‹‹በእንተ አቡነ አቢብ!››

ጥቅምት ፳፬፤፳፻፲  ዓመተ ምሕረት

በዐሥራ ሦስተኛው ክፍለ ዘመን በሮሜ ሀገር የተወለዱት ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብ የስማቸው ትርጓሜ “የብዙኀን አባት” አንድም ቡላ ማለት “የተወደደ፣ እግዚአብሔር የተለየ” ነው፡፡ መጽሐፈ ስንክሳር ታላቅና ክቡር የሆነ አቢብ የተባለ መስተጋድል አባ ቡላ ተብሎም የሚታወቅ አባት በከበረች ዕለት ጥቅምት ሃያ አምስት (፳፭) እንዳረፈ ይጠቅሳል፡፡

አስቀድሞም ከሃዲው ንጉሥ መክስምያኖስ ክርስቲያኖች ላይ ባመጣባቸው ስደት ምክንያት አባትና እናታቸው አብርሃምና ሐሪክ ተሰደው ሲኖሩ ልጅን ባማጣታቸው በጸሎትና በጾም አምላካቸው እግዚአብሔርን በመለመናቸው መልአክ ለአብርሃም ተገልጾ “ይህ ፍሬ የአንተ ነው፤ እርሱም ወደ እኔ የሚቀርብ እግዚአብሔርን የሚያስደስት ፈቃዱንም የሚፈጽም የአመረ መባዕ ነው” በማለት እግጅ መልካም ፍሬን ሰጠው፡፡ ደጉ ሰው አብርሃምም ከእንቅልፉ ነቅቶ ለሚስቱ በሕልሙ ያየውንና መልአኩ የነገረውን ሁሉ ነገራት፡፡ እርሷም ደስ ተሰኘች፤ ሁለቱም በአንድነት እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ የአብርሃም ሚስት ሐሪክ በፀነሰች ጊዜም በቤታቸው አደባባይ ሁለንተናው መልካምና ታላቅ ዛፍ በቀለ፡፡ በቅጠሉም ላይ በዕብራይስጥ ቋንቋ የተጻፈ “በጽዮን አድሮ የሚኖር የያዕቆብ ፈጣሪ የእግዚአብሔር አገልጋይ ቡላ” የሚል ጽሕፈት አገኙ፡፡ በዚህም ጊዜ በተአምሩ ተደንቁ፡፡

ቀጥሎም መልኩ ያማረ ከብርሃናት ይልቅ ፊቱ የሚያበራ ወንድ ልጅን ወለደች፡፡ ከዚህም በኋላ ለአንድ ዓመት ያህል ክርስትናን ሳይስነሡ ሲያኖሩት እመቤታችን ድንግል ማርያም ለሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ለሰለባስትሮዮስ ተገልጣ ወደ አብርሃም ቤት በመሄድ ሕፃኑን እንዲያጠምቀው ስላዘዘችው የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው፡፡  ስሙንም “ቡላ” ብላ ሰየመው፤ ወላቹም በዚህን ጊዜ አደነቁ፡፡ ጸሎትም አድርጎ የቊርባን ኅብስትና ወይን የተመላ ጽዋ ከሰማይ ስለወረደ ቀድሶ ቅዱስ ሥጋውንና ደሙን ሕፃኑንና ወላጆቹን አቀበላቸው፡፡  በዚያንም ጊዜ ሕፃኑ የአንድ ዓመት ልጅ ሲሆን “በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ አብ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው፤ በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ ወልድ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው፤ በባሕርይ በህልውና በመለኮት በአብ ከወልድ ጋር አንድ የሆነ መንፈስ ቅዱስ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው” ብሎ ተናገረ።

ጥቂት ዓመታት ካለፉም በኋላ በኅዳር ሰባት ቀን አባቱና እናቱ ዐረፉ፤ ሕፃን ቡላ ዐሥረኛው ዓመቱ ላይ ሌላ መከራ አጋጠመው፤ ሕዝቡን ለጣዖት መስገድ የሚያስገድድ መኮንን እንደመጣ በሰማ ጊዜም ሕፃኑ በፊቱ ቀርቦ የረከሱ ጣዖታትን ረገመ፡፡ በአካል ትንሽ መሆኑን የተመለከተው መኮንኑ ለጊዜው ቢያደንቅም በችንካር ቸንክረው፣ ሥጋውን ሰነጣጥቀው፣ ቆዳውንም ከአጥንቱ እንዲገፉት፣ እጁቹንና እግሮቹን በመጋዝ እንዲቀርጡ፣ በሶሾተልና በጦሮች አድርገው ከመንኮራኩር ውስጥ እንዲጨምሩት፣ ዳግመኛ በመንገድ ላይ እንዲጎትቱት አዘዘ፡፡ ሆኖም መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ ስላዳነው ያለ ጉዳት ጤነኛ ሆነ፡፡ ቅዱሱ ሕፃን ቡላ ግን ሌላ መኮንን ጋር ሄዶ የረከሱ ጣዖታትን ገረመ፡፡ በዚህም ጊዜ መኮንኑ ተቆጥቶ ሚያዝያ ወር በባተ በዐሥራ ስምንተኛው ቀን ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ ስላዘዘ ቆረጡት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ከሰማይ ወርዶ ከሞት አስነሣው፡፡ በዚህም ጊዜ የመነኮስ ልብስንና አስኬማን በመስቀል ምልክት አለበሰውና እንዲህ አለው፤ “ከቅዱሳንና ከጻድቃን አንድነት ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር አዝዞአል፡፡”

ቅዱስ አባታችንም በዚህ ጊዜ ከደረቅ ተራራ ላይ ወጥተው በውስጧ እየታገደሉ ሲኖሩ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራ መስቀል በማሰብ ከረጅም ዕንጨት ላይ በመውጣት ራሳቸውን ወደታች ሁል ጊዜ ይወረውሩ ነበር፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀንም በዛፍ ላይ ሲወረወሩ ሰይጣን በቅናት ተነሣስቶ ገደላቸው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አነሣቸውና “ከእንግዲህ ስምህ ቡላ አይሁን፤ አቢብ ይባል እንጂ፤ የብዙዎች አባት ትሆናለህና” አላቸው፡፡

ከዚህ ቀጥሎ አቡነ አቢብ የክርስቶስን ፍቅር በመጨመር ፊታቸውን ይጸፉ፣ ሥጋቸውን በጥቂት ይቆርጡ፣ ጀርባቸውን ሰባት ጊዜ ይገርፉ ነበር፡፡ ጌታችን በዚህ ጊዜም ከእርሳቸው ሳይለይ ይፈውሳቸው ነበር፡፡ በየእሑድም ቀን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም እንደተወለደ፣ በሌሎች ቀኖችም እንደተያዘና ከአይሁድ መከራ እንደ ተቀበለ ሁኖ ይገለጽላቸው ነበር። በዚህም የተነሣ ለአርባ ሁለት ዓመታት ምግብ ሳይበሉና ውኃ ሳይጠጡ ከኖሩ በኋላ  ለዐሥራ ሁለት ወር በራሳቸው ተተክለው ሲኖሩ ናላቸው ፈስሶ አለቀ፡፡

የጌታችንን መከራ በአሰቡ ጊዜ በአንዲት ቀን ሰይፉን በአንጻሩ ተክለው ከዕንጨት ላይ በመውጣት በላዩ ወድቀው ሞቱ፤ ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም ከአእላፍ መላእክት ጋር መጥታ “የእኔና የልጄ ወዳጅ ሰላምታ ይድረስህ” አለችው። ከበድኑም ቃል ወጥቶ “የሰማይና የምድር ንግሥት እመቤቴ ሰላምታ ይገባሻል” አላት፡፡ እርሷም በከበሩ እጆቿ ዳሥሣ ከሞት አስነሣቸው።

ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብ ከዚህ ዓለም ድካም የሚያርፉበት ጊዜ ሲደርስ ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ በእጁ ልዩ የሆኑ አክሊሎችን የሚያበሩ ልብሶችንም ይዞ ተገለጠለትና እንዲህ አላቸው፤ “ወዳጄ አቢብ ሆይ፥ በማያልቅ ተድላ ደስታ ደስ አሰኝህ ዘንድ ወደ እኔ ና፤ ስምህን ለሚጠራ መታሰቢያህን ለሚያደርግ እኔ ኃጢአቱን አስተሠርይለት ዘንደ በራሴ ማልኩልህ፤ ወይም ለተራቆተ የሚያለብሰውን፣ ለተራበም የሚያጠግበውን፣ ለተጠማ የሚያጠጣውን፣ የገድልህን መጽሐፍም የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውንና የሚሰማውን፣ በጸሎትህም የሚታመኑትን ሁሉ እስከ ዐሥር ትውልድ እምራቸዋለሁ፤” ይህንም ብሎ አፋቸውን ሳማቸው፤ በደረቱም ላይ አድርጎ ወደ አየር አወጣቸው፤ የመላእክትንም ምስጋና በሰማች ጊዜ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች፤ ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ገባች።

እነሆ ሰማዕቱ አቡነ አቢብ ምእመናን በሚቀምሱት የዕለት ምግብ አማካኝነት በነፍስም በሥጋም እንዲድኑ አስገራሚ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደተቀበሉ የሚናገር የገድል ተአምራታቸው ይህ ነው፡- ብዙዎች ስማቸውን ጠርተው በሚቀምሱት ምግብ አማካኝነት ከተለያዩ በሽታዎች የተፈወሱ አሉ፡፡ ይህ ቃል ኪዳናቸው ለሁላችን ይደረግልን ዘንድ ከመመገባችን አስቀድሞ የእግዚአብሔርን ስም እንጥራ (አቡነ ዘበሰማያትን ማለቱ ነው፡፡) ከተመገብን በኋላም የዕለት ምግባችንን ስለሰጠን እግዚአብሔርን እናመስግን፡፡ ዘወትር ከተመገብን በኋላ ሦስት ጊዜ ‹‹ስለ ወዳጅህ ስለ አቡነ አቢብ›› እያልን ሦስት ጊዜ እንቅመስ፡፡ አስቀድሞ ጌታችን መድኃኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአቡነ አቢብ ተገልጦላቸው ‹‹…ወዳጄ አቢብ ሆይ! የሰውን ልጅ ለማዳን የተቀበልኩትን ሕማማተ መስቀል እያሰብህ ይህንን ሁሉ ገድል ፈጽመሃልና ምን እንዳደርግልህ ትወዳለህ?›› አላቸው፡፡ ንዑድ ክቡር ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብም ‹‹ጌታዬ አምላኬ መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! መቼም ሰው ሁሉ ሳይመገብ አይውልም፤ አያድርምና በተመገበ ጊዜ ስሜን ጠርቶ የተማጸነውን ማርልኝ›› አሉት፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አባታችን አቡነ አቢብ ለሰው ልጆች ያላቸውን ፍቅር ካደነቀ በኋላ ‹‹…ከማዕድ በኋላ ስብሐት ተብሎ የተረፈውን በእንተ አቢብ ብሎ ሦስት ጊዜ የተመሰገበውን ሰው ሁሉ እምርልሃለሁ›› በማለት ታላቅ የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡

ያልተጠመቀ አረማዊ አሕዛብም እንኳን ቢሆኖ ‹‹ስለ አቡነ አቢብ›› ብሎ ከተማጸነ ጌታችን ያንን ሰው ወደ ቀናች የእምነት መንገድ ሳይመራወና በንስሓ ሳይጠራው በሞት እንደማይወስደው ለአባታችን ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ለማዳን ትንሽ ምክንያትን የሚፈልግ ያለ ምክንያትም የማያድን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ እስከ ዘለዓለም ድረስ ይክበር ይመስገን! ሰው ተመግቦ እንኳን መዳን እንዲችል ይህን ድንቅ ቃል ኪዳን ለአባታችን ሰጥቷቸዋልና በየቀኑ በዚህ ቃል ኪዳን እንጠቀምበት፡፡ ተመግበን ከጨረስንና ስብሐት ካልን በኋላ ሦስት ጊዜ ‹‹በእንተ አቡነ አቢብ›› ብለን እንቅመስ፡፡ በጥቅምት ፳፭ ቀን በዓመታዊ የዕረፍት በዓላቸው ታስበው የሚውሉት ጻድቁና ሰማዕቱ አቡነ አቢብ የቃል ኪዳናቸው ረድኤት በረከት ይክፈሉን!

(ምንጭ፡ደብረ ሰላም ቃጭልቃ አቡነ አቢብ ገዳም ያሳተመው ገድለ አቡነ አቢብ፣ ገጽ ፻፭)

በእንተ ቅዱሳን ኀሩያን)

ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ

ጥቅምት ፲፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

የቊስጥንጥንያ ንጉሥ የቴዎዶስዮስ ልጅ የቅዱስ ገብረ ክርስቶስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው ጥቅምት ፲፬ የከበረ በዓል ነው። ቴዎዶስዮስ የተባለው ንጉሥ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነው፤ ሚስቱም በጎ የምትሠራ እግዚአብሔርንም የምትፈራ ናት፤ ስሟም መርኬዛ ነው። እነርሱም ልጅ ስለሌላቸው ያዝኑ ነበር፤ ወደ ኢየሩሳሌምም ሒደው ስእለትን ተሳሉ፤ ቸር መሐሪ ወደሆነ እግዚአብሔርም ለመኑ፤ እርሱም ልመናቸውን ተቀበሎ ይህን ያማረ ልጅ ሰጣቸው፤ ስሙንም አብደልመሲህ ብለው ሰየሙት፤ ትርጓሜውም ገብረ ክርስቶስ ማለት ነው። የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ የሥጋዊንም ትምህርት አስተማሩት።

አድጎ በጕለመሰም ጊዜ የሮሜውን ንጉሥ ልጅ አጭተው እንደ ሥርዓቱ አጋቡት ከሌሊቱ እኩሌታም በሆነ ጊዜ ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ተነሥቶ ወደሙሽራዪቱ ገባ፤ እጅዋንም ይዞ ከእርስዋ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ ። ከዚያም የሃይማኖት ጸሎት በአንድ አምላክ እናምናለን የሚለውን እስከ መጨረሻ ጸለየ፤ የተሞሸረበትንም ልብስ ከላዩ አውልቆ የግምጃ ልብስን ለበሰ፤ ወደ ሙሽሪቷም ሒዶ ራስዋን ሳማት፤ እንዲህም እያለ ተሰናበታት፤ “እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ይኑር፤ ከሰይጣን ሥራ ሁሉ ያድንሽ።” እርሷም አልቅሳ “ጌታዬ ወዴት ትሔዳለህ? ለማንስ ትተወኛለህ? አለችው፤ እርሱም “በእግዚአብሔር ዘንድ እተውሻለሁ፤ እኔም ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን ልከተለው እሔዳለሁ፤ የአባቴ መንግሥት አላፊ ነውና አንቺም መሐላሽን አስቢ” አላት፤ ያን ጊዜ መሐላዋን አስባ ዝም አለች።

ለሠርጉም የታደሙት ሁሉ እንደተኙ በሌሊት ወጥቶ ሔደ፤ ወደ ባሕርም ዳርቻ ደርሶ በመርከብ የሚጓዙ መንገደኞችን አገኘ፤ የዓመት መንገድ ወደሚሆን አርማንያም እስከሚደርስ ከእነርሱ ጋር ተጓዘ።

ነግቶ ወደ ሠርጉ አዳራሽ አባትና እናቱ በገቡ ጊዜ ሙሽራውን ልጃቸውን አላገኙትም፤ ሙሽሪትንም “ልጃችን ወዴት አለ?” ብለው ጠየቋት፤ እርሷም እንዲህ አለቻቸው። “በሌሊት ወደ እኔ ገባ፤ መሐላን አማለኝ፤ ከእኔ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ፤ ራሴንም ስሞኝ ከእኔ ዘንድ ወጣ፤ እኔም እያለቀስኩ ብቻዬን አደርኩ፤” ነገርዋንም ሰምተው ወድቀው በመጮህ ታላቅ ልቅሶን አለቀሱ።

በዚያችም ጊዜ በሀገሮች ውስጥ ሁሉ ልጁን ገብረ ክርስቶስን ይፈልጉት ዘንድ ንጉሡ አምስት መቶ አገልጋዮቹን ላከ፤ ለድኆችና ለምስኪኖችም ምጽዋት አድርገው የሚሰጥዋቸውን ብዙ ገንዘብን ሰጣቸው።

ገብረ ክርስቶስ ግን በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በአርማንም አገር በተሠራች በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ደጅ የሚኖር ሆነ። አባቱ የላካቸውም ሁለቱ አገልጋዮች ከዚያ ደርሰው ስለርሱ መረመሩ፤ ግን ወሬውን ማግኘት ተሳናቸው፤ ለድኆችም ምጽዋትን ሰጡ፤ እርሱም ከድኆችም ጋር ምጽዋትን ተቀበለ።

በዚያም ዐሥራ አምስት ዓመት ከኖረ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለአንድ ቄስ ተገለጸችለት፤ ቦታውንም አመልክታ እንዲህ አለችው። “የእግዚአብሔር ሰው ገብረ ክርስቶስን ይዘህ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ አስገባው፤ ከውጭ አትተወው፤” ቄሱም እመቤታችን እዳዘዘችው አደረገ።

ከዚህም በኋላ የተመሰገነ ገብረ ክርስቶስ በሌሊት ተነሣ ከእመቤታችንም ሥዕል ፊት ቁም ጸለየ፤ እንዲህም አላት፤ “እመቤቴ ሆይ የተሠወረ ሥራዬን አንቺ ለምን ገለጥሽ፤ አሁንም ወደሚሻለኝ ምሪኝ፤” ይህንንም ብሎ የእመቤታችንን ሥዕሏን ተሳልሞ በሌሊት ወጥቶ ወደ ባሕሩ ወደብ ደረሰ፤ ወደሌላ ሀገርም ሊሔድ ወዶ በመርከብ ተሳፈረ። ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ ከአባቱ አገር ደረሰ የአባቱና የእናቱም ባሮች እየናቁትና እየሰደቡት በአባቱ ደጅ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረ።

ሲገቡና ሲወጡም “ሽታው እንዳያስጨንቀን ይህን ምስኪን አስወግዱልን” ይላሉ፤ ወጭትና ድስትም አጥበው በላዩ ይደፉበታል፤ ውሾችም እንዲናከሱበትና እንዲበሉት የሥጋ ትርፍራፊ ይጥሉበታል፤ ውሾች ግን ቁስሉን ይልሱለት ነበር፤ እንደዚህም አብዝተው አሠቃዪት።

ከዚህም በኋላ ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ለመነ፤ “ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ለአባቴና ለእናቴ ባሮች በደል እንዳይሆንባቸው ወዳንተ ውሰደኝ።” በዚያንም ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው። ከዚህም በኋላ ገድሉን ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ጻፈ፤ በእጁም ጨብጧት ዐረፈ።

በእሑድ ቀንም ሕዝቡ ሁሉና ካህናቱ ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋር በቅዳሴ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሳሉ የእግዚአብሔርን ሰው በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ቤት ፈልጉት የሚል ቃል ከሰማይ ሰሙ፤ በዚያን ጊዜ ሔደው በአረፈበት ቦታ አገኙት። በእጁም ውስጥ የተጨበጠ ክርታስን አዩ፤ ሊወስዷትም ሽተው መውሰድ ተሳናቸው።

በአንድነትም በጸለዩ ጊዜ እጁ ተፈትታ ወስደው አነበቧት፤ አባትና እናቱም ልጃቸው እንደሆነ አወቁ፤ ታላቅ ጩኸትም ሆነ፤ መሪር ልቅሶንም አለቀሱ፤ አክብረውም ቀበሩት፤ መቃብሩም በሽተኞችን ሁሉ በመፈወስ ድንቆች የሆኑ ብዙ ተአምራትን የሚያደርግ ሆነ።

አምላካችን እግዚአብሔር በቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ጸሎት ይማረን፤ በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን።

መጽሐፈ ስንክሳር ዘጥቅምት ፲፬

ጽኑ እምነት

እለእስክንድሮስ የተባለው መፍቀሬ ጣዖት፣ ጸላዬ እግዚአብሔር፣ የዲያቢሎስ ምርኮኛ የሆነው በሰው እጅ ከድንጋይ ተጠርቦ ለተሠራው ጣዖት ሕዝቡን እንዲሰግዱ ሲያስገድድ፣ ስቶ ሲያስት፣ ሲያስፈራራ ኖሯል፡፡ አብዛኛው ለሥጋው ሳስቶ፣ መከራውን ተሰቆ ለጣዖት ሲሰግድ ሕፃን ቂርቆስ ግን እምቢ አለ፤ የቀደሙ አባቶቹን የተጋድሎ ታሪክ ያውቃልና ልቡን አጸና፤ ለመከራው ተዘጋጀ፤ እናቱ ለልጇ ሳስታ፣ ለጣዖት ልትንበረከክ፣ ልትክድ ሲዳዳት ሕፃኑ ግን ጸና፤ መከራውን ሳይሰቀቅ እለ እስከንድሮስ ላቆመው ጣዖት አልሰግድም አለ፡፡

አማላጅነት

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? ትምህርት እንዴት ነው? በርትታችሁ እየተማራችሁ ነውን? ጥናቱንም ከወዲሁ ጀምሩ! ያልገባችሁንም ጠይቁ! መንፈሳዊ ትምህርትንም በዕረፍት ቀናችሁ ተማሩ፤

ወደፊት ለመሆን የምትፈልጉትን ለመሆን አሁን በርትታችሁ ተማሩ! ቤት ስትገቡ የቤት ሥራችሁን ብቻ ሳይሆን መሥራት ያለባችሁ የተማራችሁትንም መከለስ ነው! ከዚያም ያልተረዳችሁትን መምህራችሁን ጠይቁ፤ መልካም!

ባለፈው ትምህርታችን ጥያቄዎች አቅርበንላችሁ ምላሶቹን ልካችሁልን ነበር፤ እኛም ትክክለኛ የሆኑትን ምላሾች ነግረናቹኋል፤ ለዛሬ ደግሞ “አማላጅነት” በሚል ርእስ እንማራለን! ተከታተሉን!

ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ

የአባቶቻችን ቅዱሳን ሐዋርያት ተጋድሎ በጽኑ መሠረት ላይ በመገንባቱ የመከራ ዝናብ ቢዘንብ፣ የሥቃይ ጎርፍ ቢጎርፍ፣ የችግር ነፋስ ቢነፍስ አይወድቅም፡፡ (ማቴ.፯፥፳፭) ይህም የሆነው እነርሱን በመንፈሳዊ ሕይወት የተተከለ፣ በተጋድሎ ያሳደገ፣ ገቢረ ተአምራት ወመንክራት በማድረግ እንዲያብቡ ያደረገና ለፍሬ ክብር ያበቃ የክብር ባለቤት አምላካችንና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመሆኑ ነው፡፡

“ክቡር ሞቱ ለጻድቅ በቅድመ እግዚአብሔር” (መዝ.፻፲፭፥፭)

ተክለ ሃይማኖት ማለት የስሙ ትርጓሜ “የሃይማኖት ተክል ማለት” ነው። ተክል ሥርም፣ ግንድም፣ ቅጠልም፣ ቅርንጫፍም ነውና ተክለ ሃይማኖት እንጂ ሌላ አላላቸውም። በእርሳቸው ተክልነት ቅርንጫፍ የሆኑ ፲፪ ከዋክብት አሉና “ተክል” አላቸው። ተክል ባለበት ልምላሜ አለ፤ እርሳቸው ባሉበትም የኃጢአት ፀሐይ፣ የርኩሰት ግለት የለም፤ የጽድቅ ዕረፍት እንጅ። ተክል ሕይወት ያለው ነገር ሁሉ ተደግፎት ይኖራል! ቢቆርጡት ለመብል ለቤት መሥርያ ይሆናል፤ ቢያቆዩት ማረፊያ መጠለያ ይሆናል፤ አቡነ ተክለ ሃይማኖትም በዐጸደ ነፍስ ሆነው በምልጃ በጸሎት ያግዛሉ፤ ያማልዳሉ፤ በሕይወት ሳሉም በትምህርታቸውና በተአምራታቸው ኃይል ለብዙዎች ዕረፍት ሰጥተዋል።

“ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አባቴ ነህ!”

መኮንኑ አፈረና ጽኑ ሥቃይ ሊያሠቃያቸው ወድዶ እንደ ክረምት ነጎድጓድ ድምፅ ወደ ሚያስተጋባው የፈላ ውኃ እንዲጥሏቸው አዘዘ፤ ያን ጊዜ እናቱ ፈራች፤  ሕፃኑ ግን ለእናቱ ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፤ እንዲህም አላት፤ “እናቴ ሆይ አትፍሪ! ጨክኝ፤ አናንያ አዛርያ ሚሳኤልን ያዳነ አምላክ እኛንም ያድነናል” አላት። እናቱ ቀና ብላ ብትመለከት ለቅዱሳን ሰማዕታት የተዘጋጁትን የብርሃን ማደርያቸውን ተመለከተች፤ ደስም ተሰኝታ እንዲህ አለች፤ “ልጄ ሆይ ከእንግዲህ አባቴ ነህ፤ እኔም ልጅህ ነኝ፤ አንተን የወለድኩባት ቀን የተባረከች ናት፡፡”

‹‹ተዝካረ ዕረፍቱ ለቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ››

ዐሥራ ሁለተኛው የቊስጥንጥንያ መንበር የነበረ፣ ከአራቱ የምሥራቅ አብያተ ክርስቲያን ዐቃቢያነ እምነት ከሆኑት ከቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ፣ ከቅዱስ አትናቴዎስ ዘእስክንድርያና ከቅዱስ ባስልዮስ ጋር በግብር የተካከለ፣ በገዳማዊ ሕይወቱ ብሕትው፣ በንጽሕናው ተአማኒ፣ በአእምሮ ምጡቅ፣ በአንደበቱ ርቱዕ፣ በስብከቱ መገሥጽ፣ በፍርዱ ፈታሒ በጽድቅ፣ በመግቦቱ አበ ምንዱባን (የድኆች አባት) በጥብቅናው ድምፀ ግፉዓን፣ በጥቡዕነቱ መገሥጽ፣ በክህነቱ የቤተ ክርስቲያን መዓዛ፣ የዓለም ሁሉ መምህር የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የዕረፍቱ መታሰቢያ በግንቦት ፲፪ ቀን ሆነ።

ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ያሬድ

ኢትዮጵያዊው ማኅሌታይ፣ የዜማ ደራሲና ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ድንቅ ተጋድሎን ፈጽሞ ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም የገባበት ዕለት ግንቦት ፲፩ የከበረች እንደመሆኗ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በድምቀት ታከብረዋለች፡፡

“ተክለ አብ፣ ተክለ ወልድ፣ ተክለ መንፈስ ቅዱስ”

የካህን ልጅ ካህን፣ ምድራዊ የሆነ ሰማያዊ፣ ሰው ሲሆን መልአክ፣  ከሱራፌል ጋር የእግዚአብሔርን ዙፋን ያጠነ፣ ከመላእክት ጋር የተባበረ፣ ግዙፍ ሲሆን የረቀቀ፣ ባሕታዊ ሲሆን መምህር፣ ኢትዮጵያን በወንጌል ያበራ፣ የምድር ጨው፣ ስለአባታችን ተክለ ሃይማኖት ይህን እወቁ!

የፀጋ ዘአብ ዘር ምን ያህል ቡርክት ነች፤ የእግዚእኃረያ ማህፀን ምን ያህል ለምለም ነች!? አንደበቱ ለምስጋና የተፈታ፣ መላእክት የሚደሰቱበት፣ የሃማኖት ተክል፣ በዛፍ ጥላ ከፀሐይ ሙቀት እንድንጠለል የሃይማኖት ጥላ የሆነ፣ የበረከት ፍሬ፣ የበረከት ምንጭ፣ የጽዮን ደስታ፣ ፍስሐ ጽዮንን አስገኝተዋልና።