ማኅበረ ቅዱሳን የኢቢኤስ የቴሌቪዥን ሥርጭርቱ ላልተወሰነ ጊዜ መቋረጡን ገለጸ

ኅዳር 17 ቀን 2008 ዓ.ም

ዝግጅቱን በኦን ላይን፣ በስልክ እና በአሜሪካ የማኅበረሰብ ቴሌቪዥኖች ማሠራጨቱን ይቀጥላል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ አገልግሎት /EBS/ አማካይነት የሚያቀርበው ሳምንታዊ የአንድ ሰዓት መንፈሳዊ የቴሌቪዥን አገልግሎት ላልተወሰነ ጊዜ መቋረጡን የማኅበሩ ጽ/ቤት አስታወቀ፡፡

የተቋረጠበትም ምክንያት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያ ጠቅላይ ቤተ ክህነት በተጠቀሰው ማሠራጫ ጣቢያ አማካይነት በቤተ ክርስቲያኗ ስም ትምህርት የሚያስተላልፉትን አካላት ማንነትና ዓላማ አጣርቶ መመሪያና ፈቃድ እስከሚሰጥ በቤተ ክርስቲያኗ ስም የሚሠራጩ መርሐ ግብራት እንዲቆሙ በደብዳቤ በጠየቀው መሠረት ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኗ ዕውቅና በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ታቅፎ ሰፊ አገልግሎት እየሰጠ ያለ በመሆኑ የተጻፈው ደብዳቤ ይመለከተዋል ብሎ ባያምንም፤ አባቶች በጣቢያው አማካይነት የሚተላለፉትን መርሐ ግብራት ይዘትና ዓላማ በአግባቡ አጣርተው መመሪያና ፈቃድ እስከሚሰጡ ሥርጭቱን ማቆሙን መርጧል፡፡

በአስቸኳይ አገልግሎቱን ለመጀመር በሚችልበት ሁኔታም ከቤተ ክርስቲያኗ የበላይ አካላት ጋር እየተወያየ እንደሚገኝ ገልጿል፡፡ በሀገር ውስጥና በተለይ በአረብ ሀገራት መርሐ ግብሩን በቀጥታ በኢቢኤስ ማሠራጫ ጣቢያ ሲከታተሉ የነበሩ ምእምናን በትእግስት እንዲጠብቁ ጠይቆ፤ የቴሌቪዥን ሥርጭቱ እስከሚጀምር ድረስ http://onlinetv.eotc.tv/ በስልክ አሜሪካ ለሚገኙ ምእመናን በ605-475-81-72፣ ካናዳ (604)-670-96-98፣ አውሮፓ (ጀርመን 0699-432-98-11፣ እንግሊዝ(ዩኬ) 033-0332-63-60 መከታተል እንደሚችሉ ገልጿል፡፡

እኛም ሁኔታውን እየተከታተልን የምናቀርብ መሆኑን እንገልጻለን፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በኦሮምኛ ቋንቋ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር ሊጀምር ነው

ጥቅምት 23 ቀን 2008 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የአፋን ኦሮሞ ሚዲያ ፕሮጀክት ክፍል ከኅዳር 12 ቀን 2008 ዓ.ም ጀምሮ በኦሮምኛ ቋንቋ የቴሌቪዥን መርሐ ግብር እንደሚጀምር የኅትመትና ኤልክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍል ም/ክትል ሓላፊ አቶ አክሊሉ ለገሠ ገለጹ፡፡

በNilesat, OBS /Oromiya broadcast Service/ ለሠላሳ ደቂቃ ዘወትር እሑድ ከረፋዱ 4፡30-5፡00 ሰዓት እንዲሁም በድጋሚ ረቡዕ ከጠዋቱ 12፡30-1፡00 ሰዓት የሚሠራጨው መርሐ ግብር የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ዶግማ፣ ቀኖና እና ትውፊትን ጠብቆ የሚዘጋጅ ሲሆን፣ የኦሮምኛ ቋንቋ ተናጋሪ ለሆኑ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ስለ እምነታቸው እንዲያውቁ እና ጸንተው እንዲኖሩ፣ እንዲሁም ከእምነታቸው ለወጡ ወደ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው እንዲመለሱ ለማድረግ ታስቦ መጀመሩን ምክትል ሓላፊው አስታውቀዋል፡፡

የኦሮሞ ማኅበረሰብን ከቤተ ክርስቲያን ለመነጠል በርካታ መጻሕፍት ታትመው እየወጡ በመሆናቸው የማኅበረ ቅዱሳን የአፋን አሮሞ ሚዲያ ፕሮጀክት ክፍል ይህንን ለመከላከል ምእመናን ለማስተማር፣ እምነታቸውን ጠብቀው ጸንተው እንዲኖሩ ለማድረግ ፕሮጀክቱ መቀረጹንም ገልጸዋል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በኦሮምኛ ቋንቋ ምእመናንን የሚያንጹ በርካታ በትምህርተ ሃይማኖት፣ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ላይ ያተኮሩ መጻሕፍትን፣ የጸሎት መጻሕፍትንና መጽሔት በማሳተም፣ በኦሮምኛ ድረ ገጽ ጭምር ሲያሠራጭ መቆየቱ ይታወሳል፡፡ በቅርቡም Dangaa Lubbuu/ የነፍስ ምግብ/ የተሰኘ መጽሔት በማሳተም ለምእመናን በማዳረስ ላይ ይገኛል፡፡