tena gedamate

ማኅበረ ቅዱሳን የአልባሳት ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር አዘጋጀ

ታኅሣሥ 18 ቀን 2006 ዓ.ም.

በታመነ ተ/ዮሐንስ

tena gedamateበኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን ‹‹የአብነት መምህራንና ተማሪዎችን ጤና ለመጠበቅ›› በሚል ከታኅሣሥ 1 እስከ ጥር 6 ቀን 2006 ዓ.ም ድረስ የሚቆይ መርሐ ግብር አዘጋጀ፡፡

የማኅበሩ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል በሥሩ የአብነት ትምህርት ቤቶች ማጠናከሪያና ማቋቋሚያ መርሐ ግብርን ነድፎ በሁሉም አኅጉረ ስብከት በመቶ ሰባ ሁለት የአብነት ትምህርት ቤቶች ላይ ተግባራዊ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ የአብነት ት/ቤቶች እየገጠሟቸው ካለው የገንዘብ፣ የቀለብ፣ የአልባሳት፣… ችግሮች ጎን ለጎን በጤና መስኩ ያለው ተግዳሮት ጊዜ የማይሰጥ ሆኖ በመገኘቱ ይህ መርሐ ግብር ለሁለተኛ ጊዜ ሊዘጋጅ ችሏል፡፡

የጤና ችግሩ ከመምህራን አኳያ ሲታይ ምትክ የማይገኝላቸውንና በጽሑፍ ያልሰፈሩ መንፈሳዊ ዕውቀቶችን የያዙ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን እየነጠቀ ያለ ሲሆን፤ በአብነት ተማሪዎች አንጻር ከታየ ደግሞ የሚገዳደረውን ዘመናዊነት ተቋቁመው የነገ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ለመሆን የሚያደርጉትን ተጋድሎ ይበልጥ ፈተና ውስጥ የሚጥል እየሆነ ይገኛል፡፡ ከምንም በላይ የዚህ ችግር ዋነኛ ሰለባ የሚሆኑት ተማሪዎች ሲሆኑ ለዚህም ተጠቃሽ የሚሆነው ምክንያት የመኖሪያና የመማሪያ አካባቢያቸው የተፋፈገ በመሆኑ በበሽታ ተሸካሚ ነፍሳት፣ በትንፋሽና መሰል በሆኑ መንገዶች ለተለያዩ በሽታዎችና ወረርሽኞች ይጋለጣሉ፡፡

የአገልግሎት ክፍሉ ከሚሰጠው ልማት ላይ ያተኮረ የመካናት ድጋፍ በተጨማሪ ማኅበረሰቡ ውስጥ ባለው ሰፊ የማኅበራዊ አገልግሎት ድርሻ ምክንያት ይህንን መርሐ ግብር በድጋሚ ሊያዘጋጅ በቅቷል፡፡ በዚህም መሠረት ሕዝበ ክርስቲያኑ፣ በጎ አድራጊ ድርጅቶችና ግለሰቦች የተለያዩ የንጽሕና መጠበቂያ ቁሳቁስሶችን ማለትም እንደ ሳሙና፣ የውኃ ጀሪካን፣ የልብስ ማጠቢያ…እንዲሁም የተለያዩ አልባሳትን በመደገፍ ክርስቲያናዊ ርኅራኄውን ያሳይ ዘንድ ማኅበሩ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡ በዚህ መርሐ ግብር ከ10,000 በላይ ተማሪዎችን ለመታደግ የሚያስችሉ ቁሳቁሶችን ለማሰባሰብ ታቅዷል፡፡

ያመኑትም ሕዝብ አንድ ልብ አንዲትም ነፍስ ነበሩአቸው

ትኅሣሥ 17 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

tsreha tsion 2በማኅበረ ቅዱሳን የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል መደበኛና ኢ-መደበኛ አባላት በአገልግሎት ዙሪያ ለመወያየትና ከጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ የአንድነት ኑሮ ማኅበር አባላት ጋር የልምድ ልውውጥ ለማድረግ እንዲቻል ከአዲስ አበባ በምዕራብ አቅጣጫ ቡራዩ አካባቢ ወደሚገኘው ጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ የአንድነት ኑሮ ማኅበር መንደር ታኅሣሥ 12 ቀን 2006 ዓ.ም. የጉዞ መርሐ ግብር አካሒዷል፡፡

አባላቱ አንድ የማኅበረ ቅዱሳን አገልጋይ በተከራየላቸው መለስተኛ አውቶብስ (ሃይገር ባስ) በመሳፈር ከ45 ደቂቃ ጉዞ በኋላ ከረፋዱ 5፡00 ሰዓት ላይ የጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ የአንድነት ኑሮ ማኅበር ደረስን፡፡ በማኅበሩ አባላት በመሠራት ላይ የሚገኘውን የጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን እየተሳለምንና በነፋሻማው አየር እየታገዝን ወደ ውስጥ ዘለቅን፡፡ ግቢው በተለያዩ አጸዶች ተውቧል፡፡ ነፍስ ምግቧን ታገኝ ዘንድ ትክክለኛው ሥፍራ በመሆኑ የነፍሳችንን ረሃብ ለማስታገሥ ቸኩለናል፡፡ የአባቶችን ቡራኬ ተቀብለን አጭር የግል ጸሎታችንን አድርሰን ለጉብኝቱ ተዘጋጀን፡፡ ጉብኝቱ የተጀመረው ስለ ጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ የአንድነት ኑሮ ማኅበር አመሠራረት ዲያቆን ደቅስዮስ ገለጻ በማድረግ ነበር፡፡

የጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ የአንድነት ኑሮ ማኅበር አመሠራረት

የማኅበሩ መሠረት ሰንበት ትምህርት ቤት ነው፡፡ 1980 ዓ.ም. መጀመሪያ አዲስ አበባ ውስጥ በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ሰንበት ትምህርት ቤቶች መናፍቃን ሰርገው በመግባት የራሳቸውን ዓላማ ለማስፈጸም ጥረት ያደረጉበት ወቅት ነበር፡፡ ጉዳዩ ያሳሰባቸው የሰንበት ትምህርት ቤቶች ተወካዮችና አባላት በመመካከር የጋራ ጉባኤ ሊኖር እንደሚገባ ውሳኔ ላይ ተደረሰ፡፡ ነገር ግን በወቅቱ የነበረው የደርግ መንግስት እንቅስቃሴ ስላሰጋው እንዲዘጋ አደረገው፡፡

የወጣቶቹን እንቅስቃሴ ደርግ ቢዘጋውም የተወሰኑ የሰንበት ትምህርት ቤት አመራሮች በመሰባሰብ “ማኅበረ ደብረ ዘይት” በሚል ስም ማኅበር አቋቋሙ፡፡ በማኅበረ ደብረ ዘይት ሥርም “አሠረ ሐዋርያት” በሚል ከሰንበት ትምህርት ቤቶች የተውጣጣ ማኅበር ተቋቁሞ ቆይቶ ጠንካራ አገልግሎትን ለመፈጸም “በአንድነት ለምን አንኖርም? ለምን ቋሚ የሆነ ቦታ አይኖረንም?” በሚል ተነሳስተው፤ ፕሮጀክት በመቅረጽ እና ሕጋዊ ሰውነት እንዲኖረው በማድረግ በ1980 ዓ.ም. በአንድነት ለመኖር ለከተማና ቤት ሚኒስቴር ጥያቄያቸውን በማቅረብ ሕጋዊ ሰውነት አገኝቶ 41‚000 ካሬ ሜትር ስፋት ያለው መሬት ተሰጣቸው፡፡

tsreha tsion 3ማኅበሩ ዓላማዬ ብሎ የተነሳው አባላቱ ያላቸውን ሥጋዊና መንፈሳዊ ሀብት በማዋሀድ እርስ በእርስ በመረዳዳትና በመደጋገፍ በሰላምና በፍቅር በአንድነት በመኖር ለኅብረተሰቡ አርአያና ምሳሌ ለመሆን፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት በሚደረገው አገልግሎት ለቤተ ክርስቲያን እድገትና ልማት አቅም በፈቀደ ሁሉ አስተዋጽኦ ለማበርከት፤ ለኅብረተሰቡ አርኣያ ለመሆን ወዘተ የሚሉ ናቸው፡፡

የአንድነት ኑሮው በተቀናጀና በተጠናከረ ሁኔታ የሚመራ ሲሆን፤ አባላቱ በተለያዩ የሥራ መስኮች በመሠማራት በየወሩ ሰርተው የሚያገኙትን ገንዘብ ለማኅበሩ በማስረከብ፤ ማእድ በየቀኑ በአንድነት በመመገብና በአንድነት በመጸለይ የአንድነት ኑሯቸውን ይመራሉ፡፡ የእኔ የሚሉት ንብረትም ሆነ ሐብት የሌላቸው ሲሆን እርስ በእርስ በመረዳዳትና በመደጋገፍ ከራሳቸው አልፈው አቅመ ደካሞችን በመደገፍ የበጎ አድራጎት ተግባር በመፈጸም ራሳቸውን ለእግዚአብሔር አሳልፈው በመስጠት ሕይወታቸውን ይመራሉ፡፡“ያመኑትም ሁሉ አንድ ልብና አንዲት ነፍስ ሆነው ገንዘብ ይኖሩ ነበር፡፡ በውስጣቸውም የሁሉ ገንዘብ በአንድነት ነበር እንጂ ይህ የኔ ገንዘብ ነው የሚል አልነበረም፡፡ . . . እነርሱም ለእያንዳንዱ እንደፍላጎቱ ይከፍሉት ነበር፡፡” ሐዋ.ሥራ 4፡32-37 ላይ ያነበቡትን ህይወት መረጡ፡፡

ዓላማውንም ለማሳካት በአንድነት በመኖር፤በ1984 ዓ.ም. በዘጠኝ አባላት በግቢው ውስጥ የተወሰኑ መኖሪያ ቤቶችን በመገንባት የአንድነት ኑሮው ተጀመረ፡፡ በአሁኑ ወቅት 22 አባወራች በግቢው ውስጥ ሲኖሩ በአጠቃላይ 150 የሚደርሱ ሰዎች ይኖራሉ፡፡ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት በመሰማራት፤ በስነጽሑፍና ኅትመት አገልግሎት በመሳተፍ፤ ሰባኪያነ ወንጌልን በማሰልጠን አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡

ለልጆቻቸው መማሪያ የሚሆን ትምህርት ቤት ባለመኖሩ በግቢው ውስጥ መዋዕለ ሕፃናት ትምህርት ቤት በመክፈት ሥራውን የጀመረው ትምህርት ቤት እስከ 8ኛ ክፍል በማድረስ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል፡፡ በትምህርት ቤቱ ውስጥ በአነስተኛ ክፍያ፤ እንዲሁም በአካባቢው የሚገኙ እናት አባት የሌላቸው፤ አቅመ ደካማ ለሆኑ ቤተሰቦች ልጆቻቸውን የትምህርት ቁሳቁስንና ልብሳቸውን በመቻል በነጻ ያስተምራል፡፡ በጎ አድራጊ ምእመናን በሚሰጡት ገንዘብ አማካይነት ማኅበሩ እገዛ ያደርጋል፡፡፡ በቅርቡም አንድ በጎ አድራጊ በለገሱት ገንዘብ አቅም ለሌላቸው ልጆች የቁርስና የምሳ አገልግሎት መስጠት ጀምሯል፡፡ ትምህርት ቤቱንም ወደ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤትነት ለማሳደግ ማኅበሩ ጥረት በማድረግ ላይ ነው፡፡

በልማት ዘርፍ የጓሮ አትክልት በመትከል፤ የወተት ላሞችን በማርባትና ወተቱን ለልጆቻቸው በመጠቀምና በመሸጥ፤ የኦቾሎኒ ቅቤ “ጽዮን ኦቾሎኒ” የተሰኘ በማዘጋጀትና ለገበያ ያቀርባል፡፡

ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት የመለከት መጽሔትን በማዘጋጀት በሚገኘው ገቢ የልማት ሥራዎችን በመሥራትና ከበጎ አድራጊ ምእመናን በሚገኝ ድጋፍ አገልግሎት ይሰጣል፡፡ ከ1990 ዓ.ም. ጀምሮም የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ለመስጠት በመወሰን ከተለያዩ የኢትዮጵያ ጠረፋማና የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በአገልጋዮች እጥረት ምክንያት ከማይሰጥባቸው አካባቢዎች አገልጋዮችን በመመልመል፤ ከአኅጉረ ስብከት ጋር በመሥራት ሙሉ ወጪያቸውን በመቻል በበጋ ለሦስት ወራትና ከዚያም በላይ በክረምት ስልጠና መስጠት የጀመረው ማኅበሩ፤ ቤተ ክርስቲያንን በስብከተ ወንጌል ዙሪያ የሚታየውን ክፍተት ለመሙላት ተግቶ እየሠራ ይገኛል፡፡ እስከ 2005 ዓ.ም. ከተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች የተውጣጡ 800 ሰልጣኖችን በስብከተ ወንጌል አገልግሎት አሰልጥኖ ወደ ገጠሪቱ ኢትዮጵያ አሰማርቷል፡፡

ከተለያዩ በጎ አድራጊ ምእመናን በሚያገኘው ድጋፍም ባለ ሁለት ፎቅ ሕንጻ በመገንባት 120 ሰልጣኞችን ማስተናገድ የሚችል መኝታ ቤት፤ መማሪያ ክፍሎች፤ ቤተ መጻሕፍት፤ መመገቢያ አዳራሽና የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስጫ ሁለገብ አዳራሽ በመሥራት ለአገልግሎት አውሏል፤ በአሁኑ ጊዜም 60 ሰልጣኞችን በአንድ ጊዜ እየተቀበለ ያሰለጥናል፤ ቀሪው 60 ሰልጣኞችን ለመቀበል ሕንፃውን በማጠናቀቅ ላይ ሲሆን ለሰልጣኞች የሚሆን የመኝታ ቁሳቁስ ለማሟላት ጥረት በማድረግ ላይ ነው፡፡

ብፀዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የማኅበሩን የአገልግሎት እንቅስቃሴ ለመጎብኘት በመጡበት ወቅት በግቢው ውስጥ ቤተ ክርስቲያን እንዲሠሩ በመፍቀድ ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ በነበሩበት ዘመን የመሠረት ድንጋይ በማኖር፤ የጽርሐ ጽዮን ዘተዋሕዶ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በመቃኞ ተሠርቶ አገልግሎት በመሥጠት ላይ ይገኛል፡፡ አገልግሎቱንም ለማስፋት እንዲቻል አዲስ የቤተ ክርስቲያን ሕንፃ በመገንባት ላይ ነው፡፡

ማኅበሩ ዘርፈ ብዙ ተግባራትን በማከናወን ቤተ ክርስተያንን በማገልገል ላይ ሲሆን በየዓመቱ የበዓለ ጰራቅሊጦስ ዕለት የማኅበሩን አገልግሎት የሚደግፉ ምእመናንን በማሰባሰብ የእግር ጉዞ በማድረግ የገቢ ማሰባበስብ ሥራውን ያከናውናሉ፡፡ ዲያቆን ደቅስዮስ የተረከልንን በዓይናችን አየነው፡፡

tsreha tsion 6ማኅበሩ እያከናወናቸው የሚገኙ የልማት ሥራዎችን፤ በግቢው ውስጥ የሚገኙ ቤቶችን ፣ የአፀደ ሕፃናት ትምህርት ቤቱን፤ የማኅበሩ አባላት በ1985 ዓ.ም. ወደዚህ ቦታ ተመርተው ሲመጡ ልጆቻቸውን ለማስተማር አንድ ክፍል ሠርተው የአጸደ ሕፃናት ትምህርት ማስተማር እንደጀመሩ በቀጣይነትም ትምህርት ቤቱን ወደ አንደኛ ደረጃ በማሳደግ ተጨማሪ ክፍሎችን በመሥራት በአካባቢው የሚገኙትን እናት አባት የሌላቸውን፤ በችግር ውስጥ የሚገኙትን በመለየትና በነጻ በማስተማር እንዲሁም በአነስተኛ ክፍያ እየከፈሉ ሌሎችም እንዲማሩ ለማድረግ ያላቸውን ዝግጅትሁሉ ጎበኘን፡፡

ትምህርት ቤቱን ጎብኝተን እንዳጠናቀቅን ቀድሞ ቤተ ክርስቲያኑ ከመሠራቱ በፊት የአንድነት ጸሎት የሚያደርሱበት ወደነበረው አነስተኛ አዳራሽ አመራን፡፡ አዳራሹ በንጽሕና እንደተጠበቀ ወንበሮችና ጠረጴዛዎች በአግባቡ በሁለት ረድፍ ቦታ ቦታ ይዘዋል፡፡ ከፊት ለፊት ሥዕለ ማርያም ተሰቅሏል፡፡ ቀና ብለን ግድግዳውን ስንመለከት በቁጥር በርከት ያሉ ፎቶ ግራፎች ግድግዳው ላይ በረድፍ ተሰቅለዋል፡፡ ማንነታቸውንና ለምን እንደተሰቀሉ ጠየቅን፡፡ ዲያቆን ደቅስዮስ በማይሰለች አንደበቱ አንድ በአንድ ማስረዳቱን ቀጠለ፡፡

“እነዚህ አባቶች የዚህ የአንድነት ማኅበሩ ባለ ውለታዎች ናቸው፡፡ እዚህ ፎቶግራፋቸውን የሰቀለንበት ምክንያት ለማኅበሩ ከነበራቸው ፍቅርና የአገልግሎት ድርሻ ከፍተኛውን ሥፍራ የነበራቸው በመሆናቸው ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በዚህ ዓለም በሕይወት አይገኙም፡፡ እግዚአብሔር በፈቀደ ጊዜ ወደራሱ ጠርቷቸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት እናስባቸዋለን፡፡” በማለት ካስረዱን በኋላ ወደ እያንዳንዱ ፎቶ ግራፍ እየጠቆሙ ማንነታቸውን ይነግሩን ጀመር፡፡

ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ /አባ ወልደ ንሣይ/ ማኅበሩን በጸሎት በማሰብና በመጎብኘት አባታዊ ምክራቸውን በመለገስ፤ አባ ገብረ ሥላሴ ተድላ ባዕድ አምልኮን በመቃወምና በማስተማር ይተጉ የነበሩ፤ ሊቀ ጉባኤ አበራ በቀለ በጸሎትና በምክር፤ አባ ይትባረክ፤ አባ ጴጥሮስ፤ መምህር ግርማ ከበደ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ያደረገ፤ ዲያቆን ረዳ ውቤና ሌሎችንም አባቶች የቤተ ክርስቲያንና የዚህ አንድነት ኑሮ ማኅበር ባለውለታ መሆናቸውን ነገሩን፡፡ ከአዳራሹ ወጥተን የወተት ላሞች ማደሪያንና የብሎኬት ማምረቻ፤ የጓሮ አትክልት ሥፍራዎችን ጎብኝተን ለውይይት ወደ ተመረጠልን አዳራሽ አመራን ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የሚዲያ ክፍል አገልግሎት ላይ የሚስተዋሉ ክፍተቶችን ለመሙላት እና ጠንካራ ጎኖችን ለማበልጸግ እንዲቻል፤ የተሻለ አገልግሎት በጥራትና በብቃት ለመስጥት የተለያዩ አሳቦች ተነሥተው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ ወደፊት ማኅበሩ በሚዲያ ዘርፍ ሊያከናውናቸው የታሰቡትንና አሁን በመሠራት ላይ የሚገኙትን ተግባራት እንቅፋት የሆኑ ጉዳዮችም ትኩረት ተሰጥቶባቸዋል፡፡ ለቤተ ክርስቲያን የተሻለ አገልግሎት መስጠት እንዲቻል በጋራና በመደጋፍ መሥራት እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡

 

 

gebra felp 1

ግብረ ፊልጶስ ሲምፖዚየም ተካሄደ

 ታኅሣሥ 16 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ መርሐ ግብር “ግብረ ፊልጶስ” የተሰኘ ሲምፖዚየም ታኅሣሥ 12 እና 13 ቀን 2006 ዓ.ም. በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ግቢ ውስጥ አካሄደ፡፡

gebra felp 1ታኅሣሥ 12 በብፁዕ አባታችን አቡነ ማትያስ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የካናዳና አካባቢው ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በጸሎት የተከፈተ ሲሆን፤ በመርሐ ግብሩ ላይ ከተለያዩ የኢትዮጵያ ጠረፋማ አካባቢዎች ከደቡብ ኦሞና ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ወረዳዎች ተጋብዘው የመጡ ከዚህ በፊት በሀገረ ስብከቱና በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ በጋራ ተምረውና ተጠምቀው የነበሩ አገልጋዮችና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

መጋቢ ሐዲስ እሸቱ አለማየሁ “ስለ ወንጌል ሁሉን አደርጋለሁ” በሚል ርዕስ ትምህርት በመስጠት ምዕመናን በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ውስጥ የየድርሻቸውን እንዲያበረክቱ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ከጠረፋማ አካባቢ የመጡት ምእመናን የሥላሴን ልጅነት በጥምቀት ያገኙ በመሆናቸው በአካባቢያቸው ስላለው የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ምን እንደሚመስል ተጠይቀው ሲመልሱ፡- “ማኅበረ ቅዱሳን በአካባቢያችን ከፍተኛ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በመስጠት ባለፈው ዓመት ብቻ ከ3700 በላይ ምእመናን የጥምቀት አገልግሎት አግኝተናል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ወደ አካባቢያችን በመምጣት ከጨለማ ወደ ብርሃን አውጥቶናል፡፡ ማኅበሩ በቀጣይነትም በቋንቋችን የሚያስተምሩ አገልጋዮችን እንዲያሰለጥንልን እንፈልጋለን፡፡ በአካባቢያችን የተለያዩ የእምነት ድርጅቶቸ በመግባት የቀደሙት አባቶቻችን ሃይማኖት የሆነውን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶን ቤተ ክርስቲያን እንዳንከተል ከፍተኛ ግፊት እያደረጉብን ነው” ብለዋል፡፡

“የኦርቶዶክስ እምነት ጥንት የቀረ ነው፤ ማስተማር አትችሉም በማለት ከፍተኛ ስቃይ እያደረሱብን ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ስለሌለን በድንጋይ ላይ ቁጭ ብለን ነው የምንማረው፡፡ በደቡብ ኦሞ ኣሬ ወረዳ ብቻ በቅርቡ ከ800 በላይ ወገኖቻችን ጥምቀትን ያገኙ ሲሆን 365 ከሚሽን የተመለሱ፤ 200 ደግሞ ሃይማኖት አልነበራቸውም” በማለት በአካባቢያቸው ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ገልጸዋል፡፡

ምን ትፈልጋላችሁ?` ተብለው ከብፁዕ አባታችን አቡነ ማትያስ ለተጠየቁት ጥያቄ ሲመልሱም፡-

gebra felp 2“ቤተ ክርስቲያን ያስፈልገናል፤ ምዕመናንን የምናስተምርበት ማሰልጠኛ የለንም፤ ተተኪ አገልጋዮችን በቋንቋችን እንዲያስተምሩን ሥልጠና የሚሰጥልን እንፈልጋለን፤ ወጣቶችን የምናስተምርበት ሰንበት ትምህርት ቤት የለንም፤ ሰው ወደ ሃይማኖታችን አምኖ ከመጣ ማስተማር ይጠበቅብናል፤ ካልተማሩ ለምን መጣን ብለው ጥያቄ ያነሱብናል፡፡ ስለዚህ መምህራንና አገልጋዮች ያስፈልጉናል፡፡ በመምህራን እጥረት እጅግ ተጠምተናል፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶቻችን የምንከባከብበት ቁሳቁስ ያስፈልገናል፤ ምዕመናን ከፕሮቴስታንት ሃይማኖት ተመልሰው መጠመቅ ይፈልጋሉ፤ ነገር ግን ከሥራ እንባረራለን ብለው ይሰጋሉ፡፡ ስለዚህ አይዟችሁ የሚለንና የሚያስተምረን ብናገኝ ሁሉም ለመጠመቅ ዝግጁ ነው” በማለት ጥየቄያቸውን አቅርበዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን ስብከተ ወንጌል ማስተባበሪያ የትግበራ ከፍተኛ ባለሙያ መምህር ቀሲስ ይግዛው መኮንን የማኅበሩን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት አስመልከቶ ገለጻ አድርገዋል፡፡ በገለጻቸውም “ግልገል በለስ አካባቢ ምእመናን ዛሬም ተዘጋጅተው እንድናጠምቃቸው እየተማጸኑ ሲሆን ከ2100 በላይ ምእመናን ዛሬም የእኛን አገልግሎት እየጠበቁ ይገኛሉ፡፡ ምእመናን ጠረፋማ አካባቢ ሄደን ስናጠምቅ እዚህ ያለው ምእመን የክርስትና አባትና እናት መሆን ይጠበቅበታል፤ ከረዩ ላይ ሄደን ስናጠምቅ የናዝሬት ሕዝብ ተከትሎን ሄዶ ነጠላና የአንገት መስቀል በመግዛት የክርስትና አባትና እናት ሆኖ መጥቷል፡፡ ስለዚህ እኛ ስናጠምቅ እናንተ ምእመናን ከጎናችን ሆናችሁ እንድትከተሉን እንፈልጋለን፡፡

በመጨረሻም በብፁዕ አቡነ ማትያስ ቡራኬ የመጀመሪያው ቀን መርሐ ግብር የተጠናቀቀ ሲሆን “እንዲህ ዓይነት የተቀደሰ ተግባር ማኅበሩ ሲያከናውን በማየቴ ተደስቻለሁ፤ ወደ ሀገረ ስብከቴ ካናዳ ስመለስ በዚያ የሚኖሩ ልጆቼን አስተባብራለሁ፡፡ ሓላፊነቴንም እወጣለሁ” ብለዋል፡፡

እሑድ በተካሄደው የሁለተኛ ቀን መርሐ ግብርም በርካታ ምእመናንና ከደቡብ ኦሞ፤ እንዲሁም ቤንሻንጉል ጉሙዝ የተጋበዙ ምእመናንና አገልጋዮች የተገኙ ሲሆን፤ ሐዋርያዊ ተልእኮ በኢትዮጵያ በቀድሞው፣ በመካከለኛውና በአሁኑ ዘመን ያለውን ሁኔታ የሚዳስስ ጥናታዊ ጽሑፍ በዲያቆን ያረጋል አበጋዝ ቀርቧል፡፡

ዲያቆን ያረጋል ባቀረቡት ጥናትም የቤተ ክርስቲያናችን ስብከተ ወንጌል አገልግሎት በአሁኑ ሰዓት በሚጠበቀው መልኩ እየተከናወነ ባለመሆኑ ቤተ ክርስቲያናችን ልጆቿን እየተነጠቀች መሆኑንና ይህንን አገልግሎት ውጤታማ ለማድረግ የሁሉም የቤተ ክርስቲያን ልጆች ክርስቲያናዊን ግዴታ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡

“ስብከተ ወንጌል አሰጣጣችን አካባቢያዊና ወቅታዊ ሁኔታን ያገናዘበ ያለመሆን ችግር ይታይበታል፡፡ የቤተ ክርስተያናችንን ማንነትና ትምህርቷን በሚገባ የተረዳን አንመስልም፡፡ ብዙውን ጊዜ የሚታይ ነገር ላይ ትኩረት እንሰጣለን፡፡ ለስብከተ ወንጌል የምንሰጠው ትኩረት እጅግ በጣም አናሳ ነው፡፡ አብዛኛው ሰው ለስብከተ ወንጌል አስተዋጽኦ ለማድረግ ሲሳተፍ አይታይም፡፡ በስብከተ ወንጌል መጽደቅ ያለበት ሰው ነው፡፡ የሚጸድቅም የሚኮነንም ሰው ነው፤ የስብከተ ወንጌል አሰጣጣችን በብዙ ችግር የታጠረ ስለሆነ የሁላችንንም ድጋፍና ተሳትፎ ይፈልጋል፡፡”

“አንድ ወቅት አርብቶ አደር በሆኑት ቦታዎች የሚገኙ ወገኖቻችን እንዲጠመቁ ሲጠየቁ የሚጠጡት ወተት፣ የሚበሉት ሥጋ በመሆኑ ለአባቶቻችን አንድ ጥያቄ አቅርበው ነበር፡፡ መጠመቅ እንፈልጋለን፤ እንደ እናንተ ስንዴና ገብስ አናመርትም፤ እነዚህን እስክናመርት በጾም ወተትና ሥጋውን እንበላ ዘንድ ፍቀዱልን በማለት የጠየቁበት ጊዜ ነበር፡፡ ይህ የሚያመለክተን አለመሥራታችንና የስብከተ ወንጌል አገልግሎት በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ላይ ትኩረት አለማድረገችንን ያሳያል፡፡” በማለት ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም በዲያቆን ያረጋል አበጋዝ በቀረበው ጥናታዊ ጽሁፍ ላይ ምዕመናን ያላቸውን ጥያቄዎች በማቅረብ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ ከጠረፋማ አካባቢዎች ከደቡብ ኦሞና ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ወረዳዎች ተጋብዘው የመጡት የምእመናን፤ ተወካዮችና አገልጋዮች የተሰማቸውን ስሜት የገለጹ ሲሆን አገልጋይ ዲያቆናቱ መዝሙር አቅርበዋል፡፡

 

hawi 01

የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ደብረ መድኀኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን

 ታኅሣሥ 9 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ሪፖርታዥ፡-

hawi 01ማኅበረ ቅዱሳን ለአምስተኛ ጊዜ ያዘጋጀው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በደብረ ዘይት ከተማ ደብረ መድኀኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ታኅሣሥ 6 ቀን 2006 ዓ.ም. ከ6000 በላይ ምእመናን በተገኙበት በድምቀት አካሔደ፡፡

ከዋዜማው ጀምሮ መርሐ ግብሩን የተሳካ ለማድረግ የማኅበሩ ሐዊረ ሕይወት አዘጋጅ ኮሚቴ በሚመድበው መሠረት የየክፍሉ አገልጋዮች በአገልግሎት ተጠምደዋል፡፡ መርሐ ግብሩን የተሳካ ለማድረግ ሁሉም ይጣደፋል፤ የጎደለውን ይሞላል. . . ፡፡

ከሌሊቱ 12፡00 ጀምሮ አምስት ኪሎ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን አጠገብ ከሚገኘው ከማኅበረ ቅዱሳን ሕንፃ ጀምሮ በተለምዶ ሰባ ደረጃ እስከሚባለው ሠፈር ድረስ ሰባ 1ኛ ደረጃ የሚሆኑ የከፍተኛ አገር አቋራጭ አውቶቡሶች መስመራቸውን ይዘው ተሰልፈው የምእመናንን መምጣት ይጠባበቃሉ፡፡

ከሌሊቱ12፡30 ጀምሮ ምእመናን በማኅበሩ በተወከሉ አስተባባሪዎች አማካይነት መለያ ባጅ እየተረከቡ በተዘጋጀላቸው መኪና ውስጥ በመግባት ጉዞው ተጀመረ፡፡

የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ክፍል አባላት ሌሊቱን ለኢንተርኔት የቀጥታ ሥርጭት ቅድመ ዝግጅት ስናደርግ አድረን በተዘጋጀልን መኪና ወደ ደብረ ዘይት አመራን፡፡

hawi 02 2በደብረ ዘይት ደብረ መድኀኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርሰቲያን ከጠዋቱ 2፡30 ሰዓት ስንደርስ የሰንበት ትምህርት ቤቱ መዘምራን አውራ ጎዳናው ላይ ወጥተው በዝማሬ ተቀበሉን፡፡ ነጫጭ የሀገር ባሕል አልባሳት የለበሱ የማኅበረ ቅዱሳን ደብረ ዘይት ማእከል አባላት፤ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ አባላትና ትራፊክ ፖሊሶች በሰልፍ ምእመናንን ይዘው እየመጡ ያሉትን ከፍተኛ አገር አቋራጭ አውቶቡሶችን ቦታ ለማስያዝ ይረባረባሉ፡፡ የደብረ ዘይት የጸሐይ ግለት ለደመናና ነፋሻማ አየር እጇን ሰጥታለች፡፡ የአካባቢው ምእመና ነጫጭ የሀገር ባሕል ልብስና ነጠላ ለብሰው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ይጓዛሉ፡፡ ደብረ ዘይት በጠዋቱ ደምቃለች፡፡

ደብረ መድኀኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን ስንገባ የእለተ ሰንበት ቅዳሴው በመገባደድ ላይ ነበር፡፡ አስቀዳሽ ምእመናንን ላለመረበሽ አንድ ጥግ ይዘን ከተሳለምን በኋላ እቃዎቻችንን ይዘን ወደ ድንኳኑ በመገባት ለቀጥታ ሥርጭት አመቺ ቦታ ነው ባልነው ሥፍ ላይ ሆነን የኤሌክትሮኒክስ መሣሪያዎቻችንን አስተካክለን የመርሐ ግብሩን መጀመር መጠባበቅ ጀመርን፡፡

ምእመናን ከመኪናቸው እየወረዱ በአስተባባሪዎች እየታገዙ በተዘጋጀው ድንኳን ውስጥ ቦታቸውን በመያዝ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ የደብረ ዘይት ከተማ ምእመናን ጨምሮ ከስድስት ሺሕ ምእመናን በላይ ግቢውን ሞሉት፡፡ ሁሉም ፊት ላይ የደስታ ስሜት ይነበባል፡፡ ስለ ቤተ ክርስቲያን ለመወያየት፤ ቃለ እግዚአብሔር ለመስማት የመጓጓት ስሜት፡፡

ከጠዋቱ 2፡50 ሲሆን ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ማትያስ የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ሐዲስ በጎንደር መንበረ መንግስት መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን የአራቱ ጉባዔያት መምህርና የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪ፤ መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን የሊቃውንት ጉባኤ አባል፤ የኔታ ሐረገ ወይን የዝዋይ ሐመረ ኖህ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አበምኔት፤ መጋቤ ሐዲስ ደጉ ዓለም ካሳ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሐዲሳት መምህር፤ መጋቤ ሐዲስ እሸቱ አለማየሁ የቅዱስ ጳውሎስ መንሳዊ ኮሌጅ የሐዲሳት መምህርና፤ ሌሎችም አባቶች ወደ ሥፍራው ደረሱ፡፡

ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት በብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና በደብሩ ካህናት መርሐ ግብሩ በፀሎተ ወንጌል ተጀመረ፡፡

የእለቱ ምስባክ “ቀዳሚሃ ለጥበብ ፈሪሃ እግዚአብሔር ምክር ሰናይት ለኵሉ ዘይገብራ ወስብሐቲሁኒ ይነብር ለዓለም፤ የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው፤ ለሚያደርጓትም ሁሉ ምክር በጎ ናት፤ ምስጋናውም ለዘለዓለም ይኖራል” መዝ.110፡10

ጸሎተ ወንጌሉ እንደተጠናቀቀ የደብሩ ሰንበት ትምህርት ቤት መዘምራን ያሬዳዊ መዝሙር በማቅረብ መርሐ ግብሩ ቀጥሎ በቀሲስ ፋሲል ታደሰ የመጀመሪያውን ክፍል የወንጌል ትምህርት “የእግዚአብሔር መልስ” በሚል ርዕስ ተሰጠ፡፡hawi 02

በትምህርታቸውም “እግዚአብሔር ለጠየቅነው ነገር ሁሉ ጊዜውን ጠብቆ ያከናውንልናል፡፡ እግዚአብሔር ዝም የሚልበት ጊዜ አለው፤ መልስ የሚሰጥበትም ጊዜ አለው፡፡ . . . ከእኛ ሁለት ነገሮች ይጠበቃሉ፡፡ በእምነት ሆነን መጸለይና በትዕግስት እግዚአብሔርን መጠበቅ፡፡” በማለት ሰፋ ያለ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

ከትምህርቱ በኋላ ከተመሠረተ ሃያ ዓመታትን ያስቆጠረውና ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ የሚገኘው የአዲስ አበባ የደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ቤተ ክርስቲያን አንቀጸ ብርሃን ሰንበት ትምህርት ቤት የጎልማሶች ክፍል፤ እንዲሁም ዘማሪ ዲያቆን ቴዎድሮስ ዮሴፍ መዝሙር አቅርበዋል፡፡

ክፍል ሁለት የወንጌል ትምህርትን በሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ ሐዲስ በጎንደር መንበረ መንግስት መድኀኔ ዓለም ቤተ ክርስቲያን የአራቱ ጉባዔያት መምህር “አነ ውእቱ ሕብስተ ሕይወት፤ የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ” ዮሐ. 6፡32 በሚል ርዕስ አስተምረዋል፡፡

“ጌታችንን ይከተለው ከነበረው አምስት የገበያ ሕዝብ መሐል አንዳንዶቹ ሥጋዊ ምግብን ፍለጋ፣ አንዳንዶቹ ከደዌቸው ለመፈወስ፣ አንዳንዶቹ ትምህርቱን ለመስማት፣አንዳንዶቹ መልኩን ለማየት ሌሎቹ ደግሞ የኦሪትን ሕፀፅ፤ የወንጌልን መብለጥ ሰምተው ይነቅፉት ዘንድ ይከተሉት ነበር፡፡ ለእነዚህ ሁሉ እንደተነገረላቸው ትንቢት ለሁሉም የሚሹትን ይሰጣቸው ነበር፡፡ . . . ልጆቼ ምን ያህል እንጀራ አላችሁ? አላቸው ደቀመዛሙርቱን፡፡ እነሱም አምስት እንጀራ እና ሁለት አሳዎች ብቻ ነው ያለን፡፡ ነገር ግን ይህ ለአምስት ሺሀ ሕዝብ ምን ይበቃልን? አሉት እሱም አንስቶ አመሰገነ አበርክቶም ለሕዝቡ ሰጣቸው፡፡ በሉ ጠገቡም፡፡

… አስራ ሁለት መሶብ ትራፊም አነሱ፡፡ ይህም ሴቶች እና ሕፃናት ሳይቆጠሩ ነው፡፡ ለምን ቢሉ ሲቶች በወንዶች ፊት ስለሚያፍሩ ብዙ በደንብ አንስተው አይበሉም፤ ሕፃናትም ከሚበሉት የሚፈረፍሩት ስለሚበዛ ነው፡፡ … ምስጢሩን ስንመለከት ምግቡን በምሽት ያበረከተበት ምክንያት ጠዋት ቢሆን ሁሉም ቁርሱን በልቶ ስለጠገበ ብዙ ተርፎ ተነሳ እንዳይሉ፣ ሁለተኛው በለምለም ስፍራ ላይ ያስቀመጣቸው ምክንያቱ ልብሳችን እንዳይቆሽሽ ተደላድለን ስላልተቀመጥን ብዙ ስላልበላን ተርፎ ተነሳ እንዳይሉ፣ ሦስተኛው በከተማ ሳይሆን በምድረባዳ ምንም በሌለበት ማድረጉ ምግቡ ሲያንስ ደቀመዛሙርቱ ከከተማ እየገዙ እንጂ አበርክቶት አይደለም እንዳይሉ፣ አራተኛው በጥብርያዶስ ወንዝ አጠገብ ያስቀመጠበት ምክንያት እጃችንን ሳንታጠብ ስለበላን እንጂ ብዙ ተርፎ አይነሳም እንዳይሉ፤ በመጨረሻም እስከ ዛሬ ይከተሉት የነበረው ለመብል መሆኑን ስለተረዳ “የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ” አላቸው፡፡ ከጧት እሰከ ማታ ሳይበሉ መቆየታቸው ጾመው ጸልየው መንግሥቱን ያገኙ ዘንድ ነው፡፡ ሥጋዬ አውነተኛ የሕይወት መብል፤ ደሜም እውነተኛ የሕይወት መጠጥ ነው፡፡ ሥጋዬን ያልበላ፤ ደሜንም ያልጠጣ የዘላለም ሕይወት የለውም ሲላቸው በቅዱስ ሥጋውና በክቡር ደሙ አሠረው” በማለት አስተምረዋል፡፡

ከትምህርት ወንጌሉ በመቀጠል ዘማሪ ዲ/ን እንግዳ ወርቅ በቀለ፤ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን መዘምራን መዝሙር በማቅረብ ቀጥሎ የደብሩ ሰበካ ጉባኤ ምክትል ሰባሳቢ አቶ አምሳሉ ደጀኔ የደብረ መድኃኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክና እየተከናወኑ ስለሚገኙ የልማት ሥራዎች ሪፖርት አቅርበዋል፡፡

hawi 05አቶ አምሳሉ ባቀረቡት ሪፖርትም አካባቢው የኢንዱስትሪ ዞን ውስጥ የሚገኝ በመሆኑ ከ1999 ዓ.ም. ጀምሮ ቤተ ክርስቲያን ለመሥራት ከፍተኛ ጥረት መደረጉን ገልጸዋል፡፡ “በአጥቢያው ከአሥር ሺሕ በላይ ምእመናን የሚገኙበት ቢሆንም ቤተ ክርስቲያን ባለመኖሩ አምልኮተ እግዚአብሔር ለመፈጸም ባለመቻላችን ምእመናኑን ፊርማ በማሰባሰብ ከሀገረ ስብከቱ ጋር በመሆን ለማስፈጸም ችለናል፡፡ በዚህም መሠረት የካቲት 3 ቀን 2005 ዓ.ም. በብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ የምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የመሠርት ድንጋይ ተቀምጦ በሦስት ወራት ውስጥ ተሠርቶ ተጠናቋል፡፡ አሁንም ቤተ ክርስቲያኑ ጠባብ በመሆኑ ወደፊት በተሻለ ሁኔታ ለመሥራት የታሰበ ሲሆን የአንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ለመክፈት ጥረት በማድረግ ላይ እንገኛለን” በማለት ሪፖርታቸውን አጠናቀዋል፡፡

የከስዓት በፊቱ መርሐ ግብር በማጠናቀቅ የምሳ መርሐ ግብሩ ቀጥሏል፡፡

ከምሳ መልስ የማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ወረብ ” ኢየሱስ ክርስቶስ ሊቀ ካህናቲነ አስተጋብአነ ሀበ ትረፍቅ መካነ፤ እስመ ዝርዋን አግብርቲከ ንህነ፤ በኃጢዓት የተበተን እኛን ሊቀ ካህናችን ክርስቶስ በፍቅር ሰብስበን” በማለት አቅርበዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ ማኅበሩ በዩኒቨርስቲዎችና በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት፤ እንዲሁም በአብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማት እያከናወናቸው ስለሚገኙት ተግባራት ሪፖርት አቅርበዋል፡፡

ቀጥሎ የተካሔደው የጥያቄና መልስ መርሐ ግብር ሲሆን ጥያቄዎቹ ከማኅበሩ አባላትና ምእመናን በተለያዩ ጊዜያት ሲጠየቁ የነበሩ ናቸው፡፡ ጥያቄዎቹንም ለመመለስ ከሊቃውንቱ መካከል መልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪሁን የሊቃውንት ጉባኤ አባል፤ መጋቤ ሐዲስ ደጉ ዓለም ካሣ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ የሐዲሳት ትርጓሜ መምህር፤ መጋቤ ሐዲስ እሸቱ አለማየሁ በቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ኮሌጅ የብሉይና የሐዲስ ትርጓሜ መምህር ሲሆኑ ጥያቄዎቹ በዲ/ን ያረጋል አበጋዝ አቅራቢነት ተስተናግደዋል፡፡

hawi 03ከጥያቄዎቹ መካከል፡- የኑሮ ውድነት እና ሀብት የማካበት ትኩረታችን ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ጊዜ ከመስጠት እያገደን ስለሆነ ምን እናድርግ? ቅዱስ ጳውሎስ ሀገራችን በሰማይ ነው ስላለ እኛ ክርስቲያኖች በምድራዊት ሀገራችን ላይ እንዴት እንሥራ? ባለትዳሮች ከትዳር አጋራቸው ጋር የሚኖራቸው ግንኙነት እና ከሌሎች ቤተሰብ አባላት ጋር የሚኖራቸው ግንኙነት ምን መምሰል አለበት? ፖለቲካ ኃጢአት ነው? ለሱሰኛ እና ለጠጪ ባንመጸውት ኃጢአት ይሆንብናል ወይ? ንስሐ አባት ለምን ያስፈልጋል? ነፍስን ለፈጠረ እግዚአብሔር በቀጥታ ኃጢአትን መናዘዝ አይቻልም ወይ? ለሚሉ ጥያቄዎች ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡

ከጥያቄና መልሱ በኋላ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳሰ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ባስተላለፉት መልእክት “ሁሉም ነገር የሚሆነው በእግዚአብሔር ፈቃድ ነው፡፡ ይህ ሕዝብ ለእምነቱ፤ ለሀገሩና ለአንድነቱ የቆመ በመሆኑ ረጅሙን ጉዞ በመጓዝ ወደ ሀገረ ስብከታችን መጥቶ ይህንን መንፈሳዊ ጉባኤ መካፈል በመቻሉ ተደስተናል፡፡ በሊቃውንቱ ቀኑን ሙሉ ሲነገር የዋለው ቃለ እግዚአብሔር በሚገባ ከያዝነውና ወደ ሕይወታችን መለወጥ ከቻልን ቤተ ክርስቲያንና ሀገራችንን የሚጠቅም ሥራ ልንሠራ እንችላለን፡፡ ሁላችንም ሓላፊነታችንን መወጣት አለብን፡፡ ማኅበሩ በሚቀጥለው ጊዜ ሊያዘጋጅ ያሰበው ጉባኤም ከሀገረ ስብከታችን አይወጣም” ብለዋል፡፡

hawi 04ብፁዕ አቡነ ማትያስ የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለ ምእዳንም “እናንተ እድለኞች ናችሁ፡፡ እኔ በእድሜዬ እንዲህ ያለ ጉባኤ አይቼ አላውቅም፡፡ በውጭ ያሉ ወገኖቻችሁ ለተወሰኑ ሰዓታት ብቻ ተከራይተው ነው አገልግሎት የሚያገኙት፡፡ ቀኑን ሙሉ ቁጭ ብላችሁ በተረጋጋ መንፍስ ሆናችሁ ትማራላችሁ፡፡ ጆሮ ያለው ሁሉ ይስማ፡፡ ቀኑን ሙሉ ቃለ እግዚአብሔር ሲነገር ነው የዋለው፡፡ የተነገረውን ሁሉ የሰማ በሥራ መተርጎም ይጠበቅበታል፡፡ ሁላችንም የሰማነውን ለሌሎች ብናስተላልፈው ብዙ ሥራ ሊሠራ ይችላል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን! ብርሃናችሁ በሰው ፊት ይብራ፡፡ በውጭ ያሉትም በአገልግሎታችሁ ይደሰታሉ፡፡ አንዳንዶች ያልገባቸው ሌላ አድርገው ይተረጉሙት ይሆናል፡፡ ዛሬ የተማርነው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶን አስተምህሮ የተከተለ ትምህርት ነው፡፡ ይህንን የሚቃወሙ ከቤተ ክርስቲያን ተለይተው የወጡ ብቻ ናቸው” በማለት የተናገሩ ሲሆን ማኅበረ ቅዱሳንን፤ የደብሩ ሰበካ ጉባኤንና ምእመናንን አመስግነዋል፡፡

በዚሁ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡

 

1464794 583027858417920 875634623 n

የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በድምቀት ተካሔደ

ማኅበረ ቅዱሳን ለ5ኛ ጊዜ ያዘጋጀውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ደብረ ዘይት በሚገኘው ደብረ መድኃኒት ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ታኅሳስ 6 ቀን 2006 ዓ.ም. ከ 5000 ምዕመናን በላይ በተገኙበት አካሔደ፡፡ ዝርዝሩን እንደደረሰን እናቀርባለን፡፡1464794 583027858417920 875634623 n

Baptism

“ግብረ ፊልጶስ” የተሠኘ ሲምፖዚየም እንደሚዘጋጅ ተገለጸ

ታኅሣሥ 05 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

 

“ግብረ ፊልጶስ – ሐዋርያዊ ጉዞ በኢትዮጵያ በቀድሞው፤ በመካከለኛውና በአሁኑ ዘመን” በሚል መንፈሳዊ ጉባኤ በማኅበረ ቅዱሳን ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ አማካይነት ሲምፖዚየም እንደሚዘጋጅ ተገለጸ፡፡ Baptism

 

ተኅሣሥ 12 እና 13 ቀን 2006 ዓ.ም. ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ስብከተ ወንጌል አዳራሽ በሚካሔደው ሲምፖዚየም ላይ ከዚህ በፊት በተልተሌ፤ ጂንካ፤ ከረዩ፤ መተከልና ግልገል በለስ አካባቢዎች ተጠምቀው የእግዚአብሔር ልጅነትን ያገኙ ምእመናን በአካል በመገኘት በጉባኤው ላይ አሁን ያሉበትን ሁኔታ ያቀርባሉ፡፡

Baptism1የስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ክፍሉ ያከናወነውን የአራት ዓመታት የሥራ ሪፖርት፤ እንዲሁም ጥናታዊ ጽሑፍ የሚቀርቡ ሲሆን በጥናታዊ ጽሑፉ ላይና ወደፊት ሊሠሩ በታቀዱ ሥራዎች ላይ ውይይት ይካሔድባቸዋል፡፡ በተጨማሪም ከዚህ ቀደም ተጠምቀው ነገር ግን በአጥቢያቸው ቤተ ክርስቲያንና ሰንበት ትምህርት ቤት ለሌላቸው የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር ይከናወናል፡፡

ይህንን መርሐ ግብር በማኅበሩ ድረ ገጽ (www.eotcmk.org) ላይ የቀጥታ ዓለም አቀፍ ሥርጭት የሚተላለፍ በመሆኑ ምእመናን መከታተል እንደሚችሉ ክፍሉ አስታውቋል፡፡

 

0202023 1

የመስቀል በዓል አከባበር በዩኔስኮ ቅርስነት ተመዘገበ

 ኅዳር 26 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

  • የመስቀል በዓል አከባበር ኢትዮጵያ በዩኔስኮ ካስመዘገበቻቸው 10 ቅርሶች መካከል የመጀመሪያው የማይዳሰስ ቅርስ በመባል መመዝገቡን አስመልክቶ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጠ፡፡

 0202023 1
የኢትዮጵያ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን የኢትዮጵያ የመሰቀል በዓል አከባበር በተባበሩት መንግሥታት የትምህርት፤ የሳይንስና የባሕል ድርጅት (ዩኔስኮ) በማይዳሰሱ ቅርሶች (Intangible) በቅርስነት መመዝገቡን አስመልከቶ ኅዳር 26 ቀን 2006 ዓ.ም. በባለሥልጣኑ አዳራሽ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጠ፡፡

አቶ ዮናስ ደስታ የፌደራል የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ዳይሬክተር በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ “የመስቀል በዓል አከባበር በዩኔስኮ የማይዳሰስ ቅርስ (Intangible) ሆኖ የተመዘገበው ዩኔስኮ የሚጠይቀውን ሒደት ጠብቆና የተለያዩ የግምገማ መሥፈርቶችን አልፎ አዘርባጃን ዋና ከተማ ባኩ ከኅዳር 23 – 28 ቀን 2006 ዓ.ም. እያደረገ ባለው ስምንተኛው የዩኔስኮ የማይዳሰሱ ቅርሶች ጉባኤ ላይ በትናንትናው ዕለት ተቀብሎ አጽድቆታል”  በማለት ገልጸዋል፡፡

አቶ ዮናስ የመስቀል በዓል አከባበርን በቅርስነት ለማስመዝገብ የተደረገውን ጥረት ሲገልጹ በቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን ባለሙያዎች አማካይነት ጥናቱ ተከናውኖ ሰነዱ ለዩኔስኮ ዓለም አቀፍ ኖሚኔሽን  በ2004 ዓ.ም. መቅረቡን አውስተዋል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ እንዲመዘገቡ ለጉባኤው ከቀረቡት 31 የማይዳሰሱ ቅርሶች መካከል 23ቱ ሲመረጡ የመስቀል በዓል አከባበር ከተመረጡት ውስጥ አንዱ በመሆኑና እውቅና ማግኘቱን ተናግረዋል፡፡

0202023 2አቶ ዮናስ የመሰቀል በዓል አከባበር በዓለም አቀፍ ደረጃ የመመዝገቡ ፋይዳን ሲገልጹም ቅርሱን የተመለከቱ መረጃዎች በዩኔስኮ ድረ ገጽ ላይ የሚለቀቅ በመሆኑ ሀገረ አቀፍና ዓለም አቀፍ እውቅና እንዲያገኝ እንደሚረዳው፤ የቱሪስት መስህብ መሆኑ፤ ከቀድሞ በተሻለ እንክብካቤ የሚደረግለትና ለትውልድ እንዲተላለፍ እገዛ ማድረጉን፤ ዓለም አቀፍ አጥኒዎችና ተመራማሪዎችን መሳቡ ዋና ዋናዎቹ  ጥቅሞች መሆናቸውን አብራርተዋል፡፡

የሰሜን ተራሮች፤ አክሱም ጸዮን ሐውልቶች፤ የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት፤ የታችኛው ኦሞ ሸለቆ፤ ጢያ ትክል ደንጋዮች፤ የታችኛው አዋሽ ሸለቆ፤ ሐረር ጀጎል፤ የኮንሶ ባሕላዊ መልክአ ምድር እና  የፋሲል ግቢ ኢትዮያ ከዚህ ቀደም ያስመዘገበቻቸው የሚዳሰሱ (tangible) ቅርሶች መካከል ዘጠኙ ሲሆኑ ብቸኛው የመስቀል በዓል አከባበር ከማይዳሰሱ ቅርሶች መካከል ይመደባል፡፡

meskel 8

የመስቀል በዓል በዓለም ቅርስነት ተመዘገበ

 የኢትያጵያ የመስቀል ክብረ በዓል በዓለም ቅርስነት መመዝገቡን UNESCO /ዩኔስኮ/ አስታወቀ፡፡

meskel 8
ዝርዝሩን እንደደረስን እናቀርባለን፡፡

 

02 hawir hiwot

ሐዊረ ሕይወት (የሕይወት ጉዞ)

02 hawir hiwot

mesa

ማኅበረ ቅዱሳን ከስደት ተመላሾችን ለመደገፍ እንደሚሠራ አስታወቀ

 ኅዳር 24 ቀን 2006 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ማኅበረ ቅዱሳን ከሳውዲ አረቢያ ተመላሽ ወኖቻችንን ለመደገፍ ቀጣይ ሥራዎችን እንደሚሠራ አስታወቀ፡፡

mesa ማኅበረ ቅዱሳን ከሳውዲ አረቢያ በመመለስ ላይ ለሚገኙ ከ2ሺሕ በላይ ኢትዮጵያዊያን ስደተኞች ኅዳር 23 ቀን 2006 ዓ.ም. ቦሌ በሚገኘው የስደተኞች ጊዜያዊ መቀበያ ጣቢያ በመገኘት የምሳ ግብዣ ባደረገበት ወቅት የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ ማኅበሩ በዚህ በጎ አድራጎት ተግባር ላይ ለመሳተፍ የተነሣበትን ምክንያት ሲገልጹ “ማኅበረ ቅዱሳን እንደ ክርስትናም፤ እንደ ዜግነት የወገኖቻችን በዚህ ሁኔታ ላይ መገኘት ያስጨንቀዋል፡፡ ችግሩንም ለመፍታትና ወገኖቻችንን ለመደገፍ ማኅበራችን የበኩሉን ድርሻ መወጣት እንዳለበት በማመን በመንቀሳቀስ ላይ ይገኛል፡፡ ይህ የምሳ ግብዣ የመጀመሪያ ምዕራፍ ሲሆን ወንድሞቻችንና እኅቶቻችንን ለመደገፍ ምእመናንንና አባላትን በማስተባበር ቀጣይ ሥራዎችን እንሠራለን፡፡” ብለዋል፡፡

mesa 1አቶ ተስፋዬ አያይዘውም እነዚህ ወገኖቻችን ሠርተው በሚልኩት ገንዘብ በርካታ ቤተሰብ የሚተዳደር በመሆኑ ቤተሰብ እንዳይበተን፤ ተማሪዎች ከትምህርታቸው እንዳይደናቀፉ ከፍተኛ ሥራ መሠራት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም ከቅዱስ ፓትርያርኩ ጀምሮ እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድረስ በዚህ ሀገራዊ በሆነ ችግር ላይ መፍትሔ ለመሻት እየተንቀሳቀሰች መሆኗንና፤ ማኅበረ ቅዱሳንም በጋራ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመተባበር እንደሚሠራ በመግለጽ ምእመናንና አባላትም ማኅበሩ የሚያከናውነውን ተግባር እንዲደግፉ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል፡፡

አቶ ምሕረተአብ ሙሉጌታ በውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የፕሮቶኮል ጉዳዮች ዳይሬክተር ጀነራልና የጊዜያዊ ጣቢያው ከስደት ተመላሾች ጉዳይ አስተባባሪ ከስደት ተመላሾችን አቀባበል በተመለከተ ሲገልጹ “ከመንግሥት ጥረት ጎን ለጎን የተለያዩ የንግድ ማኅበረሰብ አባላት፤ ማኅበራትና በጎ አድራጊ ግለሰቦች ከስደት ተመላሽ ወገኖቻችንን ለመርዳት ድጋፍ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ 79ሺህ ኢትዮጵያዊያን ወደ ሀገራቸው የተመለሱ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ 49 ሺሕ ወንዶች፤ 26ሺሕ ሴቶች እንዲሁም ከ3ሺሕ በላይ ሕፃናት ናቸው፡፡”በማለት ገልጸዋል፡፡ አስፈላጊውንም ምዝገባና መስተንግዶ እየተደረገላቸው ወደየትውልድ ቀዬአቸው የመመለስ ሥራዎች እየተሠሩ እንደሚገኙ የገለጹት አቶ ምሕረተአብ ማኅበረ ቅዱሳንና ሌሎችም ማኅበራት እያደረጉ ላሉት ወገኖቻችንን የመርዳትና የመደገፍ ተግባር ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

አቶ መስፍን መንግሥቱ “ኢትዮጵያዊያን ለኢትዮጵያዊያን” በሚል ከነጋዴው ኅብረተሰብ የተቋቋመ ማኅበር አስተባበሪ ሲሆኑ ቦሌ በሚገኘው ጊዜያዊ የስደተኞች መቀበያ ጣቢያ ሲያስተባብሩ አግኝተናቸው ላቀረብንላቸው ጥያቄ ምላሽ ሲሰጡ “የተፈጠረው ድንገተኛ ችግር እጅግ አስደንጋጭ ነው፡፡ ኢትዮጵያዊያን በዚህ ወቅት ተባብረን ፈጣን ምላሽ መስጠት ይጠበቅብናል፡፡ በዚህም መሠረት ወገኖቻችንን ለመርዳት ተሰባስበን ለውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ለዶክተር ቴዎድሮስ አድኀኖም ደብዳቤ በማስገባት ድጋፍ መስጠት እንደሚገባን ተወያተናል፡፡ የተቀደሰ ዓላማ በመሆኑም ወደ ተግባር መግባት ትችላላችሁ በማለት ፈቃድ ሰጥተውናል፡፡ ስደተኞቹ መግባት ከጀመሩበት ጊዜ አንስቶ በአጭር ሰዓት ከ7 ሚሊዮን ብር በላይ በማሰባሰብ ከመስተንግዶ ጀምሮ እየሠራን እንገኛለን” ብለዋል፡፡

mesa 2
ከስደት ከተመለሱት መካከል ስሟን መግለጽ ያልፈለገች አንዲት እኅት በሳውዲ አረቢያ ስለነበረው የሥራዋ ሁኔታ ስትገልጽ “ከሀገሬ ከወጣሁ ሁለት ዓመት ሆኖኛል፡፡ ሁለት ሕፃናት ልጆቼን ትቼ ያልፍልኛል ብዬ ነበር አወጣጤ፡፡ ነገር ግን እዚያ የገጠመኝ እጅግ አስከፊ ሁኔታ ነበር፡፡ ከአሰሪዬ ቤት ውጪ ለሦስት ቤቶች በነጻ እንድሠራ አድርጋኛለች፡፡ ለምን ብዬ በጠየቅሁበት ወቅት ደብድባኝ ጎኔን ኦፕራሲዮን እሰከመሆን ደርሻለሁ፡፡ ሃያ አራት ሰዓት ያለማቋረጥ እንድሠራ ስታደርገኝ ቆይታለች፡፡ ከዚህ ሥቃይ በሀገሬ ልሙት ብዬ ነው የመጣሁት” በማለት ተናግራለች፡፡