“እርሱም በሌሊት ወደ ጌታችን ኢየሱስ መጣ” (ዮሐ.፫፥፩)
የዓለምን ኃጢአት አስወግዶ፣ ኃጢአተኞችን በፍቅሩ መረብ አጥምዶ፣ በቃሉ ትምህርት ልቡናቸውን ማርኮ፣ በተአምራቱ ኅሊናቸውን ገዝቶ የፈጠራቸውን ሰዎች ወደ ሕይወት መንገድ ሊጠራ የመጣው መሲሕ በአይሁድ ቤት እንደ ባላጋራ ይታይ ነበር። ከዚያም አልፎ የአይሁድ አለቆች የሥልጣናቸውን በትር ተጠቅመው፣ ቀጥቅጠው፣ ከእግራቸው በታች አድርገው ሊገዙት ይሹ ነበር። ተግሣፁን እና የተአምራቱን ኃይል በአዩ ጊዜም በቅንዓት ተነሳሥተው ሊወግሩት ምክንያት ይፈልጉ ነበር። የባሕርይ አምላክነቱን ገንዘቡ እንደሆነ ሲነግራቸው፣ ራሱንም የእግዚአብሔር ልጅ እያለ ሲጠራ ሲሰሙ የቅን ተቆርቋሪ መሳይ ጠባያቸው እስከ መግደል ድረስ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል።
