ሱባዔና ሥርዓቱ – ክፍል ሦስት (የመጨረሻ ክፍል)

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ነሐሴ ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ሱባዔ በዘመነ ሐዲስ

በዘመነ ሐዲስ በሰፊው የሚወሳው ሱባዔ ቅዱሳን ሐዋርያት ከነሐሴ ፩ – ፲፬ ቀን ድረስ የገቡት ሱባዔ ነው፡፡ ይህ ሱባዔ ተሰውሮ የነበረውን የቅድስት ድንግል ማርያምን ትንሣኤ ተረድተው በረከቷን ለመሳተፍ አብቅቷቸዋል፡፡ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሦስት ዓመት በእናት በአባቷ ቤት፣ ዐሥራ ሁለት ዓመት በቤተ መቅደስ፣ ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ከጌታችን ጋር፣ ዐሥራ አምስት ዓመት በወንጌላዊው በዮሐንስ ቤት ከኖረች በኋላ በ፷፬ ዓመቷ ጥር ፳፩  ቀን ዐርፋለች፡፡ በሐዋርያት ውዳሴ፣ ዝማሬና ማኅሌት ነሐሴ ፲፬ ቀን ከተቀበረች በኋላ ነሐሴ ፲፮ ተነሥታ በይባቤ መላእክት ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡ ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ ‹‹ተለዐለት እምድር ወበህየ ነበረት ዘምስለ ወልዳ በየማነ አብ ወመንፈስ ቅዱስ፤ እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ዐረገች፡፡ በሰማይም ከልጅዋ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች፤›› በማለት ወደ ሰማይ ማረጓንና በክብር መቀመጧን ተናግሯል፡፡ ከሺሕ ዓመት በፊትም አባቷ ዳዊት ‹‹በወርቅ ልብስ ተጐናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች›› ሲል የተናገረው ትንቢት ይህንኑ የእመቤታችንን ክብር የሚመለከት ነው (መዝ. ፵፬፥፱)፡፡

‹ፍልሰት› የሚለው ቃል የእመቤታችን ሥጋ ከጌቴሴማኒ ወደ ገነት መፍለሱን፣ በኋላም በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ከነበረበት መነሣቱን ለማመልከት የሚነገር ነው (ወላዲተ አምላክ በኢትዮጵያ፣ ገጽ 68)፡፡ ለሐዋርያት የእመቤታችን የዕረፍትና የዕርገት ምሥጢር የተገለጠላቸው በሱባዔ ነው፡፡ ይህን መሠረት በማድረግ በየዓመቱ ጾመ ፍልሰታ ወይም የሐዋርያት ሱባዔ ከሊቅ እስከ ደቂቅ በቤተ ክርስቲያን ይታሰባል፡፡ ምእመናን የተቻላቸው ከሰው ርቀው፣ ሱባዔ ገብተው፣ ያልተቻላቸው ደግሞ በአጥቢያቸው የውዳሴዋና የቅዳሴዋን ትርጕም ይሰማሉ፤ በሰዓታቱና በቅዳሴው ሥርዓት ይሳተፋሉ፡፡ በእመቤታችን አማላጅነት፣ በልጇ ቸርነት በምድር ሳሉ በሃይማኖት ጸንተው ለመኖር፤ በኋላም ለመንግሥቱ እንዲያበቃቸው እግዚአብሔርን ደጅ ይጠናሉ፡፡

የሱባዔ ዓይነቶች

፩. የግል ሱባዔ (ዝግ ሱባዔ)

የግል ሱባዔ አንድ ሰው ብቻውን ኾኖ በቤትና በአመቺ ቦታ የሚይዘው ማንም ሰው ሳያየው በግሉ የጸሎት በዓቱን ዘግቶ በሰቂለ ሕሊና ኾኖ ፈጣሪው ብቻ እንዲያየውና እንዲሰማው በኅቡዕ የሚፈጽመው ሱባዔ ነው (ማቴ. ፮፥፭-፲፫)፡፡ በዚህ ዓይነት መንገድ አንድ ሰው ሱባዔ ሲገባ ዘጋ ይባላል፡፡ ዝግ ሱባዔ የያዘ ሰው የሚያስፈልገውን ነገር ይዞ ወደ በዓቱ ከተከተተ በኋላ ሱባዔው እስኪፈጸም ድረስ ከሰው አይገናኝም (መዝ. ፻፩፥፮-፯)፡፡

፪. የማኅበር ሱባዔ

የማኅበር ሱባዔ የሚባለው ካህናት፣ ምእመናን ወንዶችና ሴቶች፣ ሽማግሌዎችና ወጣቶች በአንድነት ኾነው በቤተ ክርስቲያንና አመቺ በኾኑ ቦታዎች ዅሉ ተሰባስበው የሚገቡት ሱባዔ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩ ምእመናን ወደ እግዚአብሔር ቤት በመሔድ ይጸልዩ ነበር (፩ኛ ሳሙ. ፩፥፩፤ መዝ. ፻፳፩፥፩፤ ሉቃ. ፲፰፥፲-፲፬)፡፡ በሐዲስ ኪዳንም የሐዋርያት ተከታዮች የኾኑ መነኮሳት፣ ካህናትና ምእመናን በገዳማት፣ በአድባራት፤ የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች፣ የጽዋ ማኅበርተኞች ስለ ማኅበራቸው ጥንካሬና ከማኅበርተኞቹ መካከል አንዱ ችግር ሲገጥመው የማኅበር ሱባዔ ይይዛሉ፡፡

፫. የዐዋጅ ሱባዔ

የዐዋጅ ሱባዔ በአገር ላይ ድንገተኛ አደጋ፣ አባር ቸነፈርና ጦርነት ሲከሠት፤ እንደዚሁም ለማኅበረ ምእመናን አስጊ የኾነ መቅሠፍት ሲመጣ፤ እግዚአብሔር መዓቱን በምሕረት፣ ቍጣውን በትዕግሥት እንዲመልስ የሚያዝ የሱባዔ ዓይነት ነው፡፡ ለዚህ ዓይነቱ ሱባዔ የነነዌ ሰዎችና በፋርስ በስደት ይኖሩ የነበሩ እስራኤላውያን ምሳሌዎች ናቸው፡፡ የነነዌ ሰዎች የዮናስን ስብከት ሰምተው ከሊቅ እስከ ደቂቅ ድረስ ለሦስት ቀናት ከመብል ከመጠጥ ተከልክለው በመጾም በመጸለያቸው እግዚአብሔር መዓቱን በምሕረት፣ ቍጣውን በትዕግሥት መልሶላቸዋል፡፡ ሌላው በፋርስ በስደት ይኖሩ የነበሩ አይሁድ በአስቴር ትእዛዝ የያዙት ሱባዔ ተጠቃሽ ነው፡፡ በዚያን ዘመን አይሁድ በያሉበት እንዲገደሉ አርጤክስስ በማዘዙ ከዚህ የጅምላ ጭፍጨፋ ለመዳን አይሁድ በዐዋጅ ሱባዔ ገብተዋል፡፡ አስቴር ገብታ ንጉሡን ስታናግረው ሌላው ሕዝብ በውጭ ዐዋጅ ዐውጀው ሱባዔ ገብተው ፈጣሪያቸውን ተማጽነዋል (አስቴር ፬፥፲፮-፳፰)፡፡

በአገራችን ኢትዮጵያም ይህን የመሰለ የዐዋጅ ሱባዔ በዐፄ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት ተደርጓል፡፡ ፋሽስት ጣልያን አገራችንን በመውረር ኢትዮጵያን ቅኝ ተገዥ ለማድረግ ድንበሯን አልፎ በመጣበት ወቅት ንጉሠ ነገሥት ምኒልክ ‹‹ጉልበት ያለህ በጉልበትህ፣ ጉልበት የሌለህ በጸሎትህ ርዳኝ›› በማለት የዐዋጅ ሱባዔ መያዛቸው ይነገራል፡፡ በዚህም መሠረት በየገዳማቱ ምሕላ ተይዟል፡፡ ንጉሡም ታቦተ ጊዮርጊስን ይዘው ዓለምን እጅግ ባስደነቀ መልኩ ጥቁሮችን ለነጻነታቸው እንዲነሣሡ የሚያስችል ፋና ወጊ የኾነ ድል አግኝተው አገራችንን ለቅኝ ግዛት ያሰበውን ፋሽስት ጣልያንን ማሸነፋቸው በከፍተኛ ስሜት የምናስታውሰው ታሪክ ነው፡፡

የሱባዔ ቅድመ ዝግጅት

ሱባዔ መግባት የሚፈልግ ምእመን ቅድመ ዝግጅት ማድረግ ይኖርበታል፡፡ ያለምንም ዝግጅት ሱባዔ መግባት ለፈተና ያጋልጣል፡፡ ስለዚህ ቅድመ ሱባዔ (ሱባዔ ከመግባት አስቀድሞ)፣ ጊዜ ሱባዔ (በሱባዔ ጊዜ) እና ድኅረ ሱባዔ (ከሱባዔ በኋላ) ዝግጅት ማድረግ አስፈላጊ ነው፡፡

ቅድመ ሱባዔ (ሱባዔ ከመግባት አስቀድሞ)

በመጀመሪያ ሱባዔ የምንገባበትን ምክንያት ለይቶ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ አንድ ሰው ሱባዔ የሚገባበትን ዓላማ ለይቶ ካስቀመጠ ከሱባዔ በኋላ የሚጠበቀውን ነገር ማግኘት አለማግኘቱን ይረዳል፡፡ ይህ ሳይኾን ሱባዔ ቢገባ ከሱባዔው በኋላ የጠየቀው ነገር ስለሌለ ድካሙ ዋጋ ያጣል፡፡ ስለዚህ ሱባዔ ከመግባታችን በፊት ለምን ሱባዔ ለመግባት እንዳሰብን ለይተን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ ሱባዔ ለመግባት የወሰንበትን ምክንያት ከለየን በኋላ ምክንያታችንን ይዘን የንስሐ አባታችንን ማማከር ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም በምክረ ካህን መጓዝ ክርስቲያናዊ ግዴታ ነውና፡፡ ከዚህም ባሻገር በአባትነታቸውና በሕይወት ልምዳቸው ምን ማድረግ እንደሚገባን ምክር ለማግኘት እገዛ ያደርጉልናል፡፡ ስለኾነም ቅድመ ሱባዔ ከንስሐ አባት ጋር መመካከር ተገቢ ነው፡፡

ለምሳሌ አንድ ሰው በሱባዔ ወቅት ልዩ ልዩ ፈተናዎች ቢያጋጥሙት የተሰጠውን ምክር በመጠቀም ፈተናውን ለመቋቋም ይችላል፡፡ እንደዚሁም የንስሐ አባቱ በሱባዔ ወቅት በጸሎት እንዲያስቡት መማከር ከአንድ ምእመን ይጠበቃል፡፡ ሱባዔ ለመግባት ስናስብ ለምን ያህል ቀናት መቆየት እንዳለብን መወሰን ያስፈልጋል፡፡ ሱባዔ ከዚህ እስከዚህ እቆያለሁ ብለን ዕቅድ የምንይዝበት ነው፡፡ እንደ ዓቅማችንና እንደ ችሎታችን መጠን ከዚህ ቀን እስከዚህ ብለን በመወሰን ሱባዔ መግባት ተገቢ ነው፡፡ ለምሳሌ ምንም ዓይነት ልምድ ሳይኖረው አንድ ሰው በዋሻ እዘጋለሁ ቢል ከጥቅሙ ጉዳቱ ሊያመዝን ይችላል፡፡ ምክንያቱም በሱባዔ ወቅት ፈተና ስለሚበዛ የሚመጣበትን ፈተና መቋቋም ባለመቻሉ ሱባዔውን ሊያቋርጥ ይችላል፡፡ ስለዚህ ቅድመ ሱባዔ ዓቅምንና ችሎታን አገናዝቦ መወሰን ተገቢ ነው፡፡

ሌላው ቅድመ ሱባዔ ለሱባዔ ተስማሚ የኾነ ወቅትና ቦታ መምረጥ ተገቢ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን በአብዛኛው ሱባዔ የሚገባው አጽዋማትን ተከትሎ ነው፡፡ ስለዚህ ሱባዔ የምንገባበት ወቅት የጾም ወቅት መኾን አለመኾኑን መለየት ያስፈልጋል፡፡ በአጽዋማት ወቅት የሚያዝ ሱባዔ ለተሐራሚ ጠቀሜታው እጅግ የጐላ ነው፡፡ ምክንያቱም በአጽዋማት ወቅት ብዙ አባቶች ሱባዔ ስለሚይዙ ከአባቶች ጸሎት ጋር ልመናችንና ጸሎታችን ሊያርግ ይችላል፡፡ ስለዚህ ወቅትን ለይቶ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡

ከዚህ ላይ ከወርኃ አጽዋማት ውጭ ሱባዔ አይያዝም ለማለት አይደለም፡፡ አንድ ሰው ፈተና ከአጋጠመው በማንኛውም ጊዜ ሱባዔ ሊገባ ይችላል፡፡ ከዚህም ባሻገር ሱባዔ የምንይዝበትን ቦታ መምረጥ አለብን፡፡ ለሱባዔ የምንመርጣቸው ቦታዎች ለፈተና የሚያጋልጡ መኾናቸውን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ ይኸውም ሱባዔ ከተገባ በኋላ ሕሊናችን እንዳይበተን እገዛ ያደርግልናል፡፡ ጫጫታና ግርግር የሚበዛበት ቦታ በሰቂለ ሕሊና ለመጸለይ አያመችም፡፡ ስለዚህ ሱባዔ የምንይዝባቸው ቦታዎች ከከተማ ራቅ ያሉ ገዳማትና አድባራት ቢኾኑ ተመራጭ ነው፡፡

ጊዜ ሱባዔ (በሱባዔ ጊዜ)

በጸሎት ሰዓት ዓምድና ግድግዳ ሳይደገፉ፣ መቋሚያ ሳይዙ በሁለት እግር ቀጥ ብሎ በመቆም መጸለይ ይኖርብናል፡፡ እንደዚሁም ፊትን ወደ ምሥራቅ መልሶ መቆም ወዲያና ወዲህ፣ ወደ ግራ፣ ወደ ቀኝ አለመዟዟር፤ በሰፊሐ እድ፣ በሰቂለ ሕሊና ኾኖ መጸለይ ይገባል (መዝ. ፭፥፫)፤ መዝ. ፻፴፫፥፪፤ ዮሐ. ፲፩፥፵፩)፡፡ በመጨረሻም ሱባዔ የገባ ሰው ሱባዔውን ሳይጨርስ ወይም ሱባዔውን አቋርጦ ከማንም ሰው ጋር ፈጽሞ መገናኘት የለበትም፡፡

ድኅረ ሱባዔ (ከሱባዔ በኋላ)

ለቀረበ ተማኅጽኖ እግዚአብሔር የሚያደርግልንን ነገር መጠበቅ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሔር ላቀረብንለት ምልጃና ጸሎት እንደ ልባችን መሻት፣ እንደ እርሱ ቸርነት እርሱ በወደደ ጊዜ ያደርግልናል፡፡ ከሱባዔ በኋላ መጀመሪያ የምናገኘው የሕሊና ሰላምን ነው፡፡ ይህም ትልቅ የአምላክ ስጦታ ነው፡፡ ከዚህ ባሻገር ሱባዔ ገብተን ያሰብነውን ካላገኘን ዳግመኛ ተዘጋጅተን እስከ መጨረሻው ሰዓት መጽናትና መማጸን ይኖርብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሱባዔና ሥርዓቱ – ክፍል ሁለት

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ነሐሴ ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

፫. የተሰወረ ምሥጢር እንዲገለጥልን

በዘመነ ብሉይ እግዚአብሔር ለአንዳንድ ነገሥታት ራእይ በማሳየት ምሥጢርን ይሰውርባቸው ነበር፡፡ ለምሳሌ የግብጹን ፈርዖን፣ የባቢሎኑን ናቡከደነፆርና ብልጣሶርን መጥቀስ ይቻላል (ዘፍ. ፵፩፥፲፬-፴፮፤ ዳን. ፬፥፱፣ ፭፥፬)፡፡ እነዚህ ነገሥታት በግል ሕይወታቸውም ኾነ በአጠቃላይ ለሕዝቡ ትምህርት በሚኾን መልኩ ወደ ፊት ሊፈጸም የሚችል ራእይ ቢያዩም ቅሉ ራእዩን በትክክል ተረድተው እንዲህ ይኾናል የማለት ብቃት አልነበራቸውም፡፡ ስለዚህም በዘመናቸው ይኖር የነበሩትን ነቢያት ሱባዔ ገብተው የሕልማቸውን ትርጉም እንዲነግሩአቸው ይማጸኑ ነበር፡፡

ነቢያትም ሱባዔ በመግባት ነገሥታቱ ያዩትን የምሥጢረ ሥጋዌ ነገርና የመንግሥታቸውን አወዳዳቅ ገልጠው ያስረዱ ነበር (ዳን. ፭፥፳፰)፡፡ እንደዚሁም ቅዱሳን በየራሳቸው ያዩት ራእይ ምሥጢር ሲከደንባቸው የራእዩ ምሥጢርና ትርጕም እንዲገለጥላቸው ሱባዔ ይገባሉ፡፡ እግዚአብሔርም በንጽሕና ኾነው የገቡትን ሱባዔ ተመልክቶ ምሥጢር ይገልጥላቸዋል፡፡ ለምሳሌ ነቢዩ ዕዝራ የመጻሕፍትን ምሥጢር እንዲገልጥለት ሱባዔ ቢገባ የጠፉትን የብሉይ ኪዳን መጻሕፍት ዳግም መልሶ ለመጻፍ ችሏል (መዝ. ፰፥፩)፡፡ ከዚህ ቀጥለን የቀደምት አበውን ሱባዔና ያስገኘላቸውን ጥቅም በአጭር በአጭሩ እንመለከታለን፤

ሱባዔ አዳም

አዳም ትንቢት በመናገርና ሱባዔ በመቍጠር የመጀመሪያውን ሥፍራ ይይዛል፡፡ ምክንያቱም በገነት ሰባት ዓመት ከአንድ ወር ከዐሥራ ሰባት ቀን በተድላና በደስታ ከኖረ በኋላ ሕግ በማፍረሱና የፈጣሪውን ቃል በመጣሱ ያለ ምንም ትካዜና ጕስቁልና ከሚኖርበት ዔደን ገነት ተባርሯል (ዘፍ. ፫፥፳፬)፡፡ እርሱም ፈጣሪው እንዲታረቀው፣ በዐይነ ምሕረት እንዲጐበኘው፣ ቅዝቃዜው ሰውነትን ከሚቈራርጥ ባሕር ውስጥ በመግባት ለሠላሳ አምስት ቀን (አምስት ሱባዔ) ሱባዔ ገብቷል፡፡ በባሕርዩ የሰውን ልጅ እንግልት የማይወድ መሐሪው እግዚአብሔርም የአዳምን ፍጹም መጸጸት ተመልክቶ ‹‹በሐሙስ ዕለት ወበመንፈቃ ለዕለት እትወለድ እምወለተ ወለትከ ወእድኅክ ውስተ መርህብከ ወእትቤዘወከ በመስቀልየ ወበሞትየ፤ በአምስት ቀን ተኩል ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ፤›› ብሎ የድኅነት ተስፋ ሰጠው፡፡

አዳም የተሰጠውን ተስፋ ይዞ በዓለመ ሥጋ ለዘጠኝ መቶ ሠላሳ አመት ከኖረ በኋላ መከራና ችግር ከበዛበት ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡ በወንጀል ተከሶ በወኅኒ የተፈረደበት ሰው ከእስር የሚፈታበትን ዕለት በማውጣት በማውረድ ወራቱንና ዓመታቱን እንደሚቈጥር፣ አዳምም በሲኦል የነፍስ ቅጣት ካለበት ሥፍራ ይኖር ስለ ነበር የተሰጠውን ተስፋ በማሰብ ሱባዔውን እየቈጠረ ‹‹የተናገረውን የማያስቀር፣ የማያደርገውን የማይናገር ጌታዬ፤ እነሆ ‹አድንሃለሁ› ብሎ የገባልኝ ዘመን ተፈጸመ፤ ሰዓቱ አሁን ነው፤›› እያለ ሲያወጣ ሲያወርድ ቸሩ አምላክ ሰው ኾኖ ሥጋ ለብሶ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ‹‹ተንሥኡ ለጸሎት፤ ለጸሎት ተነሡ፡፡ ሰላም ለኵልክሙ፤ ሰላም ለእናንተ ይኹንን!›› በማለት አዳምን ከነልጅ ልጆቹ ነጻ አውጥቶታል፡፡

ሱባዔ ሔኖክ

ጻድቁ ሔኖክ የያሬድ ልጅ ሲኾን፣ በትውልድ ከአዳም ሰባተኛ ነው፡፡ እርሱም በሕይወቱ እግዚአብሔርን ደስ ለማሰኘት ቤት ንብረቱን በመተው በሱባዔና በትሕርምት እግዚአብሔርን አገልግሏል፡፡ ፍጹም አካሔዱን ከእግዚአብሔር ጋር ያደረገ ሰው በመኾኑም በብሉይ ኪዳንም ኾነ በሐዲስ ኪዳን የመልካም ግብር ባለቤት መኾኑ ተመስክሮለታል፡፡ ‹‹ሔኖክም አካሄዱን ከእግዚአብሔር ጋር አደረገ›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ዘፍ. ፭፥፳፪)፡፡ ይህም በመኾኑ እግዚአብሔር የሱባዔውን ዋጋ ቅዱስ መንፈሱን በረድኤት ስለ አሳደረበት ትንቢት ተናግሯል፤ ሱባዔ ቈጥሯል፡፡ በሰማይ ተሰውሮ ሳለ ስለ ቅዱሳን መላእክት፣ ስለ መሲሕ ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ስለ ፀሐይና ጨረቃ አመላለስ (ዑደት) የሚተርክ በስሙ የተሰየመውን መጽሐፍ ጽፏል (ዘፍ. ፭፥፳፩-፳፬፤ ሔኖክ ፩፥፱፤ ይሁዳ፣ ቍ. ፲፬)፡፡

ሱባዔ ሔኖክ የሚባለው ነቢዩ ሔኖክ በመሥፈርት የቈጠረው ሱባዔ ነው፡፡ መሥፈርቱ (ማባዣ ቍጥሩ) 35 ሲኾን 35 በ19 ሲበዛ ውጤቱ 685 ዓመት ይኾናል፡፡ 685ን በ12 ስናባዛው ደግሞ 7980 ይኾናል፡፡ ይኸውም ሐሳብ የሚያስረዳው ስለ ክርስቶስ ምጽአት ነው፡፡ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ እስከ አሁኑ ዘመን ድረስ 7509 ይኾናል፡፡ ይህን ለማረጋገጥ በ5500 ዓመት ላይ 2009 ዓመትን መደመር ነው፡፡ በነቢዩ ሔኖክ አቈጣጠር መሠረት ምጽአተ ክርስቶስ በ7980 ይኾናል፡፡ ከላይ ሔኖክ የቀመረውን ቍጥር ይዘን ከ7980 ዓመት ላይ አሁን ያለንበትን ዘመን (7509) ስንቀንስ 471 ዓመት እናገኛለን፡፡ ስለዚህ በሔኖክ ሱባዔ መሠረት ምጽአተ ክርስቶስ ሊኾን 471 ዓመት ይቀረዋል ማለት ነው፡፡

ሱባዔ ነቢያት

እግዚአብሔር ለአዳም የገባውን ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ ቀደምት ነቢያት በተነሡበት ዘመን ቅደም ተከተል ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው መኾንና ዳግም መምጣት ትንቢት ተናግረዋል፤ ሱባዔም ቈጥረዋል (መዝ. ፵፱፥፫፤ ኢሳ. ፯፥፲፬፤ ዘካ. ፲፫፥፮፣ ፲፬፥፩)፡፡ የአንዱ ነቢይ ትንቢታዊ ንግግርና ሱባዔ በአነጋገርና በአቈጣጠር ከሌላኛው ነቢይ ይለያል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ትንቢቱን ሲያናግር፣ ምሳሌውን ሲያስመስል ጐዳናው ለየቅል በመኾኑ ነው፡፡ ‹‹ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጐዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናገረ፤›› እንዲል (ዕብ. ፩፥፩)፡፡ የአቈጣጠር ስልታቸውና የሱባዔ መንገዳቸው ቢለያይም ዓላማና ግባቸው ግን አንድ ነው፡፡

ሱባዔ ዳንኤል

ነቢዩ ዳንኤል ምድቡ ከዐበይት ነቢያት ነው፡፡ እስራኤል ወደ ባቢሎን ሲማረኩ ተማርኮ ወደ ባቢሎን ወርዷል፡፡ እርሱም ስለ ክርስቶስ መምጣት ትንቢት ተናግሯል፤ ሱባዔም ቆጥሯል፡፡ ከትንቢቶቹ መካከልም፡- ‹‹ሰብአ ሰንበታተ አድሞሙ ለሕዝብከ፤ ሰባ ሰንበት ወገኖችህን ቅጠራቸው፤›› የሚለው ይገኝበታል፡፡ ይኸውም ኢየሱስ ክርስቶስ ከ490 ዓመት በኋላ ሰው መኾኑን የሚያመለክት ትንቢት ነው፡፡ እንደዚሁም ‹‹እስከ ክርስቶስ ንጉሥ ትትሐነጽ መቅደስ ወእምዝ ትትመዘበር፤ እስከ ንጉሥ ክርስቶስ ድረስ መቅደስ ትታነጻለች፤ በኋላም ትፈርሳለች፤›› በማለት የብሉይ ኪዳንን ማለፍና የሐዲስ ኪዳንን መመሥረት ተናግሯል፡፡ የዳንኤል የሱባዔ አቈጣጠር ስልቱም በዓመት ሲኾን ይኸውም ሰባቱን ዓመት አንድ እያሉ መቍጠር ነው፡፡ ይህም ‹ሱባዔ ሰንበት› ይባላል፡፡ ዳንኤል ሱባዔ ከቈጠረበትና ትንቢት ከተናገረበት ጊዜ ጀምሮ ክርስቶስ እስከ ተወለደበት ድረስ 490 ዓመት ይኾናል፡፡ መሥፈርቱ (ማባዣው) ሰባት ስለኾነ ሰባትን በሰባ ብናባዛው 490ን እናገኛለን፡፡ ይኸውም ነቢዩ ሱባዔ ከቈጠረና ትንቢት ከተናገረ ከ490 ዓመት በኋላ ክርስቶስ መወለዱን ያመለክታል፡፡

በአጠቃላይ ከላይ የተመለከትናቸው ቅዱሳን ነቢያት አካሔዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር በማድረግ ሱባዔ ገብተው በትሕርምት በመኖራቸው ድንቅ የኾነውን የክርስቶስን ልደትና ዳግም ምጽአት ለመተንበይ ችለዋል፡፡ ሱባዔ መግባት የራቀውን የማቅረብ፣ የረቀቀውን የማጉላት ጸጋን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያስገኝ መንፈሳዊ ጥበብ መኾኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

ሱባዔ ዳዊት

ነቢዩ ዳዊት ከእስራኤል ነገሥታት ዅሉ ታላቅና ተወዳጅ ንጉሥ ነበር፡፡ ዘመነ መንግሥቱ 1011 – 971 ከክርስቶስ ልደት በፊት እንደ ነበር ይታመናል፡፡ ነቢዩ ዳዊት ልበ አምላክ እንደ መኾኑ ብዙ ትንቢት ተናግሯል፡፡ ሱባዔ ቈጥሯል፡፡ ይኸውም ‹ቀመረ ዳዊት› በመባል ይታወቃል፡፡ ‹‹እስመ ዐሠርቱ ምእት ዓመት በቅድሜከ ከመ ዕለት እንተ ትማልም ኀለፈት፤ ሺሕ ዓመት በፊትህ እንዳለፈች እንደ ትናንት ቀን ናት፤›› (መዝ. ፹፱፥፬) የሚለውን ኃይለ ቃል መምህራን ሲቈጥሩት 1140 ዓመት ይኾናል፡፡ ይኸውም በጌታ ዘንድ 1140 ዓመት እንደ አንድ ቀን እንደ ኾነ ነቢዩ ዳዊት ተናግሯል፡፡ ይህም ለዳዊት ሱባዔ መቍጠሪያ (መሥፈሪያ) ኾኖ አገልግሏል፡፡ 1140 በ7 ሲባዛ 7980 ዓመት ይሆናል፡፡ ይህም ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ በ7980 ዓመት ክርስቶስ ዳግም እንደሚመጣ የሚያመለክት ነው፡፡

ይቆየን

ሱባዔና ሥርዓቱ – ክፍል አንድ

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ነሐሴ ፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

አሁን ያለንበት ወቅት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ጾመ ፍልሰታን የሚጾሙበት፣ ሱባዔ የሚገቡበት ጊዜ ነውና ወቅቱን የሚመለከት ትምህርት ይዘን ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ!

ሱባዔ ምንድን ነው?

‹ሱባዔ› በሰዋስዋዊ ትርጕሙ ‹ሰባት› ማለት ነው፡፡ ሱባዔ በመንፈሳዊ አተረጓጐም አንድ ሰው ‹‹ከዚህ ቀን እስከዚህ ቀን በጸሎት ከፈጣሪዬ ጋር እገናኛለሁ›› ብሎ የሚያቅደው መንፈሳዊ ዕቅድ ነው፡፡ ሰባት ቍጥር በእስራኤላውያን ዘንድ በሥራም በቃልም የሚገለጥ ፍጹም ቍጥር ነው፡፡ ለምሳሌ፡- ፈጣሬ ዓለማት እግዚአብሔር በሰባተኛው ቀን ሥነ ፍጥረትን ከመፍጠር ማረፉ፣ ለጸሎት የሚተጉ ምእመናን በቀን ለሰባት ጊዜ ማመስገናቸው የሰባት ቍጥርን ፍጹምነት ያመለክታል (ዘፍ. ፪፥፪፤ መዝ. ፻፲፰፥፷፬)፡፡ ከዚህ አንጻር አንድ ሰው ለሰባት ቀናት ቢጾም አንድ ሱባዔ ጾመ ይባላል፡፡ ለዐሥራ አራት ቀን ቢጾም ደግሞ ሁለት ሱባዔ ጾመ እያለ እየጨመረ ይሄዳል፡፡

ሱባዔ መቼ ተጀመረ?

ሱባዔ የተጀመረው ከውድቀት በኋላ በመጀመሪያው ሰው በአዳም ነው፡፡ ቅዱሳን መላእክት አዳምን ጸሎት መጸለይን እንዳስተማሩት የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ይናገራሉ፡፡ መላእክት ለአዳም የጊዜያትን ስሌት አስተምረውት ነበር (ቅዳሴ ማርያም ትርጓሜ)፡፡ አዳም ጥፋቱን አምኖ ከባሕር ውስጥ ሱባዔ በመግባቱና በመጸለዩ እግዚአብሔር በማይታበል ቃሉ ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ፤›› ሲል ቃል ኪዳን ገብቶለታል (መጽሐፈ ቀሌምጦስ፣ አንቀጽ አራት)፡፡

ሱባዔ ለምን?

የሰው ልጅ ኃጢአት በሚስማማው የሥጋ ሰውነቱ ዘወትር ፈጣሪውን ይበድላል፡፡ በፈጸመው በደል ሕሊናው ይወቅሰዋል፤ ይጸጸታል፡፡ በመጀመሪያ ደፍሮ በሠራው ኃጢአት በኋላ ይደነግጣል፡፡ ይህ በማንኛውም ሰብአዊ ፍጡር ሕሊና ውስጥ የሚፈራረቅ ጉዳይ፡፡ በዚህ ጊዜ የፈጣሪውን ይቅርታ ለማግኘት ያስባል፤ ይተክዛል፡፡ ‹‹ሰውነቴ በእግዚአብሔር ሕግ ደስ ይለኛል፡፡ ነገር ግን በብልቶቼ ባለ በኃጢአት ሕግ የሚማርከኝ ሌላ ሕግ አያለሁ፡፡ እኔ ምንኛ ጐስቋላ ሰው ነኝ? ለዚህ ሞት ከተሰጠ ሰውነት ማን ያድነኛል?›› እንዳለ ቅዱስ ጳውሎስ (ሮሜ. ፯፥፳፪፥፳፭)፡፡ ሰው በደፋርነቱ የኃያሉን አምላክ ትእዛዝ በተላለፈ ጊዜ የትካዜ ሸክም ሲያስጨንቀው ሸክሙን የሚያቃልልበትና የሚያስወግድበት መንፈሳዊ ጥበብ ከቸሩ ፈጣሪ ተሰጥቶታል፡፡ ይኸውም በጥቂት ድካመ ሥጋ ጸጋ እግዚአብሔር የሚያገኝበት ሥርዓት ሱባዔ ነው፡፡ ከጥንት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ አንድ ሰው በትካዜ ሸክም መንፈሱ ሲታወክ የነፍስና የሥጋ ጸጥታውን ለመመለስና ለማስከበር መጾምና መጸለይ ግድ ይኾንበታል፡፡ በዚህ ጊዜ አመክሮ (ሱባዔ) ይገባል፡፡ ሱባዔ የሚገባውም ከዚህ በታች ለተዘረዘሩት መሠረታዊ ጉዳዮች ነው፤

፩. እግዚአብሔርን ለመማጸን

ሰው ሱባዔ ከሚገባባቸው መሠረታዊ ጉዳዮች አንዱ እግዚአብሔርን ለመማጸን ነው፡፡ ማንኛውም ሰው ሱባዔ ሲገባ በቁርጥ ወደ ፈጣሪው የሚያቀርበው ተማኅጽኖ ሊኖረው ይገባል፡፡ ምንም የምንጠይቀው (የምንማጸነው) ነገር ሳይኖር ሱባዔ ብንገባ የምናገኘው መልስ አይኖርም፡፡ ያለ ምንም ቅድመ ኹኔታና ዝግጅት ሱባዔ የሚገቡ ሰዎች ከሱባዔ በኋላ ምን እንደ ተመለሰላቸው የሚያውቁት ነገር ስለማይኖር ሱባዔ በመግባታቸው የሚያገኙት ጥቅም የለም፡፡ ስለዚህ ሱባዔ ከመግባታችን በፊት ሱባዔ የምገባው ለምንድን ነው? በማለት ራሳችንን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡ ለምሳሌ አንድ ክርስቲያን በግል ሕይወቱ ዙሪያ ስለ አገር ሰላም፣ ስለ ጓደኛው ጤና፣ ወዘተ. ስለ መሳሰሉት ጉዳዮች ፈጣሪውን በጸሎት ይማጸናል፡፡ በዚህ ጊዜ በግል ሕይወቱም ኾነ በአገር ጉዳይ ለገባው ሱባዔ ወዲያውኑ መልስ ሊያገኝ ይችላል፡፡ መልሱ ሊዘገይም ይችላል፡፡ በዚህ ጊዜ ከተሐራሚው ትዕግሥት ይጠበቃል፡፡ ‹‹ለምን ላቀረብኹት ጥያቄ ቶሎ ምላሽ አልተሰጠኝም?›› በማለት ማማረርና እግዚአብሔርን መፈታተን ተገቢ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበትና ለሚማጸነውም መልስ የሚሰጥበት የራሱ ጊዜ አለውና፡፡

ከዚህ ላይ በጓደኛው ውድቀት ምክንያት ሱባዔ ገብቶ በአንድ ሳምንት ውስጥ መልስ ያገኘ የአንድ ገዳም አገልጋይን ታሪክ መመልከት ተገቢ ነው፡፡ አኃው (ወንድሞች) ለተልእኮ በወጡበት ወቅት አንዱን ድቀት አግኝቶት ያድሯል፡፡ በነጋታው ‹‹ወንድሜ እኔ ድቀት አግኝቶኛልና እንግዲህ ወዲህ ተመልሼ ከዚያ ገዳም አልሔድም፤ ዓለሙን መስዬ እኖራለሁ›› አለው፡፡ እርሱም ‹‹እኔም እንጂ አግኝቶኛል፤ ይልቁንስ ሔደን ኃጢአታችንን ለመምህረ ንስሐችን ነግረን፤ ቀኖናችንን ተቀብለን እንደ ቀደመው ኾነን እንኖራለን›› ብሎ አጽናንቶ ይዞት ሔደ፡፡ ሔደው ለመምህረ ንስሐቸው ነግረው ቀኖናቸውን ተቀብለው አንድ ሱባዔ፣ ቀኖና እንዳደረሱ ‹‹ሰረይኩ ለከ በእንተ ዘኢገብረ እኁከ፤ ኃጢአት ስላላደረገው ወንድምህ ይቅር ብዬሃለሁ›› የሚል ድምፅ አሰምቶታል (ዜና አበው)፡፡

ከላይ ታሪካቸው የሰፈረው የገዳም አገልጋዮች ለአገልግሎት በተላኩበት አገር አንዱ ድቀት አግኝቶት በዝሙት ሲወድቅ ጓደኛው እንደ እርሱ ድቀት እንዳገኘው አድርጐ ጓደኛውን በማጽናናት ወደ ገዳም በመመለስ አንድነት ኾነው ሱባዔ ይገባሉ፡፡ አንድ ሱባዔ (ሰባት ቀን) እንደ ጨረሱም የወደቀው አገልጋይ ‹‹ኃጢአት ሳይሠራ ለአንተ ብሎ ሱባዔ ስለገባው ወንድምህ ስል ይቅር ብዬሃለሁ›› የሚል ፈጣን ምላሽ ከእግዚአብሔር ዘንድ አግኝቷል፡፡ ስለዚህ በግል ሕይወትም ኾነ በጓደኛችን ሕይወት ዙርያ ሱባዔ ስንገባ እግዚአብሔር ፈጣን ወይም የዘገየ መልስ ሊሰጠን ስለሚችል በትዕግሥት መጠባበቅ ይኖርብናል፡፡

፪. ከቅዱሳን በረከት ለመሳተፍ

ቅዱሳን አባቶች እና ቅዱሳት እናቶች የተጋደሉትን ተጋድሎ በማዘከር ቃል ኪዳን በተሰጣቸው ገዳማትና አድባራት የሚገባ ሱባዔ የቅዱሳኑን በረከት ተካፋይ ያደርጋል፡፡ ቅዱሳን በሚጋደሉበት ቦታ ‹‹ከወንዶችና ከሴቶች ልጆች ይልቅ የሚበልጥ ስም እሰጣቸዋለሁ፤ የማይጠፋ የዘላለም ስም እሰጣቸዋለሁ፤›› (ኢሳ. ፶፮፥፮) በማለት እግዚአብሔር ቃል ኪዳን ስለ ገባላቸው ሱባዔ በመግባት ከበረከታቸው መሳተፍ ይቻላል፡፡ በጾመ ነቢያት የነቢያትን፣ በጾመ ሐዋርያት የሐዋርያትን፣ በጾመ ፍልሰታ የእመቤታችንን በረከት ለመሳተፍ ሱባዔ መግባት ከጥንት ጀምሮ የነበረና ወደ ፊትም የሚኖር የቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ነው፡፡

ዛሬ ይህን ሥርዓት በመከተል የልዩ ልዩ ቅዱሳንን በረከት ለመቀበል (ለመሳተፍ) የቅዱሳን ዐፅም ካረፈበት ገዳም በጾም፣ በጸሎት፣ በጉልበትም ገዳማትን በማገልገል የቅዱሳንን በረከት ደጅ የሚጠኑ ምእመናንና መናንያን በየገዳማቱ እጅግ በርካታ ናቸው፡፡ ይኸውም በመጽሐፈ ነገሥት ካልዕ ፪፥፱ ላይ እንደ ተመለከተው ነቢዩ ኤልሳዕ መምህሩን ኤልያስን በማገልገል የኤልያስ በረከት በኤልሳዕ ላይ እጥፍ ኾኖ አድሮበታል፡፡ ይህን አብነት በማድረግ በየገዳማቱ በትሕርምት (ዅሉንም ነገር በመተው) የሚኖሩ መናንያንን ያገለገሉበትን ገዳም አባት በረከት በእጥፍ እየተቀበሉ ለሌሎችም የሚያቀብሉ አባቶች በየገዳማቱ አሉ፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ኾኖ በስመ ገዳማዊ የምእመናንን ገንዘብ የሚዘርፉና የእውነተኛ መነኮሳትንና መናንያንን የተቀደሰ ሕይወት የሚያጐድፉ ሰዎች መኖራቸውንም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

ይቆየን

ዘመነ ክረምት – ክፍል አራት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በክፍል ሦስት ዝግጅታችን ከሐምሌ ፲፱ እስከ ነሐሴ ፱ ቀን ድረስ ያለው ሁለተኛው ክፍለ ክረምት መብረቅ፣ ነጐድጓድ፣ ባሕር፣ አፍላግ፣ ጠል እንደሚባል በማስታወስ ከወቅቱ ጋር ተያያዥነት ያለው ትምህርት አቅርበን ነበር፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ደግሞ ቀጣዩን ክፍል ይዘን ቀርበናል፡፡ መልካም ንባብ!

፫. ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዓይነ ኲሉ

ከነሐሴ ፲ እስከ ፳፯ ቀን (ከማኅበር እስከ አብርሃም) ድረስ ያለው ሦስተኛው የዘመነ ክረምት ክፍለ ጊዜ (ንዑስ ክፍል) ‹ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያት፣ ዓይነ ኲሉ› ይባላል፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ብቻ ሳይኾን የሰማይ አዕዋፍ፣ የምድር አራዊትና እንስሳት ሳይቀሩ እግዚአብሔርን አምነው በተስፋ መኖራቸው የሚዘከርበት፤ በተጨማሪም በዝናም አማካይነት በዙርያቸው ያለው የውኃ መጠን ከፍ ሲልላቸው ደሴቶች ዅሉ በልምላሜ ማሸብረቃቸው የሚነገርበት ክፍለ ክረምት ነው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያን የሚነገረው ቃለ እግዚአብሔር ዅሉ በእነዚህ ምሥጢራት ላይ ያተኮረ ነው፡፡ ከዚህ ቀጥለን ስለ ዕጕለ ቋዓት፣ ደሰያትና ዓይነ ኲሉ በቅደም ተከተል ማብራሪያ ለመስጠት እንሞክራለን፤

ዕጕለ ቋዓት

‹ዕጕል፣ ዕጓል› ማለት ‹ልጅ›፤ ‹ቋዕ› ደግሞ ‹ቍራ› ማለት ነው፡፡ ‹ቋዕ› የሚለው ቃል በብዙ ቍጥር ሲገለጽም ‹ቋዓት› ይኾናል፡፡ በዚህ መሠረት ‹ዕጕለ ቋዓት› የሚለው የግእዝ ቃላት ጥምረትም (ሐረግ) ‹የቍራ ልጆች (ግልገሎች፣ ጫጩቶች)› የሚል ትርጕም አለው፡፡ በዚህ ወቅት በቤተ ክርስቲያን የቍራ ጫጩቶች አስተዳደግ ከምእመናን ሕይወት ጋር ተነጻጽሮ ይነገራል፡፡ ይህም እንዲህ ነው፤ የቍራ ጫጩት ከእንቍላሉ ፍሕም መስሎ ይወጣል፡፡ በዚህ ጊዜ እናትና አባቱ ባዕድ ነገር የተወለደ መስሏቸው ትተውት ይሸሻሉ፡፡ እርሱም በራበው ጊዜ ምግብ ፍለጋ አፉን ይከፍታል፡፡ በዚህ ሰዓት ርጥበት የሚፈልጉ ተሐዋስያን ወደ አፉ ይገባሉ፡፡ ከዚያም አፉን በመግጠም ይመገባቸዋል፡፡ እንደዚሁም ተሐዋስያን በአጠገቡ ሲያልፉ በእስትንፋሱ (በትንፋሹ) እየሳበ ይመገባቸዋል፡፡ የቍራ ጫጩት እስከ ፵ ቀን ድረስ እንደዚህ እያደረገ ከቆየ በኋላ ቀስ በቀስ ፀጕር ያበቅላል፤ ከዚህ በኋላ በመልክ እነርሱን እየመሰለ ስለሚመጣ እናት አባቱ ተመልሰው ይከባከቡታል፡፡ ይህ የቍራ ዕድገትና ለውጥም እግዚአብሔር ፍጡራኑን የማይረሳ አምላክ እንደ ኾነ፣ ፍጥረቱንም በጥበቡ እየመገበ እንደሚያኖራቸው ያስገነዝበናል፡፡

ቅዱስ ዳዊት ይህን የቍራ የዕድገት ደረጃና የእግዚአብሔርን መግቦት በተናገረበት መዝሙሩ ‹‹ወሐመልማለ ለቅኔ ዕጓለ እመሕያው ዘይሁቦሙ ሲሳዮሙ ለእንስሳ ወለዕጕለ ቋዓት እለ ይጼውዕዎ፤ ለሰው ልጆች ጥቅም ለምለሙን የሚያበቅል፤ ለእንስሳትና ለሚለምኑት የቍራ ጫጩቶች ምግባቸውን የሚሰጣቸው እርሱ ነው›› ሲል ይዘምራል (መዝ. ፻፵፮፥፱)፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን በትርጓሜያቸው እንደ ገለጹት ይህ ኃይለ ቃል እግዚአብሔር አምላክ ለእርሱ ለሚገዙ የሰው ልጆች እኽሉን፣ ተክሉን የሚያበቅልላቸው፤ ለእንስሳቱና ለአዕዋፍ ምግባቸውን የሚሰጣቸው እርሱ እንደ ኾነ ያስረዳል፡፡ ‹‹… ወለዕጕለ ቋዓት እለ ይጼውዕዎ፤ … ለሚለምኑት ለቍራ ጫጩቶች›› የሚለው ሐረግም አዕዋፍ፣ ምግብ እንዲያዘጋጅላቸው እግዚአብሔርን እንደሚለምኑትና እርሱም ልመናቸውን እንደሚቀበላቸው ያስገነዝበናል፡፡ በመዝሙረ ዳዊት አንድምታ ትርጓሜ እንደ ተጠቀሰው ‹‹ወለዕጕለ ቋዓት እለ ይጼውዕዎ›› የሚለው ሐረግ ‹‹… እለ ኢይጼውዕዎ›› ተብሎ ሊነገር ይችላል፤ ይህም የቍራ ጫጩቶች አፍ አውጥተው ባይነግሩትም እንኳን እርሱ ፍላጎታቸውን ዐውቆ የዕለት ምግባቸውን እንደሚያዘጋጅላቸው የሚያመለክት ምሥጢር አለው፡፡ ምሥጢሩን ወደ እኛ ሕይወት ስናመጣውም እግዚአብሔር አምላክ ስሙን የሚጠሩትንም የማይጠሩትንም፤ ‹‹የዕለት እንጀራችንን ስጠን›› እያሉ የሚማጸኑትንም የማይጸልዩትንም በዝናም አብቅሎ፣ በፀሐይ አብስሎ ሳያደላ ዅሉንም በቸርነቱ እንደሚመግባቸው ያስተምረናል፡፡ ‹‹… እርሱ ለክፎዎችና ለደጎች ፀሐይን ያወጣልና፤ ለጻድቃንና ለኃጥአንም ዝናምን ያዘንማልና፤›› እንዳለ ጌታችን በወንጌል (ማቴ. ፭፥፵፭)፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ቍራዎችንና የሌሎችንም አዕዋፍ አኗኗር ምሳሌ በማድረግ ስለ ምድራዊ ኑሮ ሳይጨነቁ እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ መኖር እንደሚገባን በቅዱስ ወንጌል አስተምሮናል፡፡ እንዲህ ሲል፤ ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ፡፡ ነፍስ ከመብል ሰውነትም ከልብስ ይበልጣልና፡፡ ቍራዎችን ተመልከቱ፤ አይዘሩም፤ አያጭዱምም፡፡ ዕቃ ቤትም ወይም ጎተራ የላቸውም፤ እግዚአብሔርም ይመግባቸዋል፡፡ እናንተ ከወፎች ትበልጡ የለምን? … አበቦችን እንዴት እንዲያድጉ ተመልከቱ፤ አይደክሙም፤ አይፈትሉምም … ዛሬ ያለውን፣ ነገም ወደ እቶን የሚጣለውን በሜዳ የኾነውን ሣር እንዲህ የሚያለብሰው ከኾነ፣ እናንተ እምነት የጐደላችሁ! እናንተንማ ይልቁን እንዴት? … የምትበሉትን የምትጠጡትንም አትፈልጉ፤ አታወላውሉም፡፡ ይህንስ ዅሉ በዓለም ያሉ አሕዛብ ይፈልጉታልና፡፡ የእናንተም አባት ይህ እንዲያስፈልጋችሁ ያውቃል፡፡ ዳሩ ግን መንግሥቱን ፈልጉ፤ ይህም ዅሉ ይጨመርላችኋል፤›› (ሉቃ. ፲፪፥፳፪-፴፩)፡፡

ከዚህ ላይ ‹‹… ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ …›› የሚለው ኃይለ ቃል እንደ እንስሳት ሳትሠሩ እግዚአብሔር ምግብ እንዲሰጣችሁ ለምኑት ማለት እንዳልኾነ ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ኃይለ ቃሉን ለማብራራት ያህል የሰው ልጆች ከእንስሳት ከምንለይባቸው ባሕርያት አንደኛው ሠርተን መብላት መቻላችን ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም የታታሪነትንና የሠርቶ ማደርን ጥቅም እንጂ ሳይሠሩ ተቀምጦ መብላትን አላስተማሩንም፡፡ በብዙ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች የሰው ልጅ እጁ ከሥራ መለየት እንደማይገባው ተገልጿል፡፡ ለምሳሌ አባታችን አዳም ከሳተ በኋላ በምድር ጥሮ፣ ግሮ እንዲኖር ተፈርዶበታል፡፡ ይህንም ‹‹… የምድርንም ቡቃያ ትበላለህ፡፡ ወደ ወጣህበት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ›› ከሚለው ኃይለ ቃል ለመረዳት እንችላለን (ዘፍ. ፫፥፲፰-፲፱)፡፡ በተመሳሳይ መልኩ እግዚአብሔር አማላክ አዳምን ከዔደን ገነት ያስወጣው የተገኘባትን መሬት ያርስ ዘንድ መኾኑም ተጠቅሷል (ዘፍ. ፫፥፳፫)፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ ሠራቶ አዳሪ ፍጥረት መኾኑን የሚያመላክት ምሥጢር ነው፡፡ ጠቢቡ ሰሎሞንም ‹‹አንተ ታካች! እስከ መቼ ትተኛለህ? ከእንቅልፍህስ መቼ ትነሣለህ? ጥቂት ትተኛለህ፤ ጥቂት ታንቀላፋለህ፡፡ ትተኛም ዘንድ ጥቂት እጅህን ታጥፋለህ፡፡ እንግዲህ ድህነትህ እንደ ወንበዴ፣ ችጋርህም ሰይፍ እንደ ታጠቀ ሰው ይመጣብሃል›› በማለት የሰው ልጅ እንቅልፍን (ስንፍናን) ካበዛና ካልሠራ ክፉ ድህነት እንደሚመጣበት ተናግሯል (ምሳ. ፮፥፱-፲)፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ደግሞ ‹‹ከእናንተ ሊሠራ የማይወድ አይብላ›› በማለት ሥራ የማይወድ ሰው ምግብ መሻት እንደሌለበት አስረድቷል (፪ኛ ተሰ. ፫፥፲)፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ ስንፍናን የሚያወግዝ፣ ሥራን ደግሞ የሚያበረታታ ኾኖ ሳለ ‹‹ለምንድን ነው መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ …› ሲል ያስተማረው?›› የሚል ጥያቄ ሊነሣ ይችላል፡፡ ለጥያቄው ምላሽ ለመስጠት ያህል ቃሉ አትጨነቁ ማለቱ ‹‹ለሥጋዊ ጉዳይ ቅድሚያ አትስጡ፤ እየሠራችሁ እግዚአብሔርን በጸሎት ጠይቁ›› ሲለን ነው፡፡ የሰው ልጅ ሠራተኛ ፍጥረት ቢኾንም ዝናም አልጥልለት ሲል፤ የዘራበት መሬት ሳያበቅል ሲቀር፤ የወር ደመወዙ ሲዘገይ፤ እኽል የሚሸምትበት ገንዘብ ሲያጣ፤ ወዘተ. በመሳሰሉት ፈተናዎች ውስጥ በኾነ ጊዜ ምን ልበላ ነው? ልጠጣ ነው? ልጆቼ እንዴት ሊኾኑብኝ ነው? ዛሬን እንዴት ላልፍ ነው? በሚሉትና በመሳሰሉት የጭንቀትና የተስፋ መቍረጥ ስሜቶች ሳይያዝ የዕለት ጕርሱን፣ የዓመት ልብሱን ይሰጠው ዘንድ የጠፋውን ዝናም ማምጣት፤ የደረቀውን ዘር ማለምለም፤ ባዶ የኾነውን ቤት መሙላት የሚቻለውን እግዚአብሔርን (እርሱን) በእምነት ኾኖ በጸሎት ይጠይቀው ለማለት መድኀኒታችን ክርስቶስ ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ›› ብሎናል፡፡ ሐሳቡ ሲጠቃለል የሰው ልጅ ይርበኛል፣ ይጠማኛል ማለቱን ትቶ በእግዚአብሔር አምሳል መፈጠሩን በማሰብ ዓቅሙ በሚችለው ዅሉ እንዲሠራ፤ የጐደለውን እንዲሞላለት ደግሞ ጸሎቱን ወደ ፈጣሪው እንዲያቀርብ ሲያስረዳ ጌታችን ‹‹ለነፍሳችሁ በምትበሉት፣ ወይም ለሰውነታችሁ በምትለብሱት አትጨነቁ›› በማለት አስተምሯል፡፡

ይህም የሰው ልጅ ለሚበላው፣ ለሚጠጣው መጨነቅ እንደማይገባውና እየሠራ ሙሉ ተስፋውን በእግዚአብሔር ላይ ማድረግ እንዳለበት፤ ከዅሉም በላይ ለምድራዊው ኑሮው ድሎት ሳይኾን ሰማያዊውን መንግሥት ለመውረስ መትጋት እንደሚጠበቅበት ያስገነዝባል፡፡ ስለዚህም አምላካችን እንዳስተማረን ስለምንበላውና ስለምንጠጣው ሳይኾን ስለ በጎ ምግባርና ስለ ዘለዓለማዊው መንግሥት መጨነቅ ይገባናል ማለት ነው፡፡ ራሳችንን ለመንግሥተ እግዚአብሔር በሚያበቃ የጽድቅ ሥራ ካስገዛን ለሥጋችን የሚያስፈልገን ምድራዊ ዋጋም አብሮ ይሰጠናልና፡፡ ‹‹ወዘእንበለ ንስአሎ ይሁብ ፍትወተነ ዘእምፈቃዱ፤ ሳንለምነው ልባችን የተመኘውን በፈቃዱ የሚሰጠን እርሱ ነው›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (መጽሐፈ ኪዳን)፡፡ ‹‹ይሰጠዎ ወይሰምዖ ጸሎቶ ለኵሉ ለዘሰአሎ እግዚአ ለሰንበት አምላከ ምሕረት ያርኁ ክረምተ በበዓመት ይሰምዑ ቃሎ ደመናት፤›› በማለት ቅዱስ ያሬድ በዘመነ ክረምት መዝሙሩ ያቀረበው ምስጋናም ይህንኑ እውነት የሚያንጸባርቅ ኃይለ ቃል ነው፡፡ ትርጕሙም፡- ‹‹እግዚአብሔር አምላክ የለመነዉን ፍጥረት ዅሉ ጸሎት ተቀብሎ ምላሽ ይሰጣል፡፡ የሰንበት (የፍጥረታት) ጌታ እርሱ የምሕረት (የይቅርታ) አምላክ ነው፡፡ የምሕረት አምላክ በመኾኑም በየዓመቱ (በየጊዜው፣ በየዘመኑ) ወርኃ ክረምትን (ወቅቶችን) ያፈራርቃል፡፡ ደመናትም (ፍጥረታትም) ቃሉን ይሰማሉ (ትእዛዙን ይፈጽማሉ)፤›› ማለት ነው፡፡

ይቆየን

የበረዶ ናዳ በገዳመ ናዳ

ፈለገ ብርሃን ናዳ ቅድስት ማርያም

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ነሐሴ ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ፈለገ ብርሃን ናዳ ቅድስት ማርያም ገዳም በምዕራብ ጐጃም ሀገረ ስብከት ሜጫ ወረዳ ቤተ ክህነት በጉታ ቀበሌ ልዩ ስሙ ናዳ በሚባል ቦታ ይገኛል፡፡ ገዳሙ በዐሥራ ስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተመሠረተ ሲኾን፣ ታቦተ ሕጉም ከጣና ቂርቆስ ገዳም እንደ መጣ ይነገራል፡፡ ለብዙ ዓመታት ‹እንቍርቍሪት ጽዮን› እየተባለ ሲጠራ የቆየው ገዳሙ፣ ከዓመታት በኋላ ‹ናዳ ማርያም› ተብሎ ተሰይሟል፡፡ ናዳ የተባለበት ምክንያትም የሚከተለው ታሪክ ነው፤ በአካባቢው ዋናው ገዳም የሚባል ሌላ ጥንታዊ ገዳም ነበረ፡፡ በዚህ ገዳምም አባ ናዳ የሚባሉ አባት ይጸልዩበት ነበር፡፡ በዙርያውም በርካታ መነኮሳት ነበሩ፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ናዳ በመሰላል ወጥተው የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ጣርያ ሲከድኑ መሰላሉ አንሸራቷቸው ወደቁ፡፡ በዚህ ጊዜ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ተገልጻ በደኅና ካነሣቻቸው በኋላ ‹‹ወዳጄ አባ ናዳ ሆይ! ለዘለዓለም ስምህ በዚህ ቦታ ይጠራ›› በማለት ቃል ኪዳን ሰጠቻቸው፡፡ አባ ናዳም ገዳሙን አሁን ባለበት አኳኋን እንዲጸና አደረጉ፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ‹እንቍርቍሪት› የሚለው ስያሜ ተለውጦ ‹ናዳ ማርያም› ወይም ‹ናዳ ጽዮን› ተብሎ መጠራት ጀመረ፡፡

በአዲስ መልክ እየተገነባ የሚገኘው የክብረ ደናግል ናዳ ቅዱስ ላልይበላ ሕንጻ

ፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም በየጊዜው የመጥፋት ፈተና ቢያጋጥመውም በእግዚአብሔር ፈቃድ እንደ ገና እየተመለሰ እስካሁን ድረስ ክብሩ እንደ ተጠበቀ፤ ወሰኑ እንደ ተከበረ፤ ልማቱም እንደ ቀጠለ ነው፡፡ ገዳሙ የአብነት ትምህርት ማእከል በመኾኑና ዙርያው በምንጭ በመከበቡ የተነሣ ከ፲፱፻፹፮ ዓ.ም ጀምሮ በጊዜው የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በነበሩት ብፁዕ አቡነ በርናባስ ፈቃድ ‹ፈለገ ብርሃን› ተብሎ ተሰይሟል፡፡ ገዳሙ በዚህ መልኩ እየሰፋ መጥቶ በአሁኑ ሰዓት አገልግሎቱም ጉባኤ ቤቱም በአግባቡ እየተከናወነ ነው፡፡ ከፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በተጨማሪ የክብረ ደናግል ናዳ ቅዱስ ላልይበላ እና የጋፈራ ደብር ቅዱስ ይምርሃነ ክርስቶስ ሕንጻ አብያተ ክርስቲያናት ለመነኮሳቱ እና ለአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን አገልግሎት በመስጠት ላይ ናቸው፡፡ በአሁኑ ሰዓትም የክብረ ደናግል ቅዱስ ላሊበላ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በዘመናዊ ጥበብ በአዲስ መልክ በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡

(ምንጭ፡- ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ፤ ገዳሙ ያሳተመው ብሮሸር)

ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ

ምንኵስናን ከሊቅነት፣ አባትነትን ከሥራ ጋር አስተባብረው በያዙት በሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ አማካይነት ከ፲፱፻፸፱ ዓ.ም ጀምሮ እስካሁን ድረስ በገዳሙ የትርጓሜ መጻሕፍት እና የቅኔ ትምህርት በመሰጠት ላይ ነው፡፡ ከሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ ጉባኤ ቤት ተምረው በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፍ ተሰማርተው ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉ ካህናትና መምህራንም እጅግ በርካታ ናቸው፡፡ የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ፣ የትርጓሜ መጻሕፍትና የቅኔ መምህሩ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ እንደ ገለጹልን ገዳሙ ከሚታወቅባቸውና ከሚደነቅባቸው ተግባራት አንደኛው የልማት ሥራ ሲኾን፣ ልማቱ በስፋት የተጀመረውም በ፲፱፻፹ ዓ.ም ነው፡፡ በገዳሙ አካባቢ የሚገኘውን በጎርፍ የተሸረሸረ ሸለቆ በመከባከብ የተጀመረው የልማት ሥራ ውጤታማ ኾኖ ገዳሙን በፌዴራል ሁለተኛ፤ በክልል ደግሞ አንደኛ ደረጃ እንዲያገኝና የክብር ሜዳልያ እንዲሸለም አድርጎታል፡፡

የገዳሙ አትክልት በከፊል

የገዳሙ መነኮሳት ከመንፈሳዊው አገልግሎታቸው ጎን ለጎን በጕልበታቸው ያለሙት የአትክልት እና የደን ይዞታ የተመልካች ቀልብን ይስባል፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ በዘንድሮው ዓመት (፳፻፱ ዓ.ም) በወርኃ ሰኔ በአካባቢው አንድ አዲስ ነገር ተከሠተ፡፡ ነገሩም እንዲህ ነው፤

ዘመነ ጸደይ (በልግ) ተፈጽሞ ዘመነ ክረምት ሊገባ ቀናት ብቻ ቀርተዋል፡፡ ክረምቱ በይፋ ባይገባም በገዳሙ ማኅበረ መነኮሳት እና በአካባቢው አርሶ አደሮች የክረምቱ ተግባር መከናወን ከጀመረ ቆየት ብሏል፡፡ ‹‹ሰኔ እና ሰኞ›› እንደሚባለው ወርኃ ሰኔ ልዩ የሥራ ወቅት ናትና ማኅበረ መነኮሳቱ እና የአካባቢው አርሶ አደሮች ለሥራ በመሯሯጥ ላይ ናቸው፡፡ ከላይ በሚወርደው ዝናም የራሰው፤ ከምድር በእርሻ ብዛት የለመለመው የፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም እና የአካባቢው መሬትም የተዘራበትን አብቅሎ አርሶ አደሮቹንና መነኮሳቱን አስደስቷል፡፡ በማጭድ ከሚታጨዱ ሰብሎች መካከል በቆሎን የመሰሉ አዝርዕት እየፋፉ ናቸው፤ በእጅ ከሚለቀሙት መካከል ደግሞ በተለይ ገዳሙን የልማት ማእከል ያደረጉት፤ በልዩ ልዩ ጊዜ ለሽልማት ያበቁት እና ስሙ ከፍ ከፍ እንዲል፣ በመንግሥት ዘንድም ልዩ ትኩረት እንዲሰጠው ያስቻሉት፤ ለበርካታ ዓመታት የተለፋባቸው የአቦካዶ፣ ሙዝ፣ ማንጎ፣ ብርቱካን፣ ፓፓዬ፣ ትርንጎ፣ ሎሚ እና የመሳሰሉ ጣፋጭ ተክሎች ፍሬያቸው ተንዠርግጎ አላፊ አግዳሚውን ያስጎመዣል፡፡ መነኮሳቱም የድካማቸውን ዋጋ በፍሬ አይተዋልና እየተደሰቱ ፍሬውን ለቅመው አንድም ለምግብ፣ አንድም ለሽያጭ ለማቅረብ ዝግጅት ላይ ናቸው፡፡

ማኅበረ መነኮሳቱ በሥራ ላይ

በ፳፻፱ ዓ.ም፣ ወርኃ ሰኔ በገባ በሃያ ሁለተኛው ቀን ከሰዓት በኋላ እንዲህ ኾነ፤ የገዳሙ መነኮሳት እና የአካባቢው አርሶ አደር ከፊሉ በአረም፣ ከፊሉም እንስሳትን በመጠበቅ ላይ ናቸው፡፡ ወቅቱ የዘመነ ክረምት ዋይዜማ ነውና ሰማይ በመባርቅቱ ድምፅ አጅቦ ዝናም ስጦታውን ወደ ምድር ሊልክ ተቻኩሏል፡፡ የሰማይ መልእክተኛ ደመናም ከውቅያኖሶች የቀዳውን ዝናም ተሸክሞ ወደ ምድር ሊያደርስ ተዘጋጅቷል፡፡ የዝናም መጓጓዣ ነፋስም ዝናሙን በመግፋት ደመናን እየተራዳው ነው፡፡ ምድር የሚወርደውን ዝናም ትጠጣ ዘንድ ሳስታ አፏን ከፍታ በመጠበቅ ላይ ናት፡፡ አዝርዕቱም ተዘርተው ያልበቀሉት በፍጥነት ለመብቀል፤ የበቀሉት ደግሞ ፍሬ ለመስጠት በአጠቃላይ በልምላሜ ለመረስረስ ወደ ላይ አሰፍስፈው ዝናሙን ይጠባበቃሉ፡፡ የመብረቁ ድምፅ፣ ብልጭታው፣ ጉርምርምታው እና የደመናው ጥቁረት ከወትሮው ጊዜ የተለየ ነው፡፡

ጥቁር ደመና በናዳ ሰማይ

ከቆይታ በኋላ በአንዲት ቅጽበት ማንም ያልጠበቀው ልዩ አጋጣሚ ተከሠተ፡፡ ለትምህርት ይኹን ለተግሣፅ፣ ለመዓትም ይኹን ለመቅሠፍት ብቻ ከእግዚአብሔር በቀር እኛ በማናውቀው ምክንያት በቀበሌው እና በገዳሙ ዙርያ ዝናምና ማዕበል የተቀላቀለበት ከባድ የበረዶ ናዳ ወረደ፡፡ በበረዶውም ከታላላቆቹ ጀምሮ እስከ ታናናሾቹ ድረስ ዕፀዋቱ በእሳት እንደ ተቃጠሉ ኩምሽሽ፣ እርር አሉ፡፡ ፍሬ ያፈሩ ተክሎችም ረገፉ፡፡ ገና ያልበቀሉትም በማዕበል ተወሰዱ፡፡ በፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም መነኮሳት ክንድ የተተከሉ የአቦካዶ፣ ሙዝ፣ ማንጎ፣ ብርቱካን፣ ፓፓዬ፣ ትርንጎ፣ ሎሚ እና የመሳሰሉ ጣፋጭ ተክሎች ፍሬያቸው ሙሉ በሙሉ ረገፈ፡፡ ያፈሉት ችግኝ ተጨፈጨፈ፡፡ የገበሬው፣ የመነኮሳቱ እና የእንስሳቱ መኖርያ ቤቶችም በበረዶ ፈራረሱ፡፡ የጠበል መጠመቂያ ቦታዎች ተናወጡ፡፡ የገዳሙ ንቦችም ከቀፎዎቻቸው ተሰደዱ፡፡ በዚህ የተነሣም በናዳ ማርያም ገዳም እና በአካባቢው ጸጥታ ነገሠ፡፡ ፍርኃትም ሰፈነ፡፡ የአካባቢው ነዋሪዎች እንደ ነገሩን የበረዶ ናዳው ሰኔ ሃያ ሦስት ቀንም ቀጥሎ ነበር፡፡ ጥፋቱ እንደ ገና ተደገመ፡፡ በአጠቃላይ ከሰባ ሄክታር በላይ የሚገመት ሰብል በበረዶው ናዳ ወደመ፡፡

ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ በበረዶ የተጎዳውን አትክልት ሲያስጐበኙ

ከጉዳቱ በኋላ የገዳሙ ዋና አስተዳዳሪ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ ደቀ መዛሙርታቸውን እና ማኅበረ መነኮሳቱን ይዘው ጸሎተ ምሕላ ያዙ፡፡ የደረሰው ጥፋት እንዳይደገም፤ የወደመው ሰብልም እንዲመለስ፤ መነኮሳቱ፣ የአብነት ተማሪዎች እና ምእመናኑ ተስፋ ቈርጠው እንዳይበተኑ እግዚአብሔርን በጸሎት ይማጸኑት ጀመር፡፡ ዋና አስተዳዳሪው የጠፋውን ሰብል እና በአካባቢው የደረሰውን ጉዳት ላለማየት ከበዓታቸው አልወጣም ብለው ነበር፡፡ ከዕለታት በኋላ ግን የአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን ከራሱ ይልቅ የገዳሙን ጉዳይ አስቀድሞ በጉልበት፣ በእርሻ ሥራ እና ዘር በድጋሜ በመዝራት መነኮሳቱን ለማገዝ መምጣቱን ሲሰሙ ምእመናኑን ለማበረታታት ከበዓታቸው ወጡ፡፡ እኛም አባን ያገኘናቸው በዚህ ወቅት ነበር፡፡ ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ ያዩት ነገር አዲስ ኾኖባቸዋል፡፡ ‹‹ከዚህ ገዳም ከመጣሁበት ጊዜ ጀምሮ እንደዚህ ዓይነት መዓት ደርሶ አያውቅም›› ይላሉ ሊቀ ብርሃናት የደረሰውን ጉዳት ከፍተኛነት ሲገልጹ፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ ከየአቅጣጫው ስልክ ሲደውልላቸውም ‹‹ደኅና ነን፤ አልተጎዳንም›› ይላሉ፡፡ ይህ ዅሉ ጉዳት ደርሶ እንዴት ለሰዎቹ ‹‹ደኅና ነን›› ይላሉ ብለን ስንጠይቃቸው ሊቀ ብርሃናት የሰጡን ምላሽ ‹‹እናትህ ሞተች ተብሎ አይነገርም›› የሚል ነበር፡፡ በእርግጥ እርሳቸው እንደ ነገሩን በሰው እና በእንስሳት ላይ የደረሰ ጉዳት አለመኖሩ ማኅበረ መነኮሳቱን አስደስቷቸዋል፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን የደከሙበት ሰብል እና አትክልት ከጥቅም ውጪ ኾኗል፡፡

በበረዶው ናዳ የረገፈው ፍራፍሬ በከፊል

የገዳሙ ደን እና ፍራፍሬ በበረዶ ናዳ ቢወድምም ዋና አስተዳዳሪው እና ማኅበረ መነኮሳቱ ብሩህ ፊታቸው አልቀዘቀዘም፡፡ ጉባኤ ቤቱም አልተፈታም፡፡ ገዳማውያኑ በተለመደው መንፈሳዊ ቋንቋ ‹‹እግዚአብሔር ይመስገን! ደኅና ነን … በአትክልት ላይ እንጂ በሰውና በእንስሳት ላይ የደረሰ ጉዳት የለም … ዅሉም ነገር ለበጎ ነው … ከዚህ የባሰ አያምጣ …›› እያሉ እነርሱን ለመጠየቅና ጉዳን ለማየት የሚመጡ ምእመናንን ያረጋጋሉ፡፡ ገዳማውያን እንዲህ ናቸው፤ ተበድለው እንዳልተበደሉ፤ ተጎድተው እንዳልተጎዱ፤ ተቸግረው እንዳልተቸገሩ በማመን በኾነው ነገር ዅሉ እግዚአብሔርን ያመሰግናሉ፡፡ በዚህ ዓመት በፈለገ ብርሃን ናዳ ማርያም ገዳም እና በአካባቢው በወርኃ ሰኔ የደረሰው ጉዳት እግዚአብሔርን ወደማማረር የሚገፋፋ ከባድ ፈተና ቢኾንም የገዳሙ አባቶች እና እናቶች ግን እግዚአብሔርን ማመስገናቸውን ለቅጽበት አላቋረጡም ነበር፡፡ በስበብ አስባቡ እግዚአብሔርን ና ውረድ የምንል ምእመናን ከእነርሱ ትምህርት ልንወስድ ይገባል፡፡

ከበረዶው ናዳ በኋላ የአካባቢው ምእመናን የገዳሙን መነኮሳት በጕልበት ሥራ ሲደግፉ

የገዳሙ መነኮሳትና የአብነት ተማሪዎች የወደፊት ኑሯቸው አሳሳቢ ነው፡፡ ምክንያቱም ‹‹የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን›› እያሉ እየጸለዩ ለምግብ እና ለአካባቢ ጥበቃ ይጠቅም ዘንድ በጉልበታቸው ወጥተው ወርደው ያበቀሉት ሰብል፣ ያለሙት አትክልት፣ ያፈሉት ችግኝ አሁን የለምና፡፡ የያዙት አማራጭ የተጎዳውን ሰብል እየገለበጡ እንደ ገና ዘር መዝራት ነው፡፡ ይህ መፍትሔ ግን በበቆሎ ፋንታ ዳጉሳንና የመሳሰሉ አዝርዕትን ለመተካት እንጂ ሙዙን፣ አቦካዶውን፣ ፓፓዬውን፣ ማንጎውን፣ ወዘተ የመሳሰሉ አትክልቶችን ለመተካት አያስችልም፡፡ እነዚህን ተክሎች ወደ ነበሩበት ለመመለስ የዓመታት ጥረትን ይጠይቃልና፡፡ ስለኾነም መላው ሕዝበ ክርስቲያን በገዳሙ እና በአካባቢው የደረሰውን ጉዳት ከግምት ውስጥ በማስገባት በሚቻለን አቅም ዅሉ አስቸኳይ ርዳታ ልናደርግላቸው ያስፈልጋል፡፡

የ አብነት ተማሪዎች በከፊል

በእርግጥ ማኅበረ ቅዱሳን ከገዳሙ ድረስ ልዑካንን በመላክ ለመነኮሳቱ የዘር መግዣ ይኾናቸው ዘንድ ለጊዜው የሃያ ሺሕ ብር የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል፡፡ ከቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል በደረሰን መረጃ ማኅበሩ ካሁን በፊት ለገዳሙ ካበረከተው ትራክተር (የእርሻና የዕቃ ማጓጓዣ መሣርያ) በተጨማሪ ለወደፊትም በቋሚነት ገዳሙን ለመደገፍ አቅዷል፡፡ በቦታው ተገኝተን ዋና አስተዳዳሪውን ባነጋገርንበት ወቅት ላደረገው የገንዘብ ድጋፍ ማኅበረ ቅዱሳንን፤ በጉልበት ሥራ በመራዳታቸው ደግሞ የአካባቢውን ሕዝበ ክርስቲያን አመስግነዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ለገዳሙ ያበረከተው የእርሻና የዕቃ ማጓጓዣ መሣርያ

ኾኖም ግን ይህ ድጋፍ በቂ አይደለምና ሌሎች በጎ አድራጊ ምእመናንም ቀለብ በመስጠት፣ ዘር በመግዛት፣ ልብስ በመለገስ እና ከፍ ሲል ደግሞ መኖርያ ቤት በማደስ በአጠቃላይ በሚቻላቸው ዅሉ ድጋፋቸውን እንዲያደርጉ ዋና አስተዳዳሪው ሊቀ ብርሃናት ቆሞስ አባ ይባቤ በላይ በገዳሙ ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ዝግጅት ክፍላችንም የገዳሙን መነኮሳት ከስደት፣ ጉባኤ ቤቱንም ከመዘጋት ለመታደግ፤ እንደዚሁም የልማት ቦታውን ወደ ጥንት ይዘቱ ለመመለስ ይቻል ዘንድ በተቻላችሁ አቅም ዅሉ ድጋፍ በማድረግ ከበረከቱ እንድትሳተፉ ይኹን ሲል መንፈሳዊ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡ በመጨረሻም የአባቶቻችን አምላክ ገዳሞቻችንን ከድንገተኛ አደጋ እና ከጥፋት፤ መነኮሳቱንና የአብነት ተማሪዎችንም ከስደት ይጠብቅልን እያልን ጽሑፋችንን አጠቃለልን፡፡

ማሳሰቢያ

ገዳሙን በገንዘብ ለመደገፍ የምትፈልጉ ምእመናን በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ መርዓዊ ቅርንጫፍ ሒሳብ ቍጥር፡- 10000 6261 1786 ገቢ ማድረግ የምትችሉ መኾኑን የገዳሙ ጽ/ቤት ያሳስባል፡፡ ተጨማሪ መረጃ ለማግኘትም በስልክ ቍጥር፡- 09 18 70 81 36 በመደወል የገዳሙን ዋና አስተዳዳሪ ማነጋገር ይቻላል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ጾመ ማርያም ለቤተ ክርስቲያን ሰላም

በዝግጅት ክፍሉ

ነሐሴ ፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ነቢያት የተነበዩትን ትንቢት፣ የቈጠሩትን ሱባዔ መሠረት በማድረግ ቅድስት ድንግል ማርያም በኪደተ እግሯ ኢትዮጵያን መባረኳን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያስተምራሉ፡፡ ‹‹የኢትዮጵያ ድኳኖች ሲጨነቁ አየሁ፤» (ዕንባ. ፫፥፯) በማለት ነቢዩ ዕንባቆም የተናገረው ቃለ ትንቢት እመቤታችን የኢትዮጵያን አውራጃዎች ለመባረኳ ማስረጃ መኾኑንም ሊቃውንቱ ያስረዳሉ፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ኢትዮጵያን ለእናቱ ዐሥራት አድርጐ በመስጠቱ፣ ከዅሉም በላይ ክርስቶስ ከእርሷ በለበሰው ሥጋ አማካይነት የመዳናችን ምሥጢር በመከናወኑ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ልዩ ፍቅር አለን፡፡

የአብነት ተማሪዎች በትምህርት ዓለም ከአንዱ ወደ ሌላ አገር እየተዘዋወሩ የአብነት ትምህርት ሲማሩ ‹‹በእንተ ስማ ለማርያም›› (ስለ ማርያም ስም) እያሉ ነው፡፡ ተማሪዎቹ የእመቤታችን ስም ስንቅ ምግብ ኾኗቸው ይጠቀሙበታል፡፡ የልጇ ግማደ መስቀል ወደ ከተመበት ግሼን ደብረ ከርቤ አምባ የሚጓዙ ምእመናንም ‹‹አንድ እፍኝ ሽምብራ አልያዝኩም ከቤቴ ስሟ ስንቅ ነው የእመቤቴ›› እያሉ በፍቅሯ ተማርከው ግብር ሰፍረው ዕጣን ቋጥረው ሱባዔ እየገቡ ይማጸኗታል፡፡ እርሷም ከልጇ ዘንድ ባገኘችው የአማላጅነት ጸጋ ምልጃቸውን በመቀበል ጸሎታችውን በማሳረግ የእናትነት ሥራዋን ስትፈጽምላቸው ኖራለች፡፡ ዛሬም እየሠራች ነው፤ ወደፊትም አማላጅነቷ አይቋጥም፡፡ እመቤታችን ከልጇ ያገኘችውን (የተቀበለችውን) ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ በአራቱ ማዕዘን ‹‹ሰአሊ ለነ ቅድስት፤ ቅድስት ሆይ ለምኝልን›› የማይላት ክርስቲያን የለም፡፡

በፍቅሯ ተደስተው በአማላጅነቷ ተማምነው ‹‹የእመቤቴ ፍቅሯ እንደ ሰማይ ከዋክብት፣ እንደ ምድር አሸዋ በዝቶልኝ፣ እንደ ልብስ ለብሼው፣ እንደ ምግብ ተመግቤው›› እያሉ ተማጽነው ልመናቸው ሠምሮ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊው፣ ቅዱስ ያሬድ ዘኢትዮጵያና አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ፣ አባ ጽጌ ድንግል ያዘጋጁላትን፤ የደረሱላትን የምስጋና መጻሕፍት በመድገም እመቤታችንን ዘወትር መማጸን የቀደምቱም ኾነ የዛሬዎቹ ገዳማውያንና ምእመናን ዕለታዊ ተግባር ነው፡፡ ጌታችን ለቀደሙት ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችን አማላጅ እና እናት እንድትኾናቸው በገቢርም በነቢብም ከአደራ ቃል ጋር እናቱን አስረክቧቸዋል፡፡ በገቢር በቃና ዘገሊላ የሰውን ችግር ፈጥና የምትረዳ ርኅርኅት እናት አማላጅ መኾኗን አሳይቷል፡፡ ለዚሁም ‹‹የወይን ጠጅ አልቆባቸዋል›› ብላ ያቀረበችው ቃለ ምልጃ ማስረጃ ነው፡፡ ጌታችን በመስቀል ላይ ሳለ ከእግረ መስቀሉ ሥር የነበረውን ቅዱስ ዮሐንስን ጠርቶ ‹‹እነኋት እናትህ፤›› ድንግል ማርያምን ደግሞ ‹‹እነሆ ልጅሽ፤›› በማለት ለቅዱሳን ሐዋርያትም ለእኛ ለምእመናንም እመቤታችንን በእናትነት ሰጥቶናል (ዮሐ. ፲፱፥፳፮)፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችንን በእናትነት ከተረከቧት ጊዜ ጀምረው ልጇ በዕርገት በአካለ ሥጋ ሲለይ በቤታቸው አኑረው እንደ ልጅ አገልግለዋታል፡፡ እርሷም የእናትነት ሥራዋን ሠርታላቸዋለች፡፡ በምድር የነበራት ቆይታ ሲፈጸምም ልጇ በአዳምና በልጆቹ ኃጢአት ምክንያት የፈረደውን፣ ለራሱም ያላስቀረውን ሥጋዊ ሞት እናቱ እንድትቀምስ አደረገ፡፡ በእናትነት የተረከቧት ቅዱሳን ሐዋርያትም መካነ ዕረፍት ለይተው በንጹሕ በፍታ ከፍነው በጌቴሴማኒ ቀበሯት፡፡ የእመቤታችን ሥጋዊ ዕረፍቷና የትንሣኤዋ ምሥጢር ከመ ትንሣኤ ወልዳ (እንደ ልጇ ትንሣኤ) ነውና ሙስና መቃብር ሳያገኛት ከሦስት ቀናት ሥጋዊ ዕረፍት በኋላ ከሞት ተነሥታ ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡ ስታርግ በዕለተ ቀብሯ ያልተገኘው ቅዱስ  ቶማስ ደመና ጠቅሶ በደመና ሠረገላ ሲመጣ ዕርገቷን ይረዳል፡፡ ለማስረጃነትም የተከፈነችበትን በፍታ (ጨርቅ) ይቀበላታል፡፡ ለቅዱስ ቶማስ የተገለጠው የዕረፍቷ ምሥጢር ለእነርሱም እንዲገለጥላቸው ቅዱሳን ሐዋርያት ቢማጸኑ እመቤታችን ዳግም ተገልጻላቸው ትንሣኤዋን ለማየት በቅተዋል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችንን በሁለት ሱባዔ ማግኘታቸውን መሠረት በማድረግ በየዓመቱ ከነሐሴ ፩ እስከ ፲፭ ቀን የፍልሰታን ጾም እንድንጾም በቤተ ክርስቲያናችን ቀኖና ተወስኗል፡፡ ይህ እመቤታችንን የምንማጸንበት ጾመ ፍልሰታ ቤተ ክርስቲያናችን መፍትሔ የምትፈልግባቸውን ጉዳዮች ለእመቤታችን የምታቀርብበት የጸሎት ወቅት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለሚገጥማት ችግር መፍትሔው ከእመቤታችን እጅ ላይ አለ ብለን እናምናለን፡፡ አባቶች ሱባዔ ገብተው እመቤታችንን እንደሚያገኟ ዅሉ፣ እርሷ የፍቅር እናት ናትና ፍቅርን አንድነትን እንድትሰጠን፤ የዶኪማስን ጓዳ እንደሞላች የጐደለውን ሕይወታችንን እንድትሞላልን ውዳሴዋን እየደገምን ድንግል ማርያምን መማጸን ያስፈልጋል፡፡

በውዳሴ ማርያም፣ በጸሎተ ማርያም የሚመካ በጕልበቱ አይመካም፡፡ ጊዜ ረዳኝ ብሎ በወገኖቹ ላይ ግፍን አይፈጽምም፡፡ ስለዚህ በእነዚህ የጾም ሳምንታት የእመቤታችን አማላጅቷ እና ጸጋዋ በአገራችን፣ በቤተ ክርስቲያናችን ላይ እንዲያድር በሱባዔ እንማጸናት፡፡ የሁለቱ ሳምንታት ሱባዔ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ዘወትር እየተገኘን ምሕላ የምናደርስበት፣ የተጣላነውን ይቅር ለእግዚአብሔር የምንልበት፣ የበደልነውን የምንክስበት፣ ሥጋውንና ደሙን የምንቀበልበት ወቅት መኾን አለበት፡፡ ነገር ግን ቀናቱን እየቈጠርን እስከተወሰነው ሰዓት ብቻ መጾም ብቻ በሕይወታችን መሠረታዊ ለውጥ አያመጣም፡፡ ከዚህ ላይ ማስተዋል የሚገባን ሌላው ቁም ነገር በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ሱባዔ ገብተን ውዳሴ ማርያም በደገምንበት አፋችን ሰው የምናማ፣ በሰው ሕይወት ገብተን የምንፈተፍት ከኾነ እመቤታችንን አናውቃትም፤ እርሷም አታውቀንም፡፡ እናም ‹‹መክፈልት ሲሹ መቅሠፍት›› እንደሚባለው በረከት ማግኘት ሲገባን መቅሠፍት እንዳይደርስብን ዅሉንም በሥርዓቱና በአግባቡ ልናከናውን ያስፈልጋል፡፡

በጾመ ፍልሰታም ኾነ በሌላ ጊዜ በቤተ ክርስቲያናችን የሚደረሰው ውዳሴ ማርያሙ፣ ሰዓታቱ፣ ቅዳሴው ከጠላት ሰይጣን ተንኮል የሚያድን፣ ከጥፋት የሚጠብቅ መንፈሳዊ የሰላም መሣርያ ነውና በጸሎቱ እንጠቀምበት፡፡ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚተጉ አባቶች እና ምእመናን በዚህ የእመቤታችንን ጾም ወቅት ለተሰደዱ፣ ለተራቡ፣ በፈተና ውስጥ ለሚገኙ ወገኖች ይጸልያሉ፤ ይማጸናሉ፡፡ እኛም ለእነርሱና ለሌችም ነዳያን ጸበል ጸሪቅ በማቅመስ ከበረከታቸው እንካፈል፡፡ በአጠቃላይ መንፈሳዊነት፣ እውነት፣ ቅድስና፣ ሕጋዊ አሠራር በቤተ ክርስቲያን እንዲሰፍን ዅላችንም በዚህ በጾመ ፍልሰታ ሱባዔ ተግተን ልንጸልይ ይገባል፡፡

                                                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ጾመ ፍልሰታ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሐምሌ ፴ ቀን ፳፻፱ .

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጥር ፳፩ ቀን በ፵፱ ዓ.ም በ፷፬ ዓመቷ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድና ድካም ባረፈች ጊዜ ቅዱሳን ሐዋርያት ሊቀብሯት ወደ ጌቴሴማኒ ይዘዋት ሔዱ፡፡ በዚህ ጊዜ አይሁድ ‹‹እንደ ልጇተነሣች፤ ዐረገች› እያሉ እንዳያውኩን በእሳት እናቃጥላት›› ብለው ሥጋዋን ሊያጠፉ በዓመፃ ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊም አጎበሩን ይዞ ሊያወርዳት ሲል የእግዚአብሔር መልአክ ሁለት እጆቹን ቀጣው፡፡ ከዚህ በኋላ እግዚአብሔር አምላክ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስን ጨምሮ እመቤታችንን በደመና ነጥቆ ወደ ገነት ወስዶ ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጣት፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም እመቤታችን ያለችበት ቦታ እንዲገለጥላቸው ባረፈች በስምንተኛው ወር ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ሱባዔ ገብተው እግዚአብሔርን በጸሎት መጠየቅ ጀመሩ፡፡

ከዚህ ላይ ‹‹ስምንት ወር ሙሉ ምን ይዘው ቆይተው ነሐሴ ላይ ሱባዔ ገቡ?›› የሚል ጥያቄ ሊነሣ ይችላል፡፡ በመሠረቱ ቅዱሳን ሐዋርያት ከስብከተ ወንጌል፣ ከጾም፣ ከጸሎት፣ ከገቢረ ተአምራት ተለይተው እንደማያውቁ መንፈሳዊ ሕይወታቸው ምስክር ነው፡፡ በመኾኑም እመቤታችን ካረፈችበት ቀን ከጥር ወር ጀምሮ እስከ ነሐሴ ድረስ ጥያቄያቸውንና ጸሎታቸውን ባያቋርጡም ከሰው ተለይተው ሱባዔ ገብተው ጾም ጸሎት የጀመሩት ግን ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ነው፡፡ ቀድሞስ የክብር ባለቤት የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ደቀ መዛሙርት ኾነው እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም ተሰውራባቸው እንዴት ዝም ብለው ይቀመጣሉ? ቅዱሳን ሐዋርያት ሁለት ሱባዔ (ዐሥራ አራት ቀናት) ካደረሱ በኋላም የነገሩትን የማይረሳ፣ የለመኑትን የማይነሳ እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታቸውን ሰምቶ ነሐሴ ፲፭ ቀን የእመቤታችንን ሥጋ ሰጥቷቸው በክብር ገንዘው በጌቴሴማኒ ቀብረዋታል፡፡ በሦስተኛው ቀንም እንደ ልጇ እንደ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡ ትንሣኤዋን ‹‹ከመ ትንሣኤ ወልዳ፤ እንደ ልጇ ትንሣኤ›› ያሰኘውም ይህ ምሥጢር ነው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ ሲሰብክ ቆይቶ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ እመቤታችን ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ወደ ሰማይ ስታርግ ጠፈር ላይ አገኛት፡፡ በዚህ ጊዜ ‹‹ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁን?›› ብሎ ትንሣኤዋን ባለማየቱ ኀዘን ስለ ተሰማው ከደመናው ይወድቅ ዘንድ ወደደ፡፡ ‹‹ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ›› እንዲል፡፡ እመቤታችንም ‹‹አይዞህ! አትዘን፤ ባልንጀሮችህ ሐዋርያት ያላዩትን ትንሣኤዬን አንተ አይተሃልና ደስ ይበልህ!›› ብላ ከሙታን ተለይታ መነሣቷንና ማረጓን ለሐዋርያት እንዲነግራቸው አዝዛ የያዘቸውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡ ከዚያም እርሷ ወደ ሰማይ ዐረገች፤ እርሱም ወደ ኢየሩሳሌም ወረደ፡፡ ቅዱስ ቶማስ ትእዛዟን ተቀብሎ በክብር ከተሰናበታት በኋላ ወደ ሐዋርያት ሔዶ እንዳልሰማ እንዳላየ መስሎ ‹‹የእመቤታችን ነገር እንደምን ኾነ?›› ሲል ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም ‹‹አግኝተን ቀበርናት›› ሲሉት ‹‹ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር እንዴት ይኾናል?›› አላቸው፡፡

በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ከዚህ በፊት የክርስቶስን ትንሣኤ መጠራጠሩን ጠቅሶ እየገሠፀ መከራከሩንና መጠራጠሩን ትቶ ስለ እመቤታችን መቀበር እነርሱ የሚነግሩትን ዅሉ አምኖ መቀበል እንደሚገባው ለቅዱስ ቶማስ አስረዳው፡፡ ቅዱስ ቶማስም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ሲሰማው ቆየ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም ተቈጥቶ የእመቤታችንን ክቡር ሥጋ ለቅዱስ ቶማስ ለማሳየት ሔዶ መቃብሯን ቢከፍት የእመቤታችንን ሥጋ ሊያገኘው አልቻለም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ ደንግጦ ቆመ፡፡ ቅዱስ ቶማስም ‹‹ወንድሞቼ! አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ከሙታን ተለይታ ተነሥታ ስታርግ አግኝቻታለሁ›› ብሎ እመቤታን የሰጠችውን ሰበን ለሐዋርያት ሰጥቷቸዋል፡፡ እነርሱም በእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤና ዕርገት እየተደሰቱ ሰበኑን ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንደሚያስተምሩን በቅዳሴ ጊዜ ሠራዒ ዲያቆኑ በሚይዘው መስቀል ላይ የሚታሠረው መቀነት መሰል ልብስ፤ እንደዚሁም አባቶች ካህናት በመስቀላቸው ላይ የሚያደርጉት ቀጭን ልብስና በራሳቸው ላይ የሚጠመጥሙት ነጭ ሻሽ የእመቤታችን ሰበን ምሳሌ ነው፡፡

በዓመቱ ቅዱሳን ሐዋርያት ‹‹ቶማስ የእመቤታችን ትንሣኤዋንና ዕርገቷን አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን?›› ብለው ከየሀገረ ስብከታቸው ተሰባስበው ሥጋዋን ይሰጣቸው (ያሳያቸው) ዘንድ ከነሐሴ ፩ ቀን ጀምረው ሱባዔ ይዘው ጌታችንን ጠየቁት፡፡ እርሱም ልመናቸውን ተቀብሎ ነሐሴ ፲፮ ቀን እመቤታችንን መንበር፤ ጴጥሮስን ተራዳኢ ካህን፤ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ እመቤታችንንም ሐዋርያትንም አቍርቧቸዋል፡፡ እነርሱም እመቤታችንን በዓይናቸው ከማየት ባሻገር አብረው ሥጋውን ደሙን ተቀብለዋል (ነገረ ማርያም፤ ትርጓሜ ውዳሴ ማርያምና ቅዳሴ ማርያም)፡፡

ይህንን ትምህርት መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት ከነሐሴ ፩ እስከ ፲፭ ቀን ያለው ሁለት ሱባዔ ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ ኾኖ በምእመናን ዘንድ መጾም እንደሚገባው ሥርዓት ሠርተውልናል (ፍት.ነገ.አን.፲፭)፡፡ ይህ ጾምም ‹‹ጾመ ማርያም (የማርያም ጾም)›› ወይም ‹‹ጾመ ፍልሰታ ለማርያም (የማርያም የፍልሰቷ ጾም)›› እየተባለ ይጠራል፡፡ ‹ፍልሰት› የሚለው ቃል ‹‹ፈለሰ ሔደ፤ ተሰደደ›› ካለው የግእዝ ግስ የተገኘ ሲኾን ትርጕሙም ከአንድ አገር ወደ ሌላ አገር መሔድን ያመለክታል፡፡ ‹ፍልሰታ ለማርያም› ሲልም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ካረፈች በኋላ ከጌቴሴማኒ ወደ ገነት መወሰዷን (ማረጓን) የሚያስረዳ መልእክት አለው፡፡

በጾመ ፍልሰታ ወቅት በቤተ ክርስቲያናችን በየቀኑ በማኅሌቱ፣ በሰዓታቱና በቅዳሴው በሚደርሰው ቃለ እግዚአብሔር ነገረ ማርያም ማለትም የእመቤታችን ከመፀነሷ ጀምሮ እስከ ዕርገቷ ድረስ ያለው ታሪኳ፣ ለአምላክ ማደሪያነት መመረጧ፣ ንጽሕናዋ፣ ቅድስናዋ፣ ክብሯ፣ ርኅርራኄዋ፣ ደግነቷ፣ አማላጅነቷ፣ ሰውን ወዳድነቷ በስፋት ይነገራል፡፡ እመቤታችንን ከሚያወድሱ ድርሳናት መካከልም በተለይ ምሥጢረ ሥላሴን፣ ምሥጢረ ሥጋዌንና ነገረ ድኅነትን ከነገረ ማርያም ጋር በማዛመድ የሚያትተው ቅዳሴ ማርያም፤ እንደዚሁም ነገረ ድኅነትን ከምሥጢረ ሥጋዌ (ከነገረ ክርስቶስ) እና ከነገረ ማርያም ጋር በማመሣጠር የሚያትተው ውዳሴ ማርያምም በስፋት ይጸለያል፤ ይቀደሳል፤ ይተረጐማል፡፡ በሰንበታት የሚዘመሩ መዝሙራት፤ በየዕለቱ በቅዳሴ ጊዜ የሚነበቡ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በእግዚአብሔር ለተዋሕዶ መመረጧን፣ ዘለዓለማዊ ድንግልናዋን፣ ክብሯን፣ ቅድስናዋን፣ ንጽሕናዋን የሚያወሱ ናቸው፡፡

በጾመ ፍልሰታ ባሕታውያን ብቻ ሳይኾኑ ዓለማውያንም በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእመቤታችን አማላጅነት የሰይጣንን ፈተና ድል ለማድረግ እንዲቻላቸው ከቤተሰቦቻቸው ተለይተው በየገዳማቱና በየአብያተ ክርስቲያናቱ በዓት አዘጋጅተው፣ ሱባዔ ገብተው፣ ፈቃደ ሥጋቸውን ለፈቃደ ነፍሳቸው አስገዝተው ይጾማሉ፤ ይጸልያሉ፡፡ እንደዚሁም ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡ ይህ ጾም ለእመቤታችን ያለንን ፍቅርም የምንገልጽበት ወቅት ነው፡፡ በተለይ ኦርቶዶክሳውያን ሕፃናት በአብዛኛው ትምህርተ ወንጌል የሚማሩት፤ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን የሚቀበሉት በዚህ በጾመ ፍልሰታ ነው፡፡ ጌታችን በስሙ ሁለትም ሦስትም ኾነን ለጸሎትና ለመልካም ሥራ ብንሰባሰብ እርሱ በመካከላችን እንደሚገኝ የገባልንን ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ (ማቴ. ፲፰፥፳)፣ ዅላችንም በጾመ ፍልሰታ ሳምንታት በጌታችን፣ በእመቤታችንና በቅዱሳን ሐዋርያት ስም በቤተ ክርስቲያን ተሰባስበን ቅዱሳት መጻሕፍትን ከመማር ባሻገር ብንጾም፣ ብንጸልይ፣ ብናስቀድስ፤ እንደዚሁም ሥጋውን ደሙን ብንቀበል በበረከት ላይ በረከትን፤ በጸጋ ላይ ጸጋን እናገኛለን፡፡ በኋላም ሰማያዊውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ እንችላለን፡፡

ስለኾነም የእመቤታችንን ዕረፍትና ትንሣኤ በማሰብ ከልጇ ከወዳጇ የሚገኘውን ጸጋና በረከት ተስፋ በማድረግ የአባቶቻችንንና የእናቶቻችንን ፈለግ ተከትለን በየዓመቱ ጾመ ፍልሰታን እንጾማለን፤ የምንችል ደግሞ ንስሐ ገብተን አስቀድሰን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን እንቀበላለን፡፡ ነገር ግን በሕግ የተከለከለ እስኪመስል ድረስ በዚህ ወቅትም ኾነ በሌላ ጊዜ ሥጋውን ደሙን የሚቀበሉ ወጣቶች ጥቂቶች ናቸው፡፡ ስለዚህም አረጋውያንና ሕፃናት ብቻ ሳይኾኑ ወጣቶችም ጭምር የመቍረብና የመዳን ክርስቲያናዊ መብት እንዳለን በመረዳት ራሳችንን ገዝተን፣ ንስሐ ገብተን፣ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን በመቀበል መንግሥቱን ለመውረስ መዘጋጀት ይኖርብናል፡፡ አምላካችን በማይታበል ቃሉ ‹‹ሥጋዬን የሚበላ፤ ደሜንም የሚጠጣ የዘለዓለም ሕይወት አለው›› በማለት ተናግሯልና (ዮሐ. ፮፥፶፬)፡፡ የእግዚአብሔር ቸርነት፣ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ሐዋርያት ጸጋና በረከት አይለየን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ጾመ ፍልሰታና ሥርዓቱ – ካለፈው የቀጠለ

በዝግጅት ክፍሉ

ሐምሌ ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በቀሲስ ስንታየሁ አባተ አባባል የፍልሰታ ጾም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ልዩ ስፍራ አለው፡፡ ኢትዮጵያውያንም ለእመቤታችን ያላቸው ፍቅር የተለየ ነው፡፡ ይህም ከእመቤታችን ጋር ያለንን የጠበቀ ትስስር የሚያመላክት ሲኾን ከዚህም ሌላ አገራችን ኢትዮጵያ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የዐሥራት አገር ናት፡፡ እመቤታችን ልጇ ወዳጇ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስን ይዛ በተሰደደችበት ወቅት በግብጽ ብቻ ሳይኾን በኢትዮጵያ ምድርም መጥታ ዐርፋለች፡፡ በዚህ ጊዜ አራቱንም የአገሪቱን መዓዝን ባርካለች፡፡ ሊቃውንቱ እንደሚያስተምሩት ነቢዩ ዕንባቆም ‹‹የኢትዮጵያ ድንኳኖች ሲጨነቁ አየሁ›› በማለት የተናገረው ትንቢትም እመቤታችን ልጇን ይዛ ወደ ኢትዮጵያ መምጣቷን ያጠይቃል፡፡ ስለዚህ ይህን ከትውልድ ወደ ትውልድ የሚተላለፍ ሥርዓት አድርገን ፍልሰታን በልዩ ኹኔታ እንጾማለን፡፡

ድርሳነ ዑራኤልም ‹‹እመቤታችን ድንግል ማርያም በስደቷ ወራት ልጇ ሕፃኑ ኢየሱስን ይዛ ከምድረ እስራኤል ወደ ምድረ ግብጽ፣ ከዚያም ወደ ብሔረ ኢትዮጵያ መጥታ በቅዱስ ዑራኤል መሪነት በደብረ ዳሞበትግራይ፣ በጎንደር፣ በአክሱም፣ በደብር ዐባይ፣ በጐጃምና በጣና በአደረገችው የስደት ጉዞ ሕፃኑ ኢየሱስ ለድንግል እናቱኢትዮጵያን ዐሥራት አድርጌ ሰጥቼሻለሁ››› በማለት በሸዋና በወሎ፣ በሐረርጌና በአርሲ፣ በሲዳማና በባሌ፣ በከፋና በኢሉባቦር፣ በወለጋና በሌሎችም የኢትዮጵያ ክፍላተ አህጉር በብሩህ ደመና ተጭነው በአየር እየተዘዋወሩ ተራራውንና ወንዙን (አፍላጋቱን) እንደ ጐበኙ ይናገራል፡፡ ይህም የቀሲስ ስንታየሁን ሐሳብ ያጠናክራል፡፡

በጾመ ፍልሰታ ወቅት የምእመናን ቅድመ ዝግጅት

በጾመ ፍልሰታ ወቅት ምእመናን ምን ቅድመ ዝግጅት ማድረግ አለባቸው? ሱባዔ ከገቡ በኋላስ ምን ማድረግ ይጠበቅባቸዋል? የሚለውም ሌላው ጥያቄአችን ነበር፡፡ ሊቀ ማእምራን ደጉ ዓለም እንዲህ ይመልሳሉ፤

‹‹ምእመናን ጾም (ሱባዔ) ከመጀመራቸው በፊት የሥጋን ኮተት ዅሉ ማስወገድ አለባቸው፡፡ ሐሳባቸው ዅሉ ወደተለያየ አቅጣጫ ሳይከፋፈል ልቡናቸውን ሰብስበው ለአንድ እምነት መቆም፣ ከሱባዔ የሚያቋርጣቸውን ጉዳይም አስቀድሞ ማጠናቀቅ ይኖርባቸዋል፡፡ ከገቡ በኋላሥጋቸውን ማድከም፣ በጾም በጸሎት መጠመድ አለባቸው፡፡ ከዚህም ባሻገር እንደ ተሰጣቸው ጸጋ መጠን ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል ይገባቸዋል፡፡ ጉልበት ያለው በጉልበቱ፣ ገንዘብ ያለው በገንዘቡ፣ ዕውቀት ያለው በዕውቀቱ፣ አቅሙ የደከመን መርዳት የማይችል ደግሞ ምክርና ሐሳብ በመስጠት ክርስቲያናዊ ድርሻውን ይወጣ፡፡ ብዙ ከመብላት ጥቂት በመመገብ፣ ብዙ የሚያሰክር መጠጥ ጠጥቶ ከመንገዳገድ ውኃን ብቻ በመጎንጨት ለቁመተ ሥጋ የሚያበቃቸውን ያህል እያደረጉ ፈጣሪያቸውን ይጠይቁ፡፡ አለባበስን በተመለከተም ሥርዓት ያለው አለባበስ ሊኖራቸው ይገባል፡፡ ከሌላው የተለየና የሌሎችን ቀልብ የሚስብ  ልብስ መኾን የለበትም፡፡››

ቀሲስ ስንታየሁ የተናገሩትም ከሊቀ ማእምራን ደጉ ትምህርት ጋር ተመሳሳይነት አለው፡፡ እንዲህ ይላሉ ቀሲስ፤ ‹‹ጾም ማለት ለእግዚአብሔር ማመልከቻ ማስገባት ማለት ነው፡፡ የነነዌ ሰዎች ሦስት ቀን ጾሙ፤ በሦስት ቀናት ውስጥ አገራቸው ከመከራ ዳነች፡፡ የፍልሰታ ጾምም የወገኖቻችንን፣ በአጠቃላይ የሰውን ልጅ ጥፋት አታሳየን› ብለን ቦታና ጊዜ ወስነን ሱባዔ የምንይዝበት ጾም ነው፡፡ እኛ ምእመናን ከሁለት መቶ ኀምሳ ቀናት በላይ እንጾማለን፡፡ ነገር ግን ስንጾም ማየት የሚገባን ነገር አለ፡፡ ፍቅር እንደ ሸማ ያላብስህ እንደሚባለው ስንጾም ፍቅር ሊኖረን ይገባል፡፡ ጾም ያለ ፍቅር፣ ፍቅርም ያለ ጾም ዋጋ የለውም፡፡ ቁም ነገሩ እኛ በጾም ደርቆ መዋል ሳይኾን ፍቅርና ሰላም መታከል አለበት፡፡ የተጣላ መታረቅ አለበት፡፡ በቅዳሴ ሰዓት ቦታ ላጡ ቦታ መስጠት፣ አቅመ ደካሞችን መርዳት፣ በተለይ አረጋውያንንና ሕፃናትን መደገፍ የወጣቶች ድርሻ ነው፡፡ በቅዳሴ ሰዓት የበረታው ለደከመው ቦታ መልቀቅ ይኖርበታል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ሐሜትናሁካታቂም በቀል ያዘለ ንግግር ቦታ ሊኖረው አይገባም፡፡››

እንደ ቀሲስ ስንታየሁ ገለጻ ጾም መጽሐፍ ቅዱሳዊ ቃል ከኾነ ለምንድን ነው በጾማችን፣ በጸሎታችን ኅብረተሰባችን ከጉስቁልና ያልወጣው? ብለን ብንጠይቅ ሳይጾም ሳይጸለይ ቀርቶ ሳይኾን ፍቅር ስለሌለው ነው እንጂ እግዚአብሔር ጸሎቱን ሳይሰማ ቀርቶ አይደለም፡፡ እግዚአብሔር ፊትም አሁንም ኾነ ወደፊት የሕዝቡን ልመና ይሰማል፡፡

ሱባዔ የገቡ ዅሉ ራእይ ያያሉን?

ለሊቀ ማእምራን ደጉ ዓለም እና ለቀሲስ ስንታየሁ አባተ በመጨረሻ ያነሣንላቸው ጥያቄ ራእይ ከማየትና አለማየት ጋር የተያያዘ ነበር፡፡ አንዳንድ ሰዎች ሲታመሙ ከሕመማቸው ለመፈወስ ወይም በምድራዊ ሕይወት ለሚያነሧቸው ጥያቄዎች መፍትሔ ለማግኘት ሱባዔ በመግባት ራእይ ማየት አለብን ይላሉ፡፡ ራእይ ካላዩ ደግሞ ተስፋ ይቈርጣሉ፡፡ በዚህ ጉዳይ ለሕዝበ ክርስቲያኑ የምታስተላልፉት መልእክት ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ መምህራኑ ምላሽ አላቸው፡፡ ሊቀ ማእምራን ደጉ፡- ‹‹ምንም እንኳን ወሩ ከሌላው በተለየ የሱባዔና የራእይ ወቅት ኾኖ ቢገለጽም በፍልሰታ ጾም ራእይ ማየት አለማየት የሚለው የብቃት መለኪያ (ማረጋገጫ) መኾን የለበትም፡፡ ቦታ ቀይረውና ከሰው ተለይተው እግዚአብሔርን በጾም በጸሎት መጠየቅ በቅዱሳት መጻሕፍት ታዝዟል፡፡ ምእመናን ወደ ውሳኔ ከመድረሳቸው በፊት ፈቃደ እግዚአብሔርን እንወቅ ብለው እርሱን ይጠይቃሉ፡፡ ካልተሳካላቸው በተለያየ ጊዜ በሱባዔው ይቀጥላሉ እንጂ ተስፋ መቁረጥ የለባቸውም›› ሲሉ ምእመናንን መክረዋል፡፡

ቀሲስ ስንታየሁም፡- ‹‹አንድ ሰው የሚጾመው ራእይ ልይ ብሎ አይደለም፡፡ ይህ እግዚአብሔር በፈቀደ ጊዜ የሚታይ ነገር ነው፡፡ አባቶቻችን ሲጾሙ፣ ሲጸልዩ ኃጢአታቸው እንዲገለጽላቸው እንጂ እግዚአብሔር እንዲገልጽላቸው አይደለም፡፡ ኃጢአታን ከተገለጸልንና ንስሐ ከገባን እግዚአብሔርን እናየዋለን፡፡ አንድ ሰው በኃጢአት ተሞልቶ እግዚአብሔርን ልይ ቢል ሊኾን አይችልም፡፡ እኛንና እግዚአብሔርን የሚለያየን ኃጢአትና በደል ነው፡፡ ስለዚህ የሚያራርቀንን ነገር ለማስወገድ መጾም አለብን፡፡ ምእመናን በሕይወታቸው ውስጥ ስላለው ችግር፣ ለሰው ልጅና ለአገር የሚበጅ ነገር አምጣልን ብለው ሱባዔ በመያዝ መጾም መጸለይ ይገባቸዋል እንጂ ራእይ እንዲገለጥላቸው መጓጓት፣ ራእይ አላየንም ብለውም ተስፋ መቁረጥ ተገቢ አይደለም፤›› በማለት መንፈሳዊ ምክራቸውን ለግሰዋል፡፡

ጽሑፋችንን ለማጠቃለል ያህል በሕይወተ ሥጋ ሳለን ካልጾምንና ካልጸለይን ነፍሳችን ልትለመልም አትችልም፡፡ በጾም በጸሎት ዲያብሎስን፣ ዓለምንና ፍትወታት እኩያትን ድል መንሣት፤ እንደዚሁም መንፈሳዊ ሕይወትን ማሳደግ ይቻላል፡፡ ምእመናን በምንጾምበት ወቅት የተራቡትንና የታረዙትን በማሰብ ካለን ከፍለን ለተራቡና ለታረዙ ማብላት፣ ማልበስ ይገባል፡፡ ይህን የምናደርገውም በፍልሰታ ወይም በሌሎችም አጽዋማት ጊዜ ብቻ ሳይኾን በማንኛውም ጊዜ ነው፡፡ የተቸገሩትን መርዳት ወይም እርስበርስ መረዳዳት ሃይማኖታዊና መንፈሳዊ ግዴታ ብቻ ሳይኾን የኢትዮጵያዊነት መገለጫ ባህልም ነውና፡፡ ይህ ጾም ሰላምን፣ ፍቅርን፣ አንድነትን የምናሰፍንት፤ መንፈሳዊ ዕድገትን የምናመጣበት ይኾንልን ዘንድ የእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃዱ ይኹንልን፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ረድኤትና በረከት አይለየን፡፡

                                                              ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ጾመ ፍልሰታና ሥርዓቱ – ክፍል አንድ

በዝግጅት ክፍሉ

ሐምሌ ፴ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! በዚህ ዝግጅታችን ጾም ምንድን ነው? እንዴትና ለምን እንጾማለን? መጾም ምን ጥቅም ያስገኛል? ባንጾምስ ምን ጉዳት አለው? የሚሉ ጥያቄዎች በቤተ ክርስቲያን መምህራን ምላሽ እንዲያገኙ አድርገናል፡፡ በተጨማሪም ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ የኾነው የፍልሰታ ጾም በደመቀና በተለየ ኹኔታ የሚጾምበት ምክንያት ምን እንደ ኾነና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮችን ይዘን ቀርበናል፡፡ ከምላሾቹ በኋላም ጾመ ፍልሰታን እንዴት ማክበር እንደሚገባን ለመዳሰስ ሞክረናል፡፡ መልካም ንባብ!

የጾም ትርጕም

‹‹ጾም›› ማለት ‹‹ጾመ –  ተወ፤ ታቀበ፤ ታረመ፤›› ካለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ቃል ሲኾን የቃሉ ትርጕም ደግሞ ምግብ መተው፣ መከልከልና መጠበቅ ማለት ነው ሲሉ ዲያቆን ቃኘው ወልዴ በ፲፱፻፺፭ ዓ.ም ባዘጋጁት ‹‹ጾምና ምጽዋት›› በሚለው መጽሐፋቸው ገጽ ፰ ላይ ገልጸውታል፡፡ የኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላትም የሚያትተውም ይህንኑ ሐሳብ ነው፡፡ ጾም ጥሉላትን፣ መባልዕትን ፈጽሞ መተው፣ ሰውነትን ከመብልና ከመጠጥ እንደዚሁም ከሌላውም ክፉ ነገር ዅሉ መጠበቅ፣ መግዛት፣ መቈጣጠር፣ በንስሐ ታጥቦ በጸሎት ወደ እግዚአብሔር መቅረብና እርሱንም ደጅ መጥናት ማለት ነው፡፡ ሊቀ ማእምራን ደጉ ዓለም ካሣ እና ቀሲስ ስንታየሁ አባተ የሚሰጡት ማብራርያም ይህንኑ ትርጕም የሚያጠናክር ነው፡፡

የጾም ሥርዓቱና ጥቅሙ 

‹‹መላው ሕዋሳታችን ካልጾሙ የምግብና መጠጥ ጾም ብቻ ዋጋ የለውም፡፡ መጽሐፉም የሚለው ወደ አፍ የሚገባ ሰውን አያረክስም፤ ከአፍ የሚወጣ እንጂ› ነው፡፡ ስለዚህ ዐይን፣ ጆሮ፣ እግርና እጅ የመሳሰሉት የስሜት ሕዋሳታችን መጾም አለባቸው፡፡ ከምግብና መጠጥ ይልቅ የሚበልጡት እነዚህ ናቸው፡፡ ከምግብና መጠጥ የምንቆጠበው በራሱ ኃጢአት ስለ ኾነ ሳይኾን ምግብና መጠጥ ሥጋን አጥግቦ በገደል ስለሚጥል ወዳልተፈለገ አቅጣጫ ስለሚጎትት ከእግዚአብሔር ጋር ያለን ግንኙነት እንዲቋረጥ ይደረጋል፡፡ ስንጾምከሐሜት፣ ከአሉባልታ፣ ከዝሙትና በሐሰት ከመመስከርወዘተ. መቆጠብ አለብን›› ሲሉ ሊቀ ማእምራን ደጉ ያስረዳሉ፡፡

‹‹የጾም መሠረቱ ሃይማኖት ነው፡፡ በሃይማኖት የተነሣ ለተወሰኑ ጊዜያት ከምግብና ከመጠጥ የምንከለከልበት ኹኔታ ይኖራል፡፡ ነገር ግን ጾም ይህ ብቻ አይደለም፤ ሁለት ዓይነት መስመር አለው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአጽዋማት ወቅት ከምግበ ሥጋና ከኃጢአት ትከለክላለች፡፡ ከኃጢአት ዅልጊዜም እንከላከላለን፡፡ ከምግብ የምንከለከለው ምግብ ኃጢአት ስለኾነ ሳይኾን ከሃይማኖት የተነሣ ነው፡፡ ምግብ በልተን ፈቃደ ሥጋችንን ከምናደልብ እንደ ቅዱስ ጳውሎስ ሥጋችንን ጎስመን ያለ ምግብና ያለ መጠጥ እግዚአብሔርን እያመሰገንን የምንኖርበትን ሰማያዊና ዘለዓለማዊ ሕይወት የምናስብብት መንገድ ነው›› የሚሉት ደግሞ ቀሲስ ስንታየሁ አባተ ናቸው፡፡

የጾም ዓይነቶች

ጾም የግል እና የዐዋጅ (የሕግ) ጾም በመባል በሁለት ይከፈላል፡፡ የግል ጾም ደግሞ የንስሐና የፈቃድ ጾም ተብሎ በሁለት ይከፈላል፡፡ የዐዋጅ (የሕግ) አጽዋማት ሰባት ናቸው፡፡ እነዚህም ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ሐዋርያት (የሰኔ ጾም)፣ ጾመ ነቢያት (የገና ጾም)፣ ጾመ ገሃድ፣ ጾመ ነነዌ፣ ጾመ ድኅነት (ረቡዕ እና ዓርብ) እና ጾመ ፍልሰታ ናቸው፡፡ የዚህ ጽሑፍ መነሻም ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ የኾነው ጾመ ፍልሰታ ነው፡፡ ምክንያቱም አሁን ወቅቱ የፍልሰታ ጾም ስለኾነ፡፡

የፍልሰታ ጾም 

ከዚህ በመቀጠል ጾመ ፍልሰታን ከሌሎቹ አጽዋማት ልዩ የሚያደርገው ምን እንደ ኾነ እንመለከታለን፡፡ የፍልሰታን ጾም ሕፃን አዋቂው ሳይቀር በልዩ ሥነ ሥርዓትና በደመቀ ኹኔታ ይጾማል፡፡ አብዛኞቹ ምእመናን የዕረፍት ጊዜ በመውሰድ በገዳማትና በየአብያተ ክርስቲያናት ሱባዔ በመግባት ከነሐሴ አንድ ጀምሮ እስከ አሥራ አምስት ቀን ድረስ ጾም፣ ጸሎት በማድረግ ይቆያሉ፡፡ ጾም ጸሎት ሲያደርጉ ደግሞ በድሎት ሳይኾን በየዋሻው፣ በየመቃብር ቤቱና አብያተ ክርስቲያናት ዙሪያ እንጨት ረብርበውና ሳር ጎዝጉዘው ጥሬ እየበሉ ነው፡፡

ፍልሰታ ምን ማለት ነው?

ሊቀ ማእምራን ደጉ ዓለም ለዚህ ጥያቄ የሚከተለውን ምላሽ ሰጥተዋል፤ ‹‹ፍልሰታ ማለትፈለሰ – ተሰደደ› ከሚለው ግሥ የወጣ ነው፡፡ፍልሰትማለት ደግሞ የተለያየ ትርጕም ቢሰጠውምፍልሰታ ለማርያም› ተብሎ ሲገለጽ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከሚያልፈው ወደ ማያልፈው ዓለም ከመቃብር የወጣችበት (የተነሣችበት) ቀን ማለት ነው፡፡ ወይም ደግሞ ከሥጋዊው ዓለም ወደ መንፈሳዊው ዓለም የተሸጋገረችበት ማለት ነው፡፡››

ቀሲስ ስንታየሁ አባተም በተመሳሳይ መልኩ ስለ ፍልሰታ እንዲህ በማለት ማብራርያ ሰጥተዋል፡፡ ‹‹‹ፍልሰታ ለማርያም› የሚለው የግእዝ ቃል ሲኾንፍልሰታ› ማለት ደግሞፈለሰ› ከሚል ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ‹ፍልሰት› ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ መሔድን (መፍለስን) ያመለክታል፡፡ እመቤታችን ካረፈች በኋላ የሥጋዋን መፍለስ አስመልክቶ ሐዋርያት የእመቤታችን ሥጋ የት እንደ ተቀበረ አላወቁም ነበርና እግዚአብሔር የእመቤታችንን ሥጋ እንዲገልጥላቸው የጾሙት ጾም ነው፡፡ ሐዋርያት ሁለት ሱባዔ ጾመው የእመቤታችንን ሥጋዋን ሰጥቷቸው ትንሣኤዋንና ዕርገቷን በማየት በረከት ያገኙበት ጾም ነው፡፡ ስለኾነም ምእመናን ፍልሰታ ለማርያምን ከልጅ እስከ አዋቂው በጾም በጸሎትና በመቍረብ በጋራ በፍቅር፣ በሰላም ያሳልፉታል፡፡›› 

ሊቀ ማእምራን ደጉ ዓለም ካሣ እንዳብራሩት ቅዱስ ዮሐንስ እመቤታችንን እንዲጠብቃት ከተደረገ በኋላ ሐዋርያት ‹‹የእመቤታችን ነገር እንዴት ነው?›› ብለው በጠየቁት ጊዜ ‹‹እመቤታችንማ በገነት በዕፀ ሕይወት ሥር ናት››  ብሎ ነገራቸው፡፡ በዚህ ጊዜ ሐዋርያት እመቤታችን ከመቃብር መነሣቷንና ማረጓን ማየት አለብን፤ እንዴት ዮሐንስ አይቶ እኛ ሳናይ እንቀራለን ብለው በመንፈሳዊ ቅናት በመነሣሣት ነሐሴ አንድ ቀን በዕለተ ሰኞ ሁለት ሰባት ሱባዔ ያዙ፡፡ በዐሥራ አራተኛው ቀን ጌታችን የእመቤታችንን ሥጋ አንሥቶ ሰጣቸውና በጌቴሴማኒ ቀበሯት፡፡ እመቤታችን በ፷፬ ዓመቷ ጥር ፳፩ ቀን ዐርፋ ነሐሴ ፲፬ ቀን ተቀብራለች፡፡

ይኹንና ሐዋርያት ቢቀብሯትም ትንሣኤዋንና ዕርገቷን አላዩም ነበር፡፡ ትንሣኤዋንና ዕርገቷን ያየው ሲቀብሯት ያላየው ሐዋርያው ቶማስ ነው፡፡ ቶማስ እንዲያስተምር ሕንድ አገር ዕጣ ደርሶት አስተምሮ በደመና ሲመለስ ነሐሴ ፲፮ ቀን እመቤታችን ስታርግ ሕዋ ላይ ተገናኙ በማለት ሊቀ ማእምራን ደጉ ያስረዳሉ፡፡ እንደ እርሳቸው አገላለጽ ምእመናን ጾመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት፣ ትንሣኤና ዕርገቷ የሚዘከርበት ከሰባቱ አጽዋማት አንዱ የኾነ ጾም ነው፡፡ በየዓመቱ ሕፃን አዋቂው ሳይቀር የእመቤታችን ፍቅር አድሮባቸው ጾሙን ይጾማሉ፣ ያስቀድሳሉ፤ ይቈርባሉ፡፡

የፍልሰታን ጾም ከሌሎቹ አጽዋማት ልዩ የሚያደርገው ምንድን ነው?

የፍልሰታን ጾም ከሌሎቹ አጽዋማት ልዩ የሚያደርገው ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ ሊቀ ማእምራን ደጉ ምላሽ ሲሰጡም ‹‹ኢትዮጵያ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም የዐሥራት አገር በመኾኗ እና ሕዝበ ክርስቲያኑ ለእመቤታችን ልዩ ፍቅር ስላላቸው መሬት ላይ እየተኙ፣ ጥሬ እየበሉ በሰላም በፍቅር ይጾሙታል፡፡ ምእመናን ፍልሰታን ከሌሎች አጽዋማት በተለየ መልኩ መሬት ላይ እየተኙ ይጾሙታል፡፡ ይህ ደግሞ የእመቤታችን ፍቅር ስለሳባቸው ነው፤›› በማለት ያብራራሉ፡፡

ይቆየን

የ፳፻፱ ዓ.ም ጾመ ፍልሰታን አስመልክቶ ቅዱስ ፓትርያርኩ የሰጡት ቃለ በረከት

ሐምሌ ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

በአገር ውስጥና በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ!!

እኛን ለክብርና ለምስጋና የፈጠረ እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት የጾመ ማርያም ሱባዔ በሰላም አደረሳችሁ!!

‹‹ታዓብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር፤ ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች፤›› (ሉቃ ፩፥፵፯)፡፡

ይህንን የምስጋና ቃል የተናገረችው ወላዲተ እግዚአብሔር ቃልና ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የኾነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ይህንን የአምልኮ ምስጋና ለእግዚአብሔር ስታቀርብ እርሱ ያደረገላትን ሦስት ዓበይት ምክንያቶች በመጥቀስ እንደ ኾነ ከቅዱስ መጽሐፍ እናስተውላለን፡፡

እመቤታችን ይህንን ምስጋና ከማቅረቧ በፊት እግዚአብሔር ለታላቅ በረከትና ለፍጹም ደስታ እንደ መረጣት፣ የእርሱ ባለሟልና ምልእተ ጸጋ እንዳደረጋት፣ ቅዱሱን የእግዚአብሔር ልጅ በመንፈስ ቅዱስ ፀንሳ እንደምትወልድና እግዚአብሔር ከእርሷ ጋር እንደ ኾነ በመልእክተኛ በቅዱስ ገብርኤል በኩል ነግሮአታል፡፡ እርሷም በቅዱስ ገብርኤል በኩል የተላከላትን የእግዚአብሔር ቃል ተቀብላ ‹‹እነሆ የእግዚአብሔር ባሪያ ነኝ፤ እንዳልኸኝ ይኹንልኝ›› በማለት በታዛዥነትና በትሕትና ለደረሳት መለኮታዊ ጥሪ ተገቢውን የይኹንታ መልስ ሰጥታለች፡፡ በዚህ ጊዜ ቀዳማዊ ወልደ እግዚአብሔር በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍስዋ ነፍስ ነሥቶ ራሱን በማዋሐድ የዕለት ፅንስ ኾኖ በማኅፀንዋ አደረ፡፡

ጌታችን አምላካዊ ማንነቱን መግለጽ የጀመረው ከማኅፀን አንሥቶ ነውና እመቤታችን እርሱን ፀንሳ ሳለች ኤልሳቤጥን እንዴት ነሽ ብላ የሰላምታ ድምፅን ስታሰማት በማኅፀነ ኤልሳቤጥ ያለው ፅንስ በማኅፀነ ማርያም ላለው ፅንስ በደስታ ሰግዶአል፡፡ ይህ አምላካዊ ምሥጢር በድንግል ማርያም ማኅፀን ውስጥ ያለው ፅንስ የአምልኮ ስግደት የሚገባውና ዅሉን የፈጠረ፣ ዅሉንም ማድረግ የሚችል የባሕርይ አምላክ መኾኑን አሳይቶአል፡፡ ይህ ብቻም አይደለም፤ የቅድስት ድንግል ማርያም የሰላምታ ድምፅ በኤልሳቤጥ ጆሮ በተሰማ ጊዜ በማኅፀንዋ ያለ ፅንስ በደስታ ሲሰግድ፣ በዚያ ቅፅበት ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታ እግዚአብሔር በቅዱስ ገብርኤል በኩል የገለጸውን የእመቤታችን ክብርና ጸጋ፣ በረከትና ብፅዕና፣ የጌታ እናትነትና ባለሟልነት፣ የልጇ በረከትና አምላክነት በኤልሳቤጥ አንደበትም በድጋሜ  እንዲነገር ማድረጉ የነገሩ ክብደትና ታላቅነት ምን ያህል እንደ ኾነ እንዲታወቅ አስችሎአል፡፡

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በቅዱስ ገብርኤልና በቅድስት ኤልሳቤጥ በኩል ስለ እርስዋ መናገሩና የእግዚአብሔር ወልድ በማኅፀኗ ማደሩ በዚህ ዅሉ እጅግ በጣም ከኃይል ዅሉ የበለጠ ታላቅ ኃይል በእርስዋ ላይ እንደ ተደረገ እመቤታችን በሚገባ አውቃለች፡፡ ይህ እጅግ በጣም ታላቅ የኾነ ጸጋ ለሰው ልጅ ዅሉ የሚተርፍ ልዩ በረከትና የእግዚአብሔር የማዳን ቍልፍ ተግባር እንደ ኾነ ለማመልከትም ‹‹ካንቺ የሚወለደው ሕዝቡን ከኃጢአታቸው የሚያድናቸው ስለ ኾነ ስሙን ‹ኢየሱስ› ትይዋለሽ›› ተብሎ በመልአኩ ተነግሮአታል፤ እርስዋም አምና ተቀብላለች፡፡ ለዚህ ታላቅ በረከትና መዳን በመሣሪያነት እርሷ መመረጥዋንም ልዩ ዕድል መኾኑን አልዘነጋችም፡፡ እንግዲህ እነዚህ ዓበይት ነገሮች በእመቤታችን አእምሮ ውሰጥ ከፍተኛ ስፍራ ነበራቸውና ያለ ምስጋና ልታልፋቸው አልፈለገችም፡፡ በመኾኑም የኾነው ነገር በሙሉ ለእርስዋና ለሰው ልጆች ዅሉ መኾኑን በሚገልጽ ኃይለ ቃል የአምልኮ ምስጋናዋን ለፈጣሪዋ ለእግዚአብሔር ግሩም በኾነ ኹኔታ አቅርባለች፡፡

በምስጋናዋም ‹‹ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች፤ መንፈሴም በአምላኬና በመድኃኒቴ ደስ ይላታል፡፡ የባርያይቱን ውርደት አይቶአልና፤ እነሆ ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ዅሉ ‹ብፅዕት ነሽ› ይሉኛል፡፡ እርሱ ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና፤›› የሚል ጥልቅ ምሥጢር ያለው ኃይለ ቃል ይገኝበታል፡፡ ይኸውም ‹‹ብዙኃ አበዝኆ ለሕማምኪ ወለፃዕርኪ በሕማም ለዲ፤ ምጥሽን ጣርሽን እጅግ አበዛዋለሁ፤ በጭንቅም ትወልጂያለሽ›› የሚል መርገም ተሸክማ በመከራ የኖረችውና ይህንን መከራ ለልጆችዋ ያወረሰችው ሔዋን በእርስዋ ጊዜና መሣርያነት ከመርገም ተላቃ ወደ ገነት የምትመለስበት ጊዜ እየተቃረበ መምጣቱን ስታመለክት ‹‹የባርያይቱን ውርደት ተመልክቶአልና ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች›› በማለት አመሰገነች፡፡

የሰው ልጅን በአጠቃላይ ከገጠመው ውድቀት ለመታደግ እግዚአብሔር በጀመረው ነገረ አድኅኖ ከኃይል ዅሉ የበለጠ ኃይል እግዚአብሔር ወልድ በማኅፀኗ ማደሩ፣ እንደዚሁም እርስዋ ለዚህ የበቃች ቅድስት፣ ንጽሕት፣ ቡርክት፣ ልዕልት፣ ብፅዕትና ከሴቶች ዅሉ የተለየች ምልእተ ጸጋ፣ ሙኃዘ ፍሥሐ፣ የእግዚአብሔር ልዩ ባለሟልና የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ አድርጎ መምረጡንና ማክበሩን ዅሉ ለእርስዋ የተደረጉ ታላላቅ ነገሮች መኾናቸውን በመገንዘብዋ እመቤታችን ‹‹ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና መንፈሴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ደስ ይላታል›› በማለት ፈጣሪዋን አመስግናለች፡፡ ከዚህም አይይዛ በእግዚአብሔር መልእክተኛ በቅዱስ ገብርኤልና መንፈስ ቅዱስ በሞላባት በቅድስት ኤልሳቤጥ የተገለጸው ቅድስናዋና ብፅዕናዋ ዘመንና የስሑታን ትምህርት ሳይገቱት ከትውልድ ወደ ትውልድ ሳይቋረጥ እንደ ወራጅ ውኃ እስከ ዕለተ ምጽአት እንደሚነገርና እንደሚተገበር በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝታ ተናግራለች፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም የእመቤታችንን ብፅዕና አክባሪና ከአማላጅነቷ ተጠቀሚ ኾና መገኝቷ የእግዚአብሔርን ፈቃድ በደምብ ያወቀችና ቃሉን በምልአት የተቀበለች መኾኗን ያረጋግጣል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

ከቅድስት ድንግል ማርያም የምስጋና ቃል የምንማረው ብዙ ትምህርት እንዳለ ማስተዋልና መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ ከዅሉ በፊት ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም የተነገሩ ነገሮች በሙሉ ከፍጡራን መንጭተው የተነገሩ ሳይኾኑ ከእግዚአብሔር በቀጥታ ከተላከው መልአክ ከቅዱስ ገብርኤል፣ መንፈስ ቅዱስ ከሞላባት ከቅድስት ኤልሳቤጥና እንደዚሁም ‹‹መንፈስ ቅዱስ ባንቺ ላይ ይመጣል›› ከተባለላት ከቅድስት ድንግል ማርያም የተነገሩ በመኾናቸው ምንጫቸውና ተናጋሪያቸው ራሱ እግዚአብሔር እንደ ኾነ መገንዘቡ አያዳግትም፡፡ ምክንያቱም ተላኪ የላኪውን፣ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት የመንፈስ ቅዱስን ቃል እንደሚናገር ለዅሉም ግልጽ ነውና፡፡

ቅዱስ መጽሐፍም እነዚህን በጥንቃቄ መዝግቦ መገኘቱ ይህንን እንድንገነዘበው ብሎ እንደ ኾነ ጥርጥር የለውም፡፡ ከዚህ አንጻር እግዚአብሔር ራሱ በፍጹም ክብር ያከበራትንና ትውልድ ዅሉ ‹‹ብፅዕት ነሽ›› እያሉ እንዲያመሰግኗት በቅዱስ መንፈሱ ያናገረላትን ቅድስት ደንግል ማርያምን ማክበርና ማመስገን፣ ብፅዕናዋንና ቅድስናዋን ማመን፣ መስበክና ማስተማር የእግዚአብሔርን ቃል በትክክል ተረድቶ ለቃሉ መታዘዝና ለተግባራዊነቱ መቆም እንደ ኾነ ለሕዝበ ክርስቲያን ዅሉ ግልጽ ሊኾንለት ይገባል፡፡    ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ላደረገላት ታላቅ ነገር ዅሉ ምስጋናን፣ አምልኮትንና ምስክርነትን በመስጠት ለእኛ መልካም አስተማሪና አርአያ መኾኗን ማስተዋል ከዅላችንም ይጠበቃል፡፡

ዅላችንም ልብ ብለን ካየነው እግዚአብሔር ለሰው ልጅ በአጠቃላይ ታላላቅ ሥራዎችን ያልሠራበት ቀን አይገኝም፡፡ ነገር ግን በየጊዜው ለሠራልን ሥራዎች ተገቢ ዕውቅና በመስጠትና በመመስከር እንደ ቅድስት ድንግል ማርያም በደስታ የአምልኮ ምስጋናን ለእግዚአብሔር የሚያቀርቡ ስንት ናቸው? የሚለውን ጥያቄ ብናነሣ መልሱ አስቸጋሪ ሳይኾን አይቀርም፡፡ ድሮም የተፈጠርነው ለምስጋና ነውና እግዚአብሔር ያለ ማቋረጥ ዅልጊዜም ታላላቅ ነገሮችን እየሠራልን እንደ ኾነ አውቀንና አምነን ለእርሱ የሚገባ የአምልኮ ምስጋና ልናቀርብ ይገባል፡፡ ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ በቀኖና ጸድቆ በጥንታውያንና በኦርቶዶክሳውያን አብያተ ክርስቲያናት ዅሉ እየተፈጸመ የሚገኘው የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ ዓላማም እግዚአብሔርን በምስጋና፣ በቅዳሴ፣ በውዳሴ ለማምለክ፤ ለቅዱስ ቃሉ ፍጹም ታዛዥ በመኾን ምሥጢረ ቊርባንን ለመቀበልና ከኃጢአት ሸክም ተላቀን ከእግዚብሔር ጋር የጠበቀ ግንኙነት ለመፍጠር ነው፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

በዘመነ ብሉይም ኾነ በዘመነ ሐዲስ የእግዚአብሔር ሞገስና ጸጋ አግኝተው ለቅድስና ደረጃ የበቁ ቅዱሳን ዅሉ ጸሎታቸውና ተማኅጽኖአቸው ለራሳቸው ብቻ ሳይኾን ለዓለሙ ዅሉ እንደሚተርፍ ቅዱስ መጽሐፍ በትምህርትም ኾነ በተግባር ያረጋገጠውና የመዘገበው ነው፡፡ ይልቁንም ‹‹እስመ ረከብኪ ሞገሰ በኀበ እግዚአብሔር፤ ከእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሻልና ‹ምልእተ ጸጋ ነሽ፤ ደስ ይበልሽ››› ብሎ እግዚአብሔር በመልእክተኛው ያረጋገጠላት ቅድስት ድንግል ማርያም ባላት ከፍተኛ የእግዚአብሔር ባለሟልነት በጸሎቷ፣ በአማላጅነቷና ወደ እግዚአብሔር በምታቀርበው ተማኅጽኖ ግዳጃችንን እንደምትፈጽም የቃና ዘገሊላው ምልጃዋና የተገኘው በረከት በቂ ማስረጃችን ነው፡፡

በመኾኑም የጾመ ፍልሰታ ሱባዔ እግዚአብሔርን በአባትነት፣ ቅድስት ድንግል ማርያምን በእናትነት የምናገኝበት ልዩ ወቅት በመኾኑ እግዚአብሔር በቃሉ የተናገረውን በመከተልና እንደ ቃሉ በመመላለስ ጾሙን ልንጾም ይገባል፡፡ ከዅሉ በላይ ደግሞ በፍቅርና በሰላም፣ በመተጋገዝና በመረዳዳት፣ በንስሐና በጸሎት፣ ቅዱስ ቊርባንን በመቀበልና ሰውን ሳይኾን እግዚአብሔርን በማዳመጥና በመከተል መጾም ይኖርብናል፡፡ ይህ ጾም የአገራችንን አንድነትና ነጻነት፣ የሕዝባችንን አብሮነትና የእርስ በርስ መተሳሰብ፣ እግዚአብሔርን የመፍራትና ድንግል ማርያምን የመውደድ፣ ሃይማኖታዊና ኢትዮጵያዊ ዕሴቶችን ዅሉ አዳብሮ ጥሩ ሰብእና ያለው ማኅበረሰብን ያፈራ፤ እንደ አሸንዳ የመሳሰሉ ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ባህሎችን የገነባ ጾም ስለሆነ ለሃይማኖታችን መጠበቅ፣ ለአገራችን መልካም ገጽታ ግንባታና ለልማት መፋጠን እንደዚሁም ለቱሪዝም ክፍለ አኮኖሚ መበልጸግ የሚሰጠው ጥቅም ከፍተኛ ስለ ኾነ ሃይማኖታዊ፣ ባህላዊና ሀገራዊ ይዘቱ ተጠብቆ እንዲቀጥል ኢትዮጵያዊ የኾነ ዅሉ የበኩሉን ሊወጣ ይገባል፡፡

በመጨረሻም

የጾም ወቅት ምእመናን ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበት፣ ርኅራኄና አዘኔታ ለሰው ልጅ ዅሉ የሚያደርጉበት እንደ መኾኑ መጠን፣ ምእመናን እጆቻቸውን ለተቸገሩ ወገኖች እንዲዘረጉ፣ ስለ አገርና ስለ ዓለም ዅሉ ሰላም መጠበቅ ወደ እግዚአብሔር ጸሎት እንዲያቀርቡ፣ በአገራችን እየተካሔደ ያለው ዙርያ መለስ የልማትና የዕድገት ሽግግር እንዲሠምር በፍቅርና በሰላም ቆመው በአንድነት ጸሎታቸውን ዅሉን ወደሚችል ወደ ኃያሉ እግዚአብሔር ለማቅረብ እንዲተጉ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

‹‹ወትረ ድንግል ማርያም››

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

 ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

 ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ነሐሴ ፩ ቀን ፳፻ወ፱ ዓ.ም፡፡