ማእከሉ ያስገነባው G+5 ሕንፃ ተመረቀ

                                             

                                                                                                                                                              በጎንደር ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን ጎንደር ማእከል ያስገነባው  G+5  ዘመናዊ ሕንፃ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች እና የማኀበሩ አባላት በተገኙበት ግንቦት18 ቀን2010 ዓ.ም ተመረቀ፡፡

የጎንደር ማእከል አገልግሎቱን  የጀመረው  በቤተ ክርስቲያን ግቢ በሚገኙ መቃበር ቤቶች እና በግለሰቦች ቤት ሲሆን አገልግሎቱ እየጠነከረ ሲሔድ  ግን ጎንደር  ከተማ ቀበሌ 17 የጣውላ ቤት በመከራየት አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ ከ1994-1999 ዓ.ም ሰፋ ያለ ቤት በመከራየት አገልግሎቱን  ሲያከናውን ቆይቶ  አባጃሌ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አካባቢ  ሰፊ ቤት በመከራየት አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡ከ1999 ዓ.ም በኋላ አዲሱ ሕንፃ ከተገነባበት ቦታ ላይ ቆርቆሮ በቆርቆሮ ቢሮ እና አዳራሽ በመሥራት ከኪራይ ተላቆ አገልግሎቱን ለማስቀጠል በቅቷል፡፡

ማእከሉ ለቢሮ የሚሆንና  ሌሎች መንፈሳዊ አገልግሎት  የሚሰጥበት ቦታ የሌለው መሆኑን የሚገልጥ በቀን 06/05/1996 ዓ.ም እና 03/01/1997 ዓ.ም ለሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በመጻፍ ማዘጋጃ ቤት  ቦታ እንዲሰጠው የጠየቀ ሲሆን ሀገረ ስብከቱም ለጥያቄውን አፋጣኝ ምላሽ በመስጠት ለጎንደር ማዘጋጃ ቤት የቀበሌ ቤት እንዲሰጠው አሳውቋል፡፡በቀን 19/02/1997 ዓ.ም በድጋሜ በተጻፈ ደብዳቤ በአነስተኛ ኪራይ  የቀበሌ ቤት እንዲሰጠው የጎንደር ከተማ  ማዘጋጃ ቤትን ቢጠይቅም መልስ ሳያገኝ ቆይቷል ፡፡

የማእከሉ አዲስ ሕንፃ የተገነባበትን 2000 ካሬ ሜትር ቦታ በሊዝ እንዲሰጣው ጥያቄ አቅርቦ በ02/10/1998 ዓ.ም በ290.40(ሁለት መቶ ዘጠና ብር ከ40 ሣ) በመክፈል  ቦታውን ተረከበ፡፡ ክርስቲን ሻዮ የተባሉ በጎ አድራጊ 20,000.00 ዩሮ ድጋፍ ስላደረጉ የመጀመሪያው ክፍያ ተፈጸመ፡፡

በ02/13/1999 ዓ.ም የዋናው ማእከል ሙያና ማኀበራዊ አገልግሎት ማሰተባበሪያ በበኩሉ 100,000.00 ብር የሚገመት ዲዛይን በነፃ ሠርቷል፡፡ የመሠረት ድንጋይ የተጣለው በ2000 ዓ.ም በአሁኑ ሰዓት ደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ በሆኑት ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ሲሆን ግንባታው በይፋ በ23/04/2000 ዓ.ም ፈቃድ አግኝቶ ወደ ሥራ ገብቷል፡፡ሕንፃው ያረፈበት ቦታ 370 ካሬ ሜትር  ነው፡፡

በምረቃው ዕለት  ትምህርተ ወንጌል በየኔታ ዲበ ኩሉ ግርማይ የመካነ ስብሐት ልደታ ለማርያም  ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ፣ መዝሙር በማእከሉ መዘምራን፣ሪፖርት በማእከሉ ሰብሳቢ በአቶ ጌትነት መኳንንት የቀረበ ሲሆን  በመጨረሻም ለሕንፃው ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረጉ በጎ አድራጊ ግለሰቦች የምስጋና የምስክር ወረቀት ተሰጥቷል፡፡አቶ ጌትነት በሪፖርታቸው ለሕንፃው ማስፈጸሚያ  በጎንደር  ከተማ የሚገኙ  የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች የቀን ሥራ ተቀጥረው የሚገኙትን ገንዘብ ለሕንፃ ግንባታው ይሰጡ እንደነበር ተናግረዋል፡፡

የጎንደር  ማእከል  አባላትም  የወር ደመወዛቸውን  ለሕንፃው ግንባታ እንደሰጡ  የገለጡት  ሰብሳቢው  የማእከሉ አባላትና የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች  ጊዜያቸውን፣ ገንዘባቸውን፣ ጉልበታቸውን አበርክተዋል፡፡ በጎ አድራጊ ግለሰቦችም የሚቻላቸውን ሁሉ አድርገዋል ብለዋል፡፡፡፡

 

የቀዳሜ አድባራት አበራ ጊዮርጊስ የቅኔ ጉባኤ ቤት የእሳት ቃጠሎ ደረሰበት

 

የእሳት ቃጠሎ ደረሰበትየቅኔ ጉባኤ ቤቱ

                                                       ዲ.ን ዘአማኑኤል አንተነህ               

በጎንደር ከተማ የሚገኘው የቀዳሜ አድባራት አበራ ጊዮርጊስ ግንቦት 11 ቀን 2010 ዓ.ም ከቀኑ ሰባት ሰዓት የእሳት ቃጠሎ ደረሰበት፡፡ የጉባኤ ቤቱ አለቃ መምህር ናሆም አዝመራው የእሳት ቃጠሎ የተቀሰቀው በኤሌክትሪክ ምክንያት መሆኑን አስረድተው በአደጋው ምክንያት ከ120 በላይ ጎጆዎች መቃጠላቸውንና ፤ ከ30 በላይ ጎጆዎች መፈራረሳቸውን ገልጸዋል፡፡

በቃጠሎው ሳቢያ የተማሪ ጎጆዎች እና ልብሶቻቸው፣የጉባኤ  ቤቱ የማኅበር ቤት ሙሉ ለሙሉ ወድሟል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ እንደ  ግስ፣ ዝክረ ቃል፣ መዳልው፣ ዳዊት፣ ሰዓታት፣ ሃይማኖተ አበው፣ ስንክሳር፣ አገባብ፣ መጽሐፍ ቅዱስ፣ መጽሐፈ ታሪክ፣ አንድምታ ወንጌል እና የመሳሰሉት በርካታ መጻሕፍት ተቃጥለዋል፡፡

በአደጋው ምክንያት በርካታ ተማሪዎች ያለ መጠለያ የቀሩ ሲሆን በማኅበረ ቅዱሳን ጎንደር ማእከል ባሠራው ዐሥር የማደሪያ ክፍሎች፣በመቃብር ቤት፣በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በሰንበቴ ቤት በጊዜያዊነት  የአብነት ተማሪዎቹ  ተጠልለው ይገኛሉ፡፡

“የተማሪ ቤት መቃጠል የነገይቱን ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች መፍለቂያ ጠፋ ማለት መሆኑን ያስረዱት የጉባኤ ቤቱ መምህር ወላዴ አእላፍ ጌዴዎን አበበ “ሁሉም ክርስቲያን የተቃጠለውን የቅኔ ጉባኤ ቤት ወደነበረበት ለመመለስ የበኩሉን አስተዋጽኦ ሊያደርግ ይገባል”ብለዋል፡፡

በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በጎንደር ከተማ ከሚገኙ የቅኔ ጉባኤ ቤቶች የቀዳሜ አድባራት አበራ ጊዮርጊስ የቅኔ ጉባኤ ቤት አንዱ ሲሆን በጉባኤ ቤቱ ከ500 በላይ ተማሪዎች እና ከ20 በላይ አስነጋሪዎች መኖራቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

የሊቃውንቱ መፍለቂያ እንዲህ እንደምታዩት ሆነ

በእሳት የወደመው ጉባኤ ቤቱ

 

 

እምቤተ ክህነት ወመንግሥት ዘኀረይዋ ይእቲኬ ማርያም ድንግል

           በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትኩረት አድርጋ የምታከብራቸው በርካታ የቅዱሳን በዓላት አሉ፡፡ የእመቤታችን ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም በዓላትም በቤተ ክርስቲያኗ ሰፊ ቦታ ተሰጥተው የሚከበሩ ናቸው፡፡ ለአብነት ያህልም በየዓመቱ ግንቦት አንድ ቀን የሚከበረውን የቅድስት ድንግል ማርያምን የልደት በዓል መመልከት ይቻላል፡፡ ለሃይማኖታችን መሠረት፣ ለክርስትናችን ዋስትና፣ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ስንቅ የሆኑት ቅዱሳት መጻሕፍት እንደሚያስረዱን እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ግንቦት 1 ቀን በ15 ዓ.ዓ  ቅድመ ልደተ ክርስቶስ መወለዷን እንረዳለን፡፡ ይሁን እንጂ አንዳንድ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲን፣ ቅዱሳት መጻሕፍትና ሌሎች አብያተ ክርስቲያናት የእመቤታችን ልደት መስከረም 10 በማለት ያከብራሉ፡፡ ይህንንም የተኣምረ ማርያም መቅድም «ወቦ እለ ይቤሉ አመ ዐሡሩ ለመስከረም ልደታ፤ መስከረም 10 ቀን ልደቷ ነው የሚሉ አሉ» ይላል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግን በዐዋጅ ግንቦት 1 ቀን ታከብረዋለች፡፡ ወላጆችዋም ኢያቄምና ሐና ይባላሉ፡፡ አባትዋ ኢያቄም ከቤተ ይሁዳ (ከይሁዳ ነገድ) ሲሆን፣ እናትዋ ሐና ከቤተ ሌዊ (ከነገደ ሌዊ) ናት፡፡ የተወለደችበት ሀገርም ናዝሬት ይባላል፡፡

       የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ግን በዐዋጅ ግንቦት 1 ቀን ታከብረዋለች፡፡ ወላጆችዋም ኢያቄምና ሐና ይባላሉ፡፡ አባትዋ ኢያቄም ከቤተ ይሁዳ (ከይሁዳ ነገድ) ሲሆን፣ እናትዋ ሐና ከቤተ ሌዊ (ከነገደ ሌዊ) ናት፡፡ የተወለደችበት ሀገርም ናዝሬት ይባላል፡፡የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የዘር ሐረግ ነገደ ይሁዳና ነገደ ሌዊ መሆኑን በተለያዩ ቅዱሳት መጻሕፍት ተመዝግቦ እናገኘዋለን፡፡ ለአብነት ያህልም ሊቁ ቅዱስ ያሬድ «ትወጽእ በትር እምሥርዎ እሴይ ወየዐርግ ጽጌ ይእቲ በትር አምሳለ ማርያም ቅድስት ይእቲ ወጽጌ ዘይወጽእ እምኔሃ አምሳሉ ለወልድ……..” በትር ከእሤይ ሥር ትወጣለች አበባም ከእርስዋ ይወጣል፤ በትር የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ናት» በማለት እመቤታችን ከዳዊት ዘር መሆንዋን ይገልጻል፡፡ ይህንንንም ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ድርሰቱ « አንቲ ውእቱ ዘመድ ዘእምሥርወ ዳዊት፤ ከዳዊት ዘር የተገኘሽ ዘመድ አንቺ ነሽ» ሲል ያጠነክረዋል፡፡ «በሩካቤ ዘበሕግ እለ ወለድዋ እምቤተ ክህነት ወመንግሥት ዘኀረይዋ ይእቲኬ ማርም ድንግል፤ በሕጋዊ ሩካቤ የወለዱአት ከቤተ ክህነት እና ከቤተ መንግሥት የመረጡአት ድንግል ማርም ናት» በማለት ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ከቤተ መንግሥትና ከቤተ ክህነት መመረጧን ይገልጻል፡፡ (ድጓ ዘነሐሴ)
ወደ ጥንተ ነገራችን ስንመለስ፣ ኢያቄምና ሐና በመጀመሪያ ልጅ መውለድ ተስኖአቸው ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት ልጆች ባሏቸው ሰዎች ሁሉ መንፈሳዊ ቅንዓት ያድርባቸው ነበር፡፡ በመዝሙረ ዳዊት «ልጆች የእግዚአብሔር ስጦታዎች ናቸው» (መዝ. 126÷3) ተብሎ ስለተጻፈ ልጅን መመኘት መንፈሳዊ ፍላጎት ነውና ኢያቄምና ሐናም አጥብቀው ይሹ ነበር፡፡ የኢያቄምና የሐና ልጅ ማጣት ግን እጅና እግራቸውን አጣጥፈው እንዲቀመጡ አላደረጋቸውም፡፡ ይልቁንም «አንኳኩ ይከፈትላችኋል» እንደተባለው እግዚአብሔር አምላክ በቸርነቱ በልጅ ይጎበኛቸው ዘንድ አጥብቀው ይጸልዩ ነበር እንጂ፡፡ (አንዳንድ ሰዎች በትዳር ሕይወታቸው ልጅ መውለድ በተሳናቸው ጊዜ እንደ ሐናና ኢያቄም በጸሎት ከመትጋት ይልቅ መከነች መከነ ብዬ ላልክድሽ ላልክድህ ተባብለው የገነቡትን ትዳር ወደማፍረስ መሄዳቸው የሐናንና የኢያቄምን መንፈሳዊ የትዳር ተሞክሮ አለመቅሰም ነው፡፡) ጸሎታቸውም የሚጦረን፣ የሚንከባከበን፣ ርስታችንን የሚወርስልን ልጅ ስጠን ሳይሆን፣ ሰውንና እግዚአብሔርን የሚያስደስት፣ ለቤተ እግዚአብሔር የሚገባ፣ አንተን የሚስደስት ልጅ ስጠን የሚል ነበር፡፡ በዚህም ምክንያት በልጅ ቢጎበኛቸው ልጃቸውን ለእግዚአብሔር እንደሚሰጡ ተሳሉ፡፡
ከዚህም በኋላ የለመኑትን የማይነሳ፣ የነገሩትን የማይረሳው ልዑል እግዚአብሔር የሐናን ማኅጸን በጽንስ ጎበኘው፡፡ ይህም የሆነው ነሐሴ ሰባት ቀን ነው፡፡ ከዚያም ግንቦት አንድ ቀን፣ እሙ ለፀሐየ ጽድቅ፣ መድኃኒታ ለሔዋን፣ የኖኅ ቃልኪዳን፣ የአዳም ተስፋ፣ ላዘኑ መጽናኛቸው፣ ለተሰደዱ ተስፋቸው፣ ለተራቡ ምግባቸው፣ ለታረዙ ልብሳቸው፣ ንጽሕት በድንግልና ሥጋ ወሕሊና የሆነች እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተወለደች፡፡ጽንሰቷም ሆነ ልደቷ ርኩሰት የሌለበት፣ በቅድስና የተመላ፣ በሕግ የጸና ነው፡፡ «ኦ ድንግል አኮ በፍትወተ ደነስ ዘተጸነስኪ አላ በሩካቤ ዘበሕግ እምሐና ወኢያቄም ተወለድኪ፤ ድንግል ሆይ በጢአት ፍትወት (በዝሙት በርኩሰት) የተፀነስሽ አይደለሽም፤ በሕግ፣ በሩካቤ፣ በሥርዓት ከሐናና ከኢያቄም ተወለድሽ እንጅ» እንዳለ (አባ ሕርያቆስ፤ ቅዳሴ ማርያም

         የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም መወለድ ለጊዜው ደስታው ለኢያቄምና ሐና ቢሆንም በመጨረሻ ግን ለዓለም ነው፡፡ እመቤታችን በመጀመሪያ ለኢያቄምና ሐና ብትሰጥም ፍጻሜው ግን የዓለም ስጦታ ናት፡፡ ምክንያቱም የድኅነታችን ዘውድ ናትና፡፡ (ቅዳሴ ማርያም)
አዳምና ሔዋን ትእዛዘ እግዚአብሔርን ተላልፈው የሞት ሞት በተፈረደባቸው ጊዜ እግዚአብሔር ተስፋ የሰጣቸው ከልጅ ልጃቸው ተወልዶ እንደሚያድናቸው ነው፡፡ ይህም በብሉይ ኪዳን በትንቢት ሲነገር ነበር፡፡ በትንቢተ ኢሳይያስ ላይ በትር ከእሴይ ግንድ ይወጣል ተብሎ የተነገረው ትንቢትም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የዓለምን መድኅን ለመውለድ እንደምትወለድ የሚገልጽ ነበር፡፡ (ኢሳ. 11÷1) ከላይ እንደተገለጸው የአዳም የልጅ ልጅ የተባለችው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፡፡ ይህንን ቃል ኪዳን ሲሰጣቸው አዳምና ሔዋን በተስፋ መኖር ጀምረዋል፡፡ በኋላም ግንቦት አንድ ቀን እመቤታችን ስትወለድ የአዳም የድኅነት ቀን መድረሱ ታውቋል፡፡ ለዚህም ነው አባ ሕርቆስ «አንቲ ውእቱ ተስፋሁ ለአዳም አመ ይሰደድ እምገነት፤ ከገነት በተሰደደ ጊዜ የአዳም ተስፋው አንቺ ነሽ» (ቅዳሴ ማርያም) ያለው፡፡ ከገነት ተባሮ በረከቱን ሲገፈፍ የተሰጠው ቃል በእርሷ መወለድ እንደሚድን ነበርና፡፡ እግዚአብሔር አዳምን ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ ሲለው፣ ለድኅነቱ ምክንያት የሆነች የልጅ ልጁን መወለድ ተስፋ ያደርግ ነበርና፣ ምክንያተ ድኂን ቅድስት ድንግል ማርያም መወለዷ ለአዳምና ለልጆቹ ትልቅ ክብርና የብርሃን ተስፋ ነው፡፡
የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም መወለድ ለአዳም መዳን ምክንያት እንደሆነ ሁሉ ለሰው ልጆች፣ እንዲሁም በኃጢአት ለተወሰደው ዓለም ሁሉ ከኃጢአቱ ነጽቶ በሥራው ገነት መንግሥተ ሰማያትን ይወርስ ዘንድ የሚችልበት መንገድ የተጠረገበት ነው፡፡ ምክንያቱም በመጀመሪያ ቀዳማዊ አዳምና ቀዳሚት ሔዋን በሠሩት ጥፋት የመጣው ሞት የተሻረው በዳግሚት ሔዋን (በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም) መወለድና ዳግማዊ አዳምን (መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን) በመውለድ ነውና፡፡ ሔዋን ያመጣችው መርገም በእመቤታችን ቀርቷል፤ አዳም ያመጣው ሞት በክርስቶስ ድል ተደርጓልና፡፡የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ልደት በድቅድቅ ጨለማ የነበረው ዓለም ብርሃንን ያየበት ነው፡፡ ዓለም ለአምስት ሺህ አምስት መቶ ዘመን ያህል በዲያብሎስ ቁራኝነት፣ በኃጢአት ሞት ጨለማነት፣ ተይዞ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይህን ጨለማ ለማስወገድም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ኆኅተ ምሥራቅ ሆና፣ በእርሷም ፀሓየ ጽድቅ ኢየሱስ ክርስቶስ ወጥቶ ለዓለም ሁሉ ብርሃን ሆኖአል፡፡ «ብርሃን ዘበአማን ዘያበርህ ለኩሉ ሰብእ ለእለ ይነብሩ ውስተ ዓለም፤ በዓለም ውስጥ ለሚኖሩ ሰዎች ሁሉ የሚያበራ እውነተኛ ብርሃን እርሱ ነው» እንዲል ቅዱስ ኤፍሬም በሰኞ ውዳሴ ማርያም፡፡
እኛም ብርሃንን ወልዳልናለችና እሙ ለብርሃን፣ የዓለም ፀሓይ ከእርሷ ተገኝቷልናልና ኆኅተ ምሥራቅ፣ ለመዳናችን ምክንያት ናትና ምክንያተ ድኂን፣ የአዳም ተስፋው ናትና ተስፋሁ ለአዳም እያልን የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ልደት እናከብራለን፡፡የበጎ ነገር ሁሉ ጠላት የሆነው ዲያብሎስ ክብረ ድንግል ማርያምን ደብቆ ለማስቀረት ደፋ ቀና ቢልም፣ እኛ ግን ብርሃንን አይተንባታልና ልደቷን እንደ አባቶቻችን በማኅሌት፣ በቅዳሴና በሌሎች አገልግሎቶች እያከበርን «ዮም ፍስሓ ኮነ በእንተ ልደታ ለማርያም፤ በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም ልደት አማካኝነት ዛሬ በዓለም ሁሉ ደስታ ሆኗል» እያልን እንዘምራለን፡፡ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በረከትና ረድኤት ይክፈለን አሜን
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ማኅበረ ቅዱሳን 26ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን ሊያከብር ነው

በማኅበረ ቅዱሳን የሕዝብ ግንኙነት እና የትብብር አገልግሎት ማስተባበሪያ

ሚያዝያ ፳፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን 26ኛ ዓመት የምሥረታ በዓሉን በመንፈሳዊ ሥርዓት ሊያከብር መኾኑ ተገለጠ፡፡

ማኅበሩ ሚያዝያ 28 ቀን 2010 ዓ.ም፣ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ አዲስ አበባ ከተማ ከመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም አጠገብ በሚገኘው ሕንጻ፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በዓለ ልደትና ማኅበሩ የተመሠረተበትን 26ኛ ዓመት የምሥረታ ቀን በመንፈሳዊ ሥርዓት እንደሚያከብር ከማኅበሩ የሕዝብ ግንኙነትና የትብብር አግልግሎት ማስተባበርያ የተገኘው መረጃ ያመላክታል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የሕዝብ ግንኙነትና የትብብር አገልግሎት ማስተባበሪያ ሓላፊ፣ አቶ ደመላሽ አሰፋ እንዳስታወቁት በማኅበረ ቅዱሳን የምሥረታ ቀን መታሰቢያ በዓል አከባበር ላይ፣ የቤተ ክርስቲያን አባቶች፣ ተጋባዥ እንግዶችን ጨምሮ በርካታ ሕዝበ ክርስቲያንና የማኅበሩ አባላት ይገኛሉ ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በዕለቱ የእንኳን በደኅና መጣችሁ መልእክት፣ እንደዚሁም ትምህርተ ወንጌል እና መዝሙር እንደሚቀርብ አቶ ደመላሽ አስታውቀዋል፡፡ የዕለቱ መርሐ ግብርም ከቀኑ 11፡00 ሰዓት እንደሚጠናቀቅ ሓላፊው አያይዘው ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን፣ ከቅዱስ ሲኖዶስ በተሰጠው ሕጋዊ ዕውቅና መሠረት ላለፉት 26 ዓመታት በርካታ መንፈሳዊውያን ተግባራትን ለቤተ ክርስቲያን ሲያከናውን መቆየቱና አሁንም አገልግሎት በመስጠት ላይ መኾኑ ይታወቃል፡፡