንደሚያሳይ ጠቁመው፤ ወደፊትም ከሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን ብዙ እንደምትጠብቅ ተናግረዋል፡፡

የሰንበት ትምህርት ቤቱ ምክትል ሰብሳቢ ዲያቆን ደረጀ ነጋሽ በበኩሉ፤ የመጀመሪያውን ዙር መሠረታዊ የኮምፒዩተር ሥልጠና ሠልጥነው ያጠናቀቁት፤ አንድ መነኩሴ፣ አሥራ ሦስት ዲያቆናትና አንዲት የሰንበት ትምህርት ቤት አባል ወጣት እንደሆኑ አስረድቷል፡፡ በሥልጠናው ወቅት ያገኙትም የትምህርት ዓይነት ኤም ኤስ ዊንዶ፣ ወርድ፣ ኤክሴል፣ አክሰስና የኢንተርኔት አጠቃቀም የተመለከቱ መሆናቸውን ሰብሳቢው ጠቁሞ፣ ሥልጠናው አገልግሎታቸውን ለማቀላጠፍ እንደሚረዳ አስታውቋል፡፡

ሥልጠናውን ለስምንት ወራት የሰጡት ቀደም ሲል በሰንበት ትምህርት ቤቱ ተኮትኩተው ያደጉ ወጣቶች ሲሆኑ፤ አሠልጣኞች በአሁኑ ጊዜ በኮምፒዩተር ሳይንስ ሙያ በተለያዩ ተቋማት የሚያስተምሩ አባላት እንደሆኑ ምክትል ሰብሳቢው አስረድቷል፡፡ ለወደፊትም ሥልጠናውን ከገዳሙም በተጨማሪ ወደ ሌሎችም አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት በመሔድ ለአገልግሎትና ለሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ለመስጠት እቅድ መያዙን ተናግሯል፡፡

በምረቃ ሥነ ሥርዓቱ ላይ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የተገኙ ሲሆን በተለይ ቀደም ብሎ የሰንበት ትምህርት ቤቱ አባል የነበሩ አባቶች በሰጡት አስተያየት አባትና ልጅ በአንድ ሆነው መማራቸው በሰንበት ትምህርት ቤቱና በገዳሙ አባቶች መካከል ያለውን ፍቅርና አንድነት እንደሚያሳይ ገልጸዋል፡፡ሥራውም ለሌሎች ሰንበት ት/ቤት አርአያ እንደሚሆንም ተናግረዋል፡፡ ሰንበት ት/ቤቱ ከ1950 ዓ. ም. ጀምሮ እስከ 1993 ዓ. ም. ድረስ «ተምሮ ማስተማር ማኅበር» የሚል ስያሜን ይዞ ቤተ ክርስቲያንን እያገለገለ ነበር፡፡ ከ1993 ዓ. ም. ወዲህ «የተምሮ ማስተማር ሰንበት ት/ቤት» በሚል ስያሜ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡

ለሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ሥራ ድጋፍ ተጠየቀ

ደረጀ ትዕዛዙ

በሲዳማ ጌዴኦ አማሮና ቡርጁ ዞኖችና ልዩ ወረዳዎች ሀገረ ስብከት የሚገኘው የተፈሪ ኬላ ደብረ ስብሐት ቅዱስ በዓለ ወልድ ቤተ ክርስቲያን በእርጅና ምክንያት ከፍተኛ ጉዳት ላይ በመሆኑ አዲስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለማነፅ ለተጀመረው ጥረት የድጋፍ ጥሪ ቀረበ፡፡

ባለፈው የጌታችን መድኃታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት በተከበረበት ዕለት በቤተ ክርስቲያኑ በተከናወኑ ጉባኤ ላይ የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው ሰብሳቢ አቶ ሰብስቤ ካብት ይመር እንደገለፁት፤ ከአርባ ዓመት በላይ የሆነው ይህ ቤተ ክርስቲያን ያለ መሠረት የታነፀ ከመሆኑ በላይ በምስጥ እየተቦረቦረ ለመፍረስ እየተቃረበ ነው፡፡ በመሆኑም አዲስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለማነፅ ባለፈው ዓመት የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ ተዋቅሮ ገንዘብ የማሰባሰቡ ሥራ እየተካኼደ መሆኑን የገለፁት ሰብሳቢው፤ እስካሁን ሰማንያ ሺሕ ብር ከምእመናን ማሰባሰብ መቻሉን ተናግረዋል፡፡

የአዲሱን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ዲዛይን ማኅበረ ቅዱሳን ሠርቶ ለኮሚቴው ያስረከበ መሆኑን የጠቀሱት ሰብሳቢው፤ ሥራውን ለመጀመር በሚደረገው ጥረት በሀገር ውስጥና ውጪ ያሉ ምእመናን እንዲሁም በጎ አድራጊ ድርጅቶችና ማኅበራት ድጋፍ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡ በባንክ መላክ የሚፈልጉም በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ዲላ ቅርንጫፍ የባንክ ሒሳብ ቁጥር 15664   እንዲጠቀሙም ገልፀዋል፡፡

የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ መልአከ ገነት ተሾመ ወሰን በበኩላቸው፤ ሰበካ ጉባኤው፣ ሕንፃ አሠሪ ኮሚቴውና የወረዳው ቤተ ክህነት ከሕዝቡ ጋር በመተባበር ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለማሠራት በብርቱ እንቅስቀሴ ላይ ናቸው፡፡ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለማሠራት የአካባቢው ሕዝብ አቅም ባይኖረውም ተሠርቶ የማየት ከፍተኛ ጉጉት እንዳለው አስተዳዳሪው ጠቅሰው በእስካሁኑ ሂደት ጥሩ ትብብር እያደረገ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በዚሁ በዓለ ንግሥ ዕለት ምእመናኑ ሃያ ሰባት ሺሕ ብር ድጋፍ ማድረጉ ታውቋል፡፡

ማኅበሩ የንብ እርባታ ፕሮጀክቱን አስረከበ

መቀሌ ማዕከል

ማኅበረ ቅዱሳን በማዕከላዊ ዞን አክሱም ሀገረ ስብከት ቆላተንቤን ወረዳ ለሚገኘው የእንደ እጨጌ ኪዳነ ምሕረት ገዳም ከሠላሳ ስድስት ሺሕ ብር በላይ ወጪ ያሠራው የንብ እርባታ ፕሮጀክት ተጠናቆ ርክክብ ተፈጸመ፡፡

በማኅበሩ የመቀሌ ማእከል ጸሐፊ የማን ኃይሉ በዚሁ የርክክብ ሥነ ሥርዓት ላይ እንዳሉት፤  የገዳሙ መነኮሳትን ችግር ለማቃለል ማኅበረ ቅዱሳን ከ2000 ዓ.ም ጀምሮ የፕሮጀክት ጥናት በማካሄደ በ36ሺ 450 ብር ወጪ የንብ እርባታ አጠናቆ ለገዳሙ ማስረከብ ችሏል፡፡

ከቅዱስ ሲኖዶስ ከተሰጠው ሓላፊነቶች አንዱ ገዳማት አድባራትና የአብነት ት/ቤቶች በገቢ እራሳቸውን እንዲችሉ ማገዝ መሆኑን የጠቆሙት ጸሐፊው ወደፊትም ይህን ተግባሩን አጠናክሮ ይቀጥላል ብለዋል፡፡

ግብርናና ገጠር ልማት ጽ/ቤት ተወካይ አቶ ግደይ መለስ በዚሁ ወቅት ባስተላለፉት መልእክት፤ የገዳሙን ቅርስና ሀብት ለቀጣዩ ትውልድ ለማስተላለፍ በሚደረገው ጥረት ለገዳማውያኑ ጥሬ ገንዘብ እየሰጡ ተመፅዋች ከማድረግ ይልቅ እንደ ማኅበረ ቅዱሳን እራስን የሚያስችል ፕሮጀክት ማከናወን ውጤታማ ያደርጋል ብለዋል፡፡ ለፕሮጀክቱ ውጤታማነት ጽ/ቤቱ አስፈላጊውን ድጋፍ እንደሚያደርግም ቃል ገብተዋል፡፡

አበእምኔት መ/ር አባ ገ/ማሪያም ግደይ በበኩላቸው፤ «ገዳሙ ተዳክሞ መነኮሳቱም በችግር ምክንያት ፈልሰው ወደ መዘጋት በተቃረበበት ወቅት ማኅበሩ ደርሶ ለገዳሙ ፀሐይ አወጣለት» ሲሉ በገዳማውያኑ ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

በቀጣይ ሊገጥመው የሚችለውን ችግሮች እየተከታተለ ይፈታ ዘንድ የተማፅንኦ ቃል ያሰሙት አበ ምኔቱ ለፕሮጀክቱ ውጤታማነት መነኮሳቱ ተግተው እንደሚሠሩም ተናግረዋል፡፡
በርክክቡ ወቅት የተገኙት የቆላ ተንቤን ወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ መ/ር አባ እዝራ ሃይሉ ማኅበሩ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሆኖ እያከናወነ ያለው ዘርፈ ብዙ አገልግሎት የሚያስመሰግነው መሆኑን ጠቅሰው መንገዱ እጅግ አድካሚና አስቸጋሪ በሆነ ቦታ መጥቶ ከጥናት ጀምሮ እስከ ትግበራ ያከናወነው ፕሮጀክት ለሌሎች አርአያ ለመሆን የሚያስችለው ነው፡፡

ማኅበሩ የሠራውን ፕሮጀክት ተንከባክበው ውጤታማ በማድረግ ሥርዓተ ገዳማቸውን እንዲያፀኑ አሳስበዋል፡፡ በሠራው የተባበሩትን ሁሉ አመስግነዋል፡፡
ጥር 4 ቀን 2002 ዓ. ም ማኅበሩ ፕሮጀክቱን ለገዳሙ ባስረከበበት ወቅት እንደተገለፀው በሀገራችን ካሉት ቀደምት ገዳማት አንዱ መሆኑ የሚነገርለት ይኸው ገዳም በጣሊያን ወረራ ወቅት ከፍተኛ ጉዳት የደረሰበት ከመሆኑ በተ ጨማሪ ከ1966 ዓ.ም. ለውጥ በኋላ የገዳሙ ይዞታ ሙሉ በሙሉ በመወረሱ ገዳሙ ከፍተኛ ችግር ውስጥ ነበር፡፡

ፕሮጀክት ድጋፍ እንዲውል የማኅበረ ረድኤት ትግራይ ከሃያ ስድስት ሺሕ ብር በላይ ግምት ያለው የማር ማጣሪያ ዘመናዊ ማሽን እና ተያያዥ ቁሳቁሶችን በእርዳታ መለገሱ በፕሮጀክቱ ርክክብ ወቅት ተገልጿል፡፡

ደራሲዋ መጽሐፋቸውን ለሕንፃ ግንባታ ሥራ አበረከቱ

 

 በደረጀ ትዕዛዙ

 
በማኅበረ ቅዱሳን የሕንፃ ግንባታ ጽ/ቤት አሳታሚነት ለኅትመት የበቃው «እመ ምኔት» የተሰኘው የደራሲ ፀሐይ መላኩ አዲስ ረጅም ልብወለድ መጽሐፍ ተመረቀ፡፡  ጥር 9 ቀን 2002 ዓ.ም አንጋፋና ወጣት ደራሲያን፣ የሃይማኖት አባቶች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በተገኙበት በሩስያ ባህል ማዕከል /ፑሽኪን አዳራሽ/ የተመረቀው መጽሐፍ፤ በገዳማውያን ሕይወትና በውስብስብ ወንጀል ታሪክ ላይ ያተኮረ ሲሆን ደራሲዋ የመጽሐፉን ሸያጭ ገቢ ለማኅበሩ ጽ/ቤት ሕንፃ ግንባታ እንዲውል አበርክተዋል፡፡
የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ እና የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው ተወካይ ዲያቆን ዋስይሁን በላይ በዚሁ ምረቃ ወቅት ባስተላለፉት መልእክት፤ ማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ሥር ሆኖ ለበርካታ ዓመታት መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ሲያበረክት መቆየቱን ጠቅሰው ይህንኑ አገልግሎት     በተጠናከረ ሁኔታ ለማከናወን የጽ/ቤት ሕንፃ ግንባታ እያካሄደ ነው፡፡
በሕንፃ ግንባታው ሂደት በርካታ ባለሙያዎች አስተዋጽኦ ማበርከታቸውን፣ ከአሁን ቀደምም በሦስት ደራስያን ሦስት መጻሕፍት ለሕንፃ ግንባታው ሥራ በድጋፍ መልክ መለገሳቸውን የገለጹት ዲያቆን ዋስይሁን፤ ደራሲ ፀሐይ መላኩ ለዚሁ ዓላማ ያደረጉት ድጋፍ የሚያስመሰግናቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በቀጣዮቹ ሁለት ዓመታት ግንባታውን ሙሉ ለሙሉ ለማጠናቀቅ ለታቀደው ለዚሁ ሕንፃ ሥራ በጎ አድራጊዎች ድጋፍ እንዲያደርጉ በማሳሰብ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በመጽሐፉ ዙሪያ አጭር የዳሰሳ ጥናት ያቀረቡት የአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሥነ ጽሑፍ መምህር ተባባሪ ፕሮፌሰር ዘሪሁን አስፋው እንዳሉት፤ ከውስብስብስ የወንጀል ታሪክ እና ከዘመናዊ ረጅም ልቦለድ ባሕርያት አንጻር ድርሰቱ የተዋጣ ነው፡፡
«ከመጽሐፉ ውስጥ በገሀዱ ዓለም የሚታዩ እንደ ፍቅር፣ ጥላቻ፣ ቅናት፣ በቀል፣ ምቀኝነት፣ ታማኝነት፣ ጽናት፣ ወንጀል፣ ተንኮል፣ ትሕትና፣ ደግነት ይንጸባረቁበታል» ያሉት ፕሮፌሰሩ፤ «ደራሲዋ ይህንን መጽሐፍ ለሥነ ጽሑፍ ተማሪዎችና ለአጥኚዎች በማበርከታቸው ሊመሰገኑ ይገባቸዋል» ብለዋል፡፡
የደራስያን ማኅበር ፕሬዝዳንት አቶ ጌታቸው በለጠ በበኩላቸው፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለሀገራችን ሥልጣኔና እውቀት ቀዳሚ መሆኗን ጠቅሰው፤ «ማኅበሩ ለቤተ ክርስቲያን ታላቅ ክብር አለው» ብለዋል፡፡ «ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ምን ያህል ታላቅ ሥራ እንደሚሠራ ማኅበሩ ይገነዘባል፡፡» ያሉት ፕሬዝዳንቱ፤ ለሚያከናውናቸው ሥራዎች የደራስያን ማኅበር ከጎኑ እንደሚቆም ተናግረዋል፡፡ ደራሲ ፀሐይ መላኩ ያበረከቱት አስተዋጽኦም የሚያስመሰግናቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የዕለቱ የክብር እንግዳ መልአከ ምክር ቀሲስ ከፍያለው መራሒ በበኩላ ቸው፤ በመጽሐፉ ውስጥ ያለው ታሪክ ከሀገራችን የረጅም ታሪክና የበለጸገው ባህላችን የተነቀሰ የጥበብ ሀብት መሆኑን   ጠቅሰው፤ «ይህንኑ ከትውልድ ወደ ትውልድ እየተንከባለለ የመጣውን ሀብት የእግዚአብሔር ፈቃድ በመሆኑ ደራሲዋ ገልጸውታል» ብለዋል፡፡
ደራሲ ኃይለ መለኮት መዋዕልም፤ ደራሲዋ ከአሁን ቀደም ለአንባብያን ያበረከቷቸው መጻሕፍት የሚደነቁ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ «ይህን አዲስ መጽሐፋቸውን ለማኅበሩ በጎ ሥራ ማበርከታቸው የሚያስመሰግናቸው ነው» ብለዋል፡፡
የመጽሐፉ ደራሲ ፀሐይ መላኩ በዚሁ ወቅት እንደገለጹት፤ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ለቤተ ክርስቲያኒቱ የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ ሲመለከቱ መንፈሳዊ ቅናት ያድርባቸው እንደነበረ    ጠቅሰው፤ እርሳቸውም የበኩላቸውን ድርሻ ለማበርከት መጽሐፋቸውን ሲለግሱ ከፍተኛ ደስታ እየተሰማቸው መሆኑን ተናግረዋል፡፡
«በማኅበሩ ኤዲቶሪያል ቦርድ ተገምግሞ መጽሐፉ ለኅትመት እንደሚበቃ ሲነገረኝ በደስታ አለቀስኩ» ያሉት ደራሲዋ «የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው ጥያቄያቸውን በመቀበል ለኅትመት ማብቃቱ ሊያስመሰግነው ይገባዋልም» ብለዋል፡፡
ደራሲዋ እንዳሉት በንስሐ አባቶች፣ በመነኮሳትና ካህናት ላይ የሚሰነዘሩ ገንቢ ያልሆኑ ትችቶች ሲያናድዳቸው ለዚህ ምላሽ ይሆን ዘንድ በመልካም ጎኑ ይህንን መጽሐፍ ለመጻፍ ተነሣስተዋል፡፡
መጽሐፍ ከመጻፋቸው በፊት ሐይቅ እስጢፋኖስ አንድ ሱባኤ ከመቀመጣቸው በተጨማሪ ዝቋላ፣ አሰቦት፣ ራማ ኪዳነ ምሕረት፣ ዋሸራ እና ሌሎች ገዳማትን በመጎብኘት በመነኮሳት አኗኗር ላይ ጥናት በማድረግ አሥር ዓመታት ያህል እንደፈጀባቸው ተናግረዋል፡፡ ወደፊት በማንኛውም መልኩ የማኅበረ ቅዱሳንን እንቅስቃሴ ለማገዝ አንደሚጥሩም ገልጸዋል፡፡
በአሥራ አምስት ምዕራፍ የተከፈለው ይኸው «እመ ምኔት» መጽሐፍ 2002 ገጽ ያለው ሲሆን ለመጀመሪያ ጊዜ አምስት ሺሕ ኮፒ ታትሟል፡፡ መጽሐፉ በአሁኑ ወቅት በማኅበሩ ማእከላት፣ በሰንበት ት/ቤቶች እና በግቢ ጉባኤያት አማካኝነት እየተሸጠ መሆኑ ታውቋል፡፡ ደራሲዋን ለማበረታታም ከመጀመሪያው እትም ትርፍ አሥራ አምስት በመቶ ፐርሰንት እንደሚከፈላቸውም ተገልጿል፡፡
የሥነ ሥዕል፣ የሥነ ግጥም እና የእደ ጥበብ ሞያተኛ መሆናቸው የሚነገርላቸው ደራሲ ፀሐይ መላኩ ከአሁን ቀደም «አንጉዝ»፣ «ቋሳ» እና «ቢስራሔል» የተሰኙ ረጅም ወጥ ልቦለድ መጽሐፎችን ለንባብ አብቅተዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት በጡረታ ላይ የሚገኙት ደራሲ ፀሐይ በኢትዮጵያ ደራሲያን ማኅበር ሥራ አስፈጻሚ እንዲሁም የዜማ ብዕር ኢትዮጵያ ሴቶች የሥነ ጽሑፍ ማኅበር የቦርድ አባል ናቸው፡፡
በምረቃው ወቅት የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራን መዝሙር ያቀረቡ ሲሆን፣ መነባንብ እና የደራሲዋ የተለያዩ ግጥሞች በሌሎች አንባብያን ለታዳሚዎቹ ቀርበዋል፡፡ የምረቃውን ሥርዓት ያዘጋጁት የዜማ ብዕር ኢትዮጵያ ሴቶች የሥነ ጽሑፍ ማኅበር ከማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ ጋር በመተባበር መሆኑ ታውቋል፡፡
Abune Timotiwos.JPG

የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የርቀት ትምህርት መርሐግብር ጀመረ

 በመንግስተአብ አበጋዝ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በሰርተፊኬት መርሐግብር የርቀት ትምህርት መስጠት መጀመሩን የኮሌጁ ዲን ዶክተር ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ አስታወቁ፡

Abune Timotiwos.JPG

የኮሌጁ ዲን ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ/ዶክተር/

የርቀት ትምህርት መርሐግብሩን አስመልክቶ ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ በሰጡት መግለጫ፤ የትምህርት መርሐግብሩ በርካታ ሊቃውንት የደከሙበት ረዥም ጊዜ የወሰደ ዝግጅት እንደተደረገበት ገልጸዋል፡፡ የኮሌጁ ዲን አያይዘውም፤ «ኮሌጁ ወደፊት የርቀት ትምህርቱን መርሐግብር ወደ ዲፕሎማና ዲግሪ ደረጃ አሳድጎ ለመቀጠል ዛሬ መሠረቱን ጥለንለታል፡፡ ምእመናንም ካለፈው ይልቅ በቅርበት ቤተክርስቲያናቸውን የሚያውቁበትን፣ ለአገልጋዮችም የተሻለ አገልግሎት ሊፈጽሙ የሚችሉበትን ዕድል ፈጥረንላቸዋል፡፡» በማለት የትምህርት መርሐግብሩ መጀመር ኮሌጁ ለቤተክርስቲያኒቱ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ዕድገት የሚያደርገውን አስተዋጽኦ ለማሳደግ እንደሚያግዘው ብፁዕነታቸው ጨምረው ገልጸዋል፡፡

የኮሌጁ አካዳሚክ ምክትል ዲን መምህር ፍስሐጽዮን ደሞዝ እንደገለጹት፤ ኮሌጁ የማስፋፊያ መርሐግብሮችን ቀይሶ መንቀሳቀስ ከጀመረባቸው ሥራዎች የርቀት ትምህርት መርሐግብር የመጀመሪያው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም የትምህርት መርጃ መጽሐፎቹ /ሞጁል/ የተዘጋጁበትን ቋንቋ ማንበብና መረዳት የሚችሉ በውጪና በሀገር ውስጥ የሚገኙ ምእመናን ሁሉ ሊሳተፉበት የሚችሉበትን ቅድመ ዝግጅት ከየአህጉረ ስብከት ሓላፊዎች ጋር የተደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ የርቀት ትምህርቱን መከታተል የሚሹ ሁሉ በአቅራቢያው ወደሚገኙ የአህጉረ ስብከት ጽ/ቤት የርቀት ትምህርት ማእከል በመቅረብ ሊመዘግቡና ሊከታተሉ የሚችሉ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

በትምህርት ዝግጅቱ ወቅት ልዩ ልዩ እገዛዎችን ያደረጉና በማድረግ ላይ የሚገኙ ዩኒቨርስቲዎች ኮሌጆችና የኮሌጁ ማኅበረሰብ አባላትን በማመስገን የሚጀምሩት መምህር ቸሬ አበበ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ መምህርና የርቀት ትምህርት መርሐ ግብር ጸሐፊ ናቸው፡፡ እንደ መምህር ቸሬ ገለጻ፤ እስከ አሁን ሙሉ ለሙሉ ሥራቸው ተጠናቅቆ የታተሙ የትምህርት መርጃ መጻሕፍት /ሞጁልስ/ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ሥራ አመራር፣ ሥነ-ምግባር፣ ትምህርተ አበው፣ ትምህርተ ሃይማኖት መግቢያ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መግቢያ ሲሆኑ የሌሎች ትምህርቶችም ዝግጅት የቀጠለ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የትምህርቱን መጀመር ከሩቅም ከቅርብም የሰሙ የቤተክርስቲያን ልጆች መመዝገብ መጀመራቸው ታውቋል፡፡ የኮሌጁ ዲን ዶክተር ብፁዕ አቡነ ጢሞቴዎስ ዕድሉ ለመላው ምእመናን የተሰጠ በመሆኑ በተለይ የቤተክርስቲያን አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናት ተጠቃሚዎች እንዲሆኑ ጥሪያቸውን አስተላለፈዋል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔ
Asosa.JPG

በአሶሳ ከማሽ ከአራት ሺሕ በላይ የአካባቢው ተወላጆች ተጠመቁ

በሻምበል ጥላሁን

 
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የነገረ መለኮት ምሩቃን ማኅበር ከአሶሳ ሀገረ ስብከት ጋር በመተባበር ባደረገው ሐዋርያዊ ጉዞ ከአራት ሺሕ በላይ ሰዎች የክርስትና ጥምቀት እንዲጠመቁ ማስቻሉን አስታወቀ፡፡

የነገረ መለኮት ምሩቃን ማኅበር ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍል በላከው መረጃ እንዳስታወቀው፤ ሐዋርያዊ ጉዞና ጥምቀቱ የተከናወነው ከታኅሣሥ 16 እስከ 25 ቀን 2002 ዓ. ም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ሄኖክ፣ ሥራ አስኪያጁ ሊቀ መዘምራን ሐረገወይን ጫኔ፣ የከማሽ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ሥራ አስኪያጅ መልአከሰላም ተገኝ ጋሻው በተገኙበት ነው፡፡

Asosa.JPG

የጉሙዝ ተወላጆች የክርስትና ጥምቀት ሲጠመቁ

በአሶሳ ሀገረ ስብከት ከማሽ ለአሥር ቀናት በቆየው ሐዋርያዊ ጉዞ ከአራት ሺሕ በላይ የጉሙዝ ተወላጆች መጠመቃቸውን መረጃው አመልክቷል፡፡

የክርስትና ጥምቀት ያገኙት እነዚህ የአካባቢው ተወላጆች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እምነት ተከታይ በመሆናቸው መደሰታቸውን የጠቆመው መረጃው፤ ሌሎችም   ለመጠመቅ ቤተ ክርስቲያኒቱን እየተጠባበቁ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

የልዑካን ቡድኑ ምእመናኑን ለማጥመቅ ከአምስትና ስድስት ሰዓታት በላይ በእግር እንደተጓዘ መረጃው አመልክቶ፤ በዞኑ በሚገኙ አሥራ ሰባት የተለያዩ ቦታዎች ምእመናኑን ለማጥመቅ ለተደረገው እንቅስቃሴ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ የከማሼ ቤተክህነት ሥራ አስኪያጅ እና የሰበካ ጉባኤ አባላት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እና ጥረት ማድረጋቸውን ገልጿል፡፡

ምእመናኑ ለጥምቀት የበቁት ከአካባቢው ማኅበረሰብ በተለያዩ ጊዜ በማኅበረ ቅዱሳንና በጽርሐጽዮን የአንድነት ማኅበር አማካኝነት፤ የስብከተ ወንጌል ሥልጠና በተሰጣቸው የአካባቢው ተወላጆች ተተኪ መምህራን ባደረጉት ጥረት፤ እንዲሁም የከማሼ ቤተክህነት በተለያየ ጊዜ ባዘጋጀው የስብከተ ወንጌል ጉባኤ ባገኙት ትምህርት እንደሆነም መግለጫው አመልክቷል፡፡

ይሁን እንጂ ጥምቀቱን ያገኙ በከማሽ ዞን በተለያዩ ወረዳዎች የሚገኙ ምእመናን፤ እምነታቸውን የሚያጸኑበትና ሥጋና ደሙን የሚቀበሉበት፣ ልጆቻቸውን የሚያስጠምቁበት ቤተ ክርስቲያን በአቅራቢያቸው ስለሌለ በሌሎች የእምነት ድርጅቶች እንዳይወሰዱ ሥጋት እንዳለው የነገረ መለኮት ምሩቃን ማኅበሩ አስታውቋል፡፡

በመሆኑም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን በሕገ ልቡና በማመን በናፍቆት እየተጠባበቁ የሚገኙትን የዋሐን ምእመናን ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው ለመመለስና አገልግሎት የሚያገኙበትን ቤተ ክርስቲያን ለማነጽ የቤተ ክርስቲያን ልጆች ሁሉ በጋራ ሊሠሩ እንደሚገባም ማኅበሩ አስታውቋል፡፡

ማኅበሩ ወደፊት በራሳቸው ቋንቋ አገልግሎት የሚሰጡ ሃያ ስምንት የአካባቢውን ወጣቶች በመምረጥ በችግሻቅ ገብርኤልና በኮቢ ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን ግብረ ዲቁና እንዲማሩ መምህር መቅጠሩን መረጃው ጠቁሞ፤ በርካታ ተጠማቂዎች በሚገኙበት አካባቢ የቅድሰት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን እንዲታነጽ የገንዘብ ድጋፍ ማድረጉንም አመልክቷል፡፡

ማኅበሩ በቀጣይም በጊዜ እጥረትና በቦታ ርቀት ምክንያት ያልተጠመቁትን ሌሎችም ለመጠመቅ የሚፈልጉትን ለማጥመቅ እንዲቻል ለሁለተኛ ጊዜ ሐዋርያዊ ጉዞ ለማድረግ ዕቅድ መያዙንም ገልጿል፡፡

ለምእመናኑ ጥምቀት መሳካት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና ሥራ አስኪያጅ ያደረጉትን ከፍተኛ ጥረት አመስግኖ፤ በተለይ የክርስትና ጥምቀቱ የተከናወነበት የከማሽ ዞን ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ መልአከ ሰላም ተገኝ ጋሻውና ሰበካ ጉባኤው ከአሥር ሰዓት በላይ በእግር በመጓዝ ተጠማቂዎችን በማዘጋጀት ያከናወኑት ሥራ ላቅ ያለ መሆኑን አስታውሷል፡፡

ማኅበሩ ለተጠማቂዎቹ ከስምንት ሺሕ በላይ የአንገት ማተብ /ማኅተም/ እና ከአምስት ሺሕ በላይ አልባሳት፣ ለቁርባንና ለጥምቀት የሚያስፈልጉ ንዋያተ ቅድሳት አዘጋጅቶ ወደ ቦታው መጓዙንም መረጃው አመልክቷል፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

«ሙሽራ ያለችው እርሱ ሙሽራ ነው»

ከመስከረም 26 እስከ ሕዳር 6 ቀን ያለው ጊዜ ዘመነ ጽጌ ይባላል፡፡ በዚህ ዘመን ውስጥ አምስት ወይም ስድስት እሑዶች ይውላሉ፡፡

    በእነዚህ እሑዶች በቤተክርስቲያን የሚሰጡትን ትምህርቶች አቅርበናል፡፡

    የመጀመሪያ እሑድ

   

ዮሐ. 3-29

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በልደቱ ጌታን በ6 ወር እንደሚቀድመው ሁሉ በይሁዳ አካባቢዎች እየተዘዋወረ «መንግስተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ» አያለ ማስተማር የጀመረውም ጌታችን ማስተማር ከመጀመሩ 6 ወር ያህል ቀድሞ ነው፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ በእግዚአብሔር መንፈስ የተሞላና ትምህርቱ የሰዎችን ልብ የሚነካ ስለነበር፣ አለባበሱም አስደናቂ ስለነበር እንዲሁም እርሱ እስኪመጣ ድረስ አይሁድ ለ300 ዓመታት ያህል ከእግዚአብሔር የተላከ ነቢይ አይተው ስለማያውቁ በርካታ ሰዎች ትምህርቱን ተቀብለውትና ተከትለውት ነበር፡፡ እርሱም ስለ ኃጢአታቸው እየወቀሰ፣ ንሰሐ እንዲገቡ እያስተማረና ማድረግና መተው የሚገባቸውን እየነገረ የንስሐ ጥምቀት ያጠምቃቸው ነበር፡፡

በዚህም ጊዜ አይሁድ ቅዱስ ዮሐንስን «ይመጣል የተባልከው መሲህ አንተ ነህን?» እያሉ ይጠይቁት ነበር፣ እርሱ ግን «እኔ መሲህ አይደለሁም፤ እኔ የእርሱን መንገድ ለመጥረግ ከፊቱ የተላክሁ መንገደኛ ነኝ፤ እርሱ ግን ከእኔ በኋላ ይመጣል፤ እኔ የማጠምቃችሁ በውኃ ነው፤ እርሱ ግን በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፡፡ እርሱን ለመቀበል በንስሓ ልቡናችሁንና ሰውነታችሁን አዘጋጁ» እያለ ያስተምራቸው ነበር፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በዚህ መልኩ ለ6 ወራት ያህል ከአገለገለ በኋላ ጌታ ወደ እርሱ ዘንድ  መጣ፤ ተጠመቀም፡፡

ቅዱስ ዮሐንስም «እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ፤ ከእኔ በፊት የነበረው፣ ነገር ግን ከእኔ በኋላ የሚመጣው ያልኳችሁ እርሱ ነው፡፡»  ብሎ ለደቀ መዛሙርቱና አብረውት ለነበሩት አስተማራቸው፤ ብዙዎችም ጌታችንን ተከተሉ፡፡

ከዚህ በኋላ ጌታችን በገሊላ «ጊዜው ደርሷል፤ የእግዚአብሔር መንግሥት ቀርባለች፤ ንስሓ ግቡ» እያለ ማስተማር ጀመረ /ማር.1-15/፡፡ ብዙዎችም ተከተሉት፡፡ ደቀ መዛሙርቱንም ይዞ ወደ ይሁዳ ሄደ፡፡ በይሁዳም የጌታችን ደቀመዛሙርት እንደ ቅዱስ ዮሐንስ የንስሓ ጥምቀት ማጥመቅ ጀመሩ፡፡ /ዮሐ.3-22፤ 4-2/ ብዙ ሰዎችም የጌታችን ደቀመዛሙርት ሆኑ፡፡

«በዚህን ጊዜ ዮሐንስ በሳሌም አቅራቢያ ሪምን በተባለ ሥፍራ ብዙ ውኃ ሳለ ያጠምቅ ነበር፣ ሰዎችም ለመጠመቅ ይመጡ ነበር፡፡ . . . » ወደ ዮሐንስም መጥተው «ረቢ /መምህር/ በዮርዳኖስ ማዶ ከአንተ ጋር የነበረው፣ ስለ እርሱም የመሰከርህለት ሰው እነሆ ያጠምቃል፤ ሰውም ሁሉ ወደ እርሱ እየሐሄደ ነው» አሉት፡፡ /ዮሐ.3-23- 27/፡፡

ጠያቂዎቹ ነገሮችን በሥጋዊ ዓይን ይመለከቱ ስለነበር በሁለቱ /በቅዱስ ዮሐንስና በጌታችን/ መካከል ውድድርና ፉክክር ያለ መስሏቸው ነበር፡፡ ንግግራቸው «የአንተ ነገር አበቃለት፣ ሰው ሁሉ ወደዚያ አንተ ወደ መሰከርህለት እየሔሄ ነው፡፡» የሚል መንፈስ ነበረው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ግን እንዲህ ሲል መለሰላቸው፤ «ከሰማይ ካልተሰጠው በቀር ማንም አንዳች ነገርን ገንዘብ ማድረግ አይችልም፡፡ እኔ ክርስቶስ /ይመጣል ተብሎ ትንቢት የተነገረለት አዳኝ መሲህ/ አይደለሁም ብዬ እንደተናገርሁ እናንተ ራሳችሁ ትመሰክራላችሁ /ታውቃላችሁ/፡፡» በማለት የሆነው ነገር ሁሉ የእግዚአብሔር ዓላማና ፈቃድ እንደሆነ፣ እነርሱም ያሰቡት ነገር ከንቱ መሆኑን፣ እንዲሁም እርሱ ዓላማው ሰዎችን ወደ እውነተኛው መድኃኒት ማቅረብ እና መምራት እንጂ ሰዎችን በዙሪያው መሰብሰብ እንዳልሆነ ነገራቸው፡፡ በመቀጠልም የሰዎች ወደ ጌታችን መሄድ እነርሱ እንዳሰቡት እርሱን የሚያሳዝነው ሳይሆን የበለጠ የሚያስደስተው መሆኑን እንዲህ ሲል ገለጠላቸው፡፡

«ሙሽራ ያለችው እርሱ ሙሽራ ነው፤ ድምፁን ለመስማት አጠገቡ የሚቆሙ ሚዜ ግን የሙሽራውን ድምፅ ሲሰማ እጅግ ደስ ይለዋል፤ ያ ደስታ የእኔ ነው፡፡ እርሱም አሁን ተፈጽሟል፡፡ እርሱ ሊልቅ፣ እኔ ላንስ ይገባል፡፡»/ዮሐ 3. /

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ በሙሽራ በሙሽሪት እና በሚዜ መስሎ የተናገረው የክርስቶስን፣ የቤተክርስቲያንን እና እንደ ራሱ ያሉ አገልጋዮችን ነገር ነው፡፡ በክርስቶስ እና በቤተክርስቲያን መካከል ያለውን ግንኙነት በሙሽራ እና በሙሽሪት /በባል እና በሚስት/ መካከል ካለው ግንኙነት ጋር የሚያመሳስሉት በርካታ ነገሮች አሉ፡፡

–    ሙሽሪትን /ሚስቱን/ የሚመርጣት፣ የሚያጫት ሙሽራው /ባል/ ነው፡፡ ቤተክርስቲያንንም የመረጣትና ሙሽራው እንድትሆን ያደረጋት ራሱ ክርስቶስ ነው፡፡

–    ባል ሚስቱን መጠበቅ፣ መንከባከብ ራሱን አሳልፎ እስኪሰጥ ድረስ መውደድ ይጠበቅበታል፤ ክርስቶስም ስለ ቤተክርስቲያን ይህንን አድርጓል፡፡ ሚስት ራሷን ለባሏ ራሷን ማስገዛት አለባት፡፡ ቤተክርስቲያንም ለክርስቶስ እንዲሁ ማድረግ አለባት፡፡

–    ሙሽሪት በሰርጓ ቀን ራሷን አስውባ ትቀርባለች፤ ክርስቶስም ቤተክርስቲያንን ወደ ራሱ ያቀረባት ሙሽራው ያደረጋት በሥጋውና በደሙ አንጽቶ፤ ነውሯን አስወግዶና አስውቦ ነው፡፡

በዚህም ምክንያት የእግዚአብሔርን እና የሰው ልጆችን ግንኙነት በሙሽራና በሙሽሪት /በባልና በሚስት/ እየመሰሉ በብሉይ ኪዳንም በሐዲስ ኪዳንም ብዙዎች አስተምረዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን ከነበሩት መካከል በፍቅር ግጥም መልክ የተጻፈው መኅልየ መኅልይ ዘሰሎሞን፣ ትንቢተ ሕዝቅኤል /ምዕራፍ 16/፣ ትንቢተ ሆሴዕ /ምዕ.1/ ተጠቃሸ ናቸው፡፡

በሐዲስ ኪዳን ደግሞ ቅዱስ ጳዉሎስ በሁለተኛው የቆሮንቶስ መልእክቱ «እናንተ እንደ ንጽሕት ድንግል ለክርስቶስ ለማቅረብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለሁ» /11-2/ ብሎ ጽፏል፡፡ ለኤፌሶን ሰዎች በላከው መልእክቱም እንዲህ ይላል፤

«ሚስቶች ሆይ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁም ተገዙ ክርስቶስ አካሉ ለሆነችው አዳኟ ለሆናት ቤተ ክርስቲያን ራስ እንደሆነው ሁሉ ባልም የሚስቱ ራስ ነው፡፡ ባሎች ሆይ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን እንደወደዳትና ራሱንም ስለ እርሷ አሳልፎ እንደሰጠ እናንተም ሚስቶቻችሁን ውደዱ በቃሉ አማካኝነት በማንፃት እንድትቀደስ. . . አንዳች እንከን ሳይገኝባት ቅድስትና ነውር አልባ የሆነች ክብርት ቤተክርስቲያን አድርጎ ሊያቀርባት ነው. . . ይህ ምስጢር ታላቅ ነው፤ እኔም ይኽንን ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተክርስቲያን እናገራለሁ፡፡» /5-22-32/፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ነባቤ መለኮትም በራእይ መጽሐፉ ሰማያዊት ቤተክርስቲያን የሆነች አዲሲቷን ኢየሩሳሌምን የበጉ ሙሽራ ይላታል፡፡

«ቅድሰቲቱ ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም ለባሏ እንደተዋበች ሙሽራ ተዘጋጅታ ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ» /21-1-9/፡፡

በዚህ ትምህርት ይህን በሙሽራ እና በሙሽሪት መካከል ባለው የፍቅር ግንኙነት የተመሰለውን የክርስቶስ /የእግዚአብሔር/ እና የቤተክርስቲያን /የእኛን/ ግንኙነት በሁለት ከፍለን እንመለከታለን

    1. እግዚአብሔር በእኛ ውስጥ ምን ይመለከታል
    2. እኛስ በእግዚአብሔር ውስጥ ምን እንመለከታለን

1.   እግዚአብሔር በእኛ ውስጥ ምን ይመለከታል? እርሱ እንደወደደን የሚያደርግ ምን አለ?

በሕዝቅኤል የትንቢት መጽሐፍ ስለዚህ ጉዳይ የተጻፈው እንዲህ ይላል፤

«ኢየሩሳሌም    /እስራኤል/ ሆይ….. በተወለድሽ ጊዜ በዚያው ቀን እትብትሽ አልተቆረጠም፤ ንጹሕም ትሆኚ ዘንድ በውኃ አልታጠብሽም፤ በጨውም አልተወለወልሽም፤ በጨረቅም አልተጠቀለልሽም፤ በጭንም አልታቀፍሽም፡፡ በተወለድሽበት ቀን ከሰውነትሽ ጉስቁልና የተነሣ በሜዳ ላይ ተጣልሽ እንጂ ከዚህ አንዳች ይደረግልሽ ዘንድ ዓይን አልራራልሽም፤ ማንም አላዘነልሽም፡፡

«በአንቺም ዘንድ ባለፍሁ ጊዜ በደምሽም ተለውሰሽ ባየሁሽ ጊዜ ‘ከደምሽ ዳኝ አልሁ’. . . አንቺም አደግሽ፤ ታላቅም ሆንሽ፤ በእጅጉም አጌጥሽ፤ ከከተማ ወደ ከተማ ገባሽ፤ ጡቶችሽም አጎጠጎጡ፤ ጠጉርሽም አደገ፤ . . . በውኃም አጠብሁሽ፣ ከደምሽም አጠራሁሽ. . . ዘይትም ቀባሁሽ፣ ወርቀዘቦም አለበስሁሽ፣. . . በጌጥም አስጌጥሁሽ. . . እጅግም ውብ ሆንሽ፤ ለመንግሥትም የተዘጋጀሸ አደረግሁሽ . . .» /16.4-14/፡፡

እግዚአብሔር የሚያየን ትንሽ ፣በኀጢአት የቆሸሸች ¬፣ የማታምርና የተመልካችን ዓይን የማትስብ ጎስቋላ ነፍስ ሆነን ነው፡፡

ነገር ግን በዚህ ሁኔታ ሲየየን እርሱ የማያየው ዛሬ የሆንነውን ብቻ ሳይሆን ወደፊት ልንሆን የሚችለውን ነው፡፡ ኃጢአቶቻችን፣ ቆሻሻችንን አለማማራችንን አይወድም፡፡ ነገር ግን እነዚህን በንስሓ ብናስወግዳቸው የሚኖረን ውበት ያውቃል፡፡ይህም ይስበዋል፡፡

ስለዚህም ጠፍተን ሳለን ካለንበት ከወደቅንበት መጥቶ ከነቆሻሻችን ይወስደናል፡፡ አስተምሮ፣ ለውጦ፣ የተሻልን ያደርገናል፤ አጥቦ ያነጻናል፤ወዳጆቹ ሙሽሮቹ ያደርገናል፡፡

ሰዎች አብረዋቸው እንዲሆኑ የሚፈልጉት በራሳቸው ደረጃ ያሉ ሰዎችን ነው፡፡ በሌሎችም ሰዎች ዘንድ እንዲሆን የሚጠበቀው ይኸው ነው፡፡ አንዳንድ ሰዎች ይኽን ድንበር ሲያልፉና ከእነርሱ በጣም ዝቅ ካሉ ሰዎች ጋር ተወዳጅተው ማየት ብዙዎቻችንን ያስደንቃል፡፡ እስቲ የእኛን ኃጢአትና የእግዚአብሔርን ቅድስና እናስበውና በመካከላችን ያለውን ልዩነት ደግሞ እናስተውለው፡፡ የእርሱ ከእኛ ጋር መወዳጀት እንዴት አስደናቂ ነው! 

እንግዲህ እግዚአብሔር እኛን የሚወደን እንዲህ ሆነን እየተመለከተን መሆኑን ሁል ጊዜ ማሰብ ይገባናል፤ በእውነት በእርሱ እንድንወደድ የሚያደርግ ምንም መልካም ነገር የለንም፡፡    ስለዚህ ለጸሎት በፊቱ ስንቆም፣ ወደ ቤተክርስቲያንም ስንገባ ከልባችን በፍርሃት ሰግደን ይቅርታውን መጠየቅ አለብን፡፡ «ይኽ የእግዚአብሔር ቤት ነው፣ የቅዱሳን፣ የመላእክቱም ማደሪያ ነው፤ እንዴት እዚህ ልገኝ እችላለሁ?» ልንል ይገባናል፡፡ አስቀድመን እንዳልነው የሚወደው ኃጢአታችንን ሳይሆን ይህንን ስናስወግድ የሚኖረንን ውበት መሆኑን ተረድተን ውለታውን እያሰብን በተሰጠን ጊዜ ለንጽህና ለቅድስና ልንተጋ ይገባል፡፡ስብሐት ለክርስቶስ ዘአፍቀረነ፡፡

2. እኛ በእርሱ ውስጥ ምን እናያለን? በእርሱ እንድንሳብ የሚያደርገን ምን ነገር አለ?

ከላይ እንዳየነው እግዚአብሔር እኛን የወደደን እንዲሁ ነው፡፡ የሰው ልጆች ግን ለመውደድ ምክንያት (ድጋፍ) ያስፈልገናልና እርሱን ለመውደድ የሚያበቁ ነገሮችን እርሱ ራሱ አዘጋጅቶልናል፡፡

ይቅርታው

ከላይ እንደተመለከትነው አምላካችንን ስናስብ ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን፣ ሊያነጻን መውደዱን እናስባለን፡፡ ይቅር የተባለ ሰው ደግሞ ይቅር ያለውን አብዝቶ ይወዳል፤

እኛ እንደ ጠፋው ልጅ ትተነው ሄደን በጣም ርቀን ያለንን ሁሉ አጥተን ተመልሰን ስንመጣ እርሱ ቆሞ ሲጠብቀን እናገኘዋለን፤ በመምጣታችን ደስ ይለዋል እንጂ በመቆየታችን፣ እርሱን በመካዳችን አይቆጣንም፡፡ ስለዚህ እንደ ማርያም እንተ እፍረት በፍቅር በእግሩ ላይ ሽቱ እንድናፈስ፣ እንድንጠርገው እንገደዳለን፡፡

ሰማያዊ ድኅነት

በዕለተ አርብ ከጌታችን ጎን ተሰቅሎ የነበረው ወንበዴ ጌታችን ወደ ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚወሰደው መሆኑን ተረዳ፡፡ ስለዚህም «በመንግሥትህ አስበኝ» ሲል ተማፀነ፡፡ «ከአንተ ጋር ውሰደኝ» እንደማለት ያለ ነው፡፡

ከእግዚአብሔር ጋር መሆን ዘለዓለማዊ ሕይወት የሚገኝበት ብቸኛ መንገድ ነው፡፡ እርሱም ይህንን ሊሰጠን ፈቅዷል፡፡ ይህም እንድንወደው በፍቅሩ እንድንወድቅ ያደርገናል፡፡

ምድራዊ ድኅነት

በችግር ውስጥ የነበረና በእግዚአብሔር ችግሩ የተቀረፈለት ሰው እግዚአብሔርን ይወዳል፡፡ እግዚአብሔር በየቀኑ በተለያዩ መንገዶች ያድነናል፤ በጸሎተ ቅዳሴ ላይ ካህኑ እንዲህ እያለ ይጸልያል፡፡ «ለእኛ በጎ ነገርን ያደረገ  ይቅር ባይና መሐሪ እግዚአብሔርን እናመሰግነዋለን፣ ከመከራ ሰውሮናልና፣ ጠብቆናልና፣ ረድቶናልና፣ ወደ እርሱም ተቀብሎናልና፣ አጽንቶ ጠብቆናልና. . . እስከዚህም ሰዓት አድርሶናልና»

የፍቅር ዝንባሌ
 
ሰዎች በባሕርያችን መውደድንና መወደድን የመፈለግ ከፍተኛ ዝንባሌ አለን፡፡ ይህ ፍቅርም ዘለዓለማዊ እንዲሆን እንፈልጋለን፡፡ «ለዘለዓለም እወድሃለሁ፤ እወድሻለሁ» የሚለው አባባልም ከዚሁ የመነጨ ነው፡፡

እግዚአብሔር ይኽንን ዝንባሌ በውስጣችን ያስቀመጠው እርሱን እንወድበት ዘንድ ነው፡፡ በዚህ ምድር ያሉትን የቤተሰብ፣ የወንድም፣ የጓደኛ እና ጾታዊ ፍቅሮችንም ያዘጋጀው ከእርሱ ጋር ወደሚኖረን ፍፁምና ሰማያዊ ፍቅር የሚያደርሱ መለማመጃዎች፣ ቅምሻዎች. . . እንዲሆኑ ነው፡፡ፍጻሜያቸው ግን ከእርሱ ጋር የሚኖረን ዘለዓለማዊ ፍቅር ነው፡፡

ስለዚህ ይህ እርሱ ራሱ በውስጣችን ያስቀመጠው ዝንባሌ እርሱን ወደ መውደድ ያመራናል፤ እርሱ ምን ያህል እንደወደደን ስናስብም እኛም ለእርሱ ያለን ፍቅር ይጨምራል፡፡
 
እንግዲህ እግዚአብሔር እኛን ያለዋጋ ወዶናል፤ እርሱን እንወደው ዘንድ እነዚህን ሁሉ ነገሮች አዘጋጅቶ ቆሞ ይጠብቀናል፤ ደጃችንንም ያንኴኴል፤ ስለዚህም ጊዜያችን ሳያልፍ፤ እርሱም ከእኛ ፈቀቅ ሳይል ጥሪውን ልንሰማ፤ የልባችንን በር ከፍተን በፍቅር ልናስተናግደው ይገባናል፤ ቅዱስ ዳዊት አንድም ስለ ንጽሕት ነፍስ አንድም ንጽሕት ስለሆነች ስለ እመቤታችን በዘመረው መዝሙር ነፍሳችንን እንዲህ ይላታል፤ ”ልጄ ሆይ አድምጪ አስተውዪ ጆሮሽንም አዘንብዪ ሕዝብሽንና የአባትሽን ቤት እርሽ፡፡ንጉሥ በውበትሽ ተማርኴልና፡፡” /መዝ 46-10-11/

 ወስብሐት ለእግዚአብሔ