bahirdar02

የባሕር ዳር ማእከል የጽ/ቤት ግንባታ በቅርቡ እንደሚጠናቀቅ ተገለጸ

 

ኅዳር 16 ቀን 2007 ዓ.ም.

ግዛቸው መንግሥቱ /ከባሕር ዳር ማእከል/

bahirdar02በማኅበረ ቅዱሳን የባሕር ዳር ማእከል በደብረ ጽዮን ሰላም አድርጊው ማርያም ገዳም በተሠጠው ቦታ በመገንባት ላይ የሚገኘው ጽሕፈት ቤት በቅርቡ እንደሚጠናቀቅ የጽ/ቤት ግንባታ ኮሚቴ የቴክኒክ ክፍል አስተባባሪ አቶ አስናቀ ለወየ አስታወቁ፡፡

የሕንፃ ግንባታ ኮሚቴው ኅዳር 7 ቀን 2007 ዓ.ም እየተገነባ ያለውን ጽሕፈት ቤት በተያዘለት እቅድ መሠረት እየተጠናቀቀ መሆኑን ለአባላቱ ለማብሠርና ድጋፋቸውን አጠናክረው እንዲቀጥሉ ለማድረግ በተዘጋጀው መርሐ ግብር ላይ የኮሚቴው አስተባባሪ አቶ አስናቀ ለጽሕፈት ቤት ግንባታ የሚሆን ቦታ ለሰጠውና በዐሳብና ልዩ ልዩ ድጋፍ በማድረግ ላይ ለሚገኘው ለደብረ ጽዮን ሰላም አድርጊው ማርያም ገዳም ሰበካ ጉባኤ፣ እንዲሁም የግንባታውን ወጪ ወርሃዊ ደመወዛቸውን በመለገስ ሙሉ በሙሉ ለሚሸፈኑት የማኅበሩ አባላትን አመስግነዋል፡፡ እየተገነባ ያለው ጽሕፈት ቤት የመጀመሪያ ምእራፍ ሲሆን፤ የጣራ ሥራውና ቆርቆሮ ማልበሱ በኅዳር ወር፤ ሙሉ ግንባታው ደግሞ እስከ ጥር 30 ቀን 2007 ዓ.ም. ተጠናቆ አገልግልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ገልጸዋል፡፡

ኮሚቴው ባቀረበው ሪፖርት እየተገነባ ያለው ጽሕፈት ቤት በቋሚነት የሚያገለግለው ለአዳራሽነት ሲሆን፤ ለቢሮ የሚያገለግሉ ክፍሎች በሁለተኛው የግንባታ ምእራፍ ከገዳሙ በተገኘው ክፍት ቦታ ላይ እንደሚገነቡ ተጠቅሷል፡፡ የጽሕፈት ቤቱ የመጀመሪያ ምእራፍ ግንባታ ልዩ ልዩ የሙያ ድጋፎችን ሳይጨምር እስከ 600,000 ብር የሚፈጅ በመሆኑ አባላት በሙያና በገንዘብ የሚያደርጉትን ድጋፍ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ኮሚቴው ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

ግንባታው ሲጠናቀቅ የባሕር ዳር ማእከል፣ የሰሜን ምእራብ ማእከላት ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት፣ የጣና ወረዳ ማእከልና ግቢ ጉባኤያት እንደሚገለገሉበት የተጠቀሰ ሲሆን፤ የጽሕፈት ቤቱ መገንባት ለማእከሉና ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤቱ ለሚፈጽሟቸው የቤተክርስቲያን አገልግሎት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እንደሚያበረክት ተገልጿል፡፡

የማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ በ2003 ዓ.ም ጽሕፈት ቤት መገንባት እንዳለበት ለአባላቱ ዐሳብ በማቅረብ፤ የጽሕፈት ቤት ግንባታ ኮሚቴ በማቋቋም አባላት ገንዘባቸውን አሰባስበው ግንባታውን ለመጀመር ጥረት ተደርጓል፡፡ ነገር ግን በተለየዩ ችግሮች ምክንያት የዘገየ ቢሆንም በጥቅምት 2005 ዓ.ም አሁን የሚያገለግልበትን ጊዜያዊ ጽ/ቤትና የግንባታ ቦታ በደብረ ጽዮን ሰላም አድርጊው ማርያም ገዳም ለማግኘት በመቻሉ ማእከሉ አገልግሎቱን ለማጠናከርና በርካታ ሥራዎችን እንዲሠራ አስችሎታል፡፡
ግንቦት 29 ቀን 2006 ዓ.ም. ለጊዜው ተቋርጦ የነበረውን የጽሕፈት ቤት ግንባታ ፕሮጀክት አዲስ ኮሚቴ በማዋቀር ወደ ተግባር ለመሸጋገር እንቅስቀሴ ተጀመረ፡፡ ኮሚቴው ለግንባታ በሀብትነት ይዞት የተነሳው የባሕር ዳር ማእከል አባላትን ብቻ በመሆኑ አባላትን በማወያየት የወር ደመወዛቸውን በዐራት ጊዜያት ከፍለው እንዲያጠናቅቁ በማስወሰን ገንዘባቸውን በመለገስ፤ በሙያ በመደገፍ ባደረጉት ብርቱ ጥረት አሁን የጽሕፈት ቤት ግንባታው በተያዘለት እቅድ መሠረት እየተከናወነ መሆኑን ኮሚቴው አስታውቋል፡፡

የባሕር ዳር ማእከል በማእከልነት የተቋቋመውና አገልግሎቱን የጀመረው በ1985 ዓ.ም ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት በማእከልነት ተደራጅተው ሰፊ አገልግሎት እየፈጸሙ ያሉትን ዘጠኝ ማእከላት አቅፎ ነበር፡፡ ማእከሉ እንደተመሰረተ አገልግሎቱን ይፈጽም የነበረው በምእራብ ጎጃም ሀገረ ስብከት በተሰጠችው አነስተኛ አንድ ክፍል ጽሕፈት ቤትና በግለሰብ ቤት እንደነበረ የጽሕፈት ቤት ግንባታ ኮሚቴው አስታውቋል፡፡ የባሕር ዳር ማእከል ከተቋቋመበት ዓላማ አንጻር አገልግሎቱን ለመፈጸም እንዲችል ከ1985 ዓ.ም እስከ ጥቅምት 2005 ዓ.ም ድረስ በባሕር ዳር ከተማ በተለያዩ ቦታዎች ዘጠኝ ጽ/ቤቶችን በመከራየት ሰፊ አገልግሎት የፈጸመ ቢሆንም ለከፍተኛ የቢሮ ኪራይ ወጭ ሲዳረግ የቆየ መሆኑ ተጠቅሷል፡፡

ማእከሉ አገልግሎት ይፈጽምባቸው የነበሩ ጽ/ቤቶች የነበሩበት አካባቢ ለመንፈሳዊ አገልግሎት የማይመቹ አስቸጋሪና ከቤተክርስቲያን ቅጽር የራቁ በመሆናቸው ማእከሉም ሆነ አባላቱ የማይረሱ ፈተናዎችና ችግሮችን እንዳሳለፉ የቀደሙ የማእከሉ አባላት ይገልጻሉ፡፡ ለረጅም ዓመታት ጽሕፈት ቤት ባለመኖሩ የደረሰበት ፈተናና በአገልግሎቱ ላይ የተፈጠረበት ጫና የማእከሉ ሥራ አስፈጻሚ ዓላማውን ለማሳካትና ለአገልግሎቱን በአግባቡ ለመፈጸም የሚያስችለውን ምቹ ጽሕፈት ቤት መገንባት እንዲያስብና አባላቱም በቆራጥነት ለግንባታው እንዲነቃቁ እንዳደረጋቸው የጽሕፈት ቤት ግንባታ ኮሚቴው አስታውቋል፡፡

በተያዘ ዜና በማኅበረ ቅዱሳን በባሕር ዳር ማእከል የደብረ ሰላም ወረዳ ማእከል ከወረዳ ማእከሉ አባላት ገንዘብ በማሰባሰብ ከደብረ ሰላም በዓለ እግዚአብሔር ቤተክርስቲያን ባገኘው ቦታ ላይ ባለ 4 ክፍል ጽ/ቤት ገንብቶ የጣሪያ ማልበስና የግድግዳ ግርፍ ስራውን ማጠናቀቁና በአጭር ጊዜ ውስጥ ለአገልግሎት እንደሚያበቃ የወረዳው ማእከል አስታውቋል፡፡

 

 

‹‹አንተ በጎና ታማኝ አገልጋይ›› ማቴ:25

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ 

ህዳር 15 ቀን 2007 ዓ᎐ም

ልዑል እግዚአብሔር አምላካችን በክቡር ዳዊት አድሮ፤ “እከሥት በምሳሌ አፉየ፤ ወእነግር አምሳለ ዘእምትካት፤ አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ፤ ከቀድሞ ጀምሮ ያለውንም ተምሳሌት እናገራለሁ” ብሏል፡፡ /መዝ. 77፡2/
በዚሁ መሠረት ጌታችን ወንጌለ መንግሥተ ሰማያትን በልዩ ልዩ ምሳሌ አስተምሯል፤ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 25 ሁለት ምሳሌያትና አንድ ትንቢት ቀርበዋል፡፡

 

 ከምሳሌያቱ የመጀመሪያው በዐሥሩ ደናግል አንጻር የቀረበው ሲሆን ሌላኛው ደግሞ ወጥተው ወርደው ነግደው ያተርፉበት ዘንድ ገንዘቡን ስለሰጠ ነጋዴ የሚናገረው ነው፡፡ ትንቢቱም ስለ ኅልቀተ ዓለም የተነገረ ነው፡፡ እንግዲህ በዚህ ዕትማችን ነግደው እንዲያተርፉበት ከጌታቸው የተሰጣቸውን መክሊት ስለተቀበሉት አገልጋዮች እንመለከታለን፡፡ ፈጣሪያችን ለብዎውን ማስተዋሉን ያድለን፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ ያስተማራቸውን ምሳሌያዊ ትምህርቶችን በሰፊው ተጽፎ እናገኛለን፡፡

የእነዚህ ትምህርታዊ ምሳሌዎች መሠረታዊ ሀሳብና ዓላማ የእግዚአብሔርን መንግሥት የምናገኝበትን የታማኝነትን ሥራን እንዴት መሥራት እንደሚገባንና እንደምንችል ማስተማር ነው፡፡
ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስለ መንግሥተ ሰማያት ምሥጢር ያስተማራቸው ብዙ ምሳሌዎች ያሉ ሲሆን ከእነዚህ ብዙ ምሳሌዊ ትምህርቶች መካከል በማቴዎስ ወንጌልም 25 ላይ እንዲያተርፉበት መክሊት ስለተሰጣቸውና ወጥተው ወርደው ሌላ አትረፈው በጌታቸው ስለተመሰገኑት ቸርና መልካም አገልጋዮች፣ እንዲሁም መክሊቱን በመቅበሩ ምክንያት በጌታው ስለተወቀሰውና ፍርድን ስለተቀበለው ሰው ታሪክ፣ የታሪኩም ምሥጢር ምን እንደሚመስል ነው፡፡

 

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህንን ምሳሌ የተናገረው በሚከተለው መልኩ ነበር ‹‹ወደ ሌላ ሀገር የሚሄድ ሰው ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንደሰጣቸው እንዲሁ ይሆናልና ለእንዳንዱ እንደ ዓቅሙ ለአንዱ አምስት መክሊት ለአንዱ ሁለት ለአንዱም አንድ ሰጠና ወደ ሌላ ሀገር ወዲውኑ ሄደ፡፡ አምስት መክሊትም የተቀበለው ሄደ ነገደበት ሌላም አምስት አተረፈ እንዲሁም ሁለት የተቀበለው ሌላ ሁለት አተረፈ፡፡ አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ ምድርን ቆፈረና የጌታውን ገንዘብ ቀበረ፡፡
ከብዙ ዘመንም በኋላ የእነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው፡፡

 

አምስት መክሊት የተቀበለውም ቀረበና ሌላ አምስት መክሊት አስረክቦ፡- ጌታ ሆይ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፡ እነሆ ሌላ አምስት መክሊት አተረፍሁበት አለ፡፡ ጌታውም፡- መልካም አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ:: ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፡- ጌታ ሆይ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር፡፡ እነሆ ሌላ ሁለት መክሊት አተረፍሁበት አለ፡፡ ገታውም፡- መልካም አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ:: ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡

አንድ መክሊትም የተቀበለው ደግሞ ቀርቦ፡- ጌታ ሆይ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህባትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁ፤ ፈራሁም ሄጄም መክሊትህን በምድር ቀበርሁት እነሆ መክሊትህ አለህ አለው፡፡ ጌታውም መልሶ እንዲህ አለው፡- አንተ ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ ካልዘራሁበት እንዳጭድ ካልበተንሁባትም እንድሰበስብ ታውቃለህን:: ስለዚህ ገንዘቤን ለለዋጮች አደራ ልትሰጠው በተገባህ ነበር:: እኔም መጥቼ ያለኝን ከትርፉ ጋር እወስደው ነበር፡፡ ስለዚህ መክሊቱን ውሰዱበት አሥር መክሊትም ላለው ስጡት:: 

 

ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና ይበዛለትማል:: ከሌላው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል፡፡ የማይጠቅመውንም ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት:: በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል፡፡›› የሚል ነው፡፡ መክሊት ጥንት የክብደት መለኪያ ነበር:: አንድ መክሊት 30 ኪሎ ግራም ያህል ነው፡፡ በዚህ ምሳሌ ላይ እንደተገለጸውም መክሊት የሚለው ቃል ገንዘብን ያመለክታል፡፡

 

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ምሳሌ ውስጥ እርሱን የምናገለግል ሁላችን አንደየዓቅማችን ማድረግ የሚገባንን መንፈሳዊ የአገልግሎት ሥራንና በአገልግሎታችን ውጤታማ በመሆናችንም ከእርሱ የምናገኘውን ዘላለማዊ ክብርና ዋጋን እንዲሁም መሥራት የሚገባንን ባለማድረጋችንም ምክንያት የሚገጥመንን መለኮታዊ ቅጣትን አመልክቶናል፡፡ በዚህ ምሳሌ ውስጥ ባለ አምስት የተባለው ፍጹም ትምህርት ተምሮ ሌላውን መክሮ አስተምሮ ራሱን አስመስሎ ያወጣነው፡፡

 

በተመሳሳይም ባለሁለት የተባለው ፍጹም ትምህርት ተምሮ ሌላውን መክሮ አስተምሮ ራሱን አስመስሎ ያወጣ ሲሆን ባለአንድ የተባለው ደግሞ ተምሮ ሳያስተምር የቀረ ሰው ነው፡፡ በመሆኑም ባለአምስትና ባለሁለት መክሊት የሆኑት ወጥተው ወርደው ደክመው’ መከራ መስቀልን ሳይሰቀቁና ሳይፈሩ’ ነፍሳቸውን ለታመነው አምላክ አደራ በመስጠት የተማሩትን ፍጹም ትምህርት ለሌላው አስተምረው ሌላውን አንደራሳቸው የተማረ አድርገው ሲያወጡ ባለአንድ የተባለው ግን አላውያን እሳት ስለት አሳይተው ቢያስክዱኝ መናፍቃን ተከራክረው ምላሽ ቢያሳጡኝ ብሎ ፈርቶ ሃይማኖቱን በልቡ ከመያዝ በቀር የተማረውን ትምህርት ለሌላው ሊያስተምርና የተሰጠውን አደራንም ሊወጣ አልወደደም፡፡

በምሳሌው ውስጥ እንደተገለጠው ሌላ አምስትና ሁለት ያተረፉት በተሰጣቸው መክሊት ሌላ ማትረፋቸውን ለጌታቸው በገለጡ ጊዜ የመክሊቱ ባለቤት እጅግ አድርጎ እንዳመሰገናቸው ከላይ አንብበናል፡፡

ይህ የመክሊቱ ባለቤት የተባለው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን የተሰጣቸውን ኃላፊነት ለተወጡት ሁሉ እርሱ ፍጹም ዋጋን የሚሰጣቸው መሆኑን ያመለክታል፡፡ ይህም ሁኔታ ‹‹ መልካም አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ፡፡ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ›› በሚል ተገልጧል፡፡ ይህ ቃል በሃይማኖት ለእግዚአብሔር የታመኑ ሁሉ ወደ ፍጹም ደስታ ወደ መንግሥተ ሰማያት ለመግባት ለሚያደርጉት ጉዞ እጅግ ተስፋ የሆነ ቃል ነው፡፡

 

በዚህ ላይ እንደተገለጸው እግዚአብሔር አምላክ ለሁላችንም እርሱን የምናገለግልበትንና ለእርሱ በመታመን ዘላለማዊ ክብርን የምናገኝበትን ዕውቀትን ማስተዋልን’ ሀብትን’ ዓቅም ወይም ጉልበትን ሌሎችንም ልዩ ልዩ ስጦታዎችን ለእኛ ለሰው ልጆች እንደየዓቅማችን መጠን ሰጥቶናል፡፡

እነዚህ ሁሉ ነገሮች የሥጋችንን ምኞት እንድንወጣባቸው የተሰጡ ሳይሆኑ ነፍሳችን የምትከብርበትን መልካም ሥራን የምንሠራባቸው ናቸው፡፡
በመሆኑም እርሱ በሰጠን የአገልግሎት ጸጋ በታማኝነት በማገልገል በተሰጠን ነገር ሁሉ መንፈሳዊውን ሀብት የምናተርፍ ልንሆን ይገባናል፡፡ ምክንያቱም እኛ የተጠራ ነው ፍሬ ልናፈራና ሌላውንም ልናተርፍ መልካም ሥራን ልንሠራ እንጅ የሥጋችንን ፈቃድ በመከተል የኃጢኣት ባሮች ልንሆን አይደለም፡፡

ከላይ እንደተመለከትነው በልዑል አምላክ በእግዚአብሔር አንደበት አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ መባልን የመሰለ አስደሳችና አስደናቂ ነገር የለም፡፡ ይህ ደግሞ የሚገኘው ሃይማኖትን በሥራ በመግለጥ እንጅ ሃይማኖትን በልቦና በመያዝ ብቻ አይደለም፡፡ ከእነዚህም እንደ አቅማቸው መክሊት ተሰጥቷቸው ሌላ መክሊት ካተረፉት በጎና ታማኝ አገልጋዮች ከተባሉት የምንማረው እውነታ ይህ ነው፡፡ ስለዚህም በብዙ ለመሾም በጥቂቱ መታመን ግድ ነው፡፡
አንድ መክሊት የተሰጠውን ሰው ስንመለከተው ጌታውን ጨካኝ አድርጎ ከመቁጠር ውጪ በተሰጠው መክሊት ወጥቶ ወርዶ ሊያተርፍ አልወደደም፡፡ መክሊቱንም ባስረከበ ጊዜ በጌታው ላይ የተናገራቸው ቃላት የእርሱን አለመታዘዝና አመጸኝነት ይገልጡ ነበር፡፡

 

በመሆኑም ይህ ሰው በጥቂቱ መታመን ያቀተውና በአስተሳሰቡ ደካማነት እጅግ የተጎሳቆለ ሰው ነው፡፡ በዚህ ምሳሌ መሠረት ይህ ባለአንድ የተባለው ሰው ዓላውያን እሳት ስለት አሳይተው ቢያስክዱኝ መናፍቃን ተከራክረው መልስ ቢያሳጡኝ በማለት ሃይማኖቱን በልቡ ሸሽጎና ቀብሮ ከመያዙ ባሻገር በጌታ ፊት በድፍረት ቆሞ አንተ ሕግ ሳትሠራ በአዕምሮ ጠባይዕ አውቃችሁ’ መምህርም ሳትሰጥ በሥነ ፍጥረት ተመራምራችሁ በሠራችሁ ብለህ የምትፈርድ ጽኑ ጨካኝ መሆንክን አውቃለሁና ዓላውያን እሳት ስለት አሳይተው ቢያስክዱኝ መናፍቃን ተከራክረው መልስ ቢያሳጡኝ ብየ ፈርቼ ሃይማኖቴን በልቡናየ ይዠዋለው በአዕምሮየ ጠብቄዋለሁ የሚል ሃይማኖቱን ግን በሥራ የማይገልጥ ሰነፍ ሰውን ያመለክታል፡፡

ለዚህ ዓይነት ሰው የጌታ መልስ ደግሞ በምሳሌው መሠረት የሚከተለው ነው፡፡ እኔ ሕግ ሳልሠራ በአዕምሮ ጠባይዕ አውቃችሁ መምህር ሳልሰጥ በሥነ ፍጥረት ተመራምራችሁ አውቃችሁ በሠራችሁት ብየ የምፈርድ ጽኑ ጨካኝ መሆኔን ታውቃለህን? እንዲህስ ካወቅህ ሹመትክን ልትመልስልኝ ይገባኝ ነበር፡፡ ወጥቶ ወርዶ ለሚያስተምር በሰጠሁት ነበር፡፡ አሁንም የእርሱን መምህርነት ሹመት ነሥታችሁ (ወስዳችሁ) ለዚያ ደርቡለት! እርሱን ግን አውጡት የሚል ነው፡፡ ዛሬም እያንዳንዳችን በዓቅማችን መጠን መክሊት ተሰጥቶናል፡፡ በመሆኑም መክሊቱን እንደቀበረው እንደዚያ ሰው የተሰጠንን ቀብረን ለወቀሳና ለፍርድ እንዳንሰጥ በአገልግሎታችን ልንተጋ ይገባናል፡፡

 

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህንኑ ሲገልጥ ‹‹አገልግሎት ቢሆን በአገልግሎታችን እንትጋ የሚያስተምርም በማስተማሩ ይትጋ የሚሰጥም በልግሥና ይስጥ›› (ሮሜ12፥7) በማለት ተናግሯል፡፡ ለመሆኑ ዛሬ ‹‹አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ…›› ተብሎ በእግዚአብሔር ሊመሰገን የሚችል ማን ይሆን? በእውነት በዘመናችን እንዲህ ተብሎ የሚመሰገን በጎና ታማኝ ካህን’ ታማኝ መምህርና ሰባኪ’ ታማኝ ዘማሪ የመሳሰለውን ማግኘት ይቻል ይሆንን? ትልቅ መሠረታዊ ሊሆን የሚገባው ጥያቄ ቢኖር ይህ ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርት ስለ ታማኝነት የሁላችንንም ሕይወት የሚዳስስና ሁላችንንም የሚመለከት ነውና፡፡

 

በእርግጥም ዛሬም ቢሆን እንደ አባቶቻችን ማለትም እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት በእምነት’ በትዕግስት በፍቅር’ በትህትናና በትጋት በማገልገል የተሰጣቸውን መክሊት የሚያበዙ አገልጋዮች አሉ፡፡ የእነዚህ ክብራቸው በምድርም በሰማይም እጅግ የበዛና ራሳቸውን አስመስለው በትምህርት የወለዷቸው ልጆቻቸውም ለቤተክርስቲያን ውድ ልጆች ናቸው፡፡
ለምሳሌ ቅዱስ ጴጥሮስ ቀሌምንጦስን’ ቅዱስ ጳውሎስም ጢሞቴዎስን አፍርተዋል፡፡

 

ሌሎችም አበው ቅዱሳን በወንጌል ቃል መንፈሳውያንና ትጉሃን የሆኑ ምእመናንን በሚገባ አፍርተዋል፡፡ ያላመኑትንም አሳምነው ወደ ቅድስት ቤተክርስቲያን በመመለስ ለዘላለማዊ ክብር የበቁ እንዲሆኑ አስችለዋቸዋል፡፡ በመሆኑም በክርስቶስ በደሙ የተከፈለውን ወደር የሌለውን ዋጋ ዓለም አምኖና አውቆ በክርስትና ሃይማኖት እንዲድንበትና እዲጠቀምበት በማድረግ እንዲሁም በታማኝነት ሥራቸው ጥንትም ዛሬም ላለችዋና ወደፊትም ለምትኖርዋ ቅድስት ቤተክርስቲያን ድምቀትም ውበትም የሆኑት ቅዱሳን አበው ሊገኙ የቻሉት ከእግዚአብሔር ይልቅ ሰውን ደስ ለማሰኘት በመድከማቸው ሳይሆን የተጠሩበትን ዓላማና የጠራቸውን እርሱን በሚገባ አውቀውና ከልብ ተረድተው ለዘላለማዊ ህይወት ተግተው በመሥራታቸው ነው፡፡ (ገላ1፥10)

ዛሬም በዚህ ዘመን ያለንና በክርስቶስ ክርስቲያን ተብለን የተጠራን ሁላችንም የተሰጠንን መክሊት (ጸጋ) አውቀን ለእግዚአብሔር ለአምላካችን በመታመን ወጥተን ወርደን ሌላ ልናተርፍ ይገባናል፡፡ በተለይ ደግሞ በክህነት አገልግሎት ውስጥ ያለ ሰው ከምንም በላይ በከፍተኛ መንፈሳዊ ኃላፊነት ላይ ያለ እንደመሆኑ መጠን በሃይማኖትም በሥነምግባርም ለሌላው ዓርዓያ በመሆን እንደ እርሱ ሃይማኖትን ከምግባር ጋር አስተባብረው የያዙ ምእመናንን ማፍራት አለበት፡፡ ይህ ሲሆን ብቻ ነው አንተ በጎ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃልና ወደ ጌታህ ደስታ ግባ ልንባል የምንችለው፡፡ 

 

አሁን ባለንበት በዘመናችን ብዙ ፈታኝ የሆኑ ችግሮች አሉ፡፡ የችግሮቹም መሠረታዊ ምንጭ በተጠሩበት ጸንቶ መቆም ፈጽሞ አለመቻልና ለሥጋዊ ጥቅም ብቻ በማድላት ኃላፊነትን መዘንጋት ናቸው፡፡ በሥጋዊ አምሮት ፍላጎትና ምርጫ ውስጥ ደግሞ መንፈሳዊ ጸጋንና በረከትን ለማግኘት የሚያስችለንን የታማኝነት ሥራን መሥራት አይቻልምና ከምናድነው ሰው ይልቅ መክሊታችንን በመቅበር መሰናክል የምንሆንበት ሰው ሊበዛ እንደሚችል አያጠራጥርም፡፡ በመሆኑም ከእርሱ ዘንድ እንደዓቅማችን የተሰጠንን መንፈሳዊ ዕውቀት ለሌላው በማድረስ መክሊታችንን ልናበዛ የምንችለውና አገልግሎታችን ወይም ክርስትናችን ውጤታማ የሚሆነው ምርጫችንን አውቀን እንደ ቃሉ ሆነንና ጸንተን ስንገኝ ብቻ ነው፡፡

 

ይህ ባለመሆኑ ነው ዛሬ ብዙዎቻችን በህይወታችን ሌላውን ማትረፍ አቅቶን በእግዚአብሔርና በሰውም ዘንድ በሚያስወቅሰን የስንፍና መንገድ ላይ ቆመን የምንገኘው፡፡ ስለዚህም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ ጌታችሁ በምን ሰዓት እንዲመጣ አታውቁምና እንግዲህ ንቁ›› (ማቴ24፥42) ብሎናል፡፡

እንግዲህ ቃሉን የሰማንና የምናውቅ ሁላችን በሞቱ ላዳነን፣ በልጅነት ጸጋም ላከበረን፣ በትንሣኤውም ላረጋጋን፣ በመስቀሉ ጥልን ገድሎ ከራሱ ጋር ላስታረቀን፣ በደሙም መፍሰስ ህይወትን፣ ሰላምን፣ ፍቅርን፣ በረከትንና ዘላለማዊ ደስታን ለሰጠን አምላክ ለጌታችንና ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ በመታመን እርሱ ያዘዘንን ሁሉ ልናደርግ ይገባናል፡፡ ምን ጊዜም ትጉህ ሠራተኛ ደግሞ የሚሠራው መልካም ሥራ ሁሉ ለቤተ ክርስቲያንም ለሀገርም የሚሰጠው ጥቅም እጅግ ከፍተኛ ነው፡፡ በመሆኑም በጎና ታማኝ አገልጋዮች ሆነን እንድንገኝ ጠንክረን ልንሠራ ይገባናል፡፡

1ዐ.2 የአንዳንድ አገናዛቢ አጸፋዎች ዝርዝር

 ዳር 12 ቀን 2007 ዓ.ም.

በመ/ር ደሴ ቀለብ
በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የፊሎሎጂ መምህር

ካልእ = ሌላ፣ ካልእከ / ሌላህ/፤ ካልእኪ የሌላሽን
ቀደምት =/የቀድሞ ሰዎች/፤ ቀደምትክሙ / የቀድሞ ሰዎች የሆኗችሁ ለእናንተ/
ክልኤ = ሁለት፣ ክልኤሆሙ / ሁለታቸው/፤ ክልኤነ / ሁለታችን /፤ ክልኤክሙ / ሁለታችሁ/

በበይናት = በመካከል እርስ በርስ፤ በበይናቲነ/ እርስ በርሳችን /፤ በበይናቲሆሙ / እርስ በርሳቸው/፤ በበይናቲክሙ / እርስ በርሳችሁ/

ኩሎ = ሁሉ፣ ኩሎሙ / ሁላችው/፤ ኩልክሙ / ሁላችሁ/፤ ኩልነ / ሁላችን/
ባሕቲት = ብቻ፣ ባሕቲቶሙ / ብቻቸውን/፤ ባሕቲትየ / ብቻየን/፤ ባሐቲታ / ብቻዋን/
አመ = ጊዜ፣ አሜሃ / በዚህ ጊዜ፣ በዚያ፣ ጊዜ፣ ወዲያው/
ሶበ = ጊዜ፣ ሶቤሃ / በዚህ ጊዜ፣ በዚያ ጊዜ፣ ወዲያው/
ጊዜ =ጊዜ፣ ጊዜሃ / በዚህ ጊዜ በዚያ ጊዜ ወዲያው/

 

ምሳሌ

ዘትፈቅድ ለርእስከ ግበር ለካልእከ = ለራስህ የምትፈልገውን ለሌላው አድርግ፡፡
ሰማእክሙ ዘተብህለ ለቀደምትክሙ / ተብህለ = ተባለ/
ቀደምትክሙ ሰገዱ ለእግዚአብሔር አምላኮሙ
ክልኤሆሙ ሖሩ ወብልዑ ኅብስተክሙ
ተፋቀሩ በበይናቲክሙ
ተማከርነ በበይናቲነ
ተሰአሉ በበይናቲሆሙ / ተሰአለ፣ ተጠያየቀ/
ኩልነ አግብርተ እግዚአብሔር ንሕነ
መጽኡ ኩሎሙ ወሰአሉ በእንተ ንጉሦሙ
ሑሩ ኩልክሙ ኀበ ቤትክሙ ለክሙ
ኩሎሙ ነቢያት አስከ ዮሐንስ ተነበዩ
መጻእኩ እምብሔር ርኁቅ ባሕቲትየ
ዝንቱ ብእሲ ነበረ ውስተ ቤቱ ለባሕቲቱ
ዘበልዐ ባሕቲቶ ይመውት ባሕቲቶ

 

የንዑስ አንቀጽ ዝርዝር እንደ አገናዛቢ ሲያገለግል


ቀቲል/ ቀቲሎት/ –መግደል፤ ቀቲልየ = መግደሌ፤ ቀቲልክሙ = መግደላችሁ
ቀተለ = ገደለ፤ ቀቲሎትየ = መግደሌ፤ ቀቲሎትክሙ = መግደላችሁ
ቀደሰ = አመሰገነ፤ ቀድሶየ = ምስጋናየ፤ ቀደሶክሙ = ማመስገናችሁ
ቀድሶትየ = ምስጋናየ፤ ቀድሶትክሙ = ማመስገናችሁ
ገቢር/ ገቢሮት/ =መሥራት፤ ገቢርየ = ሥራየ፤ ገቢርክሙ = ሥራችሁ
ገብረ = ሥራ፤ ገቢሮትየ = ሥራየ፤ ገቢሮትክሙ = ሥራችሁ

1ዐ.3 ተጠቃሽ ተውላጠ ሥም


ነጠላ                                     ብዙ
ሊተ = የእኔ ፣ ለእኔ ፣ ልኝ          ለነ = ለእኛ
ለከ = ላንተ፣ ልህ                  ለክሙ = ለእናንተ ላቹሁ
ለኪ = ላንቺ፣ ልሽ                 ለክን = ለእናንተ / ለሴት/ ላቹሁ
ሎቱ/ሎ/ = ል፣እርሱ               ሎቶ/ሎቶሙ/ሎሙ = ለእነርሱ / ለወንድ/
ብየ = በኔ፣ ብኝ፣ አለኝ             ብነ = በእኛ ብን አለን
ብከ = በአንተ፣ አለህ               ብክሙ = በእናንተ፣ ባችሁ ፣አላችሁ
ብኪ = በአንቺ አለሽ               ብክን= በእናንተ፣ ባችሁ አላቹሁ/ለሴቶች/
ቦቱ/ ቦ/ = በት አለው ፣ በእርሱ    ቦኑ/ ቦቶሙ/ = አላቸው፣ አላችሁ ባቸው/ለወንዶች/
ባቲ/ ባ/ = ባት                   ቦን / ቦቶን/ = አላቸው፣ አላችሁ፣ ባቸው /ለሴቶች/
ላቲ= ለእርሷ                      ሎሙ = ለእነርሱ / ለወንዶች/ ፣ባቸው

 

ምሳሌ

ፍታህ ሊተ እግዚኦ ወተበቀል በቀልየ
ልበ ንፁሐ ፍጥር ሊተ
ሰላም ለከ ኦ ሚካኤል መልአከ አድኅኖ
ሰላም ለኪ እንዘ ንሰግድ ንብለኪ
ሎቱ ስብሐት
አምጽኡ ላቲ አምሐ ለድንግል
ብየ እግዚአብሔር ዘየዐቀበኒ
መጽአ ብየ ሞት አመ ነበርኩ በኃጢአት
ኦ ጎልያድ አይቴኑ ትበውእ እስመ በጽሐ ብከ ዳዊት
ብኪ ግርማ ራእይ ዘየዐቢ
ወተቀትለ ቦቱ ወልዱ ለአዳም
ወተሰቅለ ባቲ ወልዳ ለማርያም
ተአገሠ ለነ ኩሎ ኃጢአተነ
ሰአሊ ለነ ቅድስት
ሰላም ለክሙ

gundagundi 02

ማኅበረ ቅዱሳን በትግራይ ሦስት ገዳማት የተገበራቸውን ፕሮጀክቶች አስመረቀ

•ለፕሮጅክቶቹ ማስፈጸሚያ ከ3 ሚሊዮን 180 ሺሕ ብር በላይ ወጪ ሆኗል፡፡ 

ኅዳር 11 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

gundagundi 02ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት አማካይነት በምሥራቃዊ ትግራይ ሀገረ ስብከት በደብረ ገሪዛን ጉንዳጉንዲ ቅድስት ማርያም፤ በሰሜን ምዕራብ ትግራይ ሽሬ እንዳሥላሴ ሀገረ ስብከት በአስገደ ጽምባላ ወረዳ በአቡነ ቶማስ ደብረ ማርያም ዘሃይዳ፤ በምሥራቃዊ ትግራይ ሀገረ ስብከት በማቅናት አጽቢ ወምበርታ ወረዳ በደብረ ቅዱሳን ዲቦ ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳማት ያከናወናቸውን ፕሮጀክቶች አስመረቀ፡፡

 

በተለያዩ ጊዜያት ተጀምረው የነበሩት እነዚህ ፕሮጅክቶች ከኅዳር 3/2007 ዓ.ም. – ኅዳር 8/2007 ዓ.ም. ደማቅ በሆነ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ፕሮጀክቶችን አስመርቆ ለየገዳማቱ አስረክቧል፡፡ በሰሜን ምዕራብ ትግራይ ሽሬ እንዳሥላሴ ሀገረ ስብከት በአስገደ ፅብላ ወረዳ ኅዳር 3 ቀን 2007 ዓ.ም የተመረቀው የአቡነ ቶማስ ደብረ ማርያም ዘሃይዳ አንድነት ገዳም በ630 ሺሕ ብር የተሠራ የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክት ሲሆን፤ 150 ሺሕ ሊትር መያዝ ይችላል፡፡ ይህ የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክት በገዳሙ ውስጥ ተገንብቶ በመጠናቀቁ ማኅበረ መነኮሳቱ የመጠጥ ውኃ ፍለጋ በቀን ከ4-5 ሰዓት በመጓዝ የሚባክንባቸውን የአገልግሎትና የጸሎት ጊዜያቸውን እንደሚያስቀርላቸው የገዳሙ አባቶች ተናግረዋል፡፡

abune tomas zehayda 02 1ገዳሙ ያለበትን ችግር በማጥናት የውኃ ፕሮጀክቱን ተግባራዊ ለማድረግ ከፍተኛ ጥረት የተደረገ ሲሆን፤ መንገዱ በጣም አስቸጋሪና ከ3-4 ሰዓት በእግር የሚያስኬድ በመሆኑ አባቶች በሸክም፤ እንዲሁም ግመሎችን በመጠቀም የግንባታ ቁሳቁስ በማመላለስ ፕሮጀክቱን ለማጠናቀቅ ተችሏል፡፡

ገዳሙ ጥንታዊና ገዳማዊ ቀኖና እና ሥርዓት ተጠብቆ የሚገኝበት ሲሆን፤ በርካታ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትን በማፍራትም ይታወቃል፡፡

gundagundi 03በምሥራቃዊ ትግራይ ሀገረ ስብከት ከተጠናቀቁት ፕሮጀክቶች መካከል አንዱ ደግሞ ለደብረ ገሪዛን ጉንዳጉንዲ ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳም የተገነባው ሁለገብ ሕንፃ ነው፡፡ ሁለገብ ሕንፃው በአዲግራት ከተማ የተገነባ ሲሆን፤ ለተለያየ አገልግሎት በማከራየት ገቢ ማስገኘት የሚችል ነው፡፡ ሕንፃው በብር 2,326,717.87 /ሁለት ሚሊዮን ሦስት መቶ ሃያ ስድስት ሺሕ ሰባት መቶ ዐሥራ ሰባት ብር ከ87 ሣንቲም/ ተገንብቶ የርክክብ ሥነ ሥርዓቱ ተከናውኗል፡፡

ሕንፃው በ416.49 ካሬ ሜትር ላይ ያረፈ ሲሆን፤ ማኅበሩ የሠራው የምድሩን ወለል ብቻ ነው፡፡ መሠረቱ ባለ ሁለት ወለል ሕንፃን መሸከም እንዲችል ተደርጎ የተሠራ በመሆኑ ቀሪውን የግንባታ ሥራ ገዳሙ ባቋቋመው ኮሚቴ አማካይነት ይገነባል፡፡

ጉንዳጉንዲ ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳም ቀድሞ በርካታ መነኮሳት የነበሩባት ቢሆንም በደርግ መንግሥት የነበራት ሰፊ ይዞታ በመነጠቋ የመነኮሳቱ ቁጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ በችግር ምክንያት እየተመናመነ ሄዶ ሁለት መነኮሳት ብቻ ቀርተው ነበር፡፡ እነሱም በገዳሟ ውስጥ የሚገኙትን ንዋያተ ቅድሳትና በሌሎች ገዳማት የማይገኙ ቅዱሳት የብራና መጻሕፍትን ለማን ጥለን እንሔዳለን በማለት ችግሩን ተቋቁመው ዛሬ ድረስ ለመዝለቅ ችለዋል፡፡

ወደ ገዳሟ ለመድረስ መንገዱ አስቸጋሪና መኪና የማይገባ በመሆኑ የአንድ ቀን ሙሉ የእግር መንገድ መጓዝ ግድ ይላል፡፡ ለመመለስም እንዲሁ የአንድ ቀን የእግር ጉዞ ማድረግ ይጠበቃል፡፡
ገዳሟ ምንም አይነት የገቢ ምንጭ የሌላት ሲሆን፤ የሁለገብ ሕንፃው መገንባት ችግሩን እንደሚቀርፍ ይጠበቃል፡፡ በአሁኑ ወቅትም የመነኮሳቱ ቁጥር ከሁለት ወደ ሰባት ከፍ ለማለት ችሏል፡፡

dibo 02በተጨማሪም በምሥራቃዊ ትግራይ ሀገረ ስብከት በማቅናት አጽቢ ወምበርታ ወረዳ በደብረ ቅዱሳን ዲቦ ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳም ማኅበሩ በብር 225,343.65 /ሁለት መቶ ሃያ አምስት ሺህ ሦስት መቶ አርባ ሦስት ብር ከ65 ሣንቲም/ ተግባራዊ ያደረገውን የሽመና ውጤቶችን መሥሪያ አዳራሽ ሠርቶ በማጠናቀቅ፤ የሽመና ቁሳቁስ በማሟላት፤ እንዲሁም የልብስ ሥፌት መኪናዎችን ገዝቶ በማቅረብ ርክክብ ተደርጓል፡፡

የሽመና ፕሮጀክቱ ታሳቢ ያደረገው በገዳሟ ውስጥ ለሚገኙት መነኮሳይያት ሲሆን፤ መነኮሳይያቱ ቁጥራቸው ከፍ ያለ በመሆኑ የሽመና ውጤቶችን ማምረት ያስችላቸዋል፡፡

ደብረ ቅዱሳን ዲቦ ቅድስት ማርያም አንድነት ገዳም ጥንታዊ ከሚባሉ ገዳማት መካከል የምትመደብ ስትሆን በውስጧም ጥንታዊ ሥዕላትን ጠብቃ ለትውልድ በማቆየት ትታወቃለች፡፡ ለትኅርምት እና ለጽሞና የምትመረጥም ገዳም ናት፡፡

ማኅበሩ በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍሉ አማካይነት ለበርካታ ገዳማትና አድባራት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽና በመተግበር ገዳማት የልማት ሥራዎችን በመሥራት ራሳቸውን እንዲችሉ እያደረገ ሲሆን፤ ሌሎች በጅምር ላይ ያሉ ፕሮጀክቶች በተያዘላቸው ጊዜ ለማጠናቀቅ እየሠራ ይገኛል፡፡

 

 

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቀባበል ተደረገላቸው

 መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ 

ህዳር 09 ቀን 2007 ዓ.ም.

በ2007 ዓ.ም የጥቅምት ሲኖዶስ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው የተመደቡት ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ ሥራ ለመጀመር ከሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች፣ ከአጥቢያ ገዳማትና አድባራት ሓላፊዎች፣ ጸሐፊዎችና ምእመናን ጋር ትውውቅ አድርገዋል፡፡

 

ብጹዕነታቸው የሥራ መጀመሪያቸው ለሆነው የትውውቅ መርሐ ግብር ወደ ሀገረ ስብከታቸው ሲሔዱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል፡፡

 

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማቲያስ ፓትርያርክ ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት  ለጉባኤው ታዳሚዎች ባስተላለፉት ቃለ ምዕዳን ‹‹እኔ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ›› በሚለው ቃለ ወንጌል የቅድስና ሥራ መሥራት እንደሚገባ አጽንዖት ሰጥተዋል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ቀውስጦስ የፍቼ ሰላሌ ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስም ‹‹ለሁለት ጌታ፤ ለገንዘብና ለእግዚአብሔር መገዛት አንችልም፡፡ ለገንዘብ ስንገዛ የኖርንበትን ዘመን ትተን እስቲ ለእግዚአብሔር እንገዛ›› በማለት አባታዊ መልእክታቸውን ለጉባኤው ታዳሚ አስተላልፈዋል፡፡

 

አዲሱ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስም  የሀገረ ስብከቱን ሠራተኞችንና ሌሎች የአጥቢያ ባለጉዳዮችን በጽ/ቤታቸው ብቻ እንደሚያስተናግዱ ገልጸዋል፡፡

 

                    ለብፁዕነታቸው መልካም የሥራ ዘመን እንመኛለን፡፡

 

 

jinka tim02 2

ከ2004- 2007 ዓ.ም. በደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት 16,630 አዳዲስ አማንያን ተጠመቁ

 ኅዳር 8 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

jinka tim02 2የደቡብ ኦሞ ሀገረ ስብከት ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመተባበር ከ2004- 2007 ዓ.ም. 16,630 አዳዲስ አማንያንን በማስተማር መጠመቃቸውን የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ አስታወቁ፡፡

ጥቅምት 30 ቀን 2007 ዓ.ም. የጂንካ ደብረ ቀራንዮ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ቅዳሴ ቤቱ ሲመረቅም በሀገረ ስብከቱ እና በማኅበረ ቅዱሳን አማካይነት የቀረቡትን 1350 አዳዲስ አማንያን በቅዱስነታቸው እና በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ተጠምቀው የሥላሴ ልጅነትን አግኝተዋል፡፡

ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት ቃለ ምእዳን “ይህ ቀን የቤተ ክርስቲያን ሰላምና አንድነት የተፈጸመበት ቀን ነው፡፡ የመድኀኔዓለምን ቤተ ክርስቲያን ገንዘባችሁን፤ እውቀታችሁንና ጉልበታችሁን አስተባብራችሁ የሠራችሁበትና 1350 አዲስ ክርስቲያኖች የተጨመሩበት ቀን ስለሆነ ለቤተ ክርስቲናችን ታላቅ የደስታ ቀን ነው” ብለዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ትጉኀን ወንድወሰን ገ/ሥላሴ የዕለቱን መርሐ ግብር ሲያስተዋውቁ ከ2004-2007 ዓ.ም. ድረስ ሀገረ ስብከቱ ከማኅበረ ቅዱሳን ጂንካ ማእከል ጋር በመተባበር 16,630 አዳዲስ አማንያንን በማስተማር እንዲጠመቁ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያኑም ከታቀደለት ጊዜ በፊት እንዲጠናቀቅ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላደረጉ አካላት ሁሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

jinka tim02 1የጂንካ ደብረ ቀራንዮ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ሕንፃ አሠሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ጀማል ዑመር /ዐምደ ሚካኤል/ ባቀረቡት ሪፖርት የቤተ ክርስቲያኑ ሕንፃ ሥራ በፍጥነት እንዲጠናቀቅ እገዛ ላደረጉ ሁሉ ምስጋናቸውን ያቀረቡ ሲሆን፤ የቤተ ክርስቲያኑን ዲዛይን በተመለከተም ሲገልጹ “የወንጌል አርበኞች የሆኑት የማኅበረ ቅዱሳን ጂንካ ማእከል አባላት የቤተ ክርስቲያኑን ዲዛይን በነጻ በመሥራት እገዛ አድርገዋል” ብለዋል፡፡

 

 

 

 

 

 

 

jebera 01

የጀበራ ማርያም አንድነት ገዳምን ዳግም ለማቋቋም ጥረት በመደረግ ላይ መሆኑ ተገለጸ

ጥቅምት 29 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

jebera 01በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በደምቢያ ወረዳ በጣና ሐይቅ ውስጥ በ1335 ዓ.ም. ተገድማ የነበረችው የጀበራ ማርያም አንድነት ገዳም ከፈረሰች ከበርካታ ዘመናት በኋላ ዳግም ለማቋቋም ከፍተኛ ጥረት እየተደረገ መሆኑን ገዳሙን መልሶ ለማቋቋም በማስተባበር ላይ የሚገኙት አባ ዘወንጌል ገለጹ፡፡

አባ ዘወንጌል ከ23 ዓመታት በፊት በዚሁ ገዳም ውስጥ በጸሎት ከሚተጉ አባቶች መካከል አንዱ የነበሩ ሲሆን፤ ወደ ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አንድነት ገዳም በመሄድ በአገልግሎት ሲተጉ ቆይተዋል፡፡ በ2005 ዓ.ም. “የአባቶቼ ርስት እንዴት ቆይታ ይሆን?” በማለት አባቶችን ለመጎብኘት ወደ ቦታው ሲያቀኑ ቤተ ክርስቲያኗ ፈርሳ፤ አባቶችና እናቶች በርካቶቹ አርፈው፤ ገሚሶቹ ተሰደው ሁለት አባቶች ብቻ በእርግና ምክንያት የሚጦራቸው አጥተው በችግር ውስጥ እንዳሉ ይደርሳሉ፡፡

በሁኔታው የተደናገጡት አባ ዘወንጌል ከጣና ሐይቅ ማዶ ያሉትን ነዋሪዎች በመቀስቀስ፤ በጎ አድራጊ ምእመናንን በማስተባበር ገዳሟን እንደገና ጥንት ወደነበችበት ለመመለስ ከፍተኛ ጥረት ማድረጋቸውን ቀጠሉ፡፡ ኮሚቴ በማዋቀር ከበጎ አድራጊ ምእመናን በተገኘ ድጋፍም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኗን በማስገንባት ላይ ሲሆኑ፤ በገዳሟ ውስጥም በርካታ ሥራዎች እየተሠሩ ይገኛሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት ከ15 በላይ መናንያን ተሰባስበውባት በጸሎትና በአገልግሎት በመፋጠን ገዳሟን የማስፋፋት ሥራ እየተሠራ ነው፡፡

jebera 02በስድስት ወራት ውስጥ የተጀመረው ግንባታም በመፋጠን ላይ ሲሆን፤ ሠርቶ ለማጠናቀቅም በርካታ ሥራዎች ይቀራሉ፡፡ የጣሪያ ቆርቆሮ፤ የበር፤ የመስኮት፤ የቤተ መቅደስ፤ የማጠናቀቂያ ሥራዎችና ሌሎችም ስለሚቀሩት በባለሙያዎች ተጠንቶ 1.2 ሚሊዮን ብር ድጋፍ እንደሚያስፈልገውና ይህንን ለማሟላት የሕንፃ አሠሪ ኮሚቴው በችግር ውስጥ እንደሚገኝ አባ ዘወንጌል ገልጸዋል፡፡ በጎ አድራጊ ምእመናንም ገዳሟ ያለችበትን ሁኔታ በመረዳት ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በ14ኛ መቶ ክፍለ ዘመን በዐፄ ዓምደ ጽዮን ዘመነ መንግሥት አባ በረከተ አልፋ በተባሉ አባት ተገድማ እንደ ነበረች የታሪክ ድርሳናት እንደሚያስረዱ የገለጹት አባ ዘወንጌል፤ ገዳሟ በርካታ መናንያንን ስታስተናግድ የኖረች በመሆኗ በገዳማዊ ሕይወታቸውና በትሩፋታቸው ከልዑል እግዚአብሔር በረከትን ያገኙ አባቶችና እናቶች የኖሩባትና ጸሎት ሲያደርሱ የእጆቻቸው ጣቶች እንደ ፋና ያበሩ ስለነበር የአካባበቢው ነዋሪዎች “እጀበራዎች” እያሉ ይጠሯቸው ስለነበር ገዳሟ “ጀበራ” የሚለውን ስያሜ ማግኘቷን ይናገራሉ፡፡

ገዳሟ በድርቡሽ ወረራ ከፍተኛ ጉዳት ከደረሰባቸው የጣና ገዳማት መካከል አንዷ ስትሆን ገዳማውያኑም በመሰደዳቸው እስከ 1956 ዓ.ም. ሙሉ ለሙሉ ፈርሳ ቆይታለች፡፡ በ1956 ዓ.ም መምህር ካሳ ፈንታ በተባሉ አባት ዳግም ተመሥርታ ብትቆይም ከተወሰኑ ዓመታት በኋላ በማረፋቸው ገዳሟን የሚንከባከብ በመጥፋቱ ገዳማውያኑም ወደ ተለያዩ ገዳማት ተበተኑ፡፡ ተሠርታ የነበረቸው መቃኞም በምስጥ ተበልታ ፈረሰች::