“እግዚአብሔርን የምትወዱ ክፋትን ጥሉ” (መዝ.፺፯፥፲)
በባሕርይው ፍጹም፣ ቅዱስ፣ ንጹሕ የሆነና ምንም ዓይነት ርኩሰት የማይስማማው አምላካችን እግዚአብሔር መልካም አባት ነው፡፡ ዓለም ሳይፈጠር አስቀድሞ የነበረ፣ አሁን ያለ ወደ ፊትም ዓለምን አሳልፎ የሚኖር በመሆኑም ለዘለዓለም በቅድስና ይኖራል፡፡ ፍጥረቱን በሙሉም በቸርነቱ ከመፍጠሩ በፊት ሲቀደስ ሲለስ ይኖር የነበረ፣ አሁንም በፍጥረቱ እንዲመሰገን፣ እንዲቀደስ፣ እንዲወደስ የፈቀደ፣ ወደፊት ደግሞ በክብር ምስጋና በመንግሥቱ ሊገዛ የሚወድ ፈጣሪያችን ክብሩንና ቅድስናውንም ለፍጥረቱ በተለይም ለቅዱሳን መላእክት እና ሰው የሚያደርግ ነው፡፡ ይህን ሁሉም በቸርነቱ፣ በመልካምነቱ፣ በበጎነቱ፣ ስለ ቅዱስ ፈቃዱ አድርጓል፡፡


