‹‹በእንተ አቡነ አቢብ!››

ጥቅምት ፳፬፤፳፻፲  ዓመተ ምሕረት

በዐሥራ ሦስተኛው ክፍለ ዘመን በሮሜ ሀገር የተወለዱት ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብ የስማቸው ትርጓሜ “የብዙኀን አባት” አንድም ቡላ ማለት “የተወደደ፣ እግዚአብሔር የተለየ” ነው፡፡ መጽሐፈ ስንክሳር ታላቅና ክቡር የሆነ አቢብ የተባለ መስተጋድል አባ ቡላ ተብሎም የሚታወቅ አባት በከበረች ዕለት ጥቅምት ሃያ አምስት (፳፭) እንዳረፈ ይጠቅሳል፡፡

አስቀድሞም ከሃዲው ንጉሥ መክስምያኖስ ክርስቲያኖች ላይ ባመጣባቸው ስደት ምክንያት አባትና እናታቸው አብርሃምና ሐሪክ ተሰደው ሲኖሩ ልጅን ባማጣታቸው በጸሎትና በጾም አምላካቸው እግዚአብሔርን በመለመናቸው መልአክ ለአብርሃም ተገልጾ “ይህ ፍሬ የአንተ ነው፤ እርሱም ወደ እኔ የሚቀርብ እግዚአብሔርን የሚያስደስት ፈቃዱንም የሚፈጽም የአመረ መባዕ ነው” በማለት እግጅ መልካም ፍሬን ሰጠው፡፡ ደጉ ሰው አብርሃምም ከእንቅልፉ ነቅቶ ለሚስቱ በሕልሙ ያየውንና መልአኩ የነገረውን ሁሉ ነገራት፡፡ እርሷም ደስ ተሰኘች፤ ሁለቱም በአንድነት እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡ የአብርሃም ሚስት ሐሪክ በፀነሰች ጊዜም በቤታቸው አደባባይ ሁለንተናው መልካምና ታላቅ ዛፍ በቀለ፡፡ በቅጠሉም ላይ በዕብራይስጥ ቋንቋ የተጻፈ “በጽዮን አድሮ የሚኖር የያዕቆብ ፈጣሪ የእግዚአብሔር አገልጋይ ቡላ” የሚል ጽሕፈት አገኙ፡፡ በዚህም ጊዜ በተአምሩ ተደንቁ፡፡

ቀጥሎም መልኩ ያማረ ከብርሃናት ይልቅ ፊቱ የሚያበራ ወንድ ልጅን ወለደች፡፡ ከዚህም በኋላ ለአንድ ዓመት ያህል ክርስትናን ሳይስነሡ ሲያኖሩት እመቤታችን ድንግል ማርያም ለሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ለሰለባስትሮዮስ ተገልጣ ወደ አብርሃም ቤት በመሄድ ሕፃኑን እንዲያጠምቀው ስላዘዘችው የክርስትና ጥምቀትን አጠመቀው፡፡  ስሙንም “ቡላ” ብላ ሰየመው፤ ወላቹም በዚህን ጊዜ አደነቁ፡፡ ጸሎትም አድርጎ የቊርባን ኅብስትና ወይን የተመላ ጽዋ ከሰማይ ስለወረደ ቀድሶ ቅዱስ ሥጋውንና ደሙን ሕፃኑንና ወላጆቹን አቀበላቸው፡፡  በዚያንም ጊዜ ሕፃኑ የአንድ ዓመት ልጅ ሲሆን “በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከወልድ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ አብ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው፤ በባሕርይ በህልውና በመለኮት ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አንድ የሆነ ወልድ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው፤ በባሕርይ በህልውና በመለኮት በአብ ከወልድ ጋር አንድ የሆነ መንፈስ ቅዱስ በግብር በአካል በስም ልዩ ነው” ብሎ ተናገረ።

ጥቂት ዓመታት ካለፉም በኋላ በኅዳር ሰባት ቀን አባቱና እናቱ ዐረፉ፤ ሕፃን ቡላ ዐሥረኛው ዓመቱ ላይ ሌላ መከራ አጋጠመው፤ ሕዝቡን ለጣዖት መስገድ የሚያስገድድ መኮንን እንደመጣ በሰማ ጊዜም ሕፃኑ በፊቱ ቀርቦ የረከሱ ጣዖታትን ረገመ፡፡ በአካል ትንሽ መሆኑን የተመለከተው መኮንኑ ለጊዜው ቢያደንቅም በችንካር ቸንክረው፣ ሥጋውን ሰነጣጥቀው፣ ቆዳውንም ከአጥንቱ እንዲገፉት፣ እጁቹንና እግሮቹን በመጋዝ እንዲቀርጡ፣ በሶሾተልና በጦሮች አድርገው ከመንኮራኩር ውስጥ እንዲጨምሩት፣ ዳግመኛ በመንገድ ላይ እንዲጎትቱት አዘዘ፡፡ ሆኖም መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል መጥቶ ስላዳነው ያለ ጉዳት ጤነኛ ሆነ፡፡ ቅዱሱ ሕፃን ቡላ ግን ሌላ መኮንን ጋር ሄዶ የረከሱ ጣዖታትን ገረመ፡፡ በዚህም ጊዜ መኮንኑ ተቆጥቶ ሚያዝያ ወር በባተ በዐሥራ ስምንተኛው ቀን ራሱን በሰይፍ እንዲቆርጡ ስላዘዘ ቆረጡት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም ከሰማይ ወርዶ ከሞት አስነሣው፡፡ በዚህም ጊዜ የመነኮስ ልብስንና አስኬማን በመስቀል ምልክት አለበሰውና እንዲህ አለው፤ “ከቅዱሳንና ከጻድቃን አንድነት ትሆን ዘንድ እግዚአብሔር አዝዞአል፡፡”

ቅዱስ አባታችንም በዚህ ጊዜ ከደረቅ ተራራ ላይ ወጥተው በውስጧ እየታገደሉ ሲኖሩ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን መከራ መስቀል በማሰብ ከረጅም ዕንጨት ላይ በመውጣት ራሳቸውን ወደታች ሁል ጊዜ ይወረውሩ ነበር፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀንም በዛፍ ላይ ሲወረወሩ ሰይጣን በቅናት ተነሣስቶ ገደላቸው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አነሣቸውና “ከእንግዲህ ስምህ ቡላ አይሁን፤ አቢብ ይባል እንጂ፤ የብዙዎች አባት ትሆናለህና” አላቸው፡፡

ከዚህ ቀጥሎ አቡነ አቢብ የክርስቶስን ፍቅር በመጨመር ፊታቸውን ይጸፉ፣ ሥጋቸውን በጥቂት ይቆርጡ፣ ጀርባቸውን ሰባት ጊዜ ይገርፉ ነበር፡፡ ጌታችን በዚህ ጊዜም ከእርሳቸው ሳይለይ ይፈውሳቸው ነበር፡፡ በየእሑድም ቀን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም እንደተወለደ፣ በሌሎች ቀኖችም እንደተያዘና ከአይሁድ መከራ እንደ ተቀበለ ሁኖ ይገለጽላቸው ነበር። በዚህም የተነሣ ለአርባ ሁለት ዓመታት ምግብ ሳይበሉና ውኃ ሳይጠጡ ከኖሩ በኋላ  ለዐሥራ ሁለት ወር በራሳቸው ተተክለው ሲኖሩ ናላቸው ፈስሶ አለቀ፡፡

የጌታችንን መከራ በአሰቡ ጊዜ በአንዲት ቀን ሰይፉን በአንጻሩ ተክለው ከዕንጨት ላይ በመውጣት በላዩ ወድቀው ሞቱ፤ ቅድስት ድንግል እመቤታችን ማርያምም ከአእላፍ መላእክት ጋር መጥታ “የእኔና የልጄ ወዳጅ ሰላምታ ይድረስህ” አለችው። ከበድኑም ቃል ወጥቶ “የሰማይና የምድር ንግሥት እመቤቴ ሰላምታ ይገባሻል” አላት፡፡ እርሷም በከበሩ እጆቿ ዳሥሣ ከሞት አስነሣቸው።

ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብ ከዚህ ዓለም ድካም የሚያርፉበት ጊዜ ሲደርስ ክብር ይግባውና ጌታችን ክርስቶስ በእጁ ልዩ የሆኑ አክሊሎችን የሚያበሩ ልብሶችንም ይዞ ተገለጠለትና እንዲህ አላቸው፤ “ወዳጄ አቢብ ሆይ፥ በማያልቅ ተድላ ደስታ ደስ አሰኝህ ዘንድ ወደ እኔ ና፤ ስምህን ለሚጠራ መታሰቢያህን ለሚያደርግ እኔ ኃጢአቱን አስተሠርይለት ዘንደ በራሴ ማልኩልህ፤ ወይም ለተራቆተ የሚያለብሰውን፣ ለተራበም የሚያጠግበውን፣ ለተጠማ የሚያጠጣውን፣ የገድልህን መጽሐፍም የሚጽፈውን ወይም የሚያነበውንና የሚሰማውን፣ በጸሎትህም የሚታመኑትን ሁሉ እስከ ዐሥር ትውልድ እምራቸዋለሁ፤” ይህንም ብሎ አፋቸውን ሳማቸው፤ በደረቱም ላይ አድርጎ ወደ አየር አወጣቸው፤ የመላእክትንም ምስጋና በሰማች ጊዜ ነፍሳቸው ከሥጋቸው ተለየች፤ ወደ ሰማያዊት ኢየሩሳሌም ገባች።

እነሆ ሰማዕቱ አቡነ አቢብ ምእመናን በሚቀምሱት የዕለት ምግብ አማካኝነት በነፍስም በሥጋም እንዲድኑ አስገራሚ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደተቀበሉ የሚናገር የገድል ተአምራታቸው ይህ ነው፡- ብዙዎች ስማቸውን ጠርተው በሚቀምሱት ምግብ አማካኝነት ከተለያዩ በሽታዎች የተፈወሱ አሉ፡፡ ይህ ቃል ኪዳናቸው ለሁላችን ይደረግልን ዘንድ ከመመገባችን አስቀድሞ የእግዚአብሔርን ስም እንጥራ (አቡነ ዘበሰማያትን ማለቱ ነው፡፡) ከተመገብን በኋላም የዕለት ምግባችንን ስለሰጠን እግዚአብሔርን እናመስግን፡፡ ዘወትር ከተመገብን በኋላ ሦስት ጊዜ ‹‹ስለ ወዳጅህ ስለ አቡነ አቢብ›› እያልን ሦስት ጊዜ እንቅመስ፡፡ አስቀድሞ ጌታችን መድኃኒታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለአቡነ አቢብ ተገልጦላቸው ‹‹…ወዳጄ አቢብ ሆይ! የሰውን ልጅ ለማዳን የተቀበልኩትን ሕማማተ መስቀል እያሰብህ ይህንን ሁሉ ገድል ፈጽመሃልና ምን እንዳደርግልህ ትወዳለህ?›› አላቸው፡፡ ንዑድ ክቡር ቅዱስ አባታችን አቡነ አቢብም ‹‹ጌታዬ አምላኬ መድኃኒቴ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! መቼም ሰው ሁሉ ሳይመገብ አይውልም፤ አያድርምና በተመገበ ጊዜ ስሜን ጠርቶ የተማጸነውን ማርልኝ›› አሉት፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አባታችን አቡነ አቢብ ለሰው ልጆች ያላቸውን ፍቅር ካደነቀ በኋላ ‹‹…ከማዕድ በኋላ ስብሐት ተብሎ የተረፈውን በእንተ አቢብ ብሎ ሦስት ጊዜ የተመሰገበውን ሰው ሁሉ እምርልሃለሁ›› በማለት ታላቅ የምሕረት ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡

ያልተጠመቀ አረማዊ አሕዛብም እንኳን ቢሆኖ ‹‹ስለ አቡነ አቢብ›› ብሎ ከተማጸነ ጌታችን ያንን ሰው ወደ ቀናች የእምነት መንገድ ሳይመራወና በንስሓ ሳይጠራው በሞት እንደማይወስደው ለአባታችን ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ለማዳን ትንሽ ምክንያትን የሚፈልግ ያለ ምክንያትም የማያድን ልዑል እግዚአብሔር ስሙ እስከ ዘለዓለም ድረስ ይክበር ይመስገን! ሰው ተመግቦ እንኳን መዳን እንዲችል ይህን ድንቅ ቃል ኪዳን ለአባታችን ሰጥቷቸዋልና በየቀኑ በዚህ ቃል ኪዳን እንጠቀምበት፡፡ ተመግበን ከጨረስንና ስብሐት ካልን በኋላ ሦስት ጊዜ ‹‹በእንተ አቡነ አቢብ›› ብለን እንቅመስ፡፡ በጥቅምት ፳፭ ቀን በዓመታዊ የዕረፍት በዓላቸው ታስበው የሚውሉት ጻድቁና ሰማዕቱ አቡነ አቢብ የቃል ኪዳናቸው ረድኤት በረከት ይክፈሉን!

(ምንጭ፡ደብረ ሰላም ቃጭልቃ አቡነ አቢብ ገዳም ያሳተመው ገድለ አቡነ አቢብ፣ ገጽ ፻፭)

በእንተ ቅዱሳን ኀሩያን)

የሥራ አጥነት ተጽዕኖ

ጥቅምት ፳፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

“በሕይወት ዘመንህም ሁሉ በድካም ከእርሷ ትበላለህ” የሚለው አምላካዊ ቃል ሁላችንንም የሚመለከት ነው፡፡ (ዘፍ. ፫፥፲፯) ሰው በሠራው ኃጢአትና ጥፋት የተነሣ ከገነት ተባሮ ወደ ምድር ከመጣበት ጊዜ አንሥቶ እስካለንበት ጊዜ ድረስ የሥጋችንን በተለይም መሠረታዊ ፍላጎታችንን ሟሟላት የምንችለው ሥራ ሠርተን በምናገኘው ገንዘብና ቁሳዊ ነገሮች ነው፡፡

በዘመናት ሂደት ሰዎች በተለያዩ ችግሮችና መከራዎች ውስጥ ገብተው የሚዋዥቁበት ምክንያት አንድም በሥራ አጥነት ሳቢያ በሚያጋጥም የገንዘብ አቅም ማነስና ችግር በመሆኑ የምግብ አቅርቦት፣ የመጠለያ እጦትና የአልባሳት እጥረት ለረኃብ፣ ለመራቆት እንዲሁም ለተለያዩ በሽታዎች ባስ ሲል ደግሞ ለሞት ይዳርጋሉ፡፡

የሥራ አጥነት ችግር አስከፊነት ይህ ብቻ አይደለም፡፡ በደረስንበት በዚህ ወቅት በተለይም ወጣቶች ከዚህ ለባሳ ችግር ተጠቂ ሆነዋል፡፡ በዕውቀታቸው፣ በጉልበታቸው እንዲሁም በተሰጣቸው ተሰጥኦ ለፍተው፣ ጥረው፣ ግረው የመኖር ሐሳባቸው ከማንኛውም የዕድሜ ክልል የበለጠ በመሆኑ አእምሮአቸው ሥራ ሲፈታ ይረበሻል፤ ተስፋም ያጣሉ፤ ወደ ጭንቀትና የተለያዩ የሥነ ልቡና ቀውስ የሚገቡ ወጣቶች ቁጥርም ጥቂት አይባልም፡፡

በየዓመቱ ከተለያዩ የትምህርት ተቋማት በተለያዩ የትምህርት ዘርፍ ተመርቀው የወጡ ተማሪዎችም ሆነ በዘመናዊ ትምህርት ብዙ ሳይገፉ በአጋጣሚዎች ተጠቅመው በሙያቸው አልያም በጉልበታቸው ሠርተው ለመኖር የሚጥሩ ወጣቶች በልዩ ልዩ የሀገራችን ክፍሎች ይገኛሉ፡፡ ሆኖም ግን ሥራ አግኝቶ በቋሚነት አንድ ቦታ ላይ ገንዘብም፣ ዕውቀትም ሆነ ልምድ ማካበት ያልቻሉ በርካቶች ናቸው፡፡ ይህም እራሳቸው ላይ ብቻ ሳይሆን ቤተ ሰቦቻቸው እንዲሁም ማኅበረሰቡ ላይ የሚያመጣው ተጽዕኖ ከፍተኛ ነው፤ አብዛኞቻችን በእራሳችን፣ በዘመዶቻችንና በጎረቤቶቻችን ሕይወት የሰማነውና የተመለትነው ነገር ነው፡፡

በርካታ ወጣቶች የሱሰኝነት ተጠቂ የሆኑት በዚህ ምክንያት እንደሆነ ከገዛ አንደበታቸው ሰምተንም ሊሆን ይችላል፡፡ በተለይም ወጣት ወንዶች ለዚህ ችግር ተጋላጮች ናቸው፡፡ ሱሰኝነት የሚያመጣው የጤንነት እክል ብቻ እንዳልሆነ ደግሞ የጤና ባለሙያዎች አበክረው ይናገራሉ፡፡ እንደ እነርሱ ገለጻ ከሆነ ሱሰኞች ከቤተ ሰቦቻቸው ጋርም ሆነ ከማንኛውም የማኅበረሰብ አካል ጋር መልካም ግንኙነት አይኖራቸውም፡፡ የተዛበ ቀኖችን በማሳለፋቸው የተነሣ ከማንም ጋር የሰላም ግንኑነት ሊኖራቸው አይችልም፡፡ ቀኑ ለእነርሱ ሌሊት፣ ሌሊቱ ደግሞ ቀን የሚሆንባቸው ጊዜ ጥቂት አይደለም፡፡ ንግግራቸው በአብዛኛው ቀና ያልሆነና የተጣመመ እንዲሁም ስድብና አጸያፊ ቃል የተቀላቀለበት ሲሆን ከሰዎች ጋር የመጣላቱ ዕድል ሰፊ ይሆናል፡፡ የሚወዷቸውንና የሚቀርቧቸውን ሰዎች ሳይቀር ስለሚያስቀይሙ በብቸኝነት ዓለም ውስጥ ይገባሉ፡፡

ሱሰኛ የሚሆኑ ወጣቶች ዓለማዊ ሕይወትን የሚኖሩ ብቻ ሊመስለን ይችላል፡፡ ነገር ግን በስመ ኦርቶዶክስ የሚኖሩና በሥራ አጥነት እንዲሁም በሌሎች ተጓዳኝ ችግሮች ምክንያት ባክነው የቀሩ ብዙዎች እንዳሉ ማወቅ ይገባል፡፡

በዚህ ጊዜ ደግሞ የተጋፈጥነው ሌላ ትልቅ ችግር አለ፡፡ ከምዕራባውያን በኩል ወደ ሀገራችን የገባና የተስፋፋ ተብሎ የሚታመነው “የሰይጣን አማኞች ማኅበረሰብ” ወጣቶችን በገንዝብና ሌሎች ጥቅሞች በማጥመድ የጠላት መረብ ውስጥ እየከተቱ ይገኛሉ፡፡ በየአደባባይ እየተመለከትናቸው ያለነው የእምነቱ ተከታዮች ሳያውቁም ይሁን አውቀው ለሰይጣን እየተገዙ ነው፡፡ ድህነትን ሸሽተው፣ በቀላሉና በአጭር ጊዜ ችግራቸውን ፈትተው ገንዘብና ሀብት ለማካበት በሚደረግ ጥረት ነፍሳቸውን ካጡት ውስጥ ኦርቶዶክሳውያን እንዳሉበት ተአማኒ ምንጮች ይናገራሉ፡፡ ወጣቶቹ ታዲያ እያጡ ያሉትን መንፈሳዊነትም ሆነ እየገቡበት ያለውን አዘቅት በደንብ የተረዱ አይመስሉም፡፡ ብቻ የዕለት ጉርሰን ለሟሟላትና ከተቻለም በርከት ያለ ገንዘብ ለማግኘት ወደዚህ ዝቅተት ይገባሉ፡፡ በኋላ ግን ከገቡበት ለመውጣት ቢፈለግ እንኳን ቀላል እንዳልሆነ መገመት አያዳግትም፡፡

ኢትዮጵያ ሀገራችን እያስተናገደች ያለችው አስተዳደራዊ ለውጥና ማኅበረሰባዊ አኗኗር ያመጣው የኑሮ ውድነትም ለዚህ ችግር ተጋላጭ እንዲሆኑ ያደረገ ነው፡፡ ቢያንስ መሠረታዊ ነገሮች ሁሉም ሊኖረው ይገባልና በእራሱ ለፍቶ እንዲያገኝ የማድረግ ዕድል ተጠያቂው አካል ሊያመቻች ይገባል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ይህን እንደምትደግፍ አስቀድመን በጠቀስነው የአምላካችን ትእዛዝ ማረጋገጥ እንችላለን፡፡

    ይቆየን!

አቡነ አረጋዊ ዘደብረ ዳሞ

ጥቅምት ፲፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

በከበረች ጥቅምት ፲፬ ቀን አቡነ አረጋዊ ተሠወሩ፡፡ ሀገራችን ኢትዮጵያ የመጡት ቅዱስ አባታችን ዘጠኙ ቅዱሳን የእግዚአብሔር አገልጋዮችን ኢትዮጵያ እስኪደርሱ ድረስ በመንገድ የመሯቸው እርሳቸው እንደሆኑ መጽሐፈ ስንክሳር ይገልጻል፡፡

የዘንዶ ጅራት በመያዝ ከደብረ ዳሞ ተራራ ላይ የወጡት፣ በዚያም ፍጹም ገድላቸውን የፈጸሙት ቅዱስ አባታችን አቡነ አረጋዊ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የምሕረት ቃል ኪዳን ተቀብለዋል፡፡ ስማቸውን ለሚጠራና መታሰቢያቸውን ለሚያደርግ እንደሚማርላቸውም ተነግሯቸዋል፡፡

ከመምህራቸው ከአባ ዻኩሚስ በተማሩት መሠረትም ለልጆቻቸው መነኰሳት ሥርዓተ ማኅበርን ሠርተውላቸዋል፡፡ ከዚያም በእግዚአብሔር ቸርነት እንደ ነቢያቱ ሄኖክና ኤልያስ ከዚህ ምድር ተሠውረዋል፡፡

የቅዱስ አባታችን አቡነ አረጋዊ ጸሎት፣ አማላልጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!!!

ምንጭ፡- መጽሐፈ ስንክሳር ጥቅምት ፲፬

ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ

ጥቅምት ፲፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

የቊስጥንጥንያ ንጉሥ የቴዎዶስዮስ ልጅ የቅዱስ ገብረ ክርስቶስ የዕረፍቱ መታሰቢያ ነው ጥቅምት ፲፬ የከበረ በዓል ነው። ቴዎዶስዮስ የተባለው ንጉሥ እግዚአብሔርን የሚፈራ ነው፤ ሚስቱም በጎ የምትሠራ እግዚአብሔርንም የምትፈራ ናት፤ ስሟም መርኬዛ ነው። እነርሱም ልጅ ስለሌላቸው ያዝኑ ነበር፤ ወደ ኢየሩሳሌምም ሒደው ስእለትን ተሳሉ፤ ቸር መሐሪ ወደሆነ እግዚአብሔርም ለመኑ፤ እርሱም ልመናቸውን ተቀበሎ ይህን ያማረ ልጅ ሰጣቸው፤ ስሙንም አብደልመሲህ ብለው ሰየሙት፤ ትርጓሜውም ገብረ ክርስቶስ ማለት ነው። የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት ሁሉ የሥጋዊንም ትምህርት አስተማሩት።

አድጎ በጕለመሰም ጊዜ የሮሜውን ንጉሥ ልጅ አጭተው እንደ ሥርዓቱ አጋቡት ከሌሊቱ እኩሌታም በሆነ ጊዜ ሙሽራው ገብረ ክርስቶስ ተነሥቶ ወደሙሽራዪቱ ገባ፤ እጅዋንም ይዞ ከእርስዋ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ ። ከዚያም የሃይማኖት ጸሎት በአንድ አምላክ እናምናለን የሚለውን እስከ መጨረሻ ጸለየ፤ የተሞሸረበትንም ልብስ ከላዩ አውልቆ የግምጃ ልብስን ለበሰ፤ ወደ ሙሽሪቷም ሒዶ ራስዋን ሳማት፤ እንዲህም እያለ ተሰናበታት፤ “እግዚአብሔር ከአንቺ ጋር ይኑር፤ ከሰይጣን ሥራ ሁሉ ያድንሽ።” እርሷም አልቅሳ “ጌታዬ ወዴት ትሔዳለህ? ለማንስ ትተወኛለህ? አለችው፤ እርሱም “በእግዚአብሔር ዘንድ እተውሻለሁ፤ እኔም ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስን ልከተለው እሔዳለሁ፤ የአባቴ መንግሥት አላፊ ነውና አንቺም መሐላሽን አስቢ” አላት፤ ያን ጊዜ መሐላዋን አስባ ዝም አለች።

ለሠርጉም የታደሙት ሁሉ እንደተኙ በሌሊት ወጥቶ ሔደ፤ ወደ ባሕርም ዳርቻ ደርሶ በመርከብ የሚጓዙ መንገደኞችን አገኘ፤ የዓመት መንገድ ወደሚሆን አርማንያም እስከሚደርስ ከእነርሱ ጋር ተጓዘ።

ነግቶ ወደ ሠርጉ አዳራሽ አባትና እናቱ በገቡ ጊዜ ሙሽራውን ልጃቸውን አላገኙትም፤ ሙሽሪትንም “ልጃችን ወዴት አለ?” ብለው ጠየቋት፤ እርሷም እንዲህ አለቻቸው። “በሌሊት ወደ እኔ ገባ፤ መሐላን አማለኝ፤ ከእኔ ጋር ቃል ኪዳን አደረገ፤ ራሴንም ስሞኝ ከእኔ ዘንድ ወጣ፤ እኔም እያለቀስኩ ብቻዬን አደርኩ፤” ነገርዋንም ሰምተው ወድቀው በመጮህ ታላቅ ልቅሶን አለቀሱ።

በዚያችም ጊዜ በሀገሮች ውስጥ ሁሉ ልጁን ገብረ ክርስቶስን ይፈልጉት ዘንድ ንጉሡ አምስት መቶ አገልጋዮቹን ላከ፤ ለድኆችና ለምስኪኖችም ምጽዋት አድርገው የሚሰጥዋቸውን ብዙ ገንዘብን ሰጣቸው።

ገብረ ክርስቶስ ግን በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ስም በአርማንም አገር በተሠራች በአንዲት ቤተ ክርስቲያን ደጅ የሚኖር ሆነ። አባቱ የላካቸውም ሁለቱ አገልጋዮች ከዚያ ደርሰው ስለርሱ መረመሩ፤ ግን ወሬውን ማግኘት ተሳናቸው፤ ለድኆችም ምጽዋትን ሰጡ፤ እርሱም ከድኆችም ጋር ምጽዋትን ተቀበለ።

በዚያም ዐሥራ አምስት ዓመት ከኖረ በኋላ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ለአንድ ቄስ ተገለጸችለት፤ ቦታውንም አመልክታ እንዲህ አለችው። “የእግዚአብሔር ሰው ገብረ ክርስቶስን ይዘህ ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ አስገባው፤ ከውጭ አትተወው፤” ቄሱም እመቤታችን እዳዘዘችው አደረገ።

ከዚህም በኋላ የተመሰገነ ገብረ ክርስቶስ በሌሊት ተነሣ ከእመቤታችንም ሥዕል ፊት ቁም ጸለየ፤ እንዲህም አላት፤ “እመቤቴ ሆይ የተሠወረ ሥራዬን አንቺ ለምን ገለጥሽ፤ አሁንም ወደሚሻለኝ ምሪኝ፤” ይህንንም ብሎ የእመቤታችንን ሥዕሏን ተሳልሞ በሌሊት ወጥቶ ወደ ባሕሩ ወደብ ደረሰ፤ ወደሌላ ሀገርም ሊሔድ ወዶ በመርከብ ተሳፈረ። ግን በእግዚአብሔር ፈቃድ ከአባቱ አገር ደረሰ የአባቱና የእናቱም ባሮች እየናቁትና እየሰደቡት በአባቱ ደጅ ዐሥራ አምስት ዓመት ኖረ።

ሲገቡና ሲወጡም “ሽታው እንዳያስጨንቀን ይህን ምስኪን አስወግዱልን” ይላሉ፤ ወጭትና ድስትም አጥበው በላዩ ይደፉበታል፤ ውሾችም እንዲናከሱበትና እንዲበሉት የሥጋ ትርፍራፊ ይጥሉበታል፤ ውሾች ግን ቁስሉን ይልሱለት ነበር፤ እንደዚህም አብዝተው አሠቃዪት።

ከዚህም በኋላ ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎ ለመነ፤ “ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ፥ ለአባቴና ለእናቴ ባሮች በደል እንዳይሆንባቸው ወዳንተ ውሰደኝ።” በዚያንም ጊዜ ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስሙን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው። ከዚህም በኋላ ገድሉን ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው ጻፈ፤ በእጁም ጨብጧት ዐረፈ።

በእሑድ ቀንም ሕዝቡ ሁሉና ካህናቱ ከሊቀ ጳጳሳቱ ጋር በቅዳሴ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሳሉ የእግዚአብሔርን ሰው በንጉሥ ቴዎዶስዮስ ቤት ፈልጉት የሚል ቃል ከሰማይ ሰሙ፤ በዚያን ጊዜ ሔደው በአረፈበት ቦታ አገኙት። በእጁም ውስጥ የተጨበጠ ክርታስን አዩ፤ ሊወስዷትም ሽተው መውሰድ ተሳናቸው።

በአንድነትም በጸለዩ ጊዜ እጁ ተፈትታ ወስደው አነበቧት፤ አባትና እናቱም ልጃቸው እንደሆነ አወቁ፤ ታላቅ ጩኸትም ሆነ፤ መሪር ልቅሶንም አለቀሱ፤ አክብረውም ቀበሩት፤ መቃብሩም በሽተኞችን ሁሉ በመፈወስ ድንቆች የሆኑ ብዙ ተአምራትን የሚያደርግ ሆነ።

አምላካችን እግዚአብሔር በቅዱስ ገብረ ክርስቶስ ጸሎት ይማረን፤ በረከቱም ከእኛ ጋር ትኑር፤ ለዘለዓለሙ አሜን።

መጽሐፈ ስንክሳር ዘጥቅምት ፲፬

ቅዱሳት ሥዕላት

ክፍል አንድ
ዲያቆን ተስፋዬ ቻይ
ጥቅምት ፮፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! እንዴት አላችሁልን? በአዲሱ ዓመት የመጀመሪያ ትምህርታችን የሆነውን በፈቃደ እግዚአብሔር ጀምረናል፤ ባሳለፍነው ዓመት በተለያዩ ርእሰ ጉዳዮች ስንማር ቆይተን ከዚያም ክለሳ አድርገን ጥያቄና መልስ ማዘጋጀታችን ይታወሳል፡፡ እናንተም ለቀረበላችሁ ጥያቄዎች ምላሽ በመስጠት ተሳትፋችኋል፤ ጥሩ ውጤት ላስመዘገቡ የማበረታቻ ስጦታንም አበርክተንላቸዋል፡፡ (ሰጥተናቸዋል)፤ እንግዲህ በዚህም ዓመት የምናቀርብላችሁን ትምህርት በደንብ ደግሞ መከታተል እንዳለባችሁ ማሳሰብ እንወዳለን፡፡

መርሳት የሌለባችሁ ሌላው ነገር በዘመናዊ ትምህርታችሁ ከአሁኑ ያልገባችሁን በመጠየቅ፣ የቤት ሥራን በመሥራት፣ በማጥናት ጎበዞችና አስተዋይ ልጆች መሆን እንዳለባችሁ ነው!

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ወላጆቻችን ከእኛ በጣም ብዙ ነገር ይጠብቃሉ፤ ጥሩ ውጤት እንድናመጣ፣ ወደፊት ትልቅ ደረጃ እንድንደርስም ይመኛሉ፤ ስለዚህም እኛ ስንፍናን አርቀን፣ ጨዋታን ቀንሰን፣ በርትተን በመማርና በማጥናት ጎበዝ ልጆች መሆን ይገባናል! ወላጆቻችንን እኛን ለማስተማር ብዙ ነገርን ያደርጋሉ፤ ታዲያ እኛ ጎበዞች በመሆን ደስተኞች ልናደርጋቸው ይገባል፡፡ መልካም! በአዲሱ ዓመት በመጀመሪያው ትምህርታችን ስለ ቅዱሳት ሥዕላት እንማራለን፡፡

ወላጆች ከእኛ ጋር ትምህርት ቤት አይሄዱም፤ ከእኛ ክፍል ገብተው አብረውን አይማሩም፤ ግን ልጆቻችን ትምህርት ቤት ሄደው ተምረው ይመጣሉ ብለው አምነው ይልኩናል! አያችሁ እኛ ትምህርት ቤት ገብተን ተምረን በአግባቡ ወደ ቤት በመመለስ መታመናችንን መግለጥ (ማሳየት) ይገባናል፡፡

ቅዱሳት ሥዕላት

‹‹ሥዕል›› ማለት “መልክ፣ የመልክ ጥላ፣ ንድፍ፣ አምሳል፣ ንድፍ በውኃ፣ በመጽሔት፣ በጥልፍ፣ በስፌት ወይም በቀለም በወረቀት ገዝፎ ተጽፎ፣ ከዕብን፣ ከዕፅ፣ ከማዕድን ታንጦ፣ ተቀርጦ፣ ተሸልሞ፣ አጊጦ የሚታይ የሚዳሰስ ነገር” ነው፡፡›› (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመጽሐፈ ሰዋሰው ወግስ መዝገበ ቃላት)
ቅዱሳት የሚለው ቃል ደግሞ «ቀደሰ» ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲሆን ትርጒሙም “ለየ፣ አከበረ፣ መረጠ” ማለት ነው። ውድ

የእግዚአብሔር ልጆች ቅዱሳት ሥዕላት ለእግዚአብሔር የተለዩ፣ የተቀደሱ፣ ልዩ፣ ምርጥ፣ ንጹሕ እና ጽሩይ የሆኑ የቤተ መቅደሱ መገልገያ ንዋያተ ቅድሳት በመሆናቸው «ቅዱሳት» ተብለው ይጠራሉ። እንዲሁም ደግሞ ቅዱሳት ሥዕላት የቅዱሳንን ታሪክ እና ማንነት በጊዜው ላልነበርን በመንፈስ ዓይን እንድናይ ስለሚያደርጉን፣ አንድም ሥጋዊውን ዓለም ከሚያንጸባርቁ ዓለማውያን ሥዕላት ፈጽመው የተለዩ በመሆናቸው፣ አንድም የቅዱሳን ቅድስና ሥዕላቱን ቅዱስ ስላሰኛቸው፣ አንድም በሥዕላቱ አድሮ እግዚአብሔር ስለሚፈጽመው ገቢረ ተአምራት የተነሣ ሥዕላቱ «ቅዱሳት ሥዕላት» ተብለው ይጠራሉ።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት ሥዕላት ተብለው የሚጠሩት ሐዋርያዊ ትውፊትንና ቀኖናን ጠብቀው የሚሣሉ የቅዱስ እግዚአብሔር፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፣ የቅዱሳን መላእክት፣ የቅዱሳን ነቢያት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት እና የሌሎች ቅዱሳን ጻድቃን ማንነት፣ ሕይወትና ታሪክ የሚያሳዩ እና የሚወክሉ ሥዕሎች ናቸው፡፡

የቅዱሳንን ሥዕል መሳል ለምን አስፈለገ?

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ቅዱሳን ሥዕላትን በመሳል ለአገልግሎት እንጠቀም ዘንድ ያዘዘን እራሱ የሰማይና ምድር ፈጣሪ እግዚአብሔር ነው። በመጽሐፍ ቅዱስ የቃል ኪዳኑን ማደሪያ ታቦት እንዴት እንደሚሠራ ሲነግረው እግዚአብሔር ሙሴን እንዲህ ብሎ እንዳዘዘው እናነባለን፤ “ከሥርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን፥ ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርገህ በአንድ ላይ ትሠራዋለህ።” (ዘፀ.፳፭፥፲፱) ይህንንም ሊቀ ነቢያት ሙሴ ሙሴ መፈጸሙን ሲገልጥልን “ከስርየት መክደኛውም ጋር አንዱን ኪሩብ በአንድ ወገን፥ ሁለተኛውንም ኪሩብ በሌላው ወገን አድርጎ በአንድ ላይ ሠራቸው። ክንፎቻቸውን ወደላይ የዘረጉ ሆኑ” በማለት መስክሮታል። (ዘፀ. ፴፯፥፰-፱)

የቅዱሳንን ሥዕል መሳል ያስፈለገው የቅዱሳን መታሰቢያ /ማዘከርያ ስለሆነ፦ እግዚአብሔር አምላካችን ቅዱሳንን ስለ ቅድስናቸው እንዲሁም ስለ እርሱ ብለው ለፈፀሙት ተጋድሎ እንድናስባቸውና እንድንዘክራቸው ትእዛዝ እንዲህ ሲል አስተላልፎልና፤ “በቤቴና በቅጥሬ ውስጥ ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ መታሰቢያ ስም እሰጣቸዋለሁ፣ የማይጠፋ የዘለዓለም ስም እሰጣቸዋለሁ፡፡” (ኢሳ.፶፮፥፭)።

በሌላም በኩል (በመጽሐፈ ምሳሌ ፲፥፯) “የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነው።” (መዝሙረ ዳዊት ፻፲፪፥፮) “የጻድቅ መታሰቢያ ለዘለዓለም ይኖራል” ተብሎ እንደተመሠከረላቸው በረከታቸውን ለማግኘት ለመታሰቢያቸው መለያቸውን ቅዱሳት ሥዕላት እንጠቀማለን።

ሌላው ደግሞ ከእነርሱ በረከት አልፈን ቅዱሳት ሥዕላት በተሳሉበት በቅድስና ስፍራው እግዚአብሔር ራሱንም ስለምናገኝበት ነው፤ ለሊቀ ነቢያት ሙሴ “በዚያም ከአንተ ጋር እገናኛለሁ፤ የእስራኤልንም ልጆች ታዝዝ ዘንድ የምሰጥህን ነገር ሁሉ በምስክሩ ታቦት ላይ ባለው በሁለቱ ኪሩቤል መካከል በሥርየት መክደኛው ላይ ሆኜ አነጋግርሃለሁ” ብሎታልና። (ዘፀ.፳፭፥፳፪)

ጠቢቡ ሰሎሞን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ባነፀ (በሠራ) ጊዜ ቅዱሳት ሥዕላትን ሠርቶ ነበር፤ “በቅድስተ ቅዱሳኑም ውስጥ ቁመታቸው ዐሥር ክንድ የሆነ ከወይራ እንጨት ሁለት ኪሩቤል ሠራ፤ ኪሩቤልንም በወርቅ ለበጣቸው፤ በቤቱም ግንብ ሁሉ ዙሪያ በውስጥና በውጭ የኪሩቤልና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸ፤ ሁለቱንም ደጆች ከወይራ እንጨት ሠራ፤ የኪሩቤልንና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸባቸው፥ በወርቅም ለበጣቸው፤ ኪሩቤልንና የዘንባባውን ዛፍ በወርቅ ለበጣቸው፤ የኪሩቤልንና የዘንባባ ዛፍ የፈነዳም አበባ ምስል ቀረጸባቸው፤ በተቀረጸውም ሥራ ላይ በወርቅ ለበጣቸው” ተብሎ ተጽፏል። (፩ኛ ነገ ፮ ፥፳፫-፴፭)።

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! በዘመነ ሐዋርያት ደግሞ ቅዱስ ሉቃስና ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ ቅዱሳት ሥዕላትን ይሥሉ ነበር። ነባቢ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ በራእዩ የተመለከታትን የቃል ኪዳኑ ታቦት ነው፡፡ (ራእይ ፲፩፥፲፱)

ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ለዛሬ ስለ ቅዱሳት ሥዕላት የቃሉን ፍቺ እና ቅዱሳት ሥዕላት ለምን እንደሚሳሉ በመጠኑ ተመልክተናል፤ በቀጣይ ስለ ቅዱሳት ሥዕላት ጥቅምና አሳሳል እንመለከታለን፡፡ (ምንጭ ኦርዶክሳዊ ቅዱሳት ሥዕላት አሳሳል)
ሁል ጊዜም እንደምንነግራችሁ በትምህርታችሁ በርትታችሁ ተማሩ! ለወላጅ መታዘዝን፣ ለሰዎች መልካም ማድረግን እንዳትረሱ፤ በሰንበት ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመሄድ መንፈሳዊ ትምህርትንም ተማሩ፡፡ ቸር ይግጠመን!

ስብሐት ለእግዚአብሔር
ወለወላዲቱ ድንግል
ወለመስቀሉ ክቡር አሜን!!!

የንሂሳው ኮከብ

ጥቅምት ፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

በዐፄ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት፣ ዐሥራ ሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ የመጡት ግብጻዊው ቅዱስ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የትውልድ ስፍራቸው በላዕላይ ግብጽ ንሂሳ እንደሆነ ገድላቸው ይጠቅሳል፡፡

አባታቸው ስምዖን እናታቸው አቅሌስያ የተባሉት ወላጆቻቸው እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ሰዎች እንደነበሩ ሆኖም ልጅ አጥተው ፴ (ሠላሳ) ዘመን ሲያዝኑ መኖራቸውንም ታሪካቸው ያነሣል፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀንም እናታቸው አቅሌሲያ ቤተ እግዚአብሔር ገብታ ከሥዕለ ሥላሴ ሥር ወድቃ ስትማጸን ክብሩ ከሰማይ ከፍታ የሚበጥ ልጅ እንኪ ተቀበይ የሚል ድምጽ ሰማች፡፡ ‹‹ሥልጣኑ ከሰማይ ከፍታ ከፍ የሚል ንጽሕናው ከሚካኤል ከገብርኤል የሚተካከል ክህነቱ እንደ መልከጼዴቅ እንደ መጥምቁ ዮሐንስ እንደ ነቢይ ኤልያስ የሆነ ልጅ እንቺ ተቀበይ›› አላት፡፡ አቅሌስያም በመጋቢት ፳፱ ቀን ፀንሳ በታኅሣሥ ፳፱ ቀን ደም ግባቱ እጅግ የሚያምር ወንድ ልጅ እንደወለደች መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሰው አምሳል መጥቶ ‹‹የዚህ ልጅሽ ስሙ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ይሁን›› አላት፡፡ ወዲያውም ሕፃኑ ተነሥቶ ከእናቱ ጭን ወርዶ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ሦስት ጊዜ ሰገደ፡፡ ዳግመኛም ‹‹ከጨለማ ወደ ብርሃን ለአወጣኸኝ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን›› አለ፡፡

አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተፀነሱት መጋቢት ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን፣ የተወለዱት ደግሞ ታኀሣሥ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ)  ነው፡፡ አባታችን ዓይን በገለጡ ጊዜ ከሚታይ ነገር ላይ እንዲያርፍ እርሳቸውም በተወለዱ ጊዜ ተነሥተው «ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ዘዓውፃእከኒ እምጽልመት ውስተ ብረሃን» ብለው አመስግነዋል። አባታችን ለአምላክ ሰግደው አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ካመሰገኑ በኋላ እናታቸው አላቀፈቻችውም፤ ጡትም አልጠቡም፡

ጻድቁ አባታችን አኗኗራቸው እንደ መላእክት በምድረ በዳ የነበር፣ በዝቋላ ተራራ ባለው ባሕር ውስጥ ፻ (መቶ) ዓመት ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ሰዎች ምሕረትን የለመኑና ምሕረትን ያሰጡ ቅዱስ ናቸው፡፡ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ከ፭፻ (አምስት መቶ ዓመታት) በላይ በዚህ ምድር ላይ መኖራቸውንና ከትግራይ እስከ ሸዋ ባለው ክፍል ተዘዋውረው ማስተማራቸውን ገድላቸው ያትታል፡፡ በዚህም ምክንያት ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስንና ምድረ ከብድ ገዳማትን መትከላቸውን ታሪካቸው ያሳያል፡፡ ያረፉት በዐፄ ሕዝብ ናኝ ዘመን መጋቢት አምስት ቀን ነው፡፡ የምሕረት ቃልኪዳን የተቀበሉት ደግሞ ጥቅምት አምስት ቀን ነው፡፡ የከበረው በድነ ሥጋቸውም በምድረ ከብድ ይገኛል፡፡ ጻድቁ በትግራይ አቡዬ፣ በአማራው አቡነ፣ በኦሮሞዎች ዘንድ ደግሞ አቦ በመባል ይታወቃሉ፡፡

የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፤ በጸሎታቸው ይማረን!

ምንጭ፡ – ገድለ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ ተስፋ ገብረ ሥላሴ ፲፱፻፺፪ .

 

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

ያለምንም ደመወዝ በራሳቸው ዓቅም በግብርና እየተዳደሩ ቤተ ክርስቲያንን በጥሩ ሰብእና በንጽሕና እና በቅድስና ጠብቀው ያስረከቡ እልፍ አእላፍ አበው እንዳልነበሯት ዛሬ የተሻለ ኑሮና ደመወዝ እያገኘን እግዚአብሔርን እንደቀኖናው በጥንቃቄ ማገልገል አቅቶናል” ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ

ጥቅምት ፬/፳፻፲፰ ዓ.ም

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!!

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ

የደቡብ ምዕራብ ሸዋና የሸገር ከተማ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ

የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ እና የራያ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፣

ብፁዕ አቡነ ሕርያቆስ

የአዲስ አበባና ሐድያ ስልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀጳጳስ

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት፣

የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት የየመምሪያውና የየድርጅቱ ኃላፊዎች ፣

ከሀገር ውስጥና ከውጭ ሀገር የመጣችሁ የየሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጆችና የየክፍሉ ተወካዮች፣

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ኃላፊዎች፣

የገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎችና ተወካዮች

የምእመናንና የሰንበት ትምህርት ቤት ተወካዮች፣

በአጠቃላይ በዚህ ዓመታዊ ጉባኤ የተገኛችሁ ክቡራና ክቡራት

እግዚአብሔር አምላካችን ዓመቱን ጠብቆ በከፍተኛ ጉጉት ለምንጠብቀው አርባ አራተኛው የሰበካ ጉባኤ አጠቃላይ መንፈሳዊ ዓለም ዓቀፍ ጉባኤ ስላደረሰን ክብርና ምስጋና ለእርሱ እናቀርባለን፡፡ እናንተንም እንኳን በደኅና መጣችሁ እንላለን፡፡

“ዑቁ እንከ ዘከመ ተሓውሩ ከመ ጠቢባን በንጽሕ ወአኮ ከመ ዓብዳን፤ ጥበብ እንደሌላቸው ሳይሆን እንደ ጥበበኞች እንዴት በንጽሕና እንደምትመላለሱ ዕወቁ” (ኤፌ.፭፥፲፭)፤ ሁሉንም መስጠትና መንሣት የሚችለው እግዚአብሔር አምላክ ጥበብን ለሰው ልጆች ሰጥቶአል፤ የሚሰጠው የጥበቡ ደረጃ የተለያየ ቢሆንም እግዚአብሔር ከጥበብ ባዶ አድርጎ የፈጠረው ግን የለም፤ የእግዚአብሔር ስጦታዎች ለፍጡራን ሲሰጡ ሊጠቀሙባቸው እንጂ እንዲሁ በከንቱ ሊያባክኑዋቸው አይደለም፡፡

ቅዱስ መጽሐፍ ስለ ጥበብ አስፈላጊነት በብዙ ቦታ ያስተምራል፤ በተለይም ጠቢቡ ሰሎሞን “ጥበብ ትኄይስ እምኲሉ መዛግብት ወኲሉ ክብር ኢመጠና ላቲ፤ ከሀብት ሁሉ ጥበብ ትበልጣለች፤ ክብርም ሁሉ አይመጣጠናትም” በማለት የጥበብ ብልጫ ተወዳዳሪ የሌላት እንደሆነች ያስገነዝበናል፤ እግዚአብሔርም ሥራውን ሁሉ በጥበብ እንደሚሠራ “ወኲሎ በጥበብ ገበርከ፤ ሁሉንም በጥበብ አደረግህ” በሚል ተጽፎ ይገኛል፤ እግዚአብሔር ሥራውን በጥበብ እንደሚሠራ፣ እኛንም በጥበብ መሥራት እንዳለብን ሲያስተምረን፣ ‹‹ኩኑ ጠቢባነ ከመ አርዌ ምድር እንደ እባብ ብልሆች ሁኑ›› ብሎናል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት!

ክቡራን የጉባኤው ተሳታፊዎች!

ዘመንና ቦታ ሳይገድበን ምንጊዜም ሥራችንን በጥበብ መሥራት እንዳለብን ቢታወቅም ዛሬ ላይ ከምን ጊዜውም በበለጠ በጥበብ መመላለስ የሚያስፈልግበት ጊዜ ላይ እንገኛለን፤ የዛሬዎቹ ችግሮች በአንድ አካባቢ ብቻ ያሉ ሳይሆኑ ዓለም ዓለፍ ቅርጽ ያላቸው እንደሆኑ ታላላቅ መሪዎች ሳይቀሩ በዓለም መድረክ ላይ ስሞታ ሲያቀርቡ በዓይናችን አይተናል፤ በጆሮአችንም ሰምተናል፤ በሁኔታውም የክርስትና ሃይማኖት በአጠቃላይ በተለይም ደግሞ የኦርቶዶክሱ ወገን የችግሩ ገፈት ቀማሽ እንደሆነ እየተስተዋለ ነው፡፡

እኛም የዚሁ ወገን አካል በመሆናችን የችግሩ ቀማሽ መሆናችን አልቀረም፤ በየቀኑ ካህናትና ምእመናን ይገደሉብናል፤ አብያ ክርስቲያናት ይቃጠሉብናል፤ የእምነትና የኅሊና ነጻነት በእጅጉ የሳሳ ሆኖብናል፤ አላስፈላጊ ጫናዎችም በዝተውብናል፤ ከውጭና ከውስጥ በተቀነባበረ ስሌት የቤተክርስቲያናችንን ስም ማጥፋት የዕለት ተግባራቸው ያደረጉ አካላት ተበራክተዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ከነባሩና ረጅም ዘመን ካስቈጠረው ሰፊ ማእዷ እያበላቻቸው ያለች መሆኗን ዘንግተው እንብላሽ፣ እንዋጥሽ የሚሉዋት ወገኖች በዝተዋል፣ በእነዚህና በሌሎች ምክንያቶች አባቶች እንደልብ ተንቀሳቅሰው መሥራት የማይችሉባቸው አጋጣሚዎች እየተፈጠሩ ነው፤ የወለጋው ችግር ለዚህ በዋናነት ተጠቃሽ ነው፡፡

ታድያ እነዚህን ፈተናዎች ለማለፍ ጥበብ ያስፈልጋል፤ ነገር ግን ጥበብ መከተል ማለት ዝም ብሎ ማለፍ ወይም አይተው እንዳላዩ ሆኖ መኖር ማለት አይደለም፤ በጥበብ መመላለስ ማለት ከሁሉ በፊት ችግሮችንና የችግሮችን መንሥኤዎች በአግባቡ መረዳትና መለየት መቻል ነው፤ ከዚያም ራስን ለከፋ አደጋ በማያጋልጥ መልኩ የተለያዩ ስልቶችን በመጠቀም መሸጋገር መቻል ነው፤ በዚህ ዘመን እንዲህ ያለ ጥበብ መጠቀም የግድ ያስፈልጋል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት!

ክቡራን የጉባኤው ተሳታፊዎች! ቤተ ክርስቲያናችን እየተፈተነች ያለችው ከውጭ ብቻ ሳይሆን ከውስጥም ጭምር እንደሆነ መካድ የለብንም፤ ንጽሕትና ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥር የሰደደ የቅድስና ሕይወትና በፈሪሀ እግዚአብሔር የተቃኘ ሥነ ምግባር ያላት ቤተ ክርስቲያን ናት፤

በአሁኑ ጊዜ ግን እነዚህ ሁሉ ቦታቸውን እየለቀቁ ያሉ መስለዋል፤ ቤተ ክርስቲያን በረጅሙ ታሪኳ ሲያስተምሩም ሆነ ሲማሩ፣ ሲመንኑም ሆነ ሲመነኲሱ፣ ሲቀድሱም ሆነ ሲያስቀድሱ ያለምንም ደመወዝ በራሳቸው ዓቅም በግብርና እየተዳደሩ ቤተ ክርስቲያንን በጥሩ ሰብእና በንጽሕና እና በቅድስና ጠብቀው ያስረከቡ እልፍ አእላፍ አበው እንዳልነበሯት ዛሬ የተሻለ ኑሮና ደመወዝ እያገኘን እግዚአብሔርን እንደቀኖናው በጥንቃቄ ማገልገል አቅቶናል፤ ምእመናንም በዚህ ምክንያት እየተሰናከሉ እንደሆነ እየተስተዋለ ነው፡፡ ሚድያውም ስሕተቶችን ወደ ውጭ በማውጣት ሰድቦ ለሰዳቢ እየዳረገን ነው፤ ይህ ሊሆን የቻለው የቤተ ክርስቲያን ሀብትና ንብረት በአግባቡ በመያዝ ለታለመለት ዓላማ ማዋል አለመቻላችን ነው፤ ይህ ችግር ባለበት ከቀጠለ ሌላ ጦስ ይዞብን እንዳይመጣ ሁነኛ ለከት ማኖር የግድ ይሆናል፡፡

የሰበካ ጉባኤ አደረጃጀት የቤተ ክርስቲያናችንን ሀብተ ጸጋ በማሳደግ ረገድ አስተማማኝ ስልት እንደሆነ በተግባር የተረጋገጠ ነው፤ ሆኖም ሲጀመር ሳለ የነበረ መነቃቃት በአሁኑ ጊዜ የቀነሰ መስሎ ይታያል፤ አሁን በቤተ ክርስቲያን ሰፊ ሽፋን ይዞ የሚገኘው የሙዳየ ምጽዋት ገቢ እንጂ የሰበካ ጉባኤ አስተዋፅኦ እንደአይደለ ሁላችንም እናውቃለን፤ በተለይም በከተሞች ውስጥ ነገሩ ጎልቶ ይታያል፡፡

ይህ የሆነበት ምክንያት ምናልባትም በየደረጃው በኃላፊነት ያለን ሰዎች ሻል ያለ ደመወዝ ስለምናገኝ የሰበካ ጉባኤው ተልእኮ ከሚፈለገው ደረጃ ላይ  የደረሰ መስሎን ይሆናል፤ ነገር ግን ከሰማንያ ከመቶ ያላነሰ የገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ መምህርና ካህን አሁንም ያለ ደመወዝ የሚኖር ነው፤ ሕዝበ ክርስቲያኑም ከቤተ ክርስቲያኑ ሊያገኘው የሚገባ የበጎ አድራጎት የጤና የትምህርትና የማኅበራዊ ዋስትና አገልግሎት በሚጠበቀው ደረጃ ሊያገኝ አልቻለም፤ የገዳማትና የአብነት ት/ቤቶች ችግሮችም በነበሩበት የልመና ኑሮ እየቀጠሉ ነው፤ በውጤቱም በችግር የሚኖሩ ገዳማት የተዘጉ የአብነት ት/ቤቶችና አብያተ ክርስቲያናት ከተበራከቱ ሰነባብቶአል፡፡

ታድያ ይህንን ሁሉ መልክ ማስያዝና ቤተ ክርስቲያንን ለቀጣዩ ትውልድ ማሸጋገር የሚቻለው በጥበብና በጥበብ ብቻ መሥራት ሲቻል ነው፤ ይህንን ችግር መፍታት የሚያስችል ጥበብ ደግሞ በዘመናችን አለ፤ የጠፋው ቅንነቱና ፈቃደኝነቱ ነው፡፡

በየዓመቱ የምናካሄደው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ እንደነዚህ ያሉትን ችግሮች መቅረፍ የሚያስችል ካልሆነ ተሰብስበናል ማለቱ ብቻ ትርጉም ሊኖረው አይችልም፤ ስለሆነም ከዚህ በላይ የተጠቃቀሱና ሌሎችም የቤተ ክርስቲያናችን ተግዳሮቶች ካሉ በዚህ ጉባኤ በማንሣት በማየትና በመገምገም ለቤተ ክርስቲያን አሻጋሪና ጥበባዊ ውሳኔ እንዲያሳልፍ አባታዊ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም

ዓመታዊው ዓለም ዓቀፍ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዛሬው ዕለት በጸሎተ ወንጌል የተከፈተ መሆኑን በእግዚአብሔር ስም እናበሥራለን፡፡

መልካም ጉባኤ ያድርግልን!

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ !!!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር !!!

አሜን!!!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት ፬ ቀን ፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

የእምነት አርበኛ

መስከረም ፳፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ጽኑ ሰማዕት የእምነት አርበኛ፣ ጠላትን ተዋጊና ድል አድራጊ እናታችን ቅድስት አርሴማ የሰማዕትነት አክሊል የተቀበለችበት የከበረች በዓል መስከረም ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በድምቀት ይከበራል፡፡

እጅግ መልከ መልካም የነበረችው ሮማዊቷ ዕንቁ ከልጅነቷ ጅምሮ ራሷን በድንግልና ሕይወት ጠብቃ የኖረች ቅድስት እንደነበረች ታሪክ ይነግረናል። በዘመኑ ነግሦ የነበረው ከሀዲው ድዮቅልጥያኖስም መልኳ ውብ የሆነች ድንግል ሊያገባ ፈልጎ ከየሀገራቱ ቆንጆ መርጠው ያመጡለት ዘንድ አገልጋዮቹን አዘዛቸው፡፡ እነርሱም በፍለጋቸው በሮሜ አገር ባለች ቤተ ክርስቲያን ቅድስት አርሴማን በማግኘት ሥዕሏን ሥለው ለንጉሡ ላኩለት፡፡ እርሱም በእጅጉ ተደስቶ እንዲያመጧት በማዘዝ ወደ ሰርጉም እንዲመጡ ለመኳንንቱ ላከ፡፡ እርሷና አብረዋት የነበሩትም ደናግል ይህነን በሰሙ ጊዜ በማዘን ድንግልናቸውን ይጠብቅላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር በመለመን ከሮም ተነሥተው በስውር የንጉሥ ድርጣድስ ግዛት ወደነበረችው ወደ አርመን ሸሽተው ሄዱ፡፡

ቅድስት አርሴማም ወደ አርመንያ ሀገር በገባች ጊዜ ከሃድያኑ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን የሚያምኑትን ክርስቲያኖችን ላይ መከራን ሲያጸኑባቸው ተመለከተችና አምላካችን ክርስቶስ “እኔ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን የማምን ክርስቲያን ነኝ” በማለት መሰከረች፡፡ የመልኳን ደም ግባትም በማየት ንጉሥ ድርጣድስም ለራሱ ስለተመኛት አምላክን እንድትክድ በብዙ ሽንገላን ሊሸነግሏት ቢሞክሩም አልሆነላቸውም፤ ፈርታ ትክዳለችም ብለው በማሰብ ክርስቲያኖች ለአናብስት ወደሚጣሉበት አደባባይ በመውሰድ የተራቡ አናብስትን በላያቸው ለቀቁባቸው፤ ቅድስት አርሴማ በዚህ ጊዜ ወደ አምላክ ጸሎት አደረገች፤ ድንቅ በሆነው ተአምሩም እግዚአብሔር አናብስቱ ወደ ቅድስቷ ሳይሆን  ወደ ንጉሡ ወታደሮች በመወርወር ብዙዎችን እንዲገድሉ አደረገ፤ በኋላም ተንበርክከው ሰገዱላት፡፡

ንጉሡም በሌላ መንገድ የቅድስት አርሴማን ሐሳብ ለማስቀየርና በግድ ለጣዖታቱ እንድትሰግድ ለማድረግ አሳስሮ አማልክቱ ወዳሉበት ቤተ ጣዖት ወሰዳት፤ ይህን ጊዜ በመስቀል ምልክት ብታማትብ በጣዖታቱ ላይ አድረው ሰዎችን የሚያስቱ አጋንንት እየጮኹ ሲወጡ ጣዖታቱ በመላ እየተሰባበሩ ወድቁ፤ ዳግመኛም እስር ቤት አስገብቶ ሊያስርባት ቢጥርም የእግዚአብሔር መልአክ እንደ ነቢዩ ኤልያስ ኅብስትን መገባት፡፡ ቀጥሎም ንጉሡ ወዳለበት እየጐተቱ ወስደው ሲያቆሟት ንጉሡ ይዞ ወደ እልፍኙ ሊያስገባት ከአደባባይ ተነሥቶ ድንግል አርሴማን በያዛት ጊዜ ቅድስቷ በላይዋ ላይ ባደረው የእግዚአብሔር ኀይል በምድር ላይ ጣለችው፤ ያን ጊዜ በንዴትና በአፍረት አገልጋዮቹን ራሳን እንዲቈርጡ አዘዛቸው። በዚህ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምን አስከትሎ ተገለጸላት። ስሟን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ምሕረትን እንደሚያደርግ ቃል ኪዳንን ገባላት፡፡ በክርስቶስ ፍጹም ፍቅር፣ በእምነት ጽናትና ተጋድሎ ዕጹብ ድንቅ የሆነው ገድሏን ፈጽማ አንገቷን በመሰየፍ መስከረም ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጅታለች።

የቅድስት አርሴማ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፤ በጸሎቷ ይማረን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

የአበባ ወር

መስከረም ፳፮፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ጊዜ የተለያዩ ተፈጥራዊ ኩነቶችን ያስተናግዳል፤ በዓለም ላይ በሚከሰቱ የወቅቶች መፈራረቅም ምድር አንዳንዴ ስትበለጽግ ሌላ ጊዜ ደግሞ ትራቆታለች፡፡ በክረምት ወራት በሚዘንበው ዝናብ ስትረጥብ በበጋ ደግሞ በፀሐይና በሙቀቱ ትደርቃለች፡፡ በዘመነ መጸው በነፋሳት ስትናወጥ ፈክተው የሚያብቡት አበቦች ግን ያስውቧታል፡፡

ቅዱሱ ሰው አባ ጽጌ ድንግል የአበቦችን ዕጹብ ድንቅ ተፈጥሮና የላቀ ዋጋ በማወቁ ሳይሆን አይቀርም ከአበቦች ሁሉ በሚበልጥ አበባ ለምንመስላት ድንግል ማርያም አበቦችን ያበረከተላት፡፡ በዐሥራ አራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሱት ሊቁ የደረሱት የማኅሌተ ጽጌ ድርሰት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ቀን ድረስ ባለው ወቅት የእመቤታችን ከልጇ ጋር ወደ ግብፅ ብሎም ወደ ኢትዮጵያ መሰደድ እና መንከራተት እንዘክርበታለን፡፡

የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤አሜን!

የኒቂያ ጉባኤ

መስከረም ፳፪፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የአርዮስ ክህደት በተስፋፋበት በ፫፻፳፭ ዓ.ም የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት የማይቀበሉ መናፍቃን ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ ጊዜውም ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ስለነበር ንጉሡ በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሄድ በየአገሩ ለነበሩ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡

ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ሊቃውንቱ በሱባኤና በጸሎት ከቆዩ እስከ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይሁን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት ፫፻፲፰ቱ የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው /ዘፍ.፲፬፥፲፬/፡፡

፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡

የቅዱሳን አባቶቻችን ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!