baba shenouda

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ 3ኛ አረፉ፡፡

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ 3ኛ አረፉ፡፡
የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ማርቆስ መንበር 117ኛ ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ሲኖዳ ትናንት መጋቢት 8 ቀን 2004 ዓ.ም. አረፉ፡፡
ቢቢሲ የግብፅን ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጠቅሶ እንደዘገበው ቅዱስነታቸው በካንሰር ሕመም ምክንያት በ88 ዓመታቸው አርፈዋል፡፡
በሰሜናዊ ግብፅ፣ አስዩት ውስጥ ሐምሌ 27 ቀን 1915 ዓ.ም ሲወለዱ ናዚር ጋይድ የሚል መጠሪያ ከቤተሰባቸው የተሰጣቸው ቅዱስነታቸው፣  ቅስናን ሲቀበሉ አባ እንጦንስ ተብለው ይጠሩ የነበር ሲሆን አቡነ ሲኖዳ የተባሉት በ1955 ዓ.ም የክርስትና ትምህርት ኤጲስ ቆጶስ ተብለው በተሸሙበት ወቅት ነበር፡፡
ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን 117ኛ ፓትርያርክ ሆነው በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ መንበር ላይ የተሾሙት ከተአምር ሠሪው ፓትርያርክ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቄርሎስ 6ኛ በኋላ ኅዳር 4 ቀን በ1964 ዓ.ም ነበር፡፡፡
ቅዱስነታቸው ከ5ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ የቲዎሎጂ ሴሚናሪ ዲን የሆኑ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ሲሆኑ በአገልግሎት ዘመናቸው ከ3 የአሜሪካን እንዲሁም ከ1 የጀርመን ዩኒቨርስቲ የክብር ዶክትሬት ተቀብለዋል፡፡
ቅዱስነታቸው ሕይወታቸው የትሕርምት፣ የጸሎትና የአገልግሎት እንደነበር የሕይወት ታሪካቸውን የሚዘግቡ ድርሳናት የሚገልጹ ሲሆን ባለፉት 20 ዓመታት የዓለምን ሕዝብ ያስተማሩባቸው 80 መጻሕፍትን ደራሲና የቤተ ክርስቲያኗ ኦፊሴላዊ መጽሔት ኤል-ኬራዛ ዋና አዘጋጅ ነበሩ፡፡
በግብፅ ርዕሰ ብሔር አንዋር ሳዳት ጊዜ አክራሪ ሙስሊሞች በክርስቲያኖች ላይ የሚያደርሱት ጥቃት መጨመርና መፋፋም ያሳሰባቸው ቅዱስነታቸው በመንግሥቱ ላይ ባነሱት ተቃውሞ፣ ለ40 ወራት ከመንጋዎቻቸው ተለይተው ወደ ቅዱስ ቢሶይ ገዳም ተግዘው የአባቶቻቸውን በረከት ተካፍለው እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን በኋለኛው መሪ ሆስኒ ሙባረክ ዘመን ወደ መንበራቸው ተመለሰው እስከ ዛሬ ድረስ ጠቦቶችን ሲጠብቁ፣ ግልገሎችና በጎችን ሲያሰማሩ ቆይተው አርፈዋል፡፡
በግብፅ ሕዝብ በተለይም በኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ተወዳጅ አባት እንደሆኑ የሚነገርላቸው ቅዱስነታቸው በግብፃውያን ክርስቲያኖችና ሙስሊሞች መካከል ያለውን ግንኙነት ለማሻሻልና ሰላማዊ ለማድርግ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ እንደደከሙ ይመሠከርላቸዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ ኢትዮጵያን  ሁለት ጊዜ የጎበኙ ሲሆን ከመጀመሪያው ጉብኝታቸው 30 ዓመታት በኋላ በ2000 ዓ.ም ሚያዝያ ወር ላይ ያደረጉት ጉበኝት የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነበር፡፡
ጸሎታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፣ ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ለግብፃዉያን ወንድም እህቶቻችንና ቅዱስነታቸውን ለሚወዱ ሁሉ መጽናናትን ይመኛል፡፡
መጋቢት 9/2004 ዓ.ም.

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ 3ኛ ዐረፉ፡፡ የቤተ ክርስቲያኗ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳትና የቅዱስ ማርቆስ መንበር 117ኛ ፓትርያርክ የቅዱስነታቸው ዕረፍት የታወቀው ትናንት መጋቢት 8 ቀን 2004 ዓ.ም. ነበር፡፡

 

ቢቢሲ የግብፅን ብሔራዊ የቴሌቪዥን ጣቢያ ጠቅሶ እንደዘገበው ቅዱስነታቸው በካንሰር ሕመም ምክንያት በ88 ዓመታቸው ከዚህ ዓለም ድካም ዐርፈዋል፡፡
baba shenouda
በሰሜናዊ ግብፅ፣ አስዩት ውስጥ ሐምሌ 27 ቀን 1915 ዓ.ም ሲወለዱ ናዚር ጋይድ የሚል መጠሪያ ከቤተሰባቸው የተሰጣቸው ቅዱስነታቸው፣  ቅስናን ሲቀበሉ አባ እንጦንስ ተብለው ይጠሩ የነበር ሲሆን አቡነ ሲኖዳ የተባሉት በ1955 ዓ.ም የክርስትና ትምህርት ኤጲስ ቆጶስ ተብለው በተሸሙበት ወቅት ነበር፡፡ ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን 117ኛ ፓትርያርክ ሆነው በወንጌላዊው ቅዱስ ማርቆስ መንበር ላይ የተሾሙት ከተአምር ሠሪው ፓትርያርክ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቄርሎስ 6ኛ በኋላ ኅዳር 4 ቀን በ1964 ዓ.ም ነበር፡፡
ቅዱስነታቸው ከ5ኛው ክፍለ ዘመን በኋላ የቲዎሎጂ ሴሚናሪ ዲን የሆኑ የመጀመሪያው ፓትርያርክ ሲሆኑ በአገልግሎት ዘመናቸው ከ3 የአሜሪካን እንዲሁም ከ1 የጀርመን ዩኒቨርስቲ የክብር ዶክትሬት ተቀብለዋል፡፡ቅዱስነታቸው ሕይወታቸው የትሕርምት፣ የጸሎትና የአገልግሎት እንደነበር የሕይወት ታሪካቸውን የሚዘግቡ ድርሳናት የሚገልጹ ሲሆን ባለፉት 20 ዓመታት የዓለምን ሕዝብ ያስተማሩባቸው 80 መጻሕፍትን ደራሲና የቤተ ክርስቲያኗ ኦፊሴላዊ መጽሔት ኤል-ኬራዛ ዋና አዘጋጅ ነበሩ፡፡

 

በግብፅ ርዕሰ ብሔር አንዋር ሳዳት ጊዜ አክራሪ ሙስሊሞች በክርስቲያኖች ላይ የሚያደርሱት ጥቃት መጨመርና መፋፋም ያሳሰባቸው ቅዱስነታቸው በመንግሥቱ ላይ ባነሱት ተቃውሞ፣ ለ40 ወራት ከመንጋዎቻቸው ተለይተው ወደ ቅዱስ ቢሶይ ገዳም ተግዘው የአባቶቻቸውን በረከት ተካፍለው እንደነበር የሚታወቅ ሲሆን በኋለኛው መሪ ሆስኒ ሙባረክ ዘመን ወደ መንበራቸው ተመለሰው እስከ ዛሬ ድረስ ጠቦቶችን ሲጠብቁ፣ ግልገሎችና በጎችን ሲያሰማሩ ቆይተው ዐርፈዋል፡፡

 

በግብፅ ሕዝብ በተለይም በኦርቶዶክሳውያን ዘንድ ተወዳጅ አባት እንደሆኑ የሚነገርላቸው ቅዱስነታቸው በግብፃውያን ክርስቲያኖችና ሙስሊሞች መካከል ያለውን ግንኙነት ለማሻሻልና ሰላማዊ ለማድርግ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ እንደደከሙ ይመሠከርላቸዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ ኢትዮጵያን  ሁለት ጊዜ የጎበኙ ሲሆን ከመጀመሪያው ጉብኝታቸው 30 ዓመታት በኋላ በ2000 ዓ.ም ሚያዝያ ወር ላይ ያደረጉት ጉበኝት የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነበር፡፡

ጸሎታቸው ከሁላችን ጋር ይሁን፣ ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ለግብፃዉያን ወንድም እህቶቻችንና ቅዱስነታቸውን ለሚወዱ ሁሉ መጽናናትን ይመኛል፡፡

የአብነት ትምህርት ቤት ለመደገፍ የግንባታና የቋሚ ገቢ ማስገኛ ፕሮጀክት ቀረበ

መጋቢት 7/2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ


በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ፍቼ ሀገረ ስብከት፣ በሰንዳፋ አዳማ በበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስተ ማርያም ቤተ ክርስቲያን የሚገጥመን የአብነት ትምህርት ቤት ለመደገፍ የግንባታና የቋሚ ገቢ ማስገኛ ፕሮጀክት ዕቅድ ከባለድርሻ አካላት ጋር የካቲት 18 ቀን 2004 ዓ.ም. በደብሩ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ቀረበ፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት  መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የአብነት ትምህርት ቤቶች ፕሮጀክት ክትትል ባለሙያ የሆኑት ዲ/ን ጌታዬ መኮንን የአብነት ትምህርት ቤት ነባራዊ ሁኔታን በተመለከተ ባለድርሻ አካላት ግንዛቤ እንዲኖራቸው የዳሰሳ ጥናት አቅርበዋል፡፡ በመቀጠልም ለሚተገበረው ፕሮጀክት የአዲስ አበባ ማእከል የማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ፕሮጀክት ን/ክፍል ጸሓፊ አቶ አንዱዓለም ተስፋዬ የፕሮጅክቱን መነሻ ሀሳብ አቅርበዋል፡፡

 

በፕሮጀክት ትግበራው የግብርና ሥራ፣ የሰብል ምርት ፕሮጀክትና የወተት ላም እርባታ ዕቅድን ጨምሮ ለአብነት ተማሪዎቹ የማደሪያና መማሪያ ክፍል፣ የመጸዳኛና ንጽህና መስጫ፣ ቤተ መጻሕፍት እና ማብሰያ የማእድ ቤት ግንባታ ያካተተ ነው፡፡ ይህን ፕሮጀክት ለመተግበር 3.8 ሚሊዮን ብር የሚፈጅ ሲሆን ከበጎ አድራጎት፣ ከማኅበራት፣ ከሠራተኛ ጉባኤያት፣ በአካባቢው ምእመናን ወጪው እንደሚሸፈን ከቀርበው ፕሮጀክት ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

የበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የሆኑት መልአከ ምሕረት ቆሞስ አባ ገብረ አማኑኤል አያኔ በበኩላቸው የአብነት ተማሪዎቹ ያለባቸውን የመጠለያ፣ የምግብ እና የአልባሳት ችግር ለመፍታት የሚተገበረው ፕሮጀክት ዐይነተኛ ሚና እንደሚኖረው እምነታቸውን ገልጸዋል፡፡

 

ለዚህ ፕሮጀክት መሳካት አጋዥ የሚሆኑ የአካባቢው ምእመናን ተገኝተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል ለታ ቁምቢ የተባሉ ምእመን የአብነት ተማሪዎች ላለባቸው ችግር አቅሜ በፈቀደ መጠን ለትምህርት ቤቱ መሥሪያ ለሚያስፈልገው ቁሳቁስ ለመርዳት ፈቃደኛ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡

 

በበኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የሚገኘውን የአብነት ት/ቤት በዘላቂነት ለመደገፍ የታቀደው ፕሮጀክት ምእመኑ እንዲያውቀው የቀረበ ሲሆን በዚህ ፕሮጀክት ዕቅድ ትግበራ ላይ ከ90 በላይ ባለድርሻ አካላት የተገኙ ሲሆን ለዕቅዱ ስኬታማነት ሁሉም የበኩሉን እንዲወጣ ጥሪ ቀርቧል፡፡

የዐቢይ ጾም ስብክት (ክፍል 5)

መጋቢት 7/2004 ዓ.ም.

በአያሌው ዘኢየሱስ

 

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ፤

 

የዐቢይ ጾም አምስተኛ ሳምንት ሰንበት «ደብረ ዘይት» ተብሎ ይጠራል፡፡ ደብረ ዘይት ከኢየሩሳሌም በስተ ምሥራቅ የሚገኝ ተራራ ነው፡፡ ተራራው በዚህ ስም የሚጠራው ለዘይት የሚሆን የወይራ ተክል በብዛት ስለሚበቅልበት ነው፡፡ ጌታችን ቀን ሲያስተምር ውሎ በደብረ ዘይት ያድር ነበር፡፡ ለደቀ መዛሙርቱም ለሕዝቡ በምሳሌ ያስተማረውን ይተረጉምላቸው ነበር፡፡ የዓለም ፍጻሜና የዳግም ምጽአቱን ምልክት ለደቀ መዛሙርቱ ያስተማራቸው በዚሁ ተራራ ላይ ነውና የጌታን ዳግም ምጽአት የምናስብበት አምስተኛው የዐቢይ ጾም ሰንበት ስሙን ከተራራው ወስዷል ማለት ነው፡፡ ደብረ ዘይት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምዕመናን ዘንድ «እኩለ ጾም» ተብሎ ይጠራል፡፡ በዚህ ስያሜ የሚጠራውም የጾሙ ሳምንታት አጋማሽ ወይም እኩሌታ ስለሆነ ነው፡፡ አንዳንድ የቤተ ክርስቲያን አባቶች መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ እሑድ፣  የደብረ ዘይት ዕለት ይመጣል ብለው ስለሚያስተምሩ በዚህ ሰንበት የሚበዙት ምዕመናን ዕለቱን በታላቅ ዝግጅት ማለትም በንስሓና በቅዱስ ቁርባን ይቀበሉታል፡፡ በዚህ ዕለት የሚሰበከው ምስባክ፣ የሚሰጠው የወንጌል ትምህርትና የሚነበቡት የሐዋርያት ሥራና የመልእክታት ንባባት በሙሉ የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ሁለተኛ አመጣጥ የሚናገሩ ናቸው፡፡

ከአራቱ ወንጌላውያን (ማቴዎስ፣ ማርቆስ፣ ሉቃስ፣ ዮሐንስ) ስለ አምላካችን ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለተኛ አመጣጥ እና ስለ ዕለተ ደይን ማለትም ስለ ፍርድ ቀን በስፋትና በጥልቀት የጻፈው ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ነው፡፡ በመሆኑም በአምሳ አንድ ቁጥሮች የተከፋፈለው ሃያ አራተኛው ምዕራፉ ሙሉ ለሙሉ የሚናገረው ስለ አስፈሪውና ስለ አስደንጋጩ የክርስቶስ ሁለተኛ አመጣጥ ነው፡፡ ምዕራፉን በሦስት ዐበይት ክፍሎች ሥር ማሰባሰብ ይቻላል፤ኢየሱስ ክርስቶስ ከመምጣቱ በፊት፣ በመጣ ጊዜ እና ከመጣ በኋላ በምድርና በሰማይ ላይ የሚከሰቱ ክስተቶች በማለት፡፡ ይሁን እንጂ በዚህ አጭር ጽሑፍ ውስጥ የሚገኙትን አምሳ አንድ ቁጥሮች ኀይለ ቃላት አድርጎ መስበክ ስለማይቻል አንዱን ቁጥር ርእስ አድርገን በመውሰድ ለመማማር እንሞክራለን፡፡

ከላይ ርእስ ተደርጎ የተወሰደው “እነዚያ ቀኖች….” የሚለው ነው፡፡ «እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል፡፡» (ማቴ 24፥13) የሚለው ነው፡፡ አስቀድመን እንደ ተናገርን አምላካችን ከመምጣቱ በፊት፣ በመጣ ጊዜ እና ከመጣ በኋላ በምድርና በሰማይ የሚታዩ ታላላቅ ምልክቶች ተከስተው እስከሚያበቁ ድረስ በሰው ልጆች ዘንድ ከመቼውም ጊዜ የበለጠ ጽናት ስለሚያስፈልግ ነው መድኀኔዓለም ኢየሱስ ክርስቶስ እስከ መጨረሻ የሚጸና እርሱ ይድናል በማለት በግልጥ ያስተማረው፡፡ ድንጋይ በድንጋይ ላይ ሲፈርስ፣ እኔ ክርስቶስ ነኝ ብለው የሚያውጁ አሳቾች ሲነሡና ብዙዎችን ሲያስቱ፣ ጦርንና የጦር ወሬን መስማት ተደጋጋሚ ዜና ሲሆን፣ ሕዝብ በሕዝብ ላይ መንግሥትም በመንግሥት ላይ መነሳቱ ቀላል ነገር ሲሆን፣ ረሀብ ቸነፈርና የምድር መናወጥ በተለያዩ የዓለማችን ክፍሎች ላይ ሲመጣ የሚመለከቱ የሰው ልጆች መጽናት ስለሚያስፈልጋቸው ነው እስከ መጨረሻ የሚጸና እርሱ ይድናል ተብሎ የተነገረው፡፡

ከዚህ በተጨማሪ የእግዚአብሔር ልጆች በማያምኑ ሰዎች ሲጠሉ፣ ለመከራ ተላልፈው ሲሰጡና ሲገደሉ፣ ሰዎች እርስ በእርሳቸው ተላልፈው ሲሰጣጡ፣ እርስ በእርሳቸው ሲጣሉ፣ ብዙ ሐሰተኛ ነቢያት ሲነሡና ብዙዎችን ሲያስቱ፣ ዓመጻ ሲበዛና የሰው ልጆች ፍቅር ሲቀዘቅዝ ወይም ሲጠፋ፣ ከዓለም መጀመሪያ እስከዚያ ቀንድ ድረስ ያልሆነ ከእንግዲህም ከቶ የማይሆን ታላቅ መከራ ሲሆን፣ አሳቾችና ሐሰተኞች ክርስቶሶች ለእግዚአብሔር የተመረጡትን ሰዎች እስኪያስቱ ድረስ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ሲያሳዩ የሚመለከቱ ሰዎች ከሃይማኖታቸውና ከእምነታቸው ሳይናወጡ እስከ መጨረሻው ድረስ በጽናት እንዲቆዩና እንዲድኑ ነው ጌታ እስከ መጨረሻ የሚቆይ እርሱ ይድናል በማለት የተናገረው፡፡

ከዚህ ሌላ የጥፋት ርኵሰት በተቀደሰችው ስፍራ (በቤተ ክርስቲያን) ቆሞ ሲታይ፣ ፀሐይ ስትጨልም፣ ጨረቃ ብርሃንዋን አልሰጥም ስትል፣ ከዋክብት ከሰማይ ሲወድቁ፣ የሰማያት ኀይላት ሲናወጡ፣ የሰው ልጅ (ኢየሱስ ክርስቶስ) ምልክት በሰማይ ሲታይ፣ የምድር ወገኖች ሁሉ ዋይ ዋይ ሲሉ፣ ወልደ እጓለመሕያው ኢየሱስ ክርስቶስ በኀይልና በብዙ ክብር መምጣቱ ሲታይ፣ መላእክቱ ከሰማያት ዳርቻ እስከ ዳርቻው ድረስ ለእርሱ የተመረጡትን ቅዱሳን ሲሰበስቡ የሚመለከትና በጽናት የሚቆይ ሰው እርሱ ይድናል ማለት ነው፡፡

ከዚህ በላይ የተመለከትናቸውና ወንጌሉ ምንም ሳያስቀር ፍንትው አድርጎ ያሳየን የዳግም ምጽአት የመጀመሪያ፣ የቀጣይና የመጨረሻ ምልክቶች በሙሉ አሳሳቢ፣ አስፈሪና አስደንጋጭ ምልክቶች ስለሆኑ እምነትና ሥራ የሌለው ሰው ካልሆነ በስተቀር ማንም ቢሆን እስከ መጨረሻው ድረስ በጽናት ሊቋቋማቸው አይችልም፡፡ በተለይም የጥፋት ርኵሰት በተቀደሰችው ቦታ ላይ ሲቆም፣ አሳቾች ለእግዚአብሔር የተመረጡትን ሰዎች እስከሚያስቱ ድረስ ታላላቅ ምልክትና ድንቅ ሲያሳዩ መመልከትና ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብትና የሰማያት ኀይላት  ብርሃናቸውን ሲነፍጉ፣ ከሰማይ ሲረግፉና ሲናወጡ መስማትና ማየት በሃይማኖትና በምግባር የማይኖረውን ሰው ሊያጸናው አይችልም፡፡ ዛሬ በተቀደሰችው ቦታ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የጥፋት ርኵሰት መቆሙን የሚያመለክቱ ብዙ ምልክቶች በገሃድ እየታዩ ነው፤ከሊቅ እስከ ደቂቅ በጥፋትና በርኵሰት ሥራ እንጂ በእምነትና በጽድቅ ሥራ ላይ ወይም ኢየሱስ ክርስቶስን ለመቀበል በሚያስችሉ ሥራዎች ላይ ሲተጋ አይታይምና፡፡ በመሆኑም አምና እና ዘንድሮ አሳቾች መናፍቃን የክርስቶስ ነን ወይም ክርስቶስ ከእኛ ጋር ነው እያሉ ብዙዎችን ሲያስቱ፣ መንግሥት በመንግስት ላይ ሕዝብም በሕዝብ ላይ ሲነሣ፣ በዓለማችን የተለያዩ ቦታዎች ላይ ምድር ስትናወጥ፣ ረሀብና ቸነፈር ሲሠለጥኑ እየተመለከተ ያለ ሰው በዚሁ ምክንያት በሃይማኖቱ ሊጸና ስላልቻለ የምጥ ጣር መጀመሪያ በተባሉት በእነዚህ ምልክቶች ሲፈናቀል እየታየ ነው፡፡

እንዲህ ዓይነቱ ሰው ከኢየሱስ ክርስቶስ መምጣት በፊት በሚታዩት እነዚህ የምጥ ጣር መጀመሪያዎች ወይም የመጀመሪያ ምልክቶች መታየት ሃይማኖቱን የሚለውጥ ከሆነ የጥፋት ርኩሰት በቤተ ክርስቲያኑ ዓውደ ምሕረት ላይ ቆሞ ስለ ጥፋት ሲሰብክ ሲመለከት እንዴት ነው ሊጸና የሚችለው? እነዚህን ምልክቶች የተለመዱ የሰዎችና የተፈጥሮ አደጋዎች ናቸው ብሎ የሚያምንና በዚያ ዙሪያ መፍትሔ ለመስጠት የሚራወጥ ሰው ይህ ሊሆን ግድ ነውና ከጥፋት ተጠበቁ እንዲሁም ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው የሚለውን አምላካዊ ቃል በጽናት ሊያምንና ሊተገብር የሚችለውስ እንዴት ነው? ዲያቆን እገሌ ወይም ቄስ እገሌ ወይም አባ እገሌ ሰው በመሆናቸውና ደካማ የሆነውን ሥጋ በመልበሳቸው የሚፈጽሙአቸውን ስሕተቶች ሲመለከት ሃይማኖቱን ረግሞ ከመናፍቃን ጋር ጽዋውን ሊያነሣ የሚጣደፈው ሰው ነገ ያሳሳቱት አሳቾች የተመረጡትን ሰዎች እስከ ማሳሳት ሲደርሱ ሲመለከት እንዴት አድርጎ ነው ሊጸና የሚችለው? እዚህ ላይ ንባባችሁን ጥቂት በማቆም በተመስጦ ውስጥ ሁኑ እና ራሳችሁን በክርስቶስ ቃል እንዲህ ብላችሁ ጠይቁት፡- «ነገር ግን የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር እምነትን ያገኝ ይሆንን?» ሉቃ 18፥8፡፡

ይህ ቃል አስፈሪ ቃል ነው! ይህ ቃል ውስጣችንን የሚመረምር ቃል ነው! ይህ ቃል ማንነታችንን የሚያሳይ ቃል ነው! ይህ ቃል ማንነታችንን የሚገልጥ ቃል ነው! ይህ ቃል እምነትና ጽናት በእኛ ዘንድ እንደሌለ የሚመሰክር ቃል ነው! ይህ ቃል ባዶ መሆናችንን የሚያሳውቅ ቃል ነው! ይህ ቃል እውነት ነው! ይህ ቃል የእውነት አምላክ የኢየሱስ ክርስቶስ ቃል ነው! ዛሬ እምነት ከሰው ልጆች ዘንድ እየመነመነ ነው፡፡ በእምነት የሚፈጸሙ ተግባራት እየጠፉ ነው፡፡ እምነት ስለሌለም ጽናት እየጠፋ ነው፡፡ ጽናት  ስለሌለም ሰው ሁሉ እየጠፋ ነው፡፡ «እምነትን ያገኝ ይሆንን?» የሚለው ቃል «ያገኛል» ማለት አይደለም፤«አያገኝም» ማለት ነው እንጂ፡፡ «በመጣ ጊዜ» የሚለው ቃልም ለሁለተኛ ጊዜ ለፍርድ ሲገለጥ ወይም በዳግም ምጽአቱ ሲገለጥ ማለት ነው፡፡ የሚመጣውም እስከ መጨረሻው ድረስ በእምነትና በጽናት በመቆየት መንግሥቱን ሊያወርሰን የሚፈልገው መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ሰዎች እምነትና ሥራን አስተባብረው ካልያዙ ግን መንግሥቱን አያወርሳቸውም፡፡ በሰዎች ዘንድ በእምነትና በሥራ የሚገለጥ ጽናት ከሌለም መንግሥቱን ሊወርሱ አይችሉም፡፡ እምነት ብቻ አያድንም! ሥራ ብቻ አያድንም! በባዶ ነገር ላይ መጽናትም አያድንም! እምነትንና ሥራን አስተባብሮ በመያዝ በእነዚህ በሁለቱ ላይ መጽናት ግን ያድናል!! ሰው እምነትና ሥራን አስተባብሬ ይዤአለሁ እያለ በእነዚህ ላይ ሊጸና ካልቻለና በትንሹም ሆነ በትልቁ ምክንያት ወይም ፈተና የሚወድቅ ከሆነም አይድንም፡፡

ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ እስከ መጨረሻው ድረስ ሊጸኑ የቻሉና ያልቻሉ ብዛት ያላቸው ሰዎችን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ለምሳሌ፡- ጻድቁ ኢዮብ፣ ነቢዩ ኤልሳዕና ሐዋርያት ለጽናት ልዩና ድንቅ ምሳሌዎቻችን ናቸው፡፡ ጻድቁ ኢዮብ ቤቱን፣ ንብረቱን፣ ከብቶቹንና አሥር ልጆቹን በአንድ ቀን ውስጥ ያጣ ሰው ነበር፡፡ ይህ ሳይበቃውም መላው ሰውነቱ በከባድ ቁስል ተመትቶ ከፍተኛ መከራና ሥቃይ ውስጥ ገብቶ ነበር፡፡ ይህን ሁሉ ፈተና ያመጣበት ሰይጣን ሲሆን ምክንያቱም እርሱን በእግዚአብሔር ላይ ያለውን እምነት በሥራና በጽናት መግለጽ አይችልም በማለት ተስፋ ስላደረገ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ የኢዮብ አሳብና የሰይጣን አሳብ፤የኢዮብ እምነትና የሰይጣን እምነት፣ የኢዮብ ሥራና የሰይጣን ሥራ፣ የኢዮብ ጽናትና የሰይጣን ጽናት አንድ ሊሆን ስላልቻለ ኢዮብ ሰይጣንን በአራቱም ውጊያዎች ፈጽሞ አሸንፎታል፡፡ በአሳብ፣ በእምነት፣ በሥራና በጽናት፡፡

እንደ ሰው ሰውኛው (እንደ እኛ) አስተሳሰብ ኢዮብን የገጠሙት ፈተናዎች በእምነቱና በሥራው እስከ መጨረሻው ድረስ ሊያጸኑት የሚችሉ አልነበሩም፡፡ እኛ ያሉኑን ነገሮች ማለትም ሀብታችንን፣ ንብረታችንን፣ ልጆችንንና ጤናችንን አጥተን አይደለም እነዚህ ሁሉ ተሟልተውልን እግዚአብሔርን ልናምነው፣ እርሱን ደስ የሚያሰኙትን የጽድቅ ሥራዎች ልንሠራና በእነዚህ ላይ ልንጸና አልቻልንም፡፡ ሁሉንም ነገር ሰጥቶን እኮ ነው የለህም የምንለው! ሰዎች ያላቸውን ሳያጡ እኮ ነው እርሱን የሚክዱት! ሰዎች ራሳቸውን ወይም ሆዳቸውን ጥቂት ካመማቸው እኮ ነው እግዚአብሔርን የለህም ለማለት የማይሰንፉት! ኢዮብ ግን አሥር ልጆቹን ጨምሮ ሁሉንም ነገር ቢያጣና እርሱ ራሱ የቆሰለ ገላውን በገል እስከ መፋቅ ቢደርስም እንዲህ ነበር ያለው፡- «. . . እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔርም ነሣ፤የእግዚአብሔር ስም የተመሰገነ ይሁን፡፡» ኢዮ 1፥21፡፡

ያለ ነገርን ሙሉ ለሙሉ አጥቶ እግዚአብሔርን ማመስገን መቻል በእምነትና በሥራ ላይ የተመሠረተ ጽናት ነው፡፡ የቆሰለ አካልን ከእግር ጥፍር እስከ ራስ ጠጉር ድረስ በገል እየፋቁ የእግዚአብሔርን ስም ለማመስገን መነሣት በእምነትና በሥራ ላይ የተመሠረተ ጽናት ነው፡፡ እስከ መጨረሻ ድረስ በእምነት መጽናት ደግሞ ድኅነትን ስለሚያሰጥ ጻድቁ ኢዮብ ከልጆቹ ቁጥር በስተቀር የነበሩት ነገሮች ሁለት እጥፍ ሆነው ተመልሰውለታል፤የልጅ ልጆቹንም እስከ አራት ትውልድ ድረስ ሊያይ ችሏል፣ ሸምግሎና ዕድሜ ጠግቦም ሞቷል፡፡ የሚጸና ሰው ዋጋ እጥፍ ነው፡፡ የሚያዳክሙና ከእግዚአብሔር ሊለዩ የሚሞክሩ ሚስቶችን እንደ ጻድቁ ኢዮብ «አንቺ ከሰነፎቹ ሴቶች እንደ አንዲቱ ተናገርሽ፤ ከእግዚአብሔር እጅ መልካሙን ተቀበልን፤ክፉ ነገርንስ አንቀበልምን?»  (ኢዮ 2፥10) ማለት እምነት ነው! ሥራ ነው! ጽናትም ነው! በእምነትና በጽናት ላይ የሚመጡ ባልንጀራዎችን “የምታዳክሙ ባልንጀራዎች” ማለትም ጽናት ነው!

ኤልሳዕ መምህሩ ኤልያስ ከእርሱ ተለይቶ በእሳት ሰረገላና ፈረሶች ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት ከቤቴል እስከ ዮርዳኖስ ማዶ ድረስ በሚገኙት አራት ከተሞች ውስጥ የሚኖሩ የነቢያት ልጆች «እግዚአብሔር ጌታህን ከራስህ ላይ እንዲወስደው አውቀሃልን?» (2ኛ ነገ 2፥3እና5) በማለት ጽናቱን አናውጠው ከጌታው ከኤልያስ ሊለዩትና በመጨረሻ ሊያገኘው የነበረውን እጥፍ መንፈስ ሊስቀሩበት ሞክረው ነበር፡፡ ኤልሳዕ ግን ጽናቱን «አዎን አውቄአለሁ፤ዝም በሉ፤. . .» (2ኛ ነገ 2፥3እና5) በማለት አረጋግጦላቸዋል፡፡ ከቤቱ ወጥቶ እግዚአብሔር ወደሚመለክበት ሥፍራ በመሔድ ላይ ያለ ወጣትን ባልንጀሮቹ ዛሬ እኮ «አርሴ» እና «ማንቼ» ግጥሚያ እንዳላቸው አላወቅህምን? ሲሉት «አዎን አውቄአለሁ፤ዝም በሉ» በማለት ከእግዚአብሔር ጋር ያለውን ግንኙነት በእምነቱና በሥራው ላይ እስከ መጨረሻ ድረስ በመጽናት መንገዱን የማይቀጥል ከሆነ እምነቱን በሥራና በጽናት አልገለጠምና በፍርድ ቀን የጌታውን መንግሥት ሊወርስ አይችልም፡፡ ይህን የምለው የነጮቹን ኳስ ግጥሚያ ለማየት ሲሉ የተሰጣቸውን የስብከት ወይም የሰዓታት ወይም የማኅሌት አገልግሎት ሰርዘው ወደዚያው የሔዱ ሰዎችን ስለማውቅ ወይም ራሳቸው ስለ ነገሩኝ ነው፡፡ እንብላ፣ እንጠጣ፣ እንቃም፣ እናጭስ፣ እንጨፍር፣ እንሴስን. . . ወዘተ የሚሉትንም በጽናት «ዝም በሉ!» በማለት አልፎ መምጣት እስከ መጨረሻው ድረስ መጽናት ካልተቻለ የሰዎች ውድቀት የከፋ ነው የሚሆነው፡፡

የሐዋርያት ጽናትም ከዚህ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ እነርሱ ሁሉንም ነገር ትተው መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በጽናት ከተከተሉት በኋላ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንደ አረጋዊነቱ እነርሱን በመወከል «እነሆ እኛ ሁሉን ትተን ተከተልንህ፤ እንኪያስ ምን እናገኝ ይሆን?» (ማቴ 19፥27) የሚል መሠረታዊ ጥያቄ ለጌታ አቅርቦለት ነበር፡፡ አምላካችንም ለቅዱስ ጴጥሮስ ብቻ ሳይሆን እርሱ ለወከላቸው ለአሥራ ሁለቱ ሐዋርያት እንዲህ የሚል መልስ ሰጥቶአቸዋል፡- «እውነት እላችኋለሁ፡- እናንተስ የተከተላችሁኝ በዳግመኛ ልደት የሰው ልጅ በክብሩ ዙፋን በሚቀመጥበት ጊዜ እናንተ ደግሞ በአሥራ ሁለቱ የእስራኤል ነገድ ስትፈርዱ በአሥራ ሁለት ዙፋን ትቀመጣላችሁ፡፡» ማቴ. 19፥28፡፡ ጌታ ይህን ከነገራቸው በኋላ ያለውን ሁሉ የተወ ሰው እንደ ኢዮብና እንደ ኤልሳዕ ሁለት እጥፍ ዋጋ እንደሚቀበሉ እንዲህ በማለት አስረግጦ ነግሮአቸዋል፡- «. . . የተወ ሁሉ መቶ እጥፍ ይቀበላል፤የዘላለምንም ሕይወት ይወርሳል፡፡» ማቴ.19፥29፡፡

አስቀድመን እንደ ተናገርን የሚጸና ሰው ዋጋ እጥፍ ድርብ ወይም መቶ እጥፍ ነው፡፡ በክርስትና ሳይተዉ መቀበል አይቻልም፡፡ ዛሬ ብዙዎች ያላቸውን ሀብት፣ ቤት፣ ንብረት፣ ልጆች. . . ወዘተ ሊተዉ አልቻሉም፡፡ ይህ በእግዚአብሔር ፈቃድ ለዚህ አገልግሎት ለተመረጡ አባቶች ብቻ ስለሆነና ሁሉም ያለውን ትቶ በምንኩስና ሕይወት እርሱን እንዲከተሉት ስላልፈቀደ ሁሉም መነኩሴ ወይም መነኩሲት ሊሆን አይችልም፤በግድ ልሁን ቢልም አይሳካለትም፡፡ ይሁን እንጂ እግዚአብሔር አምላክ ሰዎች ሁሉ አጥብቀው እንዲተዉለት የሚፈልገው ነገር አለ፤እርሱም ኀጢአት ነው፡፡ ዛሬ ብዙዎችን እስከ መጨረሻው ድረስ እንዲጸኑ፣ እንዲድኑና ዘላለማዊ ሕይወት እንዲወርሱ የማያደርጋቸው ኀጢአት ነው፡፡ አንድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባል ወደ ክርስትና እምነት የተጠራው እስከ ሞት ድረስ በመጽናት የዘላለም ሕይወት ለመውረስ ስለሆነ ከኀጢአት መሸሽ እንጂ ኀጢአትን መከተል አልተፈቀደለትም፡፡ «እስከ ሞት ድረስ የታመንህ ሁን፤የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ፡፡» (ራእ 2፥10) በማለት የተናገረው እኮ የእግዚአብሔር አብ እና የድንግል ማርያም ልጅ ጌታችን፣ አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ጽናትና መታመን ከኀጢአትና ከጥፋት ጋር ሊስማሙ አይችሉም፡፡ ኀጢአት እስከ ሞት ድረስ የታመንን እንድንሆን አያደርገንም፡፡

ኢዮብ፣ ኤልሳዕና ሐዋርያት በእምነት፣ በሥራና በጽናት የሕይወትን አክሊል ተቀብለዋል፡፡ ሶምሶን፣ ግያዝና ዴማስ ግን እስከ መጨረሻ ድረስ ሊጸኑ ስላልቻሉ ሊጸድቁ አልቻሉም፡፡ በአንድ ወቅት ታላላቅ መንፈሳዊ አባቶች ተብለው የተጠሩ እነዚህ ሰዎች በፈተና ሊጸኑ ስላልቻሉ ለሌሎች ሁለት እጥፍ ሆኖ የተሰጠውን ዋጋ ሊቀበሉ አልቻሉም፤ አልተባረኩምም፡፡ መጽሐፍ ጽናት ስለሚያሰጠው በረከት ሲናገር እንዲህ ብሏል፡- «በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፡፡» ያዕ 1፥12፡፡ ለመባረክም መጽናት ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ በፍርድ ቀን «ኑ፤ዓለም ከተፈጠረበት ጊዜ ጊዜ ጀምሮ የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ውረሱ፡፡» (ማቴ 25፥34) የሚለውን የእግዚአብሔር ቡራኬ ለመቀበል እስከዚያው ቀን ድረስ በእምነትና በሥራ በጽናት መቆየት ያስፈልጋል፤ማስፈለግ ብቻ ሳይሆን ግድ ነው!!

ስለሆነም ዛሬ በዐቢይ ጾም አምስተኛ ሰንበት ላይ ሆነን የደብረ ዘይትን በዓል ስናከብር እስከ ጌታችን ዳግም ምጽአት ድረስ በእምነት፣ በሥራና በጽናት እንድንቆይ እርሱን «አንተ አድነን!» ልንለው ይገባናል፡፡ እንደ ጸኑት ሁለት እጥፍ ዋጋ እንዳናገኝ ዓለም በአናንያ፣ በአዛርያና በሚሳኤል ዙሪያ ያነደደችውን የፈተና እሳት በእኛም ሕይወት ዙሪያ አንድዳለችና በእሳቱ ከመሟሟቅ ይልቅ እሳቱን የምናጠፋበትን የእምነት ጽናት እንዲያድለን እንጠይቀው፡፡ ዛሬ በእምነትና በእምነት ሥራ የምናየውና የምንሰማው ዜና ሁሉ ተስፋ የሚያስቆርጥ እንጂ የሚያጸና ስላልሆነ እግዚአብሔር አምላክ ተስፋችንን እንዲሁም ጽናታችንን እንዲያለመልመልን እንጠይቀው፡፡ የሰዎች ዐይኖች በእግዚአብሔር ሥራዎች ላይ ከማተኮር ይልቅ በዲያብሎስ ሥራዎች ላይ እጅግ አተኩረዋልና ዐይኖቻቸውን ከዚህ ክፉ ሥራ መልስ እንበለው፡፡

የደብረ ዘይት በዓል የዝግጅት በዓል ነው፡፡ የደብረ ዘይት ከእግዚአብሔር ጋር የምንሆንበትን ቀን የምንናፍቅበት በዓል ነው፡፡ የደብረ ዘይት በዓል ከእግዚአብሔር ጋር አንድ የምንሆንበት በዓል ነው፡፡ ዳግም ምጽአት ከእግዚአብሔር ዋጋ የምንቀበልበት ቀን ነው፡፡ ዳግም ምጽአት ከእግዚአብሔር በስተ ቀኝ የምንቆምበት ቀን ነው፡፡ ዳግም ምጽአት ዐይን ያላየውን፣ ጆሮ ያልሰማውንና በልቦናም ያልታሰበውን የእግዚአብሔር መንግሥት ለመውረስ የምንሸጋገርበት ቀን ነው፡፡ ስለሆነም ቀኑን በፍጹም እምነት ከልባችን ሆነን በመጾም፣ በመጸለይ፣ በመስገድና በመመጽወት እናንክብረው እንጂ ከአዲስ አበባ ወደ ደብረ ዘይት ወጣ ብለን ለመዝናናት፣ ያገኘነውን ለመብላትና ለመጠጣት እንዲሁም ከዕለቱ በዓል ጋር የማይገናኙ ተራ ወሬዎችን ለማውራት እንዳናደርገው እንጠንቀቅ!! የአምላካችን የእግዚአብሔር ፍቅር፣ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት ከእኛ ጋር ይሁን፤አሜን፡፡

ይቆየን፡፡

በጎውን ሁሉ ለእኛ ያደረገና የሚያደርግ እግዚአብሔር ስሙ የተመሰገነ ይሁን፤አሜን፡፡

CALL FOR PAPER copy

የጥናታዊ ጽሑፍ ግብዣ

CALL FOR PAPER copy

CALL FOR PAPER

የአሰቦት ገዳም ደን ዳግም ቃጠሎ

መጋቢት 3/2004 ዓ.ም
በእንዳለ ደምስስ
የአሰቦት ገዳም ደን ዳግም በመቃጠል ላይ ይገኛል፡፡ ከመጋቢት 2/2004 ዓ.ም.ከቀኑ አሥር ሠዐት ጀምሮ መነሻው ባልታወቀ ምክንያት ቃጠሎው በአዲስ መልክ እንደተቀሰቀሰ የገዳሙ ማኅበረ መነኮሳት ገልጸዋል፡፡

ከገዳሙ መነኮሳት በደረሰን የድረሱልን ጥሪ መሰረት እሳቱን ለማጥፋት ከአቅማቸው በላይ እንደሆነ በመግለጽ የሚመለከተው አካል አስቸኳይ መፍትሔ እንዲፈልግላቸው በመማጸን ላይ ይገኛሉ፡፡ ከቀኑ አሥር ሠዐት የጀመረው ቃጠሎ በአባ ሳሙኤል ገዳም አቅጣጫ ሲሆን ከፍተኛ የደን ሀብት የያዘና ብዛት ያላቸው የዱር እንስሳትና አእዋፍ የሚገኙበት ነው፡፡ እንዲሁም ራሣቸውን ለእግዚአብሔር አሳልፈው የሰጡ መናንያን ስለ ሀገርና ወገን  ዘግተው የሚጸልዩበት ቦታ እንደሆነ መነኮሳቱ ያስረዳሉ፡፡ ይህንን የደን ሀብት ከቃጠሎው ለመታደግ ለሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት፤ ለወረዳ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፤ ለፖሊስና ለፌደራል ፖሊስና ለምእመናን የድረሱልን ጥሪ በማሰማት አሳቱን ለማጥፋት የሚችሉትን ሁሉ በማድረግ ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ ሆኖም ቃጠሎውን በቁጥጥር ሥር ለማድረግ እንዳልተቻላቸውና ወደ አባ ሳሙኤል ገዳም በመገስገስ በ100 /አንድ መቶ/ ሜትር ርቀት ላይ እንደደረሰ የገዳሙ መጋቢና ም/አበምኔት አባ ዘወልደ ማርያም በሀዘን ገልጸዋል፡፡ የቃጠሎው መባባስ ስጋት ውስጥ የከተታቸው መሆኑንና በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ ጽላቱን ለማውጣት እንደሚገደዱ በመግለጽ  የድረሱልን ጥሪያቸውን በማሰማት ላይ ናቸው፡፡

የገዳሙ አበምኔት አባ ተክለ ማርያም በአሁኑ ወቅት ለመንገዱ ሥራና በደኑ ቃጠሎ ዙሪያ መፍትሔ እንዲፈለግለት በተለይም መንግስት ጥበቃ እንዲመድብ አቤቱታ ለማቅረብ አዲስ አበባ ይገኛሉ፡፡ ከቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ ጋር በጉዳዩ ዙሪያ ውይይት ማድረጋቸውን የገለጹት አበምኔቱ ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ እንደሚያሳውቁና በጥበቃ ዙሪያ ያለውን ችግር በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደሚፈታ ቅዱስነታቸው ቃል ገብተውልናል ብለዋል፡፡

የአሰቦት ገዳም ደን ከየካቲት 20 እስከ የካቲት 24/2004 ዓ.ም. ድረስ ሲቃጠል ቆይቶ በመነኮሳቱ፤ በፌደራል ፖሊስ፤ በኦሮሚያ ፖሊስና ምእመናን ከፍተኛ ተጋድሎ መጥፋቱ የታወሳል፡፡ አንድ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ዳግም ቃጠሎው መቀስቀሱ እጅግ አሳሳቢ አድርጎታል፡፡

መውደቅ አዳማዊ ነው፤ ወድቆ አለመነሣት ግን ዲያብሎሳዊ ነው”

መጋቢት 3/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ኅሩይ ባየ
“ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ”

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቤተ ክርስቲያን ካፈራቻቸው መተርጉማን፣ ሰባኪያንና የእምነት አርበኞች መካከል አንዱ ነው፡፡ ከአሕዛብነት ወደ ክርስትና የተመለሱ ሰዎች ለመጀመሪያ ጊዜ ክርስቲያን ተብለው በተጠሩበት የሦርያ ዋና ከተማ በሆነችው በአንጾኪያ ተወልዶ ያደገው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሕይወቱ በአርአያነቱ የሚጠቀስ መንፈሳዊ አባት ነው፡፡

አንደበቱ ርቱዕ፣ እውነተኛ ሰባኪ ምግባሩ የታረመ መና ባሕታዊና የቤተክርስቱያን መሪ የነበረው ቅዱስ ዮሐንስ የዚህ ዓለም የእንግድነት ቆይታውን ጥሎ ከተሰናበተ በኋላ ወደ 5ተኛው መቶ ዓመት ማጠናቀቂያ አካባቢ በትምህርቱ የተደነቁ በጽሑፉ የተማረኩ ከሕይወቱ የተማሩ ምእመናን “አፈወርቅ የሚል ቅጽል ስም ሰጥተውታል፡፡ “አፈወርቅ” በግሪክኛ Chyrysostomos በእንግሊዝኛው Golden mouth ተብሎ ይጠቀሳል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በ347 ዓ.ም. ተወልዶ በ407 ዓ.ም. ይህቺን ዓለም እስኪሰናበት ድረስ የተሰጠውን የክህነት አገልግሎት የተወጣ የብዙ ብዙ መጻሕፍትን የደረሰ አባት ነው፡፡ በስብከቱና በጽሑፉ የተማረከ አንድ ጸሐፊ “He terrified the comforted and comforted the terrified ዝንጉዎችን ያስደነግጣል የተጨነቁትን ደግሞ ያጽናናል” ብሎ ጽፎለታል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በተለያዩ ክፍለ ትምህርቶች በርካታ ስብከቶችን ሰብኳል፤ ከእነዚህም ውስጥ “አጋንንት በሰው ሕይወት ላይ ሥልጣን አላቸው” ብለው ለሚናገሩ ሰዎች የሰጠው ትምህርት ይጠቀሳል፡፡ ይህን ስሕተት የሆነ አመለካከት እንዲያስተካክሉ በሦስት ተከታተይ ክፍል ትምህርቱን አቀረበ፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ በነበረበት ዘመን ሰዎች እርስ በእርሳቸው የሚጠላለፉበት የሞራል ውድቀት የበዛበት፣ ነገሥታቱ በቤተ ክህነት ላይ እጃቸውን እያስገቡ የስልጣናቸው ማራዘሚያ ያደረጉበት እጅግ ፈታኝ ወቅት እንደነበረ በታሪክ መስታወት እንመለከታለን በአሚነ ልቡና እንዘክረዋለን፡፡

አጋንንት በሰው ሕይወት ላይ ሥልጣን አላቸው ማለት ራስን ከተጠያቂነትና ከዘለዓለማዊ ፍርድ ነጻ እንደሚያደርግ ሳይፈራና ሳይታክት አስተማረ፡፡ ከአጋንንት የሚመጣውን ፈተና በፍጹም ተጋድሎ በነጻ ፈቃድ መመከት እንደሚችል፡፡ ሰበከ “ክፋት /ኀጢአት/ የሰው የተፈጥሮ ጠባይ /ባሕርይ/ ገንዘብ” ነው እያሉ የተሳሳተ መረዳት የነበራቸውን ሰዎችን አስተካከላቸው አብሮ የተፈጠረ /የባሕርይ ገንዘብ/ የሆነ ሥራ ሊታረም እንደማይችል እያሳሰበ ኀጢያት በንስሐ በምክር፣ በተግሳጽ፣ በጾም በጸሎት በተጋድሎ ሊወገድ እንደሚችል ያስገነዝባል፡፡ ኀጢአት የሚመጣው ከራስ ድካም ካልቆረጠ ኅሊና ከሰነፈ ልቡና ከላሸቀ ኅሊና ነው፡፡ አዳምና ሔዋን ከራሳቸው ድካም ተነሥተው ኀጢአትን ሠሩ እንጂ ሰይጣን እጃቸውን ጠምዝዞ እጸ በለስን ቆርጦ እንዳልመገባቸው ይታወቃል፡፡

ለኀጢአት በር ካልተከፈተ እንዝህላልነት ከታረቀ በዓቂበ ልቡና ከተተጋ አጋንንት የወደቁና የታሠሩ ጠላቶቻችን እንጂ በእኛ ላይ ምንም ኀይል የላቸውም “ሰይጣን ታስሯል እአስራቱ የሚፈቱት ፈቃዱን የሚፈጽሙ ሰዎች ናቸው” እንደሚበላው ፈቃደ ሥጋን መፈጸም በዓለሙ ብልጭልጭ ነገር መሳብ ያለልክ መብላትና መጠጣት መጠን የሌለው ሥጋዊ ደስታና ከንቱ ቅዥት አጋንትን ኀይል ያስታጥቃል፡፡

ቅዱሱ የእግዚአብሔር ሰው ዮሐንስ ተጸጽተው ንስሓ የገቡ አባቶችን ለአብነት በመጥቀስ የእግዚብሔርን መሐሪነት አስተምሯል፡፡ እምቢ ብለው ሕይወታቸውን ከንስሐ ያራቁ ሰዎች ደግሞ በጥፋት ጎዳና መጓዛቸውን ሰበከ፡፡ በመጨረሻም “መውደቅ አዳማዊ ነው ወድቆ አለመነሣት ግን ዲያብሎሳዊ ነው” ብሎ አባታዊ ምክሩን ለገሣቸው፡፡

/ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሕይወቱና ትምህርቱ 1999፥108/ “መውደቅ አዳማዊ ነው” እንዴት፥?

ከተፈጠርንበት ሰባት ባሕርያት አንዱ አፈር ነው አፈር ሲታጠብ ቢውል እንደማይነኀጻው የሰዎች ጠባይ በተለያዩ ምክንያቶች ሊጎድፍ ይችላል፡፡ ሰው እንደውሎው እንደ አካባቢው እንደ ግንዛቤው ለሚቀርቡለት ጥያቄ የራሱ የሆነ ግብረ መልስ ይኖረዋል፡፡ በቅድስና ሕይወታቸው የሚታወቁ አባቶቻችን በስሕተት መንገድ ውስጥ አልፈዋል፡፡ ለዚህም ነው አባቶቻችን “ሰው ሆኖ የማይበድል እንጨት ሆኖ የማይጨስ የለም” የሚሉት፡፡

“ጻድቅ ሰባት ጊዜ ይወድቃል” /ምሳ.24፥16 ብሎ ጠቢቡ መናገሩም በምድር ላይ ያለን እኛ በሥጋ ፈቃድ ተታለን በማወቅም ይሁን ባለማወቅ በስሕተትም ይሁን በድፍረት ልንወድቅ እንችላለን፡፡ ዋናው ጥያቄ ለምን ወደቅን? ሳይሆን ለምን አልተነሣንም ነው፡፡

ብዙ ሰዎች ለውድቀታቸው ምክንያት ማቅረብ ይወዳሉ ከተጠያቂነት ለመሸሽ /ለማምለጥ/ የማይቆፍሩት ጉድጓድ የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም፡፡ ምክንያት ጠቃሚ ቢሆን ኖሮ አዳም ሔዋንና እባብ ከተፈረደባቸው ፍርድ ባመለጡ ነበር፡፡ ምክንያት ረብ /ጥቅም/ የሌለው በመሆኑ ለበደሌ ለውድቀቄና ለሽንፈቴ ምክንያቱ እኔ ነኝ ማለትን መለማመድ አለብን፡፡

ነቢዩ ዳዊት “አንተን ብቻ በደልሁ በፊትህም ክፋትን አደረግሁ /መዝ.50፥4/ ብሎ መጸለዩ ተጠያቂነቱን በራሱ አድርጎ ነው፡፡ ነቢዩ ዮናስም የመርከቧ መታወክ የሞገዱ ማየል የነፋሱ ንውጽውጽታ በእኔ ምክንያት የሆነ ነው፡፡ ብሎ ስሕተቱን አምኗል፡፡ ነቢዩ ሙሴ እኔ አንደበቴ ኮልታፋ ነው የፈርዖን አምላክ የእሥራኤል መሪ እንዴት ታደርገኛለህ ብሎ ደካማነቱን አመነ፡፡ ለዚህ ያደረስከኝ እኔ ማን ነኝ ቤቴስ ምንድን ነው? እያሉ መጻተኛነታቸው ያመኑ ጉስቁልናቸውን የተረዱ አባቶች ራሳቸውን በመንፈስ ድኀ አድርገዋል፡፡ ቀራጩም ሲጸልይ “እኔ ኀጢያተኛውን ማረኝ” ብሎ ነበር /ሉቃ.18፥13/

መውደቅ እጅን ለዲያብሎስ መስጠት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር መለየት ነው፤ ከቅዱሳኑ ኅብረት መገለል ነው፡፡ ይህ ደግሞ የመጀመሪያው ሞት ነው፡፡ በመጀመሪያው ትንሣኤ /ትንሣኤ ልቡና/ ተስፋ የሌላቸው ሰዎች ሁለተኛው ሞት /ሞተ ነፍስ/ ይፈረድባቸዋል፡፡ /ራዕ.20፥14/

 

  • አዳም ወደቀ በአምላካችን ቸርነት ተነሣ
  • ነቢዩ ዳዊት ሳተ እግዚአብሔር ይቅር አለው
  • ቅዱስ ጴጥሮስ ካደ መሐሪው አምላክ ይቅር አለው

የአባቱን ሀብትና ንብረት ከፍሎ የኮበለለው ወጣት ወደ ልቡ ሲመለስ አባቱ በይቅርታ ተቀብሎታል፡፡ እኛም መውደቃችን ሳይሆን አለመነሣታችን ሲያሳስበን ይገባል፡፡
መውደቅ /መሳሳት/ አዳማዊ ጠባይ በመሆኑ በመውደቃችን አይፈረድብንም ማንኛውም ሰው ኀጢአትን የመሥራት ዝንባሌ ሊታይበት ይችላልና፡፡ እኛን የሚያስፈርድብን በኀጢአት ላይ አቋም ይዘን በንስሓ አለመነሣታችን ነው፡፡

ዲያብሎስ ስሕተቱን ማመን አልቻለም ስለዚህ ወድቆ ቀረ በበደል ወድቀው በንስሓ ያልተመለሱ ሰዎት የግብር አባታቸውን የዲያብሎስን ፈቃድ ፈጻሚዎች በመሆናቸው ታላቁ ሊቅ ቅዱስ ዮሐንስ መውደቅ አዳማዊ ጠባይ ነው ይለናል፡፡

ዲያብሎስን ተቃወሙት ከእናንተም ይሸሻል እግዚአብሔርን እሺ በሉት ወደ እናንተ ይቀርባል፡፡ /ያዕ.4፥8/ ዲያብሎስን መቃወም ፈቃዱን አለመፈጸም ነው፡፡ ዲያብሎስን መቃወም የምንችለው በጾምና በጸሎት ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሳይጸልዩ ወደ ዕለት ሥራቸው የሚሔዱትን ሰዎች እንዲህ እያለ ይመክራቸዋል፡፡ “ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተህ እግዚአብሔርን ለአምላክነቱ እንደሚገባ አምልከህ ከዚያ በኋላ ወደ ሥራህ ብትሔድ የምትሠራው ሥራ የተባረከና የሰመረ እንደሚሆንልህ አታውቅምን? የሚያስጨንቅህ የዚህ ዓለም ገዳይ አለብህ? እዚህ በምታሳልፈው ጊዜ የእግዚአብሔርን ርዳታና ምሕረት ታገኝ ዘንድ በመረጋጋትና በመጽናናት መንፈስ ሆነህ ትሔድ ዘንድ ስለዚህ ምክንያት ወደዚህ ና፡፡

እርሱ ኀይልህ ጋሻህ ይሆን ዘንድ በሰማያዊ ሥልጣን በመጠበቅ ለጠላቶችህ ለአጋንንት የማትሸነፍ ትሆን ዘንድ ወደዚህ ወደ ጸጋው ዙፋን ና፡፡ በአባቶች ከሚደርሰው ጸሎት ሲታርፍ ካለህ በማኅበር ጸሎት ከተሳተፍክ ቅዱስ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቃል ከሰማህ የእግዚአብሔርን ርዳታ ካገኘህ እነዚህን መሳሪያዎች ከታጠቅህ የትም ብትሔድ እንደአንተ ያሉ ሠሪጋ የለበሱ ጠላቶችህ  ክፉዎች ሰዎች ይቅርና ዲያብሎስ ራሱ ፊትህን ማየት አይችልም ነገር ግን ከቤትህ እንደተነሣህ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሳትመጣ ወደ ገበያ ወደ ሥራ ወዘተ ብትሔድ ብቻህን ያለምንም መንፈሳዊ ትጥቅና ጸጋ እግዚአብሔር ስለምትሆን ሁሉም ነገር በአንተ ላይ ይበረታብሀል፡፡ ጠላቶችህም በቀላሉ ያጠቁሃል፡፡ በቤታችን ውስጥም ሆነ በውጭ ብዙ ነገሮች እንደ ጠበቅነው ሳይሆን በተቃራኒው የሚሆኑብን አስቀድመን ለመንፈሳዊ ነገር ቅድሚያ ስላልሰጠንና ሌላውን የዚህ ዓለም ነገር ከዚያ በኋላ ማድረግ ሲገባን እኛ ግን ቅደም ተከተሉን ስለ ስለምናገለባብጥ ነው፡፡ ስለዚህ ነገሮች ዝብርቅርቃቸው ይወጣል” ይለናል፡፡

ዲያብሎስ ሆይ ብወድቅ እነሣለሁና በጨለማ ብቀመጥ እግዚአብሔር ብርሃን ይሆንልኛልና በእኔ ደስ አይበልህ /ሚክ.7፥8/ ማለት የምንችለው በንስሓ ወደ አባታችን ወደ እግዚአብሔር ስንመለስ ነው፡፡ ኀይልን በሚሰጠን በክርስቶስ ሁሉን ስለምንችል ክፉ ሥራውን እንጂ ዲያብሎስን አንፈራውም፡፡ የሠራዊት አምላክ አቤቱ መልስን ፈትህንም አብራ እኛም እንድናለን” መዝ.79፥7

ለንስሓ ሞት
ለአዘክሮ ኀጢአት
ለቅዱስ ቊርባን የበቃን ያድርገን
“ሁሉ ከእርሱና በእርሱ በእርሱም ነውና ለእርሱ ለዘላለም ክብር ይሁን አሜን” ሮሜ.11፥36

ሐዊረ ሕይወት-ወደ በኬ ደብረ ምሕረት ቅድስት ማርያም

IMG_0018IMG_0028

_MG_0119

_MG_0183

_MG_0110

ተጨማሪ ፎቶዎችን ለመጎብኘት www.facebook.com/mahiberekidusan  ሐዊረ ሕይወት ፤የሕይወት ጉዞ መጋቢት 2/2004 ዓ.ም የሚለውን የፎቶ ማህደር ይመለከቱ

hiwer ticket1

ሐዊረ ሕይወት ፤የሕይወት ጉዞ መጋቢት 2/2004 ዓ.ም

hiwer ticket1

ተጨማሪ ፎቶዎችን ለመጎብኘት www.facebook.com/mahiberekidusan  ሐዊረ ሕይወት ፤የሕይወት ጉዞ መጋቢት 2/2004 ዓ.ም የሚለውን የፎቶ ማህደር ይመለከቱ

assebot2

የአሰቦት ገዳም ደን ቃጠሎ ሪፖርታዥ

መጋቢት 1/2004 ዓ.ም.


በእንዳለ ደምስስ

አይቴ ሀሎከ አምላከ አበዊነ? /የአባቶቻችን አምላክ ወዴት አለህ?/

የአሰቦት ቅድስት ሥላሴና የአባ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ገዳም ደን በእሳት የተቃጠለ ሲሆን  ለማጥፋት በማኅበረ መነኮሳቱና ምዕመናን እንዲሁም በፌደራል ፖሊስና በኦሮሚያ ፖሊስ ከፍተኛ ጥረት ከአምስት ቀናት በኋላ ሊጠፋ ችሏል፡፡

 

የአሰቦት ገዳም በ13ኛው መቶ ክ/ዘመን በአባ ሳሙኤል ዘወገግ የተመሠረተ ሲሆን በ15ኛው መቶ ክ/ዘመን አህመድ ግራኝ አጠፋው፡፡ የገዳሙ መነኮሳትም ከሞት የተረፉት ተበታተኑ፡፡ በዚህ ጊዜ ውስጥ ለረጅም ዘመናት አገልግሎት መስጠት ያልቻለ ቢሆንም አንዳንድ መናንያን ወደቦታው በመሔድ በጸሎት ተወስነው ይኖሩ እንደነበር ይነገራል፡፡ በ1911 ዓ.ም. ንግስት ዘውዲቱ እንደገና ገዳሙ እንዲመሰረት አደረጉ፡፡

 

በ1928 ዓ.ም. የጣሊያን ጦር ኢትዮጵያን በመውረሩ ገዳሙን ለማጥፋት ጥረት አድርጎ ነበር፡፡ አፄ ኃ/ሥላሴ በ1936 ዓ.ም. በተጠናከረ ሁኔታ ገድመው፣ መተዳደሪያ፣ ርስት ጉልት ሰጥተውና ለመነኮሳት መኖሪያ አሰርተው በሥርዓት እንዲጠበቅ አደረጉ፡፡ ሣራ ማርያም አካባቢ / ከአሰቦት ገዳም በስተምዕራብ/ እስከ 300 ወታደሮች ተመድበው ገዳሙንና ደኑን ሲጠብቁ እንደነበር አበመኔቱ የታሪክ ማኅደርን ጠቅሰው ይገልጻሉ፡፡ በ1969 ዓ.ም. የሶማሊያ ጦር ኢትዮጵያን ለመውረር ያደረገውን ጥረት ተከትሎ ወታደሮቹ በመወሰዳቸው ገዳሙ አደጋ ስላንዣበበበት ከገዳሙ የተውጣጡ አራት መነኮሳት ብቻ በየቀኑ መጠበቅ ጀመሩ፡፡ አሁንም በዚህ ሁኔታ ላይ ይገኛል፡፡

 

ለመሆኑ የእሳት ቃጠሎው መነሻው ምንድነው? እንዴትስ አለፈ?

 

የካቲት 20 ቀን

እንደ ገዳሙ አባቶች ገለጻ አራት የሚሆኑ ሰዎች የአሰቦት ቅድስት ሥላሴና የአባ ሳሙኤል ዘደብረ ወገግ ገዳም ከቀኑ 10፡00 ሰዓት ሲሆን ማንነታቸው ያልታወቀ ዘራፊዎች ጥቅጥቅ ያለውን ጫካ ሰንጥቀው በመገሥገስ ላይ ናቸው፡፡ ከሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ጀርባ የገዳሙ 62 ከብቶችና 25 አህዮች ለግጦሽ ተሰማርተዋል፡፡ ወደ ገዳሙ እየቀረቡ የመጡት ማንነታቸው ያልታወቁ ግለሰቦች ከብቶቹን ፍለጋ ጥቅጥቅ ያለው ደን ውስጥ ተሸጎጡ፡፡ ከዚያም ደኑ ሳይበግራቸው ከብቶቹን አግኝተው መንዳት ጀመሩ፡፡ የገዳሙ መነኮሳት እንዳይደርሱባቸውም በተጠንቀቅ ግራ ቀኝ እየተገላመጡ የሚመጣውን ኀይል ለመመከት በመዘጋጀት በጥድፊያ ከብቶቹን ነዷቸው፡፡

 

የገዳሙ ጥበቃ አባላት የእለቱ ተረኞች ሁለት ብቻ ሲሆኑ ከብቶቹ መነዳታቸውን በመረዳታቸው እየጮሁ ተከተሏቸው፡፡ ማኅበረ መነኮሳቱም ተሰባስበው ከብቶቹን ለማስጣል ተረባረቡ፡፡ ከብቶቹን ለመውሰድ የቋመጡት ዘራፊዎች እንዳልተሳካላቸው ሲረዱ ከብቶቹን ጥለው ፈረጠጡ፡፡ መነኮሳቱ ከብቶቻቸውን ይዘው ወደ ገዳማቸው በመመለስ አገር ሰላም ነው ብለው ጸሎት ላይ ተጠምደዋል፡፡

 

ድንገት ከአሰቦት ሥላሴ ገዳም በስተጀርባ ከሚገኘው ደን የተወሰኑ ኪሎ ሜትሮች ርቀት ላይ የእሳት ጭላንጭል መታየት ጀመረ፡፡  ከብቶቹን ለመዝረፍ ያደረጉት ጥረት ያልተሳካላቸው  ደኑን በእሳት አያይዘው ጠፍተዋል፡፡ የደኑን መያያዝ ያስተዋሉት ማኅበረ መነኮሳት እሳቱን ለማጥፋት ያደረጉት ጥረት ሳይሳካ ቀረ፡፡ እሳቱ ደኑን እየበላ ወደፊት ለፊት ወዳለው የተራራው ክፍል መቅረቡን ቀጠለ፡፡ ሌሊቱን ሙሉ መነኮሳቱና መነኮሳይያት ለማጥፋት ሳይቻላቸው ንጋቱ ተተካ፡፡ የደረሰላቸው ግን አልነበረም፡፡

 

የካቲት 21 ቀን

የገዳሙ ዋና መጋቢና ምክትል አበመኔት በሆኑት አባ ዘወልደ ማርያም አስተባባሪነት ለሚመለከታቸው ለሐገረ ስብከቱና ለወረዳው ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ፤ እንዲሁም ለማኅበረ ቅዱሳን የሜኤሶ ወረዳ ማዕከል አባላት ህዝበ ክርስቲያኑን እንዲቀሰቅሱ በመደወል አሳወቁ፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን የሜኤሶ ወረዳ ማእከል አባላት ከወረዳው ቤተ ክህነት ሓላፊዎች ጋር በመሆን ለሚመለከታቸው አካላት ለሐገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ፤ ለአሰበ ተፈሪ፣ ለድሬዳዋ፣ ለሐረር፣ ለአለማያ፤ ለበዴሳ፤ ለናዝሬትና ሌሎችም የማኅበረ ቅዱሳን ማእከላት በማሳወቅ ምእመናንን አስተባብረው እንዲመጡ ለማድረግ ጥረት ተደረገ፡፡ በሜኤሶ ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያንና አጎራባች አብያተ ክርስቲያናት የአደጋ ጊዜ ጥሪ ደወል በማሰማት ለምእመናን ስለ ጉዳዩ ተገለጸ፡፡ ለፌዴራል ፖሊስ፤ ለኦሮሚያ ፓሊስ፣ ለሐገረስብከት ጽ/ቤት፣ ለወረዳ አስተዳደሮች ሁሉ ለማሳወቅ ጥረቶች ተደረጉ፡፡

 

የገዳሙ አበምኔት ከአሰቦት ከተማ እስከ ገዳሙ ያለውን የ18 ኪሎ ሜትር የመኪና መንገድ ለመሥራት የተቋቋመው የመንገድ ሥራ ኮሚቴ ለውይይት ባቀረበላቸው ጥሪ መሠረት አዲስ አበባ ነው የሚገኙት፡፡ የገዳሙ ደን በእሳት መያያዝ የሰሙት በ21/6/2004 ዓ.ም. ጠዋት ነው፡፡፡ ገዳሙ በዋና መጋቢና ም/አበምኔቱ አባ ዘወልደ ማርያም በመመራት ላይ ነው፡፡

 

ምእመናን ጀሪካን ከየቤታቸው በማሰባሰብ ውኃ ሞልተው ወንዶች በጭንቅላታቸው፤ ሴቶች በወገባቸው አዝለው የቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ተቀብለው በእንባ እየተራጩ ከአሰቦት ከተማ እስከ ገዳሙ ያለውን የ18 ኪሎ ሜትር መንገድ መጓጓዣ ስለሌለ በእግር ጉዞ ተያያዙት፡፡

 

የሜኤሶ ከተማ ግብርና ጽ/ቤት የመኪና እርዳታ እንዲያደርጉ በመጠየቃቸው አንድ ፒክ አፕ መኪና በመስጠት ውኃዎቹ በጀሪካን እየተሞሉ ተጫኑ፡፡ 30 የሚደርሱ የመጀመሪያዎቹ ግብረ ኃይሎች በመኪናው ተሳፍረው ቦታው  ደርሰው በጀሪካን ውኃ እያፈሰሱ በቅጠል ለማጥፋት ጥረት አደረጉ፡፡ ከእሳቱ ፍጥነትና ከእሳት አጥፊው ማነስ ጋር ተዳምሮ የማይመጣጠን ሆነ፡፡ አካባቢዉ የሃዘን ቀጠና ሆነ፡፡ አቅመ ደካሞች መነኮሳትና መነኮሳይያት የአገር ሽማግሌዎች አንገታቸውን ቀና አድርገው ወደ ሰማይ በማንጋጠጥ በእንባ የታገዘ ጸሎት ከማድረስ ውጪ ሌላ አማራጭ አልነበራቸውም፡፡ እሳቱ እየገሰገሰ ነው፡፡

 

የሀገረ ስብከትና የየወረዳዎቹ ቤተ ክህነት ሓላፊዎች፤ የኦሮሚያ ፓሊስ ኃይል፤ የፌደራል ፖሊስ ልዩ ኃይል፤ በተለይም ወጣቶች፤ የየቤተ ክርስቲያኑ ሰ/ት/ቤቶች አባላት፤ ማኅበራትና ምእመናን እየገሰገሱ ነው፡፡ ገዳሙ ከተገደመ ጀምሮ ለ800 ዓመታት በግርማ ሞገሳቸው የሚታወቁት የዝግባ፣ የጥድ፣ የዋርካ፣ የወይራ ሰማይ ጠቀስ ዛፎች የእሳቱን ቃጠሎ መቋቋም ተስኗቸው በመገንደስ ላይ ናቸው፡፡

 

ሕዝበ ክርስቲያኑ እየወደቀ እየተነሣ ማጥፋቱን ተያይዞታል፡፡ እሳቱ በነፋሱ ታግዞ ይምዘገዘጋል፡፡ የዱር እንስሳትና አዕዋፍ የሚደርሱበት ጠፍቷቸው ይተራመሳሉ፡፡ ምእመናን ለማጥፋት ይሯሯጣሉ፡፡ የእሳቱ ነበልባል ከ10 ሜትር በላይ ከፍ ብሏል፡፡ እንደ ዘንዶ እየተጥመለመለ እየተወረወረ የሚወጣውን ፍለጋ ይወነጨፋል፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ የሚተመውን እሳት እያዩ  “አንቺ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከምትቃጠይ እግዚአብሔር እኛን ያስቀድመን፡፡ ጥፋትሽን አያሳየን” የሚሉ ምእመናን ያለ የሌለ ጉልበታቸውን በመጠቀም ጦርነት ከእሳቱ ጋር ገጥመዋል፡፡ እሳቱ ፍጥነቱን ጨመረ፡፡ ብርሃንም ለጨለማ እጇን ሰጠች፡፡ ክርሰቲያን ተስፋ አይቆርጥም አይደል? እሳቱ ቢያንስ ቤተ ክርስቲያኑንና የልማት ተቋማቱን እንዳይበላ ለመከላከል እየተፍጨረጨሩ ነው፡፡

 

አንድ ወር ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ከሦስት ጊዜ በላይ የእሳት አደጋ ተከስቷል፡፡ በራሳቸው ጥረት እሳቱን በቁጥጥር ስር አውለውት ነበር፡፡ የዛሬው ግን  የሚቻል አልሆነም፡፡

ምእመናን በጨለማው እየተሯሯጡ ጀሪካኖቻቸውን ተሸክመውና አዝለው የቻለ ለመነኮሳቱና ለምእመናን የሚሆን ስንቅ እየያዘ 18 ኪሎ ሜትሩን እየወደቁ እየተነሱ፣ ስለ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እያነቡ ይከንፋሉ፡፡

 

እግዚአብሔር በአውሎና በወጀብ መካከል መንገድ አለው

እሳቱን በማጥፋት ሂደት ውስጥ እያሉ የካቲት 21 በግምት ከምሽቱ 1፡00 ሰዓት አካባቢ አንድ አሳዛኝ ክስተት ተፈጠረ፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን የሜኤሶ ወረዳ ማእከል ሰብሳቢ ዲያቆን ዘውገ በቀለ እንደገለጹት እሳቱ 10 ሜትር ያህል ተምዘግዝጎ እየነጎደ በንፋሱ ታግዞ በቡድን በማጥፋት የነበሩ ወንድሞችና እኅቶችን ለሁለት ከፈላቸው፡፡ በመካከላቸው ታላቅ የእሳት ባሕር ተከሰተ፡፡ ነበልባሉ ገረፋቸው ራሳቸውን ለመከላከል ትግል ገጠሙ፡፡ ወደላይ የተከፈለው ቡድን እንደምንም አመለጠ፡፡ የታችኛው ቡድን 18 ወጣቶች ግን ዙሪያቸውን በእሳት ተከበቡ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ አብዛኞቹ የሜኤሶ ወረዳ ማኅበረ ቅዱሳን አባላትና የሰ/ት/ቤት አባላት ነበሩ፡፡ ከእነሱም ውስጥ ደግሞ ሁለቱ ሴቶች ናቸው፡፡ ከላይ ያሉ ምእመናን ከለቅሶና ዋይታ ውጪ ምንም ማድረግ አልቻሉም፡፡ እሳቱ ጥርሱን አግጦ አፉን ከፍቶ እነሱንም ሊበላ በመጣደፍ ላይ ነው፡፡ “አይቴ ሀሎከ አምላከ አበዊነ?” የአባቶቻችን አምላክ ወዴት ነህ?  ከዚህ መዓት አውጣን?! በማለት ወደ እግዚአብሔር ጮሁ፣ ያድናቸው ዘንድ መማጸን ወይም በእሳቱ መበላት፡፡ እንደ ንሥር ክንፍ ኖሯቸው በረው አይወጡ ነገር እሳቱ አያስጠጋም፡፡ ተሰባስበው አንድ ነገር አደረጉ፡፡ የኅብረት ጸሎት ማድረግ፡፡ እንባና ለቅሶ ተደባለቀ፡፡ውዳሴ ማርያም ተጀመረ፡፡ በጸሎት ይተጋሉ፡፡ እሳቱ እየተምዘገዘገ ሊውጣቸው በመቅረብ ላይ ነው፡፡ ከላይ ዋይታና ለቅሶ ይሰማቸዋል፡፡ እነሱ ደግሞ ውዳሴ ማርያም በመድገም ላይ ተጠምደዋል፡፡ በዚህ ቅጽበት አሁንም አንድ እፎይታን የሚፈጥር ክስተት ተፈጠረ፡፡ ዞር ብለው ሲመለከቱ አጠገባቸው አነስተኛ ዋሻ አገኙ፡፡ ሁሉም ዘለው ዋሻው ውስጥ ገቡ፡፡ እሳቱ በአምስት ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡ ዋሻው እላዩ ላይ የእሳት ዝናብ እየወረደበት ነው፡፡ እሳቱን አመለጥን ሲሉ በጪሱ ደግሞ ታፈኑ፡፡

 

ውዳሴ ማርያም ጸሎቱ ቀጥሏል፡፡ እኩለ ሌሊት እየተቃረበ ቢሆንም እሳቱ እያየለ ወንድሞችና እኅቶችም በእሳቱ እንደተከበቡ ነው፡፡ ከላይ ነበልባል ከስር ፍምና ጪስ ብቻ፡፡ ከላይ ካሉትና እሳቱን በማጥፋት ላይ ከሚገኙት መካከል በትርፍ ጊዜያቸው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በማገልገል ላይ የሚገኙ ሁለት የፌደራል ፖሊስ አባላት ከዚህ በላይ መታገስ አልቻሉም፡፡ በፌስታል የታሰረ ዳቦ ይዘው ብንሞትም ስለ ሃይማኖታችን እንሙት፡፡ እነዚህ ወንድሞቻችንና እኅቶቻችን ሲሞቱ ዝም ብለን አንመለከትም” በማለት አንድ ወንድም አስከትለው ከሞቱ አጽማቸውን እንሰበስባለን፡፡ ካልሞቱም በሕይወት አብረን እንድናለን፡፡ ከሞትንም አብረን እንሞታለን፡፡ በማለት አፉን ከፍቶ ወደሚጠብቃቻው እሳት ውስጥ ተወርውረው ገቡ፡፡

assebot2

የእግዚአብሔር ተአምር ሆነና እየተንሸራተቱ እሳቱ ላይ እየተረማመዱ እየተለበለቡ ከወንድሞቻቸውና እኅቶቻቸው ጋር ዋሻው ውስጥ ተቀላቀሉ፡፡ አልሞቱም ተቃቅፈው በእንባ ተራጩ፡፡ በድካምና በረሃብ የደከመ ሰውነታቸውን ያጠነክሩ ዘንድ የያዙትን ዳቦ ሰጧቸው፡፡ መዝሙር ይዘመራል፣ እሳቱ ደግሞ ይቀርባል፡፡ መውጫ ቀዳዳ ሁሉ ተደፍኗል፡፡ ከሞት ጋር ተፋጠዋል፡፡ ራሳቸውን ለአምላካቸው ከመስጠት ውጪ ምንም ምርጫ አልነበራቸውም፡፡ ሰለስቱ ደቂቅን ያዳነ አምላክ እንዲያድናቸው ይማጸናሉ፡፡ ባያድናቸውም ስለ ሐይማኖታቸውም እንኳን ለመሞት ቆርጠዋል፡፡ ዝማሬው ግን ቀጥሏል፡፡ “አድኝኝ እናቴ ከስጋ ፈተና….” በዝማሬው መካከል አንዱ በጭንቀት እንደ ተዋጠ አንድ ነገር ትዝ አለው፡፡ ከነኀጢያቴ ልሞት ነው ማለት ነው? ከመሞቴ በፊት የንስሐ አባቴ ጋር መደወል አለብኝ” በማለት ስልኩን ደወለ፡፡ “አባቴ በእሳት ተከበናል፤ እኔና ጓደኞቼ መሞታችን ነው፤ እባክዎ ከመሞታችን በፊት ይፍቱን!” ያቀረበው ጥያቄ ነበር፡፡ የተደናገጡት አባት፡፡” “አይዟችሁ፡፡ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይሁን፤ ሁላችሁንም እግዚአብሔር ይፍታችሁ!” አሏቸው የመረጋጋ ስሜት ውስጡ ተፈጠረ፡፡ በእሳት ውስጥ ከተከበቡት መካካል አንዱ የማኅበረ ቅዱሳን የሜኤሶ ወረዳ ማእከል ሰብሳቢ ዲ/ን ዘውገ በቀለ ሲሆን ስለሁኔታው ሲገልጽ ” በሕይወትና በሞት መካከል ሆነን ምንም ማድረግ ሳንችል ቀርተን በጣም ያዘንኩት የእኛ መሞት ሳይሆን በዝምታ ተውጠን ተራራው በእሳት ሲበላ ፤ከአባቶቻችን  ለትውልድ የተላለፈ ማንነትና ቅርስ ሲናድ ማየቴ ነበር ያስለቀሰኝ” በማለት ነበር የገለጸው፡፡ ሊነጋ ሲል ደግሞ እግዚአብሔር ከንጋቱ ጋር ተገለጠ፡፡ እሳቱ በአንደኛው አቅጣጫ ነፋስ ወደታች ገፍቶት ጠፋ፡፡ ነገር ግን ፍሙን መርገጥ ስለማይችሉ ጥቂት መጠበቅ ነበረባቸው ታግሰው ቆዩ፡፡ ምንም እንዳልተፈጠረ በመቁጠር፤ ከሞት ጋር ግብግብ የፈጠሩበትን ሁሉ ረስተው የሚቃጠለውን ደን ለማጥፋት ፈጠኑ፡፡

 

የካቲት 22 ቀን

የገዳሙ አበምኔት አዲስ አበባ የሔዱበትን ጉዳይ ሳይጨርሱ ወደ ገዳሙ ተመለሱ፡፡ እሳቱን የማጥፋት ተግባር ቀጥሏል፡፡ ከሐረር፣ ከድሬዳዋ፣ ከአለማያና ከናዝሬት ምእመናን እየጎረፉ ነው፡፡  እሳቱን ለማጥፋት ውኃው በእጅ ይረጫል በቅጠል ይቀጠቀጣል፡፡  እሳቱ ተራራውን ጨርሶ ጫፍ ላይ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ እየገሰገሰ ነው፡፡ ከመነኮሳት መኖሪያ የ50 ሜትር ርቀት ብቻ ቀርቶታል፡፡ ባሕታዊ መርአዊ /መነኮሳቱ አይዋ መርኣዊ ይሏቸዋል/ የ80 ዓመት አዛውንት ናቸው፡፡ ከዐርባ ዓመታት በላይ በገዳሙ ውስጥ ኖረዋል፡፡ እሳቱ ከበአታቸው ጋር ፊት ለፊት ተፋጠዋል፡፡ የ50 ሜትር ርቀት ላይ አባ ዘወልደ ማርያም እቃቸውን እንዲወጣ ቢጠይቋቸው አሻፈረኝ አሉ፡፡ “የኔን በአት እግዚአብሔር አያቃጥለውም” በማለት ጸኑ፡፡ በጀሪካን ጸበል ይዘው በመሔድ በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ በማለት ሦስት ጊዜ ረጩት፡፡ እሳቱ ተጥመልምሎ ወደ ምዕራብ ዞረ፡፡ እግዚአብሔር ተአምራቱን ገለጠ፡፡ የመነኮሳቱ ቤቶችም ከመቃጠል ዳኑ፡፡

 

assebot3እሳቱ ተራራውን አገባዶታል፡፡ በልምላሜ ግርማ ሞገስ ተውቦ የሀገር ሀብት፣ የብርቅዬ የዲር እንስሳት አእዋፍ የመናንያንና የተሰወሩ አባቶች መኖሪያ ያ አሰቦት ተራራ እርቃኑን ቀርቷል፡፡ ድንጋዩ ገጦ ባዶውን ተጋልጧል፡፡ ጥቁር የሃዘን ልብስ ለብሷል፡፡ ከሰዓት በኋላ ጋብ ለማለት ሞከረ፡፡ ምእመናን ዝለዋል፤ አቅማቸው ተሟጧል፡፡ እሳቱም አብሮ ተዳከመ፡፡ ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ሲሆን እሳቱም ምእመናንና ማኅበረ መነኮሳቱ የእፎይታን አየር ተነፈሱ፡፡ እሳቱ ቢጠፋም ፍሙ ሙሉ ለሙሉ ባለመጥፋቱ ደግሞ ሊቀሰቀስ ይችላል የሚለው ሥጋት የሁሉም ቢሆንም ምእመናን በተከሰተው ነገር እያዘኑና እያለቀሱ ወደ መጡበት መመለስ ግድ ሆነ፡፡ የሜኤሶ ወረዳ የማኅበረ ቅዱሳን አባላትና የወረዳው ቤተ ክህነት ጸሓፊና ሌሎችም ከመነኮሳቱ ጋር በመነጋገር ለማደር ወሰኑ፡፡

 

የካቲት 23 ቀን

እሳቱ በመጥፋቱ ቀኑን ሙሉ ለሚመለከታቸው አካላት በስልክ በማሳወቅ የጥበቃው ሁኔታ እንዲጠናከር ለማድረግ አቤቱታ በማቅረብ ተዋለ፡፡ መነኮሳቱም በመሰባሰብ ወደፊት በገዳሙ ሕልውና ዙሪያ ምን ማድረግ እንዳለባቸው በመመካከር ነው ያለፈው፡፡ የገዳሙ ግርማ ሞገስ የነበረው በሺዎች ሄክታር የሚገመተው ደን ወድሟል፡፡ የቀረው በአባ ሳሙኤል ገዳም በኩል ያለው ደን ብቻ ነው ማለት ይቻላል፡፡ በመጋቢት 2000 ዓ.ም. ደግሞ 11,000 /አስራ አንድ ሺህ/ ሄክታር ደን መቃጠሉ ይታወሳል፡፡

 

አመሻሽ ላይ የማኅበረ ቅዱሳን አባላትና የወረዳው ቤተ ክህነት ጸሓፊን ጨምሮ ሁላችንም ከአባቶች ቡራኬ ተቀብለን ጉዟችንን ወደ ሜኤሶ ለማድረግ ወስነን ተሰናብተን፡፡ 6 ኪሎ ሜትር ቁልቁለቱን ተያያዝነው ከምሽቱ አንድ ሰዓት ሲሆን ቁልቁለቱን እንደጨረስን ቀና ብለን ወደ ተራራው ተመለከትን፡፡ በልምላሜና በሰንሰለታማነት የሚታወቀው ሰማይ ጠቀሱ ተራራ፤ የገዳማውያን አባቶች መኖሪያ ፤ ጤዛ ልሰው ድንጋይ ተንተርሰው ዳዋ ለብሰው ግርማ ለሊቱን ድምጸ አራዊቱን ጸበ አጋንንቱን ታግሰው ለሃገር ለወገን  የሚጸልዩበት ደንና ዋሻ በከፊል ወድሟል፡፡

 

አንገታችንን ወደ ላይ እንዳቀናን እንባችን ፈሰሰ፡፡  መልሰን ደግሞ ወደ አባ ሳሙኤል ገዳም ተመለከትን፡፡ ከተወሰኑ ኪሎ ሜትሮች ርቀት ላይ አዲስ የደን ቃጠሎ መከሰቱን ተመለከትን፡፡ በዚያች ቅጽበትና ሰዓት የተለኮሰ ነው፡፡ እሳቱ ገና መጀመሩ ነው፡፡ እኛ ካለንበት ቢያንስ የ3 ሰዓት መንገድ ሊያስኬድ የሚችል ነው፡፡ በስልክ ለአበምኔቱ አሳውቀን ሕዝቡን የመቀስቀስ ሥራ ተጀመረ፡፡ በምሽት መሔዱ አደጋ ስለሚያስከትል ያለው ምርጫ እስኪነጋ መጠበቅ ነው፡፡ እሳቱም ባለበት ቆሞ አይጠብቅ ያገኘውን እያጨደ እየሰለቀጠ መጓዙን ይቀጥላል፡፡ ምን ምርጫ አለን?! እሳቱ ወደ ለአባ ሳሙኤል ገዳም  መነኮሳይያት መንደር ተምዘገዘገ፡፡

 

የካቲት 24 ቀን

መረጃው የደረሳቸው ምእመናን፣ የፌዴራል ፖሊስና የኦሮሚያ ፖሊስ በመሰብሰብ በሌሊት ጉዞ ተጀመረ፡፡ ቦታው ሲደረስ ግን ያጋጠመው ችግር የከፋ ነበር፡፡  ማንነታቸው ያልታወቀ ግለሰቦች በምእመናንና በፌደራል ፖሊስ ላይ የተኩስ እሩምታ ከፈቱ፡፡ በቦታውም ብፁዕ አቡነ ዳንኤል የምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና ከቅዱስ ፓትርያርኩ የተላኩ ልኡካን በተገኙበት የፌደራል ፖሊስ በወሰደው እርምጃ ተኩስ የከፈቱ ታጣቂዎችን ከአካባቢው ማራቅ በመቻሉ እሳቱን ለማጥፋት ጥረቱ ቀጠለ፡፡ ወደ የቤቱ ተበታትኖ የነበረው ማኅበረ ምእመናን ጀሪካናቸውን ውኃ ሞልተው ለማጥፋት ተፋጠኑ፡፡ አመሻሽ ላይ በቁጥጥር ስር ዋለ፡፡

 

ማኅበረ መነኮሳቱ ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ከፌደራል ፖሊስ ተወካዮችና ባለሥልጣናት ጋር በጥበቃ ዙሪያ ውይይት የተካሔደ ሲሆን በፌደራል ደረጀ መፍትሔ እንደሚሰጥ ለመነኮሳቱ ተገልጾላቸዋል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ዳንኤል የምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመነኮሳቱ ከመንግሥት የጥበቃ ኀይል እንዲመደብላቸው ለጠየቁት ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ “በተከሰተው ቃጠሎ አዝኛለሁ ለቅዱስ ፖትርያርኩ ስለ ጉዳዩ አሳውቃለሁ፡፡ ከሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጋር በመነጋገር መፍትሔ ይሰጥበታል” በማለት ማኅበረ መነኮሳቱንና ምእመናንን አጽናንተዋል፡፡

 

assebot1የገዳሙ አበምኔት ከዚህ በፊት ስለተከሰተው የደን ቃጠሎ ሲገልጹም በ2000 ዓ.ም. በተመሳሳይ ሁኔታ ከፍተኛ መጠን ያለው ደን በእሳት ቃጠሎ እንደወደመ በማስታወስ “ደኑን ለመጠበቅ ከመንግሥት ጥበቃ እንዲመደብልን በተደጋጋሚ አሳውቀናል፡፡ ደኑ የገዳሙ ብቻ ሳይሆን የሐገር ሀብት ነው፡፡ በረሃማነትን ለመከላከል መንግሥት ጥረት እያደረገ ባለበት ሁኔታ ውስጥ እንዲህ አስከፊ የደን ውድመት መድረሱ አሳዝኖኛል” ብለዋል፡፡ ስጋቱ ግን አሁንም ቀጥሏል፡፡

 

በተደጋጋሚ እየተከሰተ ያለው ቃጠሎ መንስኤዎች ሁለት እንደሆኑ ማኅበረ መነኮሳቱ ይገልጻሉ፡፡ አንደኛው በዋነኛነት አንዳንድ የአካባቢው ነዋሪዎች ከብቶቻቸውን ሳር ለማብላት በሚል የገዳሙን ክልል ጥሰው መግባትና የገዳሙን ከብቶች በየጊዜው ለመዝረፍ መሞከራቸው ነው፡፡ ካልተሳካላቸው ደኑ ላይ እሳት ለቀውበት ይጠፋሉ፡፡ በተደጋጋሚ ከብቶችን የዘረፉ ሲሆን ጉዳዩ በሽምግልና እየተያዘ ለመስተዳደር አካላት አቤቱታ በማቅረብ የማስመለስ ሒደት ነው ያለው፡፡ አልፎ አልፎም እያስቀሩባቸው እንደሆነ በሃዘን ተውጠው መነኮሳቱ ይገለጻሉ፡፡ አሁንም በስጋት ውስጥ ይገኛሉ፡፡

 

ሁለተኛው ደግሞ ከተለያዩ አካባቢዎች የመጡ በምሽት ተደብቀው ዛፍ እየቆረጡ በመውሰድ መተዳደሪያ ያደረጉ ሕገ ወጥ ዛፍ ቆራጮች ከጊዜ ወደጊዜ ቁጥራቸው መጨመሩ ሌላው ስጋታቸው ነው፡፡ ቀን ስለሚደርስባቸው ጨለማን ተገን በማድረግ በቡድን ወደገዳሙ ክልል በመግባት፣ እንዲታያቸው እሳት በማቀጣጠል ዛፎችን ይጨፈጭፋሉ፡፡ እሳቱን ሳያጠፉት ይሔዳሉ፡፡ ቃጠሎም ይቀሰቀሳል፡፡

 

በገዳሙ ውስጥ የመነኮሳት መኖሪያ በቅድስት ሥላሴ ገዳም ዙሪያ ሲሆን የመነኮሳይያት መኖሪያ ደግሞ ገዳሙን በመሠረቱት በአባ ሳሙኤል ዘወገግ ገዳም ዙሪያ ነው፡፡ 50 መነኮሳት፣ 25 መነኮሳይያት፣ መናንያን ባህታውያን የአብነት ተማሪዎችን ጨምሮ 170 የሚሆኑት በገዳሙ ውስጥ ይኖራሉ፡፡

 

የገዳሙ አበምኔት አባ ተክለ ማርያምና የገዳሙ ማኅበረ መነኮሳት እሳቱን በማጥፋት የተባበሩትን ሁሉ በእግዚአብሔር ስም አመስግነዋል፡፡ ለመሆኑ ለገዳሙ ደህንነት ማነው ኃላፊነቱን የሚወስደው? “ ዲያብሎስ ቀስቱን ጨረሰ ዝናሩንም አራገፈ ቤተ ክርስቲያንን ግን ሊያጠፋት አልቻለም” እንዳለው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቅድስት ቤተክርስቲያን በክርስቶስ ደም ላይ ተመስርታለችና ከቶ የሲኦል ደጆች ሊያነዋውጧት አይችሉም!!!