ውድ የእግዚአብሔር ልጆች እንዴት አላችሁልን? ዘመነ አስተርእዮ ተብሎ በሚጠራው ወርኃ ጥር በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ብዙ በዓላትን አክብረናል፤ የጥምቀት፣ የቃና ዘገሊላ እንዲሁም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የዕረፍቷ መታሰቢያ ዓመታዊ ክብረ በዓልና የቅዱሳን መላእክት፣ የቅዱሳን አባቶቻችን፣ እናቶቻችንን በዓላት አክብረናል፡፡ እንዴት ነበር ልጆች! በጣም ልዩ ነበር አይደል? ታዲያ እነዚህ መንፈሳዊ በዓላት ወደፊትም እንዲከበሩ የእናንተ ጉልህ አስተዋጽኦ ያስፈልጋል፤ ምክንያቱም የነገዋን አገርና ቤተ ክርስቲያን የምትረከቡት እናንተ ስለሆናችሁ በዓሉን ከማክበራችሁ በተጓዳኝ ለምን እንደሚከበርና የአከባበበር ሥርዓቱን በመጠየቅ መረዳት አለባችሁ፡፡
ውድ የእግዚአብሔር ልጆች! ታዲያ ይህን አደራ ለመረከብ በመንፈሳዊውም፣ በዘመናዊው ትምህርት ጎበዞች መሆን አለባችሁ! በነገራችን ላይ ዘመናዊ ትምህርታችሁ የመንፈቀ ዓመት ፈተናችሁን እየተፈተናችሁ ያላችሁ፣ ለመፈተንም በዝግጅት ላይ ያላችሁም በርትታችሁ ማጥናት እንዳለባችሁ መዘንጋት የለበትም፡፡ ልጆች! ባለፈው ትምህርታችን በሥዕለ አድኅኖ ከተደረጉ ተአምራት ለአብነት ያህል ተመልክተን ነበር፤ ለዛሬ ደግሞ ቅዱሳን ሥዕላትን እንዴት አክብረን መያዝ እንዳለብን እንመለከታለን፡፡