የነፋስ ነገር
እግዚአብሔር ያለ ምክንያት የፈጠረው ፍጥረት የለምና ነፋስንም በምክንያት ፈጥሮታል፡፡ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት በመዝሙሩ “ሰማያት የእግዚአብሔርን ክብር ይናገራሉ፤ የሰማይም ጠፈር የእጁን ሥራ ያወራል፡፡ ቀን ለቀን ነገርን ታወጣለች፤ ሌሊትም ለሌሊት እውቀትን ትናገራለች” በማለት እንደዘመረው ሥነ ፍጥረት አእምሮ ላለው የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን ባሕርያዊ መገለጫዎች ሥራና ፈቃዳት ያስተምራሉ፡፡ (መዝ.፲፰፥፩) ሰውንም ሲፈጥረው ከዐራቱ ባሕርያተ ሥጋ አምስተኛ ባሕርየ ነፍስን አድርጎ በመልኩና በምሳሌው እንደፈጠረው የታወቀ ነው፡፡ (ዘፍ. ፩፥፳፮) እነዚህ አራቱ ባሕርያተ ሥጋ የሚባሉትም ነፋስ፣ እሳት፣ መሬትና ውኃ ናቸው፡፡ በሥነ ፍጥረት ትምህርት እግዚአብሔር ሰውን ከእነዚህ ዐራት ባሕርያት የፈጠረበት ምክንያት በምልዓትና በስፋት ይተነተናል፡፡ በዚህ አጠር ያለ ጽሑፋችንም ከነፋስ ምን እንማራለን? የሚለውን እናነሣለን፡፡