ክብረ ቅዱሳን እና ዐሥሩ መዓርጋት

በሊቀ ማእምራን ደጉ ዓለም ካሣ

ሚያዝያ ፳፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹ቅዱሳን› ማለት ‹የተቀደሱ፣ የከበሩ፣ የተመሰገኑ፣ የተለዩ፣ የተመረጡ፣ ንጹሐን የኾኑ፣ የጠሩ› ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር ቅዱስ ነውና የጌትነቱ መገለጫ የኾኑ ዂሉ ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ ቅዱሳን፣ በሃይማኖት ጸንተው፣ በምግባር ጐልምሰው፣ የሥጋ ምኞታቸውን ትተው ሲገኙ የቅድስና ባለቤት ቅዱስ እግዚአብሔር እነርሱን (ቅዱሳንን) መሣሪያ አድርጐ ኀይሉንና ሥልጣኑን የገለጸባቸው ማኅደረ እግዚአብሔር (የእግዚአብሔር ማደሪያ) ናቸው፡፡ ቅዱሳን እንደ መላእክት ውሉደ እግዚአብሔር (የእግዚአብሔር ልጆች) ይባላሉ (ኢዮ. ፩፥፮፤ ሮሜ. ፰፥፲፬)፡፡

ቅዱሳን፣ በግብር መላእክትን መስለው፣ ኾነው የእግዚአብሔርን ፈቃድ ፈጽመው በመገኘታቸውና ከዚህ ዓለም ፈቃድ በመለየታቸው ቅዱሳን፤ የፈጣሪያቸውን መንግሥት ወራሾች በመኾናቸው ደግሞ ‹ውሉደ እግዚአብሔር› (የእግዚአብሔር ልጆች) ይባላሉ፡፡ በሌላም ቃል ‹ውሉደ ብርሃን› (የብርሃን ልጆች) ተብለው ይጠራሉ (ሉቃ. ፲፮፥፰)፡፡ ‹ውሉደ ሕይወት› (የሕይወት ልጆች) ይባላሉ፤ ሞትንና የሞት ከተማ የኾነውን ይህን ዓለም ንቀውታልና፡፡ በክብር ተነሥተው ዳግመኛ ሊሞቱ የማይገባቸው ናቸውና (ሉቃ. ፳፥፴)፡፡ ቅዱሳን፣ ‹ውሉደ ጥምቅት› (የጥምቀት ልጆች) ተብለዋል፤ ሀብተ ወልድናን (የእግዚአብሔርን ልጅነት)፣ ስመ ክርስትናን ተጐናጽፈዋልና፡፡ ‹ውሉደ መንግሥትም› ተብለዋል፤ የመንግሥተ ሰማያት ባለቤቶች ናቸውና፡፡

ቅዱሳን፣ በጸጋ እግዚአብሔር በመበልጸጋቸው ወይም የእግዚአብሔር የምሕረቱ ዓይኖች በመኾናቸው ‹አዕይንተ እግዚአብሔር› (የእግዚአብሔር ዓይኖች) ተብለዋል (መዝ. ፴፫፥፲፭)፡፡ ልመናቸው፣ ጾማቸው፣ ምጽዋታቸው ዂሉ የተወደደ መሥዋዕት ነው፡፡ ቅዱሳን በዓላማቸው ጾምን ግብዣ (ድግስ)፣ ለቅሶን ደስታ፣ ደስታን ሐዘን አድርገው በመኖራቸው ይህ ተለዋዋጭ ዓለም በየጊዜው የሚያቀርብላቸው መርዶ በእነርሱ ዘንድ ዋጋ የለውም፡፡ ዓለምም ለእነርሱ የሚያቀርበው ዓለማዊ የምኞት ስጦታ እንደ ኢ ምንት የተናቀ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ገጸ መዓቱ ወደ ዓለማውያን ሰነፎች እንደ ኾነ ዂሉ ገጸ ምሕረቱ ደግሞ ወደ ቅዱሳን ነው፡፡ የእግዚአብሔር ፈቃድና ቸርነት መገለጫዎችም ናቸውና፡፡ ስለዚህ አማላጅነታቸው፣ ጸሎታቸው ጠቃሚ ነው፡፡

‹‹አፍቅርዎ ለእግዚአብሔር ኵልክሙ ጻድቃኑ እስመ ጽድቀ የኀሥሥ እግዚአብሔር፤ ቅዱሳን፣ እውነትን ይዛችሁ ትሕትናን ተላብሳችሁ እግዚአብሔርን ውደዱት፡፡ እግዚአብሐር እውነትን፣ ትሕትናን ይወዳልና፤›› (መዝ. ፴፥፳፫) ተብሎ እንደ ተጻፈ፣ የቅዱሳን ፍሬ ትሕትና ነው፡፡ በዓይነ ሕሊናቸው ፈጣሪያቸውን፣ በዓይነ ሥጋቸው የእነርሱን ምንነት እንደዚሁም የዓለምን ከንቱነት ይመለከታሉ፡፡ ፍሬ የያዘ ተክል ዂሉ ቁልቁል የተደፋ መኾኑ ትሕትናን ያስተምራል፡፡ ይህም የጻድቃን ምሳሌ ነው፡፡ በፈሪሃ እግዚአብሔር ልቡ የተሰበረ፣ እሱርነቱን (ማንነቱን፣ ምንነቱን) የመረመረ ሰው በዓይነ ሕሊናው የፈጣሪውን ቸርነት፣ በዓይነ ሥጋው የራሱን ውድቀት ይመለከታል፡፡

ይህ አመለካከት ለጸጋ እግዚአብሔርና ለፍሬ ክብር ያደርሰዋል፡፡ በመቅረዝ ላይ ያለች መብራት መሰወር እንዳይቻላት፣ የመቅረዙ ከፍታ እንደሚገልጻት በተራራ ላይ ያለች ቤትም ለእይታ እንደማትሰወር፣ የተራራው ከፍታ እንደሚገልጻት በጥበበ እግዚአብሔር ከብረው በጸጋ እግዚአብሔር ተውበው የሚኖሩ ቅዱሳን ጻድቃንም ደረጃ በደረጃ መዓርጋትን አልፈው ከመለኮት ባሕርይ ተካፍለው የተአምራት መገለጫ ይኾናሉ፡፡ ‹‹መንክር እግዚአብሔር በላዕለ ቅዱሳኒሁ፤ እግዚአብሔር በቅዱሳኑ በወዳጆቹ አድሮ የሚሠራው ሥራ ድንቅ ነው፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መዝ. ፷፯፥፴፭፤ ፪ኛ ጴጥ. ፩፥፫)፡፡

ቅዱሳን፣ ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ጸጋ ሙታንን ማስነሣት፣ ዕውራንን ማብራት፣ በአጠቃላይ ድንቅ ድንቅ ተአምራትን ማድረግ የዘወትር (የዂልጊዜ) ተግባራቸው ነው፡፡ የጸጋና የክብር ባለቤቶች ኾነዋልና በዓለም ላይ ሳሉ የሚመጣባቸውን ፈተና ዂሉ ተቋቁመው የጸጋ መቅረዞች ይኾናሉ፡፡ በዚህ ጸጋቸውም የአናብስቱን አፍ ዘጉ (ዳን. ፯፥፩-፰)፡፡ ውኃውን ወደ ኋላው መለሱ (ዘፀ. ፲፬፥፳፪)፡፡ ዝናም እንዳይሰጥ ሰማይን ለጎሙ (፩ኛ ነገ. ፲፯፥፩፤ ያዕ. ፭፥፲፯)፡፡ ነበልባለ እሳትን አበረዱ (ዳን. ፫፥፩-፲፫)፡፡ የቅዱሳን ወዳጅ እግዚአብሔር አምላካችን ሥጋዊ ሀገረ ተድላን ጥለው፣ ኃላፊ ጠፊ ምድራዊ ምቾታቸውን ንቀው ጸጋውን ከሚጠባበቁት ጋር ዂሉ አብሮ ይኖራል፡፡ ትዕግሥትን የጠዋት ቍርስ፣ የቀን ምሳ፣ የማታ እራት አድርገው የሚመገቧትን ዂሉ ማደሪያ ቤተ መቅደሱ ያደርጋቸዋል፡፡

ቅዱሳን በዚህ ዓለም ይጠበቡበታል፤ ወጥተው ወርደው ሰውነታቸውን ከስስት፣ ኃጢአት ጠብቀው ለወዲያኛው ዓለም ደግሞ በትዕግሥት ደጅ ይጠኑበታል፡፡ ‹‹ፈሪሃ እግዚአብሔር ትፍሥሕተ ልብ ውእቱ ወይሁብ ሐሤተ ወያስተፌሥሕ ወያነውኅ መዋዕለ ሕይወት ለፈራሄ እግዚአብሔር ይሤኒ ደኃሪቱ ወይትባረክ ዕለተ ሞቱ፤ እግዚአብሔርን መፍራት የልብ ደስታ ነው፡፡ ፍጹም የሥጋና የነፍስን ደስታ ይሰጣል፤ በሕይወትም ያኖራል፡፡ እግዚአብሔርን የሚፈራ ሰው ፍጻሜው ያምርለታል፡፡ እንደ ኢዮብ ከደዌው ተፈውሶ ልጅ የልጅ ልጅ አይቶ ይሞታል፤›› ተብሎ እንደ ተጻፈው ይህ ዂሉ በረከት የቅዱሳን ፍሬ ነው (ኢዮብ ፴፩፥፲፮)፡፡

ቅዱሳን በሚሠሩት ሥራ በያዙት ቅን መንገድ፣ ኢዮባዊ ትዕግሥት፣ አብርሃማዊ ኂሩት፣ ይስሐቃዊ ፈቃደኝነት፣ ያዕቆባዊ ቅን አገልግሎት፣ ዮሴፋዊ ኀዳጌ በቀልነት ሙሴአዊ ለወገን ተቆርቋሪነት እየጨመሩ በመኖራቸው የፈጣሪአቸው ኃይልና ጌትነት እንደዚሁም የድንቅ ሥራው መገለጫዎች ይኾናሉ፡፡ በጸጋ ላይ ጸጋ እየተጨመረላቸው ወደ ዐሥሩ መዓርጋት ይወጣሉ፡፡ ማዕረጋቸውንም ከዚህ ላይ ይናገሩታል፡፡ ዐሥሩ መዓርጋት የሚባሉት በሦስት ይከፈላሉ፡፡ ሦስቱ የንጽሐ ሥጋ መዓርጋት፣ አራቱ የንጽሐ ነፍስ መዓርጋት፣ እና ሦስቱ የንጽሐ ልቡና መዓርጋት ናቸው፡፡

  • ሦስቱ የንጽሐ ሥጋ መዓርጋት የሚባሉት፡- ጽማዌ፣ ልባዌ እና ጣዕመ ዝማሬ ናቸው፡፡
  • አራቱ የንጽሐ ነፍስ መዓርጋት፡- አንብዕ፣ ኵነኔ፣ ፍቅር እና ሑሰት ናቸው፡፡
  • ሦስቱ የንጽሐ ልቡና መዓርጋት ደግሞ፡- ንጻሬ መላእክት፣ ተሰጥሞ እና ከዊነ እሳት (ነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ) ናቸው፡፡ በጠቅላላው ዐሥር ይኾናሉ፡፡

ሀ. የንጽሐ ሥጋ መዓርጋት

፩ኛ መዓርገ ጽማዌ

ይህ የመጀመሪያው መዓርግ ነው፡፡ በዚህ መዓርግ ማስተዋል፣ ውስጣዊ ትዕግሥት፣ ውስጣዊ ትሕትና፣ ውስጣዊ የራስ ሚዛንን ይዞ ማሰላሰል ይጀምራል፡፡ ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ሲደርሱ እግዚአብሔርን ብቻ መዘከር ይችሉ ዘንድ የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ ከማውራት ይከለከላሉ፡፡ በዚህ መዓርግ ላይ ሳሉ መላእክት ሲወጡና ሲወርዱ ያየሉ፡፡ ነገር ግን ለምን እንደሚወጡና እንደሚወርዱ አያውቁም፡፡ ዮሐንስ ሐፂር የሰፋውን ስፌት ገበያ ላይ ለመሸጥ ተቀምጦ እያለ በተመስጦ ቅዱስ ሚካኤልንና ቅዱስ ገብርኤልን እንደዚሁም ሌሎች መላእክትን በየመዓርጋቸው እያየ ያደንቅ ነበር፡፡ ስፌቱን የሚገዛ ሰው ቁሞ ‹‹እንቅቡ ዋጋው ስንት ነው?›› ብሎ ሲጠይቀው እርሱ የሚያየውን የሚያይ መስሎት ‹‹ሚካኤልኑ የዓቢ ወሚመ ገብርኤል ሚካኤል፤ ይበልጣል ወይስ ገብርኤል?›› ብሎ በአንክሮ ጠየቀው፡፡ ሰውየውም ‹‹ይኼስ እብድ ነው›› ብሎ ትቶት ሔዷል፡፡

፪ኛ መዓርገ ልባዌ

መዓርገ ልባዌ፣ ማስተዋል፤ ልብ ማድረግ፤ አሰሙኝ እንጂ ስሙኝ አለማለት፤ ልማር እንጂ ላስተምር አለማለት፤ የተነገረው ትንቢትና ተግሣፅ ምዕዳን ዂሉ የራሱ እንደ ኾኑ መገመት፤ መመርመር፤ ዓይነ ሥጋን ከመጽሐፍ፣ ከሥነ ፍጥረት፣ ዓይነ ነፍስን ከምሥጢር ማዋል ነው፡፡ እንደዚሁም የእግዚአብሔርን ቸርነት ማድነቅ፣ ለሰው ልጅ ያደረገዉን ውለታ ማሰላሰል፣ ከሰማየ ሰማያት መውረዱን፣ ከሰው መወለዱን፣ በገዳም መጾሙን፣ መገረፉን፣ ሥጋውን መቍረሱን፣ ደሙን ማፍሰሱን፣ መሰቀሉን፣ መሞቱን፣ መቀበሩን፣ መነሣቱን፣ እያሰቡ ልብን በፍቅረ እግዚአብሔር፤ አንደበትን በመንፈሳዊ ሕይወት መስበር፤ ዓላማን በገጸ መስቀል (ትዕግሥት) መትከል የመሳሰሉት ናቸው፡፡

፫ኛ መዓርገ ጣዕመ ዝማሬ

ከዚህ ደረጃ ሲደረስ አንደበትን ከንባብ፣ ልቡናን ከምሥጢር ማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ሲደርሱ አንደበታቸው ዝም ቢልም በልባቸው ግን ዝም አይሉም፡፡ ከአፍ እስትንፋስ፣ ከአፋፍ ላይ ነፋስ እንደማይለይ ዂሉ ቅዱሳንም ከአንደበታቸው ትዕግሥት፣ ከእጃቸው ምጽዋት፣ ከልቡናቸው ትሕትና፣ ከሰውነታቸው ንጽሕና አይለይም፡፡ የሚጸልዩትና የሚያነቡት ቃል ዂሉ ምሥጢሩ እየገባቸው ስለሚያደርጉት አይሰለቻቸውም፡፡ ከዚህ መዓርግ የደረሰ አንድ ባሕታዊ ለብዙ ዘመናት ‹‹አቡነ ዘበሰማያት›› እያለ ብቻ ሲጸልይ የእግዚአብሔር መልአክ መጥቶ ‹‹‹ይትቀደስ ስምከ› በል እንጂ›› ቢለው ‹‹ኧረ ጌታዬ፥ እኔስ ‹አቡነ ዘበሰማያት› የሚለው ኃይለ ቃል ምሥጢሩና ጣዕሙ በአፌ እንደ ጨው እየሟሟ አልጠገበኝ ብሏል፤ እንዴት አድርጌ ወደ ፊት ልሒድ?›› ብሎታል፡፡

ለ. የንጽሐ ነፍስ መዓርጋት

፩ኛ መዓርገ አንብዕ

ቅዱሳን ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ ኢየሱስ ክርስቶስ (እግዚአብሔር) ለሰው ልጅ ያደረገውን ፍቅር፣ እስከ ሞትና መቃብር የተጓዘውን የመከራ ጉዞ እያሰቡ በአንጻሩም ምረረ ገሃነመ እሳትን ጣዕመ መንግሥተ ሰማያትን እያሰላሰሉ ውሉደ አዳም ይህን ዂሉ መከራ ባለመገንዘብ ወደ ሰፊው የፈቃደ ሥጋ መንገድ ሲጓዝ በማየታቸው ያለቅሳሉ፡፡ ያለምንም መሳቀቅ ሲያለቅሱ እንባቸው እንደ ምንጭ ይፈሳል፤ እንደ ሰን ውኃ ይወርዳል፡፡ ሰዎች ለዚህ ዓለም ድሎት ብለው የሚያለቅሱት ልቅሶ ፊትን ያንጣጣል፤ ዓይንን ያመልጣል፡፡ የቅዱሳን ልቅሶ ግን ፊትን ያበራል፤ ኀጢአትን ያስወግዳል፡፡ እርጥብ እንጨት ከእሳት ጋር በተያያዘ ጊዜ እንጨቱ ከነበልባለ እሳት ሲዋሐድ እንጨቱ እርጥብነቱን ትቶ ውኃውን በአረፋ መልክ እያስወገድ ይነዳል፡፡ ቅዱሳንም በግብር (በሥራ) ከመለኮት ጋር ሲዋሐዱ የዚህ ዓለም ምስቅልቅል ሥራ በሰማያዊ የረጋ ሕይወት ተለውጦ አሠራራቸው፣ አካሔዳቸው ፍጹም፤ ሕይወታቸው መልአካዊ ይኾናል፡፡

፪ኛ መዓርገ ኵነኔ

ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ላይ ሲደርሱ ሥጋዊ ፈቃድ ዂሉ ለነፍስ ፈቃድ ይገዛል፡፡ ነፍስ በሥጋ ባሕርያት ላይ ትሠለጥናለች፡፡ ምድራዊ (ሥጋዊ) ምኞት ዂሉ ይጠፋና መንፈሳዊ (ነፍሳዊ) ተግባር ቦታውን ይወርሳል፡፡ ያለምንም ማወላወል መንፈሳዊ ተግባር ዂሉ ይከናወናል፡፡

፫ኛ መዓርገ ፍቅር

ቅዱሳን ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ እንደ ፈጣሪያቸው እግዚአብሔር ዂሉን አስተካክለው ይወዳሉ፡፡ አማኒ፣ መናፍቅ፣ ኃጥእ፣ ጻድቅ፣ ዘመድ፣ ባዕድ፣ ታላቅ፣ ታናሽ፣ መሐይም፣ መምህር፣ ሳይሉ ዂሉንም አስተካክለው በመውደድ የመፍቀሬ ሰብእ እግዚአብሔር ልጆች መኾናቸውን ይገልጻሉ፡፡

፬ኛ ማዕረገ ሑሰት

ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ላይ ሲደርሱ ባሉበት ኾነው ዂሉን ማየትና መረዳት ይችላሉ፡፡ ጠፈር ሳይከለክላቸው ርቀት ሳያግዳቸው ዂሉን በዂሉ ይመለከታሉ፡፡ 

ሐ. የንጽሐ ልቡና ማዕረጋት

፩ኛ ማዕረገ ንጻሬ መላእክት

ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ መላእክትን ለአገልግሎት ሲወጡ ሲወርዱ ማየት፤ ተልእኳቸውን ያለ ምንም አስተርጓሚ መረዳት፤ ማነጋገርና ማማከር የመሳሰሉትን ዂሉ መፈጸም ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ መልአኩን ዐሥር ዓመት እንዳቆመው እንደ ዮሐንስ አፈወርቅ ማለት ነው፡፡

፪ኛ መዓርገ ተሰጥሞ

ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ሲደርሱ በባሕረ ብርሃን መዋኘት፣ ባሉበት ኾነው ወደ ላይም ወደ ታችም መመልከት ይቻላቸዋል፡፡

፫ኛ መዓርገ ከዊነ እሳት (ነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ)

መዓርገ ከዊነ እሳት በሌላ አጠራር ነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ ይባላል፡፡ ይኸውም ሥላሴን በዓይነ ሥጋ ለማየት የሚቻልበት መዓርግ ነው፡፡ ቅዱሳን ከዚህ መዓርግ ሲደርሱ በተዋሕዶ ከመላእክት ጋር ኾነው፣ ረቀው እግዚአብሔርን ማመስገን ይቻላቸዋል፡፡ የለበሱትን ሥጋ ለብቻቸው ለይተው ማየት፤ በአካለ ነፍስ ሰማየ ሰማያትን መጐብኝት፤ ገነት ውስጥ መግባት ይችላሉ፡፡

በአጠቃላይ ‹‹ኩኑ ቅዱሳነ እስመ ቅዱስ አነ›› (ዘሌ. ፲፱፥፪) ተብሎ እንደ ተጻፈው፣ ቅዱሳን የቅዱስ እግዚአብሔር ቤተ መቅደሶች ናቸውና ሕይወታቸው የቅድስና ነው፡፡ ዐሥሩ የቅዱሳን መዓርጋት የሚባሉትም ከላይ የዘረዘርናቸው ናቸው (ዮሐ. ፩፥፵፤ ፪ኛ ጴጥ. ፩፥፬-፲)፡፡ እነዚህም የዐሠርቱ ትእዛዛት ምሳሌዎች ናቸው (ዘፀ. ፳፥፫-፲፯፤ ዘሌ. ፲፱፥፲፰)፡፡ አንድም የዐሥሩ ብፁዓን ምሳሌዎች ናቸው (ማቴ. ፭፥፫-፲፪፤ ዮሐ. ፲፫፥፫፯)፡፡ የቅዱሳን በረከት አይለየን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – የመጨረሻ ክፍል

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ   ቀን ፳፻፲ .

ማጠቃለያ

የጋብቻ ሕይወት፣ የሰው ልጅ ፈቃደ ሥጋዉን እንዲፈጽምበት፣ ዘሩን እንዲተካበትና እንዲረዳዳበት እግዚአብሔር አምላካችን ያዘጋጀው ሥርዓት ነው፡፡ በስእለት ወይም በሌላ ምክንያት ለመመንኰስ ከወሰኑ አባቶችና እናቶች በቀር ለሰብአዊ ፍጡር ዂሉ ጋብቻ አስፈላጊ ነው፡፡ ስለዚህ ወይ በጋብቻ አለዚያም በድንግልና መጽናት እንጂ እንዲሁ እየዘሞቱ መኖር ኀጢአት ነው፡፡ ትዳር ለመመሥረት ወስነን ዝግጅት ላይ የምንገኝ ምእመናንም የጋብቻ መሥፈርታችን ሃይማኖትን፣ ክርስቲያናዊ ምግባርንና መልካም ሰብእናን መሠረት ያደረገ ሊኾን ይገባዋል፡፡ ሀብትን፣ ዝናንና ውበትን ምክንያት አድርጎ መተጫጨት መጨረሻው አያምርምና፡፡ እነዚህ ቁሳውያን መሥፈርቶች ከጊዜ በኋላ ሲጠፉ ጋብቻም አብሮ ሊፈርስ ይችላል፡፡ ስለዚህም መሥፈርታችን ከሃይማኖትና ከምግባር ጋር የተገናኘ መኾን ይኖርበታል፡፡ እነዚህ ከተሟሉ ሀብቱና ሌላው ጉዳይ በጊዜ ሒደትና በጥረት የሚመጣ ነውና፡፡

ጋብቻ፣ የመለኮትና የትስብእት ምሳሌ ነው፡፡ ‹‹እፎ ቤተ ነዳይ ኀደረ ከመ ምስኪን፤ እንደ ምስኪን እንዴት ከደሃ ቤት አደረ?›› እንደ ተባለው እግዚአብሔር አምላካችን ለተዋሕዶ የመረጠው የድሆችን ሥጋ ነው፡፡ የተዋሕዶ ምሳሌ የኾነዉን ጋብቻ የምንመሠርት ምእመናንም ሰዎችን ገንዘብ፣ መልክ፣ ዝና የላቸውም ብለን ልንንቃቸውና ከምርጫ ውጪ ልናደርጋቸው አይገባም፡፡ ጋብቻ፣ አንደኛው የሌላኛውን ድክመት እየሸፈነ የሚኖርበት እንጂ በሁለት ፍጹማን ሰዎች የሚመሠረት ሕይወት አይደለም፡፡ ፍጹም አመለካከት ያለዉን ሰው ማግኘት ይከብዳልና፡፡ በመኾኑም ጥንካሬያችንን በመጋራት፣ ድክመታችንን በማስተካከልና በመተራረም ለመኖር መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡

በሥራ፣ በአመለካከት ወይም በሞትና በልዩ ልዩ ምክንያት መለያየት ሲመጣ ሕይወታችንን እንዴት እንደምንቀጥልና ሌሎች የመሳሰሉ ጉዳዮችንም መጻሕፍትን በማንበብ፣ ሥልጠና በመውሰድ፣ የልምድ ተሞክሮ ያላቸውን ሰዎች በመጠየቅ ከመተጫጨት በፊት ስለ ጋብቻ ሕይወት ትምህርት ብንቀስም መልካም ነው፡፡ ይህም ለወደፊቱ ሕይወታችን ደስታና ስኬት ይጠቅመናል፡፡ ከዂሉም በላይ እግዚአብሔር አምላካችን መልካምና ታማኝ የትዳር አጋር ይሰጠን ዘንድ በጸሎት መትጋት ይጠበቅብናል፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ጋብቻ የሚከለከልባቸው መንገዶች እንዳሉም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እነዚህም ሩካቤን የሚከለክል ደዌ ወይም ተፈጥሯዊ ችግር፣ ምንኵስና (ለመመንኰስ ቃል መግባት)፣ በእምነት መለያየት፣ እንደዚሁም ሥጋዊ፣ መንፈሳዊና የጋብቻ ዝምድናዎች ናቸው፡፡

በሥጋዊ ዝምድና እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ መጋባት የተከለከለ ነው፡፡ ስለዚህም በጋብቻ ዝምድና ወደ ላይ፡- ወንድ የአባቱን፣ የአያቱን የቅድመ አያቱን ሚስት፣ ልጅ፣ እኅት፣ እናት አያገባም፡፡ ወደ ታች፡- የልጁን፣ የልጅ ልጁን ልጅ ሚስት፣ ልጅ፣ እኅት፣ እናትና አያት ማግባት ክልክል ነው (ዘሌ. ፲፰፥፮-፳፩፤ ፪፥፩-፳፩)፡፡ ወደ ጎን፡- ወንዱ የወንድሞቹንና የልጆቻቸውን ሚስት ልጅ፣ እኅት፣ እናትና አያት ማግባት አይችልም፡፡ እንደዚሁም የሚስቱን አያት፣ እናት፣ አክስት፣ እኅት፣ ልጅ፣ የልጅ ልጅና በዚህ የዝምድና ሐረግ የሚገኙትን ማግባት አይፈቀድለትም፡፡ መንፈሳዊ ዝምድናን ስንመለከት ደግሞ ወደ ላይ፡- ወንዱ የክርስትና አባቱን ልጅ፣ ሚስት፣ የልጅ ልጅና እኅት፤ ወደ ታች፡- የክርስትና አባት የክርስትና ልጁን እናት፣ እኅት፣ የእኅቱንና የወንድሙን ልጅ ማግባት አይፈቀድለትም (ፍት. ነገ. ፳፬፣ ቍ. ፰፻፵፪-፰፻፶፮)፡፡

እንደዚሁም በእምነት ከማይመስለን ሰው ጋር መጋባት ክልክል ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረው ጋብቻ የኢየሱስ ክርስቶስና የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነው፡፡ ጋብቻ፣ በሚያምኑና በማያምኑ ሰዎች መካከል ከተፈጸመ ምሥጢሩ ከክርስቶስና ከቤተ ክርስቲያን ተዋሕዶ ጋር አይስማማም፡፡ ስለዚህም በሃይማኖት ከማይመስሉን ጋር መጋባት እንደሌለብን እናስተውል፡፡ በእርግጥ ከአሕዛብ ወይም ከመናፍቃን ወገን የትዳር አጋር የመረጥን ካለን ትምህርተ ሃይማኖትን እንዲማሩና የክርስትና ጥምቀትን እንዲጠመቁ በማድረግ ማግባት እንችላለን (፩ኛ ቆሮ.፯፥፲፪-፲፯፤ ፍት. አን. ፳፬፣ ቍ. ፱፻፲፪-፱፻፲፭)፡፡

ጠቢቡ ሰሎሞን እንደ ቀለበት በልብህ አኑረኝ  በማለት እንደ ተናገረው (መኃ. ፰፥፮)፣ ጋብቻ ለሚጠብቁትና ለሚያከብሩት ሰማያዊ ዋጋ የሚያስገኝ የፍቅርና የአንድነት ሕይወት ነው፡፡ ለቃል ኪዳን የሚታሰረው ክብ ቀለበትም የጋብቻ ሕይወት የማይቋረጥ አንድነት መኾኑን የሚያመላክት ምሥጢር አለው፡፡ በመተጫጨትና በቃል ኪዳን ቀለበት የተመሠረተው ጋብቻ በሥርዓተ ተክሊል ይፈጸማል፡፡ ጋብቻ ምሥጢራዊነቱና ትክክለኛነቱ የሚታወቀው በሥርዓተ ተክሊል ወይም በሥርዓተ ቍርባን ሲፈጸም ብቻ ነው፡፡ ከሥርዓተ ተክሊል ወይም ከቍርባን ውጪ ጋብቻን መፈጸም በሕገ ቤተ ክርስቲያን የተከለከለ ነው (ፍት. ነገ. ፳፬፣ ምዕ. ፳፭፣ ክፍል ፪)፡፡ በድንግልና ጸንተው የቆዩ ምእመናን ጋብቻ በሥርዓተ ተክሊል፤ የመዓስባን (ሁለተኛ የሚያገቡ) ጥንዶች ደግሞ በሥርዓተ ቍርባን ይፈጸማል፡፡ ከሚጋቡት አንዳቸው በድንግልና የቆየ (የቆየች) ከኾነ ለብቻው (ለብቻዋ) ትባረክ ዘንድ ሥርዓት ተሠርቷል (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፱፻፮)፡፡

ክርስቲያናዊ ጋብቻ፣ በቃል ኪዳንና በቡራኬ፣ በጸሎተ ተክሊልና በቅዱስ ቍርባን መፈጸሙ ምሥጢርነት አለው፡፡ አንድነቱ ወይም ተዋሕዶው የክርስቶስና የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነውና (ኤፌ. ፭፥፴፪)፡፡ በሥርዓተ ተክሊል ሙሽሮቹ የሚያደርጉት ቀለበት፣ የሚለብሱት ነጭ ልብስ፣ የሚቀቡት ቅብዓ ቅዱስ፣ የሚቀዳጁት አክሊል፣ እንደዚሁም የካህናቱ ጸሎትና ቡራኬ ሙሽሪትና ሙሽራው ከመንፈስ ቅዱስ ለሚቀበሉት በዓይን ለማይታይ ጸጋ ምክንያቶች ናቸው፡፡ ጸሎቱ ከደረሰ በኋላ ሥርዓተ ቅዳሴ ተደርጎ ሙሽሮቹ ሥጋውንና ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ሥጋውና ደሙ የምሥጢራት ዂሉ ማኅተም ነውና፡፡ ያለ ሥጋውና ደሙ ሥርዓተ ተክሊልም ሥርዓተ ቍርባንም አይፈጸምም (ፍት. ነገ. ፳፬፣ መጅ ፩)፡፡ ከሥርዓተ ተክሊልና ከሥርዓተ ቍርባን ሥርዓት ውጪ ጋብቻን መመሥረት በፍጹም ሊለመድ አይገባም፡፡

ክርስቲያን ነን እያልን በሕገ ቤተ ክርስቲያን ካልተመራን ሰው ኾነን ተፈጥረን ሳለን እንደ እንስሳ መኖር ይኾንብናልና በትዳር ያልተወሰንን ወገኖችም የቤተ ክርስቲያናችንን መመሪያ ተቀብለን በሥርዓተ ተክሊል፣ ካልኾነም በሥርዓተ ቍርባን ለመጋባት እንዘጋጅ መልእክታችን ነው፡፡ ከዚህ በፊት በዓለማዊ መንገድ ትዳር የመሠረትን ምእመናንም ንስሐ ገብተን ሥጋዉን ደሙን እየተቀበልን ኑሯችንን ብንቀጥል፣ ለልጆቻችንም ለሌሎች ወገኖችም አብነት መኾን እንችላለን፡፡

ከዚህ በተለየ በሚስት ላይ ሚስት፤ በባል ላይ ባል መደረብ አስጸያፊና በእግዚአብሔር ዘንድ የሚያስጠይቅ ድርጊት መኾኑን ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ከጋብቻ በፊትም እንኳንስ ከማያገቡት ሰው ጋር ከእጮኛ ጋርም ቢኾን ሩካቤ ሥጋ መፈጸም ኀጢአትም ነውርም ነው፡፡ ከዝሙት እንድትርቁ እግዚአብሔርን እንደማያውቁ አሕዛብ በፍትወት ድል አትነሡ፤ ከእናንተ እያንዳንዱ የራሱን ዕቃ በቅድስና እና በክብር ያገኝ ዘንድ እንዲያውቅ፤” በማለት ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረው ሰውነታችንን በቅድስና መያዝ ይገባናልና (፩ኛ ተሰ. ፬፥፭)፡፡ ይህን በመረዳት በዚህ ዓይነት ኀጢአት የምኖር ምእመናን ከዚህ ክፉ ተግባር መውጣትና ንስሓ መግባት ይኖርብናል፡፡ በንጽሕና የምንኖርም ንጽሕናችንን በመጠበቅ ከሚኾነን ሰው ጋር ጋብቻ መመሥረት፤ ትዳር የመሠረትንም አንድነታችንን ማጥበቅ ይገባናል፡፡ እንደዚህ ብናደርግ በምድርም በሰማይም እንጠቀማለን፡፡

ፍቺን በተመለከተ የጋብቻ ሕይወት ሃይማኖትን፣ ንጽሕናን እንደዚሁም መንፈሳዊ ሕይወትን የሚፈታተን እንደ ዝሙትና ሃይማኖትን መለወጥ ዓይነት ኀጢአት ወይም ሞት ካልመጣ በቀር በአንድነት እንደ ጸና ይኖራል እንጂ በቀላሉ አይፈርስም፡፡ ስለዚህም በጋብቻ አንድነት ውስጥ መለያየት (ፍቺ) እንዳይኖር በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡ በመኾኑም ችግሮችን በውይይት በመፍታት፣ በመመካከርና በመፈቃቀር ተስማምቶ እስከ ሞት ድረስ መኖር ተገቢ ነው፡፡ አብሮ ለመኖርና ለሃይማኖት እንቅፋት የሚኾኑ፣ የጋብቻን ክብር የሚያቃልሉ ለምሳሌ ሩካቤ ሥጋ ለመፈጸም አለመቻል፣ ሃይማኖትን መለወጥ፣ በትዳር ላይ መሴሰንና የመሳሰሉ እንቅፋቶች ካጋጠሙ እንደዚሁም ሞት ከመጣ ግን መፋታት ይፈቀዳል፡፡ ቢኾንም በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ከተደነገገው ምክንያት በቀር መፋታት አይገባም (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፲፩-፲፯)፡፡

የጋብቻን ሕይወት ከሚፈታተኑ፣ የሩካቤ ሥጋ ሥርዓትን ከሚያዛቡ ተግባራት መካከል ዝሙት ዋነኛው ነው፡፡ ከፍተኛ የኾነ የሩካቤ ሥጋ ጥማት ወይም ሴሰኝነት ዝሙት ይባላል፡፡ ይኸውም ከጋብቻ ውጪ ሩካቤ ማድረግን፣ ግብረ ሰዶምንና በገዛ ሰውነት ላይ ፍትወተ ሥጋን መፈጸምን ያጠቃልላል፡፡ በሥልጣኔና በሌሎችም ሰይጣናዊ ተፅዕኖዎች የተነሣ በዓለማችን እየተለመደ የመጣው የዝሙት ኀጢአት ማለትም የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻ፤ የወንዶች ከአንድ በላይ ሴት፣ የሴቶች ደግሞ ከአንድ በላይ ወንድ የማግባት ልማድ፣ ካገኙት ዂሉ ጋር በሩካቤ የመተዋወቅና የመሳሰለው አስነዋሪ ድርጊት ሊወገዝ ይገባል፡፡

ባለፉት ክፍሎች ለመዳሰስ እንደ ሞከርነው ሩካቤ ሥጋ፣ በጥንቃቄና በሥርዓት የሚፈጸም ግንኙነት ነው፡፡ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መሠረት ጋብቻቸውን የፈጸሙ ሕጋውያን ሩካቤ የሚያደርጉበት ቀንና ሥርዓት ተወስኖላቸዋል፡፡ ለባለ ትዳሮቹ የሩካቤ ሥርዓት ከተሠራ ያለ ጋብቻ ከተገኘው ዂሉ ጋር መተኛት ምን ያህል የእግዚአብሔርን ሕግ መተላለፍ እንደ ኾነ ለመረዳት አያዳግትም፡፡ ከተመሳሳይ ፆታ ጋር ስለሚደረገው ግንኙነትስ (ግብረ ሰዶም) ይህ ነው ብሎ ለመናገር ይከብዳል፡፡ ምክንያቱም እንደ አስፈላጊነቱ እንጠቀምበት ዘንድ የተሰጠንን የተፈጥሮ ሕግ መጣስ፤ የሰውነት ክፍሎቻችንንም ማርከስ ነውና፡፡

እያንዳንዱ የሰውነት ክፍል የሥራ ድርሻ አለው፤ አንዱ ሕዋስ የሌላዉን ሥራ ማከናወን አይችልም፡፡ በፆታ ደረጃ ለወንድና ለሴት ለተመሳሳይ አገልግሎት የተሰጡን ሕዋሳት እንዳሉን ዂሉ ለወንዶች ብቻ ወይም ለሴቶች ብቻ የተሰጡ የአካል ክፍሎችም አሉ፡፡ ለሩካቤ ሥጋም ራሱን የቻለ ሕዋስ ተሰጥቶናል፡፡ ይህን የሰውነት ክፍል በጋብቻ ተወስነን ፈቃዳችንን በሥርዓት እንፈጽምበታለን፡፡ ነገር ግን ከዚህ በተለየ ዂኔታ ከተመሳሳይ ፆታ ጋር መገናኘት የእግዚአብሔርን ሥራ ከማንቋሸሽ ባለፈ ርኵሰትም ነው፡፡ ደግሞም ከእንስሳት ማነስ ነው፡፡ ማሰብና ማመዛዘን የማይችሉ እንስሳት እንኳን ከየትኛው ፆታ ጋር መገናኘት እንደሚገባቸው ይገነዘባሉ፡፡ እንስሳት የማያደርጉትን ይህን የረከሰ ተግባር መፈጸም ነባቢት፣ ሕያዊትና ለባዊት ነፍስ ካለችው፤ በዚያውም ላይ በእግዚአብሔር አርአያና ምሳሌ ከተፈጠረ የሰው ልጅ የማይጠበቅ አስነዋሪ ድርጊት ነው፡፡

ግብረ ሰዶም ከኀጢአት ዂሉ የከፋ ኀጢአት ነው፡፡ የኀጢአት ደመወዙ ደግሞ ሞት ነው፡፡ በምድር የነፍስና የሥጋ መለየት፣ በሰማይ ደግሞ በሲዖል (በገሃነመ እሳት) መጣል ሞት ይባላል፡፡ ግብረ ሰዶምን የሚፈጽሙ ሰዎችም ከተፈጥሮ ሥርዓት ውጪ በመጓዝ ከእንስሳት በታች ኾነዋልና ፍጻሜያቸው ሞት፤ የሞት ሞት ነው፡፡ ወይስ ዓመፀኞች የእግዚአብሔርን መንግሥት እንዳይወርሱ አታውቁምን? አትሳቱ፤ ሴሰኞች ቢኾን ወይም ጣዖትን የሚያመልኩ ወይም አመንዝሮች ወይም ቀላጮች ወይም ከወንድ ጋር ዝሙት የሚሠሩ፣ ወይም ሌቦች ወይም ገንዘብን የሚመኙ ወይም ሰካሮች ወይም ተሳዳቢዎች ወይም ነጣቂዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም፤ እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛ ቆሮ. ፮፥፱-፲)፡፡

በብሉይ ኪዳን ከተመሳሳይ ፆታ ጋር ግንኙነት ሲፈጽሙ የነበሩ ሰዶማውያን ንስሓ ባለመግባታቸው ምክንያት በእሳትና በዲን ተቀጥተዋል፡፡ በዚህ ዘመን የተነሡ ሰዶማውያንም በምድር በመቅሠፍት፤ በሰማይም በገሃነመ እሳት መቀጣታቸው አይቀርም፡፡ ምክንያቱም ቅዱሱን የእግዚአብሔር ሰውነት አርክሰዋልና፡፡ በዚህ የርኵሰት ኀጢአት የሚገኙ ወገኖቻችን ከመጥፋታቸው በፊት በመምከርና በማስተማር ክርስቲያኖች ከኾኑ ለንስሓ እንዲበቁ፤ ሃይማኖት ከሌላቸውም ብንችል አስተምረን ማስጠመቅ፤ ባንችል ደግሞ የሚሠሩት ሥራ ከሰው የማይጠበቅ ተግባር መኾኑን ማስገንዝብ ይገባል፡፡ ሐዋርያው ይሁዳ እንዲሁም እንደ እነርሱ ዝሙትን ያደረጉና ሌላን ሥጋ የተከተሉ ሰዶምና ገሞራ በዙሪያቸውም የነበሩ ከተማዎች በዘላለም እሳት እየተቀጡ ምሳሌ ኾነዋል፤  በማለት ሰዶምና ገሞራ መጥፋታቸውን መጥቀሱ ግብረ ሰዶም የሚያመጣውን  መሪር ቅጣት በመገንዘብ ይህን ኀጢአት እንድንጸየፈውና እንድንርቀው ለማስተማር ነው (ይሁዳ. ፩፥፯)፡፡

የጽድቅ ሥራ እና የኀጢአት ተግባር በአንድ ልብ አመንጪነት ይፈጸማሉ፡፡ ልዩነቱ ጻድቃን ልቡናቸውን መልካም ነገርን ሲያሳስቡት፤  ኃጥኣን ደግሞ ለክፉ ነገር ማዋላችን ነው፡፡ “ደግ ሰው ከመልካም ልቡ መዝገብ መልካም ነገርን ያወጣል፤ ክፉ ሰው ግን ከክፉ ልቡ መዝብ ክፉ ነገርን ያወጣል፤” እንዲል (ማቴ. ፲፪፥፴፭)፡፡ በዚህ ዓለም እግዚአብሔርን የሚያስረሱን ሥጋውያን ተግባራት ብዙ ቢኾኑም፣ በአንጻሩ ደግሞ ፈቃደ ሥጋችንን በማሸነፍ ሕግጋቱን ጠብቀን ለመኖር የምንችልባቸው አጋጣሚዎችም አሉ፡፡ ጣዖት በሚመለክበት አካባቢ ቤተ ክርስቲያን እናገኛለን፤ ዓለማዊ ጫጫታ በሚበዛበት ቦታ ቅዳሴ እንሰማለን፡፡ እንግዲህ ለሥጋችን ነጻነት፣ ለነፍሳችን ድኅነት የሚጠቅመንን መምረጥ የእኛ ድርሻ ነው፡፡ ስለኾነም እሺ ብትሉ፣ ለእኔም ብትታዘዙ የምድርን በረከት ትበላላችሁ እንደ ተባልነው (ኢሳ. ፩፥፲፱) እንደ ዝሙት ያሉ አስነዋሪ ተግባራትን ከሚያስፈጽመን ሰይጣን ሸሽተን ቅዱሱን የእግዚአብሔርን መንፈስ ልንከተል ይገባናል፡፡

በአጠቃላይ መላው ምእመናን በተለይ እሳታዊ ባሕርይ የሚበረታብን ወጣቶች በምድር በልዩ ልዩ ደዌያት እንዳንያዝ፣ በሰማይም በገሃነመ እሳት እንዳንጣል ከዝሙት ሥራ ዂሉ ራሳችንን በመጠበቅ በተቀደሰው ጋብቻ ልንወሰን ያስፈልገናል፡፡ ከዝሙት ኀጢአት ነጻ ለመኾንም ፈሪሃ እግዚአብሔርን ገንዘብ ማድረግ፤ ሥጋን በጸሎት፣ በጾምና በስግደት እንደዚሁም በሥራ ማድከም፤ በስሜት አለመነዳት፤ ራስን ከስሜታዊነት መጠበቅ፤ ከዚህም ባሻገር ሞተ ወልደ እግዚአብሔርንና የቅዱሳንን ተጋድሎ ማስታወስ ዋነኛ መፍትሔዎች ናቸው፡፡

ስናውቅ በድፍረት፣ ሳናውቅ በስሕተት በሠራነው ኃጢአት እግዚአብሔር ይቅር እንዲለን ንስሓ ልንገባ ያስፈልጋል፡፡ እንደዚሁም እስመ ፍትወት ይእቲ እሞን ለኃሣራት ወለድካማት ወፃማት ወኃሣር ወበአማን ወላዲተ ሕማም ይእቲ ለሥጋውያን ወለመንፈሳውያን እስመ ይእቲ ታተልዎን ለመፍቅዳት ብዙኃት እለ ኢይትፈቀዳ ወትሬስዮን ከመ ዘይትፈቀዳ፤ የፈቲው ፆር የኃሣረ ሥጋ፣ የኃሣረ ነፍስ፣ የድካመ ሥጋ፣ የድካመ ነፍስ፣ የፃማ ሥጋ፣ የፃማ ነፍስ መገኛ ናት፡፡ ለሥጋውያንም ለመንፈሳውያንም መከራ ሥጋ መከራ ነፍስን የምታመጣ ናት፡፡ የማይወደዱ ብዙዎችን ፈቃዳት እንደሚወደዱ አድርጋ ታሳያለችና  እንደ ተባለው አምላካችን በዝሙት ከመውደቅ እንዲጠብቀን በጾም በጸሎት ልንተጋ ይገባናል፡፡

… ወንስአሎ ለእግዚአብሔር ተሰናዕዎ ወረድኤተ ወኃይለ ወምሕረተ …፤ የፈቲው ፆር የሚጸናብን አራቱ ባሕርያት ባይስማሙልን፤ አለመስማማታቸውም እግዚአብሔር ባይረዳን፤ አለመርዳቱም ኃይሉን ባያሳድርብን፤ ኃይሉን አለማሳደሩም ይቅር ባይለን ነውናይቅር በለን፤ ኃይልህን አሳድርብን፤ ርዳን፤ አራቱን ባሕርያት አስማማልንብለን እግዚአብሔርን ዘወትር እንለምነው” ተብሎ እንደ ተጻፈው በጸሎት ኃይል የሠለጠነብንን ዝሙት ድል ማድረግ ይቻለናልና (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፹፯-፹፰)፡፡

አምላከ ቅዱሳን እግዚአብሔር፣ በስሕተት ወይም በድፍረት የሠራነውን ዂሉ ኀጢአት ይቅር ብሎ፣ ለወደፊቱም ከኀጢአት ጠብቆ ዂላችንንም የመንግሥቱ ወራሾች ለመኾን ያብቃን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፱

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፲ .

፪. የሩካቤ ሥጋ ሥርዓት

በባልና በሚስት መካከል የሚደረግ የመኝታ ግንኙነት ወይም መተዋወቅ ‹ሩካቤ ሥጋ፣ ግብረ ሥጋ› ይባላል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ሩካቤ ሥጋ ለአዳም የተሰጠውን ተስፋ ተከትሎ የመጣ ሥርዓት መኾኑን ይናገራሉ፡፡ ጥንተ ታሪኩም እንዲህ ነው፤ አዳምና ሔዋን ሕገ እግዚአብሔርን ጥሰው ከገነት ከወጡ በኋላ ጥረው ግረው በምድር እንዲኖሩ ተፈርዶባቸዋል፡፡ በዚህ ጊዜ አዳም እግዚአብሔርን “የሥጋዬን ነገርስ ነገርኸኝ፤ የነፍሴ ነገርስ እንደምን ይኾን?” ብሎ ጠየቀው፡፡ እግዚአብሔርም ይቅር ባይና ሰውን ወዳድ አምላክ ነውና ከአምስት ቀን ተኩል (አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን) በኋላ ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከልጅ ልጁ፣ (ከድንግል ማርያም) ተወልዶ፣ በፈቃዱ ተገፍፎ፣ ተገርፎ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ሥጋዉን ቆርሶ፣ ደሙን አፍስሶ፣ ሞቶ፣ ተነሥቶ እንደሚያድነው ቃል ኪዳን ገብቶለታል፡፡

የተስፋው ቃል እስከሚፈጸም ድረስ፣ አዳምና ሔዋን በሞተ ሥጋ ሞተ ነፍስ፣ በርደተ መቃብር ርደተ ገሃነም ተፈርዶባቸው በማዘንና በመተከዝ እያለቀሱ ይኖሩ ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ እግዚአብሔር አምላካችን አዳምን “አእምራ ለሔዋን፤ ሔዋንን በግብረ ሥጋ ዕወቃት” በማለት እንዲበዙ፣ እንዲባዙና ምድርን እንዲሞሏት አዘዛቸው (ዘፍ. ፫፥፲፯)፡፡ “ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ” የሚለው የተስፋው ቃል ይፈጸም ዘንድ ሩካቤ ሥጋ መፈጸም አስፈላጊ ነበረና አዳም ሔዋንን በግብር አውቋታል፡፡ “አዳምም ሚስቱን ሔዋንን አወቀ፤ ፀነሰችም፤ ቃየንንም ወለደች” እንዲል (ዘፍ. ፬፥፩፣ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡

ከዚህ ታሪክ እንደምረዳው ሩካቤ ሥጋ፣ በአንድ በኩል ፈቃደ ሥጋን ለመቋቋም፤ በሌላ በኩል ደግሞ ለዘር መብዛትና ለትውልድ መቀጠል የሚያስፈልግ፤ በጋብቻ ለሚኖሩ ለሰው ልጆች የተሠራ ሥርዓት ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር እግዚአብሔር አምላካችን ወንድና ሴትን ያስተሳሰረበት ማለት እንዲፈላለጉ ያደረገበት የድንቅ ጥበቡ መገለጫም ነው፡፡ ሁለቱን የጋብቻ ዓላማዎች ማለትም መረዳዳትንና ዘርን መተካትን የሚያስተሳስራቸውም ሩካቤ ሥጋ ነው፡፡ ባልና ሚስት በሩካቤ ወቅት የሚያገኙት የደስታ ስሜት እርስበርስ እንዲፈላለጉ የመሳሳቢያ መንገድ ይኾናቸዋል፤ የጋብቻ ሕይወታቸዉንም የጣፈጠ ያደርግላቸዋል፡፡ የሩካቤ ሥጋ ስሜት ባይኖር ኖሮ ሴትና ወንድ ላይፈላለጉ ይችሉ ነበር፡፡ ምክንያቱም ፈቃድን ለመፈጸም ካልተቻለ ልጅ ለመውለድ ብቻ ወይም ለመረዳዳት ብሎ ወደ ጋብቻ ሕይወት የሚገባ ሰው ለማግኘት ይከብዳልና፡፡

ስለዚህም የሰው ልጅ መጋባትን እንዳይጠላ እግዚአብሔር አምላክ ሴትና ወንድ የሚፈላለጉበትን ስሜት (ሩካቤ ሥጋን) ፈጥሯል፡፡ ኾኖም ግንኙነቱ ሥርዓት ባለውና በሕጋዊ መንገድ እንጂ እንደ እንስሳት በዘፈቀደ አይፈጸምም፡፡ አዳምና ሔዋን በሩካቤ ሥጋ የተዋወቁት ከገነት ወጥተው ቆይተው ንስሓ ከገቡ በኋላ መኾኑም ሩካቤ ሥጋ ጥንቃቄ የሚያስፈልገው ግንኙነት መኾኑን ያመለክታል፡፡ ከጋብቻ ውጪ ሩካቤ ሥጋ መፈጸም እንደማይቻልም ቤተ ክርስቲያናችን በአጽንዖት ታስተምራለች፡፡ በጋብቻ እስካልተወሰንን ድረስ ካገኘነው ዂሉ ጋር መተኛት ሕገ እግዚአብሔርን መጣስ፣ ሰውነትን ማርከስ ነውና፡፡ ከዚህም ባለፈ ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያመጣብን ቅጣትም የከፋ መኾኑን መረዳት ይኖርብናል፡፡

በመኾኑም ያላገባን እስክናገባ ድረስ ክብራችንን መጠበቅ፤ በጋብቻ የተወሰንን ሰዎችም እስከ መጨረሻው ድረስ ተዋሕዷችንን ማጥበቅ ይገባናል፡፡ ስለ ተጋባን ብቻ ከሥርዓት ውጪ ሩካቤ ሥጋን መፈጸም እንደማይገባም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ እያንዳንዱ ቀን የሥራ፣ የጸሎት፣ የጾምና የመመገቢያ (የደስታ) ሰዓት እንዳለው ዂሉ ሩካቤን ለመፈጸምም የተወሰነ ሥርዓት አለው፡፡ በቂ የሕሊና ዝግጅትና ስምምነትም ያስፈልገዋል፡፡ በጋብቻ ግንኙነት የሚወለዱ ሕፃናት የተባረኩና የተቀደሱ ይኾኑ ዘንድ መኝታው ንጹሕ ሊኾን ይገባዋልና፡፡ “ጋብቻ ክቡር፣ መኝታውም ንጹሕ ይኹን፤ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል” እንዳለ (ዕብ. ፲፫፥፬)፡፡ ሩካቤ ሥጋን ሥርዓት በሌለው መንገድ መፈጸም የጋብቻን ክቡርነት፣ የመኝታውንም ንጽሕና ማቃለል ነው፡፡

፪.፩ ሩካቤ ሥጋ የማይፈጸምባቸው ጊዜያት

ሩካቤ ሥጋ፣ በምን ዓይነት ሥርዓት ሊፈጸም እንደሚገባው በሕገ ቤተ ክርስቲያን እንዲህ ተደነግጓል፤ “ወሰብሳብሰ ዘሠርዖ እግዚአብሔር ለደቂቀ ዕጓለ እመሕያው አኮ በእንተ ወሊደ ውሉድ ባሕቲቱ አላ በእንተ መፍቅድ ዘኢዕቁብ ወባሕቱ ኢይኩን በርኵስ፤ እግዚአብሔር ሩካቤን ለሰው የሠራው ልጅ ለመውለድ ብቻ አይደለም፤ የማይወሰን የማይገታ የፈቲውን ፆር ለማራቅ ጭምር ነው እንጂ፡፡ አንድ ጊዜ የሚከለከሉበትን፣ አንድ ጊዜ ፈቃዳቸውን የሚፈጽሙበትን ሠራ፡፡ ነገር ግን አንድ ወንድ ለአንድ ሴት፣ አንዲት ሴት ለአንድ ወንድ ብለው ዘወትር ሊያደርጉት አይገባም፡፡ አጽዋማትን፣ በዓላትን፣ ኅርስን፣ ትክትን ለይቶ ሊያደርጉት ይገባል እንጂ፤” (ፍት. ነገ. አን. ፲፭፥፣ ቍ. ፴፰-፵፰)፡፡ ከላይ እንደ ገለጽነው ሩካቤ ሥጋ በሥርዓት የሚፈጸም እንደ መኾኑ የማይፈጽምባቸው ጊዜያትም አሉ፡፡ እነዚህም የሚከተሉት ናው፤

ሀ. የእርግዝና እና የንጽሕ ጊዜያት

ሚስት በፀነሰችበት ወይም ባረገዘችበት ወቅት፤ በወር አበባዋና በመውለጃዋ ጊዜ (ወንድ ከወለደች ከዐርባ፣ ሴት ከወለደች ከሰማንያ ቀን በፊት) ሩካቤ ሥጋ መፈጸም አይገባም (ዘሌ. ፳፥፲፰)፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም “ወበመዋዕለ ትክቶሃ ወኅርሳ ኢትቅረባ ከመ ኢይኩን ተዋስቦትከ ዘእንበለ ሕግ፤ በኅርሷ፣ በደሟ ወራት ሚስትህን አትድረስባት፡፡ ግቢህ ከመጽሐፍ ሥርዓት የወጣ እንዳይኾን” በማለት በፅንስ (እርግዝና) እና በንጽሕ ጊዜያት ማለትም በአራስነትና በወር አበባ ወቅት ግንኙነት መፈጸም እንደማይገባ አዝዟል (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፷፬)፡፡ በተመሳሳይ መልኩ የሚስት ፅንሷ ከታወቀ በኋላ ለመረዳዳት ካልኾነ በቀር ባሏ ሊቀርባት እንደማይገባ ተደንግጓል (አን. ፳፬፣ ቍ. ፰፻፴፰)፡፡

ለ. ወደ ቤተ ክርስቲያን የሚሔዱባቸው ቀናት

እስራኤላውያን እግዚአብሔር ከሙሴ ጋር ሲነጋገር ከመስማታቸው (ሕጉን ከመቀበላቸው) ከሦስተኛው ቀን በፊት እንዲቀደሱ፣ ልብሳቸውን እንዲያጥቡና ሩካቤ እንዳይፈጽሙ ታዝዘው ነበር፡፡ ዛሬም በሐዲስ ኪዳን ባለ ትዳሮች ትምህርተ ወንጌል ለማዳመጥ፣ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለመቀበል፣ ጠበል ለመጠመቅና ለመጠጣት፣ ወይም ለሌላ አገልግሎት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲሔዱ ከሩካቤ ሥጋ እንዲከለከሉ ታዝዟል (ዘፀ. ፲፱፥፲-፳፭)፡፡ ከዚህም ሌላ በጥምቀት ክርስትና የሚያነሡ (የክርስትና እናት ወይም አባት የሚኾኑ ምእመናን) ክርስትና ከማንሣታቸው በፊትና በኋላ ለሁለት ቀናት ከሩካቤ ሥጋ መከልከል ይገባቸዋል፡፡ ይኸውም መንፈስ ቅዱስን ለማክበር ነው፡፡ ምሥጢረ ጥምቀት ጸጋን፣ ክብርንና ልጅነትን የሚያሰጥ ምሥጢር ስለ ኾነ፡፡ ካህኑ ዘካርያስ የቤተ መቅደሱን አገልግሎት ከፈጸመ ከሁለት ቀን በኋላ ከኤልሳቤጥ ጋር መገናኘቱም ለዚህ ትምህርት ነው፡፡ “ወእምድኅረ ክልኤ መዋዕል ፀንሰት ኤልሳቤጥ ብእሲቱ፤ ከሁለት ቀን በኋላም ሚስቱ ኤልሳቤጥ ፀነሰች” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ሉቃ. ፩፥፳፬፤ ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፴፰)፡፡

ሐ. በዓላት

ቅዳሜ፣ እሑድና በዓበይት በዓላት ሩካቤ ሥጋ መፈጸም የተከለከለ ነው፡፡ ይኸውም በመንግሥተ ሰማያት ጋብቻና ፈቃደ ሥጋን መፈጸም አለመኖሩን ለማጠየቅ ነው፡፡ በዓላት፣ የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌዎች ናቸውና ፡፡ “በትንሣኤስ እንደ እግዚአብሔር መላእክት በሰማይ ይኾናሉ እንጂ አያገቡም አይጋቡምም” እንዲል (ማቴ. ፳፪፥፴)፡፡ ሌላው ምክንያት ደግሞ “ንጹሕ የኾነ ነውርም የሌለበት አምልኮ በእግዚአብሔር አብ ዘንድ ይህ ነው … በዓለምም ከሚገኝ እድፍ ሰውነቱን መጠበቅ ነው” በማለት ቅዱስ ያዕቆብ እንደ ተናገረው (ያዕ. ፩፥፳፯)፣ በእነዚህ ዕለታት ወደ ቤተ ክርስቲያን በመሔድ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን መቀበልና ራስን መጠበቅ ተገቢ ስለ ኾነ ነው፡፡ “ፈቃድህን በተቀደሰው ቀኔ ከማድረግ እግርህን ከሰንበት ብትመልስ፣ ሰንበትንም ደስታ፣ እግዚአብሔርም የቀደሰውን ‹ክቡር› ብትለው፣ የገዛ መንገድህንም ከማድረግ፣ ፈቃድህንም ከማግኘት፣ ከንቱ ነገርንም ከመናገር ተከልክለህ ብታከብረው፣ በዚያን ጊዜ በእግዚአብሔር ደስ ይልሃል፤ በምድርም ከፍታዎች ላይ አወጣሃለሁ፤ የአባትህንም የያዕቆብን ርስት አበላሃለሁ” ተብሎ ተጽፏልና (ኢሳ. ፶፰፥፲፫-፲፬)፡፡

መ. አጽዋማት

“ጸዋሚ ሆይ፥ መላው አካልህ ይጹም፤ አፍህ ክፉ ከመናገር፣ አንደበትህ ከሐሜትና ከስድብ፣ ዓይንህ ሴቶችን ከማየት፣ ጆሮህም ዘፈንና ጨዋታ ከመስማት ይጹም” ተብሎ እንደተ ነገረን (ርቱዐ ሃይማኖት) ሩካቤ ሥጋም ሰውነት የሚደሰትበት ፈቃድ ስለ ኾነ በጾም ወቅት መታቀብ ይገባል፡፡ “ወመፍቅደ ሕግሰ በጾም ከመ ትድክም ኃይለ ፍትወት … ወዓዲ ከመ ያምልኮ ለእግዚአብሔር በኵለንታሁ በአሠንዮተ ጾም እመንገለ ተአንስሶ ወበጸሎት እመንገለ ነባብያን፤ ጾምን ያሻው ፈቃድ የፈቲው ፆር ትደክም ዘንድ ነውና … ዳግመኛም ሰው እንስሳትን በሚመስልበት ባሕርዩ በጾም፤ መላእክትን በሚመስልበት ባሕርዩ በጸሎት እግዚአብሔርን በነፍስ በሥጋው ያገለግል ዘንድ ነው” ተብሎ ተጽፏል (ፍት. ነገ. ፲፭)፡፡ ስለዚህም በጾም ጊዜያት ሩካቤ ሥጋ ከመፈጸም መታቀብ ያስፈልጋል፡፡ “ኢታርስሖን ለመዋዕላት ቅዱሳት እንተ ጾም፤ ጾም የሚጾምባቸውን ዕለታት አታሳድፋቸው” እንዳለ ቅዱስ ባስልዮስ፡፡

ይኸውም ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ለማስገዛትና የሚወለዱ ልጆችን ከደዌ ለመጠበቅ ሲባል የተሠራ ሕግ ነው፡፡ “በጾም ወቅት ከሩካቤ መከልከል ስለ ጾም የሚኾን ፈቃደ ነፍስ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ ይኸውም ነባቢት ነፍስን ለማክበር ደማዊት ነፍስን ከእንስሳዊ ግብር መከልከል ነው፡፡ ሰውነትን (ሥጋ) በሚጐዳ በጾም ወራት ሰውነቱን፣ ልጁን ከደዌ ለመጠበቅ ለሰው ዂሉ እያንዳንዱ ከሩካቤ መከልከል ይገባዋል” እንዲል (ፍት. ነገ. አን. ፳፭፥፣ ቍ. ፶-፶፪)፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ባልና ሚስት በንስሓ አባታቸው የተሰጣቸዉን የንስሐ ቀኖና ወይም በራሳቸው ፈቃድ የገቡትን የጾም ሱባዔ እስከሚፈጽሙ ድረስ ከሩካቤ ሥጋ መከልከል ይገባቸዋል፡፡

በአጠቃላይ ባልና ሚስት በፅንስ፣ በአራስነትና በወር አበባ ወቅት፤ እንደዚሁም በበዓላትና በአጽዋማት ቀን ሩካቤ ሥጋ ማድረግ እንደማይገባቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ታስተምራለች፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን ሰይጣን የሚፈትንበትን ክፍተት እንዳያገኝ ባልና ሚስት ሊለያዩ አይገባም፡፡ “ለጸሎት ትተጉ ዘንድ ተስማምታችሁ ለጊዜው ካልኾነ በቀር እርስ በርሳችሁ አትከላከሉ፤ ራሳችሁን ስለ አለመግዛት ሰይጣን እንዳይፈታተናችሁ ደግሞ አብራችሁ ኹኑ፤” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፭)፡፡ ይህ የሐዋርያው ትምህርት “ሰውነታችሁን ንጹሕ አድርጋችሁ በምትጾሙበት፣ በምትጸልዩበት ጊዜ ነው እንጂ ሥራችሁን ከፈጸማችሁ በኋላ ግን ወደ ፈቃዳችሁ ተመለሱ፡፡ የምትሹትን ስላጣችሁ ሰይጣን ድል እንዳይነሳችሁ” ተብሎ በፍትሐ ነገሥትም ተጠቅሷል (አን. ፲፭፣ ቍ. ፳፬)፡፡ ይህም ባልና ሚስት፣ የጾም፣ የጸሎት፣ የበዓል ወቅት ካልኾነ በቀር ሳይለያዩ ፈቃዳቸዉን መፈጸም እንደሚገባቸው ያስገነዝባል፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፰

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፰ ቀን ፳፻፲ .

ለ. ምንኵስና

ምንኵስና፣ ‹መንኰሰ – ሞተ› ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ቃል ሲኾን ትርጓሜውም ሥጋዊ ስሜትን መግደልን (ማሸነፍን) ያመላክታል፡፡ ይኸውም ሥጋዊ ስሜትን በመግታት ራስን የመንፈስ ደሃ ማድረግን፤ ምድራዊ ደስታን በመናቅ ለሰማያዊው መንግሥት መዘጋጀትን የሚያጠይቅ ነው፡፡ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ብልና ዝገት በሚያጠፉት፣ ሌቦችም ቆፍረው በሚሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በምድር ላይ መዝገብ አትሰብስቡ፡፡ ነገር ግን ብልም ዝገትም በማያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በማይሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በሰማይ መዝገብ ሰብስቡ፤” በማለት ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ሰማያዊ ዋጋ እንደሚያስገኝ ተናግሯል (ማቴ. ፮፥፲፱-፳)፡፡ ምንኵስና፣ ጌታችን የሰጠውን ይህን ተስፋ መሠረት በማድረግ አባቶችና እናቶች በብሕትውና (በብቸኝነት) የሚኖሩበት ሕይወት ሲኾን፣ ይኸውም ምድራዊውን ተድላና ደስታ የሚያስተው፤ ከሥጋ ጥቅም ይልቅ ለነፍስ የሚያደላ የቅድስና ኑሮ ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት ምንኵስና፣ ቍምስናንና ጵጵስናን የመሰሉ የክህነት መዓርጋትን ለመቀበል አንደኛው መሥፈርት ነው፡፡ ስለዚህም አንድ ዲያቆን በሕግ ተወስኖ (ሚስት አግብቶ) መኖር ካልፈለገና በቍምስና ወይም በኤጲስ ቆጶስነት ከፍ ሲልም በጵጵስና የማገልገል ዓላማ ካለው ቅስና ከመቀበሉ አስቀድሞ መመንኰስ ግድ ይለዋል፡፡ ሚስት ማግባትን ከመረጠ ግን ከቅስና መዓርግ ባለፈ ለኤጲስ ቆጶስነትም ለጵጵስናም ሊበቃ አይችልም፡፡ ኾኖም ምንኵስና፣ ለደናግል ብቻ ሳይኾን ለመዓስባንም ማለትም ትዳር መሥርተው ለኖሩ ምእመናንም ይፈቀዳል፡፡ የተቻላቸው ከሴት ጋር ሳይተዋወቁ (ትዳር ሳይመሠርቱ) በድንግልናቸው እንደ ጸኑ ይመነኵሳሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ ጋብቻ መሥርተው ከቆዩ በኋላ በሞት ወይም በሌላ ምክንያት ከትዳር አጋራቸዉ ጋር ቢለያዩ መመንኰስ ይችላሉ፡፡ በእርግጥ ይህ የሚኾነው ፈቃደ ሥጋቸዉን (የፍትወት ስሜታቸዉን) ለማሸነፍ ከቻሉ ብቻ ነው፡፡ ሁለተኛ የማግባት ፍላጎቱ ያላቸው ወገኖች ግን እንዲመነኵሱ አይገደዱም፡፡

ወደ መነሻ ርእሳችን ስንመለስ ፍቺ ከሚፈቀድባቸው መንገዶች አንደኛው ምንኵስና ነው፡፡ ይኸውም በፍትሐ ነገሥት እንደ ተገለጸው ባልና ሚስት “አይበላስ የለም፤ አይጠገብ ይባስ” ብለው በፈቃዳቸው ለመመንኰስ ሲወስኑ ነው፡፡ ውሳኔው ግን የሥጋ ስሜትንና የቤተሰብ ኹኔታን ባገናዘበ መልኩ መኾን አለበት፡፡ ምክንያቱም አንዳቸው ለመመንኰስ ፈልገው አንዳቸው ፈቃደኛ ካልኾኑ ወይም ልጆችን የሚረከብና የሚያሳድግ ሰው ከሌለ ቤተሰብን በትኖ መመንኰስ ተገቢ አይደለምና፡፡ ሁለቱም ጥንዶች ፈቃደ ሥጋ ጠፍቶላቸው ከኾነ፣ ልጆቻቸዉን የሚያሳድግላቸውም ከተገኘ (ወልደው ከኾነ) ተመካክረው መመንኰስና መለያየት ይችላሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ጋብቻ ይፈርሳል (ፍቺ ይፈቀዳል)፡፡ ከዚህ ላይ ልናስተውለው የሚገባን ቁም ነገር ከመነኰሱ በኋላ ወደ ጋብቻ መመለስ በፍጹም አይፈቀድም፡፡ ስለዚህም ያላገባንም ኾነ ያገባን ሰዎች በስሜታዊነት ተነሣሥተን ፈቃደ ሥጋችንን በትክክል ሳናዳምጥ መመንኰስ የለብንም፡፡ የምንኵስና ሕይወት ከገቡ የማይወጡበት የመላእክት ሥርዓት ነውና፡፡

ሐ. ሞት

መፋታት የሚፈቀድበት ሌላኛውና ዋነኛው መንገድ ሞት ነው፡፡ ሞት ለሰው ልጅ የማይቀር ጥሪ ነውና ባልና ሚስት ተስማምተው እየኖሩ ሳሉ ከሁለት አንዳቸው በሞት ሊለዩ ይችላሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ሁለተኛ ጋብቻ (ፍቺ) ይፈቀዳል፡፡ በሕይወት የቀረው ወገን ለብቻው መኖር ከተቻለው ራሱን ጠብቆ ቢኖር መልካም ነው። ፍትወትን መጠበቅ ካልተቻለ ግን ለሁለተኛ ወይሜ ለሦስተኛ ጊዜ ማግባት ይፈቀዳል፡፡ የትዳር አጋር በሞት ከተለየ በኋላ በሕይወት ያለው ወገን ከጋብቻ ሕግ ነጻ ነውና፡፡ ለዚህም ማስረጃ የሚኾነን የሚከተለው የቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት ነው፤ “ያገባች ሴት ባልዋ በሕይወት ሲኖር ከእርሱ ጋር በሕግ ታስራለችና፤ ባልዋ ቢሞት ግን ስለ ባል ከኾነው ሕግ ተፈታለች፡፡ ስለዚህ ባልዋ በሕይወት ሳለ ለሌላ ወንድ ብትኾን አመንዝራ ትባላለች፤ ባልዋ ቢሞት ግን ከሕጉ አርነት ወጥታለችና ለሌላ ወንድ ብትኾን አመንዝራ አይደለችም … ሴት ባልዋ በሕይወት ሳለ የታሰረች ናት፤ ባልዋ ቢሞት ግን በጌታ ይኹን እንጂ የወደደችውን ልታገባ ነጻነት አላት” (ሮሜ. ፯፥፪፤ ፩ኛ ቆሮ. ፯፥፲፩-፴፱)፡፡

መ. ሌሎች መንገዶች

ከዝሙት፣ ከምንኵስና እና ከሞት በተጨማሪ በተፈጥሮ ወይም በድንገተኛ ምክንያት የመራቢያ አካላትን ጤንነት የሚያውክ ደዌ ወይም ሌላ ችግር ከተከሠተ ፍቺ እንደሚፈቀድ በሕገ ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል፡፡ ለምሳሌ የአባለ ዘርዕ መሰለብ ካጋጠመ፣ ሩካቤ ሥጋ መፈጸም ካልተቻለ ማለት የመራቢያ አካላት ለሩካቤ ሥጋ ብቁ ካልኾኑ ለአንደኛው ደኅነትና ደስታ ብሎም ሰላማዊ ሕይወት ሲባል መፋታት ይቻላል፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም አንዱ በሌላው ሕይወት ላይ ለሞት የሚያበቃ በደል ወይም ድብደባ በየጊዜው የሚፈጽም ከኾነ፤ ከዚህ ክፉ ልማድም በምክር ካልተመለሰ፤ እንደዚሁም አንደኛው ወገን ሃይማኖቱን ከለወጠና አልመለስም ካለ መፋታት ይፈቀዳል፡፡ ከዚህም ሌላ አንደኛው ወገን ባልታወቀ ምክንያት ከአገር ቢጠፋና ባይመለስ አንደኛው አካል ለአምስት ዓመታት ከጠበቀ በኋላ ሌላ ማግባት ይችላል፡፡

በተመሳሳይ መልኩ የዕድሜ ልክ ወይም የብዙ ዓመታት እስራት ቢፈረድበትና አንደኛው ወገን መታገሥ ካልቻለ ከንስሐ አባት ጋር ተመካክሮ ፍቺ መፈጸምና ሌላ ማግባት ይቻላል፡፡ እንደዚሁም አንደኛው አካል ወደ ውትድርና ሔዶ መሞቱ በምስክር ከተረጋገጠ፣ ከሞተ ከአንድ ዓመት በኋላ ያልሞተው ወገን ሌላ ትዳር መመሥረት ይችላል፡፡ ከላይ በተጠቀሱ ምክንያቶች መፋታትና ሁለተኛ ጋብቻን መመሥረት ቢቻልም ከመለያየት በፊት ችግሮችን በውይይት ለማስተካከልና ለመስማማት ከፍተኛ ጥረት ማድረግ እንደሚገባን መዘንጋት የለብንም፡፡ ምክንያቱም ‹‹መፋታት ይፈቀዳል›› በሚል ሰበብ በሚረባውም በማይረባውም ጉዳይ ጋብቻን ማፍረስ ተገቢ አይደለምና፡፡

ግጭት፣ ሐሜት፣ አሉባልታ፣ ጭቅጭቅ፣ ቅናት፣ ሱስና የመሳሰሉ ጎጂ ልማዶች ጋብቻን ከሚፈታተኑ ችግሮች መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡ እነዚህ ልማዶች የትዳር ሕይወትን አሰልቺ ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ለፍቺ የሚያበቁ አይደሉም፡፡ ምክንያቱም በሁለቱ ጥንዶች መካከል ውስጣዊ መናበብ ካለ ለችግሮቹ መፍትሔ ማምጣት ይቻላልና፡፡ ለዚህም መፍትሔው ከጸሎት ቀጥሎ የችግሩን መንሥኤ በትክክል መረዳትና መውጫ መንገዱን መፈለግ ነው፡፡ በመሠረቱ በጋብቻ ሕይወት የሚያጋጥሙ መሰናክሎችን እንደ መልካም አጋጣሚ መውሰድ እንችላለን፡፡ እንዴት ከተባለ የትዳራችንን መሥመር ለማስተካከል በምናደርገው ጥረት ውስጥ ልዩ የፍቅር ጕዞ ልንጀምር ስለምንችል፡፡ ለምሳሌ ከጥንዶች አንዱ እያመሸ የሚገባ፣ በሱስ የተጠመደ፣ የሚጨቃጨቅ፣ የሚሳደብ፣ ወዘተ ከኾነ ከመቈጣትና ከማጥላላት ይልቅ ከዚህ ልማድ እንዲወጣ ልዩ ክብካቤ ማድረግ ውጤቱ ጥሩ ይኾናል፡፡ ይህም ትዳሩን ይበልጥ እንዲወድና ራሱን እንዲያይ ሊያግዘው ይችላል፡፡ ፍቅር፣ የጠብ ዂሉ መድኀኒት ናትና፡፡

በአጠቃላይ የመጀመሪያ ጋብቻን ማፍረስና ሁለተኛ ወይም ከዚያ በላይ ማግባት ባይፈቀድም ሃይማኖትን የሚያስክድ፣ ሩካቤ ሥጋን የሚከለክልና ለሕይወት የሚያሠጋ ይኸውም ሊቀረፍ የማይችል ችግርና ጭንቅ ከመጣ መፋታት ተፈቅዷል፡፡ ፍቺ የሚፈቀድባቸው መንገዶችም በፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፳፬፣ ከቍጥር ፱፻፵-፱፻፶፰ ተዘርዝረዋል፡፡ በዚህ መሠረት ጋብቻ እንደ አስፈላጊነቱና እንደ ኹኔታው እስከ ሦስት ጊዜ ድረስ ሊፈቀድ ይችላል፡፡ ከዚያ በላይ ግን እንደ ርኵሰት ይቈጠራል፡፡ ከላይ የተዘረዘሩትን የመሰለ ችግር ካልመጣ በቀር ቀላ (ቀላች)፤ ጠቈረ (ጠቈረች) ከሣ (ከሣች)፤ አጠረ (አጠረች)፤ ቀጠነ (ቀጠነች)፤ ደኸየ (ደኸየች) ብሎ ትዳርን ማፍረስ ተገቢ አለመኾኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ያስተምራሉ፡፡ ሕመም ቢያጋጥም ማስታመም፣ ድህነት ቢመጣ አብሮ ማሸነፍ፣ ፈተና ቢበዛ በጋራ ድል ማድረግ እንጂ ትዳርን በየሰበቡ ማፍረስ ክርስቲያናዊ ምግባር አይደለምና፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፯

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፯ ቀን ፳፻፲ .

፩.፰ ፍቺ የሚፈቀድባቸው መንገዶች

በክፍል ስድስት ዝግጅታችን እንደ ጠቀስነው ጋብቻ፣ ፈተና ቢበረታበትም መነጣጠል፣ መለያየት የማይስማማው ጥምረት ነው፡፡ ስለዚህም ‹‹ከዛሬ ጀምሮ በቃኝ›› ተብሎ የሚቋረጥ የኮንትራት ኑሮ አይደለም፡፡ ኾኖም ለጥንዶቹ ሰላማዊ ኑሮ፣ ለሕይወቱ ክብርና ለተጣመሩበት ሥጋ ወደሙ ቅድስና እንቅፋት የሚያመጡና በውይይት ወይም በእርቅ የማይስተካከሉ ችግሮች ከተከሠቱ መፋታት ይፈቀዳል፡፡ ሁለተኛ ጋብቻ መመሥረትም ይቻላል፡፡ ፍቺ መፈጸምና ሁለተኛ ጋብቻ መመሥረት ከሚቻልባቸው መንገዶች መካከል ዋና ዋናዎቹም የሚከተሉት ናቸው፤

ሀ. ዝሙት

መፋታት ከሚፈቀድባቸው መንገዶች መካከል አንደኛው ዝሙት ነው፡፡ ዝሙት፣ ያገቡትንም ያላገቡትንም የሚፈታተን የኀጢአት ዓይነት ነውና ስለዚህ ኀጢአት መጠነኛ ትምህርት ማቅረብ አስፈላጊ ነው፡፡

ወደ ትምህርቱ ስንገባ ከጋብቻ ውጪ የሚደረግ ማንኛውም ዓይነት ሩካቤ ሥጋ (አመንዝራ) ‹ዝሙት› ይባላል፡፡ ይህም በትዳር ላይ ሌላ ሴት (ወንድ) መደረብ ወይም መሰራረቅ (ከሌላ መሔድ) ነው፡፡ ሴሰኝነት ደግሞ ከፍተኛ የዝሙት ስሜትን ያመለክታል፡፡ ዝሙት፣ አመንዝራ፣ ሴሰኝነት ዂሉም ካልጠግብ ባይነትና ራስን ካለመግዛት የሚመጡ የኀጢአት ዘሮች ናቸው፡፡ የዝሙት መንፈስ የስስት ውጤትም ነው፤ ይኸውም ያለኝ ይበቃኛል አለማለትና ዐዲስ ነገርን ያውም የራስ ያልኾነን ነገር መመኘት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን “የባልጀራህን ሚስት አትመኝ፡፡ የባልንጀራህንም ቤት እርሻዉንም ሎሌዉንም ገረዱንም በሬዉንም አህያዉንም፣ ከባልንጀራህ ገንዘብ ዂሉ ማናቸውንም አትመኝ፤” በማለት መፈጸም ይቅርና መመኘት እንኳን እንደማይገባን አዝዞናል (ዘፀ. ፪፥፲፯፤ ዘዳ. ፭፥፳፩)፡፡ ዝሙት ማለት እንግዲህ የእግዚአብሔርን ሕግ በመተላለፍ ከሚስት (ከባል) ውጪ በመሴሰን ሰውነትን ማቆሸሽ ነው፡፡

የእግዚአብሔር ቃል የሚናገረው ዐቂበ ርእስን (ራስን መጠበቅ) ገንዘብ ስለ ማድረግና በንጽሕና ስለ መጽናት ቢኾንም ቃሉን በተግባር የሚፈጽሙት ግን ጥቂቶች ናቸው፡፡ ዝሙትን ልማድ አድርገን የምንኖር ኀጥኣን በርካቶች ነን፡፡ ከዚህ ክፉ ልማድ የምንረዳውም ሰይጣን ወደ ምድር ከለቀቀብን የወረርሽኝ በሽታዎች መካከል ዝሙት ከፍተኛውን ቦታ እንደሚይዝ ነው፡፡ በልዩ ልዩ የዓለም ክፍሎች እንደምንሰማው አንድ ለአንድ መወሰንና ከጋብቻ በፊት ራስን መጠበቅ እንደ ኋላ ቀርነት የተቈጠረ ይመስላል፡፡ “ጓደኛ” በሚል ሰበብ አንድ ወንድ የብዙ ሴቶች ባል፤ አንዲት ሴት የብዙ ወንዶች ሚስት የሚኾኑበት አጋጣሚ ተለምዷል፡፡ በተለይ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት በሚገኙባቸው አካባቢዎች ግብረ ዝሙት እየተስፋፋ ይገኛል፡፡ በስካር፣ በስሜታዊነት ወይም በግዴለሽነት ተገፋፍተን ካገኘነው ዂሉ ጋር በዝሙት የምንድቅ ወነኖች ቤት ይቍጠረን፡፡ ይህ ዂሉ ከዘማዊነታችን የመነጨ ውጤት ነው፡፡

ከጣልያን ወረራ ጊዜ ጀምሮ በአገራችን እንደ ተስፋፋ የሚነገርለት የሴተኛ አዳሪነት ልማድ ባለ ትዳሮችን ጨምሮ የበርካታ ወጣቶችን ሕይወት እየበከለ ይገኛል፡፡ በየመገናኛ ብዙኃኑ እንደምንሰማው ሕፃናትን ጨምሮ በርካታ ወጣት እኅቶቻችን ገንዘብ ለማግኘት በሚል ሰበብ ለከፍተኛ ችግር ተጋልጠዋል፡፡ ለሥነ ልቡናዊ ችግርና ለልዩ ልዩ በሽታ የሚጋለጡ እኅቶቻችን ጥቂቶች አይደሉም፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም ፅንስ ለማስወረድ በሚያደርጉት ጥረት የሚሞቱም ብዙዎች ናቸው፡፡ ከማያውቁት ወንድ የሚወልዱ እናቶችና አባታቸውን የማያውቁ ልጆችም እንዳሉም ለመገመት አያዳግትም፡፡ ይኼ ደግሞ በእናቶችም በልጆችም የሚያስከትለው የሥነ ልቡና ተጽዕኖ ቀላል አይደለም፡፡ የእግዚአብሔር አገር በምትባለው በኢትዮጵያ የምንኖር ክርስቲያኖች ሳይቀር የዚህ ኀጢአት ሰለባዎች መኾናችን እጅግ ያሳፍራል፤ ያሳዝናልም፡፡

በዝሙት መተዳደር ከሚያስገኘው ገንዘብና ከመብትነቱ ይልቅ ነጻነትን የሚቀማና ማንነትን የሚያሳጣ ተግባር መኾኑን በማስተዋል ይህን ድርጊት የሚከለክል ሕግ በአገራችን መንግሥት ሊወጣም ይገባል፡፡ መብት ማለት ለሰዎች የሚጠቅም ምርጫ እንጂ እየተጎዱ እንዲኖሩ መፍቀድ ማለት አይደለምና፡፡ በመኾኑም የዝሙት ተግባር ከመብትና ከገቢ ምንጭነት በተለየ መንገድ ቢታይ መልካም ነው፡፡ ወገኖቻችን በእንጀራ ምክንያት ራሳቸውንም ሌሎችንም ወደ ጥፋት እየወሰዱ ነውና፡፡

ጋብቻ የመሠረትን ትዳራችንን ወደ ኋላ በመተው፣ ያላገባንም ራሳችንን በመጣል ከማናውቃቸው ሴቶች ጋር ሰውነታችንን ማሳደፍ በምድርም በሰማይም ያስጠይቀናልና ላለፈው በደላችን ንስሐ ገብተን ለወደፊቱ ራሳችንን እንጠብቅ መልእክታችን ነው፡፡ በሕግ ያልተወሰንን ወጣቶችም የራሳችን አጋር እስኪትመጣልን ድረስ ፈቃደ ሥጋችንን ልንቈጣጠር ይገባል፡፡ “ከሴት ጋር የሚያመነዝር ግን አእምሮው የጐደለ ነው እንዲሁም የሚያደርግ ነፍሱን ያጠፋል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ምሳ. ፮፥፴፪)፣ የዝሙት ኀጢአት ሰይጣናዊ ደዌ ነውና በዝሙት ኀጢአት የምንኖር ዂሉ የሰይጣንን አሽክላ ሰባብረን በራሳችን ጊዜ ከገባንበት እስራት ነጻ እንውጣ፡፡ ወደ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሔደንም እንፈወስ፡፡

ወደ ቀደመ ርእሳችን እንመለስና ባልና ሚስት በሕይወተ ሥጋ እያሉ ሊፋቱ የሚችሉት በአመንዝራ (በዝሙት) ምክንያት ነው፡፡ የፍትወት ፆር ከመበርታቱ የተነሣ ከትዳር አጋር አልፎ ወደ ሌላ የሚሔድ ካለ ስለ አንደኛው ደኅንነትና ስለ ጋብቻ ክቡርነት፣ እንደዚሁም ስለ ሥጋ ወደሙ ቅድስና ሲባል መፋታት ይፈቀዳል፡፡ አምላካችን “ኢትዘሙ፤ አታመንዝር” በማለት እንዳስተማረን ዝሙት መሥራት ኃጢአት ነው (ዘፀ. ፳፥፲፬)፡፡ ቢቻል ከኀጢአት ተለይቶ ለመኖርና በጽድቅ ሥራ ለመትጋት መሽቀዳደም ተገቢ ነው፤ ኾኖም ኀጢአት እየሠሩ አብሮ ከመኖር ተለያይቶ በጽድቅ መኖር ይገባልና ከመዘሞት መፋታት ይሻላልና፡፡ ደግሞም በአንድነት ወደ ገሃነመ እሳት ከመጣል ይልቅ ተለያይቶ ወደ መንግሥተ ሰማያት መግባት ይመረጣል፡፡ “… ሁለት ዓይና ኾነህ ወደ ገሃነመ እሳት ከምትገባ ይልቅ አንድ ዐይና ኾነህ ወደ መንግሥተ ሰማያት ብትገባ ይሻልሃልና” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፭፥፳፱-፴)፡፡

ይህ ሲባል ግን የሐሰት ወሬ በመስማትና በይኾናል (በጥርጥር) ብቻ ለመፋታት መወሰን ተገቢ አይደለም፡፡ ከተጋቢዎቹ አንዱ ወይም ሁለቱም በዝሙት እየወደቁ ከኾነና በንስሐ መመለስ ካልቻሉ ፍቺ ይፈጸማል፡፡ በጋብቻ ወቅትም ይኹን ከጋብቻ በፊት ወይም በኋላ መዘሞት (መሴሰን) አስነዋሪ ድርጊት ነው፡፡ ስለዚህም መፋታት ከሚቻልባቸው መንገዶች አንዱ ዝሙት እንዲኾን ተደንግጓል፡፡ ይህም ዝሙት ቊርባንን ከማፍረሱም ባለፈ ከጋብቻ ውጪ ልጅ መውለድን፣ እንደዚሁም በጥንዶቹም፣ በልጆቻቸውም ላይ ሞትን ያመጣልና የሰውን ልጅ ከጥፋት ለመታደግ ነው፡፡

ከዚህ ላይ ልብ ማለት የሚገባን ቁም ነገር ቢኖር ወንድም ኾነ ሴት በዝሙት ምክንያት የተፈቱትን ማግባት አይፈቀድላቸውም፡፡ “ያለ ዝሙት ምክንያት ሚስቱን የሚፈታ ዂሉ አመንዝራ ያደርጋታል፤ የተፈታችውንም የሚያገባ ዂሉ ያመነዝራል” እንዳለ ጌታችን (ማቴ. ፭፥፴፩)፡፡ ማግባት የሚቻለው ንስሐ ግበተው፣ ከዝሙት ርቀው፣ ራሳቸውን ጠብቀው፣ በቅዱስ ሥጋው በክቡር ደሙ ተወስነው ከሚኖሩት ወገን ነው፡፡ ዂሉም ምእመናን በዚህ ክርስቲያናዊ ግብር መኖር መንፈሳዊ ግዴታችን ነውና፡፡ “ኢይደልዎ ለመኑሂ ከመ ያውስብ ብእሲተ ኅድግተ እምዝሙት በጕጕዓ አላ ይጽናሕ እስከ ትኔስሕ፤ ስትሰስን ተገኝታ የተፈታችዉን ሴት ለማንም ፈጥኖ ማግባት አይገባውም፡፡ በንስሐ እስክትመለስ ድረስ ይጠብቅ እንጂ” እንዲል ፍትሐ ነገሥት፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፮

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፮ ቀን ፳፻፲ .

ጋብቻ በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ በሁለት ተፈላላጊ ፆታዎች ስምምነት የሚገነባ መንፈሳዊ ተቋም ነው፡፡ “ወንህነሰ ንብል ከመ ሰብሳብ ንጹሕ ወልደት ዘአልቦ ርኵስ፤ እስመ ፈጠሮሙ እግዚአብሔር ለአዳም ወለሔዋን ከመ ይብዝኁ ሕዝብ፤ እኛስ ጋብቻ ንጹሕ እንደ ኾነ፣ ልደትም ርኵሰትም እንደሌለበት እንናገራለን፡፡ ሕዝቡ ይበዙ ዘንድ እግዚአብሔር አዳምንና ሔዋንን ፈጥሯቸዋልና” እንዳሉ ቅዱሳን ሐዋርያት (አመክንዮ)፡፡ ስለኾነም ሃይማኖትን የሚያስክድ፣ ንጽሕናን የሚያሳጣ ፈተና እንደዚሁም ሞት ካልኾነ በቀር መሠረቱ እግዚአብሔር ነውና ጋብቻ እንዲሁ አይፈርስም፡፡

ለዚህም ነው ባልና ሚስት ሥርዓተ ተክሊል በሚፈጽሙበት ዕለት በሕመም፣ በችግር ወይም በሌላ ጥቃቅን ምክንያት እንደማይለያዩ በእግዚአብሔር ፊት የመሐላ ቃላቸውን የሚሰጡት፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ከሚገጥመን ልዩ ልዩ ፈተና ሁሉ እንዲጠብቀንና መፍትሔ እንዲያመጣልን ወደ ትዳር ሕይወት ከመግባታችን በፊትም ኾነ ከገባን በኋላ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ የሕይወት መመሪያችን ብናደርግ ሕይወታችን የተስተካከለ ይኾናል፡፡ በእግዚአብሔር ቃል የተሰበረ ልብ መንፈሳዊነትን ያላብሳልና፡፡ መንፈሳዊነት ደግሞ ፍቅርን እንጂ ጥላቻን አያስቀድምም፤ መቀራረብን እንጂ መለያየትን አይመርጥም፡፡

ጌታችን “ቃሌን ሰምቶ የሚያደርገው ዂሉ ቤቱን በዓለት ላይ የሠራ ልባም ሰውን ይመስላል፡፡ ዝናብም ወረደ፤ ጐርፍም መጣ፤ ነፋስም ነፈሰ፤ ያንም ቤት ገፋው፡፡ በዓለት ላይም ስለ ተመሠረተ አልወደቀም፤” በማለት እንደ ተናገረው (ማቴ. ፯፥፳፭)፣ ቃሉን በሕይወቱ የተገበረ ክርስቲያን ምንም ዓይነት ፈተና ቢደርስበት ሳይሰናከል ሃይማኖቱን ይጠብቃል፡፡ እንደዚሁ ዂሉ በጋብቻ የሚኖሩ ክርስቲያኖችም ልዩነታቸውን በማጥበብ በጋራ ይኖራሉ እንጂ መፋታትን አይመርጡም፡፡

በመንፈሳዊ ፍቅር የሚያምን ክርስቲያን በየሰበቡ ጥላቻን አያመነጭም፤ ትዳሩን ለማፍረስም አይጣደፍም፤ ነገሮችን በጥንቃቄ ይመረምራል እንጂ፡፡ ፍቅር፣ ትዕግሥትን፣ እዝናትን፣ መተሳሰብን፣ ትሕትናን፣ ቅንነትን፣ ጽድቅንና ተስፋን ያመጣልና፡፡ “ፍቅር ያስታግሣል፤ ያስተዛዝናል፤ ፍቅር አያቀናናም፤ ፍቅር አያስመካም፤ ፍቅር ልቡናን አያስታብይም፡፡ ፍቅር ብቻዬን ይድላኝ አያሰኝም፤ አያበሳጭም፤ ክፉ ነገርን አያሳስብም፡፡ ጽድቅን በመሥራት ደስ ያሰኛል እንጂ፣ ግፍን በመሥራት ደስ አያሰኝም፡፡ በዂሉ ያቻችላል፤ በዂሉም ያስተማምናል፡፡ በዂሉም ተስፋ ያስደርጋል፤ በዂሉም ያስታግሣል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ (፩ኛ ቆሮ. ፲፫፥፬-፯)፡፡

ጋብቻ ክቡር፣ መኝታውም ቅዱስ እንደ መኾኑ አንድ ባል ለአንዲት ሚስት፤ አንዲት ሚስት ለአንድ ባል ኾነው እንዲኖሩ እግዚአብሔር አምላካችን ሥርዓት ሠርቶልናል፡፡ አምላካችን “ሰው ብቻውን ይኖር ዘንድ መልካም አይደለም፤ ስለዚህ የምትረዳውን ጓደኛ እንፍጠርለት” እንጂ “የሚረዱትን ጓደኞች እንፍጠርለት” አላለም (ዘፍ. ፪፥፲፰)፡፡ ይህም አንድ ወንድ ለአንዲት ሴት፤ አንዲት ሴት ለአንድ ወንድ መፈጠሯን የሚያመለክት ነው፡፡ ይህን አምላካዊ ሕግ በመጣስ በሚስት ላይ ሌላ ሚስት፤ በባል ላይ ሌላ ባል መደረብ ነውርም ኀጢአትም ነው፡፡ ከብዙ ወንዶች (ሴቶች) ጋር መዘሞት፤ የትዳር አጋርን በየጊዜው መቀያየር የእግዚአብሔርን ሕግ መተላለፍ ነው፡፡ ከዚህም ባሻገር ቅዱሱን ጋብቻ ማሳደፍ፤ ሰውነትንም ማቈሸሽ ነው፡፡ እንደዚህ የምናደርግ ሰዎች ካለን ይህ ልማዳዊ ኀጢአት ፍጻሜው ውርደትና ሞት መኾኑን በመረዳት በንስሓ ልንመለስ ይገባናል፡፡

፩.፯ ፍቺ እና ሁለተኛ ጋብቻ

ጋብቻ፣ ዓላማውም ጠባዩም አንድነት ነው፡፡ ስለዚህም በጋብቻ ሕይወት መፋታት እንደማይገባ ቅዱሳት መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ምክንያቱም ጋብቻ እስከ ሞት ድረስ አብረው የሚዘልቁበት፣ ዘርን የሚተኩበትና ልጆችን ወልደው ለቁም ነገር የሚበቁበት፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተው ከኖሩበት ደግሞ ሰማያዊ መንግሥትን የሚወርሱበት የአንድነት ሕይወት ነውና፡፡ ስለኾነም እንዲሁ በቀላሉ አይፈርስም፤ ጥንዶቹም በሰበብ አስባቡ ሊፋቱ አልተፈቀደላቸውም፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ ባልና ሚስት ሕይወት ሲያስተምር “ፈጣሪ በመጀመሪያ ወንድና ሴት አደረጋቸው፡፡ ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል፤ ከሚስቱም ጋር ይተባበራል፡፡ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይኾናሉ፡፡ ስለዚህ አንድ ሥጋ ናቸው እንጂ ወደ ፊት ሁለት አይደሉም። እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው” በማለት አንድነታቸው እንደማይለያይ ማስተማሩ መፋታት ተገቢ አለመኾኑን ያስረዳናል (ማቴ. ፲፱፥፭-፮)፡፡

በተመሳሳይ ትምህርት “እግዚአብሔር የሕይወትን መንፈስ አንድ አድርጎ ጠብቆልን የለምን? እርሱም የሚፈልገው ምንድር ነው? ዘር አይደለምን? ስለዚህ መንፈሳችሁን ጠብቁ፤ ማንም የልጅነት ሚስቱን አያታልል፡፡ ‹መፋታትን እጠላለሁ› ይላል የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር፤” በማለት ባልና ሚስት ሊፋቱ እንደማይገባ ነቢዩ ሚልክያስ ተናግሯል (ሚል. ፪፥፲፭)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም “ሚስትም ከባልዋ አትለያይ፤ ብትለያይ ግን ሳታገባ ትኑር፡፡ ወይም ከባልዋ ትታረቅ፤ ባልም ሚስቱን አይተዋት … በሚስት ታስረህ እንደ ኾንህ መፋታትን አትሻ” በማለት ፍቺ ተገቢ አለመኾኑን አስተምሯል (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፲-፳፯)፡፡

መምህራነ ቤተ ክርስቲያንም የቅዱሳት መጻሕፍትን ቃለ ትምህርት መነሻ አድርገው “ወአልቦ ዘይጸልዕ እግዚአብሔር ዘየዐቢ ኃጢአት ዘእንበለ ዘይድኅር ብእሲቶ ወያወስብ ካልእተ …፤ ሚስቱን ፈትቶ ሌላ ከሚያገባ ሰው የበለጠ እግዚአብሔር የሚጠላው ኀጢአት የለም፡፡ ይህ ሥራ በእግዚአብሔር ዘንድ የተናቀ ነውና፡፡ በነቢያትና በሐዋርያት ሥልጣንም የተለየ (የተወገዘ) ነውና” ሲሉ የባልና ሚስት መፋታት በእግዚአብሔር ዘንድ የተጠላ ተግባር መኾኑን ይናገራሉ (ተአምረ ማርያም፣ ፲፩ኛ ተአምር፣ ቍ. ፳፰)፡፡

የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በፍቅርና በአንድነት መኖርን የሚሰብክ በመኾኑ ፍቺን አጥብቆ ይከለክላል፡፡ ከተጋቡ በኋላ የሕይወት መሰናክሎችን በመፍታት አብሮ መኖር እንጂ መለያየት ክርስቲያናዊ ሥርዓት አይደለምና፡፡ በመኾኑም ችግሮችን በውይይት በመፍታት፣ በመመካከርና በመፈቃቀር ተስማምቶ እስከ ሞት ድረስ መኖር ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን በትዳር ሕይወት እጅግ የከበደና መፍትሔ የሌለው ችግር ሊመጣ ይችላል፡፡ በዚህ ጊዜ ለጉዳዩ መፍትሔ በሚያመጣ መልኩ መወያየት፣ ከንስሓ አባት ጋር መመካከር፣ በጾም በጸሎት መትጋትና እግዚአብሔርን መማጸን ይገባል፡፡

ኾኖም በመካከላቸው በሃይማኖት ወይም ሊፈታ በማይችል ልዩ ልዩ ምክንያት ለጉዳትና ለሞት የሚያደርስ ግጭት በተደጋጋሚ ከተከሠተ፤ አንዳቸው ወይም ሁለቱም ከትዳር ውጪ ከሔዱ (ዝሙት ከፈጸሙ) እነዚህን ችግርች በምክክር መፍታት፣ በንስሓም ማጽዳት ካልተቻለ መፋታት ይፈቀዳል፡፡ ከዂሉም በላይ ከሁለቱ አንዱ በሞት ከተለየና በሕይወት የቀረው አካል ጋብቻ መመሥረት ከፈለገ ሁለተኛ ማግባት ይቻላል፡፡ ያም ኾኖ ግን በሕገ ቤተ ክርስቲያን ከተጠቀሰው ምክንያት በቀር መፋታት አይገባም (ፍትሐ ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፲፩-፲፯)፡፡

ከላይ በተጠቀሱ ምክንያቶች መፋታትና ሁለተኛ ጋብቻን መመሥረት ቢቻልም ከዚያ በፊት ችግሮችን በውይይት ለማስተካከልና ለመስማማት ከፍተኛ ጥረት ማድረግ እንደሚገባን መዘንጋት የለብንም፡፡ ምክንያቱም ‹‹መፋታት ይፈቀዳል›› በሚል ሰበብ በሚረባውም በማይረባውም ጉዳይ ጋብቻን ማፍረስ ተገቢ አይደለምና፡፡ ነገር ግን እጅግ የከበደና መፍትሔ የሌለው ችግር ከመጣ ቀደም ሲል እንደ ገለጽነው መፋታትና አስፈላጊ ከኾነም ሁለተኛ ጋብቻ መመሥረት ይፈቀዳል፡፡ በዚህ መልኩ የተፋቱ ጥንዶች አስፈላጊነቱ ተጣርቶ እስከ ሦስት ጊዜ ድረስ ጋብቻ ሊፈጽሙ እንደሚችሉ በሕገ ቤተ ክርስቲያን ተወስኗል፡፡ ከሦስት ጊዜ በላይ ጋብቻን መፈጸም ግን እንደ ዝሙትና እንደ ርኵሰት ይቈጠራል፡፡

“እስመ አውስቦ ቀዳማዊ ዘበአሐቲ ብእሲት፤ ወአውስቦሰ ዳግሚት ካልእት ተሐፅፅ እምቀዳሚት፡፡ ወአውስቦሰ ሣልስ ምኑን ውእቱ፤ ወአልቦ በኀቤነ እምድኅረዝ አውስቦ ሕጋዊ፤ በአንዲት ሴት የሚኾን (የሚፈጸም) የመጀመሪያ ጋብቻ ደግ ነው፤ ሁለተኛይቱ ግቢ ከመጀመሪያይቱ ታንሳለች፡፡ ሦስተኛው ግቢ ግን የተናቀ ነው፡፡ ከሦስተኛው ግቢ በኋላም መጽሐፍ ያዘዘው ግቢ የለም፤” እንዲል (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ክፍ. ፩፣ ቍ. ፵፮-፵፫)፡፡ ጉዳዮቹን በመጠኑ ለመዳሰስ ያህል፣ ሁለተኛ ጋብቻ (ፍቺ) ከሚፈቀድባቸው መንገዶች መካከል ዋና ዋናዎቹን እንደሚከተለው አቅርበናቸዋል፤

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፭

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

፩.፭ ሥርዓተ ተክሊል

ቅድስት ቤተ ክርስቲያ፣ አምነው ለሚመጡ ምእመናን ዂሉ ጸጋ እግዚአብሔርን በነጻ ታድላለች፡፡ ለምእመናን ጸጋ የምታድልባቸው መሣሪያዎችም ‹ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን› ተብለው ይጠራሉ፡፡ እነዚህም፡- ምሥጢረ ጥምቀት፣ ምሥጢረ ሜሮን፣ ምሥጢረ ቍርባን፣ ምሥጢረ ተክሊል፣ ምሥጢረ ክህነት፣ ምሥጢረ ንስሓና ምሥጢረ ቀንዲል ናቸው፡፡  ከሰባቱ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን መካከል አንዱ የኾነው ምሥጢረ ተክሊል፣ ክብራቸውን ጠብቀው የኖሩ ደናግል ጋብቻ ሲመሠርቱ የሚፈጸም ሥርዓት ነው፡፡ ክብረ ንጽሕናቸውን ጠብቀው የኖሩ ደናግል ከተጫጩና በፈቃዳቸው ለመጋባት ከተስማሙ በኋላ ጋብቻቸው በሥርዓተ ተክሊል ይፈጸማል፡፡

ከቃሉ ትርጓሜ ስንጀምር ‹ተክሊል› ማለት ‹መቀዳጀት› ማለት ነው፡፡ ይህም ሙሽራውና ሙሽራይቱ የጋብቻ ሥርዓታቸው በሚፈጸምላቸው ጊዜ እንደ ንጉሥና ንግሥት በራሳቸው ላይ አክሊል ደፍተው፣ የክብር ካባ ደርበው፣ በነጭ ልብስ ደምቀው መታየታቸውን ያመለክታል፡፡ ይኸውም ለሙሽሮች የሚፈጸመዉን ጸሎትና ቍርባን የሚያሳይ ሲኾን፣ አፈጻጸሙም ሥርዓተ ተክሊል ይባላል፡፡ ሥርዓተ ተክሊል ሲፈጸም ጸሎቱ፣ ልብሱ በጆሮ የሚሰማ፤ በዓይን የሚታይ ቢኾንም በሙሽሮቹና በዕለቱ በተገኙ ምእመናን ላይ የሚያድረው ጸጋና በረከት ግን በዓይን የማያዩት፤ በእጅም የማይዳስሱት፤ በጆሮም የማይሰሙት ረቂቅ ነውና ሥርዓቱ ምሥጢረ ተክሊል ይባላል፡፡

በሥርዓተ ተክሊል ጋብቻቸዉን የሚፈጽሙ ምእመናን እስከ ሞት ድረስ ላይለያዩ በፍጹም ፍቅር ይዋሓዳሉ፡፡ ሽንገላና ግብዝነት በሌለበት እውነተኛ ፍቅር ይጣመራሉ፡፡ እግዚአብሔርን የሚፈሩና ወላጆቻቸውን የሚያከብሩ ልጆችንም ያፈራሉ፡፡ ጥንዶቹ የመከባበርና የመፈቃቀር፣ የመረዳዳትና የመተማመን፣ የመስማማትና የመተማመን ጸጋ ይታደላሉ፡፡ ፍቅራቸውም ወረተኛ ማለት ከጥቅማ ጥቅም ጋር የተሳሰረ ሳይኾን በመተሳሰብና በመደጋገፍ ላይ የተመሠረተ ይኾናል፡፡ በኑሯቸው የሚያጋጥሙ ፈተናዎችንም በጸሎትና በትዕግሥት የሚወጡበትን ጥበብ ይታደላሉ፡፡ ይህን ጸጋ በመገንዘብ በጋብቻ ሕይወት ለመኖር ዓላማውና ዕቅዱ ያለን ዂሉ በዘፈቀደ መንገድ ከመነዳትና ሰይጣናዊ ባህልን ተከትሎ ከመጥፋት ይልቅ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ በመጠበቅና አንድ ለአንድ በመጽናት በዚህ ቅዱስ ሥርዓት ጋብቻችንን መመሥረት ይገባናል፡፡ በዚህም እኛ ተጠቅመን ለመጭው ትውልድም አርአያና ምሳሌ ለመኾን እንችላለን፡፡

ከላይ እንደ ተመለከትነው ምሥጢረ ተክሊል ለደናግል ማለትም ክብረ ንጽሕናቸውን ጠብቀው ለኖሩ ክርስቲያኖች ብቻ የሚፈጸም ሥርዓት ነው፡፡ ሥርዓቱ በዓላማ ጸንተው ክብራቸውን ጠብቀው ለቆዩ ዲያቆናትና ምእመናን ይፈጸማል፡፡ ከዚህ ላይ የዲያቆናት የጋብቻ ሥርዓት ከምእመናን የተለየ መኾኑን ለመጠቆም እንወዳለን፡፡ ምክንያቱም ወደ መዓርገ ቅስና የሚሸጋገሩበት አንዱ መሥፈርት ነውና፡፡ በሕግ የተወሰኑ ማለትም ትዳር የመሠረቱ ዲያቆናት (ቀሳውስት) በሞት ወይም በሌላ አስገዳጅ ምክንያት ከትዳር አጋራቸው ጋር ቢለያዩ ሁለተኛ ሚስት ማግባት አይፈቀድላቸውም፡፡ ካገቡም በመዓርገ ክህነት ማገልገል አይችሉም፡፡ ስለዚህም ዲያቆናት ሚስት በሚያጩበት ጊዜ ከምእመናን በተለየ መልኩ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡

በእርግጥ ምእመናን እንዲሁ ሳይጠናኑ ይጋቡ ለማለት ሳይኾን የክህነት ሕይወት ከምእመንነት ሕይወት ስለሚለይ ዲያቆናት አስተውለው ወደ ሕይወቱ እንዲገቡ ለማስታዎስ ነው፡፡ ምእመናን ከትዳር አጋራቸው ጋር በሞት ወይም በሌላ ምክንያት ቢለያዩ ሁለተኛ ማግባት ይፈቀድላቸዋል፤ ዲያቆናት (ቀሳውስት) ግን ከአንድ ጊዜ በላይ ሚስት ማግባት አይችሉም፡፡ በክህነታቸው ለመቀጠል የግድ መመንኰስ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሕጉን ተላልፈው ወይም ፈቃደ ሥጋቸዉን ማሸነፍ አልችል ብለው ሁለተኛ ጋብቻ ከመሠረቱም ሥልጣነ ክህነታቸው ይያዛል (ይሰረዛል)፡፡ ከቀሳውስት (ዲያቆናት) በተለየ ሥርዓት ምእመናን ከትዳር አጋሮቻቸው ጋር ቢፋቱ የተለያዩበት ምክንያት ተጣርቶ ሁለተኛ ጋብቻ መመሥረት ይችላሉ፡፡ ነገር ግን ሁለተኛ ጋብቻ በቍርባን እንጂ በተክሊል አይፈጸምም፡፡ ምክንያቱም ምሥጢረ ተክሊል ተጋቢዎቹ (ሁለቱም) ድንግልናቸውን አክብረው ከቆዩ ብቻ የሚፈጸምና የማይደገም ሥርዓት ነውና፡፡

፩.፮ ሕይወት በጋብቻ ወቅት

የጋብቻ ሕይወት፣ በእግዚአብሔር ፈቃድና በሰዎች ምርጫ የሚመሠረት የአንድነት ኑሮ ነው፡፡ በጋብቻ ከተዋሐድንበት ጊዜ ጀምሮ ያለው ወቅት ከነጠላነት ወደ ጥንድነት፣ ከብቸኝነት ወደ ሁለትነት ብሎም ወደ ሦስትነት (ልጅ ሲመጣ) የምንሸጋገርበት ጊዜ ነው፡፡ በዚህ ጊዜ ከቀድሞው በበለጠ መልኩ በጾም በጸሎት መትጋት፣ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን መጓዝ ይጠበቅብናል፡፡ ይህ ወቅት ለራሳችን ብቻ ሳይኾን ለትዳር አጋራችን ብሎም ለልጆቻችን ሕይወት የምናስብበት የሓላፊነት ጊዜ ነውና፡፡ በመኾኑም ከቤት ጀምሮ እስከ ጎረቤት ያለን ማኅበራዊ ግንኙነት የጠነከረ፣ ፍቅራችንም የሠመረ መኾን ይገባዋል፡፡ ጋብቻ ከመሠረትን በኋላ ከትዳር አጋራችን ጋር ተቻችለን ሳይኾን ተስማምተን በፍቅርና በሰላም መኖር ይጠበቅብናል፡፡

በእርግጥ በኑሯችን ላይ ልዩ ልዩ ፈተናዎች ሊመጡብን ይችላሉ፡፡ ለምሳሌ ደዌ ሥጋ፣ ስንፈተ ሩካቤ ወይም በተፈጥሮ ሩካቤ ማድረግ አለመቻል፣ ሊፈወስ የማይችል በሽታ (ለምሳሌ ኤድስ)፣ የአባላዘር በሽታዎችና እነዚህን የመሰሉ ችግሮች ይጠቀሳሉ፡፡ ከዚህም ባሻገር በአሉባልታ ወይም በሰዎች ጣልቃ ገብነት ለመግባባትና በአንድነት ለመቀጠል እንቅፋት የሚኾኑ ችግሮች ሊገጥሙን ይችላሉ፡፡ ለዚህም መፍትሔው ቢቻል ዂሉን ነገር ከመጋባት በፊት መወያየትና ለችግሮች መፍትሔ መስጠት ነው፡፡ የጤና እክሉ ወይም አለመግባባቱ ከጋብቻ በኋላ የመጣ ከኾነ ሕመሙን በጠበልና በሕክምና አለመግባባቱን ደግሞ በመወያየት፣ በጾምና በጸሎት መፍታት ይገባል፡፡ ከዚህ በተረፈ በየሰበቡ መጨቃጨቅም መናተረክም አስፈላጊ አይደለም፡፡

የባልና ሚስት ሕይወታቸው በአንድ አሳብ፣ በአንድ ልብ፣ በአንድ ምክርና የጋራ ፈቃድ ሊመራ ይገባዋል፡፡ እንደዚሁም በመፈቃቀር፣ በመከባበር፣ በመተሳሰብ፣ በመተዛዘንና በመደጋገፍ ሊኖሩ ያስፈልጋል፡፡ ልጆችን በክብካቤና በመንፈሳዊ ሥርዓት ማሳደግም ሌላው የባልና ሚስት ሓላፊነት ነው፡፡ በአጠቃላይ ባል ለሚስቱ፤ ሚስትም ለባሏ መታዘዝ የሕይወታቸው መርሕ መኾን አለበት፡፡ ከዚህም ባሻገር በቤት ውስጥም ኾነ ከቤት ውጪ ክርስቲያናዊ ምግባርን ገንዘብ በማድረግ ለልጆቻቸው መልካም አርአያ ሊኾኑ ይገባቸዋል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ የባልና የሚስት ሕይወት እንዴት መቀጠል እንዳለበት ሲያስረዳ የሚከተለውን ትእዛዝ ከምሳሌያዊ ማብራሪያ ጋር ሰጥቷል፤ “ሚስቶች ሆይ፥ ለጌታ እንደምትገዙ ለባሎቻችሁ ተገዙ፤ ክርስቶስ የቤተ ክርስቲያን ራስ እንደ ኾነ ባልም የሚስት ራስ ነውና፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለክርስቶስ እንደምትገዛ እንዲሁ ሚስቶች ደግሞ በዂሉ ለባሎቻቸው ይገዙ፡፡ ባሎች ሆይ፥ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን እንደ ወደዳት ሚስቶቻችሁን ውደዱ፡፡ ባሎች እንደ ገዛ ሥጋቸው አድርገው ሚስቶቻቸውን ሊወዱአቸው ይገባቸዋል፤ ሚስቱን የሚወድ ራሱን ይወዳል፤ የገዛ ሥጋውን የሚጠላ ከቶ የለምና፤” (ኤፌ. ፭፥፳፪-፴፫)፡፡

ከኃይለ ቃሉ እንደምንረዳው ባልና ሚስት ‹‹በአንተ ይብስ፤ በአንቺ ይብስ›› ተባብለው የጋራ ችግሮቻቸውን በጋራ በመፍታት፣ የሕይወት ምሥጢራቸውን በመጠበቅ በመንፈሳዊ ፍቅር መኖር ይገባቸዋል፡፡ በባልና በሚስት መካከል አንዱን የበላይ፣ ሌላውን የበታች የሚያደርግ ልዩነት ሊኖር አይገባም፡፡ ባል ስለ ሚስቱ፣ ሚስትም ስለ ባሏ ሰውነታቸዉን ለመከራ አሳልፈው እስከ መስጠት ድረስ በፍጹም ፍቅር መዋደድ ይገባቸዋል፡፡ ሁለቱም ከእናትና አባታቸው ተለይተው በአንድነት መኖር ጀምረዋልና (ዕዝራ ፬፥፳-፳፭)፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፬

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፬ ቀን ፳፻፲ ዓ.

ለ. መባዛትና ዘርን መተካት

ሁለተኛው የጋብቻ ዓላማ ለመባዛትና ዘርን ለመተካት ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አዳምና ሔዋንን ብዙ፤ ተባዙ፡፡ ምድርንም ሙሉአት፤ ግዙአትም” በማለት ዘራቸውን እየተኩ በምድር ይበዙ ዘንድ፣ ፍጥረታትንም ይገዙ ዘንድ አዝዟቸዋል (ዘፍ. ፩፥፳፪-፳፰፤ ፱፥፯)፡፡ በዚህ ሕግ መሠረት የሰው ልጅ መሰሉን እየተካና እየተባዛ እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ትውልድ ይቀጥላል፡፡ ይህ ትእዛዝ ለእንስሳትም የተሰጠ ሕግ ቢኾንም የሰው ልጅ ግን ከፍጥረት ዂሉ የከበረ ነውና እንደ እንስሳት በዘፈቀደ ሳይኾን በሕግ ተወስኖ ይባዛና ዘሩን ይተካ ዘንድ የጋብቻ ሕግ ተሠርቶለታል፡፡ ከእንደዚህ ዓይነቱ ክቡር ጋብቻ የሚወለዱ ልጆችም የተባረኩና እግዚአብሔርን የሚፈሩ ይኾናሉ፡፡ የቅኖች ትውልድ ትባረካለች” በማለት ቅዱስ ዳዊት እንደ ተናገረው (መዝ. ፻፲፪፥፪)፡፡

ሐ. ከዝሙት መጠበቅ

ሦስተኛው የጋብቻ ዓላማ ከዝሙት ፆር ለመጠበቅ ማለትም ፍትወተ ሥጋን ለመከላከል ወይም ለመቋቋም ነው፡፡ እንደሚታወቀው የሰው ልጆች መልአካዊና እንስሳዊ ባሕርያት አሉን፡፡ በመልአካዊ ባሕርያችን እንደ መላእክት ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ›› እያልን እግዚአብሔርን ማመስገን፣ ጾም፣ ጸሎት ይስማማናል፡፡ በእንስሳዊ ባሕርያችን ደግሞ መራብ፣ መጠማት፣ ፍትወተ ሥጋ ይሠለጥንብናል፡፡ የጋብቻ ሕይወት የዝሙትን ፆር ለማሸነፍ ከእግዚአብሔር የተሰጠን መከላከያ መንገድ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ጋብቻ የዝሙትን ጠንቅ ለመከላከል እንደሚያስችል ሲያስረዳ ስለ ዝሙት ጠንቅ ለእያንዳንዱ ለራሱ ሚስት ትኑረው፤ ለእያንዳንዲቱ ደግሞ ለራስዋ ባል ይኑራት” በማለት አስተምሯል (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፪-፱)፡፡ ፍትሐ ነገሥትም ሕግ ወደማፍረስ የሚያደርስ የፈቲው ፆር በብዙ ሰዎች ቢጸና ጋብቻ መፈጸም እንዲገባ ይናገራል (አንቀጽ ፳፬፣ ክፍል ፩)፡፡

በአጠቃላይ ጋብቻ፣ እንከብርበትና በጋራ እንኖርበት ዘንድ፤ እንደዚሁም ራሳችንን ከኃጢአት እንጠብቅበት ዘንድ እግዚአብሔር ያዘጋጀልን መንፈሳዊ ሥርዓት ነው፡፡ ሦስቱ የጋብቻ ዓላማዎችም ከላይ የተጠቀሱት ናቸው፡፡ የጋብቻ ዓላማዎች ጠቢብ፣ ልዑል ከሚኾን ከፈጣሪ የተሰጡ ጸጋዎች፤ ከአብርሃም፣ ከይስሐቅ፣ ከያዕቆብ የተገኙ ግብራት ናቸው፡፡ ከእነዚህ የተለየ የጋብቻ ዓላማ ሊኖር አይችልም፡፡ ወኢረከብነ አሐደ እምእሉ ዘይፈቅዳ ለሕገ አውስቦ ዘእንበለ ዘርእ ባሕቲቱ፤ ከነቢያት ከሐዋርያት አንዱ ስንኳ የግቢን ሥርዓት ‹ለዝሙት ትኹን› ብሎ ያስተማረ አላገኘንም፡፡ ልጅ ለመውለድ ብቻ ነው እንጂ” ተብሎ እንደ ተጻፈ (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ቍ. ፷)፡፡

ከዚህ ላይ የጋብቻ አስፈላጊነቱ በሦስት ዓላማዎች ብቻ የተወሰነ አለመኾኑን መረዳት ተገቢ ነው፡፡ ምክንያቱም በሦስቱ ዓላማዎች ውስጥ የሚካተቱ ብዙ ቁም ነገሮች ይኖራሉና፡፡ ለምሳሌ መረዳዳት በስሜት፣ በአሳብ፣ በገንዘብ፣ በመሳሰሉትና በሌሎችም ማኅበራዊ ዘርፎች መተጋገዝን ያጠቃልላል፡፡ ዘርን በመተካት ውስጥም ወልዶ መሳም፣ ዓይንን በዓይን ማየት፣ በወሊድ ጊዜ የሚደረግ ክብካቤና ሥርዓት ያለው የልጅ አስተዳደግ ተግባራት ተጠቃሾች ናቸው፡፡ ስለዚህ ጋብቻ ዓላማው በሦስት ዋና ዋና ክፍሎች ቢጠቀስም በእነዚህ ዓላማዎች ሥር ግን ሌሎች ቁም ነገሮችም ይካተታሉ፡፡

፩.፫ ሕይወት ከጋብቻ በፊት

የጋብቻ ሕይወት በዓላማ የተዘጋጀልን ሥርዓት ይኹን እንጂ ሰውነታቸውን መቈጣጠር የሚችሉ ቢኖሩ እንዲያገቡ አይገደዱም፡፡ ማግባትም አለማግትባም አንድም በእግዚአብሔር ፈቃድ አንድ በግል ፍላጎትና ስሜት ይፈጸማልና፡፡ ነገር ግን እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር ለራሱ የጸጋ ስጦታ አለው፤ አንዱ እንደዚህ፣ ሁለተኛውም እንደዚያ … ዂሉ እንደ ተጠራ እንዲሁ ይኑር” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፯-፳)፡፡ ስለዚህ አንድ ሰው የፈቲውን ፆር ማሸነፍ ከቻለ እንዲያገባ አይገደድም ማለት ነው፡፡ ወእመሰ ኮንከ ዘኢትፈቅድ ብእሲተ ኢትኅሥሥ ኪያሃ፤ ሚስት ማግባት የማትሻ ከሆነ ሚስት ላግባ አትበል” እንዲል ፍትሐ ነገሥት፡፡ ሥርዓቱ ለሴቶችም ተመሳሳይ ነው፡፡

ጋብቻ የሚከልከልባቸው ኹኔታዎችም እንዳሉ ማወቅም ይገባናል፡፡ ለምሳሌ ሩካቤ ለመፈጸም የማያስችል (የሚከለክል) ደዌ ወይም ተፈጥሯዊ ችግር፣ ምንኵስና (ለመመንኰስ ቃል መግባት) ተተቃሾች ናቸው፡፡ ከተጋቡ በኋላ ጥላቻ እንዳይመጣ እንደዚህ ዓይነት የጤና ክሎችን አስቀድሞ ማወቅና መፍትሔ ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም በእምነት መለያየት፣ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ ዝምድናም ጋብቻን የሚከለክሉ ጉዳዮች ናቸው፡፡

ለመጋባት ከመስማማታችን በፊት በእምነት አንድ መኾናችንን፣ በዕድሜ መመጣጠናችንንና መዋደዳችንን ማረጋገጥ ይገባል፡፡ የሁለቱ ተጋቢዎች ስምምነት፣ የቤተሰቦቻቸው ወይም የአሳዳጊዎቻቸው ፈቃድ ለጋብቻ ሕይወት አንደኛው ቅድመ ኹኔታ ነው፡፡ እንደዚሁም የሚያምኑ ከማያምኑ ጋር መጋባት የለባቸውም፡፡ ቢዋደዱም እንኳን ከመጋባት በፊት ያላመነውን (ችውን) ወደ ክርስትና ሃይማኖት መመለስና ማስጠመቅ ይኖርባቸዋል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ለጋብቻ የተዘጋጁ ጥንዶች ዕድሜም ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው ጉዳይ ነው፡፡ ይህም በልጅነት መንፈስ ቃል ከተጋቡ በኋላ ቃላቸውን እንዳያፈርሱ ሲባል ነው፡፡ ቃላቸውን ቢጠብቁም እንኳን ልጅ ለማሳደግና ቤተሰብን ለመምራት ሊከብዳቸው ይችላልና ነው፡፡

በዚህም ምክንያት ተገቢ ወዳልኾነ እርምጃ ማለትም ፅንስን ወደማስወረድ ዓይነት ተግባር ሊገቡ ይችላሉና የሚጋቡ ጥንዶች ለአካለ መጠን የደረሱ መኾን ይገባቸዋል፡፡ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለወደፊቱ በትዳር ተወስነን ለመኖር የምናስብ ከኾነም ጊዜው ደርሶ አጋራችንን እስክናገኝ ድረስ በትሕትና፣ በንጽሕናና በክርስቲያናዊ ሥነ ምጋባር ጸንተን ልንኖር ይገባናል፡፡ ይህንን ለማድረግም ኾነ ዕቅዳችንን ለማሳካት እንዲቻለን ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ፣ መጾም፣ መጸለይ፣ መማር፣ ቅዳሴ ማስቀደስና ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን መቀበል ያስፈልጋል፡፡

ከዚህ ውጪ ትዳር የመመሥረት ፍላጎትና አቅም ኖሯቸው ዕድሜያቸው ከፍ በማለቱ ምክንያት አፍረው ወይም ‹‹ሰው ምን ይለኝ›› በሚል ሥጋት ተይዘው ትዳር ያልመሠረቱ ሰዎች ካሉ በጋብቻ የመኖር ዕቅድ እስካላቸው ድረስ በመዘግየታቸው ምክንያት ሳይሳቀቁ ትዳር ሊመሠርቱ ይገባል፡፡ “‹ሲያረጁ አምባር ይዋጁ› ይሉኛል” ብሎ በመሳቀቅ ጋብቻን መሸሸ ተገቢ አይደለም፡፡ ስለዚህ ጉዳይ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ሲል ያስተምራል፤ ዳሩ ግን ማግባት ወደሚገባው ዕድሜ በደረሰ ጊዜ ስለ ድንግልናው ያፈረ ሰው ቢኖር የወደደውን ያድርግ፤ ቢያገባም ኀጢአት የለበትም፤ የወደደውን እንዲያደርግ ተፈቅዶለታል” (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፴፮)፡፡

፩.፬ የእጮኝነት ጊዜ

ጋብቻ ለመመሥረትና የትዳር አጋር ለመምረጥ የሚያስችል ዕድሜ ላይ የደረሱ ሰዎች ለጋብቻ ከተፈቃቀዱና ከተስማሙ በኋላ በቅድሚያ ለመምህረ ንስሓቸው ይነግራሉ፡፡ ከዚያም ለወላጆቻቸው (ለአሳዳጊዎቻቸው) ያሳውቃሉ፡፡ ጋብቻ የሚመሠረተው ከዚህ በኋላ ነው፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን ግንኙታቸው ወደ ኀጢአት እንዳይወስዳቸውና ከመጋባታቸው በፊት በሩካቤ ሥጋ እንዳይወድቁ መጠንቀቅ ይገባቸዋል፡፡ ምክንያቱም እጮኛ መምረጥ ማለት መጋባት ማለት አይደለምና፡፡ የመተጫጨት ባህልና ሥርዓትን መጠበቅም ይገባል፡፡ ይህም ፈቃድና ስምምነትን፣ ዕድሜን፣ ዝምድናን፣ እንደዚሁም ሃይማኖትን ያገናዘበ መኾን ይኖርበታል፡፡

በመተጫጨት ጊዜ ሊታሰብበት የሚገባው ሌላኛው ጉዳይ የሚጋቡት ጥንዶች የዕድሜ ደረጃ ነው፡፡ የመተጫጫና የመጋቢያ ዕድሜም የወንዶች ከሃያ ወይም ከሃያ አምስት፤ የሴቶች ደግሞ ከዐሥራ አምስት ወይም ከዐሥራ ስምንት ዓመት በላይ ሊኾን እንደሚገባው በሕገ ቤተ ክርስቲያን ተደንግጓል (ፍት. ነገ. አን. ፳፬፣ ምዕ. ፫፣ ክፍ. ፪)፡፡ ተጋቢዎቹ በዕድሜ ብዙ የተራራቁ ከኾነ በጋብቻቸው ላይ ችግር ሊያስከትል ይችላል፡፡ በተጋቢዎች መካከል ምንም ዓይነት ዝምድና እንዳይኖርም መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት ሥጋዊና መንፈሳዊ ዝምድናን ለማስጠበቅ ሲባል እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ መጋባት አይፈቀድም፡፡

የእጮኝነት ጊዜ፣ ጋብቻ ከምንመሠረትበት ጊዜ በፊት ማለት ከቤተሰብ ወይም ከአሳዳጊ ጋር ከምናሳልፈው ጊዜ ጀምሮ ለዓቅመ አዳም (ሔዋን) እስከምንደርስበት ያለውን የወጣትነት የዕድሜ ክልል ያጠቃልላል፡፡ ከነጠላነት እስከ እጮኝነት ያለውን ይህን ወቅት ሕገ እግዚአብሔርንና ክብራችንን በመጠበቅ በንጽሕና ማሳለፍ ይኖርብናል፡፡ እንዲህ ካደረግን የወደፊቱ የጋብቻ ሕይወታችን የሠመረ፣ ፍቅር የሞላበትና በረከት የበዛበት ይኾንልናል፡፡ ይህን የዕድሜ ክልል ክርስቲያናዊ ባልኾነ፣ ሥርዓት በሌለው መንገድ ካሳለፍነው ግን ቀጣዩ ሕይወታችንም ፈተና የበዛበት ሊኾን ይችላል፡፡ ስለዚህ በኋላ እንዳንሰናከል አስቀድመን በጠንካራ መሠረት ላይ ልንታነጽ ይገባናል፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፫

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፫ ቀን ፳፻፲ .

፩.፩ የጋብቻ ክቡርነት እና ምሥጢር

እግዚአብሔር አምላካችን በብሉይ ኪዳን የአዳምንና የሔዋንን፤ የሌሎችንም አባቶች እና እናቶች ጋብቻ ባርኳል፡፡ በሐዲስ ኪዳንም በዶኪማስ ቤት ተገኝቶ፣ ውኃውን ወደ ወይን ቀይሮ ቤቱን በበረከት ሞልቶለታል፡፡ ይህም ጋብቻ በእግዚአብሔር ዘንድ የተወደደና የከበረ ምሥጢር መኾኑን አመላካች ነው፡፡ ምክንያቱም አምላካችን ያልፈቀደዉን ሕይወት ባርኮ አይሰጥምና ነው፡፡ ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ባልና ሚስት አንድ ሥጋ ናቸው እንጂ ሁለት አይደሉም፡፡ እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው” በማለት ማስተማሩም ጋብቻ የአንድነት ውጤትና ታላቅ ሥርዓት መኾኑን ያስረዳል (ማቴ. ፲፱፥፮፤ ዮሐ. ፪፥፩-፲፩)፡፡

በዚህም ሥርዓት በብሉይ ኪዳን፡- አዳምና ሔዋን፣ አብርሃምና ሣራ፣ ይስሐቅና ርብቃ፣ ያዕቆብና ራሔልን የመሰሉ፤ በሐዲስ ኪዳን፡- ኢያቄምና ሐና (የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ወላጆች)፣ ጸጋ ዘአብና እግዚእ ኀረያ (የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ወላ ጆች)፣ ኖኅና ታቦትን (የቅዱስ መርቆሬዎስ ወላጆች) የመሰሉ ደጋግ አባቶች ልጆችን አፍርተውበታል፤ ተጠቅመውበታልም፡፡ ለዚህም ነው “ጋብቻ በዂሉ ዘንድ ክቡር ነው፤ ለመኝታቸውም ርኵሰት የለበትም” ተብሎ የተነገረው (ዕብ. ፲፫፥፬)፡፡ በሥርዓት ከኖሩበት የሚያስከብር ሕይወት ነውና፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም በውዳሴ ማርያም ድርሰቱ “… ማርያም ድንግል ከብካብ ንጹሕ ወመርዓ ቅዱስ፤ ድንግል ማርያም ሙሽራዋ ንጹሕ የኾነ የሰርግ ቤት ናት፤” በማለት እመቤታችንን አመስግኗታል፡፡ ሊቁ እመቤታችንን በሰርግ ቤት መመሰሉ ጋብቻ ንጹሕ ሥርዓት መኾኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ይህም ምሥጢራዊ ትርጕም አለው፤ በሰርግ ቤት ደስታ፣ ጨዋታ፣ መብልና መጠጥ፣ የሙሽራውና የሙሽሪት አንድነት ይከናወንበታል፤ የሙሽራውና የሙሽሪት ዘመዶች አንድ ይኾኑበታል፡፡ መብልና መጠጡ የትምህርተ ወንጌል (የሥጋ ወደሙ)፤ ደስታና ጨዋታው የተአምራት፤ የሙሽራውና የሙሽሪት ተዋሕዶ የትስብእትና የመለኮት አንድነት ምሳሌዎች ናቸው፡፡ በሰርግ የሙሽራውና የሙሽሪት ዘመዶች አንድ እንደሚኾኑባት ዂሉ፣ በድንግል ማርያምም ሰውና መላእክት፣ ሰውና እግዚአብሔር፣ ነፍስና ሥጋ፣ ሕዝብና አሕዛብ አንድ ኾነውባታል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ኤፍሬም እመቤታችንን ‹‹ሙሽራዋ ንጹሕ የሚኾን የሰርግ ቤት›› ይላታል (የረቡዕ ውዳሴ ማርያም፣ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም ዳግመኛም “ከመ ከብካብ ዘአልቦ ጥልቀት መንፈስ ቅዱስ ኀደረ ላዕሌኪ፤ እንደ ሰርግ ቤት አደፍ፣ ጉድፍ የሌለብሽ ኾነሽ ቢያገኝሽ መንፈስ ቅዱስ አድሮብሻል” በማለት እመቤታችንን ጋብቻ በሚፈጸምበት ንጹሕ የሰርግ ቤት መስሎ አመስግኗታል፡፡ ይህም በተመሳሳይ መልኩ የጋብቻን ክቡርነት የሚያመለክት ነው (ውዳሴ ዘቀዳሚት)፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ጳውሎስ “ይህ ምሥጢር ታላቅ ነው፤ እኔ ግን ይህን ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተ ክርስቲያን እላለሁ” በማለት ጋብቻ የክርስቶስና የቤተ ክርስቲያን ተዋሕዶ ምሳሌ መኾኑን ያመሠጠረልን (ኤፌ. ፭፥፴፪)፡፡ በአጠቃላይ ጋብቻ፣ ይከብርበትና በጋራ ይኖርበት ዘንድ እንደዚሁም ራሱን ከኃጢአት ይጠብቅበት ዘንድ እግዚአብሔር አምላክ ለሰው ልጅ ያዘጋጀው መንፈሳዊ ሥርዓት ነው፡፡

፩.፪ የጋብቻ አስፈላጊነትና ዓላማዎቹ

ሰው ኾነን የመፈጠራችን ዓላማው የእግዚአብሔርን ስም ለመቀደስ (ለማመስገን)፣ ክብሩን (መንግሥቱን) ለመውረስ እንደ ኾነው ዂሉ ጋብቻንም አምላካችን በዓላማ አዘጋጅቶልናል፡፡ የጋብቻ አስፈላጊነቱ ወይም ዓላማው እጅግ የጎላ ነው፡፡ በሕገ ቤተ ክርስቲያን እንደ ተገለጸው ጋብቻን የሚያሹ (የሚያስፈልጉ) ፈቃዳት ሦስት ናቸው፤ እሊህም ጠቢብ፣ ልዑል ከኾነው ከእግዚአብሔር የተሰጡ፤ እንደዚሁም ከአብርሃም፣ ይስሐቅ፣ ያዕቆብ የተወረሱ ግብራት ናቸው፡፡ ከሦስቱ ዓላማዎች የተለየ የጋብቻ ጥቅም (አስፈላጊነት) አይኖርም፡፡ መምህራነ ቤተ ክርስቲያን “ከነቢያት ከሐዋርያት አንዱ ስንኳ ‹ጋብቻ ለዝሙት ትኹን› ብሎ ያስተማረ የለም፡፡ ልጅ ለመውለድ ብቻ ነው እንጂ” በማለት የጋብቻን ዓላማዎች ያስረዳሉ (ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፳፬፣ ቍ. ፷)፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትን መሠረት በማድረግ ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው ጋብቻ የሚከተሉት ሦስት መሠረታውያን ዓላማዎች አሉት፤

ሀ. መረዳዳት

ከጋብቻ ዓላማዎች አንደኛው እርስበርስ መረዳዳት ነው፡፡ መረዳዳት ማለት መተጋገዝ፣ መተሳሰብ፣ መደጋገፍ፣ መጠያየቅ፣ ለራሳችን ሊደረግልን የምንፈልገውን መልካም ነገር ዂሉ ለሌሎችም ማድረግ ማለት ነው፡፡ ጋብቻ ሁለት ጥንዶች በአንድነት የሚኖሩበትና እርስበርስ የሚረዳዱበት ሕይወት ነው፡፡ በጋብቻ ውስጥ የሚደረግ መረዳዳት በማኅ በራዊ፣ በሥነ ልቡና፣ በምጣኔ ሀብትና በቤተሰብ አስተዳደር መተጋገዝን፣ መተሳሰብን፣ በአንተ ይብስ፤ በአንቺ ይብስ መባባልን እንደዚሁም በስሜት መተዋወቅን ያጠቃልላል፡፡

በጋብቻ ሊኖር ስለሚገባው የመረዳዳት ዓላማ መነሻው “ሰው ብቻውን ይኾን ዘንድ መልካም አይደለም፤ የሚመቸውን ረዳት እንፍጠርለት” የሚለው አምላካዊ ቃል ነው (ዘፍ. ፪፥፲፰)፡፡ ስለዚህም በተቻላቸው አቅም ዂሉ ባል ለሚስቱ የሚገባትን፣ ሚስትም ለባሏ የሚገባውን ማሟላት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ጋብቻ የአንድነት ሕይወት በመኾኑ ሚስት በራሷ፣ ባልም በራሱ ሥልጣን እንደሌላቸው ቅዱስ ጳውሎስ ይናገራል፡፡ አንዳቸው በአንዳቸው ላይ ማዘዝ እንደሚችሉም ያስረዳል፡፡ ምክንያቱም ሁለቱም አንድ አካል ናቸውና (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፴፬)፡፡ በመኾኑም ባልና ሚስት እንደ ዓይን ብሌን ሊጠባበቁ፣ ሊከባበሩና አንዳቸው ለአንዳቸው ሊታዘዙ ይገባቸዋል፡፡ መረዳዳት ማለት አንዱ የሌላውን ስሜት መጠበቅ ነውና፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስም በጋብቻ ሕይወት ውስጥ መኖር ስለሚገባው የመደጋገፍና የመረዳዳት ዓላማ ሲያስረዳ “እናንተ ባሎች ሆይ፥ ደካማ ፍጥረት ስለ ኾኑ ከሚስቶቻችሁ ጋር በማስተዋል አብራችሁ ኑሩ፤ ጸሎታችሁ እንዳይከለከል አብረው ደግሞ የሕይወትን ጸጋ እንደሚወርሱ አድርጋችሁ አክብሩአቸው፡፡ በመጨረሻው ሁላችሁ በአንድ ልብ ሁኑ፤ የሌላው መከራ ለእናንተ እንደሚሆን አድርጉ፤ እንደ ወንድሞች ተዋደዱ፤ ርኅሩኆችና ትሑታን ኹኑ፡፡ ክፉን በክፉ ፈንታ ወይም ስድብን በስድብ ፈንታ አትመልሱ፤ በዚህ ፈንታ ባርኩ እንጂ፡፡ በረከትን ልትወርሱ ለዚህ ተጠርታች ኋልና” ሲል በአጽንዖት አስተምሯል (፩ኛ ጴጥ. ፫፥፩-፱)፡፡

በዚህ ኃይለ ቃል ውስጥ ‹‹ደካማ ፍጥረት ስለ ኾኑ›› የሚለው ሐረግ ሴቶች በዕውቀት ወይም በዓቅም ዝቅተኛ ናቸው ለማለት አይደለም፡፡ በትዳር አጋሮቻቸው በሚደርስባቸው ጫና፣ ከውጪ በሚገጥማቸው ልዩ ልዩ ፈተና በቀላሉ የሚሰናከሉ መኾናቸዉን የመሚጠቁም ነው እንጂ፡፡ ለዚህም ማስረጃ የሚኾነን የሔዋን ጠባይዕ ነው፡፡ አዳምና ሔዋን በገነት በነበሩበት ወቅት የሰይጣን የማሰሳሳት ጥረት የተሳካው በሔዋን የመታለል ጠባይዕ ነበር፡፡ የሔዋን ውዳሴ ከንቱ (የማይጠቅም ምስጋና) የመውደድና በቀላሉ የመሸነፍ ስሜት አሁንም ድረስ በሴቶች ላይ ይስተዋላል፡፡ ሐዋርያው ድክመት ያለውም ይህንን ዓይነት የሴቶችን ጠባይዕ ነው እንጂ በተፈጥሮማ ሴቶችም በሥላሴ አርአያና አምሳል ነው የተፈጠሩት፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ በባልና በሚስት መካከል ሊኖር ስለሚገባው መልካም ግንኙነትና መተሳሰብ ሲያስረዳ ሣራ፣ አብርሃምን ትታዘዘው፤ ‹‹ጌታዬ›› ትለው እንደ ነበረው፤ በበጐ ሥራ ፍጹማን የኾኑ ልጆችን ይወልዱ ዘንድ ወንዶች ሚስቶቻቸውን እንዲያከብሩ ይመክራል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም በዲድስቅልያ “አእምራ አንስት ከመ ብእሲት እንተ ታፈቅር ምታ ትረክብ ክብረ በኀበ እግዚአብሔር፤ ሴቶች ሆይ፥ ባሏን የምትወድ ሚስት በእግዚአብሔር ዘንድ ክብርን እንደምታገኝ ዕወቁ” በማለት በባልና በሚስት መካከል ሊኖር ስለሚገባው መከባበርና መተጋገዝ፤ እንደዚሁም መከባበር ስለሚያስገኘው ጸጋ አስተምረዋል (ዲድስቅልያ፣ አን. ፫፣ ቍ. ፳፭)፡፡ በተአምረ ማርያምም “ከእናንተ ወገን ሚስት ያለችው ሰው ቢኖር እንደ ዓይን ብሌን ይጠብቃት፤ እግዚአብሔር ያስጠበቀው አደራ ናትና” ተብሎ ተጽፏል (፲፩ኛ ተአምር፣  ቍ. ፳፮)፡፡

በጋብቻ ሕይወት ውስጥ ሊኖር ስለሚገባው መረዳዳት ቅዱሳት መጻሕፍት የሚናገሩትን ኃይለ ቃል ጠቅለል ስናደርገው ባልና ሚስት በመካከላቸው የራስ ወዳድነትና የትዕቢት መንፈስን በማስወገድ እንደ ዓይን ብሌን ሊጠባበቁ፣ ሊከባበሩና እርስበርስ ሊከባበሩ እንደሚገባቸው እንገነዘባለን፡፡ በየትኛውም ዓይነት ሕይወት ውስጥ መረዳዳት መኖሩ ተገቢ ነው፡፡ በጋብቻ ሕይወት ግን መረዳዳት ልዩ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል፡፡ ምክንያቱም ጋብቻ ሁለት ሰዎች በአንድ ጣሪያ ሥር በአንድነት የሚኖሩበት ሕይወት ከመኾኑም ባሻገር ኑሮንም ስሜትንም በጋራ የሚመሩበት የአንድነት ተቋም ነውና፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የጋብቻን ሕይወት፣ ‹‹በቤት ውስጥ ያለች ትንሿ ቤተ ክርስቲያን›› በማለት የሚገልጸው፡፡

ይቆየን

የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት – ክፍል ፪

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፪ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ቅዱስ ጳውሎስ ጋብቻ የፈቃድ ሕግ መኾኑን ሲያስተምር ራሳቸውን መጠበቅ ለሚችሉ አለማግባት ቢቻልም ሰውነትን ለመጠበቅ ከአልተቻለ ግን ማግባት እንደሚሻል አስገንዝቧል፡፡ ሐዋርያው እንዳስተማረው ከሴት ጋር አለመገናኘት (ጋብቻ አለመምሥረት) ለሰው መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ስለ ዝሙት ጠንቅ ለእያንዳንዱ ወንድ አንድ ሚስት ሊኖረው፤ ለእያንዳንዲቱ ሴት ደግሞ አንድ ባል ሊኖራት ይገባል፡፡ ነገር ግን ሰው ዂሉ እግዚአብሔር እንዳደለው (እንደ ፈቀደለት) ይኑር፡፡

ላላገቡና ለመበለቶች ደግሞ የሚከተለዉን ትምህርት ሰጥቷል፤ “ላላገቡና ለመበለቶች ግን እላለሁ፤ እንደ እኔ ቢኖሩ ለእነርሱ መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ራሳቸውን መግዛት ባይችሉ ያግቡ፤ በምኞት ከመቃጠል መጋባት ይሻላልና፡፡” ይኸውም “ሚስት የሌላቸው ወንዶች፣ ባል የሌላቸው ሴቶች እንደ እኔ ከሴት (ከወንድ) ርቆ፣ ንጽሕ ጠብቆ መኖር ይሻላቸዋል፡፡ ንጽሕ ጠብቆ፣ ከሴት (ከወንድ) ርቆ መኖር ባይቻላቸው አግብተው ይኑሩ፡፡ አንዲት ሴት (ባል) አግብታችሁ፣ በሕግ ተወስናችሁ ኑሩ ማለቴ ንጽሕ ጠብቆ፣ ከሴት ርቆ መኖር ለማይቻላቸው ሰዎች ነው፡፡ ‹እንደ እኔ ንጽሕ ጠብቃችሁ፣ ከሴት ርቃችሁ ኑሩ› ብዬ አላስገድዳችሁም፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር እንዳደላችሁ ኑሩ፤” ማለቱ ነው (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፩-፱፣ አንድምታ ትርጓሜ)፡፡

ሐዋርያው፣ ቈነጃጅት ባል አግብተው፣ ልጆች ወልደው፣ ቤት፣ ንብረት ይዘው ቢኖሩ መልካም መኾኑን ጠቁሟል፡፡ በተጨማሪም ሳይናወጥ በልቡ የጸና ግን የማግባት ግዴታ እንደደሌለበትና የወደደውን ማድረግ እንደ ተፈቀደለት ማለትም ድንግልናውን ጠብቆ መኖር ከፈለገ በምንኵስና፤ ማግባት ከፈለገም በጋብቻ ሕይወት ጸንቶ መኖር እንደሚችል አስረድቷል፡፡ ትምህርቱም ወንዶችን ብቻ ሳይኾን ሴቶችንም የሚመለከት ነው (፩ኛ ቆሮ. ፯፥፴፯-፴፰)፡፡ ይህም ጋብቻ የፈቃድ እንጂ የግዴታ ሕግ አለመኾኑን ያመለክታል፡፡

ከትምህርቱ እንደምንረዳው ጋብቻ በሰው ፍላጎት ብቻ ሳይኾን በእግዚአሔር ፈቃድና ዕቅድ የተመሠረተ መንፈሳዊ ሥርዓት ነው፡፡ ሕይወቱ ከምድራዊ አንድነት ባሻገር ለምሥጢረ ተዋሕዶም ምሳሌ ኾኖ ይጠቀሳል፡፡ “ዐቢይ ውእቱ ዝ ነገር አንሰ እብሎ ላዕለ ክርስቶስ ወላዕለ ቤተ ክርስቲያኑ፤ ይህም ምሥጢር ታላቅ ነው፤ እኔም ይህንኑ ስለ ክርስቶስና ስለ ቤተ ክርስቲያኑ እናገረዋለሁ፤” እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (ኤፌ. ፭፥፴፪)፡፡

የጋብቻ ክቡርነትና ምሥጢር ይህ ኾኖ ሳለ አንዳንዶቻችን ለጋብቻ የምንሰጠው ትርጕም ግን ዝቅ ያለ ይመስላል፡፡ በስውር ከጋብቻ ውጪ ፈቃዳቸዉን የሚፈጽሙ ምእመናን መኖራቸውም ከዚህ አመለካከት የመነጨ ነው፡፡ ከዚህ የተሳሳተ ግንዛቤ በመውጣትና ንጽሕናን በመጠበቅ አንድም ጋብቻ መመሥረት፤ ካለዚያም ራስን ጠብቆ በድንግልና ጸንቶ መኖር ከክርስቲያኖች የሚጠበቅ ግዴታ ነው፡፡ ስለ ጋብቻ ሕይወት ሲነገር ከጋብቻ ዓላማዎች አንደኛው ከዝሙት ጠንቅ ለመሸሽ ነው፡፡ ይህም በሕጋዊ ሥርዓት ሩካቤ ሥጋን ለመፈጸም ያስችላል፡፡

ሩካቤ ሥጋ የተለየ ዓላማና ምሥጢር አለው፡፡ አፈጻጸሙም በሥርዓተ ተክሊል ወይም በሥርዓተ ቍርባን ይጸናል፡፡ በሕጋዊ ጋብቻ ተወስነን ካልኾነ በቀር ከጋብቻ በፊትም ኾነ በኋላ ካገኘነው ዂሉ ጋር ፆታዊ ግንኙነት መፈጸም ክቡራን ኾነን ተፈጥረን ሳለ በግብራችን ግን ከእንስሳት ጋር እንድንመሳሰል ያደርገናል፡፡ ቅዱስ ዳዊት ሰብእሰ እንዘ ክቡር ውእቱ ኢያእመረ ወኮነ ከመ እንስሳ ዘአልቦ ልብ ወተመሰሎሙ፤ ሰውስ ክቡር ሳለ አላወቀም፤ ልብ እንደሌላቸው እንስሳትም መሰለ በማለት እንደ ተናገረው (መዝ. ፵፰፥፲፪)፡፡

በዓለማችን ላይ እንደምንሰማውና እንደምናስተውለው የሰው ልጅ ራሱን ከሚጥልባቸው መንገዶች አንደኛው ዝሙት ነው፡፡ ለዚህም ነው በተለያዩ የዓለም ክፍሎች አስጸያፊ ፆታዊ ድርጊቶች ማለትም ከአንድ በላይ የትዳር አጋር መያዝ፣ ሴት አዳሪነት ብሎም የተመሳሳይ ፆታ ጋብቻ ምእመናንን ሳይቀር እየተፈታተነ የሚገኘው፡፡ ይህም በሰው ልጆች ዘንድ የመንፈስ ዝለትና የዝሙት ስሜትን የመቈጣጠር ስንፍናን አመላካች ነው፡፡ ከእንደዚህ ዓይነት አጸያፊ የዝሙት ሥራ ራሳችንን እንድንጠብቅ ለማስጠንቀቅ፣ ጋብቻችንንም በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ብቻ እንድንፈጽም ለመጠቆም እንደዚሁም ሩካቤ ሥጋ በሥርዓትና በሕግ እንደሚፈጸም ለማስገንዘብ ‹‹የጋብቻ ሕይወት እና የሩካቤ ሥርዓት›› በሚል ርእስ ይህን ትምህርት አዘጋጅተናል፡፡ በድጋሜ መልካም ንባብ!

፩. የጋብቻ ምንነትና አመሠራረት

ከቃሉ ትርጓሜ ስንጀምር ጋብቻ፡- መጣመር፣ መዋሐድ (አንድ መኾን)፣ በአንድ ጎጆ ውስጥ መኖር ማለት ነው፡፡ ቃሉ፣ የትዳር ሕይወትን ለመመሥረት የሚያስችል የሁለት ተቃራኒ ወይም ተፈላላጊ ፆታዎችን (ጥንዶችን) ዘላቂ ጥምረት (ግንኙነት) ያመለክታል፡፡ ‹ትዳር› የሚለው ቃልም ከጋብቻ ጋር በአቻነት ሊጠቀስ ይችላል፡፡ ይኸውም ባልና ሚስት በአንድ ጎጆ ጥላ ሥር የሚያከናውኑት ቤተሰብኣዊ ኑሮ ነው “በአንድ ልብ በእግዚአብሔር ቤት ተራመድን” በማለት ቅዱስ ዳዊት እንደ ተናገረው (መዝ. ፶፬፥፲፬)፡፡ ትዳር፣ ሁለቱም (ብልና ሚስት) በመስማማትና በመተሳሰብ በአንድነት መኖራቸውን ያመለክታል፡፡ ስለዚህ ጋብቻ ወይም ትዳር ማለት በሁለት የማይተዋወቁና ባዕድ ተቃራኒ ጥንዶች (ፆታ) የሚመሠርቱት የአንድነት ሕይወት ነው፡፡

አመሠራረቱን ስንመለከት ጋብቻ የተመሠረተው በእግዚአብሔር ፈቃድ፣ በአዳምና ሔዋን አማካይነት ነው፡፡ ከአዳም በፊት የተፈጠሩ አራዊት፣ እንስሳትና አዕዋፍ በዝተው፣ ተባዝተው ይኖሩ ዘንድ የተፈጠሩት ጥንድ ጥንድ (ሴትና ወንድ) ኾነው ነበር፡፡ ለአዳም ግን ገና ሔዋን አልተሰጠችውም ነበር፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለአራዊት፣ ለእንስሳትና ለአዕዋፍ ስም ያወጣላቸው ዘንድ ወደ አዳም በላካቸው ጊዜ እንስሳቱ ተባዕትና አንስት ኾነው መፈጠራቸዉን አዳም ተመልክቶ “ከእኔ በቀር ብቻውን የተፈጠረ የለም” ብሎ ማዘኑን የቤተ ክርስቲያን መተርጕማን ይናገራሉ፡፡ በዚህ ጊዜ እግዚአብሔር አምላካችን፣ “ኢኮነ ሠናየ ለእጓለ እመሕያው ይንበር ባሕቲቶ፤ አላ ንግበር ሎቱ ቢጸ ዘትረድኦ፤ ሰው ብቻውን ይኖር ዘንድ መልካም አይደለም፤ የምትረዳውን ጓደኛ እንፍጠርለት እንጂ” አለ፡፡

ከዚህ በኋላ አዳም እንዲያንቀላፋ አደረገ፡፡ ከጎኑም አንድ አጥንት ነሥቶ (ወስዶ)፣ መልክ ከደም ግባት አስተባብራ የያዘችና ውብ አድርጎ፤ ዓይን፣ አፍንጫ፣ እጅ፣ እግር አውጥቶ፤ የሴት አካል ሰጥቶ ሔዋንን ፈጠረለት፡፡ ሔዋን ከአዳም ጎድን መፈጠሯም ባልና ሚስት ተከባብረው፣ ተቻችለውና ተመካክረው በእኩልነት እንዲኖሩ የሚያመለክት ምሥጢር አለው፡፡ ከዚህ ላይ የእግዚአብሔር ዓላማ ሴትንና ወንድን ማበላለጥ አለመኾኑን ልብ ማለት ያስፈልጋል፡፡ እንደዚያ ቢኾን ኖሮ ሔዋንን አንድም ዝቅ ብሎ ከአዳም እግር፤ አንድም ከፍ ብሎ ከራሱ ሊፈጥራት ይችል እንደ ነበር መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ሔዋን ከአዳም ጎን መፈጠሯ ባልና ሚስት እርስበርስ በመተጋገዝ፣ በመተሳሰብና በመደጋገፍ መኖር እንደሚገባቸው ያመላክታልና፡፡

አዳምም ከእንቅልፉ ሲነቃ ከጎኑ ሔዋንን በአገኘ ጊዜ “ይህቺ አጥንት የአጥንቴ ፍላጭ፣ ይህቺ ሥጋ የሥጋዬ ቁራጭ ናትና፤ ከኔ ከባሏ ተገኝታለችና ሚስት ትኹነኝ” በማለት ለሚስትነት እንደ ተሰጠችው አረጋግጦ ተናግሯል፡፡ ስለዚህም ወንድ አባትና እናቱን ትቶ ሚስቱን ተከትሎ ይሔዳል፡፡ ቈላ ብትወርድ፣ ደጋ ብትወጣ አብሯት ይወርዳል፤ ይወጣል፡፡ አንድ ክብር በመውረስና በመልበስ፤ እንደዚሁም በግብር (በሩካቤ ሥጋ) ሁለቱም አንድ አካል ይኾናሉ፡፡ ወንድ ቢወለድ ‹‹ያንተ ነው፤›› ሴት ብትወለድ ‹‹ያንቺ ናት›› አይባባሉምና፡፡ ዳግመኛም ሁለት ኾነው አንድ ልጅ ያስገኛሉና፤ እንደዚሁም ከእናት ደም፣ ከአባት ዘር ተከፍሎ አንድ ሰው እንዲወለድ ምክንያት ናቸውና እግዚአብሔር ‹‹አንድ አካል ይኾናሉ›› አለ (ዘፍ. ፩፥፳፰፤ ፪፥፳-፳፬)፡፡

ይቆየን