ጸሎተ ፍትሐት ምንድ ነው? ለምንስ ይጠቅማል?

ሰኔ 23 ቀን 2007 ዓ.ም.

ፍትሐት ማለት ከዚህ ዓለም በሞት ለሚለዩ ሰዎች በሕይወተ ሥጋ ሳሉ ከሠሩትና ከፈጸሙት በደል እንዲነጹ ከማእሠረ ኃጢአት እንዲፈቱ ወደ እግዚአብሔር የሚቀብ ጸሎት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለሙታን ጸሎተ ፍትሐት እንዲደረግ ታዝዛለች፡፡

ጸሎተ ፍትሐት ለበደሉት ሥርየት ኃጢአትን፣ ይቅርታን ዕረፍተ ነፍስን ያሰጣል፡፡ ለደጋጎች ደግሞ ክብርን፣ ተድላን፣ ዕረፍትን ያስገኛል፡፡

ሙታንና ሕያዋን የሚገናኙት በጸሎት አማካኝነት ነው፡፡ ሕያዋን ለሙታን ይጸልያሉ፤ ሙታንም ለሕያዋን ይለምናሉ፡፡ /ሄኖ. 12፤34/ ሕያዋን ለሙታን የሚጸልዩት ጸሎትና የሚያቀርቡት መሥዋዕት በግልጽ እንደሚታይ ሁሉ ሙታንም በአጸደ ነፍስ ሆነው በዚህ ዓለም ለሚቆዩ ወገኖቻቸው ሕይወትና ድኅነትን፣ ስርየተ ኃጢአትንና ተስፋ መንግሥተ ሰማያትን፣ ጽንዓ ሃይማኖትን እንዲሰጣቸው፣ በንስሐ ሳይመለሱ፣ ከብልየተ ኃጢአት ሳይታደሱ እንዳይሞቱ ፈጣሪያቸውን ይለምናሉ፡፡ ይህም ሥርዓት እስከ ዕለተ ምጽአት ሲፈጸም የሚኖር ነው፡፡

ለሙታን ጸሎተ ፍትሐት እንዲደረግ፣ መሥዋዕት እንዲቀርብላቸው በቤተ ክርስቲያንና በመካነ መቃብራቸው እንዲጸለይላቸው ቅዱሳን ሐዋርያት በቀኖና ሐዋርያት አዝዘዋል፡፡ በክርስቶስ አምነው ስለሞቱ ወንድሞቻችሁ ክርስቲያኖችና ሰማዕታት በቤተ ክርስቲያን ያለሐኬት ተሰብሰቡ፡፡ በቤተ ክርስቲያን መሥዋዕት ሠውላቸው፤ ወደ ቤተ ክርስቲያን ወደ መቃብር ስትወስዱአቸውም መዝሙረ ዳዊት ድገሙላቸው፡፡ ዲድስቅልያ አንቀጽ 33 ገጽ 481

ነቢዩ ዳዊትም የጻድቅ ሞቱ በእግዚአብሔር ዘንድ ክቡር ነው፡፡ ነፍሴ ሆይ ወደ ዕረፍትሽ ተመለሽ፣ እግዚአብሔር ረድቶሻልና፣ ነፍሴን ከሞት አድኖአታልና፡፡ በማለት ሙታን በጸሎት፣ በምስጋና፣ በመሥዋዕት ወደ እግዚአብሔር እንዲሸኙ በመዝሙሩ ተናግሯል፡፡ /መዝ. 115፤114-7/

የቤተ ክርስቲያን የሕግና የሥርዓት መጽሐፍ ፍትሐ ነገሥትም በፍትሕ መንፈሳዊ በዲድስቅልያ የተጠቀሰውን ያጸናል፡፡ /አንቀጽ 22/ ስለ ሙታን የሚጸለየው መጽሐፈ ግንዘትም ካህናት ለሞቱ ሰዎች ሊጸልዩላቸው፣ በመሥዋዕትና በቁርባን ሊያስቧቸው ይገባል ይላል፡፡ ካህናት ጸሎተ ፍትሐት በሚያደርጉላቸው መሥዋዕት እና ቁርባን ስለ እነርሱ በሚያቀርቡላቸው ጊዜ መላእክት ነፍሳቸውን ለመቀበል ይወርዳሉ፡፡ ኃጢአተኞች ከሆኑ ስለ ሥርየተ ኃጢአት ይለምኑላቸዋል፤ ይማልዱላቸዋል፡፡ ንጹሐንም ከሆኑ ደስ ይላቸዋል፡፡ ሰውን ለወደደው ለእግዚአብሔር በሰማያት ክብር ምስጋና ይገባል፣ በምድርም ሰላም፡፡ እያሉ እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል፡፡ ይህም የመላእክት ምስጋናና ደስታ ስለ ሰው ልጅ ድኅነት ነው ተብሎ ተጽፎአል፡፡

የደጋግ ሰዎችን ነፍሳት ቅዱሳን መላእክት እንደሚቀበሏቸው በቅዱስ ወንጌል ተጽፎአል፡፡ አልዓዛርም ሞተ፤ መላእክትም ወደ አብርሃም ዕቅፍ ወሰዱት፡፡ /ሉቃ. 16፤22/

ጸሎተ ፍትሐት የዘሐን ጊዜ ጸሎት ነው፡፡ ቅዱስ ያዕቆብ በእናንተ ባለው መሠረት ከመንጋው መካከል በሞተ ሥጋ የተለዩትን ምእመናን በጸሎትና በዝማሬ እንሸኛቸዋለን፡፡ /ያዕ. 5፤13/ ጸሎተ ፍትሐት የሚደረገው ለከሀድያንና ለመናፍቃን ሳይሆን ለሃይማኖት ሰዎች ነው፡፡

â€Â¹Ã¢€Â¹ማንም ወንድሙን ሞት የማይገባውን ኃጢአት ሲያደርግ ቢያየው ይለምን፣ ሞትም የማይገባውን ኃጢአት ላደረጉት ሕይወት ይሰጥለታል፡፡ ሞት የሚገባው ኃጢአት አለ፡፡ ስለዚህ እንዲጠይቅ አልልም፡፡ ዓመፃ ሁሉ ኃጢአት ነው፡፡ ሞትም የማይገባው ኃጢአት አለ፡፡â€ÂºÃ¢€Âº /ዮሐ. 5፤16/ ለምሳሌ በተለያየ መንገድ ራሱን ለገደለ ሰው ጸሎተ ፍትሐት አይደረግም፡፡ ምክንያቱም ቤተ መቅደስ ሰውነቱን በገዛ እጁ አፍርሷልና፡፡ የእግዚአብሔርም መንፈስ እንዲኖራችሁ አታውቁምን? ማንም የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ቢያፈርስ እግዚአብሔር እርሱን ያፈርሰዋል፡፡ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ነውና ያውም እናንተ ናችሁ፡፡ ይላልና፡፡ /1ቆሮ. 3፤16/ እንዲሁም ለመናፍቃን፣ ለአረማውያንም ጸሎተ ፍትሐት አይደረግም፡፡ ምክንያቱም ብርሃን ከጨለማ ጋር አንድነት የለውምና፡፡ /2ቆሮ. 6፤14/

ቤተ ክርስቲያን ለሰው ልጅ የማትጸልይበት ጊዜ የለም፡፡ ሰውን ያህል ክቡር ፍጥረት ከመጸነሱ በፊት የተባረከ ጽንስ እንዲሆን እንደ ኤርምያስ በማኅፀን ቀድሰው /ኤር. 1፤5/ እንደ መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ በማኅፀን መንፈስ ቅዱስን የተመላ አድርገው እያለች ትጸልያለች፡፡ በወሊድ ጊዜም ችግር እንደያጋጥመው ትጸልያለች፣ በጥምቀትም የእግዚአብሔር ልጅ እንዲሆን ትጸልያለች፣ ታጠምቃለች፡፡ በትምህርት እየተንከባከበች ጸጋ እግዚአብሔርን እየመገበች ታሳድጋለች፡፡ እርሷ የጸጋው ግምጃ ቤት ናትና፡፡ በኃጢአት ሲወድቅም ኃጢአቱ እንዲሠረይለት ንስሐ ግባ ትለዋች፡፡ እንዲሠረይለትም ትጸልያለች፡፡ በሞቱም ጊዜ እግዚአብሔር ኃጢአቱን እንዳይዝበት በደሉን እንዳይቆጥርበት ትጸልይለታለች፡፡ እንዲህ እያደረገች የእናትነት ድርሻዋን ትወጣለች፡፡ አንድ ሰው ሲሞት ዘመድ አዝማድ በዕንባ ይሸኘዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ግን ዕንባዋ ጸሎት ነውና በጸሎቷ የዚያን ሰው ነፍስ ለታመነ ፈጣሪ አደራ ትሰጣለች፣ ነፍሳቸውን ተቀበል ብላ ትጸልያለች፡፡

ቤተ ክርስቲያን ጸሎተ ፍትሐትን የምታደርገው ይሆናል ይደረጋል ብላ በፍጹም እምነት ነው፡፡ ምክንያቱም ክርስቲያን እስከ መጨረሻ ተስፋ አይቆርጥምና፡፡ ወኵሎ ዘሰአልክሙ በጸሎት እንዘትትአመኑ ትነሥኡ፡፡ በሃይማኖት ጸንታችሁ የለመናችሁትን ሁሉ ታገኛላችሁ፡፡ /ማቴ.21፤22/ ስለዚህ እላችኋለሁ፤ የጸለያችሁትን ሁሉ እንዳገኛችሁ እመኑ ይሁንላችሁማል፡፡ /ማር.11፤24/ ለምኑ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ ታገኛላችሁ፤ መዝጊያ አንኳኩ ይከፈትላችሁማል፤ የሚለምነው ሁሉ ይቀበላልና የሚፈልገውም ያገኛል፡፡ መዝጊያውንም ለሚያንኳኳ ይከፈትለታል፡፡ /ማቴ. 7፤7/ በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ አደርገዋለሁ፤ ማናቸውንም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ አደርገዋለሁ፡፡ /ዮሐ. 14፤13/ ይላልና፡፡ ወንጌላዊው ዮሐንስም በመልእክቱ የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ታወቁ ዘንድ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ለምታምኑ ይህን ጽፌላችኋለሁ፡፡ በእርሱ ዘንድ ያለን ድፍረት ይህ ነው፡፡ እንደ ፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናል፡፡ የምንለምነውንም እንዲሰማልን ብናውቅ ከእርሱ የለመነውን ልመና እንደተቀበልን እናውቃለን፡፡ /ዮሐ. 5፤3/ ብሏል፡፡ እንግዲህ የቤተ ክርስቲያን ትምህርቷ ሙሴን ከመቃብር አስነሥቶ ፊቱን ያሳየ አምላክ /ማቴ 17፤3/ ለእነዚህም ሳይንቃቸው የምሕረት ፊቱን ያሳያቸዋል የሚል ነው፡፡ መሐሪ ይቅር ባይ ለሆነው አምላክ የሚሳነው ነገር የለምና፡፡ /ዘፍ. 18፤13፣ ሉቃ. 1፤37/

ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ â€Â¹Ã¢€Â¹ሞት የሚገባው ኃጢአት አለ፤ ስለዚህ እንዲጠይቅ አልልም፤ እንዳለ ቤተ ክርስቲያንም የምትከተለው ይህንኑ ነው፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር ዕድሜ ለንስሐ ሰጥቷቸው ከኃጢአት መመለስ ከበደል መራቅ፣ ንስሐ መግባት፣ ሥጋወደሙን መቀበል ሲችሉ በሕይወታቸውና በእግዚአብሔር ቸርነት እየቀለዱ መላ ዘመናቸውን የሚያሳልፉ ሰዎች አሉ፡፡ እነዚህም በራሳቸው ላይ የፈረዱ ናቸው፡፡ ደግሞም ስሞት በጸሎተ ፍትሐት ኃጢአቴ ይሰረይልኛል ኃጢአትንም አልተውም ማለት በእግዚአብሔር መሐሪነት መቀለድና እርሱንም መድፈር ስለሆነ ይህም ሞት ከሚገባው ኃጢአት የሚቆጠር ነው፡፡

እንግዲህ ለበጎ የተሠራልንን ጸሎተ ፍትሐት ክብር የምናገኝበት ያደርግልን ዘንድ የእግዚአበሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡ አሜን፡፡

 ምንጭ፡-ሃይማኖት የለየንን መቃብር አንድ አያደርገንም፤ ገጽ 20

ፊደል፣ ጥንቱ እድገቱና ተግዳሮቱ ላይ ያተኮሩ ጥናታዊ ጽሑፎች ቀረቡ

ሰኔ 17 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ጉባኤ ፊደል የተሰኘና በፊደል ላይ ያተኮረ ፊደል፤ ጥንቱ እድገቱና ተግዳሮቱ በሚል በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የሥነ ሰብእ፣ ቋንቋዎች ጥናት፣ ጋዜጠኝነትና ተግባቦት ኮሌጅ አዘጋጅነት በርካታ ጥናታዊ ጽሑፎች በዘርፉ ምሁራን ሰኔ 16 ቀን 2007 ዓ.ም በእሸቱ ጮሌ ሕንፃ መሰብሰቢያ አዳራሽ ቀርበዋል፡፡

ከተለያዩ ዩኒቨርስቲዎች የተጋበዙ ምሁራን በግእዝ ፊደል ዙሪያ ለበርካታ ዘመናት እንደ ችግር የሚነሡ በተለይም â€Â¹Ã¢€Â¹ሞክሼ ፊደላትâ€ÂºÃ¢€Âº መቀነስ ይገባል፤ አይገባም በሚል ክርክር እያስነሳ ቆይቷል፡፡ ይህንን ችግር ለመፍታት በመረጃ ላይ የተደገፈ ጥናት ማድረግ እንደሚገባ ምሁራኑ በጥናቶቻቸው ላይ ጠቁመዋል፡፡ የግእዝ እያንዳንዱ ፊደል የራሱ የሆነ ትርጉም፤ ፊደሉም ሆነ ድምጹ አንዱ ከአንዱ ፊደል እንደሚለይ ነገር ግን አማርኛ የግእዝ ፊደላትን እንዳሉ መቀበሉን በጥናቶቻቸው አመላክተዋል፡፡

ለአንድ ቀን በቆየው ጉባኤም፡-

ዶ/ር አየለ በከሪ፡- የግእዝ ፊደል አመጣጥ ከታሪክ አኳያ

ዶ/ር ደርብ አዶ፡- የአማርኛ ሞክሼ ፊደላት በፍጥነት መለየት፣ የሥነ አእምሯዊ ሥነ ልሣናዊ ጥናት

ዲ/ን ዶ/ር መርሻ አለኸኝ፡- አንዳንድ ነጥቦች ስለ መጽሐፈ ፊደል /ወ/ጊዮርጊስ በተባሉ የኢ/ኦ/ተ/ ቤተ ክርስቲያን ሊቅ በብራና የጻፉት መጽሐፍ ላይ ተመሥርተው ያቀረቡት/

አቶ ይኩኖ አምላክ መዝገቡ፡- ሄዋን፣ ሔዋን፣ ፊደልና ትርጓሜ /በየኔታ አስረስ የኔሰው ጽሑፍ ላይ ተመስርተው ያቀረቡት/

ፕሮፌሰር ባዬ ይማም፡- ፊደል /ፊደልና ሥርዓተ ጽሕፈት፣ የሥርዓተ ጽሕፈት ዓይነት፣ ሥርዓተ ጽሕፈት ለማን. . /

አቶ ታደሰ እሱባለው፡- ተናባቢና አናባቢ ፊደሎች በእንዚራ ስብሐት መጽሐፍ /አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ የጻፉት መጽሐፍ ላይ በመነሣት ያቀረቡት/

ዶ/ር ሙሉ ሰው አስራቴ፡- ለውጥና የለውጥ ሙከራ በኢትዮጵያ ሥርዓተ ጽሕፈት

መ/ር ካሕሳይ ገ/እግዚአብሔር፡- ሞክሼ ቃላትና ዲቃላ ፊደላት በግእዝና በአማርኛ ቋንቋዎች ያላቸው ጠቀሜታ

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም፡- የኢትዮጵያ ፊደል ለኢትዮጵያ ቋንቋዎች

በሚሉ ርእሰ ጉዳዮች ላይ ጥናቶቻቸውን አቅርበዋል፡፡ በቀረቡት ጥናቶች መሠረት ከታሳታፊዎች አስተያየቶችና ጥያቄዎች በጥናት አቅራቢዎቹ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

የባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ የአማርኛ ቋንቋ ማበልጸጊያ ተቋም ምሁራን ከጥናቶቹ በመነሣት ሰፊ ግንዛቤ መጨበጣቸውንና በዩኒቨርስቲው ወደፊት ሊሠሩ የሚገባቸውንና በአገር አቀፍ ደረጃ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመወያየት በጥናት ላይ የተመረኮዘ ሥራዎችን በማዘጋጀትና በማቅረብ በፊደል ላይ እየታዩ ያሉ ተግዳሮቶችን ለመፍታት እንደሚሠሩ ገልጸዋል፡፡

በጉባኤው ላይ ከአዲስ አበባ የኒቨርስቲ፤ ከመቀሌ ዩኒቨርስቲ፤ ከባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ፤ እንዲሁም ከሌሎቹም ዩኒቨርስቲዎች የመጡ ምሁራን ጥናቶችን በማቅረብ፤ እንዲሁም ሐሳቦችን በማቅረብ ተሳትፈዋል፡፡

ስንክሳር በሰኔ አሥራ ሁለት ቀን የሚነበብ

ሰኔ 12ቀን 2007 ዓ.ም.

አንድ አምላክ በሆነ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሰኔ ዐሥራ ሁለት በዚች ዕለት የከበረ የመላእክት አለቃ የመልአኩ የሚካኤል የመታሰቢያውን በዓል ያከብራሉ፡፡

“ወበ እንተዝ ኢየኃፍር እግዚአብሔር ከመ ይትበሃል አምላኮሙ”

(ክፍል 2)

ሰኔ 8 ቀን 2007 ዓ.ም.

በቀሲስ ይግዛው መኰንን

4. ሰማያዊውን ሕይወት ናፋቂዎች ስለሆኑ

ክቡር ዳዊት “በቤትህ የሚኖሩ ሁሉ የተመሰገኑ ናቸው፤ ለዓለምና ለዘለዓለምም ያመሰግኑሃል፡፡ አቤቱ እርዳታው ከአንተ ዘንድ የሆነለት በልቡም የላይኛውን መንገድ የሚያስብ ሰው ምስጉን ነው፡፡” በማለት ሰማያዊውን መናፈቅ እንደሚያስመሰግን በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ተናገረ፡፡ መዝ. 83፥4

ቅዱስ ጳውሎስም የሚጠበቅበትን አገልግሎት ካከናወነ በኋላ “ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፤ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤” በማለት ምድራዊ ያይደለ ሰማያዊ ሕይወት ምን ያህል እንደሚናፈቅ ገልጿል፡፡ ፊል.1፥23 ለዚህ ነው ቅዱሳን በሥጋ የምኞት ፈረስ እንዲጋልቡ፥ በኃጢአት ባሕር እንዲዋኙ፥ በክፉ አሳብ ጀልባ እንዲቀዝፉ የሚፈታተናቸውን ርኩስ መንፈስ በመልካም ሥራቸው በመቃወም ድል የሚያደርጉት፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “ለእኛም ይገለጥ ዘንድ ካለው ክብር ጋር ቢመዛዘን የአሁኑ ዘመን ሥቃይ ምንም እንዳይደለ አስባለሁ፡፡” በማለት የአሁኑን ችግርና ፈተና ከሚመጣው ጋር በማመዛዘን የተናገረው፡፡ ሮሜ.8፥18

ቅዱስ ኤፍሬምም በውዳሴ ማርያም ጸሎቱ “ሰማዕታት በእውነት የዚህን ዓለም ጣዕም ናቁ፤ ስለ እግዚአብሔርም ሲሉ ደማቸውን አፈሰሱ፤ ስለመንግሥተ ሰማያትም ሲሉ መራራ ሞትን ታገሡ፡፡” በማለት የዚህን ዓለም መከራ መታገሥ ሰማያዊውን ክብር በማስታወስና የሚገኘውን ዋጋ በማመን እንደሆነ ገልጿል፡፡ /የሐሙስ ውዳሴ ማርያም/ ለዚህም ነው ሰማእታት እሳቱን ስለቱን፣ ጻድቃን ግርማ ሌሊቱን፥ ጽምፀ አራዊቱን፣ ጸብአ አጋንንቱን ታግሰው ሥጋቸውን ለነፍሳቸው አስገዝተው የኖሩበት ዐቢይ ምሥጢር፡፡

ሰማዕታት የሚታሰሩበትን ገመድ፣ የሚሰቀሉበትን ግንድ ይዘው ወደ ሞት ሲነዱ ጻድቃንም አስኬማቸውን ደፍተው፣ ደበሎአቸውን ለብሰው፣ ከምግበ ሥጋ ተለይተው ርሃቡን ጥሙን ችለው ሲኖሩ ደስ ይላቸዋል፡፡ ምክንያቱም ከፈጣሪያቸው እንደሚያገኙ ያውቃሉና ነው፡፡ መሬት ፊቷን ወደ ፀሐይ ስታዞር ብርሃን እንደምታገኝ፣ ፊቷን ስትመልስ ደግሞ ጨለማ እንደሚሆን ሳይንሱ ይነግረናል፡፡ የሰው ልጅም ፊቱን ወደ እግዚአብሔር ካዞረ ብርሃን ይሆንለታል፤ ፊቱን ከፈጣሪው ካዞረ ግን ይጨልምበታል፡፡ ኑሮው፣ ትዳሩ፣ መንገዱ ሁሉ የተሳካ እንዲሆን፣ የውስጥ ሰላምን እንዲያገኝ፣ በሚያገኘው ተደስቶ እንዲኖር፣ ሰላም፣ ጤና በረከት ከቤቱ እንዳይርቁ፣ አሸሼ ገዳሜ በሉ፣ አይዟአችሁ ጨፍሩ የሚለውን የጥንት ጠላት የአጋንንት ስብከት በመልካም ሥራ በዝማሬ በማኅሌት በሰዓታት በቅዳሴ፣ በኪዳን ተጠምዶመቃወም ያስፈልጋል፡፡

የዘወትር ስብከት “ሥጋችሁ በነፍሳችሁ ላይ ትንገሥ” የሚል ስለሆነ እኛ ግን ነፍሳችንን በሥጋችን ላይ ልናነግሣት እንደ አባቶቻችን ቅዱስን ሰማያዊውን ናፋቂዎች ልንሆን ያስፈልጋል፡፡ “ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈርስ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘለዓለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንፃ እንዳለን እናውቃለንና፡፡ በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፣ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና ለብሰን ራቁታችንን አንገኝም፡፡” እንዲል፡፡ 2ቆሮ.5፥1

5. ለሌላው አሳቢዎች በመሆናቸው

ለሌላው ማሰብ፥ ለሌላው መጨነቅ፥ ከሚደሰቱ ጋር መደሰት፥ ከሚያዝኑ ጋር ማዘን፥ ችግር የወደቀባቸውን ሰዎች የችግራቸው ተካፋይ መሆን ፈጣሪን መምሰል ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ “በአንድ አሳብ ተስማሙ፣ አንድ ፍቅር፣ አንድም ልብ፣ አንድም አሳብ ይሁንላችሁ፤ ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፤ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቁጠር፤ እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፡፡ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ፡፡

በክርስቶስ ኢየሱስ የነበረ ይህ አሳብ በእናንተ ዘንድ ደግሞ ይሁን፡፡” በማለት ከራስ ይልቅ ለሌላው ማሰብን እንድናስቀድም ያስተምረናል፡፡ ፊልጰ.2፥1 ታላቁ ሊቅም በሰቆቃወ ድንግል ላይ “ኢየሱስ ስዱድ ተስፋሆሙ ለስዱዳን፡፡ ኢየሱስ ግፉዕ ምስካዮሙ ለግፉዓን፡፡ እግዚአብሔር ማኅደር ዘአልቦ ከመ ነዳያን..” በማለት የጌታችን መሰደድ የተሰደደውን የሰውን ልጅ ለመመለስ እንደሆነ፤ ጌታችን ያለ በደሉ የተገፋው የተገፋ የሰውን ልጅ ሊያድን እንደሆነ፤ እግዚአብሔር ተስፋ፣ ላጡ ተስፋ ማረፊያ ቤት ለሌላቸው ማረፊያ እንደሆነ ይነግረናል፡፡ ይህንን ስለሚያውቁ ቅዱሳን ከራሳቸው በላይ ለሌላው ያስባሉ፡፡

“ይህንን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው፤ ያለዚያ ግን ከጻፍኸው መጽሐፍ እባክህ ደምስሰኝ አለ፡፡” የሚለውን የታላቁን ሰው የሙሴን ልመና ስንመለከት ምን ያህል ለሌላው ማሰብ እንደሚገባ እንማራለን ዘፀ.32፥32 ዛሬ ቢሆን ምናልባት ሌላውን ደምስሰህ እኔን ጻፍ ሳይባል ይቀራል ትላላችሁ፡፡ ቅዱሳን ግን እንደፈጣሪያቸው ለሌላው አሳቢወች በመሆናቸው “እግዚአብሔር አያፍርባቸውም” ተባለ፡፡

ዛሬም ሰው ለድሃ እጁን ሲዘረጋ እግዚአብሔር ደግሞ የምሕረት እጁን ይዘረጋለታል፡፡ የወደቀ ባልንጀራውን ሲያነሣ እግዚአብሔር እርሱን ከወደቀበት ያነሣዋል፡፡ የተጨነቀውን ሲያጽናና፥ የተጨቆነውን ነጻ ሲያወጣ ተስፋ ለቆረጠው ሲደርስለት በእውነት ዋጋው አይጠፋበትም፡፡ ለዚህ ነው ክቡር ዳዊት “ለችግረኛና ለምስኪን የሚያስብ ምስጉን ነው፤ እግዚአብሔር ይጠብቀዋል፤ ሕያውም ያደርገዋል፡፡” በማለት ያስተማረን፡፡ መዝ. 40፥1 ስለዚህ በዘመናችን ያለውን የወገንተኝነት፥ የትዕቢትና የሥጋዊነትን አስተሳሰብና አመለካከት በወንጌል መሣሪያነት አፈራርሶና ንዶ ለራስ ነጻ በመውጣት ለሌላውም መትረፍ ያስፈልጋል፡፡ ከነዚህ ክፉ ተግባራት ካልተለየን ገና ዛሬም በጨለማ ውስጥ ስላለን እንጠንቀቅ፡፡

“ልጄ ድሃውን ምጽዋቱን አትከልክለው ከሚለምንህ ከድሃውም ዓይኖችህን አትመልስ፡፡ የተራበች ሰውነትን አታሳዝን ያዘነ ሰውንም አታበሳጭ፡፡ ያዘነ ልቡናን አታስደንግጥ፣ የሚለምንህን ሰው አልፈኸው አትሂድ፡፡ የሚገዛልህ ቤተ ሰብህን አትቆጣ፤ ከድሃም ፊትህን አትመልስ፡፡” ካለ በኋላ ቀጥሎ “ከሚለምንህ ሰው ፊትህን አትመልስ፤ በልቡናው አዝኖ ቢረግምህ ፈጣሪው ልመናውን ይሰማዋልና፡፡”

በማለት ምስካየ ኅዙናን፣ ረዳኤ ምንዱባን የሆነ እግዚአብሔር የድሃውን ኀዘን ሰምቶ እንደሚበቀል ይነግረናል፡፡ ሲራ.4፥2 ስለዚህ የነዚህ ቅዱሳን ልጆች የሆን እኛ ፍትሕ ተጓድሎባቸው የሚሰማቸው አጥተው የሚገባቸውን፣ ተነፍገው፣ መከበር ሲገባቸው ተዋርደው ከሰው በታች ሆነው ለሚቆዝሙ ወገኖች ፈጥነን ልንደርስላቸው ይገባል፡፡ “ሳትሞት ለባልንጀራህ በጎ ነገርን አድርግ፡፡” ተብለን ተመክረናልና፡፡ ሲራ.14፥13

6. ለመከራ ራሳቸውን ያዘጋጁ በመሆናቸው

ከላይ እንዳየነው እምነታቸው በማዕበል ቢመታ የማይፈርስ እውነተኛ እምነት ስለሆነ ለመከራ አይበገሩም፡፡ ከእሳቱ ከሰይፉ ከመከራው በስተጀርባ የሚወርድላቸው አክሊለ ሕይወት ስለሚታያቸው ወደሞት ሲነዱ ደስ እያላቸው ይሄዳሉ፡፡ ራሳቸውን ለሞት ራሳቸውን ለስቅላት፣ ራሳቸውን ለእንግልት አዘጋጅተው በሃይማኖት ስለሚኖሩ፣ ፈጣሪ ያዝንላቸዋል፡፡ ደስ ይሰኝባቸዋልም፡፡ ያለ መከራ ዋጋ እንደማይገኝም ስለሚያውቁ “አቤቱ ቅጣኝ ነገር ግን እንዳታዋርደኝ በመጠን ይሁን እንጂ በቁጣ አይሁን፡፡” እያሉ ድሎትን ሳይሆን መከራ ሥጋን ይለምናሉ፡፡ ኤር.1፥24 ሥጋ ሲጎሰም ለነፍስ እንደሚገዛ ይረዳሉ፡፡

“ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል መከራ ወይስ ጭንቀት ወይስ ስደት፣ ወይስ ረሃብ ወይስ ራቁትነት፣ ወይስ ፍርሃት፣ ወይስ ሰይፍ ነውን “ስለ አንተ ቀኑን ሁሉ እንገደላለን፣ እንደሚታረዱ በጎች ተቆጥረን” ተብሎ እንደተጻፈ ነው፡፡ በዚህ ሁሉ ግን በወደድን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን፡፡ ሞት ቢሆን፣ ሕይወትም ቢሆን፣ መላእክትም ቢሆኑ ግዛትም ፍጥረትም ቢሆን፣ በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ፡፡” የሚለው የቅዱስ ጳውሎስም ትምህርት የሚያስተምረው ራስን ለመከራ ማዘጋጀትን ነው፡፡ ሮሜ.8፥35

ገበሬ ብርዱን፣ ዝናቡን፣ ፀሐዩን ታግሦ እሾሁን ነቅሎ መሬቱን አለምልሞ ተክል የሚተክለውና ከበቀለም በኋላ የሚኮተኩተው የሚያርመው ፍግ እያስታቀፈ የሚንከባከበው ውኃ እያጠጣ፣ ፀረ ተባይ መድኀኒት እየረጨ ከተባይ የሚጠብቀው፣ ቅጥር ምሶለት፣ አጥር አጥሮለት ከእንስሳት የሚያስጠብቀው በአጠቃላይ ብዙ የሚደክምለት መልካም ፍሬን ለማግኘት ነው፡፡ እንዲህ ከለፋ በኋላ አመርቂ ውጤት ቢያገኝ በልፋቱ ይደሰታል፡፡ በሚቀጥለውም ከመጀመሪያው የበለጠ እንክብካቤ ያደርግለታል፡፡ ካልሆነ ግን ያዝናል፡፡ ተክሉ ፍሬ አልባ ቢሆን ወይም ደግሞ ጣፋጭ ፍሬን እየጠበቀ መራራ ፍሬን ቢያፈራ ከማዘንም አልፎ እንዲቆረጥ ያደርገዋል፡፡ ዮሐ.15፥5፣ ማቴ.21፥18

ሰውም የእግዚአብሔር ተክል ነው፡፡ በቃለ እግዚአብሔር በምክረ ካህን ተኮትኩቶ በረድኤተ እግዚአብሔር አጥርነት ተጠብቆ የሚኖር የእግዚአብሔር የእጁ ሥራ ነው፡፡ ታዲያ ይህንን ስለሚያውቁ ቅዱሳን መልካም ፍሬን አፍርተው በመገኘታቸው እግዚአብሔር ተደስቶባቸዋል፡፡

ፍሬአቸው መራራ የሆኑ ተክሎች /ሰዎች/ ጨለማን ተገን አድርገው ሰው አየን አላየን ብለው ኀጢአትን የሚፈጽሙትን ያህል በእግዚአብሔር ቤት የተተከሉ፣ ፍሬአቸው ያማረ ቅዱሳን ጨለማው ሳይከለክላቸው ጽድቅን ሲሠሩበት ያድራሉ፡፡ በዓለም ላይ ለ5 ሺሕ 5 መቶ ዘመናት ኀጢአት በዓለም ላይ ነግሦ ይኑርም እንጂ በዚህ ኀጢአት በነገሠበት ዘመን ጽድቅን ሲሠሩ የኖሩ አባቶችና እናቶች ነበሩ፡፡ ዛሬም ኀጢአት በዓለማችን ላይ ጠፍንጎ ይዞ እያስጨነቀን እንዳለ ብንረዳም የነዚህ የቅዱሳን አበው በረከት ያደረባቸው በየገዳማቱ ወድቀው ለጽድቅ ራሳቸውን ሲያስገዙ እንመለከታለን፡፡

ማጠቃለያ

አንድን መንፈሳዊ ሥራ መጀመር ብቻውን የጽድቅ ምልክት አይደለም፡፡ ከላይ ያየናቸው የቅዱሳን ሕይወት ጽድቃቸው ከሰውም አልፎ በእግዚአብሔር የተመሰከረላቸው ከመጀመሪያው ይልቅ መጨረሻቸው በማማሩ ነው፡፡ ጀምረው ያቋረጡማ የሚነገርላቸው ማቋረጣቸው እንጂ ጽድቃቸው አይደለም፡፡ እንደሚታወቀው ሳጥናኤል የመላእክት አለቃ ነበር፡፡ አርዮስ ካህን፣ ይሁዳ ከሐዋርያቱ ጋር ተቆጥሮ የነበረ፣ ዴማስ ከአርድዕተ ክርስቶስ ከነ ሉቃስ ጋር ተደምሮ የነበረ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ ታዲያ እነዚህ ሰዎች የጀመሩትን መንፈሳዊ አገልግሎት ችላ ማለታቸው ከሰማይ ወደ ምድር፣ ከክብር ወደ ውርደት፣ ከሹመት ወደ ሽረት፣ ከማግኘት ወደ ማጣት ተወረወሩ እንጂ ምን ጠቀማቸው? በትናንት ማንነት ብቻ ድኅነት አይገኝም፡፡ ዛሬ የማያሳፍር ሥራን መሥራት እንጂ፡፡

ትናንት ዘመነኞች፣ ቅንጦተኞች፣ ኩሩዎች፣ የነበሩ ነገሥታት ወመኳንንት ዛሬ የት አሉ? በሀብታቸው የሚኩራሩ፣ በሥልጣናቸው የሚንጠራሩ፣ ፊታቸውን ከፈጣሪ ያዞሩ ሁሉ ጊዜ አልፎባቸው ገንዘባቸው፣ ሥልጣናቸው፣ ወገናቸው አላድናቸው ብሎ በጸጸት አለንጋ ከመገረፍ ውጪ ምንም አላገኙም፡፡ ስለዚህ ከዚህ መማር የዘመኑ ትውልድ ድርሻ ነው፡፡ በሃይማኖት ቁመው ከተጠቀሙት በሃይማኖት የመቆምን ጥቅም፣ ወድቀው ከተጎዱት የመውደቅን አስከፊነትና ጉዳት መማር እንችላለን፡፡

ስለዚህ ቆም ብለን ራሳችንን እንመርምር፡፡ በየመሥሪያ ቤታችን የምንሠራው ሥራ ሰውንና እግዚአብሔርን የሚያስደስት ነው ወይስ የሚያሳዝን፣ በአርአያውና በአምሳሉ ፈጥሮ በተለይ በሐዲስ ኪዳን “ከአሁን በኋላ ባሮች አልላችሁም፣ ልጆች ብያችኋለሁ፡፡” በማለት ያቀረበውን ፍጹምም የወደደውን የሰው ልጅ እንዴት እያየነው ነው? እውነት የምንሠራው ሥራ አሳፋሪ ነው ወይስ የሚያስደስትና የሚያስከብር? የሚለውን ጠይቀን ለራሳችን ምላሽ ልንሰጥ ያስፈልጋል፡፡ ያለ እግዚአብሔር መልካም ፈቃድ መልካምን ማድረግም አይቻልምና ለመልካም ሥራ እንዲያነሣሣን ኃይሉን ብርታቱንም እንዲሰጠን መልካም ፈቃዱ ይሁንልን፡፡

ልዩ የምክክር ጉባኤ

ግንቦት 27ቀን 2007ዓ.ም

በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእክል ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ አባላት ከአባለቱ ጋር ግንቦት 29ቀን 2007ዓ.ም ከቀኑ 10፡30 ጀምሮ የምክክር ጉባኤ ያደርጋል፡፡ ስለዚህ የአዲስ አበባ ማእከል አባላት በምክክር ጉባኤው እንድትገኙ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

የአዲስ አበባ ማእከል፡፡

የጎንደር ከተማ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት 3ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤውን አካሄደ

ግንቦት 25ቀን 2007 ዓ.ም

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ ከጎንደር ማእከል

ከግንቦት 22-23 ቀን 2007 ዓ.ም በመካነ ነገሥት ግምጃ ቤት ማርያም ቤተ ክርስቲያንና በደብረ ጽጌ መጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንት ቤተክርስቲያን 3ኛው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ሲካሄድ በጉባኤው ተገኝተው የመክፈቻ ንግግር ያደረጉት የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት የሰንበት ት/ቤት ምክትል ኃላፊ መልአከ በረሃ ገብረ ሥላሴ አድማሱ ናቸው፡፡ በአንድነት መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤው በአፈጻጸማቸው ከ1-3 ለወጡት ለደብረ ምሕረት አቡን ቤት ቅዳሴ ለገብርኤል ሰንበት ት/ቤት፤ ለልደታ ለማርያም ሰንበት ት/ቤትና ለወልደነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ሰንበት ት/ቤት በቅደም ተከተል ተሸልመዋል፡፡ ልምዳቸውንም አካፍለዋል፡፡ በሰንበት ት/ቤቶች በአገልግሎት ዘመን ቆይታ ያላቸው ወንድሞች የሕይወት ልምዳቸውንና ምክራቸውን ለጉባኤው ተሳታፊዎች አካፍለዋል፡፡

የጎንደር ከተማ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት በሥሩ በ፬ት ክፍለ ከተማ የተከፈለ መዋቅር አለው (ሰሜን፣ ደቡብ፣ ምዕራብና ምሥራቅ ተብለው የሚጠሩ) በሥራቸው 5 ወይም 6 ሰንበት ት/ቤቶች ይገኛሉ፡፡

በየክፍለ ከተማው የሚገኙ የሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶች መንፈሳዊ ጉባኤ በኅብረት ያካሂዳሉ በየ6 ወሩ ደግሞ በየክፈለ ከተማው ያሉት 24ቱም ሰ/ትቤቶች የጋራ ጉባኤ ያካሂዳሉ፡፡

በ2008 ዓ.ም የአራተኛው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ አዘጋጅ የምዕራብ ክፍለ ከተማ ሰንበት ት/ቤት እንደሆነ በዕለቱ ተገልጿል፡፡

በጉባኤው ከ800 በላይ የሰንበት ተማሪዎች ተገኝተዋል፡፡

በአንድነት መርሐ ግብሩ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ትኩረት የሚሹ ጉዳዮች

1. የሰ/ትቤት የአለበት በቁጥር መቀነስ
2. ከሰበካ ጉባኤና ከማኅበረ ካህናት ሰ/ትቤቱ ድጋፍ ያለመኖር
3. የሰንበት ት/ቤት የአዳራሽ እጥረት
4. የሰ/ትቤቶችና የሰበካ ጉባኤያት የፋይናንስ መዋቅር ግንኙነት የተስተካከለ አለመሆን
5. የመምህራን እጥረት
6. የገቢ ምንጭ አለመኖር የተወሰኑት ነበሩ

የሰንበት ተማሪዎች የወደፊቱ የቤተክርስቲያኒቱ ተተኪዎች በመሆናቸው ሁሉም የሚመለከታቸው አካላት ለሰንበት ት/ቤቶች መጠናከር የበኩሉን አስተዋጽኦ ማድረግ ይኖርበታል፡፡

ƒƒ

የጅማ ማእከል የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር አካሄደ

ግንቦት 25 ቀን 2007 ዓ.ም.

ጅማ ማእከል

በማኅበረ ቅዱሳን የጅማ ማእከል ያዘጋጀው ሁለተኛው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ግንቦት 22 ቀን 2007 ዓ.ም. በኮሳ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ተካሄደ፡፡

የጉዞውን መነሻ በጅማ ሀገረ ስብከት ሁለገብ( አቡነ እስጢፋኖስ) ሕንፃ በማድረግ ከጠዋቱ 12:00 ሰዓት ጀምሮ ከ800 በላይ ምእመናንን በማሳተፍ በሊሙ ኮሳ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር ወደምትገኘው ኮሳ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አድርጓል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ከ2000 በላይ የሚሆኑ የአጥቢያው ምእመናን፣የሀገረ ስብከቱ ስራ አስኪያጅ መልአከ ብርሃን ስለሺ አስፋው፣የወረዳው ቤተ ክህነት ሊቀ ካህን ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ መሰረት፣ ሌሎች የሀገረ ስብከቱ የሥራ ሓላፊዎች፣ በጅማ ከተማ የሚገኙ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ፣ የአጎራባች ወረዳ ማእከላትና የግንኙነት ጣቢያ አባላት፣ የጅማ ማእከል አባላት፣ በከተማዋ ውስጥ የሚገኙ መንፈሳዊ ማኅበራት እና በጎ አድራጊ ተጋባዥ እንግዶች ተገኝተዋል፡፡

ክፍል አንድ ትምህርት ወንጌል በመጋቤ ሐዲስ ቀሲስ መንግስቱ አማረ፤ የጥንታዊቷና ታሪካዊቷ ቤተክርስቲያን የ200 መቶ ዓመት ታሪክ በሰበካ ጉባኤ ተወካይ ፡ እንዲሁም የማኀበረ ቅዱሳን የአገልግሎት እንቅስቃሴና መልእክት በአቶ ቡሩክ ወልደ ሚካኤል ቀርበዋል፡፡

ከምእመናን ለቀረቡ ጥያቄዎች ምክረ አበው መርሐ ግብር በሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ እና በመጋቤ ሐዲስ ቀሲስ መንግስቱ አማረ ማብራርያ ተሰጥቷል፡፡በመቀጠል ክፍል ሁለት የወንጌል ትምህርት በሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ ተሰጥቷል፡፡

የትምህርት መርሐ ግብሩ እንደተጠናቀቀ ቤተክርስቲያኗን በአዲስ መልክ ለመሥራት የተጀመረውን ጥረት የሚያግዝ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር የተካሄደ ሲሆን ከ130,000(አንድ መቶ ሰላሳ ሺህ )በላይ በጥሬ እና በቁሳቁስ ለማሰባሰብ ተችሏል፡፡

በመጨረሻም የሀገረ ስብከቱ ስራ አስኪያጅ መልአከ ብርሃን ስለሺ ስለነበረው መርሐ ግብር እና አስፈላጊነት ሰፊ ማብራርያና ግንዛቤ ለምዕመናን የሰጡ ሲሆን ይህንን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ያዘጋጀውን የጅማ ማዕከልን አመስግነዋል፡፡በማስከተልም ማኀበረ ቅዱሳን የቤተክርስቲያንን አገልግሎት ለማገዝ እየፈጸመ ያለውን አገልግሎት አድንቀው ምእመናንም ይህንን የማኀበሩን አገልግሎት ከጎን በመሆን ማገዝና መረዳት እንደሚገባ በማስገንዘብ መርሐግብሩ በጸሎት ተዘግቷል፡፡

ከመርሐግብሩ መጠናቀቅ በኃላ የምእመናንን አስተያየት የተሰበሰበ ሲሆን በመርሐግብሩ መደሰታቸውንና ለወደፊቱም እንደዚህ አይነት መርሐግብር በአመት ሁለት እና ሦስት ጊዜ መዘጋጀት እንዳለበት ገልጸው፤ ስለቤተክርስቲያን ወቅታዊ ሁኔታና የማኀበሩን አገልግሎት ለማወቅ እንደረዳቸው ገልጸዋል ፡፡

የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፡፡ (ዮሐ.16፡13)

ግንቦት 23ቀን 2007ዓ.ም

ዲ/ን ሚክያስ አስረስ

ይህች ዓለም ከእውነትን የራቀች መኖሪያዋን ሐሰት ያደረገች መሆኗ ይታወቃል፡፡ ሰው ማንነቱን አጥቶ በበደል ምክንያት በሐሰት ሰጥሞ ኖሯል፡፡ ሰው በፈቃዱ ጥመት ምክንያት ከሚፈጽማቸው በደሎች ትልቁ በደል ውሸት ነው፡፡ ውሸት ተሸንፎ ይወድቃል፤ ከሕይወት ይርቃል፡፡ የኀጣውእ ሁሉ ራስ ሐሰት ናት፡፡ ለዚህ ነው ክፋትን ከራሱ አንቅቶ የበደለ ዲያብሎስ አቡሃ ለሐሰት፤ የሐሰት አባት(ዮሐ.8፡44) የተባለው፡፡

አዳም እና ሔዋንን ለሞት ያደረሰ ያልሆኑትን፤ ሊሆኑ የማይችሉትን እንሆናለን ብሎ ከሐሰት ጋር መተባበራቸው ነው፡፡ ሐሰት የሆኑትንና የተሰጣቸውን እንደዘነጉ አድርጎ ማግኘት የማይችሉትን የባሕርይ አምላክነትን አስመኛቸው፡፡ እነርሡ በበደል ወድቀው፤ ከገነት ርቀው ልጆችን በመውለድ ሲባዙ ሐሰት ግዛቷን አስፍታ በኃይል በርትታ እውነት እስኪገለጥ ድረስ ቆየች፡፡ እውነት እግዚአብሔር በሰው ባሕርይ ሲገለጥ የእውነት መንገድን (ሃይማኖትን) ዳግመኛ ሰጠ፡፡ የዓለም መድኃኒት ክርስቶስ ከፈጸመው ድኅነት ለመሳተፍ ሰው ሐሰት ከተባሉ አምልኮ ጣዖት፣ ራስ ወዳድነት እና ሴሰኝነት ርቆ በእውነት ሊኖር የግድ ነው፡፡ እርሡ ሁሉ እንዲድኑ እውነትንም እንዲያውቁት ይወዳልና፡፡(1.ጢሞ 2፡4) እንደተባለ ሰውም ቢሆን በእውነት ጸንቶ ለመኖር በመፍቀድ ከእግዚአብሔር ጋር በፈቃድ አንድ መሆን አለበት፡፡

የአንድነት ሦስትነት ምሥጢር የተገለጠው አምላክ ሰው በመሆኑ ነው፡፡ ይልቁንም ሰው ወደዚህ እውነት እንዲመጣ የሚያደርገው መንፈስ ቅዱስ ወደ ደቀመዛሙርት የወረደው ሰው የሆነ አምላክ ክብሩን በመስቀል ሞት ሲገልጽ ነው፡፡ ክርስቶስ ስለእኛ ብሎ በመስቀል ላይ ባይሞት መንፈስ ቅዱስ አይወርድም ነበር፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ ሕይወቱ መንፈስ ቅዱስ እንደሚመጣ አካሉ ለሆነች ለቤተ ክርስቲያንም ሕይወት እንደሚሆናት የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል(ዮሐ 16፡13) በማለት አስቀድሞ ተናገረ፡፡ መንፈስ ቅዱስ መምጣቱ አምላክ ሰው ሆኖ የፈጸመውን ለመረዳት እና ለማመን ለማስቻል ነው፡፡ ክርስቶስን በመድኃኒትነቱ ለመግለጽ ነው፡፡ ለዚህ ነው የተወደደ ሐዋርያ ዮሐንስ መነሻ ያደረግነውን ኃይለ ቃል ከተናገረ በኋላ ወውእቱ ኪያየ ይሴብሕ፤ እርሱ እኔን ይገልጻል፡፡(ዮሐ.16፡14) ያለው፡፡ እንዲሁ በበደል ከወደቀ በኋላም በሥላሴ ፈቃድ በወልድ ሰው መሆን በመንፈስ ቅዱስ መሠጠት ከወደቀበት ተነሥቶ ድኅነት (ሁለተኛ ተፈጥሮ) ተፈጸመለት፡፡ አዳም ሲፈጠር መንፈስ ቅዱስን ተቀብሎ እንደከበረ (ዘፍ.2፡1) እንዲሁ ይኸው መንፈስ ቅዱስ በእሳት አምሳል ለክርስቶስ ደቀመዛሙርት ወረደ፡፡ ጸጋ ሆኖ ተሠጣቸው፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ሰማይ ከማረጉ በፊት የአብን ተስፋ መንፈስ ቅዱስን ደጅ እንዲጸኑ ይኸንንም በኢየሩሳሌም በአንድነት በመቆየት እንዲያደርጉ አዘዛቸው፡፡ (ሉቃ 24፡49) ደቀ መዛሙርቱም መቶ ሃያ ሆነው በኢየሩሳሌም በማርቆስ እናት ቤት አስቀድሞ ምሥጢረ ቁርባን በተመሠረተበት ቦታ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን እናት እመቤታችንን በመሐል አድርገው በጸሎት በአንድነት በኢየሩሳሌም ቆዩ፡፡ (ሐዋ.1፡14)፡፡ እመቤታችን ባለችበት መንፈስ ቅዱስ ይወርዳልና፤ አስቀድሞ በወንጌል ቅድስት ኤልሳቤጥ እመቤታችን ወደ እርሷ ስትሄድ “መንፈስ ቅዱስ ሞላባት” (ሉቃ.1፤41 ) ተብሎ እንደተነገረላት፡፡ ከዚያም ረቂቅነቱን እና ኃያልነቱን ሲያጠይቅ መንፈስ ቅዱስ ከወደ ሰማይ እንደ ዐውሎ ነፋስ ባለ ድምፅ መጣ፡፡ ደቀመዛሙርት ባሉበት ቤት ገብቶ ሲመላው የተከፋፈሉ የእሳት ልሳኖች ሆኖ ታያቸው፤ በሁሉም አደረባቸው (ሐዋ.2፡3) ሁሉም ኃይልን ዕውቀትን አገኙ፤ በአገራትም ሁሉ ቋንቋዎች ተናገሩ፡፡ ስለ እውነት ደፋሮች ሆኑ፡፡ በነቢይ እሰውጥ እምነ መንፈስየ ዲበ ኩሉ ዘሥጋ፤ በሥጋ ለባሽ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ(አዩ 3፡1) ተብሎ የተነገረው ዛሬ ተፈጸመ፡፡

አንዲት ቤተክርስቲያንን በአንድነቷ ለዘለዓለም የሚያኖራት እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ እንዲህ ስንል አብን እና ወልድን በመተው አይደለም፡፡ የሦስቱም ማደርያ ትሆናለች እንጂ፡፡ ዛሬም በቤተ ክርስቲያን ምሥጢራትን ይገልጥልን ዘንድ አለ፡፡ â€Ãƒ‚¹ÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚¹እኛስ የክርስቶስ ልብ አለን፡፡â€Ãƒ‚ºÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚º (1ቆሮ.2፡16) እንዳለ ብርሃን ቅ/ጳውሎስ፡፡ የክርስቶስ ልብ የሆነ እግዚአብሔር አብ â€Ãƒ‚¹ÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚¹እኛâ€Ãƒ‚ºÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚º በተባልን በቤተ ክርስቲያን አለ ማለቱ ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተለየ አካሉ ሰው ሆኖ በሕማሙ እና በሞቱ፤ በትንሣኤውና በዕርገቱ ድኅነትን ፈጸመ፡፡ አሁንም በቤተ ክርስቲያን እርሱ ሊቀ ካህናት ኢየሱሰ ክርስቶስ በአባቶች ካህናት ላይ በረድኤት አድሮ ምሥጢራትን ይፈጽማል፡፡ â€Ãƒ‚¹ÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚¹ኦ እግዚኦ በከመ አሜሃ ዘንተ ኅብሰተ ባርክ ወቀድስ ወወሃብ፤ አቤቱ እንደዚያን ጊዜ ይህን ኅብስት ባርከው ሥጋህን አድርገው ቁረሰው እንዲሁ ስጥâ€Ãƒ‚ºÃƒÃ‚¢€Ãƒ‚º (ቅዳሴ ማርያም) የተባለውን ማስተዋል በቂ ነው፡፡ መንፈስ ቅዱስ የአንድነት መንፈስ ነውና፡፡

ከእግዚአብሔር ጋር አንድ የሚያደርጉንን ምሥጢራት ራሱ እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ያከናውናቸዋል፡፡ ካህኑ ውኃውን ሲባርኩት በዕለት ዓርብ ከጌታ ጎን የፈሰሰውን ውሃ ያደርግላቸዋል በዚያ ማየገቦ (የጎን ውሃ) አዲስ አማኝ ተጠምቆ የእግዚአብሔርን ልጅነት አግኝቶ ከእርሱ ጋር አንድ ይሆናል፡፡ ካህናቱ የከበረውን የቅዳሴ ጸሎት ሲጀምሩ ያቀረቡትን ኅብስት እና ወይን እንዲህ ነው በማይባል አኳኋን የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ እና ደም የሚያደርገው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ከእርሱ ጋር አንድነትን እናገኛለን፡፡ ሰው ንስሐ እንዲገባ በበደሉ እንዲጸጸት በሰው ውስጥ ሆኖ የንስሐን ደወል የሚያሰማው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ይህን የንስሐ ጥሪ በእሽታ ቢቀበል ዳግመኛ ከቤተ ክርስቲያን ተደምሮ ከእግዚአብሔር ጋር በአንድነት ይኖራል፡፡ ጥሪውን በእንቢታ አልፎ እስከ ሞት ድረስ በዚህ ቢጸና መንፈስ ቅዱስን ተሳድቧልና ኃጢአቱ አይሠረይለትም፤ ከሞት በኋላ ንስሐ የለምና፡፡ (ማቴ. 12፡32) ለተቀበሉት ግን አሁንም መንፈስ ቅዱስ አንድነትን የሚያድል መሆኑን እናስተውል፡፡ እኛ እርስ በእርስ በአንዲት ሃይማኖት ተባብረን ከአንድ መሥዋዕት ተካፍለን አንድ ርስትን ተስፋ በማድረግ አንድ የሚያደርገን እርሱ መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡

በቅዳሴያችን ሀበነ ንኅበር በዘዚአከ መንፈስ ቅዱስ፤ ባንተ ህልውና ባለ መንፈስ ቅዱስ አንድ አድራጊነት አንድ እንሆን ዘንድ አንድ መሆንን ሰጠን፡፡ በማለት አንድ አድራጊያችን እርሱ እንደሆነ እንመሠክራለን፡፡ አንድ ሆነን በአንድነት ከጸናን እንደ ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስን ለመቀበል የበቃን የተዘጋጀን ስለምንሆን ቀጥለን ፈኑ ጸጋ መንፈስ ቅዱስ ላዕሌነ፤ በእኛ ላይ ጸጋ የሚባል መንፈስ ቅዱስን ላክበማለት እንለምናለን፡፡ በዚህ በግዙፉ ዓለም ባለች ሰማያዊ መንግሥት በቤተ ክርስቲያን እንደተባበርን በዚያች ለምድራውያን ሰዎች ዓለም ሳይፈጠር በተዘጋጀችው መንግሥት አንድ እንሆናለን፡፡ ሐዋርያው መንግሥተ ሰማያትን የእግዚአብሔር መንግሥት በመንፈስ ቅዱስ የሆነ ደስታ እንጂ መብል መጠጥ አይደለምና(ሮሜ.14፡17) በማት ይናገርላታል፡፡

መንፈስ ቅዱስ በወረደላቸው ዕለት ደቀ መዛሙርት ምሥክርነታቸውን ማሠማት ጀመሩ፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ህዝቡ በተሰበሰቡበት በዚያን ዕለት መንፈስ ቅዱስ መውረዱና እነርሱ በቋንቋዎች መናገራቸው እንዲሁ እንደ እንግዳ ደርሶ የመጣ ሳይሆን አስቀድሞ በነቢያት ትንቢት የተነገረ መሆኑን አስታወቀ፡፡ ዳግመኛም ክርስቶስ በነቢያት እንደተነገረለት ሞቶ ከሙታን እንደተነሣ ሰበከላቸው፡፡ የሚሰሙት ሕዝቡ እርሱ የተናገራቸው ከልባቸው ስለገባ ምን እናድርግ አሉ (ሐዋ 2፡37)፡፡ ነስሑ ወተጠመቁ ኩልክሙ በስሙ ለኢየሱስ ክርስቶስ፤ ንስሐ ግቡ ሁላችሁም በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አምናችሁ ተጠመቁ(ሐዋ 2፡38) ብሎ ቅዱስ ጴጥሮስ መለሰ፡፡ እንዲህ ባለ ሁኔታ ነፍሳት ወደ ቤተክርስቲያን እየተደመሩ ቤተክርስቲያን ከኢየሩሳሌም እስከ ዓለም ዳርቻ ምሥክርነቷን አደረሠች፡፡ እንዲሁ ሰው የክርስትናን ጥምቀት ተጠምቆ ጸጋ መንፈስ ቅዱስን ገንዘብ ካደረገ ከሚኖርበት ከቤቱ ጀምሮ ምሥክር ሆኖ ወደ ዓለም መውጣት እንዳለበት መገንዘብ ይቻላል፡፡ 

ቤተ ክርስቲያን ከእግዚአብሔር ምሥጢራት ተሳትፋ ጸጋ ነሣእነ ወሕይወተ ረከብነ፤ ጸጋን ተቀበልን ሕይወትንም አገኘን፡፡ብላ በዚያው ባለችበት አትቀመጥም፡፡ ምእመናን ይህን የእግዚአብሔርን ቸርነት እንደቀምሱ ለዓለሙ ሁሉ ምሥክር እንዲሆኑ በቅዳሴ ምክንያት ወደ ሰማይ በሕሊና የወጣችው እትዉ በሰላም፤ በሰላም ወደቤታችሁ ግቡ ትላቸዋለች፡፡ በዓለም ሲኖሩ ከፈቃዱ ባይተባበሩ እንደ ክርስቶስ በፍቅር ያገለግሉ ዘንድ፡፡ የቀመሱትን የእግዚአብሔር ፍቅር በምግባራቸው ለዓለም ይመሠክራሉ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር