የእምነት አርበኛ

መስከረም ፳፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ጽኑ ሰማዕት የእምነት አርበኛ፣ ጠላትን ተዋጊና ድል አድራጊ እናታችን ቅድስት አርሴማ የሰማዕትነት አክሊል የተቀበለችበት የከበረች በዓል መስከረም ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በድምቀት ይከበራል፡፡

እጅግ መልከ መልካም የነበረችው ሮማዊቷ ዕንቁ ከልጅነቷ ጅምሮ ራሷን በድንግልና ሕይወት ጠብቃ የኖረች ቅድስት እንደነበረች ታሪክ ይነግረናል። በዘመኑ ነግሦ የነበረው ከሀዲው ድዮቅልጥያኖስም መልኳ ውብ የሆነች ድንግል ሊያገባ ፈልጎ ከየሀገራቱ ቆንጆ መርጠው ያመጡለት ዘንድ አገልጋዮቹን አዘዛቸው፡፡ እነርሱም በፍለጋቸው በሮሜ አገር ባለች ቤተ ክርስቲያን ቅድስት አርሴማን በማግኘት ሥዕሏን ሥለው ለንጉሡ ላኩለት፡፡ እርሱም በእጅጉ ተደስቶ እንዲያመጧት በማዘዝ ወደ ሰርጉም እንዲመጡ ለመኳንንቱ ላከ፡፡ እርሷና አብረዋት የነበሩትም ደናግል ይህነን በሰሙ ጊዜ በማዘን ድንግልናቸውን ይጠብቅላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር በመለመን ከሮም ተነሥተው በስውር የንጉሥ ድርጣድስ ግዛት ወደነበረችው ወደ አርመን ሸሽተው ሄዱ፡፡

ቅድስት አርሴማም ወደ አርመንያ ሀገር በገባች ጊዜ ከሃድያኑ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን የሚያምኑትን ክርስቲያኖችን ላይ መከራን ሲያጸኑባቸው ተመለከተችና አምላካችን ክርስቶስ “እኔ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን የማምን ክርስቲያን ነኝ” በማለት መሰከረች፡፡ የመልኳን ደም ግባትም በማየት ንጉሥ ድርጣድስም ለራሱ ስለተመኛት አምላክን እንድትክድ በብዙ ሽንገላን ሊሸነግሏት ቢሞክሩም አልሆነላቸውም፤ ፈርታ ትክዳለችም ብለው በማሰብ ክርስቲያኖች ለአናብስት ወደሚጣሉበት አደባባይ በመውሰድ የተራቡ አናብስትን በላያቸው ለቀቁባቸው፤ ቅድስት አርሴማ በዚህ ጊዜ ወደ አምላክ ጸሎት አደረገች፤ ድንቅ በሆነው ተአምሩም እግዚአብሔር አናብስቱ ወደ ቅድስቷ ሳይሆን  ወደ ንጉሡ ወታደሮች በመወርወር ብዙዎችን እንዲገድሉ አደረገ፤ በኋላም ተንበርክከው ሰገዱላት፡፡

ንጉሡም በሌላ መንገድ የቅድስት አርሴማን ሐሳብ ለማስቀየርና በግድ ለጣዖታቱ እንድትሰግድ ለማድረግ አሳስሮ አማልክቱ ወዳሉበት ቤተ ጣዖት ወሰዳት፤ ይህን ጊዜ በመስቀል ምልክት ብታማትብ በጣዖታቱ ላይ አድረው ሰዎችን የሚያስቱ አጋንንት እየጮኹ ሲወጡ ጣዖታቱ በመላ እየተሰባበሩ ወድቁ፤ ዳግመኛም እስር ቤት አስገብቶ ሊያስርባት ቢጥርም የእግዚአብሔር መልአክ እንደ ነቢዩ ኤልያስ ኅብስትን መገባት፡፡ ቀጥሎም ንጉሡ ወዳለበት እየጐተቱ ወስደው ሲያቆሟት ንጉሡ ይዞ ወደ እልፍኙ ሊያስገባት ከአደባባይ ተነሥቶ ድንግል አርሴማን በያዛት ጊዜ ቅድስቷ በላይዋ ላይ ባደረው የእግዚአብሔር ኀይል በምድር ላይ ጣለችው፤ ያን ጊዜ በንዴትና በአፍረት አገልጋዮቹን ራሳን እንዲቈርጡ አዘዛቸው። በዚህ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምን አስከትሎ ተገለጸላት። ስሟን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ምሕረትን እንደሚያደርግ ቃል ኪዳንን ገባላት፡፡ በክርስቶስ ፍጹም ፍቅር፣ በእምነት ጽናትና ተጋድሎ ዕጹብ ድንቅ የሆነው ገድሏን ፈጽማ አንገቷን በመሰየፍ መስከረም ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጅታለች።

የቅድስት አርሴማ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፤ በጸሎቷ ይማረን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

የአበባ ወር

መስከረም ፳፮፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ጊዜ የተለያዩ ተፈጥራዊ ኩነቶችን ያስተናግዳል፤ በዓለም ላይ በሚከሰቱ የወቅቶች መፈራረቅም ምድር አንዳንዴ ስትበለጽግ ሌላ ጊዜ ደግሞ ትራቆታለች፡፡ በክረምት ወራት በሚዘንበው ዝናብ ስትረጥብ በበጋ ደግሞ በፀሐይና በሙቀቱ ትደርቃለች፡፡ በዘመነ መጸው በነፋሳት ስትናወጥ ፈክተው የሚያብቡት አበቦች ግን ያስውቧታል፡፡

ቅዱሱ ሰው አባ ጽጌ ድንግል የአበቦችን ዕጹብ ድንቅ ተፈጥሮና የላቀ ዋጋ በማወቁ ሳይሆን አይቀርም ከአበቦች ሁሉ በሚበልጥ አበባ ለምንመስላት ድንግል ማርያም አበቦችን ያበረከተላት፡፡ በዐሥራ አራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተነሱት ሊቁ የደረሱት የማኅሌተ ጽጌ ድርሰት ከመስከረም ፳፮ እስከ ኅዳር ፭ ቀን ድረስ ባለው ወቅት የእመቤታችን ከልጇ ጋር ወደ ግብፅ ብሎም ወደ ኢትዮጵያ መሰደድ እና መንከራተት እንዘክርበታለን፡፡

የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤አሜን!

የኒቂያ ጉባኤ

መስከረም ፳፪፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የአርዮስ ክህደት በተስፋፋበት በ፫፻፳፭ ዓ.ም የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት የማይቀበሉ መናፍቃን ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ ጊዜውም ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ስለነበር ንጉሡ በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሄድ በየአገሩ ለነበሩ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡

ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ሊቃውንቱ በሱባኤና በጸሎት ከቆዩ እስከ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይሁን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት ፫፻፲፰ቱ የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው /ዘፍ.፲፬፥፲፬/፡፡

፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡

የቅዱሳን አባቶቻችን ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

 

ግሸን ማርያም

መስከረም ፳፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የግሸን ማርያም ደብር መመሥረት ከግማደ መስቀል ጋር የተያያዘ ዋነኛ ምክንያት አለው፡፡ ግማደ መስቀሉ ከእስክንድርያ የገባው መስከረም ፲ ቀን ቢሆንም ኢትዮጵያ ‹‹ግሸን አምባ›› የገባበት፣ መቅደስ ተሠርቶ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረውና ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ለመላው ኢትዮጵያ በጽሑፍ በመዘርዘር የገለጹበትም መስከረም ፳፩ ቀን ነው፡፡

በየዓመቱ መስከረም በባተ በ፳፩ኛው ቀንም በግሸን ደብር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች ከበረከተ መስቀሉና ከቅዱሳን ዐፅም በረከት ለማገኘት ከየክፍለ ሀገራቱ እየመጡ ያከብራሉ፡፡ ምእመናንም በግሸን ማርያም ለመገኘት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ይሄዳሉ፡፡ ኃጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ሁሉ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ‹‹ጤፉት›› በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡

አምላካችን እግዚአብሔር ከበረከተ መስቀሉ ያሳትፈን፤ አሜን!!!

 

መስቀል

መስከረም ፲፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ፍጹም ድንቅ የሆነው የጌታ ፍቅር የተገለጸበት፣ ሰላም የተበሠረበት፣ የነጻነታችን መገለጫ፣ የድኅነታችን መረጋገጫ ቅዱሱ መስቀል የተገኘበት ዕለት የከበረ ነውና በየዓመቱ በድምቀት ይከበራል፡፡ የመጀመሪያው ሰው አዳም በበደሉ ምክንያት ዕዳውን ይከፍለለት ዘንድ ሰው ሆኖ በሞቱ ሕይወትን የሰጠን አምላክ በመስቀል ተሰቅሎ ስለሆነም የመስቀሉ ነገር ለክርስቲያኖች ብዙ ትርጒም አለው፡፡

ለሰው ዘር በሙሉ በተገባለት ቃል ኪዳን መሠረት ጌታችን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ፣ ሰው ሆኖ፣ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ድኅነትን ለሰው ልጆች ሰጥቶ፣ በመስቀሉ ተጣልተው የነበሩ ሰባቱን መስተፃርራን (ሰውና እግዚአብሔርን መላእክትና ሰውን፣ ነፍስና ሥጋን፣ ሕዝብና አሕዛብን) አስታርቋል፡፡

በሐዲስ ኪዳን መስቀል የመዳን ምልክት መሆኑ የተረጋገጠበት በክርስቶስ ደም የተቀደሰ፣ የጠብ ግድግዳን ያፈረሰ፣ ቅድስናና ክብር ያለው የአበው ተስፋ የተፈጸመበት፣ ሰው ከውድቀቱ የተነሣበት መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ ነቢዩ ዳዊት ‹‹እግዚአብሔር ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማእከለ ምድር … እግዚአብሔር ግን ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድርም መካከል መድኃኒትን አደረገ›› (መዝ. ፸፫፥፲፪) እንዳለው መድኃኒት የሆነው አምላካችን በመስቀሉ አዳነን፡፡ (ዮሐ. ፲፱፥፲፯፣ኤፌ. ፪፥፲፮፣ ቆላ. ፩፥፳)

ከበዓሉ በረከት ይክፈለን፤ አሜን!!!

 

የአበባ በዓል

 

መስከረም ፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ምድር በአበባ በምታሸበርቅበት በክረምት መውጫ በተለየ መልኩ የሚከበረው ተቀጸል ጽጌ (የአበባ በዓል) መስከረም ፲ ቀን ነው፡፡ ተቀጸል ጽጌ ማለትም (አበባን ተቀዳጀ) የሚባለውን በዓል ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታከብራለች፡፡

በአበባ በምትዋብበት ወቅት ምድር በአረንጓዴ ተክሎች በምትዋውበት፣ በዕፅዋቶች ልምላሜ በምትደምቅበት፣ በአዝእርቶች ቅጠል ልምላሜ በምትሸለመብበት ጊዜ በዘመኑ የነበሩት የኢትዮጵያ ንጉሥ ዐፄ ገብረ መስቀል በመስከረም ፲ በአረንጓዴ፣ በቢጫ እና በቀይ ቀለም ደምቆ የጽጌረዳ አበባ በመሰለ ፈርጥ የተሠራ ዘውድ ደፍተው በአደባባይ በሠራዊቶቻቸው ታጅበው የክረምቱን ማለፍ እያበሰሩ በክብር በሰዎች መካከል ይገኛሉ፡፡

በዚያን ጊዜም በወቅቱ የነበሩት ካህናት በዝማሬ ምእመናኑ በእልልታ የክረምቱን ማለፍ የዘመነ ጸደይን መተካት እያገለጹ እግዚአብሔር አምላክን ያመሰግናሉ፡፡ ዐፄ ገብረ መስቀል በዚሁ  ግብር ያበላሉ፡፡ ተቀጸል ጽጌ በዚህ መልኩ እየተከበረ አስከ ዐፄ ዳዊት ፲፫፻፺፭ ዓ.ም እንደደረሰ ታረክ ያወሳናል፡፡ ከዚህም በኋላ በዐፄ ዳዊት ዘመነ መንግሥት ከሊፋ የሚባል የግብጽ ንጉሥ ተነሥቶ በግብጻውያን ክርስቲያኖች ላይ ጭቆና ሲያደርስባቸው ፓትርያርካቸውን ጭመር በማሰር በብዙ አሠቃያቸው፡፡

ንጉሡም ወደ ግብጽ ንጉሥ “እርዳን፤ እምነትህ እምነታችን ነው” የሚል መልእክት ላኩ፡፡ ከዚያም ሠራዊቱን አስከትሎ የኢትዮጵያን ድንበር አልፎ ሱዳን እና የግብጽ ድንበር ላይ ስናር በሚባለው ቦታ ሆኖ ለግብጹ መሪ “በክርስቲያኖች ላይ የሚያደርሰውን መከራ የማታቆም ከሆነ ዘምቼ እዋጋሃለው፤ አባይንም እገድባለሁ” በማለት መልእክት ይልክበታል፡፡ ከዚያም የግብጹ መሪ በክርስቲኖች ላይ የሚያደርሰውን ግፍና መከራ አቆመ፡፡

የግብጽ ክርስቲኖችም ነጻነታቸውን በማግኘታቸው ደስ ተሰኝተው ለኢትዮጵያው ንጉሥ እጅ መንሻ አድርገው ወርቅ፣ ብር እና አልማዝ ይልካሉ፤ ንጉሡ ዐጼ ዳዊት ግን “ይህ ምን ያደርግልኛል፤ ወርቅማ በሀገሬም ሞልቶኛል፤ የምፈልገው የክርስቶስን ግማደ መስቀል የቀኝ እጁ ያረፈበትን መስቀል ነው” በማለት ይመልሳል፡፡ ምንም እንኳን ለመስቀሉ ያላቸው ፍቅር ታላቅ ቢሆንም በእምነታቸው ተከብረው እንዲኖሩ ያደረጋቸው የንጉሡ የዐፄ ዳዊት እርዳታ ስለሆነና አሁንም ከንጉሡ ጋር ካልተባበሩ የግብጹ መሪ ሊያጠቃቸው ስለሚችል ዐጼ ዳዊትን ለማስደሰት የክርስቶስን ግማደ መስቀል ከልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳት ጋር ላኩላቸው፡፡ ሆኖም ንጉሡ መስቀሉን ወደ ኢትዮጵያ ሳያስገቡ ያርፏሉ፡፡

ለ፵፯ ዓመትም መስቀሉም በዚያው ቆይቶ ንጉሡ ልጅ በዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ በ፲፬፻፵፫ ዓ.ም መስከረም ፲ ቀን ወደ ኢትዮጵያ ገባ፡፡ ለመስቀሉ ክብር እንዲሆን በማሰብም በመስከረም ፳፭ ቀን የሚከበረው የተቀጸል ጽጌ በዓል መስከረም ፲ ቀን እንዲከበር ተወሰነ፡፡ በዚህም ሁኔታ እስከ ዐፄ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት መጨረሻ “ተቀጸል ጽጌ፣ የዐፄ መስቀል፣ ሐፀጌ” በማለት እየተከበረ እስከ ፲፱፻፷፮ ቆይቶአል፡፡  በቤተ መንግሥት በመሪዎች ደረጃ ግን መከበሩ አልቀጠለም፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ግን ቅዱስ ፓትርያርኩ እና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ባሉበት የተወሰኑ አድባራት ካህናት አባቶች፣ መዘምራን በተገኙበት እስከ አሁን ድረስ ታከብራለች፡፡ በዓሉ መስከረም ፲ ቀን በየዓመቱ በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ዛሬም ይከበራል፡፡

ከመስቀሉ በረከት ሁላችንንም ያሳትፈን፤ አሜን!

 

 

 

 

ተአምረኛዋ ሥዕል

መስከረም ፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

እጅጉን የሚያስደንቀው የአምላክ ሥራ የተገለጠበት፣ ለሰው ልጆች ተስፋ፣ ፈውስ ሥጋ እንዲሁም ፈውስ ነፍስን ሊሰጠን በፈቀደ እርሱ ድንቅ ተአምራትን በምድር አደረገ፤ ጌታ በትስብእቱ በዓለም ተገልጦ ካደገጋቸው ተአምራትም በተጨማሪ እርሱ ካረገ በኋላም በሰዎች አድሮ ላይ አድሮም ይሁን በተለያዩ መንገዶች ዕጹብ ሥራውን አሳይቶናል፡፡

ከዚሀ ሁሉም በበለጠ መልኩ በክብርት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም የተደረገው ምሥጢር እጅግ ይልቃል፤ ነገረ ድኅነቱን የፈጸመባት እመቤታችን ለአዳም ዘር በሙሉ ተስፋ በመሆኗ ጌታ ከእርሷ በለበሰው ሥጋ ተገልጦ ያደረገልንን ለመግለጽ ቃላት ባይኖርም ምስጋና ግን ማቅረብ የሁላችንም ፈንታ ነው፡፡ አልፎ ተርፎም እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታ ካረገች በኋላ ድንቅ ተአምርም በእርሷ ተደርጓል፡፡ ቅዱሳት መጽሐፍት በተለያዩ ጊዜ እመቤታችን ያደረገችውን ተአምር ገልጸው ጽፈዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል በመጽሐፈ ስንክሳር መስከረም ፲ ቀን ተመዝግቦ የምናገኘው አንድ ተአምረኛ ሥዕል እንዳለ ነው፤ ታሪኩም እንዲህም ይነበባል፡፡

አንዲት ማርታ የምትባል ሴት እመቤታችን ድንግል ማርያምን የምትወድና በሚቻላትም ሁሉ የምታገለግላት፣ ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባሉ ኢትዮጵያዊ መነኰስ ከእርሷ ዘንድ በእንግድነት አድረው በማግሥቱ ከቤቷ ሲወጡ ማርታ የሚሔዱበትን አገር በጠየቀቻቸው ጊዜ እርሳቸውም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ቅዱሳት መካናትን እንደሚሳለሙ ነገሯት፡፡ ማርታም ከእርሷ ገንዘብ ወስደው የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተው ይዘውላት እንዲመጡ ለመነቻቸው፡፡ መነኵሴውም በራሳቸው ገንዘብ ሥዕሉን ገዝተው እንደሚያመጡላት ቃል ገቡላት፡፡

አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሰው ቅዱሳት መካናትን ከተሳለሙ በኋላ ሥዕሏን ሳይገዙ ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ጉዞ ጀመሩ፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ?›› የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰምተው ተመልሰው መልኳ ያማረና የተወደደ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ገዝተው በሐርና በንጹሕ ልብስ ጠቅልለው ይዘው እየተጓዙ ሳሉ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ሲደርሱ ወንበዴዎች ተነሱባቸው፡፡ ሊሸሹ ሲሉም ‹‹መንገድህን ሒድ›› የሚል ቃል ከሥዕሏ ወጣ መነኵሴውም መንገዳቸውን በሰላም ተጓዙ፡፡ ሁለተኛም አንበሳ ሊበላቸው በተነሣባቸው ጊዜ ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረላቸው፡፡

አባ ቴዎድሮስ ይህን ኹሉ ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜም ያቺን ሥዕል ለማርታ ከመስጠት ይልቅ ወደ አገራቸው ሊወስዷት ወደዱ፡፡ በመርከብ ተሳፍረው በሌላ አቅጣጫ ሲሔዱም ታላቅ ነፋስ ተነሥቶ ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያ ወሰዳቸው፡፡ ከመርከብም ወርደው ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ደረሱ፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን ለማርታ አልገለጡላትም ፤ እርሷም አላወቀቻቸውም ነበር፡፡

በማግሥቱም ተሠውረው ወደ አገራቸው ሊሔዱ ሲሉ የቅፅሩ ደጃፍ ጠፍቶባቸው ሲፈልጉ ዋሉ፤ በመሸባቸው ጊዜም ወደ ማደሪያቸው ተመለሱ፡፡ ማታ ማታ በሩን ያዩታል፤ ነግቶ መሔድን ሲሹ ግን የበሩ መንገድ ይሠወርባቸዋል፡፡ እንዲህም ኾነው እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቆዩ፡፡ ማርታም ‹‹አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን? ስትቅበዘበዝ አይሃለሁና ምን ሆነህ ነው?›› ስትል ጠየቀቻችው፡፡ እርሳቸውም ከእመቤታችን ሥዕል የተደረገውን ተአምር ሁሉ ነገሯት፤ ራሳቸውንም ገለጡላትና ሥዕሏን ሰጧት፡፡ እርሷም የእመቤታችንን ሥዕል ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ልብስ በፈታችው ጊዜ ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋ ብዛት የተነሣም የአባ ቴዎድሮስን እጃቸውንና እግራቸውን ሳመች፡፡ ሥዕሏም ቅዱስ ሉቃስ የሳላት ነበረች፡፡

 

አንኳን ለበዓለ ጼዴንያ ማርያም አደረሳችሁ!

 

 

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የአዲስ ዓመት አባታዊ መልእክት !!!

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ የ፳፻፲፰ ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓል መግባትን አስመልክተው የእንኳን አደረሳችሁ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሰጥተዋል፣ የቅዱስነታቸው ሙሉ መልእክት የሚከተለው ነው።

ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ዓሠርቱ ወሰንመቱ ዓመተ ምሕረት፤

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ኣሜን!

  • በሀገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፣
  • ከሀገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ፣
  • የሀገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፣
  • በሕመም ምክንያት በየጸበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፣
  • እንዲሁም የሕግ ታራሚዎች ሆናችሁ በየማረሚያ ቤቱ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያት በሙሉ፣

አምላክነቱን ኣውቀን እንድናመልከው ዕድሜንና ዘመናትን የሚሰጠን እግዚብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺህ ዐሥራ ስምንት ዓመተ ምሕረት የርእሰ ዐውደ ዓመት በዓል አደረሰን አደረሳችሁ!

‹‹ወገብረ ኵሎ ኅቡረ ወኵሎ ኣሕዛበ እምአሐዱ ዕጓለ እመሕያው ከመ ይንበሩ ዲበ ኵሉ ገጸ ምድር፤ ወሠርዐ ዕድሜሁ ወዓመታቲሁ መጠነ ይነብሩ በዘየኃሥዎ ለእግዚአብሔር፤ እመ ይረክብዎ፤ ወያደምዕዎ፤ ወኢኮነ ርሑቀ እምኵልነ፡-

ምናልባትም እየመረመሩ ያገኙት እንደሆነ እግዚአብሔርን ይፈልጉ ዘንድ በምድር ሁሉ ላይ እንዲኖሩ የሰውን ወገኖች ሁሉ ከኣንድ ፈጠረ፤ የተወሰኑትንም ዘመኖችና ለሚኖሩበት ስፍራ ደረጃ መደባላቸው፤ ቢሆንም ከእያንዳንዳችን የራቀ ኣይደለም›› (የሐ. ሥራ. ፲፯÷፳፮)፤

ፈጣሬ ፍጥረታት እግዚአብሔር ትዕይንተ ዓለምንና በውስጡ የሚገኙ ፍጥረታትን የፈጠረ አምላክ ነው፤ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት የሚታዩና የማይታዩ ተብለው በጥቅል በቅዱስ መጽሓፍ ተገልጸዋል፤

የሰው ልጅ ከፍጥረታት መካከል ሆኖ ከኣንድ ወገን የተገኘ እንደሆነ በዚህ ጥቅስ ተጽፎአል፤

የሰው ልጅ ከፍጥረታት ሁሉ የተለየ ክብርና ደረጃ እንዳለው በቅዱስ መጽሓፍ በተደጋጋሚ ተገልጾአል፤ ልዩ የሚያደርገውም ከኣፈጣጠሩ ጀምሮ ነው፤

ሰው ልዩ ፍጡር መሆኑን ከሚገለጽባቸው መካከል እግዚአብሔር በሦስትነቱ “ሰውን በኣርኣያችንና በኣምሳላችን እንፍጠር” በሚል ልዩ ኣገላለጽ መፈጠሩ፣ ኣፈጣጠሩም በእግዚአሔር መልክና ኣምሳል መሆኑ፣ በእግዚአብሔር እፍታ ሕያው ነፍስ እንዲኖረው መደረጉ፣ በሥልጣንም የፍጥረታት ሁሉ የበላይ ሆኖ መሾሙ ከሌሎች ፍጥረታት ልዩ ያደርገዋል፡፡

ከዚህ አንጻር ሰው በዚህ ዓለምም ሆነ በወዲያኛው ዓለም ከፍጥረታት ሁሉ በላይ ነው፤ የሁሉም ገዥ ነው፤ በተለይም በዚህ ዓለም ከሰው በላይ ሆኖ የፍጡራን ገዥ የሆነ ፍጡር እንደሌለ ሁላችንም የምናየውና የምናውቀው ነው፤

በላይኛው ዓለምም ቢሆን መላእክትን ጨምሮ ሰማይና ምድርን ከነግሣንግሡ እየገዛ ያለው ሰው የሆነ ጌታ ነው፤ ምክንያቱም ኢየሱስ ክርስቶስ የፍጥረት ገዥ ነው፤ እሱ ሰብእናችንን በፍጹም ተዋሕዶ የተዋሓደ በመሆኑ ሰብእናችን በተዋሕዶተ ቃል ኣምላክ ሆኖ የፍጥረታት ሁሉ ገዥ ሆኖኣልና ነው፤

ቅዱስ መጽሓፍም “ወተኰነኑ ሎቱ መላእክት ወሥልጣናት ወኵሉ ኃይል፡- መላእክት፣ ሥልጠናትና ኃይል ሁሉ ተገዙለት” በማለት ይህንን ያረጋግጣል፤ ይህ እግዚአብሔር ለኛ ለሰዎች ያጐናጸፈን ግሩምና አስደናቂ ጸጋ ነው፤ ለዚህም ነው “ወሰብእ ይከብር እምኵሉ ፍጥረት፡- ሰው ከፍጥረት ሁሉ ይከብራል” ተብሎ የሚዘመረው፤

  • የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውንና ኢትዮጵያውያት!

እኛ ሰዎች የእግዚአብሔር ክብር መገለጫ ሆነን እንድንኖር በእግዚአብሔር ስንፈጠር በሕይወት እንድንኖር ነው፤ እግዚአብሔር በምድር ላይ በሕይወት ይኖሩ ዘንድ ሰውን ከኣንድ ፈጠረ የሚለው መጽሓፍ ቅዱሳዊ አስተምህሮም ይህንን ያመለክታል፤

ሰዎች በምድር ላይ በሕይወት እንዲኖሩ የተፈጠሩ ሆነው እያለ በሕይወት እንዳይኖሩ ማድረግ ከፈቃደ እግዚአብሔር ጋር መጋጨትን ያስከትላል፤በዘመናችን ዓለማችንን እየፈተነ ያለው ተቀዳሚ ፈተና ሰዎች በሕይወት እንዳይኖሩ የማድረግ ዝንባሌ ነው፤

እንደዚህ ዓይነቱ ዝንባሌ በዓለም ባይኖር ኖሮ በመቶ ሚሊዮኖች የሚቈጠሩ ድሆች ባሉበት ዓለም ለሰው ልጅ ሕይወት ማጥፊያ የሚሆን መሳሪያ ለማምረት ኁልቈ መሣፍርት የሌለው ገንዘብ አይወጣም ነበር፤

ይህ ክፉ የዓለም ዝንባሌ እንደ ክፋት ብቻ ሳይሆን እንደ ሞኝነትም የሚያሳይብን ነው፤ማንኛችንም ሰዎች ‹‹ሰው ማጥፋት ይሻላል ወይስ ማዳን›› ተብለን ብንጠየቅ መልሳችን ምን እንደሚሆን ይታወቃል፤

ነገር ግን ኣንፈጽመውም፣ ሞኝነት የሚያሰኘውም እዚህ ላይ ነው፤ የሚጠቅመንንና የመሰከርንለትን ትተን የሚጐዳንንና፣ ያልመሰከርንለትን እንፈጽማለንና ነው፤ ስለሆነም በሕይወት እንዲኖር የተፈጠረውን ሰው በሕይወት የመኖር መብቱን ከመንፈግ መቆጠብ የኣዲሱ ዓመት ትልቁ ኣጀንዳ ኣድርገን ብንወስድ ለሁላችንም ይበጀናልና እንቀበለው እንላለን፤

  • የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን! ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት!

ሰው በሕይወት እንዲኖር በእግዚአብሔር ሲፈጠር እግዚአብሔርን የሚፈልግበትና የሚያገኝበትን ዕድሜና ዘመንም እንደተሰጠው ከተጠቀሰው ክፍለ ንባብ እንገነዘባለን፤ መቼም እግዚአብሔር ሁሉን የፈጠረ በስራ ለስራ እንደሆነ የምንስተው ኣይሆንም፤

እግዚአብሔር ዕድሜና ዘመን ለሰዎች ሲሰጥ ሊሠራበት ነው፤ ስራውም መንፈሳዊና ዓለማዊ ነው፤ ተደምሮ ሲታይ ደግሞ ለሰው ጥቅም የሚውል ነው፤

እኛ ሰዎች በተሰጠን ዕድሜና ዘመን በመንፈሳዊው ሥራችን እግዚአብሔርን ፈልገን እንድናገኝ ተፈጥረናል፤ እሱን ማግኘት የማይቻል የሚመስለን ካለንም እሱ ከእያንዳንዳችን የራቀ አይደለም ተብለናልና በመንፈስ ከፈለግነው በመንፈስ እንደምናገኘው መጽሐፉ ያስረዳናል፤ ስለሆነም በተሰጠን ዘመን ይህንን ሥራ መሥራት ይኖርብናል፤

በሌላ በኩል ለኑሮኣችን የሚያስፈልገንን ፍጆታ በበቂ ሁኔታ እንድናገኝ ላባችንን ኣንጠፍጥፈን መስራት ይገባናል፤ ይህም ከሰራን ያለጥርጥር የምናገኘው ነው፤ ሁለቱም የጐደሉብን በኛ አስተሳሰብ፣ አሠራርና አጠቃቀም እንጂ እግዚአብሔር ሳይፈቅድልን ቀርቶ ወይም ነፍጎን አይደለም፤

እግዚአብሔር የሰጠን ምድር በልዩ ልዩ ሀብተ ጸጋ የተሞላች እንደሆነች፣ የምንረግጠው መሬትም ወደ ሀብት መቀየር እንደሚቻል የተረጋገጠ ነው፤

ነገር ግን እኛ በምንራመድበት በእግራችን ሥር ያለውን ሀብት ትተን በሩቅ ያለውን ስንመለከት ሁሉን ያጣን ሆነን በችግር ወድቀን እንገኛለን፤ በተለይም እኛ ኢትዮጵያውያን በአሁኑ ጊዜ እየተፈታተነን ያለው ይኸው የተሳሳተ እሳቤ ነው፤

ኢትዮጵያ የሁላችንም ኢትዮጵያውያን ኣድርገን በማመን በእኩልነት፣ በኣንድነትና በስምምነት ከመጠቀም ይልቅ ያ የኔ ነው ያም የኔ ነው በሚል ኣባባል ምን ያህል ዋጋ እየተከፈለ እንደሆነ እያየን ነው፤

ይህ ግለኝነት ያየለበት አስተሳሰብ ገታ አድርገን በእኩልነትና በአብሮነት የሚያሳድገንን አስተሳሰብ በእጅጉ ይጠቅመናል፤ ይህንንም የአዲሱን ዓመት ምርጥ እሳቤ ኣድርገን ብንወስድ የተሻለ መግባቢያ ሊሆን ይችላል፤ አዲሱ ዓመት በኣዲስ እሳቤ ካላጀብነው አዲስ ሊሆን አይችልምና ነው፤

ስለሆነም ኣዲሱን ዓመት መልካም በሆነ ኣዲስ ኣሳብ ፣እግዚአብሔርንና ሰውን በሚያገናኝ ቅዱስ ተግባር፣ በልማት፣ በሰላም፣ በፍቅር፣ በዕርቅና በስምምነት እንድንቀበለው ወቅታዊ ጥሪያችን ነው፤

በመጨረሻም፣ አዲሱ ዓመት ለሀገር ሰላምና ልማት፣ ለሕዝቦች ኣንድነትና ስምምነት እንደዚሁም ኣለመግባባትን በፍትሕና  በዕርቅ ለመፍታት ከልብ የምንተጋበት መልካም የስኬት ዘመን እንዲሆንልን እንጸልይ፣ በዚህም መላ ሕዝባችን ጠንክሮ እንዲሠራ ለመላ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ሁሉ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፤

እግዚአብሔር ኣምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝቦችዋን ይባርክ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ኣሜን

አባ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጰሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኲስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣

መስከረም ቀን ፳፻፲፰ .

አዲስ አበባኢትዮጵያ

በጎ መካሪ

የሰውን ልጅ የውድቀት ታሪክ ስንመለከት፣ የመጀመሪያው መንሥኤ የክፉ ምክር ውጤት እንደሆነ እንረዳለን። አባታችን አዳም የእግዚአብሔርን ሕግ ጠብቆ ለሰባት ዓመታት ያህል በገነት ቢኖርም፣ በሰይጣን ክፉ ምክር ተታሎ እግዚአብሔርን ያህል ጌታ ገነትን የመሰለ ቦታ አጥቷል። ይህ የሆነው በክፉ ምክር ምክንያት ነው። ዛሬም በዚህች ምድር፣ እንደ ጥንቱ ሁሉ፣ በማወቅም ሆነ ባለማወቅ በክፉ ምክር የሚያታልሉና ላልተገባ ነገር የሚዳርጉ ክፉ አማካሪዎች አይጠፉም።

በተቃራኒው ደግሞ ለበጎ ነገር የሚያነሣሱ፣ ትክክለኛውን መንገድ የሚያሳዩ፣ መርተው ወደ እግዚአብሔር የሚያደርሱ እንደ ሐዋርያው ፊልጶስ ያሉ መልካም አማካሪዎችና የልብ ወዳጆችም ብዙ ናቸው። (ዮሐ ፩፥፵፮-፶፩)

ነገረ ጳጕሜን

ኢትዮጵያ የራሷ ባህል፣ ታሪክና ሃይማኖት ያላት ይህንም በትውፊትና በመጽሐፍ ቅዱስ ይዛ የቆየች ሀገር ናት፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው ውሸት ቢናገርና በውሸታሞች መካከል ቢደገፍ ሌሎችም ውሸት ይናገሩ እንደማይባል ኢትዮጵያም ሌሎች በንጉሣቸው በጣዖታቸው ስም በየጊዜው እየቀያየሩ የዘመን ቆጠራን ቢያከብሩ የራሷን እውነት ትታ የእነርሱን ውሸት ትቀበል እንደማይባል መረዳት ይጠይቃል።