“የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ. . . ይጠቅማል” ክፍል ሁለት

 ግንቦት 23 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

አዋልድ መጻሕፍት ከመጽሐፍ ቅዱስ ጋር ያላቸው ተዛምዶ፡

ቀደም ተብሎ እንደተለጠው አዋልድ መጻሕፍት ልጅነታቸው ለአሥራው መጻሕፍት (ለመጻሕፍት አምላካውያት) ነው፡፡ ልጅ ከአባቱ አብራክ፣ ከእናቱ ማኅጸን ተከፍሎ ወላጆቹንመስሎ እንዲወጣ እነዚህም በምሥጢርም በእምነትም በሥርአትም የአሥራውን መጻሕፍት ሥርና መሠረት ይዘው ተገኝተዋል፡፡ በምሥጢርም ኾነ በሥርዓት ከአሥራው መጻሕፍት ጋር የሚቃረኑት መጻሕፍት ከአዋልድ አይቆጠሩም፡፡ ምክንያቱም በሐዋርያው ቃል “ነገር ግን እኛ ብንሆን ወይም ከሰማይ መልአክ፥ ከሰበክንላችሁ ወንጌል የሚለይ ወንጌልን ቢሰብክላችሁ፥ የተረገመ ይሁን” ተብሏልና (ገላ.፩፥፰)፡፡

አዋልድ መጻሕፍት ከአሥራው መጻሕፍት ጋር ያላቸውን ተዛምዶ በሚከተሉት ነጥቦች መረዳት ይቻላል፡፡

ሀ. በዓይነታቸው፡- አሥራው መጻሕፍት ተብለው የሚታወቁት ሰማንያ አንዱ መጻሕፍት የሕግ፣ የታሪክ፣ የጥበብ፣ የትንቢት ተብለው ይመደባሉ፡፡

እንደዚሁም ሁሉ አዋልድ መጻሕፍት በዚሁ አንጻር የተዘጋጁ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ያህል ይህንን የማሳያ ሰንጠረዥ እንመልከት፡-

የመጻሕፍቱ

ዓይነት

የመጻሕፍቱ ይዘት

የሕግ

የታሪክ

የጥበብ

የትንቢት

አሥራው

ብሔረ ኦሪት

መጽሐፈ ሳሙኤል

መዝሙረ ዳዊት

ትንቢተ ኢሳይያስ

አዋልድ

ፍትሐ ነገሥት

ተአምረ ማርያም

ውዳሴ ማርያም

ፍካሬ ኢየሱስ

 

 

 

  

 

 

 

ለ. በባለቤታቸው፡-የቅዱሳት መጻሕፍት ባለቤታቸው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ምክንያቱም ቅዱሳት መጻሕፍት የእግዚአብሔር ገንዘቦች፣ በእርሱም ፈቃድና ምሪት የተፃፉ ሲሆኑ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ እግዚአብሔር በደሙ የዋጃት በምድር የእግዚአብሔር እንደራሴ የሆነች፣ የጸጋው ግምጅ ቤት ናት (የሐዋ.፳፥፳፰)፡፡ ስለሆነም ከእግዚአብሔር የተላኩ ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ ገልጦላቸው ወንጌልንና መልእክታትን የጻፉት ለቤተ ክርስቲያን ነው፡፡

የአዋልድ መጻሕፍት ጸሐፊዎች የቤተ ክርስቲያን ልጆች ሲሆኑ እነርሱም መንፈሰ እግዚአብሔር እንደገለጠላቸው መጠን መጻፍቱን የጻፉት ለቤተክርስቲያን ልጆች ለምእመናን ነው፡፡ በመሆኑም ባለቤታቸው ቤተ ክርስቲያን በመሆኗ ለትርጉማቸው፣ ለታሪካቸውና ለምሥጢራቸው መጠየቅ ያለባት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡

ሐ. በቅድስናቸው፡- አሥራው መጻሕፍትንም ሆነ አዋልድ መጻሕፍትን ያጻፈው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ የአሥራው መጻሕፍትን ጸሐፍት እንደመረጠ እንዳተጋ ምሥጢር እንደገለጠላቸው፣ የአዋልድ መጻሕፍትን ጸሐፍት የመረጠ፣ ያተጋ፤ ምሥጢር የገለጠላቸው መንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ከአንዱ ምንጭ ከመንፈስ ቅዱስ በመገኘታቸውም የአሥራውም ሆኑ የአዋልድ መጻሕፍት ዓላማቸው ነገረ ሃይማኖትን ማስረዳት ደግሞም ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር መጥቀም ነው፡፡(፪ኛ.ጢሞ.፫፥፲፮)

በልዩ ልዩ ዘመናትና ሰዎች በተራራቀ ሀገር ተጽፈው ለየብቻቸው የነበሩትን አሥራው መጻሕፍት ከመሠረተ ሃይማኖት አንጻር መርምራ አረጋግጣ በአሥራው መጻሕፍትነት የተቀበለችው ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ አዋልድ መጻሕፍትንም የምትቀበለው በተመሳሳይ መልኩ ከትምህርቷ አንፃር መርምራ አረጋግጣ ነው፡፡

መ. የእግዚአብሔርን ሥራ በመግለጥ፡- የቅዱሳት መጻሕፍት ተቀዳሚ ዓላማ የእግዚአብሔርን ሥራ መግለጥ ነው፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍት እግዚአብሔር በቀጥታ ራሱ ወይም በወዳጆቹ አድሮ ለሕዝቡ ያደረገውን ተአምር፣ መግቦት፣ ቸርነት ያብራራሉ፡፡ይህ እውነታ በአሥራው መጻሕፍት በስፋትና በይፋ የተገለጠ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ዓላማቸው የእግዚአብሔርን ሥራ መግለጥ ከመሆኑ የተነሣ የእግዚአብሔር ሥራ ተአምር የተፈጸመላቸውንና የተፈጸመባቸውን ሰዎች፣ ቦታዎች እምብዛም ትኩረት አይሰጧቸውም፡፡ ተአምሩን ብቻ ገልጠው የሰዎችንና የቦታዎችንስምእገሌ፣አንድሰው ብለው ያልፋሉ፡፡ (ማቴ.፳፮፥፲፰፣፩ኛ. ነገ፲፫፥፩፣ ማቴ.፰፥፪፣ ሉቃ.፲፩፥፲፭) ይህ በአሥራው መጻሕፍት ብቻ የሚንጸባረቅ ሳይሆን የአዋልድ መጻሕፍትም ዓላማ ነው፡፡ በገድለ ተክለሃይማኖት፣ በገድለ ጊዮርጊስ፣ በተአምረ ማርያም ውስጥ በቅዱሳን አማላጅነት የእግዚአብሔር ሥራ (ተአምር) የተፈጸመላቸው ወይም የተፈጸመባቸው ሰዎችን ስም፣ ቦታ ሳያነሡ እገሌ፤ እገሊት አንድ ሰው ብለው የሚጠሩት ሰዎቹና ቦታዎቹ መጠሪያ ስለሌላቸው ሳይሆን ዓላማቸው የእግዚአብሔርን ሥራ መግለጥ ስለሆነ ነው፡፡

ሠ. የሃይማኖትን ታላቅነት በመግለጥ፡- ቅዱሳት መጻሕፍት በሃይማኖት፣ ለሃይማኖት፣ ስለሃይማኖት የተጻፉ ናቸው፡፡ ከጥርጥር፣ ከአጉል አሳብ ተጠብቆ በመጻሕፍቱ የተገለጠውን፣ የታዘዘውን ለጠበቀ የተባለው ይፈጸምለታል፡፡ ሠለስቱ ደቂቅ ሃይማኖትን ገንዘብ አደረጉ፡፡ በሃይማኖትም ሕግ ታዝዘው ለጣዖት መስገድን እምቢ አሉ፡፡ በዚህ የተነሣ ከእሳት ቢጣሉ በሃይማኖት የእሳትን ኃይል አጠፉ፡፡ ነቢዩ ዳንኤል በሃይማኖት የአናብስትን አፍ ዘጋ፡፡ ጌዴዎን ያለ ጦር መሣሪያ አእላፍ የአሕዛብን ሠራዊት ድል አደረገ፡፡ ይህ የሃይማኖትን ታላቅነት ያስረዳል (ዕብ.፲፩፥፴፫-፴፬)፡፡ በአዋልድ መጻሕፍትም አቡነ ኤውስጣቴዎስ በአጽፋቸው (በመጎናጸፊያቸው) ባሕር ሲከፍሉ፣ ፃድቁ አቡነ ተክለሃይማኖት ከንብ ቀፎ ተከተው በቆዳ ተጠቅልለው ከተወረወሩበት ገደል ሲወጡ፣ ከእሳት መካከል ቆመው እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ፤ቅዱስ ጊዮርጊስ የሚቆራርጥ መርዝ ሲያጠጡት ሕያው ሆኖ የሚያሳየን የሃይማኖትን ታላቅነት ነው፡፡

በአሥራውም ሆነ በአዋልድ መጻሕፍት የተጠቀሱት ሰዎች ታላላቅ ተአምራት ሲፈጽሙ የምንመለከተው መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በቅዱስ ወንጌሉ “አማን አማን እብለክሙ ዘየአምን ብየ ዘአነ እገብር ውእቱሂ ይገብር ወዘየዐቢ ይገብር፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፤ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል፤” ያለው ቃል ተፈጽሞላቸው ነው፡፡(ዮሐ.፲፬፥፲፪)፡፡

ረ. የሃይማኖትሰዎች ያደረጓቸውን ልዩ ልዩ ተጋድሎዎችን መግለጥ፡- እግዚአብሔር ድንቅ የሆነ ሥራውን ለፍጥረቱ የሚሠራው በፍጥረቱ አማካኝነት ነው፡፡ ይህም በልዩ ልዩ መንገድ ይፈጸማል፡፡ የእግዚአብሔር ሥራ በስፋትና በግልጥ ከሚሠራባቸው ፍጡራን መካከል ደግሞ ቅዱሳን ዋንኞቹ ናቸው፡፡ ቅዱሳን ለሕገ እግዚአብሔር ተገዝተው ፈቃዱን በመፈጸማቸው ንጽሐ ልቡናን ገንዘብ አደረጉ፡፡ በዚህ ሰውነታቸውም ከእግዚአብሔር በተቀበሉት ኃይል ብዙ ተጋድሎ ፈጽመዋል፡፡ የአሥራውም ሆኑ አዋልድ መጻሕፍት ይህን የቅዱሳንን የተጋድሎ ሕይወት ይገልጣሉ፡፡ ነሕምያ የኢየሩሳሌምን ቅጥር መሥራቱ፣ አስቴር በጾም በጸሎት ሕዝበ እሥራኤልን ስለመታደጓ፣ ዮዲት በጥበብ ሆሊፎርንስን መግደሏ፣ ቅዱስ ጴጥሮስ በጥላው ሕሙማንን መፈወሱ፣ እመቤታችን፣ጻድቃን ሰማእታት ልዩ ልዩ ገቢረ ተአምራት መፈጸማቸው በየቅዱሳት መጻሕፍቱ ተገልጦ እናገኛለን፡፡

አዋልድ መጻሕፍትን ቤተ ክርስቲያን የምትቀበለው እንዴት ነው?

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን አዋልድ መጻሕፍትን የምትቀበልበት ሥርዓት አላት፡፡ ቀደም ተብሎ በተደጋጋሚ እንደተገለጠው የአዋልድ መጻሕፍት ልጅነታቸው በይዘት፣በመንፈስ፣ በምሥጢርና በመሠረተ ሐሳብ ነው፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ መጻሕፍት “አሥራው መጻሕፍት” ይባላሉ፡፡ አሥራው ማለት ሥሮች ማለት ሲሆን፣ አሥራው መጻሕፍት ሲላቸው ደግሞ የሌሎች መጻሕፍት መገኛዎች፣ ሥሮች ማለት መሆኑን ልብ ይሏል፡፡ ይህም ማለት ለአዋልድ መጻሕፍት በይዘትና በመንፈስ፣ በምሥጢርና በመሠረተ ሐሳብ አስገኚ ሥራቸውና ወላጃቸው መጽሐፍ ቅዱስ ኾኖ በእርሱ ሥርነት የሚበቅሉና የሚያድጉ ማለት ነው፡፡

ይህ ኾኖ ሳለ በአንዳንድ ይዘታቸው፣ መጽሐፍ ቅዱስን ቢመስሉም ከመጽሐፍ ቅዱስ አስተምህሮ፣በጌታችን ከተገለጠውና ከሐዋርያት ጀምሮ ሲያያዝ ከመጣው የቤተክርስቲያንእምነትና ትምህርት ጋር ተቃርኖ ያላቸውን መጻሕፍት ቤተ ክርስቲያን ታወግዛለች እንጂ አትቀበልም፡፡ መጻሕፍቱም “ዲቃሎች” እንጂ “አዋልድ” አይባሉም፡፡

አዋልድ መጻሕፍትን በተመለከተ በሚከተሉት ነጥቦች መለየት እንደሚቻል ሕንዳዊው የነገረ መለኮት ሊቅ ጢሞቴዎስ አለን ይገልጡታል፡-

  • ዓላማቸው መንግሥተ እግዚአብሔር የሆነ፣

  • በሃሳብ፣ በመንፈስ፣ በምሥጢር፣ በነገረ መለኮት ከአሥራው መጻሕፍትና ከቅዱሳት የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ጋር የማይጋጩ፣

  • ለክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር፣ ሕይወትና አኗኗር ተስማሚ የሆኑ፣

  • የቤተ ክርስቲያን አበው፣ትውፊት ወይም ጉዞ ምስክር ያላቸው፣

  • ውስጣዊ ተቃርኖ የሌለባቸው፡፡

እንግዲህ በጎ ትምህርት የሚያስተምሩንን፣ ስለ ቅዱሳን አበውና እመው ሃይማኖታዊ ተጋድሎ የምንረዳባቸውን፣ አሥራው መጻሕፍትንም የሚያብራሩልንና የሚተረጉሙልንን አዋልድ መጻሕፍትን በመጠቀም በሃይማኖት ለመጽናት፣ በጎ ሥራ ለመሥራት ፈጣሪያችን ልዑል እግዚአብሔር ይርዳን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

 

የማቴዎስ ወንጌል

ግንቦት 22 ቀን 2006 ዓ.ም.

ይህ ወንጌል በምዕራፎች ብዛት የመጀመሪያው ወንጌል በመሆን 28 ምዕራፎች ዐቅፏል፡፡ በቁጥሮች ብዛት ደግሞ ሁለተኛ ወንጌል ሆኖ 1068 ቁጥሮችን አካቷል፡፡ የተጻፈው ከማርቀስ ወንጌል ቀጥሎ በ58 ዓ.ም. አካባቢ ነው፡፡ የጌታን ትምህርት በሰፊው በማቅረብ ቀዳሚውን ሥፍራ ይዟል፡፡ ከ1068 ቁጥሮች መካከል 644ቱ የጌታ ትምህርቶች ናቸው፡፡ ይኸም ከወንጌሉ 60% ማለት ነው፡፡ በዚህ አቀራረቡ ከዮሐንስ ወንጌል ጋር ሲዛመድ ከሉቃስና ከማርቆስ ወንጌል ይለያል፡፡

ወንጌሉን የጻፈው ለአይሁድ በመሆኑ ከ150 በላይ የብሉይ ኪዳን ጥቅሶችን አቅርቢል፡፡ በዚህም የተነሣ ብሉይ ኪዳንን አብዝቶ በመጥቀስ ከሌሎቹ ወንጌሎች ይበልጣል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቀድሞ በነቢያት የተነገረለት መሲሕ መሆኑን ለማስረገጥ ሲል አንድን ታሪክ ከጻፈ በኋላ “በዚህም…. ተብሎ የተነገረው /በነቢይ የተጻፈው/ ተፈጸመ” ብሎ ይመሰክራል፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ ትውፊትን በብዛት የተጠቀመ ሐዋርያ ነው፡፡ ማቴዎስ ወንጌሉን ስለ ጻፈበት ቋንቋ ሦስት ዓይነት አሳብ ቀርቧል፡፡

  1. በዕብራይስጥ፡- የቤተ ክርስቲያናችንን ሊቃውንት ጨምሮ ብዙ ምሁራን የተስማሙት ቅዱስ ማቴዎስ ወንጌሉን በዕብራይስ ቋንቋ ጻፈው በሚለው አሳብ ነው፡፡ ነገር ግን አስካሁን ድረስ የዕብራይስጡ ዋና ቅጅ (original copy) አልተገኘም፡፡

  2. በአራማይክ፡- ፖፒያስ የተባለው አባት በ2ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደገለጠው ሐዋርያው ቅዱስ ማቴዎስ አስቀድሞ የጌታችንን ትምህርቶችን በአራማይክ ቋንቋ ሎጂያ (logia) በተባለው መጽሐፍ ሰብስቦት ነበር፡፡ በኋላም ወንጌሉን ሲጽፍ የጌታን ትምህርቶች የገለበጠው ከዚህ መጽሐፉ ነው፡፡ አራማይክ ከዕብራይስጥ ዘዬዎች (dialects) አንዱ ሲሆን በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን አካባቢ የመካከለኛው ምሥራቅ /በተለይም በፍልስጥኤም ምድር/ ዋና ቋንቋ (lingual franca) ነበረ፡፡ ጌታም ወንጌሉን የሰበከው በአራማይክ ቋንቋ በመሆኑ ማቴዎስ የወንጌሉን መነሻ ረቂቅ በዚህ ቋንቋ ጽፎታል፡፡ በወንጌሉ ግን እጅግ በጣም ጥቂት ቃላትን /ለምሳሌ ኤሎሄ ኤሎሄ ላማ ሰበቅታኒ፡፡ ማቴ.27፥46/ ብቻ ከመጠቀሙ በቀር የአራማይክ ቃላት ተተርጉመው ቀርበዋል እንጂ አጻጻፉ አራማይክን አልተከተለም፡፡

  3. በግሪክ፡- አብዛኞቹ ጥንታውያን ቅጂዎች የሚገኙት በግሪክ ቋንቋ በመሆኑ በግሪክ ቋንቋ ተጻፈ የሚል አሳብ አለ፡፡ ጥንታውያን አበው (apologists) የማቴዎስን ወንጌል ሲጠቅሱ የተጠቀሙትም የግሪኩን ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት መሠረት ግን የማቴዎስን ወንጌል ወደ ግሪክ /ፅርዕ/ የተረጎመው ዮሐንስ ወንጌላዊ ነው፡፡

የማቴዎስ ወንጌል ከማርቆስ ወንጌል በኋላ በሁለተኛነት ተጽፎ እያለ የመጀመሪያውን ተርታ ያገኘበት ዋናው ምክንያት አቀራረቡ ለብሉይ ኪዳንና ለሐዲስ ኪዳን ድልድይ ስለሆነና የብሉይ ትንቢትና ምሳሌ በሐዲስ ኪዳን መፈጸሙን ስለሚያሳይ ነው፡፡ ወንጌሉን የጻፈው በምድረ ይሁዳ ተቀምጦ እንደሆነ ይነገራል፡፡

ምዕራፍ አንድ

ይህ ምዕራፍ ቅዱስ ማቴዎስ የጌታችንን የልደት ሐረግ የዘረዘረበት ነው፡፡ ዓላማውም ያላመኑት አይሁድ የጌታችንን መሢሕነት አምነው የተቀበሉትን ጌታ ወልደ ዳዊት ወልደ አብርሃም መሆኑን ሰፍራችሁ ቆጥራችሁ አስረክቡን ስላሉአቸው ለእነርሱ ግልጽ ለማድረግ ነው፡፡ አይሁድ በትንቢት መሢህ ከዳዊትና ከአብርሃም ዘር እንደሚወለድ ያውቁ ነበርና፡፡

የዳዊት ልጅ የአብርሃም ልጅ ብሎ አብርሃምንና ዳዊትን ብቻ ማንሳቱ ከነገሥታት ዳዊት፣ ከአበው አብርሃም ብቻ ይወልዱታል ማለት ሳይሆን እነዚህ ሁለቱ ምክንያት ስላላቸ ነው፡፡

ለአብርሃምና ለዳዊት ብዙ ትንቢት ተነግሮላቸው ስለነበርና እንዲሁም ተስፋ ለተስፋ ሲያነጻጽር ነው “የምድር ወገኖች በዘርህ ይባረካሉ” ተብሎ ለአብርሃም ተስፋ ተሰጥቶታል፡፡ ለዳዊት ደግሞ “ከሆድህ ፍሬ በዙፋንህ ላይ አስቀምጣለሁ” መዝ.131፥11፡፡

አንድም ዳዊት ሥርወ መንግሥት ነው፡፡ አብርሃምም ሥርወ ሃይማኖት ነውና፡፡ እንዲሁም ከአይሁድ ወገን በክርስቶስ ያመኑትን ገና ያላመኑት የአብርሃም የዳዊት ዘር መሆኑን አስረዱን ስላሉአቸው ወንጌላዊውም ይህን ለማስረዳት የአብርሃምንና የዳዊትን ስም ለይቶ ጠራ፡፡

“አብርሃም ይስሐቅን ወለደ”

የአብርሃም ልጆች ብዙዎች ሆነው ሳለ ይስሐቅን ብቻ ለይቶ ለምን አነሣ?

ወንጌላዊው የተነሣበት ዋና ዓላማ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ልደት ከነማን እንደሆነ ለማስረዳት ነው፡፡ የጌታ መወለድ ደግሞ ከይስሐቅ እንጂ ከአጋር ከተወለደው አስማኤል ወይም ከኬጡራ ከተወለዱት አይደለምና፡፡

“ይስሐቅም ያዕቆብን ወለደ” ያዕቆብና ኤሳው በአንድ ቀን ከአንድ እናት ተወልደው ሳለ ኤሳውን ለይቶ ለምን ተወው? ቢባል

ነቢይ የሆነ እንደሆነ ልደተ አበውን ጠንቅቆ ይቆጥራልና መላውን ዘር ያነሣል፡፡ ወንጌላዊ ግን የሚሻ የጌታን ልደት ነው፡፡ የጌታም መወለድ ከያዕቆብ ነው እንጂ ከኤሳው አይደለምና፡፡ ትንቢት የተነገረለት ምሳለ የተመሰለለት ለያዕቆብ ነው፡፡

  1. ትንቢት፡- “ከያዕቆብ ኮከብ ይወጣል ከእስራኤል ኃጢአትን ያስወግዳል” ዘኁ.25፥17፡፡

  2. ምሳሌ፡- ያዕቆብ ከወንድሙ ከኤሳው ተጣልቶ ወደ አጎቱ ወደ ላባ ሲሄድ ከምንጭ አጠገብ ደረሰ፡፡ ውኃው ድንጊያ ተገጥሞ በጎቹ ከምንጩ ዙሪያ ከበው ቆመው ኖሎት /እረኞች/ ተሰብስበው አገኘ፡፡ /ድንጊያውን አንስታችሁ በጎቹን አታጠጧቸውም? ብሎ እረኞቹን ቢጠይቃቸው፡፡ መላው ኖሎት ካልተሰበሰቡ ከፍቶ ማጠጣት አይሆንልንም አሉት፡፡ ውኃው ኩሬ ነው ጠላት ጥቂት ራሱን ሆኖ መጥቶ መርዝ እንዳይበጠብጥበት ለሃምሳ ለስድሳ የሚከፈት ድንጊያ ገጥመው ይሄዳሉ፡፡ ያዕቆብም ራሔል ስትመጣ ባየ ጊዜ ብቻውን ለስድሳ የሚነሳውን ድንጊያ አንሥቶ ውኃ ተጠምተው በጉድጓዱ ዙሪያ ተመስገው ለነበሩት በጎች አጠጥቷቸዋል፡፡ ዘፍ.2፥1-12፡፡ ይህም መሳሌ ነው፡፡

  • ያዕቆብ የጌታችንና የመድኀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ፣

  • ደንጊያው የመርገመ ሥጋ የመርገመ ነፍስ፣

  • ውኃው የሕይወት የድኅነት፣ የጥምቀት፣

  • በጎች የምዕመናን፣

  • እረኞች የነቢያት የብሉይ ኪዳን ካህናት፣

  • ራሔል የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም ምሳሌ ናቸው፡፡ በሰው ልጅ ሕይወት ላይ ተጭኖ ይኖር የነበረውን መርገም አንሥቶ ለዘላለም ሕይወትን የሰጠ ከድንግል ማርያም በሥጋ የተወለደው ጌታ ነውና፡፡

  • “ያዕቆብም ይሁዳንና ወንድሞቹን ወለደ”

  • የይስሐቅን ልደት በተናገረ ጊዜ ሌሎች የአብርሃም ልጆችን አላነሣም፡፡ የያዕቆብንም ልደት ሲናገር መንትያውን ኤሳውን አላነሣም አሁን ግን “ይሁዳንና ወንድሞቹን” በማለት ወንድሞቹን ጭምር ለምን አነሣ? ቢሉ

  • ጌታችን የተወለደው ከአሥራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል መሆኑን ለማስገንዘብ፡፡ የሁሉም አባታቸው ያዕቆብ ነውና፡፡

  • ይሁዳን ብቻ አንሥቶ ቢተው ሌሎቹ አባቶቻችንን ከቁጥር ለያቸው ነቢያት ቢሆኑ ባልለዩ ነበር እንዳይሉት መልእክቱ ለሁሉም ነገድ ነው የሚጻፈው፡፡

  • እንዲሁም ለምሳሌ እንዲመቸው ብሎ ነው ከአሥራ ሁለቱ ነገደ እስራኤል ያልተወለደ ምድረ ርስትን አይወርስም፡፡ የአሥራ ሁለቱ ሐዋርያትንም ትምህርት ያልተቀበለ ሁሉ መንግሥተ እግዚአብሔርን አይወርስምና፡፡

  • “ይሁዳም ከትዕማር ፋሬስንና ዛራን ወለደ”

የይስሐቅን ልደት በተናገረ ጊዜ እናቱ ሣራን፣ የያዕቆብን ልደት በተናገረ ጊዜም ርብቃን የይሁዳንና የወንድሞቹን ልደት በተናገረ ጊዜ እነ ልያን እነ ራሔልን አላነሣም አሁን ደርሶ የትዕማርን ስም ለምን አነሣ?

ትዕማር የተነሣችበት ለየት ያለ ምክንያት ስላላት ነው፡፡ ይሁዳ የሴዋን ሴት ልጅ አግብቶ ኤርን፣ አውናንን፣ ሴሎምን ይወልዳል፡፡ ለበኽር ልጁ ለኤር ከአሕዛብ ወገን የምትሆን ትዕማር የምትባል ብላቴና አምጥቶ አጋባው፡፡ ኤርም በእግዚአብሔር ፊት ክፉ ነበርና እግዚአብሔርም ቀሠፈው፡፡ ይሁዳም ከበኲር ልጁ ሞት በኋላ ሁለተኛ ልጁ አውናንን “ወደ ወንድምህ ሚስት ግባ አግባትም ለወንድምህም ዘርን አቁምለት አለው፡፡ አውናንም ዘሩ ለእርሱ እንዳይሆን ዐወቀ ወደ ወንድሙ ሚስት በገባ ጊዜ ለወንድሙ ዘር እንዳይሰጥ ዘሩን በምድር ያፈስሰው ነበር፡፡ ይህም ሥራው በእግዚአብሔር ዘንድ ክፉ ነበር እርሱንም ደግሞ ቀሰፈው፡፡

ይሁዳም ምራቱን ትዕማርን “ልጄ ሴሎም እስኪያድግ ድረስ በአባትሽ ቤት መበለት ሆነሽ ተቀመጪ አላት እርሱ ደግሞ እንደ ወንድሞቹ እንዳይሞት ፈርቶ፡፡ ትዕማርም ሄዳ በአባትዋ ቤት ተቀመጠች፡፡

ከብዙ ጊዜ በኋላ የይሁዳ ሚስት ሞተች ይሁዳም ተጽናና የበጎቹን ጠጉር ወደሚሸልቱት ሰዎችም ወደ ተምና ወጣ፡፡ ሴሎም እንደ አደገ ይሁዳም ያላት ነገር እንዳልተፈጸመላት ባየች ጊዜ እንዳታለለኝ ላታልለው ብላ ልብሰ ዘማ ለብሳ ጃንጥላ አስጥላ ድንኳን አስተክላ ከተመሳቀለ መንገድ ቆየችው፡፡ ምራቱ እንደ ሆነች አላወቀም ነበርና ወደ እርሷ ሊገባ ወደደ፡፡ እርስዋም፡- ወደ እኔ ብትገባ ምን ትሰጠኛለህ አለችው የፍየል ጠቦት ከመንጋዬ እሰድድልሻለሁ አላት እርስዋም እስክትሰድድልኝ ድረስ መያዣ ትሰጠኛለህ አለችው እርሱም ምን መያዣ ልስጥሽ አላት፡፡ እርስዋም ቀለበትህን፣ አምባርህን በእጅህ ያለውን በትር አለች፡፡ እርሱም ሰጣትና ከእርስዋ ደረሰ እርስዋም ፀነሰችለት፡፡

ይሁዳም መያዣውን ከሴቱቱ ይቀበል ዘንድ በወዳጁ በዓዶሎማዊው እጅ ፍየሉን ጠቦት ላከላት እርስዋንም አላገኛትም፡፡ እርሱም የአገሩን ሰዎች በኤናይም በመንገድ ዳር ተቀምጣ የነበረች ጋለሞታ ወዴት ናት? ብሎ ጠየቃቸው፡፡ እነርሱም፡- በዚህ ጋለሞታ አልነበረችም አሉት፡፡

ከሦስት ወር በኋላ ለይሁዳ ምራትህ ትዕማር ሴሰነች በዚህም የተነሣ ፀነሰች ብለው ነገሩት ይሁዳም፡- አውጡአትና በእሳት ትቃጠል አለ፡፡ እርስዋም ባወጡአት ጊዜ ወደ አማትዋ እንዲህ ብላ ላከች፡- ለዚህ ለባለ ገንዘብ ነው የፀነስሁት ተመልከት ይህ ቀለበት፣ ይህ ባርኔጣ /መጠምጠሚያ/ ይህ በትር የማን ነው? ይሁዳም ዐወቀ፡- ከእኔ ይልቅ እርስዋ እውነተኛ ሆነች ልጄን ሴሎምን አልሰጠኋትምና አለ፡፡ ዘፍ.38፥1-30፡፡

የፀነሰችውም መንታ መሆኑን ዐውቃ ነበርና በምትወልድበት ጊዜ አዋላጂቱን አስቀድሞ የተወለደውን በኲሩን እንድናውቀው ቀይ ሐር እሠሪበት አለቻት፡፡ አስቀድሞ ዛራ እጁን ሰደደ አዋላጂቱም ቀይ ፈትል ወስዳ በእጁ አሰረች፡፡ ፋሬስ እሱን ወደ ኋላ ስቦ ተወለደ ፋሬስ ማለት ጣሽ ማለት ነው፡፡ እንዲሁም ያየነው ቀርቶ ያላየነው ወጣ ማለት ነው፡፡ ዛራ /ዘሐራ/ መልከ መልካም ማለት ነው፡፡ ይህ ሁሉ ምሳሌ ነው፡፡

 

  • ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 3ኛ ዓመት ቁጥር 1 ታኅሥሥ 1988 ዓ.ም.

ይቀጥላል

meglecha 2006 01

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የግንቦቱ ርክበ ካህናት መግለጫ በማውጣት ተጠናቀቀ

ግንቦት 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

  • በቅዱስ ሲኖዶስ የቀረበው መግለጫ ውሳኔ ያላገኙ አጀንዳዎችን አካቷል

meglecha 2006 01ከግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ. ም. ጀምሮ ሲካሔድ የቆየው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ግንቦት 19 ቀን 2006 ዓ. ም. መግለጫ በመስጠት ተጠናቋል፡፡ ጉባኤው ሲጠናቀቅ በቀረበው መግለጫም ውሳኔ ሳያገኙ የቀሩ አጀንዳዎችን አካቷል፡፡ ከእነዚህም ውስጥ፡-

  • የብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የቅዱስ ፓትርያርኩ ረዳት ሊቀ ጳጳስ፤ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ረዳት ሊቀ ጳጳስነት ተነስተው የጅማ ሀገረ ስበከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው እንዲሠሩ ሲወሰን፤ ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሳይመደብለት ታልፏል፡፡

  • የማኅበረ ቅዱሳን መተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያ ረቂቅ 34 ገጽ ለጉባኤው ቀርቦ ምልዓተ ጉባኤው በስፋት ውይይት ማድረጉን ከመግለጽ ውጪ ውሳኔ ሳይሰጠው ቀርቷል፡፡

ዝርዝሩን ከሙሉ መግለጫው ይከታተሉ፡፡

 meglecha 2006 02

sino 2006 01 2

የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት የተመሠረተበትን 50ኛ ዓመት አከበረ

 ግንቦት 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

sino 2006 01 2የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዩበልዩ በዓል ግንቦት 16 ቀን 2006 ዓ.ም. ቦሌ በሚገኘው በድርጅቱ ሕንፃ አከበረ፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ቅዱስ ፓትርያርኩ፤ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የቀድሞው የኢፌዲሪ ፕሬዚዳንት አቶ ግርማ ወልደ ጊዮርጊስ፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ጥሪ የተደረገላቸው የክብር እንግዶችና የድርጅቱ አባላት ተገኝተዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በሰጡት ቃለ ምእዳን “የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት 50ኛ ዓመት የወርቅ ኢዩቤልዩ ክብረ በዓል የቤተ ክርስቲያናችን በተለይምsino 2006 01 4 በኢየሩሳሌም ውስጥ ለሚገኙት ገዳማት ታላቅና ታሪካዊ የሆነ በዓል ነው፡፡ 50 ዓመታትን ተስፋ ሳይቆርጡ እዚህ ላደረሱት የድርጅቱ ሓላፊዎችና ምእመናን ሁሉ ምሥጋናዬን አቀርባለሁ፡፡ የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት አገልግሎት ወደፊትም ሳይቋረጥ እንዲቀጥል ከሥሩ ተተኪ ምእመናንን ማፍራት አለበት” ብለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ ድርጅቱን በመምራትና በአባልነት ላገለገሉ ምእመናን ከቅዱስ ፓትርያርኩ እጅ ድርጅቱ ያዘጋጀላቸውን ስጦታ ተረክበዋል፡፡ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ዴር ሡልጣን ገዳም ታሪካዊ ይዞታና የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅትን የሚዘክር መጽሐፍም ተመርቋል፡፡ የታእካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያሬዳዊ ዝማሬና ቅኔ አቅርበዋል፡፡

ethiopian-monestary-jerusalem-18819346 1የድርጅቱ መሥራችና የቦርድ ሰብሳቢ የሆኑት አቶ አለማየሁ ተስፋዬ የድርጅቱን አመሠራረት አስመልክቶ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ በ1955 ዓ.ም. ሠላሳ አባላት ያሉት የምእመናን ቡድን በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ውስጥ የሚገኙትን የኢትዮጵያ ገዳማትን ለመጎብኘት ተጉዘው እንደነበር ይገልጻሉ፡፡ አባላቱ በአውሮፕላኑ ሠራተኞች አማካይነት ወደ ዴር ሱልጣን ገዳም ተወስደው በዴር ሱልጣን ገዳም በሚገኙ ኢትዮጵያውያን መነኮሳት ላይ የኮፕት ኦርቶዶክሶች ያደርሱባቸው የነበረውን ከፍተኛ በደል ተመልክተዋል፡፡ መነኮሳቱም ተጎሳቁለው በከፍተኛ ችግር ውስጥ ወድቀው እንዳገኟቸው አቶ አለማየሁ ተስፋዬ ይናገራሉ፡፡

መነኮሳቱም “እኛ የራበን ሰው ነው፤ ረሃባችን ወገን የሚሆነን ማጣታችን ነው፡፡ እባካችሁ ወደ ሀገራችን ስትሔዱ ኢትዮጵያውያን እንዲጎበኙን አድርጉ” በማለት ነበር በወቅቱ መልእክታቸውን ያስተላለፉት፡፡

ከተጓዦቹ መካከል ታላላቅ ኢትዮጵያውያን ምሁራን እንደነበሩበት የሚገልጹት አቶ አለማየሁ የጉዳዩ አሳሳቢነት እረፍት ስለነሳቸው እዚያው እያሉ ጥናቶችን በማድረግ አንድ ማኅበር መመሥረት እንዳለበት በመነጋገር ስምምነት ላይ ይደርሳሉ፡፡ በዚህም መሠረት አዲስ አበባ ተመልሰው ለጉዳዩ ትኩረት በመሥጠት ተጨማሪ ሰዎችን በማሰባሰብ ውይይት በማድረግ “የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት” የካቲት 16 ቀን 1956 ዓ.ም. ተመሠረተ፡፡ የመጀመሪያውን ጉዞ 85 ምእመናንን በመያዝ በአንድ ሰው 302 ብር በማስከፈል ወደ ኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ጉዞ ተደረገ፡፡ ለ50 ዓመታት በተደረገ ያልተቋረጠ ጉዞም ከ15,000 በላይ ምእመናን በድርጅቱ አማካይነት ተጉዘው ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ቦታዎቹን ለማየት እንደቻሉ አቶ አለማየሁ በመግለጫቸው አስታውሰዋል፡፡

የኢየሩሳሌም መታሰቢያ ድርጅት በሀገር ውስጥ በርካታ የበጎ አድራጎት ሥራዎችን እየሠራ የሚገኝ ሲሆን በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማትን ችግር በመከታተልና በመፍታት፤ በተለይም የዴር ሱልጣን ገዳም ወደ ኢትዮጵያ ባለቤትነት ለማስመለስ እንዲሁም ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ አካላት ጋር መፍትሔ በመፈለግ ከፍተኛ ጥረት በማድረግ ላይ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡

sino 2006 01 3
የዴር ሱልጣን ገዳም ከብዙ ውጣ ውረድና ትግል በኋላ ገዳሙ የኢትዮጵያ ይዞታ እንደሆነ ተረጋግጦ በ1953 ዓ.ም. ቁልፉ ኢትዮጵያውያን እንዲረከቡት ተደርጎ እንደነበር የሚያስረዱት አቶ አለማየሁ ለአንድ ወር ከአስራ አምስት ቀናት ብቻ እንደተጠቀሙበት ኢየሩሳሌም የሚገኙት የኮፕት ኦርቶዶክስ አባቶች በወቅቱ የግብጽ መሪ ለነበሩት አቤቱታ አቀረቡ፡፡ ተጨማሪ መረጃዎች አሉን ፍርዱ እንደገና ይታይልን በሚል የተፈረደው ፍርድ እንዲሻር ተደርጓል፡፡ የዴር ሱልጣን ገዳም ጉዳይ ዛሬም ድረስ እንዳልተፈታ የሚገልጹት አቶ አለማየሁ ድርጅቱ በዓመት አንድ ጊዜ በሚያደርገው ጉዞ በርካታ ችግሮች እንደሚያጋጥሙ ይገልጻሉ፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በኢየሩሳሌም የዴር ሡልጣን፤ የደብረ ገነት ኪዳነ ምሕረት፤ የአልዓዛር ተክለ ሃይማኖት፤ የኢያሪኮ ቅዱስ ገብርኤል፤ የቤተልሔም ቅዱስ በዓለ ወልድ፤ የኢያሪኮ ቅድስት ሥላሴ /በ6ቱ ቀን ጦርነት የተከማቹ ፈንጂዎች ስለሚገኙበት አገልግሎት አይሰጥም/ የመሳሰሉ ገዳማት ያሏት ሲሆን በነገሥታቱና በመኳንንቱ የተሠሩ ሕንፃዎችም ይገኛሉ፡፡

 

 

a washa 1

አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ክፍል ሁለት

 ግንቦት 19 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በካህናቱ መሪነት ከተራራው ሥር ወደምትገኘው ወደ ቀድሞ ዋሻ ቤተ ክርስቲያን ስናመራ፤ ከተራራው አናት ላይ ሆነን ቁልቁል ስንመለከት ትልቅ ወንዝና ደረቱን ለኛ የሰጠ ተራራ ተመለከትን ፡፡ ካህናቱንና ዲያቆናቱን ተከትለን ቁልቁል የሚወስደውንa washa 1 ቀጭን መንገድ ተያያዝነው፡፡ ወንዙ ምን ይባላል አልናቸው ለአንድ አዛውንት “ የማርያም ዥረት ነው የሚባለው” አሉን ፡፡ እንደመቀነት የሚጠማዘዘውን ቀጭን መንገድ እየተከተልን ወደ ዋሻው አፋፍ ደረስን፡፡ ወደ ዋሻው መግቢያ በስተቀኝ በኩል በመጠኑ የጎደጎደ ሥፍራ ይታያል፡፡ ምን እንደሆነ ጠየቅን፡፡ “ከተራራው ሥር እየፈለቀ የሚወርድ ማየገቦ የሚጠራቀምበት ጉድጓድ ነበር፤ (ማየገቦ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተሰቀለ ጊዜ በቦታው ያልነበረው አንድ ዓይና ሌንጊኖስ ከአይሁድ ጋር ለመተባበር ብሎ ኢየሱስ ክርስቶስን በጦር ቢወጋው ውኃና ደም እንደ ለ ፊደል ፈሷል ፡፡ የፈሰሰው ውኃ ማየገቦ ይባላል፡፡) ዋሻው ቤተ መቅደስ ከተደረመሰ በኋላ ደርቋል” አሉን አዛውንቱ፡፡

የተናደው የድንጋይ ክምር አልፈን ወደ ውስጥ ዘለቅን፡፡ ቀድሞ ቅድስትና መቅደስ ሆኖ ሲያገለግል የነበረውን ቤተ ክርስቲያን ለማየት ቻልን፡፡ ቀጥለን በጧፍ ብርሃን እየተመራን ሰፋፊ የዋሻውን ክፍሎች ተመለከትን፡፡ ውስጥ ለውስጥ በሚያስኬደው መንገድ ሽቅብ ወጥተን እንደገና ወደጎን በመሄድ በሌላ መንገድ ከዋሻው ወጣን፡፡

በቀጣይነትም የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ መቅደስ የነበረውን ዋሻ ለማየት ተጓዝን፡፡ ቤተ መቅደሱ መጠነኛ እድሳት ከመፈለግ ውጪ በጥሩ ሁኔታ ላይ የሚገኝ ነው፡፡ ቅኔ ማኅሌቱ፤ ቅድስቱና መቅደሱ በር ቢገጠምላቸው ዛሬም አገልግሎት ሊሰጥ ይችላል፡፡ የጉዶ በረት የቅዱስ ጊዮርጊስ ጽላት ከዚህ ዋሻ መሄዱንም ከካህናቱ ተነገረን፡፡ በገዳሙ ውስጥ 24 የሚደርሱ ጽላት ሲኖሩ፤ በተለያዩ ዘመናት የተጻፉ የብራና መጻሕፍት በብዛት እንደሚገኙም ተገለጸልን፡፡

ይህ የዋሻ ቤተ ክርስቲያን እስከ 1951 ዓ.ም. ድረስ አገልግሎት ሲሰጥ እንደነበረና በወቅቱ በሥፍራው የነበሩት መምሬ ጥላዬ ስለሁኔታው እንዲህ ይገልጻሉ፡፡ “ሰኔ 21 ቀን 1951 ዓ.ም. ምሽት ወደ ቤተ መቅደስ የምንገባበት ስዓት እስኪደርስ እረፍት ለማድረግ ተኝተን ሳለ ከተራራው የተፈነቀለ ትልቅ ድንጋይ እኛ ወዳለንበት ተምዘግዝጎ በመውረድ ለጥቂት ዳንን፡፡ በሁኔታው ተደናግጥን ቦታ ቀየርን፡፡ ሐምሌ 23 ቀን 1951 ዓ.ም. ተራራው ተንዶ ቅኔ ማኅሌቱ መሉ ለሙሉ ፈርሷል፡፡

a washa 2ዋሻው የተደረመሰበት ዋነኛ ምክንያት እንደሆነ የሚታመነውም በወቅቱ አንዲት ሴት ለአሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ገዳም አንድ ጋሻ መሬት ለመገበሪያ ብላ በስጦታ ለግሳ ነበር፡፡ አገልግሎት ሲሰጥ የተወሰኑ ዓመታት እንደተቆጠሩም ሴትየዋ ቃሏን በማጠፍ መሬቱን ከእመቤታችን በመውሰድ ለሌላ ግለሰብ ሰጠችው፡፡ ሴትየዋም ይህንን በማድረጓ ለሰባት ዓመታት በደዌ ዳኛ ተይዛ ስትማቅቅ ቆይታ አርፋለች፡፡ አስከሬኗንም በዚሁ ገዳም አምጥተው ይቀብሩታል፡፡ እመቤታችን ለአባቶች እየተገለጠች “የዚህችን ሴት አስከሬን ከዚህ ቦታ አውጡልኝ፤ ሸተተኝ” እያለች ነግራቸዋለች፡፡ ነገር ግን ተግባራዊ ባለማድረጋቸው ሐምሌ 23 ቀን 1951 ዓ.ም. ዋሻ ቤተ ክርስቲያኑ ሊፈርስ ችሏል፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስም የሴትየዋ ግማሽ አስከሬን ከአንድ ድንጋይ ተጣብቆ ተንጠልጥሎ የነበረ ሲሆን አሁን የት እንደሔደ አይታወቅም በማለት የዋሻውን መደርመስ ምክንያት አወጉን፡፡

ከሁለቱም ዋሻዎች ግራና ቀኝ ተራራው ተቦርቡሮ በድንጋይ የተከደኑ መቃብሮች ይታያሉ፡፡ ከሌሎቹ መቃብሮች ለየት ባለ ሁኔታ በድንጋይ ሳይዘጋ የቀረና በግልጽ የሚታይ የሬሳ ሳጥን ተመለከትን፡፡ ምንድ ነው? ማለታችን አልቀረም፡፡ ለመስዋእት a washa 3የተዘጋጀውን መገበሪያ የበላችው አቃቢት አስከሬን እንደሆነና እንደ ሎጥ ሚስት የጨው አምድ ሆና መድረቋን ነገሩን፡፡ ሳጥኑ በቀላሉ የሚከፈት ሲሆን በአቡጀዲ የተጠቀለለውን አስከሬን ለማየት ቻልን፡፡ አስከሬኑ ሙሉ ለሙሉ አልፈረሰም፡፡

በአካባቢው በርካታ ዋሻዎች እንዳሉ ለማየት ችለናል፡፡ ስንጠይቅም ከተለያዩ አካባቢዎች የሚመጡ ምእመናን ሱባኤ መያዣ እንደሆኑና በርካታ ዋሻዎች እንዳሉ ተነገረን፡፡

መምሬ ጥላዬ “በግራኝ ወረራ ዘመን ብዙ ታቦታት በዚህ አካባቢ ተሰውረው ተቀምጠው ነበር ሲሉ ሰምቻለሁ” አሉን ፡፡ እውነትም የተዘጉ ዋሻዎች እንዳሉ ተረዳን፡፡ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑን እያስተባበረ የሚያሰራው ወጣቱ አቶ ይስማ “ ይህ ዋሻ እስከ ጅብ ዋሻ ማርያም ይወስዳል አለን፡፡”

jibwasha mariyamትኩረታችንን ሳበውና ጅብ ዋሻ ማርያም የት ነው? ጅብ ዋሻ ለምን ተባለ? ጅብ ዋሻ እንዴት ይኬድ ነበር? በማለት ለጠየቅነው ጥያቅ የጅብ ዋሻ ማርያም የተባለበትንም ምክንያት የቀይት ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህናት ቀሲስ ብርሃኑ ለገሰ እንዲህ በማለት ያስረዱን ጀመር “ጀብ ዋሻ ማርያም /አሁን ገነት ዋሻ ቅድስት ማርያም ተብሎ ይጠራል/ ከተመሠረተ 620 ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ በአካባቢው አንድ ሰው ሞቶ ፍታት ለማድረግ በቤተ ክርስቲያን የነበረውን ከበሮ ወደ ውጪ ወጥቶ ፀሐይ እንዲሞቅ ይደረጋል፡፡

ከአገልግሎት በኋላ ከበሮው ተረስቶ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሳይገባ ይቀራል፡፡ ምሽት ላይ ጅብ መጥቶ ከበሮውን ይደበድባል፤ በአካባቢው የከበሮው ድምጽ ይሰማል፡፡ በወቅቱ የነበሩት ሰዎች ማነው ከበሮ የሚደበድበው? ብለው ቢወጡ ከበሮውን የሚደበድበው ጅቡ መሆኑን ተረዱ፡፡ በዚህ ጊዜ ኧረ ቦታው የጅብ ዋሻ ሆኗል ብለው በመናገራቸው ጅብ ዋሻ ማርያም ተብሎ ሲጠራ ኖሯል፡፡ አሁን ግን ስሙ ገነት ዋሻ እየተባለ የሚጠራና ብዙ ተአምራት እየተደረገበት የሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ነው” ብለውናል፡፡

አለቃ ተሰማ ወልደ ጊዮርጊስ አሁን የ97 ዓመት አረጋዊ ናቸው፡፡ ቀድሞ በደብረ ሲና መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡ ስለ አስገድመኝ ማርያምና ጅብ ዋሻ ማርያም የሚያውቁትን ንገሩን አልናቸው “ከልጅነቴ ጀምሮ የማውቃት aleka tesemaታቦት ነች፡፡ ስዕለት ሰሚ፤ ተአምር አድራጊ በመሆኗ ወደዚህ ቦታ የማይመጣ ክርስቲያን አልነበረም፡፡ ልጅ ስለነበርን “እስከ ጅብ ዋሻ ማርያም ድረስ ውስጥ ለውስጥ የሚያስኬድ መንገድ አለ፡፡” ሲሉ ሰምተን ከጓደኞቼ ጋር ቅብዓ ኑግ የኑግ ጭማቂ በገል አድርገን እያበራን ውስጥ ለውስጥ ሄደናል፡፡ በጣም ያስፈራል፤ በዋሻው ውስጥ ባህር አለ፡፡ ማን እንዳዘጋጀው ለምን እንደተዘጋጀ ባናውቅም በዋሻው ውስጥ ወደ ጅብ ዋሻ ሄደናል” ሲሉ የቦታዋን ታሪክ ነገረውናል፡፡

የደብረ ብርሃን አውራጃ አስተዳዳሪ በኋላም በደርግ ዘመን የወንበሮና ጠቆ ቀበሌ ገበሬ ማኅበር ሊቀ መንበር የነበሩት አቶ ተሾመ በቀለ መሬት ለአስግድመኝ ማርያም ሰጥተዋል፡፡ ስለ አሰግድመኝ ማርያምና ጅብ ዋሻ ማርያም የነገሩን “ልጅ ሳለሁ ወደ ጅብ ዋሻ የሚወስድ መንገድ መኖሩን ሰምተን በጨለማ ጉዞ ጀምረን ነበር ነገር ግን በጣም ስለሚያስፈራ ተመልሰናል፡፡” በማለት የዋሻውን መኖር ነገሩን፡፡

ከአስግድመኝ ማርያም ቤተ ክርስቲያን ጀርባ ከተራራው አናት ጀምሮ ቁልቁል በቀጭኑ መስመር ሰርቶ የሚወርደው ጸበል መቀበያ ቀጭን ቱቦ ገብቶለት ያለማቋረጥ ይወርዳል፡፡ ሥፍራው በድንጋይ ተከልሏል፡፡ ገዳሙ ሲመሠረት ጀምሮ ጸበሉ እንደነበር አባቶች የሚገልጹ ሲሆን በፈዋሽነቱም ይታወቃል፡፡

በጸበሉ በርካታ አገልጋዮችና ምእመናን የተፈወሱ ሲሆን ዓይን ከማብራት እስከ ዘመናችን በሽታ በኤድስ የተያዙ ሰዎችን ጭምር ተፈውሰዋል፡፡ ወደዚህ ቅዱስ ቦታ መጥቶ ሳይፈወስ የተመለሰ እንደሌለ በእርግጠኝነት መረጃ በመጥቀስ አገልጋዮቹ ይናገራሉ፡፡

አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ገዳም ለ800 ዓመታት አገልግሎት ሲሰጥ የቆየ ነው፡፡ ነገር ግን የዋሻው ቤተ መቅደስ አገልግሎት ካቆመ 55 ዓመታትን አስቆጥሯል፡፡ ዋሻ ቤተ መቅደሱን ወደ አገልግሎት ለመመለስ የእድሳትና ጥገና ለማከናወን፤ እንዲሁም ዋሻው ቤተ መቅደስ ከፈረሰ በኋላ የተሰራው መቃኞን ወደ ዘመናዊ ሕንፃ ለመለወጥ ኮሚቴ ተዋቅሮ በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛል፡፡

በንቡረ ዕድ አባ ገብረ ሕይወት መልሴ የበላይ ጠባቂነት ሁለቱንም ሥራዎች ለማከናወን የመሠረት ድንጋዩ ከተቀመጠበት መስከረም 21 ቀን 2006ዓ.ም. ጀምሮ አዲስ አበባ፤ ጉዶ በረትና፤ አጥቢያው በተዋቀሩ ኮሚቴዎች አማካይነት አዲሱን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት ርብርቡ ቀጥሏል፡፡ ኮሚቴው ከሌሎች ልምድ ካላቸው መሰል የቤተ ክርስቲያን አሰሪ ኮሚቴዎች ጋር በመወያየትና ልምድ በመቅሰም የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር በማዘጋጀት ሕንፃውን በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡

ቤተ ክርስቲያኑ እስከ 4 ሚሊዮን ብር ሊፈጅ ይችላል ተብሎ ተገምቷል፡፡ ካህናቱና ምእመናን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑን ለመሥራት ቁርጠኛ ሆነዋል፡፡ ንቡረ ዕድ ግን ፍቅር ሳይኖር ቤተ ክርስቲያን መሥራት ተገቢ አይደለም በማለት፤ የተጣላ አስታርቀው ጉልበታቸውን ሳይቆጥቡ ሌት ተቀን በማስተባበር ሕዝቡም ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይል በመሥራት ላይ ናቸው፡፡ ለሥራው ቀና እንዲሆን ከጉዶ በረት ጀምሮ ያለውን የስድስት ኪሎ ሜትር ጥርጊያ መንገድ ምንም አስቸጋሪ ቢሆንም በመሥራት መኪና እንዲገባ ለማድረግ ችለዋል፡፡

ንቡረ ዕድ አባ ገብረ ሕይወት መልሴ መልእክታቸውን ሲያጠቃልሉ “ሕዝቡ በጉልበቱ ከመሥራት ውጪ አሥራት በኩራት የማውጣት ልምድ የለውም፡፡ ማስተማራችንና መቀስቀሳችንን እንቀጥላለን፡፡ በብዙ ነገር ይረዱናል፡፡ የቤተ ክርስቲያኑ ግንባታ መጀመሩን መረጃ የደረሳቸው ከካናዳ፤ ከአሜሪካና ከተለያዩ የዓለም ሀገራት የሚገኙ ልጆቻችን ገንዘብ እየላኩልን ነው፡፡ ስለዚህ የዋሻ ቤተ መቅደሱንም ወደ ቀድሞ ይዞታው ለመመለስና የታሪክ ቅርስነቱን ጠብቆ ለማቆየት እንሰራለን፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ታንጻ አይቼ መሞት ምኟቴ ነው፡፡ እግዚአብሔር ይህንን ምኟቴን ይፈጽምልኛል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ፡፡ ምእመናንም በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገር ያሉ ሁሉ እንዲረዱን ጥሪዬን ነው የማስተላልፈው” ብለዋል፡፡

 

ger.hawira 2006 2

ሐዊረ ሕይወት በሀገረ ጀርመን ተካሄደ

 ግንቦት 15 ቀን 2006 ዓ.ም.

ከጀርመን ቀጣና ማእከል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የጀርመን ቀጣና ማእከል በአውሮፓ የመጀመሪያውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ከግንቦት 8-10, 2006 በክሩፈልባክህ (Kroeffelbach) በሚገኘው የኮፕቲክger.hawira 2006 2 ቅዱስ እንጦንስ ገዳም (Sankt-Antonius Kloster) በደማቅ ሁኔታ አካሄደ።

በዚህ ከ80 በላይ ምእመናን በተሳተፉበት መርሐ ግብር ላይ ሰፊ ትምህርት የተሰጠ ሲሆን በተለይ ነገረ ድኅነት እና መንፈሳዊ አገልግሎት ላይ የተሰጡት ጥልቅ ትምህርቶች ተሳታፊዎች በጉዳዮቹ ላይ የነበራቸውን እውቀት በከፍተኛ ሁኔታ ያሳደጉ እና ታዳሚው ሐዊረ ሕይወት በቅርቡ ይደገምልን የሚል ጥያቄን እንዲሰነዝር ያነሳሱ ነበሩ። በተጨማሪም መዝሙራት በዘማርያንና በሕብረት የቀረቡ ሲሆን ማኅበረ ቅዱሳን በሀገር ቤት ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋትበተለይም በተመረጡ ጠረፍና ገጠር አብያተ ክርስቲያናት ላይ አቅዶ እያከናወነው ስላለው የስብከት ወንጌል ማስፋፊያ ፕሮግራም ገለጻ ተደርጓል።

ወደ ጀርመን ሀገር የሚመጡ አዳዲስ ስደተኞችን ከቅድስት ቤተክርስቲያን ለማስኮብለል የሚደረገውን የተቀናጀ ዘመቻም ትኩረት ተሰጥቶ ውይይት የተደረገበት ሲሆን ይህንንም ለመከላከል ቀጣና ማእከሉ ከሀገረ ስብከቱ፣ ከሌሎች አገልጋዮች እና ከምእመናን ጋር በመተባበር የበኩሉን ድርሻ እንዲወጣ ከተሳታፊዎች ማሳሰቢያ ተሰጥቷል። አርብ ምሽት የተጀመረው መርሐ ግብር እስከ ቅዳሜ ምሽቱ 5 ሰዓት ድረስ በትምህርት፣ መዝሙርና ውይይት ከቀጠለ በኋላ ፍጻሜውን ያገኘው እሁድ ከግብፃውያን አባቶች ጋር ቅዳሴ በመሳተፍ ነበር።

ger. hawira 2006
በስደት አገር ይህንን የመሰለ ትልቅ ገዳም ሰርተው ይህንን የተሟላ ሊባል የሚችል ማረፊያ ቦታቸውን በነፃ የሰጡን የግብፃውያን ትጋት ለቦታው አዲስ የሆኑ ታዳሚዎችን ያስደመመ ሲሆን የሊቀ ጳጳሱ አቡነ ሚካኤል ደግነትና ትህትናም በቀላሉ የሚረሳ አይሆንም። መርሐ ግብሩ እሁድ ከምሳ በኋላ የተፈጸመ ሲሆን ሁለተኛ የምንገናኘው መቼ ነው የሚለው የብዙዎች ጥያቄ ሆኖ ይቆያል። ቀጣና ማእከሉ ለዝግጅቱ መሳካት የተለያዩ ድጋፍ ያደረጉ ምእመናንን ፣ በአገልግሎቱ የተሳተፉ መምህራንንና በገዳሙ በነጻ መጠቀም እንድንችል ለፈቀዱልን ለብፁዕ አቡነሚካኤል ከፍተኛ ምስጋናውን ያቀርባል፡፡

 

adama HawirHiwot

ሐዊረ ሕይወት(አዳማ ማዕከል)

adama HawirHiwot

methehaf awalede

“የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ. . . ይጠቅማል” 2ኛ ጢሞ.3፤16-17

 ግንቦት 12 ቀን 2006 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖአምላክ

methehaf awalede“መንፈሰ እግዚአብሔር ያለበት፣ ሰውን ከክፋት፣ ከኃጢአት፣ ከበደል የሚመልስ፤ ይልቁንም ሃይማኖቱን የሚያጸናለት መጽሐፍ ከእግዚአብሔር ነውና ይጠቅማል” በማለት ቅዱስ ጳውሎስ የተናገረው ቃል ነው፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ቃል ያስተላለፈው ለጊዜው በሃይማኖት ትምህርት ወልዶ ላሳደገው ለደቀመዝሙሩ ጢሞቴዎስ ቢኾንም ፍጻሜው ግን እስከ ሕልፈተ ዓለም ለሚነሡ ክርስቲያኖች ሁሉ የተናገረው ነው፡፡ “የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል።” (፪ኛ. ጢሞ.፫፥፲፮-፲፯)

 

መንፈሰ እግዚአብሔር ያለባቸው መጻሕፍት ሁሉ እንደሚጠቅሙና እንደሚያስፈልጉ ሐዋርያው በመልእክቱ ያስተላለፈውን ቃል መመሪያ አድርጋ ቅድስት ቤተክርስቲያንየአሥራው መጻሕፍት ልጆች የምንላቸውን አዋልድ መጻሕፍትን አዘጋጅታልናለች፡፡
አዋልድ መጻሕፍት፡-

“አዋልድ መጻሕፍት” የሁለት ቃላት ጥምር ሐረግ ሲሆን ቀጥተኛ ትርጉሙ የመጻሕፍት ልጆች ማለት ነው፡፡ መጻሕፍት የተባሉትም በቀኖና ቤተ ክርስቲያን ተለይተውና ተቆጥረው የምናውቃቸው ሰማንያ አንዱ መጻሕፍተ ብሉያትና ሐዲሳት ናቸው፡፡

አዋልድ መጻሕፍት የአሥራው መጻሕፍት ምሥጢር ትርጓሜ ተብራርቶ የሚገኝባቸው መጻሕፍት ናቸው፡፡ ቅዱሳን ነብያት እንዲሁም ሐዋርያት፤ በየዘመናቱ የተነሡ መምህራንና ሊቃውንት አዋልድ መጻሕፍት መጠቀማቸው መጽሐፍ ቅዱስ ያስረዳል፡፡ /ኢያሱ 10፤13, 2ኛ ሳሙ.1፤18/ መጽሐፍ ቅዱስን ለማብራራት አዋልድ መጻሕፍት አስፈላጊ ናቸው፡፡

ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአንድ ወቅት ‹ሕግን አውቃለሁ›ለሚል ሰው ወንበዴዎች ደብድበው በሞትና በሕይወት መካከል ጥለውት ስለሄዱ አንድ መንገደኛ በምሳሌ አስተምሮታል፡፡ ይህን ቁስለኛ አንድ ሩኅሩኅ ሳምራዊ ወደ እንግዳ ማረፊያ ቤት ወስዶ ከጠበቀው በኋላ ለእንግዶች ማደረፊያ ቤት ጠባቂውሁለት ዲናር አውጥቶሰጠውና፤ “ጠብቀው፥ ከዚህ በላይ የምትከስረውን ሁሉ እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ አለው፡፡(ሉቃ.፲፥፴-፴፭) ይህ ምሳሌ ነው፡፡ በወንበዴዎች የቆሰለው ቁስለኛ፤ በኃጢአት መርዝ የተለከፈና የቆሰለ የሰው ልጅ ሁሉ ሲሆን፤ ወንበዴው ደግሞ ዲያብሎስ ነው፡፡

የአዳምን ቁስል የፈወሰው ርኁሩኁ ሳምራዊ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሲሆን፤ ይህን ቁስለኛ ያሳደረበት የእንግዶች ማረፊያ ቤት የተባለች ቤተ ክርስቲያን ናት (መዝ.፴፰፥፲፪፣ዘፍ.፵፯፥፱)፡፡ የእንግዶች ማረፊያ ቤት (የቤተ ክርስቲያን) ጠባቂዎች የተባሉት ደግሞ አባቶቻችን መምህራን ናቸው፡፡ (የሐዋ.፳፥፳፰) ራሱን በሩኅሩኁ ሳምራዊ የመሰለው ጌታችን ለቤተ ክርስቲያን መምህራን የሰጣቸው ሁለት ዲናር የተባሉት መጻሕፍተ ብሉያትና መጻሕፍተ ሐዲሳት ናቸው፡፡ ሁለቱን ዲናር ከሰጠ በኋላበነዚያ ብቻ ሳይወሰን “ከዚህም በላይ የምትከስረውን ሁሉ እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ” አለው፡፡ ይህ ቃል የሚያመለክተው በሁለቱ ዲናሮች (በብሉያትና ሐዲሳት) ተመሥርተው የረቀቀውን አጉልተው፣ የተሠወረውን ምሥጢር ገልጠው ምእመናንን የሚያስረዱ ልዩ ልዩ የትርጓሜ፣ የምክር፣ የተግሳጽ፣ የታሪክና የመሳሰሉትን መጻሕፍትን ጽፈው እንዲያስተምሩና እነዚህም ተጨማሪ መጻሕፍት በመጻፋቸው የድካማቸው ዋጋ እንደማይጠፋባቸው ሲገልጽ ነው፡፡ “እኔ ስመለስ እከፍልሃለሁ” ማለቱ በዳግም ምጽአቱ የድካማቸውን ዋጋ እንደሚከፍላቸው ያሳያል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ነገር ግን እንደምታውቁት በፊልጵስዮስ አስቀድመን መከራ ተቀበልን ተንገላታንም፥ በብዙ ገድል የእግዚአብሔርን ወንጌል ለእናንተ እንናገር ዘንድ በአምላካችን ደፈርን፡፡” (፩ኛ.ተሰ.፪፥፲፪) ብሏል፡፡ ገድል ያለው መከራውን ነው፡፡

የአዋልድ መጻሕፍት አስፈላጊነት፡-

ፍቁረ እግዚእ የተባለ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ በወንጌሉ “ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ፤” ካለ በኋላ “ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ባልበቃቸው ይመስለኛል” (ዮሐ.፳፥፴፤፳፩፥፳፭) በማለት ተናግሯል፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ ሠላሳ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ሲመላለስ ያደረጋቸው ተአምራት እያንዳንዳቸው እንዳልተመዘገቡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ በአጽንዖት አስረድቷል፡፡

በሌላ በኩል ቅዱስ ጳውሎስ “የእግዚአብሔር ሰው ፍጹምና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀ ይሆን ዘንድ፥ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበት መጽሐፍ ሁሉ ለትምህርትና ለተግሣጽ ልብንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ምክር ደግሞ ይጠቅማል።”በማለት የአዋልድ መጻሕፍት አስፈላጊነት ምን እንደሆነ ገልጦ ተናግሯል፡፡

በዚህ የተነሣ በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ እየተመሩ ቅዱሳን ነቢያትና ሐዋርያት በልዩ ልዩ ጊዜና ቦታ ሆነው መጽሐፍ ቅዱስን ሲጽፉ አዋልድ መጻሕፍትን ለትርጓሜ፣ ለምክር፣ ለተግሳጽ፣ ለታሪክ አስረጂነት እንደተጠቀሙባቸው አስረድተዋል፡፡ (ኢያ. ፲፥፲፫፤ ፩ኛ.ሳሙ .፩፥፲፰፤ ይሁ.፱)

እንግዲህ በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ከታነጽን በእነርሱ መንገድ መመራት ያሻናል፡፡ አዋልድ መጽሐፍቱ ከትምህርት ሰጪነት ባሻገርበእለት እለት ሕይወታችንለጸሎት የምንጠቀምባቸው ናቸው፡፡ በገመድ ያለ የኤሌክትሪክ ኃይል የሚፈካውና የሚታየው በአምፖል ሲበራ እንደሆነ ሁሉ በአሥራው መጻሕፍት የሚገኝ ጥበብ፣ ትምህርትና ምሥጢርም የሚረዳው የሚገለጠው በአዋልድ መጻሕፍት ተብራርቶ ሲታይ ነው፡፡

ይቆየን

 

 

 

addis yemeseraw bete

አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ገዳም

 ግንቦት 11 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

addis yemeseraw beteበሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በቀይት ወረዳ ቤተ ክህነት ሥር በጉዶ በረት አካባቢ የምትገኘውን ጥንታዊትና ታምረኛዋን ገዳም እንድንዘግብላቸው በተደጋጋሚ ቢሯችን በመምጣትና ስልክ በመደወል ቀጠሮ ያስያዙንን የርዕሰ አድባራት ወገዳማት ዳግሚት ፅዮን አዲስ ዓለም ማርያም ገዳም አስተዳዳሪ ንቡረ ዕድ አባ ገብረ ሕይወት መልሴ ጋር በነበረን ቀጠሮ መሠረት ሚያዚያ 15 ቀን 2006 ዓ.ም. ከሌሊቱ 12፡30 ወደ አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ገዳም ለመጓዝ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በር ላይ እና ላም በረት አካባቢ ከሚገኘው መናኸሪያ በር ተገናኝተናል፡፡

ሰላምታ ተለዋውጠን ንቡረ ዕድ በመስቀላቸው ባርከውን ጉዟችንን ለመቀጠል ስንዘጋጅ ንቡረ ዕድ “ጸሎት እናድርግ” አሉ፡፡ የዘውትር ጸሎት፣ የዕለቱን ውዳሴ ማርያም በማድረስ ጉዞው ተጀመረ፡፡ ሾፌራችን ኢንጂነር መኮንን ለቤተ ክርስቲያንና ለንቡረ ዕድ ካላቸው ፍቅርና አክብሮት የተነሣ ላንድ ክሩዘር መኪናቸውን ለአገልግሎት ይዘው የመጡ አባት ናቸው፡፡ በተገቢው ፍጥነትና ምቹ አነዳድ በሰሜን ሸዋ ይዘውን እየሄዱ ነው፡፡

leke lekawent astedadaryንቡረ ዕድን በረድእነት እያገለገሏቸው የሚገኙት ታናሽ ወንድማቸውን ቀሲስ እንግዳወርቅ መልሴ ድርሳናትንና ገድላትን እንዲያነቡ አዘዟቸውና እያደመጥን በየመሐሉ አቡነ ዘበሰማያት እየተሰጠን እየጸለይን ደብረ ብርሃን ከተማ የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ቤት ደረስን፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤፍሬምና ንቡረ ዕድ የፍቅርና የአክብሮት ሰላምታ ተለዋውጠው የመጡበትን ሁኔታ አስረዷቸው፡፡ ብፁዕ አቡነ ኤፍሬምም ጸሎት አድርገው እግዚአብሔር ከእናንተ ጋራ ይሁን ብለው ሸኙን፡፡ ደብረ ብርሃን ከተማ ሲጠብቁን የነበሩትን የቀይት ወረዳ ሊቀ ካህናት ቀሲስ ብርሃኑ ለገሠ እና ጸሐፊያቸውን ይዘን ጉዶ በረት ደረስን፡፡

በጉዶ በረት የሚገኙትን አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም የልማት ኮሚቴ አባላት እነ ዲ/ን ይስማን ይዘን ከጉዶ በረት በ6 ኪሎ ሜትር ርቀት ወደምትገኘው አሰግድመኝ ማርያም የአስፋልቱን መንገድ በመልቀቅ የአምስት ቀበሌ ሕዝብ ጉልበቱን ሳይቆጥብ ቆፍሮ ያስተካከለውና አሁንም አስቸጋሪ የሆውን ጥርጊያ መንገድ ተያያዝነው፡፡ ወጣ ገባውን መንገድ ለማለፍና ለመኪናችን ክብደት ለመቀነስ በእግራችን መጓዙን በመምረጥ ከመኪናው ወርደን ተከተልናቸው፡፡

አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ገዳም ስንደርስ የተመለከትነው ሰፊ ሜዳ ላይ በቆርቆሮ የተራች መቃኞ ሆና አገኘናት፡፡ ከአዲስ አበባ ስንነሳ ተነግሮን የነበረው ዋሻ ቤተ ክርስቲያን ስለነበር ግር አለን፡፡ ዋሻ ቤተ ክርስቲያኑን ከማየታችን በፊት መቃረቢያውንና አሁን በመገንባት ላይ የሚገኘውን ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን እንድንጎበኝ ተነገረን፡፡ ከመቃኞው አጠገብ መሠረቱ ከፍ በማለት ላይ የሚገኝ ጅምር ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን ይታያል፡፡ ይህንን ጅምር ቤተ ክርስቲያን በበላይነት እያስተባበሩ የሚያሠሩት ንቡረ ዕድ መሆናቸውን፤ ከትጋታቸውና የአካባቢው ምእመናን ለንቡረ ዕድ ካለው ከበሬታና ምስክርነት አንጻር ለማወቅ ችለናል፡፡ ግንበኞች ግንባታቸውን ቀጥለዋል፤ እኛም ስለ ቤተ ክርስቲያኑ መጠየቃችንን ቀጠልን፡፡

ንቡረ ዕድ አባ ገብረ ሕይወት መልሴ የገዳሙ የበላይ ጠባቂና ሌሎችም የቤተ ክርስቲያኑ አገልጋዮች ስለገዳሙ መረጃ መስጠታቸውን ቀጠሉ፡፡ ንቡረ ዕድ ርእሰ አድባራት ወገዳማት አዲስ አለም ገደምን በማስተዳደር ፣ደብረ ገሊላ አማኑኤል ቤተ ክርስቲያንን በማሠራትና በማስተዳደር፣ አሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴና አባ ሳሙኤል ገዳምን በማስተዳደርና አሁንም ከፍተኛ እገዛ በማድረግ፣ሳር አምባ ኪዳነ ምረትን በማራትና እና ሌሎች ገዳማትና አድባራትን በማደራጀትና በማቋቋም የሚታወቁ አባት ናቸው፡፡ የንቡረ ዕድ የመንፈስ ጥንካሬና ትጋታቸውን እያደነቅን ቦታውን እንዴት እንደሚያውቁት ጠየቅናቸው፡፡

“አስግድመኝ ቅድስት ማርያም ገዳምን ከሕፃንነቴ ጀምሮ አውቃታለሁ፡፡ እንደ ጻድቃኔ ማርያም ገዳም ታላቅ በረከት ያላት ቦታ ናት ፡፡ በዚህ ቦታ ሰፊ ጉባኤ ነበር፡፡ ታቦቷም ስዕለት ሰሚና ተአምረኛ መሆኗን አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን ከአስፋልት ገባ ያለና መንገዱ ለመኪና አመቺ ባለመሆኑ ምክንያት ማንም አይጎበኛትም፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙት ታላላቅ ገዳማት አንዷ ናት፡፡ የቀድሞ እውቅናዋን ለመመለስና ታሪኳ ተደብቆ መቅረት የለበትም በሚል ሀሳባችንን ለተለያዩ ሰዎች ስናካፍል እንረዳችኋለን በርቱ አሉን፡፡ ጊዜው ሲደርስ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑን ለመሥራትና ታሪኳን ለማስተዋወቅ ተነሳሳን፡፡” ይላሉ ፡፡

memera telayeመምሬ ጥላዬ በአስግድመኝ ማርያም አካባቢ ተወላጅና ለረጅም ዘመናት ታቦቷን በማገልገል የሚታወቁ የእድሜ ባለጸጋ አባት ናቸው፡፡ ስለ አሰግድመኝ ማርያም የሚያውቁትን እንዲነግሩን ጠየቅናቸው፡፡

“አሰግድመኝ ማለት በሁለት የተለያየ አቅጣጫ እየሄዱ የነበሩ ሰዎች አንድ ሰው ብቻ ማሳለፍ በሚችል ጠባብ ቦታ ላይ ተገናኙ “አሰግድመኝ” – አሳልፈኝ – አሳልፈኝ በመባባል በየተራ ያለፉበት ቦታ ስለሆነ አሰግድመኝ የሚለውን ስያሜውን እንዳገኘ ይነገራል” አሉን መምሬ ጥላዬ፡፡ ንቡረ ዕድም ቀድመው ይህንን ስያሜ ነግረውን ስለነበረ አጠናከሩልን፡፡ አብረውን ያሉ አገልጋዮችም ራሳቸውን በመነቅነቅ በአዎነታ አጸኑልን፡፡

ቀጠሉ መምሬ ጥላዬ “አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ገዳም ከተመሠረተች ከ800 ዓመታት በላይ ያስቆጠረችና ዐፄ ይኩኖ አምላክ እንደመሠረቷት ይነገራል፡፡ ዐፄ ይኩኖ አምላክ ከላስታ ወደ ተጉለት አውራጃ በመምጣት በላስታ የተጀመረውን ፍልፍል ቤተ ክርስቲያን የማነጽ እንቅስቃሴ በዚህም ተግባራዊ አድርገውታል፡፡ በፄ ይኩኖ አምላክ አማካኝነት ፀሐይ ልዳ፤ ልዳ ጊዮርጊስ፤ ብፅዐተ ጊዮርጊስ በተባሉ አባቶች የዋሻ ቤተ ክርስቲያኑ ተፈልፍሎ አገልግሎት መስጠቱን ከአባቶቻችንና ከአያቶቻችን ስንሰማ አድገናል” ይላሉ መምሬ ጥላዬ፡፡

“ለገዳሙ መተዳደሪያ ፄ ይኩኖ አምላክ ሦስት ጋሻ መሬት አንደኛው ጋሻ መሬት መዘዞ ላይ፤ ሁለተኛውን ደግሞ ሞጃና ዳራ ወረዳ ላይ፤ ሦስተኛውን መሐል ተጉለት ላይ ሰጥተው እስከ ደርግ መንግሥት ለውጥ ድረስ ለገዳሙ አገልግሎት ሲሰጥ ቆይቷል” አሉን መምሬ ጥላዬ፡፡

የቀይት ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህናት ቀሲስ ብርሃኑ ለገሠ ስለ አሰግድመኝ ማርያም ከተለያዩ መረጃ ምንጮች እንዲሁም ከአባቶች የተረዱትን ሲያጫወቱን፡፡ “አሰግድመኝ ቅድስት ማርያምናkeyet wereda ወንበሮ ኪዳነ ምሕረት በአንድ አቅራቢያ የሚገኙ አድባራት በመሆናቸው አንድ ላይ አገልግሎት ይሰጥባቸው ነበር፡፡ በተለይ በወንበሮ ኪዳነ ምሕረት በርካታ የአብነት ተማሪዎችና መሪ ጌቶች ይገኙ ነበር፡፡ በዚህ ሥፍራም የንባብና የዜማ ትምህርት ሲሰጥበት የቆየ ሲሆን ዛሬም የአገልጋዮቹ ቁጥር ቢቀንስም አገልግሎት እየተሰጠበት ነው፡፡ ድሮ አባቶች አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ቀድሰው እዚያው መክፈልት አይቀምሱም ነበር፡፡ ለቦታው ካላቸው አክብሮት የተነሣ በገዳሙ ዙሪያ ምግብ ስለማይበላ ከቅደሴ መልስ ወንበሮ ኪዳነ ምሕረት እየሄዱ ነበር ምግብ የሚቀምሱት፡፡”

“ገዳሙ ከተመሠረተ በኋላ የፄ ይኩኖ አምላክ ታናሽ ወንድም አባ ሂሩተ አምላክ በምእራብ ጎጃም ዳጋ እስጢፋኖስን ያስተዳድሩ ስለነበር በሀገር እና በህዝቡ ላይ ረሃብ፣ ቸነፈርና ጦርነት ሲከሰት ወደ አሰግድመኝ ማርያም በመምጣት ጸሎት ያደርሱ ነበር፡፡ የመጣውም መቅሰፍት በእመቤታችን ምልጃ በምረት ይመለስ ነበር” አሉን ሊቀ ካህናት፡፡ ሌላም ታሪክ ይነግሩን እንደሆነ ለመረዳት ሌላስ? አልናቸው፡፡

“በ14ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የነበሩት ፄ ዘርዓ ያዕቆብ ወደ ጻድቃኔ ማርያም ሲሔዱና ሲመለሱ በአሰግድመኝ ቅድስት ማርያም እረፍት አድርገው ይሄዱ እንደነበር ይነገራል፡፡ እረፍት ያደርጉበት የነበረው ጠፍጣፋ ድንጋይም በአሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እስከ ቅርብ ዘመን ድረስ ነበር፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ታሪክ ከፍተኛ ግፍና ጭካኔ በመፈጸም ቀሳውስቱን በማረድ፤ አብያተ ክርስቲያናትን በማቀጠል ከፍተኛ ውድመት ያደረሰው አሕመድ ግራኝ ወደ አካባቢው ሲመጣ ጉልላት ያላቸውንና በግልጽ የሚታዩትን አብያተ ክርስቲያናት ሲያቃጥል አሰግድመኝ ቅድስት ማርያም ገዳም ግን ጉልላት ስላልነበራትና ሊደርስበትም ስላልቻለ ምንም አይነት ዝርፊያና ቃጠሎ ሳይደርሰባት ድናለች” በማለት በዝርዝር አጫወቱን፡፡

የዋሻውን ቤተ ክርስቲያን ማየት ጓጓንና ንቡረ ዕድን ዋሻው ወዴት ነው? አልናቸው፡፡ ንቡረ ዕድም “ እኔ ቁልቁለቱን መውረድ፤ ዳገቱን መውጣት ስለሚያዳግተኝ ካህናቱ ያሳይዋችሁ” ስላሉን ልብሰ ተክህኖ የለበሱና ሌሎች ምእመናን ወደ ዋሻው ይዘውን ሄዱ፡፡

ይቀጥላል

 

seno 2006

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልኣተ ጉባኤ የ2006 ዓ.ም. ሁለተኛ መደበኛ ጉባኤ ተጀመረ

ግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

  • ለቤተ ክርስቲያን አይደለም ለራሱ እንኳን በአግባቡ መቆም ያልቻለ የሰው ኃይል ይዘን የትም መድረስ አንችልም / ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ/

seno 2006የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የግንቦቱ ርክበ ካህናት ሁለተኛ መደበኛ ጉባኤ ግንቦት 5 ቀን 2006 ዓ.ም. በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በጸሎት ተጀምሯል፡፡ ግንቦት 6 ቀን 2006 ዓ.ም. በቅዱስ ፓትርያርኩ የመክፈቻ መልእክት ጉባኤው ቀጥሏል፡፡

ብፀዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃማኖት ለቅዱስ ሲኖዶስ ባስተላለፉት መልእክት “ ወንጌልን ለዓለም የማድረስ ተልእኮ የኛ የሊቃነ ጳጳሳቱ እስከሆነ ከሁሉም ዘንድ ለመድረስ ጠንክሮ መሮጥ የኛ ግዴታ ነው፤ ሆኖም ሩጫው እንቅፋት አጋጥሞት ለጉዳት እንዳይዳርገን ቅዱስ ጳውሎስ እንዳስተማረን ትዕግስትና ማስተዋል ያልተለየው ሊሆን ይገባል፡፡ ትዕግስትንና ማስተዋልን ገንዘብ አድርጎ ሥራን መሥራት ትልቅ ጥበብ እንጂ ቸልተኝነት አይደለም፤ ሃይማኖት የሚጠበቀው ድኅነትም የሚገኘው በትዕግስት እንደሆነ ራሱ ባለቤቱ “በትዕግስትክሙ ታጠርይዋ ለነፍስክሙ” በማለት አስተምሮናል” ብለዋል፡፡

 

a holy syno 2006
ቅዱስነታቸው ባለፈው ዓመት ርክበ ካህናት ጉባኤ ላይ ቅዱስ ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያን መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን፤ ብልሹ አሰራር እንዲታረም፤ ቤተ ክርስስቲያን ልዕልናዋን፤ ክብሯን፤ ንፅሕናዋንና ቅድስናዋን ጠብቃ እንድትቀጥል የሚያስችሉ ውሳኔዎችን አሳልፎ እንደነበርም አስታውሰዋል፡፡ ውሳኔዎቹም በጥናት ተመሥርተው በተግባር ይተረጎሙ ዘንድ ልዩ ልዩ ኮሚቴዎች መቋቋማቸውን ጠቅሰው፤ ኮሚቴዎቹ የመጀመሪያ ዙር ጥናታቸውን ለጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አቅርበው እንዲታይ ተደርጓል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ነገር ግን ጥናቶቹ በሊቃውንትና በባለሙያዎች እየታገዙ የቀጠሉ ቢሆንም በሥራው ሂደት በመጠኑም ቢሆን መሰናክሎች እንደነበሩና ቋሚ ሲኖዶስ በሚያደርገው ክትትልና በሚሰጠው አመራር መልክ እያያዙ በመምጣታቸው ሥራዎች እየተሰሩ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡ በማዕከል የተቋቋመው ኮሚቴና ለአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ደንብ አጥኚ ተብሎ በድጋሚ የተሰየመው ኮሚቴም በአንድነት ለመሥራት ያሳዩት ተነሳሽነት፤ ጥራትና ቅልጥፍና ተስፋ የሚሰጥ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡

“በቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር ላይ የሚታየው ክፍተት ሥር የሰደደ ከመሆኑ አንጻር በአጭር ጊዜ ውስጥ ይስተካከላል የሚል እምነት ብዙ ላይኖረን ይችላል” ያሉት ቅዱስነታቸው ይሁንና በጀመርነው መስመር ከቀጠልን ሩቅ በማይባል ጊዜ ውስጥ ለውጦችን ማየት እንደምንችል ጥርጥር የለንም ሲሉ ገልጸዋል፡፡

መልካም አስተዳደርን በፍጥነት ለማስፈን “በየአቅጫው ለሚነፍሱ የውጭ ነፋሳት የማይበገር አንድነት፤ ሕግ ቤተ ክርስቲያንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ብቻ ማእከል አድርጎ መሥራት፤ በእናውቅላችኋለን ባዮች ግራ ሳይጋቡ በራስ በመተማመን መወሰን፤ የቅዱስ ሲኖዶስ ሉዓላዊ ሥልጣን በማንም ይሁን በማን እንዳይገሰስ ጥብቅና መቆም የመሳሰሉ ባሕርያት ለዚህ ጉባኤ አስፈላጊ መሳሪያዎች ናቸው” ብለዋል፡፡

ቅዱስነታቸው ቤተ ክርስቲያን ያላትን የሰው ኃይል እንደሌላው ዓለም አጠቃቀም ብንጠቀምበት ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለዓለም ሁሉ ይበቃ እንደነበር ጠቁመው፤ የሰው ኃይልን በእውቀት አምልቶ ክፍተቱን ከመሙላት ይልቅ ከመቶ ዓመት በፊት የነበሩት አስገዳጅ ሁኔታዎች ያመጡብንን የዘመናት ልምዶች እንደመልካም ባህል ይዘን በዚያው በመቀጠላችን ክፍተቱ ተፈጥሯል የሚል እምነት እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡
“ለቤተ ክርስቲያን አይደለም ለራሱ እንኳን በአግባቡ መቆም ያልቻለ የሰው ኃይል ይዘን የትም መድረስ አንችልም፤ ሆኖም ይህን ችግር ለማስተካከል ያለውን በማፍለስ ሌላ አዲስ ተክልን መትከል ሳይሆን ያለውን የሰው ኃይል ማስተካከል እንዳለብን ሊሰመርበት ይገባል” ብለዋል፡፡

በዓለም ላይ የሚገኙ ካህናት ብዛት በአጠቃላይ ቢበዛ ከሁለት ሚሊዮን ላይበልጥ ይችላል፤ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያናችን ከግማሽ ሚሊዮን ካህናት በላይ ይዛ ለምን ብዙ የሥራ ክፍተቶች ይከሰታሉ የሚለውን ጥያቄ ቅዱስ ሲኖዶስ በውል ሊያጤነው እንደሚገባም አሳስበዋል፡፡

ቅዱስነታቸው ልማትን አስመልክቶ ሲናገሩም “ቤተ ክርስቲያናችን የልማት በረከቱ ባለበት ብቻ እንዲቀጥል ሳይሆን ካለበት በበለጠ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሕዝቡን በማስተማር ለልማቱና ለእድገቱ በሰፊው መንቀሳቀስ አለባት፤ የተለመደውን ሀገራዊ ሓላፊነቷንም መወጣት አለባት” ሲሉ አሳስበዋል፡፡

“ቤተ ክርስቲያናችን ለዚህች ሀገር አንድነት መጠበቅና ለሕልውናዋ ቀጣይነት ለሦስት ሺሕ ዘመናት ያህል የሰራችው ጉልህና ደማቅ ሥራ አሁንም መድገም አለባት፡፡ ቤተ ክርስተያናቸችን ዛሬም እንደቀድሞው ሃይማኖታዊና ልማታዊ ሥራን በመሥራት የመሪነት ሚናዋን የምታጠናክርበት አቅጣጫ ይህ ጉባኤ መቀየስ አለበት” በማለት ቅዱስነታቸው መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡