ወርኃ ጥቅምት
የጥቅምት ወርን በተመለከተ መጽሐፈ ስንክሳር በወርኃ ጥቅምት ንባብ መግቢያው “የጥቅምት ወር የቀኑ ሰዓት ዐሥራ አንድ ነው፤ ከዚህም በኋላ ይቀንሳል” ይላል፤ ይህም ማለት በቀን ውስጥ ካለው ሃያ አራት ሰዓት ውስጥ የሌሊቱ ሰዓት ዐሥራ ሦስቱን ሲይዝ የቀኑ ጊዜ ደግሞ ዐሥራ አንዱን ሰዓት ይይዛል ማለት ነው፡፡ ስለዚህ በጥቅምት ወር የሌሊቱ ጊዜ ቀኑ ጊዜ ይረዝማል ማለት ነው፡፡
ጥቅምት ቃሉ “ጠቂም ጠቂሞት” ከሚለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጉሙም “የተሠራች፣ ሥር” ማለት ነው፤ ዓለም የተፈጠረው በዚህ ወር በመሆኑ “ጥንተ ግብር (የሥራ መጀመሪያ)” ማለት ነው፡
ጥቅምት የሚለውን ቃል ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ሲተረጉሙ “ስመ ወርኅ፣ ካልእ መስከረም፣ ጽጌውን መደብ አድርጎ ፍሬ፣ ወርኃ ፍሬ፣ መዋዕለ ሰዊት ይሰኛል” ይላሉ፡፡ (መጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ፭፻፰)