በጅማ ሀገረ ስብከት በምእመናን ላይ በደረሰው ጉዳት ማኅበረ ቅዱሳን አዝኗል

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዝግጅት ክፍሉ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በጅማ ሀገረ ስብከት የም ልዩ ወረዳ ቁንቢ ቀበሌ ሰኔ ፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም በምእመናን ላይ በደረሰው ጉዳት በእጅጉ ማዘኑን ገለጸ፡፡

አቶ ተስፋዬ ቢኾነኝ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊ ‹‹ስለ ኹኔታው የሚደረገው የማጣራት ሥራ እንደ ተጠበቀ እና ወደፊት የሚገለጽ ኾኖ፣ አጥቂዎቹ በወገኖቻችን ላይ ያደረሱት ጉዳት በእጅጉ የሚያሳዝን፤ ሊወገዝ የሚገባው ድርጊትም ነው፡፡ ይህንን ድርጊት የፈጸሙት ሰዎች አካሔዳቸው በየትኛውም የእምነት መሥፈርት፣ ይልቁንም በክርስትና አስተምህሮ ከመንፈሳዊ እምነትና ዓላማው ውጪ ነው›› ሲሉ ተናግረዋል፡፡

ዋና ጸሐፊው አያይዘውም ‹‹ክርስትና የመስቀል ጉዞ እንደ መኾኑ ብዙ ፈተና አለው፡፡ እምነታችን እስከ ዛሬ ድረስ የቆየውም በደማቸው ሰማዕት ኾነው ባለፉ አበውና እማት ተጋድሎ ነው፡፡ በመኾኑም ምእመናን ይህንን ተረድተው በጉዳዩ መደናገጥ የለባቸውም፡፡ ማኅበራችንም በተደጋጋሚ ጉዳት እየደረሰበት ያለውን የጅማ ሀገረ ስብከት ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ከብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ጋር በመተባበር እና መመሪያቸውንም በመቀበል በተቻለው ኹሉ ድጋፍ ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ወደፊትም ድጋፉን ይቀጥላል›› ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ፣ የኢሉባቡርና የጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከዝግጅት ክፍላችን ጋር በስልክ ባደረጉት ቃለ ምልልስ በምእመናን ላይ በደረሰው ጉዳት ማዘናቸውን ገልጸው፣ ከሀገረ ስብከቱ፣ ከእስልምና ጉዳዮች ምክር ቤት፣ ከፌዴራልና ከክልሉ መንግሥት በተመረጡ አባላት የተዋቀረ ኰሚቴ ጉዳዩን እያጣራ መኾኑን አስረድተዋል፡፡ የኰሚቴውን የምርመራ ውጤትም በሀገረ ስብከታቸው በኩል ለሕዝበ ክርስቲያኑና ለዝግጅት ክፍላችን ይፋ እንደሚያደርጉ ብፁዕነታቸው አስታውቀዋል፡፡

በአጥቂዎች ጉዳት የደረሰባቸው ሁለት እኅትማማች ምእመናት በጥቁር አንበሳ ሆስፒታል የሕክምና ርዳታ እየተደረገላቸው ሲኾን፣ በትናንትናው ዕለት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመኾን በሆስፒታሉ ተገኝተው ጉዳት የደረሰባቸውን ምእመናትና ቤተሰቦቻቸውን ማጽናናታቸው ይታወሳል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቭዥንና ሬድዮ ሥርጭቶች ብዙ አድማጭ ተመልካች እንዳላቸው ተጠቆመ፡፡

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ዋና ክፍል በብሮድካስት ሚድያ ክፍል ተዘጋጅተው በየሳምንቱ የሚተላለፉት የማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቭዥንና ሬድዮ ሥርጭቶች ከፍተኛ ተመልካችና አድማጭ እንዳላቸው ተጠቆመ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የብሮድካስት ሚድያ ክፍል ምክትል ዳይሬክተር የኾኑት ዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ፤ ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በኅትመት ውጤቶች (ሐመር መጽሔትና ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ) በመታገዝ በመላው ዓለም ለሚገኙ ምእመናን መንፈሳዊ ትምህርት ሲሰጥ መቆየቱን፤ እንደዚሁም ከ፲፱፺፯ ዓ.ም ጀምሮ በሬድዮ፣ ከ፳፻፭ ዓ.ም ጀምሮ ደግሞ በቴሌቭዥን መርሐ ግብር አገልግሎቱን በማፋጠን ላይ እንደሚገኝ አውስተዋል፡፡

በአኹኑ ሰዓትም ዘወትር እሑድና ሐሙስ በኢቢኤስ የቴሌቭዥን ጣቢያ ይቀርብ የነበረው የአንድ ሰዓት መርሐ ግብር አገር ውስጥ በቀጥታ ባይተላለፍም፣ በአሜሪካን አገር በበርካታ ግዛቶች በማኅበረሰብ ቴሌቭዥን በመተላለፍ ላይ እንደሚገኝ፤ በአገር ውስጥና በሌሎች የዓለም ክፍሎች ለሚገኙ ተመልካቾች ደግሞ ለዚሁ ተብሎ በተዘጋጀው ድረ ገጽ ላይ በሰፊው እየታየ መኾኑን ዲ/ን ቴዎድሮስ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናን የቤተ ክርስቲያናቸውን ትምህርት በስፋት ያገኙ ዘንድ በአማርኛ ቋንቋ ከሚያስተላልፈው ከሁለት ሰዓታት የኢንተርኔት ቴሌቭዥን ዝግጅት በተጨማሪ ለኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ ምእመናን በየሳምንቱ እሑድ ከረፋዱ 4፡30-5፡00 በኦቢኤስ አማካይነት በአፋን ኦሮሞ ልዩ ልዩ ዝግጅቶችን እንደሚያስተላልፍ የጠቀሱት ዲ/ን ቴዎድሮስ፣ ኹሉም የማኅበሩ ዝግጅቶች በመላው ዓለም ብዙ ተመልካቾችና አድማጭች እንዳሏቸው በየጊዜው ከሚያደርጓቸው የዳሰሳ ጥናቶች መረዳታቸውንም ተናግረዋል፡፡

አያይዘውም ከቴሌቭዥን ዝግጅቶቹ በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያኗ ትምህርተ ሃይማኖትና ሥርዓተ እምነት እንዲሁም ልዩ ልዩ መንፈሳዊ ጉዳዮች የሚቀርቡበት ሳምንታዊ የሬድዮ መርሐ ግብር መኖሩንም ተናግረዋል፡፡

በተጨማሪም የማኅበሩ የየሳምንቱ የሬድዮና የቴሌቪዥን ዝግጅቶች Radio/Tv by Phone በሚል መርሐ ግብር በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች በመሠራጨት ላይ እንደሚገኙ፤ እነዚህን መርሐ ግብሮችም አሜሪካ፡- በ(605)475-8172፤ ጀርመን፡- በ+49699.432.98.11፤ ዩናይትድ ኪንግደም፡- በ+4433.0332.63.60፤ ካናዳ፡- በ(604) 670-9698 ላይ ስልክ በመደወል መከታተል እንደሚቻል ዲ/ን ቴዎድሮስ የሰሜን አሜሪካ ማእከል የላከውን ምንጭ ጠቅሰው ጠቁመዋል፡፡

በአጠቃላይ ኹሉንም የማኅበረ ቅዱሳን የሬድዮና ቴሌቭዥን መርሐ ግብሮች በwww.eotc.tv እና በfacebook አድራሻ mahiberekidusan.mkusa መከታተል እንደሚቻል ዝግጅት ክፍሉ አስታውቋል፡፡

የጎንደር ማእከል ፮ኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር አካሔደ፡፡

ሰኔ ፱ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በጎንደር ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ጎንደር ማእከል ግንቦት ፳፰ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ፮ኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በደንቢያ ወረዳ በግራርጌ መካነ ሕይወት አባ ሊባኖስ ቤተ ክርስቲያን አካሔደ፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የአካባቢው ምእመናን፣ የየወረዳ ማእከላት አባላት፣ የደንቢያ ከተማ መንፈሳውያን ማኅበራት እና የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የተገኙ ሲኾን፣ በአጠቃላይ የአካባቢውን ማኅበረሰብ ጨምሮ ከ፲፭፻ በላይ ምእመናን በጉባኤው ተሳትፈዋል፡፡ በዕለቱ በተደረገው ጉባኤም በጎንደር ማእከል የመዝሙርና የኪነ ጥበባት ክፍል አባላት መዝሙርና መንፈሳዊ ሥነ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡

በጠዋቱ መርሐ ግብር የቤተ ክርስቲያኑ ታሪክ በአስተዳዳሪው ከተነገረ በኋላ እጅግ ጠቢብ አትሁን /ጥበ.፯፥፲፯/ በሚል ኃይለ ቃል በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ትምህርተ ወንጌል የቀረበ ሲኾን፣ በመቀጠልም የአብርሃም ቤት እንግዳ ተጋባዥ የኾኑት በማኅበረ ቅዱሳን ቅዱሳት መካናት እና ገዳማት ክፍል ምክትል የቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት ስለ ማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረትና እስከ ዛሬ ድረስ ስላለው የአገልግሎት ኹኔታ ሰፋ ያለ ገለጻ በማድረግ የሕይወት ተሞክሯቸውን አካፍለዋል፡፡

በተጨማሪም ማኅበረ ቅዱሳን ለገዳማት፣ ለአብያተ ክርስቲያናት እና ለአብነት ትምህርት ቤቶች እያደረገ ያለውን አስተዋጽኦ ተናግረዋል፡፡

ከሰዓት በቀጠለው መርሐ ግብርም በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት በደብረ ሃይማኖት መካነ ኢየሱስ የመጻሕፍት ጉባኤ ቤት ደቀ መዝሙር የኾኑት አባ ገብረ ኪዳን ግርማ መንግሥተ ሰማያት በመካከላችሁ ናት /ሉቃ.፲፯፥፳፩/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ከሰጡ በኋላ ሰባኬ ወንጌል ዋኬ ጉንዳ በቤንሻንጉል ጉምዝ ክልል በመተከል ሀገረ ስብከት ዙሪያ ያለውን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ኹኔታ ለጉባኤው ተሳታፊዎች አቅርበዋል፡፡

ሰባኬ ወንጌል ዋኬ አያይዘውም የመተከል ሀገረ ስብከት የሰባክያነ ወንጌል፣ የአገልጋይ ካህናትና የሕንፃ አብያተ ክርስቲያናት እጥረት ያለበት አካባቢ መኾኑን ጠቅሰው ምእመናኑ ቃለ እግዚአብሔርን ለተራቡ ለአካባቢው ወገኖች ሰፊ እገዛ እንዲያደርጉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በዕለቱ በወጣትነት እና ክርስትና፣ በክርስቲያናዊ አለባበስ፣ በፈቃደ እግዚአብሔር፣ በ፵ ቀን ዕድል፣ በካህኑ መልከ ጼዴቅ የዘር ሐረግ፣ ለአብርሃም በተገለጹት ሥላሴ ዙሪያ ከምእመናን የተነሡ ጥያቄዎች በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ሰፊ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

የማእከሉ ሰብሳቢ መምህር ዓለማየሁ ይደግ ንግግር ባደረጉበት ወቅት እንዲህ አይነት መርሐ ግብራት መዘጋጀታቸው በዓለም የባዘኑትን ምእመናን ሕይወት ለመለወጥ ትልቅ ድርሻ እንዳላቸው የገለጹ ሲኾን፣ በመርሐ ግብሩ የተሳተፉ ምእመናንም ጉባኤው አእምሯቸውን ያጎለመሱበት፣ መንፈሳቸውን ያደሱበት፣ ሕይወታቸውን የተፈተሹበትና የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የተረዱበት መኾኑን ገልጸው እንደዚህ ዓይነቱ መርሐ ግብር ለወደፊቱ በዓመት ሦስት አራት ጊዜ ቢዘጋጅ ሲሉ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

በመጨረሻም ለቤተ ክርስቲያኑ ገቢ የሚሆን ገንዘብ ከጉባኤው ተሳታፊዎች ከተሰበሰ በኋላ መርሐ ግብሩ በአባቶች ጸሎትና ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን Encyclopedia ዝግጅት መጀመሩ ተበሠረ፡፡

ሰኔ ፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል ሰኔ ፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከረፋዱ 5፡45 ጀምሮ ከቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትና የዩኒቨርሲቲ ምሁራን ጋር በአዲስ አበባ ከተማ በሰሜን ሆቴል አዳራሽ ባደረገው ውይይት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን Encyclopedia (በጊዜያዊ ትርጕሙ ባሕረ ጥበባት) ዝግጅት በይፋ መጀመሩ ተበሠረ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊ አቶ ሰይፈ ዓለማየሁ የመክፈቻ ንግግር ባደረጉበት ወቅት እንደ ገለጹት ማኅበረ ቅዱሳን በዕቅድ ከሚሠራቸው ዐበይት ተግባራት መካከል ይህ በማኅበሩ ጥናትና ምርምር ማእከል የሚሠራው የEncyclopedia ዝግጅት አንዱ መኾኑን ጠቅሰው ለዚህ ተግባር መሳካት አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ የሚገኙትን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የዩኒቨርሲቲ ምሁራን አመስግነዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል ዳይሬክተር ዶ/ር አባተ መኩሪያው የማእከሉን ዓላማ ለጉባኤው ባቀረቡበት ወቅት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የብዙ ሀብት ምንጭ፣ የጥንታውያን ቅርሶች ባለቤትና የብዙ ሺሕ ምእመናን መገኛ ኾና ሳለ እስከ አሁን ድረስ Encyclopedia ሳይኖራት መቆየቷ ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን ለአገርም ክፍተት የሚፈጥር መኾኑን ገልጸው የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል ይህንን ችግር ግምት ውስጥ በማስገባትና የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለትውልድ ለማስተላለፍ ይቻል ዘንድ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመመካከር ባሕረ ጥበባት ለማዘጋጀት መወሰኑን አብሥረዋል፡፡

የዝግጅት ሥራውን በተመለከተ የEncyclopedia ዝግጅቱ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ ሊቀ ጳጳስ የሚመራ የአማካሪ ቦርድ፣ እንደዚሁም የአርትዖት ክፍል አባላት እንዳሉትና በዝግጅቱም ከሦስት መቶ ሰባት ባላይ የአገር ውስጥና የውጭ አገር ባለሙያዎች እንደሚሳተፉበት ዶ/ር አባተ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

ከአማካሪ ቦርድ አባላት መካከል አንዱ የኾኑት መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን በዕለቱ አስተያየት ሲሰጡ የአንድ ሺሕ ኪሎ ሜትር ጉዞ በአንድ ርምጃ ይጀምራል የሚለውን ብሂል ጠቅሰው ይህ የባሕረ ጥበባት ዝግጅትም ጥሩ ጅማሬ ነውና እንደ ጥሩ ፍጻሜ ይቈጠራል ብለዋል፡፡ ሥራው ብዙ ፈተናና ድካም እንደሚኖረው የተናገሩት መልአከ ታቦር እኛ ከማለፋን በፊት ጅማሬውን ብናየው ደስ ይለናል ካሉ በኋላ አቋራጭ መንገዶችን በመጠቀም በቅርቡ ለንባብ እንዲበቃ ጥረት ማድረግ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ Encyclopedia ከሚለው ቃል ትርጕም አኳያም መድበል የሚለው ቃል በትርጕሙ ውስጥ ቢካተት የተሻለ መኾኑን ጠቅሰዋል፡፡

ሌላው የአማካሪ ቦርድ አባል ቀሲስ ዶ/ር ምክረ ሥላሴ ገብረ አማኑኤል በበኩላቸው ለዚህ ሥራ እዚህ ደረጃ ላይ መድረስ ጥረት ሲያደርግ የቆየውን ማኅበረ ቅዱሳንን አመስግነው የቤተ ክርስቲያን Encyclopedia እስከ አሁን ድረስ አለመዘጋጀቱ ቢያስቈጭም እኛ ግን መቀመጥ የለብንም ብለዋል፡፡ አያይዘውም Encyclopedia የሚለው ቃል ከግሪክ ቋንቋ የተወሰደና ትርጕሙም የጥበብ (የዕውቀት) መገኛ (ስብስብ) ማለት መኾኑን ጠቅሰው ባሕረ ጥበባት ከሚለው ትርጕም በበለጠ ሊገልጸው የሚችል አቻ ትርጕም ሊሰጠው እንደሚገባ ጠቁመው እንደ መነሻም መዝገበ አእምሮ፣ መዝገበ ጥበባት ወይም ፈለገ አእምሮ፣ ፈለገ ጥበባት፣ ወዘተ በሚል ቢተረጐም የሚል ዐሳብ ሰጥተዋል፡፡

ሌሎች የአማካሪ ቦርዱ እና የአርትዖት ክፍሉ አባላትም አስተያየት በሰጡበት ወቅት በዝግጅቱ መጀመርና የዝግጅቱ አባላት በመኾቸው የተሰማቸውን ደስታ ገልጸው ይህ ሥራ በሚሠራበት ጊዜ ልዩ ልዩ ፈተናዎችና ነቀፋዎች ሊያጋጥሙ እንደሚችሉ ከወዲሁ በመረዳት ኹሉንም ነገር ለበጎ መኾኑን ማስተዋልና ችግሮችንም በትዕግሥት ማለፍ አስፈላጊ መኾኑን ተናግረዋል፡፡ ለዚህም እግዚአብሔርን በጸሎት መጠየቅ እንደሚገባ ለራሳቸውም ለሌሎች የዝግጅቱ አባላትም አባታዊና ወንድማዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

በውይይቱ ማጠቃለያም የአማካሪ ቦርድ እና የአርትዖት ክፍል ሥራ አስፈጻሚ ኰሚቴ የተዋቀረ ሲኾን፣ በዚህ መሠረት ለአማካሪ ቦርዱ፡- ፕ/ር ሽፈራው በቀለ ሰብሳቢ፣ ፕ/ር ባየ ይማም ምክትል ሰብሳቢ፣ ዶ/ር አባተ መኩሪያው ጸሐፊ፤ ለአርትዖት ክፍሉ ደግሞ፡- ዶ/ር ዮሐንስ አድገህ ሰብሳቢ፣ ዶ/ር አበባው ምናዬ ምክትል ሰብሳቢ፣ ዲ/ን ሙሉዓለም ካሣ ጸሐፊ ኾነው በምልዓተ ጉባኤው ተመርጠዋል፡፡

በመጨረሻም በዕለቱ የመርሐ ግብሩ መሪ የነበሩት የEncyclopedia ዝግጅት ክፍል ሰብሳቢው ዶ/ር ዮሐንስ አድገህ ለጉባኤው ተሳታፊዎችና ውይይቱ የተካሔደበትን አዳራሽ በነጻ ለፈቀደው ለሰሜን ሆቴል ምስጋና ካቀረቡና ለእንግዶቹም የምሳ መስተንግዶ ከተደረገ በኋላ መርሐ ግብሩ በጸሎት ተፈጽሟል፡፡

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈሰ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን::

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፭ ቍጥር ፻፷፬ በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው የዘንድሮዉን መደበኛ የርክበ ካህናት ስብሰባ የጉባኤው መክፈቻ ሥርዓተ ጸሎት ከተፈጸመበት ከበዓሉ ዋዜማ ከግንቦት ፲፮ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ጀምሮ እስከ ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረ ለዐሥራ ስድስት ቀናት ያህል ባደረገው ጉባኤ ጠቀሜታ ባላቸው የአጀንዳ ነጥቦች ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳልፏል፡፡

ከእነዚህ መካከል የሚከተሉት በዋናነት ይጠቀሳሉ፤

፩. የ፳፻፰ ዓ.ም የርክበ ካህናት ጉባኤን በተመለከተ ቅዱስ ፓትርያርኩ ያደረጉት የመክፈቻ ንግግር እንዳበቃ ጉባኤው ሥራውን ቀጥሏል፡፡

፪. የቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ዓመታዊ ሪፖርት በጽሑፍ ቀርቦ ጉባኤው ካዳመጠ በኋላ በሪፖርቱ ላይ ውይይት በማድረግ ለወደፊቱ የሚወሰኑት ኹሉ የአፈጻጸምƒƒ‚ ችግር እንዳይደርስባቸው ክትትል ይደረግ ዘንድ ተወስኗል፡፡

፫. እስከ አሁን እየተሠራበት ያለው ቃለ ዓዋዲ የቤተ ክርስቲያናችን መተዳደሪያ ደንብ ወቅቱን ባገናዘበ መልኩ እንዲሻሻል በተሰጠው መመሪያ መሠረት የተዘጋጀው ረቂቅ ቀርቦ ምልዓተ ጉባኤው ከተነጋገረበትና ከታየ በኋላ የረቂቁ ዝግጅት በቋሚ ሲኖዶስ ታይቶ እንዲታተም ተወስኗል፡፡

፬. ስለ ቅዱስ ፓትርያርክ እንደራሴ አስፈላጊነት ጉዳይ ቅዱስ ሲኖዶስ ከተነጋገረ በኋላ የእንደራሴ አስፈላጊነት በምን ዓይነት ሕግ ላይ ተመሥርቶ መመረጥ አለበት የሚለዉን በማጥናት ለጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የሚያቀርቡ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትን ጨምሮ ሰባት አባላት እንዲመረጡ ተደርጓል፡፡

፭. ተፈጥሮ ባስከተለው ድርቅ ምክንያት በየመጠለያው ለሚገኙ ወገኖች የዕለት ደራሽ ርዳታ፣ ለተፈናቀሉ ወገኖችም ለመልሶ ማቋቋሚያ አገልግሎት የሚውል የገንዘብና የቁሳቁስ ርዳታ ይደረግ ዘንድ ቤተ ክርስቲያን ጥሪዋን ታስተላልፋለች፤ የድርሻዋንም አስተዋፅኦ አድርጋለች፡፡

፮. በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት የሚያገለግል ሕንፃ ƒƒመገንባት ይቻ ዘንድ ቦታ እንዲሰጥ ከገዳሙ ማኅበረ መነኰሳት የቀረበውን ጥያቄ ምልዓተ ጉባኤው የተቀበለው ስለኾነ፣ በቤተ ክርስቲኒቱ ማእከላዊ አስተዳደር በኩል ቦታ ተፈልጎ እንዲሰጥ ተዋስኗል፡፡

፯. ቅዱስ ሲኖዶስ በየአህጉረ ስብከቱ ክፍት በኾኑ መንበረ ጵጵስናዎች ብቁ የኾኑ ኤጲስ ቆጶሳትን መርጦ ለመሾም ባለው ዕቀድ መሠረት፣

ፈተናዉንና መሰናክሉን ኹሉ አልፈው ዕውቅና ያገኙትን፤

በብሔር ዓቀፍና በዓለም ዓቀፍ ትምህርት የበሰሉትን፤

የወቀውቱንም ችግር ይፈታሉ ተብለው እምነት የተጣለባቸውንና የሚጣልባቸውን፤

ለተልእኮ የሚፋጠኑትን መነኰሳት በመመርመር፣ በማጥናትና በማጣራት ውጤቱን እስከ ሰኔ ፴ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ድረስ የሚያቀርብ አስመራጭ ኰሚቴ እንዲቋቋም ተደርጓል፡፡

፰. ሀ. ብፁዕ አባ ያሬድ ሊቀ ጳጳስ የኢትዮጵያ ሱማሌ ሀገረ ስብከት ሥራን እንደያዙ በአርሲ ሀገረ ስብከት፤

ለ.ብፁዕ አባ እንጦንስ ሊቀ ጳጳስ በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከ፤

ሐ.ብፁዕ አባ ያዕቆብ ሊቀ ጳጳስ በደቡብና ምዕራብ አፍሪካ አህጉረ ስብከት፤

መ.ብፁዕ አባ እንድርያስ ሊቀ ጳጳስ የሊቃውንት ጉባኤ የበላይ ሓላፊነቱን ሥራ እንደያዙ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል የበላይ ሓላፊ በመኾን ተመድበው እንዲሠሩ ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡

፱. በውጭ ላሉት አህጉረ ስብከት ጥናት ተደርጎ በቋሚነት የሚሠሩ አባቶች እስኪመደቡ ድረስ፣

ሀ/ ሰሜን፣ ሰሜን ምሥራቅና ሰሜን ምዕራብ አውሮፓ አህጉረ ስብከት፣

ለጊዜው በብፁዕ አባ ሙሴ የደቡብ ምዕራብና የደቡብ ምሥራቅ አውሮፓ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

ለ/ አውስትራልያ ሀገረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ሔኖክ የምዕራብ ወለጋና የአሶሳ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

ሐ/ ምሥራቅ አፍሪካ፣ ኬንያና ጅቡቲ አህጉረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ዳንኤል የድሬዳዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ፤

መ/ ሥራቅ አፍሪካ፣ ሰሜን ሱዳንና ግብፅ አህጉረ ስብከት፣

በብፁዕ አባ ሉቃስ በክልል ትግራይ ዞን ወልቃይት ጸገዴ ሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ ኾኖ፣

በተጨማሪም የትንሣኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት የበላይ ሓላፊ ኾነው እንዲሠሩ፤

ሠ/ ደቡብ ሱዳን ሀገረ ስብከት፤

በብፁዕ አባ እስጢፋኖስ የጅማ፣ የኢሉባቡርና ጋምቤላ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ተደርቦ እንዲሠራ ሲል ምልዓተ ጉባኤው በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ወስኗል፡፡

፲. በውጭ አህጉረ ስብከት ካሉት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር ያለው የሰላሙ ንግግር ይቀጥል ዘንድ ሰላም ለማንኛውም መሠረት መኾኑ ታምኖበት ይህንኑ ሰላም ለማምጣት አስፈላጊው ጥረት ኹሉ እንዲደረግ፡፡

፲፩. ስለ አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ረዳት ሊቀ ጳጳስ ምደባ ጉዳይ ቅዱስ ሲኖዶስ ከተወያየ በኋላ በሕገ ቤተ ክርስቲያን አንቀጽ ፶ መሠረት ብፁዕ አባ ሕዝቅኤል በያዙት ሀገረ ስብከት ሥራቸው ላይ ደርበው እስከ ጥቅምት ወር ፳፻፱ ዓ.ም ድረስ የፓትርያርክ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ኾነው እንዲሠሩ ተስማምቷል፡፡

፲፪. በየሦስት ዓመቱ የሚደረገው የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ እኪኪያጅና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ምርጫ ካሉት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል በማወዳደር፡-

ሀ. ብፁዕ አባ ዲዮስቆሮስ ሊቀ ጳጳስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣

ለ. ብፁዕ አባ ሳዊሮስ ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ኾነው ለሚቀጥሉት ሦስት ዓመታት እንዲሠሩ በቅዱስ ሲኖዶስ ተመርጠዋል፡፡

፲፫. በሕፃናትና ቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት ሓላፊነት በቤተ ክርስቲያናችን እየተረዱ የሚያድጉ እጓለ ማውታ ሕፃናት በየአህጉረ ስብከቱ መኖራቸው የሚታወቅ ነው፤ ይኸው የሕፃናትና የቤተሰብ ጉዳይ ድርጅት እጓለ ማውታ ሕፃናትን በማሳደግና በማስተማር ረገድ ለሀገራችንና ለቤተ ክርስቲያናችን ትልቅ አለኝታ ስለኾነ፣ አስከ አሁን ከነበረው ይዘት በበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል በቅዱስ ሲኖዶስ ተወስኗል፡፡

፲፬. የቤተ ክርስቲያናችን እምነትና ሥርዓተ አምልኮ እስከ አሁን ድረስ ተከብሮና ተጠብቆ እንደ ኖረ ኹሉ አሁንም ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ያለው የመንፈሳዊና የማኅበራዊ አገልግሎት መዋቅር በበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡

፲፭. በቤተ ክርስቲያኒቱ ማእከላዊ አሰዝተዳደር ቀልጣፋና ቅንነት የሰፈነበት አሠራር እንዲኖር፣ በየደረጃው የተዘረጉትም የልማት አውታሮች የበለጠ ውጤት እንዲኖራቸው ለማስቻል፣ ከመንበረ ፓትርያርክ ሥራ አስኪያጅ ጀምሮ ኹሎችም የየአህጉረ ስብከቱ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሓላፊነት ያለባቸው ስለኾነ ተከታትለው እየሠሩ እንዲያሠሩ ተወስኗል፡፡

፲፮. በመከናወን ላይ ለሚገኘው የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ፕሮጀክት አጀማመር ኹሉም ኅብረተሰብ እጁን ሲዘረጋ እንደቆየ ኹሉ፣ አሁንም ለፕሮጀክቱ አፈጻጸም መላው ኀብረተሰብ የበኩሉን ድርሻ ይፈጽም ዘንድ ቀዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡

፲፯. ከሀገራችን ኢትዮጵያ ውጭ ባሉት አንዳንድ አህጉር እየደረሰ ያለውን የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ ችግር በጆራችን እንሰማለን፤ በዓይናችንም እናያለን፡፡ ለማስረጃም ያህል፡-

በመሬት መንቀጠቀጥ፣ በጎርፍ መጥለቅለቅና በሰደድ እሳት ዘግናኝ አደጋ የሚደርስ ኅልፈተ ሕይወት፤

በእርስበርስ የውስጥ ጦርነት የደረሰውና እየደረሰ ያለው ዕልቂት፤

የእግዚአብሔርን ህልውና በሚፈታተኑ አንዳንድ ግለሰቦች ግንዛቤ ጉድለት እየደረሰ ያለው የጦርነት አደጋ፤

በየብስ፣ በውቅያኖሶችና በሰማይ ላይ በሚበሩ አውሮፕላኖች የሚደርሰው ዘግናኝ ዕልቂትና የመሳሰሉት ከሚጠቀሱት መካከል ናቸው፡፡

ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችን ጉዳት ለደረሰባቸው መጽናናትን፣ መረጋጋትን እንዲሰጥልን፤ ቅን ልቡና፣ ትሑት ሰብእና ለሚጎድልባቸው የኅብረተሰብ ክፍሎችም ትዕግሥቱን፣ ርኅራኄውን እንዲያበዛልን እንጸልያለን፡፡

በመጨረሻም በሀገራችን ጎልቶ የሚታየው ድህነት እንዲወገድ፤ የተራበው፣ የተጠማው፣ የታረዘው መሠረታዊ ፍላጎቱ ተሟልቶለት እንዲኖር፤ በሀገራችን ኢተዮጵያ፣ በዓለሙም ኹሉ ሰላም እንዲሰፍን ቅዱስ ሲኖዶስ በመጸለይ ስብሰባውን በጸሎት አጠናቋል፡፡

እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቦቿን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤

አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም

ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሰኔ ፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም፡፡

፲፰ኛው የአሜሪካ ማእከል ጠቅላላ ጉባኤ ተካሔደ።

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአሜሪካ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል ፲፰ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በሲያትል ዋሺንግተን ቅዳሜ ግንቦት ፳ እና እሑድ ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ተካሔደ።

በጉባኤው ወደ ፬፻ የሚደርሱ የማእከሉ አባላት፤ የዲሲና የአካባቢው እንዲሁም የካሊፎርንያና ምዕራብ አሜሪካ አህጉረ ስብከት ተወካዮችና የሥራ አስፈጻሚ አባላት፤ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎችና ካህናት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ተገኝተዋል።

ጉባኤው በጸሎተ ኪዳን በተጀመረበት ቅዳሜ ግንቦት ፳ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የማእከሉ ሰብሳቢ ዶ/ር ሕልምነህ ስንሻው የእንኳን ደኅና መጣችሁና የመክፈቻ ንግግር ካደረጉ በኋላ በማእከሉ የተተገበሩ ዋና ዋና የአገልግሎት ሥራዎችን ዘገባ አቅርበዋል። የዲሲ እና የአካባቢው ሀገረ ስብከት ዋና ጸሐፊ መልአከ ሰላም ቀሲስ ዶ/ር መሥፍን ተገኝም የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የብፁዕ አቡነ ፋኑኤልን መልእክት ለጉባኤው ካስተላለፉ በኋላ በመልአከ ሰላም ቀሲስ ደጀኔ ሽፈራው “ሥራ የበዛበት ትልቅ በር” /፩ኛቆሮ. ፱፥፲፮/ በሚል ኃይለ ቃል ትምህርተ ወንጌል ተሰጥቷል፡፡

በመቀጠል የማእከሉ የአገልግሎት ክፍሎች ዓመታዊ ጠቅላላ ሪፖርትና የቀጣይ ዓመት ዕድቅ ለጉባኤው ቀርቧል፡፡ በቀረበው ሪፖርትም በንዑሳን ማእከላት በርካታ ትምህርታዊ ጉባኤዎች እንደተካሔዱ፣ በልዩ ልዩ ከተሞች የማኅበረሰብ ቴሌቪዥን ፕሮግራም እንደተጀመረ፣ ለገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች፣ እንዲሁም ኢአማንያንን ለማስተማርና ለማስጠመቅ ለተዘረጋው የስብከተ ወንጌል ፕሮጀክት ከአባላት እና ከምእመናን የተሰበሰበ የእርዳታ ገንዘብ ወደ ዋናው ማእከል እንደተላከ ተገልጿል።

የማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል ተወካይ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም የዋናውን ማእከል መልእክት እና ሪፖርት ባቀረቡበት ወቅት ከጉባኤው ለቀረቡላቸው ጥያቄዎች ምላሽ ከመስጠታቸው በተጨማሪ የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴና ወቅታዊ ጉዳዮችን በማስመልከት ሰፊ ማብራሪያ አቅርበዋል።

በሁለቱ ቀናት ጉባኤ ላይ በሲያትል ንዑስ ማእከል የአቡነ ጎርጎርዮስ ትምህርት ቤቶች ተማሪዎች ውዳሴ ማርያምና ሰዓታት በንባብና በዜማ፤ የጸሎተ ቅዳሴ ተሰጥኦና ምስባክ፤ እንደዚሁም የአብነት ትምህርትን አሰጣጥና ሒደት የሚያሳይ ሥርዓተ ማኅሌት፣ ቅኔ፣ የመጻሕፍት ትርጓሜ እና የተለያዩ መንፈሳዊ ዝግጅቶችን አቅርበዋል።

በተጨማሪም የሲያትል ንዑስ ማእከል የአገልግሎት ተሞክሮዉን ለጉባኤው ያካፈለ ሲኾን፣ የማእከሉ የአገልግሎት ክፍሎች የበጀት ሪፖርትም ለጉባኤው ቀርቦ ውይይት ተደርጎበታል። ከስድስት ወር በኋላ የማእከሉ የዕቅድ ክለሳ እንደሚደረግም በጉባኤው ተገልጿል።

እንዲሁም ዝክረ አበው በሚል መርሐ ግብር የሊቀ ጉባኤ አባ አበራ ሰባተኛ ዓመት የዕረፍት መታሰቢያ በማስመልከት የተዘጋጀ ፊልም ለእይታ በቅቷል።

በዕለቱ ላለፉት ሁለት ዓመታት ማዕከሉን ይመራ የነበረው የሥራ አስፈጻሚ የሥራ ዘመን በመፈጸሙ፣ ለሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት ማእከሉን በሥራ አስፈጻሚነት የሚመሩ ፲፫ አባላት በጸሎትና በዕጣ ተመርጠዋል።

በጉባኤው ማጠቃለያ በማእከሉ ፲፰ኛ ጠቅላላ ጉባኤ አዘጋጅ ኮሚቴ የዝግጅቱ ሒደትና በሲያትል ከተማ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የሰበካ ጉባኤ አባላት፣ የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶችና ምእመናን በልዩ ልዩ መንገድ ያበረከቱት ከፍተኛ አገልግሎት በዝርዝር የቀረበ ሲኾን ይህ አሳታፊነትና ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ጋር በቅንጅት የመሥራት ልምድ ለሌሎች ንዑሳን ማእከላትና ግንኙነት ጣቢያዎች ያለው አርአያነት የጎላ መኾኑ ተገልጿል።

በመጨረሻም ፲፱ኛው የማእከሉ ጠቅላላ ጉባኤ በቦስተን፣ ፳ኛው ጠቅላላ ጉባኤ ደግሞ በቨርጂንያ እንዲካሔድ ተወስኖ ጠቅላላ ጉባኤው በዝማሬ እና በጸሎት ተጠናቋል።

የቅዱስ ያሬድን ፲፭፻፫ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የቅኔ ውድድር ተካሔደ፡፡

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በጎንደር ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤተፐች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በጎንደር ማእከል አዘጋጅነት ግንቦት ፲፬ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የቅዱስ ያሬድን ፲፭፻፫ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ በጎንደር ከተማ በርእሰ አድባራት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ ውድድር ተካሔደ፡፡

የውድድሩ ተሳታፊ ጉባኤ ቤቶች፡- የደብረ ፀሐይ ቍስቋም ማርያም፣ የደብረ ምሕረት አቡን ቤት ቅዱስ ገብርኤል፣ የቀዳሜ አድባራት አበራ ጊዮርጊስ፣ የመካነ ሕይወት ፊት አቦ እና የደብረ ገነት አዘዞ ቅዱስ ሚካኤል ቅኔ ጉባኤ ቤቶች ሲኾኑ፣ መምህራኑ የመረጧቸው ደቀ መዛሙርትም ጉባኤ ቤቶቹን ወክለው ለውድድር ቀርበዋል፡፡

ውድድሩን በዳኝነት የመሩትም መምህር ፍቅረ ማርያም የመንበረ መንግሥት መድኃኔ ዓለም የ፬ቱ ጉባኤያት ምክትል መምህር፣ ሊቀ ብርሃናት ኤልያስ አድማሴ በዐቢየ እግዚእ ኪዳነ ምሕረት የብሉይ ኪዳን መምህር እና መምህር ቃለ ሕይወት በመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት የሐዲስ ኪዳን መምህር ሲኾኑ የውድድሩ መሥፈርቶችም አንደኛ የቅኔው ምሥጢር፣ ሁለተኛ የዜማው ልክ፣ ሦስተኛ ገቢር ተገብሮ አገባብ፣ አራተኛ የቃላት አመራረጥ እና አምስተኛ የጊዜ አጠቃቀም ናቸው፡፡ እያንዳንዱ መሥፈርት ፳፣ ባጠቃላይም ፻ ነጥቦችን የያዘ ሲኾን ለእያንዳንዱ ተወዳዳሪም የ፲፭ ደቂቃ የማቅረቢያ ጊዜ ተሰጥቶታል፡፡

በውድድሩ ከአንደኛ አስከ ሦስተኛ ደረጃ የያዙት የወንጌል አንድምታ ትርጓሜ መጻሕፍትን፤ አራተኛና አምስተኛ የወጡት ደግሞ የትንቢተ ኢሳይያስን አንድምታ ትርጓሜ መጽሐፍ ተሸልመዋል፡፡ ይኸውም ቅኔ ተምረናል በቃን ብለው እንዳያቆሙ እና ቀጣይ መጻሕፍትን እንዲማሩ ለማሳሰብ ነው፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የማእከሉ ሰብሳቢ መምህር ዓለማየሁ ይደግ እንደተናገሩት የውድድር መርሐ ግብሩ የተዘጋጀበት ዓላማ በጉባኤ ቤቶች መካከል መልካም የሆነ የውድድር መንፈስ እንዲኖር፣ ተማሪዎቹ ራሳቸውን እንዲፈትሹ ለማድረግ፣ የቅኔ ትምህርት በማኅበረሰቡ ዘንድ እንዲታወቅ፣ የበታቾቻቸውን ለማነሣሣት እና በዋናነት ቅዱስ ያሬድን ለመዘከር ነው፡፡

የጎንደር ከተማ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህናት ሊቀ አእላፍ ጥበበ አወቀ በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው እንደዚህ ዓይነቱ መርሐ ግብር እየቀዘቀዘ የመጣውን የአብነት ትምህርት በተለይ የቅኔ ትምህርት እንደሚያጠናክር ጠቅሰው ይህም ማኅበረ ቅዱሳንን እንደሚያስመሰግነው ገልጸዋል፡፡ አያይዘውም ለደቀ መዛሙርቱ አባቶቻችን ይህን ትምህርት በእግዚአብሔር ኃይል ጸንተው፣ ኮቸሮ በልተው፣ በውሻ ተበልተው አቆይተውናል፤ እኛም ጠብቀን ለትውልድ ማቆየት ይኖርብናል ሲሉ ተናግረዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ በስድስቱም ጉባኤ ቤቶች የሚገኙ በርካታ የአብነት ተማሪዎች እና በርካታ ምእመናን የተገኙ ሲኾን፣ ከምእመናኑም ይህ የቅኔ ትምህርት እንዲስፋፋ ሰፊ ትኩረት ተሰጥቶት ሊሠራ እንደሚገባው አስተያየት ተሰጥቷል፡፡

የጎንደር ማእከል መዘምራንም ቅዱስ ያሬድን የሚዘክሩ የሰማይ ምስጋና የሚል የንስሐ መዝሙር እና ያሬድ ማኅሌታይ ለእግዚአብሔር ካህኑ የሚል ወረብ አቅርበዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ መምህር በጽሐ ዓለሙ በመንበረ መንግሥት መድኃኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን የ፬ቱ ጉባኤያት ምክትል መምህር በአብነት ትምህርት ቤት ሦስት ዓይነት ተማሪ አለ፤ እነሱም፡- እግረ ተማሪ፣ ልብሰ ተማሪ እና ልበ ተማሪ ናቸው ካሉ በኋላ ኹላችንም ልበ ተማሪን ኾነን ትምህርታችንን በሚገባ መማር አለብን ብለዋል፡፡

በመጨረሻም በአባቶች ጸሎት መርሐ ግብሩ ተጠናቋል፡፡ ይህ መርሐ ግብር በፋና ኤፍ ኤም 98.1 የሬድዮ ጣቢያም የሚዲያ ሽፋን ማግኘቱ የሚታወስ ነው፡፡

የአዳማ ማእከል የሕክምና አገልግሎት ሰጠ፡፡

ግንቦት ፳፭ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በአዳማ ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል በዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ለሚገኙ አባቶችና እናቶች መነኮሳት እንዲሁም ለአብነት ተማሪዎች ግንቦት ፯ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም የሕክምና አገልግሎት ሰጠ፡፡

በሕክምና አገልግሎቱም በአዳማ ማእከል፣ በደብረ ዘይት ወረዳ ማእከልና በአዱላላ ግንኙነት ጣቢያ የሚገኙ ስፔሻሊስት ሐኪሞች፣ ሜዲካል ዶክተሮች፣ የጤና መኮንኖች፣ የላቦራቶሪ ቴክኒሻኖች እና የአዳማ ሆስፒታል ሜዲካል ኮሌጅ ግቢ ጉባኤ የሕክምና ተማሪዎች በአጠቃላይ ፴፰ የሕክምና ባለሞያዎች ተሳትፈዋል፡፡

በሕክምና አገልግሎቱም ለገዳሙ መነኮሳት እና አብነት ተማሪዎች ሙሉ የጤና ምርመራና የመድኃኒት ድጋፍም ተደርጓል፡፡ ለአባቶች መነኮሳትና ለእናቶች መነኮሳይያት የስኳር፣ የደም ግፊት እና የዓይን ምርመራ ተደርጎላቸዋል፡፡ የመድኃኒት አቅርቦቱም ከዋናው ማእከል ቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል እና ከአንድ በጎ አድራጊ ወንድም የተገኘ ነው፡፡ የአዳማ ኢዮር ክሊኒክ የመድኃኒትና የሕክምና መመርመሪያ መሣሪያ ከማቅረቡ ባሻገር የክሊኒኩ ስፔሻሊስት ሐኪሞችም ከፍተኛ አገልግሎት ፈጽመዋል፡፡

በዕለቱ ሕክምና የተደረገላቸው አባቶች መነኮሳት፣ እናቶች መነኮሳይያትና የአብነት ተማሪዎች ከ፪፻፶ የሚበልጡ ሲኾን፣ ከሕክምናው በተጨማሪ ለአብነት ተማሪዎች የግልና የአካባቢን ጤና አጠባበቅ የተመለከተ ሥልጠና በጤና ባለሞያዎች ተሰጥቷቸዋል፡፡ ከዚህ ጋር ተያይዞ በአዳማ ማእከል የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ለአብነት ተማሪዎች የተዘጋጀው አልባሳት፣ የገላና የልብስ ሳሙና በገዳሙ በኩል ለአብነት ተማሪዎቹ እንዲከፋፈል ተደርጓል፡፡

የገዳሙ አባቶች፣ እናቶች መነኮሳትና እና የአብነት ተማሪዎቹ በተደረገላቸው የሕክምና፣ የአልባሳት እና የጤና መጠበቂያ ድጋፍ እጅግ መደሰታቸውን ገልጸው ማኅበረ ቅዱሳን በገዳማት ላይ እየሠራ ያለው አገልግሎት የሚያስመሰግነው መኾኑንና ይህንንም ሁልጊዜ ሲያስታውሱት እንደሚኖሩ በመጥቀስ ማኅበሩ በገዳማት ላይ የሚያደርገውን አገልግሎት አጠናክሮ እንዲቀጥል በማሳሰብ ማኅበሩን ያስፋልን ይጠብቅልን በማለት መርቀው የሕክምና ቡድኑን በቡራኬና በጸሎት አሰናብተዋል፡፡

አምስተኛው ዐውደ ርእይ በሰላም ተጠናቀቀ፡፡

ግንቦት ፳፫ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ማኅበረ ቅዱሳን የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተክርቲያንን አስተምህሮዋን እንጠንቅቅ፤ ድርሻችንን እንወቅ በሚል መሪ ቃል ከግንቦት ፲፯-፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ለስድስት ቀናት በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ያዘጋጀው አምስተኛው ዐውደ ርእይ ግንቦት ፳፪ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም ከምሽቱ 4፡00 በሰላም ተጠናቀቀ፡፡

ዐውደ ርእዩ ከተጀመረበት ዕለት እስከ ተጠናቀቀበት ሰዓት ድረስ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በብዙ ሺሕ ምእመናን፣ በመንግሥት ባለ ሥልጣናትና በሌሎች ቤተ እምነት ተከታዮችም ተጎብኝቷል፡፡

በዐውደ ርእዩ ከተሳተፉ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊና የሰቲት ሑመራ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ይህ ዛሬ ያየነው በማኅበረ ቅዱሳን የተዘጋጀ ትልቅና አስደናቂ ዐውደ ርእይ ነባሩን ኢትዮጵያዊ ሥርዓት፣ ቅርስ፣ ታሪክና ትውፊት የሚገልጽ ዐውደ ርእይ ነው፤ በመኾኑም በጣም የሚወደድ፣ የሚከበርና የሚደነቅ ነው ብለዋል፡፡ አክለውም ይህንን ነባር ሥርዓት ለማጥፋት የሚጥሩ ብዙ ሐሳውያንን ስላሉ ኹላችንም ከመንበረ ፓትርያርክ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ጠንክረን መሥራት ይኖርብናል፤ ዐውደ ርእዩም እስከ ወረዳ ድረስ መታየት ይገባዋል ካሉ በኋላ በርቱ፤ ጠንክሩ፡፡ ኹሉም ነገር ለሰላም፣ ድህነትን ለማጥፋት፣ አንድነትን ለማጽናት፣ በአጠቃላይ ድንቁርናን ለማስወገድ መኾን ይኖርበታል በማለት አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋና የደቡብ ኦሞ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስና የሲኖዶስ አባል ደግሞ ይህንን የመሰለ ያማረ ጉባኤ ሳይ በጆሯችን የሰማነውን በዓይኖቻችንም ያየነውን እንመሰክራለን ተብሎ እንደተጻፈ የሰማሁትንና ያየሁትን መመስከር ግድ ይለኛል፡፡ ልጆቻችንን በዚህ ደረጃ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ያበቋቸው ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ናቸው፡፡ ብፁዕነታቸው እኔ ለኩሸዋለሁ፤ እናንተ አንድዱት የሚል ቃል ተናግረው ነበር፡፡ በእውነትም እርሳቸው የለኮሱት መንፈሳዊ ሕይወት፣ መንፈሳዊ አገልግሎት ነዷል፡፡ ከኢትዮጵያም ተርፎ በመላው ዓለም ተዳርሷልና ይህንን በማየታችን እጅግ በጣም ደስ ብሎናል ሲሉ የተሰማቸውን ደስታ ገልጸዋል፡፡ በተጨማሪም እግዚአብሔር የሚቋረጥ ሥራ አይወድምና በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የአባቶቻቸውን አደራ እንደ ጠበቁ ልጆች ማኅበረ ቅዱሳንም የአባታችሁን የብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስን አደራ በመጠበቅ አገልግሎታችሁን ልትቀጥሉ፤ ፈተናዎችንም በመወያየትና በመነጋገር ልታልፏቸው ይገባል የሚል አባታዊ ምክር ለግሰዋል፡፡

በሰሜን አሜሪካ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል የኾኑት ብፁዕ አቡነ ፋኑኤልም የዚህ ታላቅ ማዕድ ተካፋይ በመኾኔ እጅግ በጣም ደስ ብሎኛል፡፡ በእናንተ በልጆቻችንም መንፈሳዊ ኩራት ይሰማናል፡፡ ልበ አምላክ ዳዊት በአባቶች ፈንታ ልጆች ተወለዱልሽ እንዳለው ኹሉ ተዋሕዶ እምነታችን እንደዚህ ለሃይማኖታችሁ የምትቆረቆሩ የምታስቡ ልጆች በማግኘቷና እኛም እንደዚህ ዓይነት ትውልድ ባለበት ሰዓት በመነሣታችን እጅግ ደስ ይለናል ሲሉ ስሜታቸውን ከገለጹ በኋላ ማኅበሩ የሠራው ሥራ የሚያስመሰግነው ቢኾንም በቅዱስ ወንጌል እንደ ተጻፈው እኛ ለጌታ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን ማለት እንደሚገባውም ተናግረዋል፡፡ አያይዘውም ይህ ሥራ የመጨረሻችሁ ሳይኾን የመጀመሪያችሁ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ከእናንተ ጋር ናቸው፡፡ ከአባቶቻችሁ መመሪያ እየተቀበላችሁ ከዚህ የበለጠ እንድታገለግሉ አደራ እላለሁ የሚል አባታዊ ምክር ሰጥተዋል፡፡

ሌሎች ብፁዓን አበውም ማኅበረ ቅዱሳንን አስነሥቶ ሕዝበ ክርስቲያኑን በዚህ መልኩ እንዲሰባሰብና ስለ ቤተ ክርስቲያኑ፣ ስለ ሃይማኖቱ እንዲማር በማድረጉ እግዚአብሔርን አመስግነዋል፤ በማኅበሩ ሥራ መደሰታቸውንም ገልጸዋል፡፡ ለወደፊትም ከአባቶች ጋር በመመካከር ከዚህ የበለጠ መትጋት እንደሚገባ አባታዊ ምክራቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አንዳንድ ያነጋገርናቸው ምእመናን እንደገለጹልን በዝግጅቱ ከመደሰታቸው የተነሣ ከቤተሰቦቻቸውና ከልጆቻቸው ጋር በመኾን ስድስቱን ቀን በሙሉ በዐውደ ርእዩ ተሳትፈዋል፡፡ በዐውደ ርእዩ መሳተፍ የሚኖረውን ጠቀሜታ አስመልክቶ ቃለ መጠይቅ ያደርግንላቸው ምእመናንም ዐውደ ርእዩ ኹሉም ምእመን ስለ ሃይማኖቱ፣ ስለ ቤተ ክርስቲያኑና ስለ አገሩ ታሪክ እውቀት እንዲኖረው ከማድረጉ በተጨማሪ ራሱን እንዲያይና ድርሻውን በማወቅ የሚጠበቅበትን ሓላፊነት እንዲወጣ የሚያስችል ግንዛቤ ያስጨብጠዋል ብለዋል፡፡

ከአስተያየት መስጫ መዛግብት ላይ ከሰፈሩ ዐሳቦች ውስጥም ዐውደ ርእዩ በጣም አስተማሪ መኾኑን ገልጸው፣ የአዘጋጆቹን፣ የአስተናጋጆቹንና የገላጮቹን ጥንካሬ በማድነቅ እንደዚህ ዓይነቱ ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይኾን፣ በየክፍለ ሀገሩና በየወረዳው መዘጋጀት እንደሚገባው፤ ትዕይንቶቹም ቀለል ባለ መልኩ በብሮሸርና በሲዲ መልክ ለምእመናን መዳረስ እንደሚኖርባቸው አስተያየት የሰጡ ሰዎችን ዐሳብ በአብዛኛው አንብበናል፡፡ በተጨማሪም ማኅበሩ በዐውደ ርእዩ ላይ የበጎ አድራጎት ማኅበራት ሥራዎች እንዲተዋወቁ ማድረጉ ያስመሰግነዋል፤ ለወደፊቱ እንደዚህ ዓይነት ዐውደ ርእይ ሲያዘጋጅ ከቤተ ክህነትና ከሰንበት ትምህርት ቤቶች ጋር በጋራ ቢሠራ ደግሞ የበለጠ ውጤታማ ይኾናል የሚሉና ሌሎችም አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡

በአንጻሩ የዐውደ ርእዩ ጊዜ ጠባብ መኾኑ፣ ማኅበሩ ኤግዚብሽን ማዕከሉ ውስጥ ለታዳሚዎች የሚኾን ምግብ ቤት ስላልተዘጋጀ፣ እንደዚሁም በትዕይንቶቹ አዳራሾች ውስጥ ጎብኝዎቹ ስለሚደራረቡና የልዩ ልዩ ትዕይንቶች ገላጮች ድምፅ ስለሚቀላቀል ለወደፊቱ ሰፊ ዝግጅት ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡ ከዚህ በተለየ ደግሞ ማኅበሩ ራሱን የሚያስተዋውቅበት የትዕይንት ክፍል ማዘጋጀት ነበረበት የሚል አስተያየት በጽሑፍም በቃልም ተነሥቷል፡፡

ከውጪ አገር ከመጡ ጎብኝዎች መካከል ማርቆስ ሀይዲኛክና ባለቤቱ አገራቸው ቡልጋርያ በሃይማኖታቸውም የምሥራቅ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባል መኾናቸውን ጠቅሰው በዚህ ዐውደ ርእይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክና ሥነ ጽሑፋዊ ጥበብ፣ የክርስቲያኖቹን ትጋትና መንፈሳዊ ሕይወት እንደዚሁም የአገሪቱን ሕዝብ ባህል እንደተረዱበት ለዝግጅት ክፍላችን ገልጸዋል፡፡

ከሌላ ቤተ እምነት ከመጡ ግለሰቦች መካከልም ማርሺያ ሲንግልተን የምትባል አንዲት አሜሪካዊት የፕሮቴስታንቲዝም እምነት ተከታይ በዚህ ዐውደ ርእይ በመሳተፏ እድለኛ መኾኗን ጠቅሳ በጉብኝቱም የኢትዮጵያ ኦርቶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በታሪክ የበለጸገና በመጽሐፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮ ላይ የተመሠረተ መኾኑን ከገለጸች በኋላ ዐዲስ እውቀት እንዳገኝ ስላደረጋችኹኝ አመሰግናለሁ የሚል አስተያየቷን በእንግሊዝኛ ቋንቋ አስፍራለች፡፡

በተያያዘ ዜና አንድ ጣልያናዊ ጎልማሳ የእስልምና ሃይማኖት ተከታይ በዐውደ ርእዩ የኢትየጵያን ታሪክና የክርስትናን አስተምህሮ እንደተረዳበትና በመታደሙም ደስተኛ እንደኾነ ገልጾ፣ ዐውደ ርእዩ በርካታ ምሁራን የተሳተፉበት መኾኑን ከትዕይንቶቹ ይዘት መረዳቱን ከተናገረ በኋላ ማኅበሩንና አዘጋጆቹን አመስግኗል፡፡

በመጨረሻም በትናንትናው ዕለት ከምሽቱ 4፡00 ዐውደ ርእዩ ሲጠናቀቅ የማኅበሩ ሥራ አስፈጻሚዎች፣ የዝግጅቱ አስተባባሪዎች፣ የትዕይንት ገላጮች፣ የአብነት ተማሪዎችና ሌሎችም ድጋፍ ሰጪ አካላት በኤግዚብሽን ማዕከሉ ግቢ ውስጥ ተሰባስበው ንሴብሖ ለእግዚአብሔር ስቡሐ ዘተሰብሐ እያሉ በሰላም ያስፈጸማቸውን ልዑል አግዚአብሔርን በዝማሬና በዕልልታ አመስግነዋል፡፡

አምስተኛው የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል

ግንቦት ፳፩ ቀን ፳፻፰ ዓ.ም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ከፍ ብሎ የሚሰማው የመዝሙር ድምፅና በማዕከሉ መግቢያ በር ላይ የተለጠፉ መንፈሳውያን ማስታወቂያዎች አካባቢው አንዳች ብርቱ ጉዳይ እንዳለበት ይመሰክራሉ፡፡ ብዙ የቆሙ መኪኖች፣ በሺሕ የሚቈጠሩ ምእመናን መንገዱን አጨናንቀውታል፡፡

ከዐዲስ አበባ ከተማ ብቻ ሳይሆን ከልዩ ልዩ የኢትዮጵያ ክፍላተ አህጉር የሚመጡ ምእመናንና ምእመናት ከግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ እግሮቻቸውን ወደ አንድ አቅጣጫ አድርገዋል፤ ወደ ዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል፡፡ የጉዟቸው ምክንያት ደግሞ የማኅበረ ቅዱሳን አምስተኛው ዙር መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን ዐውደ ርእይ ለማዘጋጀት ከዓመታት በፊት ዓቅዶ ሠርቷል፤ ዐውደ ርእዩ ለምእመናን ሊቀርብ የነበረውም ከመጋቢት 15-21 ቀን 2008 ዓ.ም የነበረ ቢኾንም ዳሩ ግን በሰዓቱ የእግዚአብሔር ፈቃዱ ባይኾን ግልጽ ባልነበረ ምክንያት ዐውደ ርእዩ መታገዱ ሲሰማ ብዙ ምእመናን ተደናገጡ፡፡

የማኅበሩ ሥራ አመራር አባላትም፡- አይዟችሁ አትደንግጡ፤ ኹሉም በጊዜው ይኾናል፡፡ እግዚአብሔር በፈቀደበት ጊዜ ዐውደ ርእዩን እናሳያችኋለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን በትዕግሥት ኾነን እንጠባበቅ፤ ወዘተ እያሉ ዐውደ ርእዩን በጉጉት ሲጠባበቁ የነበሩትን ምእመናን እያጽናኑ ከሚመለከታው አካላት ጋር ውይታቸውን ቀጠሉ፡፡

እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት ጊዜ ሲደርስ በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት፣ በአባቶችና በእናቶች ጸሎት የማኅበሩና የተባባሪዎቹ ጥረት ተሳክቶ ዐውደ ርእዩ የሚታይበት ቀን ደርሶ እነሆ ከግንቦት 17 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል ለተመልካቾቹ ይፋ ኾነ፡፡

መስቀል ዐደባባይን በማቋረጥ ከሰሜን ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ከፍ ብሎ ወደሚገኘው ቅፅር ግቢ ውስጥ ሲገሰግሱ የኢትዮጵያውያንን ባህል ገላጭ የኾነውንና ጠቢባኑ የተካኑበትን በረጅሙ ቆሞ ከርቀት የሚታየውን በኅብረ ቀለማት ያጌጠውን መሶብ ያገኛሉ፡፡

ይህንን መሶብ አለፍ እንዳሉ በግዙፉ መግቢያ በር ላይ አምስተኛው ዙር የማኅበረ ቅዱሳን ዐውደ ርእይ በዐዲስ አበባ ኤግዚብሽን ማዕከል፣ ከግንቦት 17-22 ቀን 2008 ዓ.ም የሚሉ ማስታዎቂያዎች በረጅም ብራና ቁልቁልና አግድም ተለጥፈው ይነበባሉ፡፡

ከታች ደግሞ የጸጥታ ባለሙያዎች ተመልካቾችን በጥንቃቄ እየፈተሹ ወደ ኤግዚብሽን ማዕከሉ ቅፅር እንዲገቡ ያደርጋሉ፡፡ የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎችም በሩ ውስጥ የተመደቡትን የቲኬት ሽያጭ አስተባባሪዎች ፈቃድ ካገኙ በኋላ ወደ አዳራሾቹ ጥቂት እንደተጓዙ ከአስፋልቱ በስተቀኝ በኩል ተንጣሎ የሚታየውን ቍጥር አንድ አዳራሽን ያገኛሉ፡፡ ይህ አዳራሽ በቍጥር የመጀመሪያው ይሁን እንጂ በዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ግን የመጨረሻው ነው፡፡

በአስተባባሪዎች መሪነት ወደ ሰሜን ምዕራብ አቅጣጫ ጥቂት ተጉዘው ጊዜያዊ የእንግዶች ማረፊያ ድንኳን ውስጥ ቁጭ ብለው በድምፅና በምስል የታገዙ ልዩ ልዩ መንፈሳውያን መረጃዎችን ሲከታተሉ ከቆዩ በኋላ በተራ ቅደም ተከተላቸው መሠረት ወደ ትዕይንቱ አዳራሾች ያመራሉ፡፡

የኤግዚብሽን ማዕከሉ በስተሰሜን በኩልም ተጨማሪ የመግቢያ በር ያለው ሲኾን፣ እንደዋናው በር ኹሉ የመግቢያ ቅድመ ኹኔታዎችን ካሟሉ በኋላ ወደ ደቡብ አቅጣጫ ሲያመሩ በዋናው በር ከገቡ ታዳሚዎች ጋር በአንድ ድንኳን ውስጥ አብረው እንዲቆዩ ይደረጉና ወደ ትዕይንቶች ይገሰግሳሉ፡፡

ይህ መንፈሳዊ ዐውደ ርእይ በአባቶች ጸሎት ከተከፈተበት ዕለት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በርካታ ምእመናን እየተመለከቱት ሲኾን፣ የምእመናኑ ቍጥርም ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ ነው፡፡

የዐውደ ርእዩ አዘጋጆችና አስተባባሪዎቹ ምእመናኑ ረጅም ሰዓት በመቆም እንዳይጉላሉ በማሰብ የሚቻላቸውን ኹሉ ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ስለዚህም ከኤግዚብሽን ማዕከሉ አዳራሾች በተጨማሪ ሰፋፊ ድንኳኖችን በማዘጋጀት ተጨማሪ መመልከቻ ቦታዎችን አመቻችተዋል፡፡

ትዕይንታተ ዐውደ ርእይ

ዐውደ ርእዩ በሦስት መንገድ ይጎበኛል፤ ይኸውም በገላጮች ማብራሪያ፣ በባነሮች (ብራናዎች) ላይ በተቀመጡ ጽሑፎችና መረጃዎች እንደዚሁም በድምፅ ወምስል በመታገዝ ነው፡፡ የዐውደ ርእዩ ዐበይት አርእስትም አራት ሲኾኑ እነዚህም፡-

የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት፤ ሁለተኛው የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ፤ ሦስተኛው የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ፤ አራተኛው ደግሞ ምን እናድርግ የሚሉ ናቸው፡፡ የእያንዳንዳቸውን ጭብጥ ለማስገንዘብ ያህል የአርእስቱን ዐሳብ በአጭሩ እንመልከት፤

ትዕይንት አንድ፡- የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነት

ይህ ትዕይንት ሀልዎተ እግዚአብሔር፣ ነገረ ድኅነት፣ ነገረ ማርያም፣ ነገረ ቅዱሳን እና ነገረ ቤተ ክርስቲያን የተካተቱበት ክፍል ነው፡፡ ሀልዎተ እግዚአብሔር በሚለው ርእስ እግዚአብሔር አምላክ በጊዜና በቦታ የማይወሰን፣ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፣ የፍጥረታት ኹሉ አስገኝ፣ ከመሥፈርትና ከአመለካከት ውጪ፣ እርሱ በገለጠው መጠን ብቻ የሚታወቅ እንጂ ባሕርዩ ተመርምሮ ሊደረስበት እንደማይቻል እንደዚሁም መልዕልተ ኵሉ (የኹሉ የበላይ) ኾኖ ሳለ በፈቃዱ የትሕትና ሥራ መሥራቱን ያስረዳል፡፡

ነገረ ድኅነት ደግሞ በአዳምና በሔዋን ምክንያት የዘለዓለም ሞት ተፈርዶበት የነበረው የሰው ልጅ ከሦስቱ አካላት አንዱ በኾነው በጌታችን በመድኀኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማተ መስቀልና ሞት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ መቻሉን፤ ንደዚሁም እምነት፣ ምግባር እና ምሥጢራተ በቤተ ክርስቲያንን መፈጸም የሰው ልጅ ለመዳን የሚያስፈልጉት ነገሮች መኾናቸው በዚህ ርእስ ሥር ተካቷል፡፡

ትዕይንት ሁለት፡- የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልዕኮ

በዚህ ትዕይንት የሐዋርያነትና የሐዋርያዊ አገልግሎት ትርጕም፣ ዓላማና አመሠራረትን ጨምሮ ስብከተ ወንጌል አንዴት እንደተስፋፋና እስከ ዛሬ ድረስ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሱ ፈተናዎችን እንደዚሁም መልካም አጋጣሚዎችን በማካከተት ልዩ ልዩ መረጃዎችና ትምህርቶቸ ቀርበውበታል፡፡

ትዕይንት ሦስት፡- የቤተ ክርስቲያን ተጋድሎ

ይህ ትዕይንት ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳለፈችውን ተጋድሎ፣ የመናፍቃንን ተፅዕኖና የሰማዕታትን ታሪክ፣ የተዋሕዶ ሃይማኖትን አስተምህሮ ለማስጠበቅ የተደረጉ ልዩ ልዩ ዓለም ዓቀፍና አገር ዓቀፍ ጉባኤያትን በዝርዝር ይዟል፡፡

ትዕይንት አራት፡- ምን እናድርግ?

ይህ ትዕይንት ደግሞ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ከተመለከቷቸውና ከሰሟቸው እውነታዎች በመነሣት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ከመጠበቅና ድርሻን ከማወቅ አኳያ ልዩ ልዩ ችግሮችን ለመቅረፍ ወደፊት ምን ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው የሚያስረዱ መረጃዎችን አካቷል፡፡

ዐውደ ርእዩ ከነዚህ ዐበይት ትዕይንቶች በተጨማሪ የሕፃናት ትዕይንትም የተካተተበት ሲኾን፣ በዚህ ትዕይንት ለሕፃናት አእምሮ የሚመጥኑ መንፈሳውያን ትምህርቶች ተዘጋጅተውበታል፡፡ ሕፃናቱም ክፍሉ ውስጥ እየዘመሩ ይማራሉ፤ ይደሰታሉ፡፡

ከሁሉም በተለየ መንገድ ደግም የሁሉም ገባኤያት (የንባብ፣ የዜማ/የድጓ፣ የቅዳሴ፣ የቅኔ፣ የአቋቋም፣ የመጻሕፍትና የአቡሻሕር ጉባኤ ቤቶች) ሊቃውንት (መምህራን) ደቀ መዛሙርታቸውን ሲያስተምሩ እስከ ጎጆዎቻቸውና እስከሚጠቀሙባቸው ዕቃዎች ድረስ በተግባር ይታያሉ፡፡ የብራና መጻሕፍት አዘገጃጀትም በባለሙያ አባቶች ይብራራል፡፡

የማኅበረ ቀዱሳንን ልዩ ልዩ ክፍሎች፣ እንደዚሁም የጽርሐ ጽዮንና የደጆችሽ አይዘጉ መንፈሳውያን ማኅበራት አገልግሎት የሚቃኝባቸው ክፍሎችም የትዕይንቱ አካላት ናቸው፡፡ በማኅበሩ የሚዘጋጁ ንዋያተ ቅድሳትና መጻሕፍትም በሽያጭና በዕጣ መልክ ቀርበዋል፡፡

ማኅበረ ጽዮን የጉዞ ማኅበር፣ መቄዶንያ የአረጋውያንና የአእምሮ ሕሙማን መርጃ ማዕከል፣ ዮድ አቢሲንያ አስጎብኚና የጉዞ ወኪል ስለሚሰጧቸው ተግባራት የሚገልጹባቸው ክፍሎችም ተካተዋል፡፡

ትዕይንቶቹን ተመልክተው የሚወጡ ምእመናንም ኾኑ የሌሎች እምነት ተከታዮች ለሚያነሷቸው ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን መውጫው በር ላይ ተሠይመዋል፡፡

የዐውደ ርእዩ ታዳሚዎች ጉብኝቱን ጨርሰው ሲወጡ ደግሞ የተሰማቸውን ስሜት ወይም ደግሞ ቅሬታ የሚያሰፍሩባቸው የአስተያየት መስጫ መዛግብት በብዛት ተደርድረዋል፤ ጎብኝዎቹም ስሜታቸውን እየጻፉ ወደየመጡበት ይመለሳሉ፡፡

ከዐውደ ርእዩ ትዕይንቶች ጎን ለጎንም ከግንቦት 17 ቀን 2008 ጀምሮ የአብነት ትምህርቶችን የተመለከቱ ጥናቶችና መንፈሳውያን ተውኔቶች እንደዚሁም መዝሙራት ከቀኑ 11፡00 እስከ ምሽት ድረስ ለጎብኝዎቹ በመቅረብ ላይ ይገኛሉ፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለአምስተኛ ጊዜ ያዘጋጀው ይህ ዐውደ ርእይ መታየት ከጀመረ እነሆ ዛሬ አምስተኛውን ቀን ያስቈጠረ ሲኾን፣ እጅግ በሚማርክ ኹኔታ በአባቶች ካህናትና በምእመናን ብቻ ሳይኾን በሌሎች ሰዎችም እየተጎበኘ ይገኛል፡፡

ትናንትናና ዛሬም በርካታ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በዐውደ ርእዩ ተገኝተው አባታዊ ቡራኬ ሰጥተዋል፤ ማኅበሩ እየሠራ ያለውን ተግባር በማድነቅም ስሜታቸውን መዝገብ ላይ አስፍረዋል፡፡

ለዐውደ ርእዩ ድምቀት ከሰጡ ክሥተቶች መካከልም የሰንበት ት/ቤት ዘማርያን የመዝሙር ልብስ ለብሰው እየዘመሩ፤ እንደዚሁም በዛሬው ዕለት (ግንቦት 21 ቀን 2008 ዓ.ም) ጋብቻቸውን የፈጸሙ ጥንዶች ከአጃቢዎቻቸው ጋር በመኾን በዐውደ ርእዩ መታደማቸው ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡

ዐውደ ርእዩ ከተከፈተበት ቀን ጀምሮ በአስተያየት መስጫ መዛግብቱ ላይ የሰፈሩትን አስተያየቶች ስናነብና ቃለ መጠይቅ ስናደርግ ብዙ ምእመናን በዐውደ ርእዩ ራሳቸውን እንዳዩበትና ስለሃይማኖታቸው በቂ ግንዛቤ እንዳስጨበጣቸው እንደዚሁም የድርሻቸውን ለመወጣት እንዳነሣሣቸው ተረድተናል፡፡

በተጨማሪም ዐውደ ርእዩ በዐዲስ አበባ ብቻ ሳይኾን በየአገሩ ቢታይ፣ ትዕይንቶቹ በብሮሸርና በሲዲ መልክ ቢሠራጩ፣ ከጠቅላይ ቤተ ክህነትና ከሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ጋር በጋራ በመኾን ማቅረብ ቢቻል መልካም ነው የሚሉና የመሳሰሉ አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡

በአንጻሩ በትዕይንቶቹ ገላጮችና በምስል ወድምፅ ዝግጅቶች መካከል የድምፅ መጋጨት እንዳይኖር ጥንቃቄ ቢደረግ፤ ግቢው ውስጥ በማኅበሩ የተዘጋጁ ምግቦችና መጠጦች ለሽያጭ ቢቀርቡ፤ ትዕይንቶቹ ሰፊ ጊዜ ተሰጥቷቸው በስፋት ቢተነተኑ፤ አዳራሾቹ ውስጥ ረጅም ሰዓት መቆየት ባይኖር፤ ወዘተ የመሰሉ በርካታ አስተያየቶችንም ከአንዳንድ ጎብኝዎች ለመረዳት ችለናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡