‹‹እኔ ሰላማዊ ነኝ!›› (መዝ.፻፲፱፥፯)
ሰላም “ፍጹም ጤና፣ ዕረፍት፣ ዕርቅ፣ ፍቅር፣ አንድነት” ነው፡፡ (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት ገጽ ፰፻፷፮) አንድ ሰው ሰላም አለው ሲባል ጤነኛ እና ለሰዎች ፍቅር ያለው ኅብረትን አንድነትን የሚወድ ማለት ነው፡፡ ሰላም ለሰዎች ሁሉ አስፈላጊና መሠረታዊ ከሆኑ ነገሮችም አንዱ ነው፤ ማንኛውንም ነገር ለማከናወን ቅድሚያ ሰላም መሆን አስፈላጊ ነው፤ በሕይወታችን ደስተኛ ሆነን ለመኖር፣ አእምሮአችንን ከጭንቀት ነጻ ለማድረግ፣ ለሰዎች መልካም ነገርን ለማሰብ እኛም ደስተኛ እና ጤነኛ ለመሆን ሰላማዊ መሆን አለብን፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ለሮሜ ምእመናን በላከው መልእክቱ እንዲህ ይመክረናል፤ ‹‹…ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ…፡፡›› (ሮሜ ፲፪፥፲፰) ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ለመኖር እኛ የሰላም ሰዎች ነገሮችን በትዕግሥት የምናልፍ፣ ለሰዎች መልካም የምናስብ ልንሆን ይገባል፡፡
