“እንስሳትን ጠይቅ ያስተምሩህማል፤ የሰማይ ወፎችን ጠይቅ ይነግሩህማል” (ኢዮብ ፲፪፥፯)
በጻድቁ ኢዮብ መጽሐፍ የተጻፈ ኃይለ ቃል ነው፡፡ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በዕለተ ሐሙስ “ውኃ ሕያው ነፍስ ያላቸውን ተንቀሳቃሾች ታስገኝ” በማለት ቃል በተናገረ ጊዜ በልባቸው የሚሳቡ፣ በእግራቸው የሚሽከረከሩ፣ በክንፋቸው የሚበሩ ፍጥረታት ከባሕር ተገኙ፡፡ (ዘፍ.፩፥፳)
በባሕር ከተፈጠሩ ከነዚህ ፍጥረታት የሚበሉና የሚገዙ፣ የማይበሉ የማይገዙም አሉ፡፡ ከባሕር ጸንተው የሚኖሩ አሉ፤ አንድ ጊዜ በየብስ አንድ ጊዜ በባሕር የሚኖሩ አሉ፤ በክንፋቸው በረው ከባሕር ወጥተው የቀሩም አሉ፡፡ (መጽሐፈ ሥነፍጥረት ምስለ አምስቱ አእማደ ምሥጢር፤ ገጽ ፷፤ ሥነ ፍጥረት ክፍል ሦስት ለከፍተኛ የመንፈሳዊ ትምህርት ተማሪዎች የተዘጋጀ ገጽ ፵)