የብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ህልፈተ ሕይወት

 

ያቆን ዘአማኑዔል አንተነህ

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ በቀድሞው አጠራር በሰሜንና በጌምድር ጠቅላይ ግዛት በአሁኑ ደቡብ ጎንደር ዞን አስተዳደር በደራ ወረዳ አፈሯ እናት በመካነ ሰማዕት ቅዱስ ገላውዴዎስ ደብር ልዩ ስሙ አባ ጉንቸ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ከአባታቸው ከአቶ ፈንታ ወልድዬ ከእናታቸው ከእሙሐይ ጥዑምነሽ አብተው በ፲፱፻፳፯ ዓ/ም ግንቦት ፳፱ ቀን ተወለዱ፡፡ብፁዕነታቸው በአባታቸውና በእናታቸው በሥርዓትና እንክብካቤ ካደጉ በኋላ ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በወላጆቻቸው መልካም ፈቃድ በተወለዱበት በመካነ ሰማዕት ቅዱስ ገላውዴዎስ ቤተ ክርስቲያን ከታዋቂው የድጓ መምህር ከየኔታ ኃይሉ ፊደል ቆጥረው ዳዊት ከደገሙ በኋላ ጾመ ድጓ፤ ውዳሴ ማርያም ዜማ እስከ አርያም ክስተት አጠናቀው ተመርዋል፡፡

የቁም ጽሑፍ ከአጎታቸው ከቀኝ ጌታ ዓለሙ ወልድዬ ተምረው ከሕጻንነታቸው ጀምሮ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ፀጋ የዲቁና ማዕረግ ከብጹዕ አቡነ ሚካኤል ደብረ ታቦር ከተማ ተቀብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ባላቸው የትምህርት ፍላጎት መሠረት ትምህርታቸውን በመቀጠል ቅኔ ጎጃም ሞጣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከመምህር ፀሐይ ተምረዋል፡፡ በተጨማሪም የቅኔ ትምህርታቸውን ለማጠናከር ወደ ሰሜን ሽዋ በመሄድ ምንታምር ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከየኔታ ኃይለ ጊዮርጊስ በመግባት ቅኔ በመማር ተቀኝተዋል፡፡ ዝማሬ መዋሥዕት ለመማር ወደ ደቡብ ጎንደር ተመልሰው ከየኔታ መርዓዊ ዙርአባ በመግባት የዝማሬ መዋሥዕት ትምህርታቸውን አጠናቀው በመምህርነትም ተመርቀዋል፡፡ ከዛም ወደ ደብረ ፅጌ ተመልሰው በመሄድ ከየኔታ ገብረ እግዚአብሔር ደብረ አባይ ቅዳሴ ተማሩ፡፡ ከመምህር ገብረ ሕይወት ሐዲሳት፤ ፍትሐ ነገስት አንድምታ ትርጓሜ፤ ዳዊት  አንድምታ ትርጓሜ፤ ውዳሴ ማርያም  አንድምታ ትርጓሜ፤ ባሕረ ሐሳብ  የኪዳንና ትምህርተ ኅቡአት አንድምታ ትርጓሜም ተምርዋል፡፡

በደብረ ፅጌ በነበሩበት ወቅት ትንቢተ ኢሳይያስና ትንቢተ ዳንኤል አንድምታ ትርጓሜና የቀሩትን መጻሕፍተ ብሉያት ተምረዋል፡፡ በደብረ ፅጌ ከመምህር ቀለመወርቅ አቋቋምም ለመማር ችለዋል፡፡ በወቅቱ ዘመናዊ ትምህርት ለመማር በነበራቸው ፍላጎት ኃይሌ ደጋጋ ከሚባል ትምህርት ቤት ገብተው ከ፩ኛ እስከ ፰ኛ ክፍል በደብረ ጽጌ ተምረዋል፡፡ ብፁዕነታቸው በመንፈሳዊ ትምህርት ቤት እያሉ ከአጎታቸው በተማሩት ቁም ጽሑፍ ተአምረ ማርያም ፤ ፍትሐ ነገስት፤ ፬ቱ ወንጌላትና መልእክተ ጳውሎስ እስከ ዮሐንስ ራእይ እንዲሁም ዚቅ በእጃቸው ጽፈዋል፡፡  ቤተ ክርስቲያንን በመንፈሳዊ አባትነት ለማገልገል መንፈሳዊ ሕይወታቸውን በማጠናከር ደብረ ሊባኖስ ገዳም ገቡ፡፡ አገልግሎታቸውንም በቅንነት፤ በታማኝነትና በትሕትና እየፈጸሙ ከገዳሙ ከቆዩ በኋላ በዛው ገዳም መንኩሰዋል፡፡ ስማቸውም መምህር አባ ኅሩይ ፈንታ እየተባሉ ይጠሩ ነበር፡፡ ከዚያም በመቀጠል ከብፁዕ አቡነ ሚካኤል ኤርትራዊ የቅስና ማዕርግ ተቀበሉ፡፡ብፁዕነታቸው ቤተ ክርስቲያኗን ለማገልገል ጽኑ ፍላጎት ስለነበራቸው ወደ አርባ ምንጭ በመሄድ የሀገረ ስብከቱ ስብከተ ወንጌል ክፍል ኃላፊ ሆነው በሀገረ ስብከቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የካህናት ማሰልጠኛ እንዲከፈት ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡ በወቅቱ ከነበሩት ሊቀ ጳጳስ መመሪያ እየተቀበሉ ማሰልጠኛው እንዲከፈትም ሆኗል፡፡ በዚሁ በአርባ ምንጭ ቆይታቸውም ከብፁዕ አቡነ ሰላማ የቁምስና ማዕርግ ተቀብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው በደብረ ሊባኖስ ገዳም ለመኖር ባላቸው ፍላጎት መሠረት ከአርባ ምንጭ ተመልሰው የደብረ ሊባኖስ ገዳም አንዱ አካል በሆነው በደብረ ጽጌ አገልግሎት እየሰጡ ለሕዝበ ክርስቲያኑ አባት በመሆን ስብከተ ወንጌል እያጠናከሩ ለብዙ ዓመታት ቆይተዋል፡፡

ከዚያም ለከፍተኛ የቤተ ክርስቲያን ማዕርግና አገልግሎት ታጭተው ወደ አዲስ አበባ ሄዱ፡፡ ጥር  ፲፫ ቀን በ፲፱፻፸፩ ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለሃይማኖት ፓትርያርክ ሊቀ ጳጳስ ዘኢትዮጵያ  ከተሸሙት ከ፲፫ቱ ሊቃነ ጳጳሳት መካከል አንዱ በመሆንም ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ተብለው በአንብሮተ ዕድ ቆጶስነት ማዕርግ ተቀብለዋል፡፡

የብፁዕነታቸው የ፵ ዓመታት የሥራ ዘመን

ከ፲፱፻፸፩ አዲስ ዓ.ም እስከ ፲፱፻፸፮ ዓ.ም ድረስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተሾሙ፡፡  ለመጀመሪያ ጊዜ ሥራ የጀመሩበት ሀገረ ስብከትም ነበር፡፡ በዚሁ ሀገረ ስብከት መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ በጅማ ሀገረ ስብከት ብፁዕነታቸው ተመድበው ሲሄዱ የካህናት ማሰልጠኛ የሌለ በመሆኑ ዲያቆናት፤ካህናት፤መምህራን ካላቸው እውቀት በተጨማሪ በሥልጠና ከዘመኑ ጋር ተዋሕደው ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲያገለግሉ ለማድረግ የካህናት ማሰልጠኛ ከፍተዋል፡፡ ከነበሩት አብያተ ክርስቲያናት በተጨማሪ ፶ አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናት በመትከል ሕዝቡን በማስተማርና በመምከር ቅዳሴ ቤታቸውን አክብረው ቤተ ክርስቲያን እንድትስፋፋ አድርገዋል፡፡

ከ፲፱፻፸፮ ዓ.ም እስከ ፲፱፻፸፰ ዓ.ም ድረስ የከፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተመድበው ሲሄዱም ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተባበር ተዋሕዶ ሃይማኖት እንዲስፋፋ ባላቸው ጠንካራ አቋም ፳፮ አብያተ ክርስቲያናትን በመትከል ቅዳሴ ቤታቸውንም አክብረዋል፡፡

ብፁዕነታቸው ከ፲፱፻፸፰ ዓ.ም እስከ ፲፱፻፹፩ ዓ.ም ድረስ ለ፬ ዓመታት የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊና የጠቅላይ ቤተ ክህነት ፍትሕ መንፈሳዊ የበላይ ጠባቂ ሆነው በተመደቡበት ወቅት በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገራት የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ማህበራዊ አገልግሎት እንዲጠናከርና እንዲስፋፋ በማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊነት ለ፬ ዓመታት ቤተ ክርስቲያኗን እያገለገሉ በቆዩበት ወቅት የጽሕፈት ቤቱን አደረጃጀት በሚገባ በመምራት የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በአግባቡ እንዲፈጸም በማድረግ ከብፁዕ ወቅዱስ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ፓትርያርክ የሚሰጡ መመሪያዎችን በመተግበርና በማስተግበር ለቤተ ክርስቲያናችን ትልቅ ሥራ ሰርተዋል፡፡

 ከ፲፱፻፹፩ ዓ.ም እስከ ፳፻፩ ዓ.ም ድረስ ለ፳ ዓመታት የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ሲመደቡ ሀገረ ስብከቱ አዲስ ከመሆኑ የተነሳ ለሊቀ ጳጳስ ማረፊያ (መንበረ ጵጵስና) የሌለው ከመሆኑም በላይ የሀገረ ስብከቱ አደረጃጀትም ገና ብዙ ሥራ ይጠይቅ ነበረ፡፡ በአዲስ መልክ ለማደራጀት ብዙ ድካም የሚጠይቅም ስለነበረ ብፁዕነታቸው ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ፀጋ ራሳቸው አቅደው ሀገረ ስብከቱ ምንም ገንዘብ ባይኖረውም መጀመሪያ መንበረ ጵጵስና መሠረት እንዳለበት ወሰኑ፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተባበር አብያተ ክርስቲያናቱም የተቻላቸውን እንዲያወጡና ሀገረ ስብከቱን እንዲያጠናክሩ በማስተማር ከአዲስ አበባና ከውጪ ሀገራት ገንዘብ በማሰባሰብ ለመጀመሪያ ጊዜ ፲ ክፍል ያለው መንበረ ጵጵስና፤  ፳፩ ክፍል ያለው የሀገረ ስብከት ቢሮ ፤ ፩ ንብረት ክፍል፤ ፩ አዳራሽ እና ፩ መጋዝን በማሠራት ሀገረ ስብከቱ እንዲጠናከር በማድረግ ሠራተኞችን አደራጀተው የተሠራውን መንበረ ጵጵስና ከተለያዩ ቦታ የተጠሩ እንግዶች በተገኙበት መርቀው ሀገረ ስብከቱ በይፋ የመንበረ ጵጵስና ቢሮ አንዲኖረው አድርገዋል፡፡

ብፁዕነታቸው ወደ ደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ተመድበው ሲሄዱ ጥንታዊና ታሪካዊ የሆነው የተክሌ ምስክር አቋቋም ጉባኤ ቤት ተዳክሞ ስለነበረ የምስክር አቋቋም ጉባኤ ቤቱን ከአካባቢው ተወላጆች ጋር በመመካከር በአዲስ መልክ በማቋቋም ጉባኤ ቤቱ እንዲጠናከር በማድርግና ዘመናዊ ጉባኤ ቤት በማሠራት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ (ዶክተር) አስመርቀው ለጉባኤ ቤቱ አድራሾች በጀት አስበጅተው እንዲጠናከር አድርገዋል፡፡ በ፳ ዓመታት የደቡብ ጎንደር ሊቀ ጵጵስና አገልግሎታቸው ውስጥ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተባበር ቦታ ከመንግሥት በማስፈቀድ ፮፻፹፭ አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናት በሀገረ ስብከቱ እንዲተከሉ በማድረግ የቤተ ክርስቲያን ማስፋፋት ሥራ ሠርተዋል፡፡ በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ተተክለው ከቆዩት አብያተ ክርስቲያናት መካከል በደብርነት ያሳደጓቸው ከ፭፻ በላይ ሲሆኑ ወደ አንድነታቸው እንዲመለሱ ያደረጓቸው ገዳማትም ፲፪ ናቸው፡፡ ከእነዚህም በዋናነት ከሚጠቀሱት መካከል ጣና ቂርቆስ፤ጣራ ገዳም እና ምጽሌ ፋሲለደስ በምሳሌነት ይጠቀሳሉ፡፡

ወደ ሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በቅዱስ ሲኖዶስ መልካም ፈቃድ ሲመደቡ የመጀመሪያ ሥራቸው የሀገረ ስብከቱን ሰላም ማስጠበቅ ነበር፡፡ ሠራተኛው ተግባብቶ ሥራውን እንዲሠራ የተለያዩ ሥራዎችንም ሠርተዋል፡፡ በዚህም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ «የሰላም አባት» የሚል የክብር ዋንጫ ተሸልመዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ሀገረ ስብከቱ በልማት ጠንክሮ አብያተ ክርስቲያናት ተስፋፍተው ማየት የሁልጊዜ ሕልማቸው ነው፡፡ሀገረ ስብከቱ የራሱ የሆነ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ኖሮት፤ ማኀበረ ካህናትንና ምእመናንን አሰባስቦ፤ ስለስብከተ ወንጌል መስፋፋት፤ ስለ ቤተ ክርስቲያን ልማት፤ ስለመልካም አስተዳደርና ሌሎችንም የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች ተሰባስቦ ለመወያየት የራሱ የሆነ የመሰብሰቢያ አዳራሽ አልነበረውም፡፡ ለዚህም በመንበረ ጵጵስናው ግቢ ከሚገኘው ቦታ በስተደቡብ በኩል ዘመናዊ ቢሮ ያለው ሁለገብ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ለመሥራት ራሳቸው አቅደው ሥራው እንዲጀመር በማድረግ የሕንፃ ማሰሪያ ገንዘቡን በተለያዩ ወረዳዎች ቆላ ደጋ ሳይሉ፤ አቀበት ቁልቁለት ሳይበግራቸው፤ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተባበር ገንዘብ በማሰባሰብ በተጨማሪም ከክህነትና ከንዋየ ቅድሳት መባረኪያ የሚገኘውን ገቢ በሙሉ ለሕንፃ ግንባታው ሥራ እንዲውል በመፍቀድ ከስድስት መቶ ሽህ ብር በላይ በብፁዕነታቸው ስም ተበርክቷል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ንብረት በሆነው በሐዋርያው ጳውሎስ ግቢ ባለ ፬ ፎቅ የገቢ ማስገኛ ሕንፃ ለመገንባትና ሌሎችንም ሥራዎች በግቢው ለመሥራት ዕቅድ አውጥተው የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል፡፡ በድርቡሽ ወቅት ከጠፉት ከ፵፬ቱ አብያተ ክርስቲያናት መካከል ፫ቱ ምዕት ቤተ ክርስቲያን በቦታው ለመመለስ ብፁዕነታቸው ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥተው አዲስ ኮሚቴ በማቋቋም በከፍተኛ ጥረት ቀደም ሲል ከነበረበት ቦታ ላይ የ፫ቱ ምዕት ቤተ ክርስቲያን መቃረቢያ እንዲሠራ በማድረግ ታቦተ ሕጉ እንዲገባና ቀድሰው ቅዳሴ ቤቱን አክብረው ታሪክ እንዲመለስ አድርገዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ከ፭፻ በላይ አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናት እንዲተክሉ በማድረግ ምእመናን እንዲበዙና ቤተ ክርስቲያን እንድትስፋፋ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርከተዋል፡፡ በላይ አርማጭሆ ወረዳ ትክል ድንጋይ ገዳም በበቅሎ በመሄድም አዲስ ገዳም እንዲመሠረት አድርገዋል፡፡ በተለይ ለሀገረ ስብከቱ ካቀዷቸው እቅዶች መካከል፤ በመንበረ ጵጵስናው ግቢ በስተምስራቅ በኩል የሀገረ ስብከቱ ንብረት የሆነ ፬ ክፍል ቤት ተሠርቶበት ከሚገኘው ቦታ ላይ ባለ ፬ ፎቅ ሕንፃ በመሥራት ለገቢ ማስገኛ አገልግሎት እንዲውል አቅደዋል፡፡ ይህን ሥራና ሌሎችንም ባቀዱት መሠረት ለማስፈጸም ደፋ ቀና ሲሉ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት የግልና የጎንደር ሪፈራል ሆስፒታል በሕክምና ሲረዱ ከቆዩ በኋላ ሕመሙ ሊሻላቸው ባለመቻሉ በተወለዱ በ፹፬ ዓመታቸው ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. ዐርፈዋል፡፡ የቀብር ሥነ ሥርዓታቸውም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የመንግሥት ተወካዮች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ሕዝበ ክርስቲያኑ በተገኙበት በመካነ ሰማዕት ቅዱስ ገላውዲዎስ ቤተ ክርስቲያን ግንቦት ፳ ይፈጸማል፡፡

ፊደል

ዲያቆን ዐቢይ ሙሉቀን

ፊደል፤ ፈደለ፤ ጻፈ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ሲሆን፤ ትርጉሙም የጽሕፈት ሁሉ መጀመሪያ፤ ምልክት፤ የመጽሐፍ ሁሉ መነሻ ማለት ነው፡፡

ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ፊደል የሚለውን ቃል ሲተረጉሙ በቁሙ ልዩ፤ምርጥ ዘር፤ ቀለም፤ ምልክት፤ አምሳል፤ የድምጽና የቃል መልክ ሥዕል፤ መግለጫ፤ ማስታወቂያ፤ ዛቲ ፊደል፤ ሆህያተ ፊደል፤ ወዘተ በማለት ያብራሩታል፡፡

ካሕሳይ ገብረ እግዚአብሔር ሊቀ ሥልጣናት ሀብተ ማርያም ወርቅነህን ጠቅሰው፡-

፩.ፊደል ማለት መጽሔተ አእምሮ ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ያለ ፊደል ማንበብም መጻፍም አይቻልምና የአእምሮ መገመቻ፤ የምሥጢር መመልከቻ ማለት ነው፡፡

፪. ፊደል ማለት ነቅዐ ጥበብ ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም የጥበብ ሁሉ መገኛ ፊደል ናትና፡፡

፫. ፊደል ማለት መራሔ ዕዉር ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም የሰውን ልጅ ሁሉ ከድንቁርና ጨለማ አውጥቶ ወደ ብርሃን ዕውቀት ይመራልና፡፡

፬. ፊደል ማለት ጸያሔ ፍኖት ማለት ነው፡፡ ምክንያቱም ድንቁርናን ጠርጎ አጽድቶ ከፍጹም ዕውቀት ያደርሳልና፡፡

፭. ፊደል ማለት ርዕሰ መጻሕፍት ማለት ነው ምክንያቱም የመጽሐፍ ሁሉ ራስ ፊደል ነውና፡፡

፮. ፊደል ማለት ጽሑፍ ማለት ነው፣ ፊደል ማለት ፍጡር፣ ወይም መፈጠሪያ ማለት ነው ብለው አስረድተዋል፡፡

በአጠቃላይ ፊደል ማለት በዚህ መልክ የሚገለጽ ሲሆን፤ እያንዳንዱ ፊደል ሀልዎተ እግዚአብሔርን፤ የሥነ ፍጥረትን ነገር ወዘተ የሚገልጽ ትርጉም አለው፡፡

የግእዝ ፊደል ቅደም ተከተል በአበገደ ወይስ በሀለሐመ የሚለው ሐሳብ ላይ በርካታ ሊቃውንት ጠንከር ያለ ክርክር ያነሳሉ፡፡ ለምሳሌ ካሕሳይ ገብረ እግዚአብሔር በሁለቱም ጎራ ካሉት እየጠቀሱ የምሁራኑንም ሐሳብ ካቀረቡ በኋላ የእርሳቸውንም ያቀርባሉ፡፡ የተወሰኑትን እንመልከት፡-

አለቃ ኪዳነ ወልድን፤ ደስታ ተክለ ወልድን፤ መምህር ዘሚካኤል ገብረ ኢየሱስን ጠቅሰው በአበገደ እንደሚጀምር ያስረዳሉ፡፡ እንደነዚህ ሊቃውንት አባባል ሌላው ቀርቶ አብዛኞቹ የፈጣሪ መጠሪያ ስሞች በአልፋው አ ነው የሚጀምሩት ይላሉ፡፡

ለምሳሌ እግዚአብሔር፣ አኽያ (/ያ/ አይጠብቅም)፤ አዶናይ፤ ኤልሻዳይ፤ አብ፤ አውሎግዮስ፤ አማኑኤል፤ ኤሉሄ፤ ወዘተ የመሳሰሉትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ዳዊትም እግዚአብሔርን ባመሰገነበት መዝሙሩ ከአሌፍ እስከ ታው ሲደርስ የተጠቀመው በአበገደ ነው በማለት በአበገደ የሚጀምረው ትክክል እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ ስለዚህ ቀዳሚውና ትክክለኛው በአበገደ የሚነበብ ሲሆን፤ ከአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከአባ ፍሬምናጦስ ከሣቴ ብርሃን ጀምሮ ግን በሀለሐመ ቅደም ተከተል እያገለገለ ይገኛል፡፡

በሁለተኛው ጎራ ደግሞ የመጀመሪያውና ትክክለኛው በሀለሐመ የሚነበበው ነው ይላሉ፡፡ ከጥንት ከጥዋቱ ጀምሮ ፊደላችን የሚጀምረው በሀለሐመ ቅደም ተከተል ነው፡፡ በአበገደ ነበር የሚሉት በልማድ የመጣ ከጽርዕና እብራይስጥ በተውሶ የተገኘ ሐሳብ ነው፡፡ በዚህም ጎራ ካሕሳይ የጠቀሷቸው ዶክተር ፍሥሓ ጽዮን ካሳና አስረስ የኔሰው ግንባር ቀደምቶች ናቸው፡፡ የነሱንም መሟገቻ እንዲህ በማለት ጠቅሰውታል፡፡

‹‹…በመሠረቱ በሕገ ጠባይዕም ከአ ሀ ይቀድማል፤ አንድ ሰው ሀ ካላለ አ ማለት አይችልም፡፡ ሀ ማለት አፍ መክፈት ማለት ነው፡፡ ጥንት በሳባውያን ወይም በአግዓዝያን ቋንቋ ሀ አፍ መክፈት ማለት ሲሆን በትርጓሜም ቢሆን ሀ ትልቅ ምሥጢር ያለው ፊደል ነው፡፡ ሀ ሀገር፤ ሀ ሀብት ከማለት ጋር በግእዙ ግስ “ሀለወ” አለ፤ ኖረ፤ ነበረ ማለት ነው፡፡ ይህ የዶክተር ፍሥሐ ጽዮን ሲሆን፤ የአስረስ የኔሰውም እንዲህ ቀርቧል፡፡

ትክክለኛው የግእዝ ፊደል ቅደም ተከተል ሀለሐመ ለመሆኑ ከዕብራይስጥና ጽርዕ የማይገናኝ ለመሆኑ፡-

፩.የግእዝ ጽሑፍ ከግራ ወደ ቀኝ መሆኑ፤

፪.የዕብራውያን ፊደል ደረጃ አምስት ሲሆን የግእዝ ግን ሰባት መሆኑ፤

፫. የግእዝ ፊደሎች ተራ ቊጥር ፳፮  መሆናቸው ነው፡፡

በአጠቃላይ የፊደላቱ ቅደም ተከተል በሁለቱም ቢሆን እያንዳንዱ ፊደል ትርጉም አለው፡፡ ትርጉሙ ነገረ እግዚአብሔርን ማለትም ዘለዓለማዊነቱን፤ ፈጣሪነቱን በአጠቃላይ ትምህርተ ሃይማኖትን የሚያስረዳ ነው፡፡ በዚህ እትም የምንመለከተው ከሀ እስከ ፐ የፊደላትን ትርጉም ከትምህርተ ሃይማኖት አንጻር ይሆናል፡፡

ሀ፡- ሀልዎቱ ለአብ እምቅድመ ዓለም፤ የአብ አኗኗር ከዓለም በፊት ነው፡፡

ለ፡- ለብሰ ሥጋ እምድንግል፤ አካላዊ ቃል ከድንግል ሥጋን ተዋሐደ፡፡

ሐ፡- ሐመ ወሞተ እግዚእነ፤ ጌታችን መከራን ተቀብሎ ሞተ፡፡

መ፡- መንክር ግብሩ ለእግዚአብሔር፤ የእግዚአብሔር ሥራው ድንቅ ነው፡፡

ሠ፡- ሠረቀ በሥጋ አምላክ፤ አምላክ በሥጋ ተገለጠ

ረ፡- ረግዓት ምድር በቃሉ፤ ምድር በቃሉ ረጋች ፡፡

ሰ፡- ሰብአ ኮነ እግዚእነ፤ ጌታችን ሰው ሆነ፡፡

ቀ፡- ቀዳሚሁ ቃል ውእቱ፤ በመጀመሪያ ቃል ነበረ፡፡

በ፡- በትሕትናሁ ወረደ እምሰማይ፤ ጌታችን በትሕትናው ከሰማይ ወረደ፡፡

ተ፡- ተሰብአ ወተሰገወ፤ ጌታችን ፈጽሞ ሰው ሆነ፡፡

ኀ፡- ኃያል እግዚአብሔር፤ እግዚአብሔር ኃያል ነው፡፡

ነ፡- ነሥአ ደዌነ ወጾረ ሕማመነ፤ ጌታችን ደዌያችንን ተቀበለ፣ ሕማማችንንም ተሸከመ፡፡

አ፡- አአኵቶ ወእሴብሖ ለእግዚአብሔር፤ እግዚአብሔርን ፈጽሜ አመሰግነዋለሁ፡፡

ከ፡- ከሃሊ እግዚአብሔር፤ እግዚአብሔር ቻይ ነው፡፡

ወ፡- ወረደ እምሰማይ እግዚእነ፤ ጌታችን ከሰማይ ወረደ፡፡

ዐ፡- ዐርገ ሰማያተ እግዚእነ፤ ጌታችን ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

ዘ፡- ዘኩሎ ይእኅዝ እግዚአብሔር፤ እግዚአብሔር ሁሉን የሚይዝ ነው፡፡

የ፡- የማነ እግዚአብሔር ገብረት ኃይለ፤ የእግዚአብሔር ሥልጣን ኃይልን አደረገች፡፡

ደ፡- ደመረ ሥጋነ ምስለ መለኮቱ፤ ሥጋችንን ከመለኮቱ ጋር አንድ አደረገ፡፡

ገ፡- ገብረ ሰማያተ በጥበቡ፤ ጌታ በጥበቡ ሰማያትን ፈጠረ/አዘጋጀ/፡፡

ጠ፡- ጠዐሙ ወታእምሩ ከመኄር እግዚአብሔር፤ እግዚአብሔር ቸር እንደሆነ ቅመሱና ዕወቁ፡፡

ጰ፡- ጰራቅሊጦስ መንፈሰ ጽድቅ፤ የእውነት መንፈስ ጰራቅሊጦስ ነው፡፡

ጸ፡- ጸጋ ወክብር ተውህበ ለነ፤ ጸጋና ክብር ለእኛ ተሰጠን፡፡

ፀ፡- ፀሐየ ጽድቅ እግዚአብሔር፤ እግዚአብሔር የእውነት ፀሐይ ነው፡፡

ፈ፡- ፈጠረ ሰማየ ወምድረ፤ ሰማይና ምድርን ፈጠረ፡፡

ፐ፡- ፓፓኤል ስሙ ለአምላክ፤ ፓፓኤል የአምላክ ስም ነው፡፡

ከሀ እስከ ፐ ያሉት ፊደላት እንዲህ ያለ ትርጉም ሲኖራቸው በአበገደ ቅደም ተከተልም እንዲሁ የየራሳቸው ትርጉም አላቸው፡፡ በአበገደው ቅደም ተከተል መጠሪያም ስላላቸው ያን መሠረት አድርጎ ትርጉማቸውንም መመልከት ይቻላል፡፡ ለምሳሌ አ አሌፍ የሚል መጠሪያ አለው፡፡ በመሆኑም አሌፍ ማለት አብ ፈጣሬ ኵሉ ዓለም፤ ዓለምን ሁሉ የፈጠረ አብ ነው ማለት ነው፡፡ ሌሎቹም በዚህ መልክ የየራሳቸው ትርጉም ያላቸው ሲሆን፤ በዋናነት መመልከት የፈለግነው የግእዝ ፊደላት እያንዳንዳቸው ትርጉም ያላቸውና ነገረ እግዚአብሔርን መግለጽ የሚችሉ መሆናቸውን ነው፡፡

ፊደላት ነገረ እግዚአብሔርን የሚገልጹ እንደመሆናቸው ሁሉ የመጻሕፍት ራስ ናቸው፡፡ መንፈሳውያን መጻሕፍት ሁሉ የእግዚአብሔር እስትንፋስ ናቸውና፡፡ እግዚአብሔር ለአበው ቃል በቃል፤ በራእይ እና በምሳሌ እየተገለጠ መልእክቱን እንዳስተላለፈ ሁሉ በመጽሐፍም ተናግሯል፡፡ «እስመ ይነግሮሙ ለሕዝቡ በመጽሐፍ፤ ለሕዝቡ በመጽሐፍ ይነግራቸዋልና» በማለት ልበ አምላክ ዳዊት እንደተናገረው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ለሕዝቡ መልእክቱን የሚናገርባቸው መጻሕፍት የሚጀምሩት ከፊደል ነው፡፡ በመሆኑም ፊደል የመጻሕፍት ሁሉ ራስም እግርም ናት፡፡ ከላይ ቢሉ ከግርጌ የምትገኝ እርሷ ናትና፡፡

እንግዲህ በዚህ እትም የሀለሐመ ፊደላትን ትርጉም ተመልክተናል በሚቀጥለው ደግሞ የአበገደን ፊደላት ትርጉም እንመለከታለን፡፡

ይቆየን

ምንጭ፤ ሐመር መጽሔት ፳፮ኛ ዓመት ቊጥር ፱

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጸሎት ተከፈተ!

በሕይወት ሳልለው

በዓመት ፪ ጊዜ የሚካሔደው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ግንቦት ፲፬ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. በጸሎት ተከፈተ! በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰባት ያለውን ችግር ለመፍታት ከአሁን ቀደም ጸሎተ ምሕላው በአግባቡ ያልተካሔደ መሆኑን በመግለጫቸው ያሳወቁት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት «በአክሱምና በሌሎች ጥቂት ገዳማትና አድባራት በዕንባና በልቅሶ የታጀበ ጸሎተ ምሕላ ቢደረግም፤ በርእሰ ከተማ ከአዲስ አበባ ጀምሮ በብዙ ቦታ ጸሎተ ምሕላው ተጠናክሮ እንዳልተካሄደ ለማወቅ ተችሏል» በማለት አስታውቀዋል፡፡

ሁላችንም ከእህልና ውኃ በመለየት መጸለይና ፈጣሪያችንን  መማጸን እንዳለብንም ቅዱስ ፓትርያርኩ አስገንዝበዋል፡፡ «ሁሉን ማድረግ የሚቻለው፤ ምንም ምን የሚሳነው የሌለ፤ እግዚአብሔር አምላካችን ብቻ ነውና፤ እሱ በመሠረተልን ስልት እጃችንን ወደ እግዚአብሔር እንድንዘረጋ፤ ሕዝቡም ሁሉ፤ ሀገሪቱም በአጠቃላይ እጆችዋን ወደ እግዚአብሔር እንድትዘረጋ፤ እኛም በየሀገረ ስብከታችን ተገኝተን፤ራሳችን መሪዎች ሆነን ጸሎተ ምሕላውን እንድንመራ፤ ትምህርተ ወንጌሉን እንድንሰጥ፤ቂም በቀል እንዲከስም፤ ይቅርታ እንዲያብብ፤ ያለማቋረጥ የሽምግልና ሥራን መሥራት ከሁላችን ይጠበቃል» ሲሉም መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

እንዲሁም አያይዘው በሀገራችን ውስጥ ያለውን ጦርነት በመንቀፍ፤ ቅዱስ ሲኖዶሱ ከሕዝቡ ጋር በመወያየት በሰላማዊ መንገድ ያሉትን ችግሮች ለመፍታት፤ ማንኛውንም አይነት ግጭት በመቃወምና አንድነትን በመፍጠር፤ ዘላቂ መፍትሔ ለማግኘት እንደሚጥር ገልጸዋል፡፡ ከዚህም በአሻገር ተፎካካሪ ፓርቲዎች ኃይለ ቃል ከመጠቀምና ስም ከማጥፋት እንዲታቀቡ በእግዚአብሔር ስም አሳስበዋል፡፡

በመጨረሻም የዚህ ዓመት የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ  በአቤቱታ ከተመለሱት የቤተ ክርስቲያኗ ታላላቅና ሁለት መለስተኛ ሕንጻዎች ማግስት በመከናወኑ ከሌላው ዓመት እንደሚለይ አስታውቀዋል፡፡

 

ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ያሬድ

ምስክርነት

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

በሐዋርያት ሥራ ምዕራፍ ፩ ቁጥር ፰ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ የተናገራቸው ቃል «በኢየሩሳሌምና በይሁዳ ሁሉ፤ በሰማርያ እስከ ምድር ዳርቻ ድረስም ምስክሮቼ ትሆኑኛላችሁ» የሚል ነው፡፡

ይሁዳ ኢየሩሳሌምን የሚያጠቃልል ግዛት ነው፤በኢየሩሳሌም የጌታችን ተአምር የተፈጸመበት፤ ብዙ ሰው ስለ እርሱ የሰማበትም ከተማ ነው፡፡ ከኢየሩሳሌም ይልቅ በይሁዳ ስለ ክርስቶስ የሚያውቁም የሚሰሙም ዝቅተኛ ናቸው፡፡ ሌላው ሰማርያ ነው፤ ሳምራውያን ከአይሁድ ጋር በሥርዓት አይተባበሩም፤ በመጽሐፍ ቁጥርም፤ በባህልም፤ በቤተ መቅደስም አይገናኙም፤ አንዱ አንዱን ይጸየፈዋል፡፡

እኛስ በሕይወታችን ውስጥ ለሃይማኖታችን እየመሰከርን ነው? ከሐዋርያት ሥራ እንደምናነበው ቅዱስ እስጢፋኖስ መከራ በተቀበለ ጊዜና በክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ላይ ሰይፍ በተመዘዘ ጊዜ ሁሉም ከኢየሩሳሌም እየወጡ ተጉዘዋል፡፡ ቤተሰቦቻቸውን፤ ቤታቸውንና ሀገራቸውን ትተው ወደ አሕዛብ ሀገር ሄዱ፤ በሔዱበት ቦታ ግን ወንጌል ተሰበከች፤ እነርሱ በሥጋ ቢጎዱ ቤተ ክርስቲያን ግን ተጠቅማለች ፡፡ የእኛ ወገኖች ቻይና፤ ዓረብ፤ አውሮፓና አፍሪካ ገብተዋል፤ ኢትዮጵያዊ ዘር ምናልባት ያልገባበት አንታርቲካ ብቻ ሊሆን ይችላል፤ እነርሱ በሄዱበት ሁሉ  ወንጌል አስተማሩ የሚል መጽሐፍ ተጽፎልናል? ዛሬ ግን ኢትዮጵያ ወንጌል ተሰበከ ሳይሆን የሚሰማው ተጣሉ፤ተበጣበጡ፤ይተማማሉ ይቀናናሉ የሚል ነው፤ ይህ ነው ወንጌል? ወንጌል የሰላም፤ የፍቅርና የደኅንነት ምንጭ ነው፤የብጥብጥ፤ የጦርነት ፤የጭቅጭቅ ግን አይደለም፡፡

ከሐዋርያት ዕጣ ፈንታ በገዛ እጁ በጠፋው በይሁዳ ምትክ ሰው ለመተካት ሐዋርያት ዕጣ ሲጣጣሉ «ከእኛ ጋር አብረው ከነበሩት ከእነዚህ ሰዎች አንዱ የትንሣኤው ምስክር ይሆን ዘንድ ይገባል» ብለዋል፤ በሐዋርያት ሥራ ፩፥፳፪፡፡ ሁለቱን ሰዎች ዕጣ የምንጥለው ለምንድን ነው? ለሚለው የሰጡት መልስ «ከሁለቱ አንዱ ከእኛ ጋር የትንሣኤው ምስክር እንዲሆን» የሚል ነው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ተወለደ፤ አስተማረ፤ ተያዘ፤ ተገረፈ፤ ተሰቀለ፤ሞተ፤ተቀበረ፤ተነሣ የሚለው ቃል የትንሣኤው ምስክር ነው፡፡

እኛስ የማን ምስክር ነን? ብዙዎቻችን ጥሩ የፊልም ተዋናዮች ነን፤ ስለ እነርሱ ተናገሩ ብንባል የምንናገረውን ስለ ቅዱስ ጳውሎስ ተርኩ ብንባል አንተርክም፡፡ ስለ አንድ ዘፋኝ የምንናገረውን ያህል ስለ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፤ ስለ ቅዱስ ያሬድ ተናገሩ ብንባል አንናገርም፤ የፊልም ተዋናዮቹንና የዘፋኞቹን ፎቶ ደረታችን ላይ ለጥፈን እየተንጠባረርን የምንሄደውን ያህል የቅዱሳንን ሥዕል በቤታችን ለመስቀል እናፍራለን፡፡ ታዲያ የማን ምስክሮች ነን? ዛሬ ኢትዮጵያውያንን በየቦታው እያጨቃጨቀን ያለው ስለ ምግብ ነው? ይበላል ወይስ አይበላም፤ ያገድፋል ወይስ አያገድፍም፤ የማያገድፍ ነገር በዚህ ምድር ላይ መተው ብቻ ነው፡፡

የሁላችንም ምስክርነት የትንሣኤው መሆን አለበት፤ ለምን የትንሣኤው የሚለውን መረጡ? ኢየሱስ ክርስቶስ ሙስና መቃብርን ድል አድርጎ መነሣቱንና በሞት ላይ፤ በዲያብሎስ ላይ ኀይል እንዳለው፤ የተረዳነው በትንሣኤው ስለሆነ ነው፡፡ የትንሣኤው ምስክር ነው ወይስ ነገ የምንቃጠለውን ቃጠሎ ዛሬ እየመሰከርን ነው?‹‹እነሆ ቀን እንደ እሳት እየነደደ ይመጣል፤ ትዕቢተኞችና ኃጢአትን የሚሠሩ ሁሉ ገለባ ይሆናሉ፤ የሚመጣውም ቀን ያቃጥላቸዋል፤ ሚል.፬፥፩፡፡

ምስክሮቼ ትሆናላችሁ የሚለው ስም ለመጀመሪያ ጊዜ የተሰጠው ለሐዋርያት ነው፤ በኋላ ግን ሃይማኖታቸውን የገለጡ፤ ያስፋፉ፤ የመሰከሩ፤ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ለአሕዛብ የሰበኩ ሁሉ ምስክሮች ተብለዋል፡፡ ጌታም በወንጌል፤ «በሰው ፊት የሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤ በሰው ፊት የሚክደኝን ግን እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እክደዋለሁ» ብሏል፤ ማቴ. ፲፥፴፪፡፡ ዛሬ ስለ ምስክሮች ስንሰማ በአእምሮአችን የሚመጡት እነዚህ ስለ እምነት ብለው በፈቃዳቸው መከራን መቀበል የቻሉ ምስክሮች ናቸው፡፡

ከትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ ያሉት ዕለታት ስያሜያቸውና ታሪካዊ አመጣጣቸው

ዲያቆን ተመስገን ዘገየ

ከትንሣኤ ሌሊት ፩ ሰዓት ጀምሮ እስከ ዳግም ትንሣኤ ያለው ሳምንት የፉሲካ ምሥጢር የተገለጠበት፤ ከግብፅ ወደ ምድረርስት ከሲኦል ወደ ገነት መሻገርን የሚያመላክት ሳምንት ነው። ለፉሲካ የሚታረደውም በግ ፉሲካ ይባላል (ዘዳ. ፲፮÷፪:፭÷፮)፤ ፉሲካ ማለት ደግሞ ማለፍ ነው፤ ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበትም ሳምንት የፉሲካ ሳምንት ነበር፤ (ሉቃ. ፳፪፥፲፬-፲፮፤ ዮሐ. ፲፰፥፴፰-፵)።

እርሱም ንጹሕ የእግዚአብሔር በግ ሆኖ ደሙን ስላፈሰሰልን ፉሲካችን ክርስቶስ ተባለ፤ ብሉይ ደግሞ የሐዲስ አምሳል ነው። ይኸውም ሙሴ የእስራኤልን ሕዝብ ባሕረ ኤርትራን ካሻገራቸው በኋላ ወደ ምድረ ርስት፤ ነፍሳት ደግሞ በክርስቶስ መሪነት ከሲኦል ወደ ገነት መግባታቸውን የሚገልጽ ነው፡፡ ዕለቱም ሙሴ የወልደ እግዚአብሔር፤ በትረ ሙሴ የመስቀል ምሳሌ፤ግብፅ የሲኦል፤ የገሃነመ እሳት፤ የፈርዖን የዲያብሎስ፤ ሠራዊቱ የሠራዊተ ዲያብሎስ፤ እስራኤል የምእመናንና ባሕረ ኤርትራ የባሕረ ሲኦል ምሳሌ ነው፡፡

ሰኞማዕዶት (ፀአተ ሲኦል)

ማዕዶት የቃሉ ትርጓሜ መሻገር ሲሆን፤ በዚህ ቀን ቤተ ክርስቲያን ነፍሳት በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከሐሳር ወደ ክብር፤ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሲኦል ወደ ገነት መሻገራቸውንና ፉሲካችን ክርስቶስ መሆኑን ታስባለች።

ማክሰኞቶማስ

ቅዱስ ቶማስ በጦር የተወጋ ጎኑን፤ በቀኖት የተቸነከረው እጁንና እግሩን ካላየሁ አላምንም በማለቱ ክርስቶስም «ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤እጅህንም አምጣና ወደ ጎኔ አግባ፤ እመን እንጂ ተጠራጣሪ አትሁን» ብሎታል። ቶማስም «ጌታዬ አምላኬም»፤ ብሎ በመለሰ ጊዜ ጌታችን ኢየሱስም «ስለ አየኸኝ አመንህን? ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓንስ ናቸው» አለው (ዮሐ ፳፥፳፯-፳፱)፤ ቶማስ የጌታን ፍቅር ተገንዝቦ ትንሣኤውን ስላመነ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዕለቱን ቶማስ ብላ ታስበዋለች።

ዲዲሞስ የተባለ ከአሥራ አንዱ ደቀ መዛሙር አንዱ ቶማስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዝግ ቤት ገብቶ «ሰላም ለሁላችሁ ይሁን» ባላቸው ጊዜ ከእርሳቸው ጋራ አልነበረም»። ከ፲፪ቱ ሐዋርያት አንዱ (ማቴ. ፲፥፪-፫) ቶማስ በአራማይክ ዲዲሞስ በግሪክ መንታ ማለት ነው፤ (ዮሐ. ፳፥፳፬)፡፡ ቶማስ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ በፋርስና በሕንድ ወንጌልን እንዳስተማረ ይነገራል። ለቶማስ ጎኑን እንዲዳስስ የፈቀደው ለሌሎችም ቅዱሳን ሐዋርያት የተቸነከረውን እጅና እግሩን ያሳየው ካህናት ሥጋውና ደሙን እንዲፈትቱ ነው፤ ዮሐንስም በእጃችን ዳሰስነው ብሏል፤ (ሉቃ. ፳፬፥፴፱)፡፡

ለማርያም መግደላዊት ግን የተነሣ ዕለት አትንኪኝ ማለቱ ለሴቶች ሥጋውን ደሙን መፈተት አልተፈቀደም ሲል ነው ብለው ሊቃውንት ያትታሉ፤ «አትንኪኝ፤ ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሂጅና፡- ወደ አባቴ÷ ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬ÷ ወደ አምላካችሁም አርጋለሁ አለ ብለሽ ንገሪአቸው» አላት፤ (ዮሐ. ፳፥፲፯)። ገቦ መለኮቱን የዳሰሰች እጁ በሕይወት ትኖራለች፤ በሕንድ ሀገር ከታቦት ጋር በመንበር ላይ ትኖራለች። በየዓመቱ በእመቤታችን በዓል በአስተርእዮ ሊያጥኑ ሲገቡ የሚሾመውን ወጥታ ቀኝ እጁን ትይዘዋለች፤ ዓመት አገልግሎ ያርፋል።

ረቡዕአልዓዛር

አልዓዛር ክርስቶስ ያስነሣው የማርያምና የማርታ ወንድም ነው፤ የስሙም ትርጓሜ እግዚአብሔር ረድቷል ማለት ነው፤ (ዮሐ. ፲፩፥፯-፵፰)፤ አልዓዛር የሞተው መጋቢት ፲፯ ነበር፡፡ እህቶቹም ክርስቶስ እንዲመጣ መልእክት ልከውበት ነበር፤ ክርስቶስ ግን በ፬ኛው ቀን ማለትም  መጋቢት ፳ መጥቶ ከሞት አስነሥቶታል፤(ዮሐ.፲፩፥፵፬)፡፡ ፋሲካውንም በወዳጁ በአልዓዛር ቤት ያከብር ዘንድ  ከቀደ መዛሙርቱ ጴጥሮስንና ዮሐንስን አስቀድሞ ላከ፤ ከዚያም በአልዓዛር ቤት ሆኖ የሐዲስ ኪዳንን ሥርዓት ምሥጢረ ቁርባንን ሰርቶ ለደቀ መዛሙርቱ አሳያቸው፤ አልዓዛር ከተነሣ በኋላ በሐዋርያት ኤጲስ ቆጶስነት ተሸሞ ፵ ዓመት አገልግሎ ግንቦት ፳፯ ቀን ዐርፏል (ስንክሳር ግንቦት ፳፯)፡፡

አዳም ሐሙስ

አዳም የመጀመሪያ ሰውና የሰው ሁሉ አባት ነው፤ በ፮ኛው ቀን የተፈጠረ የሰው ሁሉ ምንጭ ስለሆነ የሰው ዘር ሁሉ ከእርሱ ተገኝቷል፡፡ በዚህ ዕለት ለአዳም የተሰጠው የተስፋ ቃል ስለመፈጸሙ፤ (ዘፍ. ፫÷፲፭) አዳም ከነልጆቹ በክርስቶስ ሞትና ትንሣኤ ነጻ ስለመውጣቱ ይታሰብበታል፡፡ ክርስቶስ በተነሳበት በአምስተኛው ቀን ሐሙስ  አዳም ይባላል፤ ጌታችን አዳምን ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ  አድንሃለሁ ብሎ  ቃል ገብቶለት  እንደነበር በቀሌምንጦስ ተጽፏል፡፡

አዳምና ሔዋን በገነት ፯ ዓመት ከቆዩ በኋላ ትእዛዙን በመተላለፋቸው ከኤደን ገነት አስወጣቸው (ኩፋ.፬፥፲፮፤ዘፍ.፫፥፳፫) «ብዙ ተባዙ» ያለው ቃል እንዳይቀር በምድር ላይ ወርደው ልጆችን ወለዱ ይላል፡፡ የተወለዱትም ልጆችም በቁጥር ፷ እንደሆኑ (፩መቃ. ፳፰፥፮) የተወለዱት ልጆች ደጎችና ክፉዎች እንደ ነበሩ በአቤልና በቃየል ታውቋል፤ (ዘፍ. ፬፥፰)፤ አዳም በዚህ ዓለም ፱፻፴ ዓመት ኑሮ ቅድመ ልደተ ክርስቶስ በ፵፻፭፻፸ ሚያዚያ ፮ ዐርፏል፡፡

ዐርብቤተ ክርስቲያን

ዐርብ የእግዚአብሔር ቅድስት ማደሪያ በሆነችው ቤተ ክርስቲያን ተሰይማለች፤ ይህም ሁሉም ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን የተፈጸመባት ዕለት በመሆኗ ነው፤ ዕለተ ዐርብ፤ የሥራ መከተቻ፤ ምዕራብና መግቢያ በሚሉት ስያሜዎችም ትጠራለች፡፡

በዕለቱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል ያደረገውን ተአምር በመስቀሉ ድኅነትን እንዳሳየ፤ በቀራንዮ የሕንጻዋ መሠረት እንደተተከለላትና ሥጋ መለኮት እንደተቆረሰላት፤ ልጆቿን ከማሕፀነ ዮርዳኖስና ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ የምትወልድበት ማየ ገቦ እንደፈሰሰላት ተገልጾባታል፤(ኤፍ.፪፥፲፱፤ራዕ.፩፥፮-፰)፡፡

ቅዳሜቅዱሳት አንስት

ቅዳሜ ቅዱሳት አንስት ተብሎ ይጠራል፤ ይህም ስያሜ በስቅለት ዕለት በልቅሶና በዋይታ የሸኙትን፤(ሉቃ. ፳፫፥፳፯) በዕለተ ትንሣኤ ሽቱና አበባ ይዘው ወደ መቃብር የገሰገሱትን፤ ከሁሉም ቀድሞ ጌታችን በዕለተ ሰንበት ተነሥቶ ለተገለጸላቸው ማርያም መግደላዊት፤ የታናሹ ያዕቆብ እና የዮሳ እናት ማርያም፤ የዘብዴዎስም የልጆቹ እናት ሰሎሜንም መታሰቢያ ለማድረግ ነው፤«ከሳንምንቱ በመጀመሪያዩቱ ቀን ያዘጋጁትን ሽቶ ይዘው እጅግ ማልደው ወደ መቃብሩ ሄዱ፤ሌሎች ሴቶችም አብረዋቸው ነበሩ (ሉቃ. ፳፬ ፥ ፩ )፡፡

እሑድዳግም ትንሣኤ

«ያም ከሳምንቱ የመጀመሪያው ቀን በመሸ ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ አይሁድን ስለ ፈሩ ተሰብስበው የነበሩት ቤት ደጁ ተቆልፎ ሳለ ጌታችን ኢየሱስ መጥቶ በመካከላቸው ቆመና÷«ሰላም ለእናንተ ይሁን» አላቸው፤ ማቴ.፳፥፲፱፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከደቀ መዛሙርቱ ተሰውሮ ከሰነበተ በኋላ በዕለተ እሑድ በዝግ ቤት እንዳሉ ዳግም ተገለጸላቸው፤ስለዚህም ዳግም ትንሣኤ ተባለ፡፡

(ምንጭ:-መዝሙረ ማኅሌት ወቅዳሴ፤ ሥርዓተ አምልኮ ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ፤ የዮሐንስ ወንጌል አንድምታ፤ ምዕ. ፳፥፳፬)