ht

ፍኖተ ሐመረ ጽድቅ ዐውደ ርዕይ ተከፈተ

ነሐሴ 24 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ዐውደ ርዕዩ እሰከ ከነሐሴ 28 ቀን 2005 ዓ.ም. ይቆያል፡፡
የማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዋና ክፍልን የሃያ ዓመታት የአገልግሎት ጉዞ የሚያሳይ ፍኖተ ሐመረ ጽድቅ ዐውደ ርዕይ በማኅበሩ ሕንፃ ላይ ተከፈተ፡፡

ht
ፍኖጸተ ሐመረ ጽድቅ ዐውደ ርዕይ ነሐሴ 23 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቀኑ 11፡00 ሰዓት ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የቦረና፤ አማሮና ቡርጂ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ ብፁዕ አቡነ ሰላማ የታዕካ ነገሥት ባዕታ ለማርያም ገዳምና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የበላይ ጠባቂ ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችና አገልጋዮች በተገኙበት መርቀው ከፍተዋል፡፡

ht 2ብፁዕ አቡነ ገብርኤል የቦረና አማሮና ቡርጂ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የሐመር መጽሔትና የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና ምእመናን ያደረጉትን አስተዋጽኦ፤ እንዲሁም ከአመሠራረታቸው ጀምሮ የተጓዙበትን ሂደት በጥልቀት አብራርተዋል፡፡ በ1985 ዓ.ም. ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና የማኅበሩ አባላት በተገኙበት ውይይት በማካሔድ ሐመር መጽሔት ተብሎ እንዲሰየም ውሳኔ ላይ መደረሱን ተናግረዋል፡፡

ብፁዕነታቸው የኅትመት ውጤቶቹ እየሰጡ የሚገኙትን አገልግሎት ሲገልጹም “በሐመር መጽሔትና በስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የሚጻፈው፤ የሚነበበው ነገረ ድኅነትን ያመለክታል፡፡ የምንድንበትን መንገድ የሚያስተምሩ፤ ፃድቃን ሰማዕታት አማላጅ መሆናቸውን የሚያውጁ፤ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርሰቶስ የሁሉ ጌታ፤ የሁሉ ፈጠሪ መሆኑን የሚመሰክሩ፤ እምነትንና ምግባርን የሚያስተምሩ ናቸው” ብለዋል፡፡

ምእመናንን በማነጽ ረገድም “ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው የማያውቁ ወንድሞችና እኅቶች የኅትመት ውጤቶቹን በማንበብ ራሣቸውን በማረም እምነታቸውን እንዲያውቁና እንዲጸኑ አድርጓቸዋል፡፡ ከኢትዮጵያ አልፎም በዓለም ዐቀፍ ደረጃ እየተሰራጩ ምእመናንን በመታደግ ላይ ይገኛሉ፡፡ ይህም ታላቅ ሐዋርያዊ አገልግሎት ነው” በማለት ወደፊትም ተጠናክረው እንዲቀጥሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

ht 3
የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የማኅበሩ የኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ለቤተ ክርስቲያንና ለምእመናን ያላቸውን ፋይዳ በማስመልከት “በሐመር መጽሔትና ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ የተጀመረው አገልግሎት እድገት በማሳየት ሌሎች የኅትመት ውጤቶችን በመውሰድ ምእመናንን በማስተማር ላይ ይገኛሉ፡፡ የዘመኑ ቴክኖሎጂ ውጤቶችንም በመጠቀም የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያው ዘርፍ በተለያዩ ቦታዎች ላይ በአንድ ጊዜ በመድረስ የተሻለ አገልግሎት መስጠት ያስችለዋል” ብለዋል፡፡

ዲያቆን ዶክተር መርሻ አለኸኝ የሚዲያ ዋና ክፍል ሓላፊ የዐውደ ርዕዩ አስፈላጊነት በሚመለከት “ዐውደ ርዕዩ የሐመር መጽሔትና የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ በሃያ ዓመታት ጉዞ ውስጥ ያሳዩአቸውን ጠንካራና ደካማ ጎን ለይተን እንድናውቅ፤ የኅትመትም ይሁን የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያው የአገልግሎት ዘርፍ የወደፊት አቅጣጫ እንድንተልም ይረዳናል” ብለዋል፡፡ በተጨማሪም በሚቀጥለው ወር በመንፈሳዊው ሚዲያ ዘርፍ ልምድ ባላቸው አንጋፋ ጋዜጠኞች አማካይነት በማኅበሩ የኅትመት ሚዲያ ላይ ዐውደ ጥናት እንደሚካሔድ ገልጸዋል፡፡

ht 4ዐውደ ርዕዩ አራት አበይት ክፍሎች ሲኖሩት ዝክረ ሐመረ ጽድቅ፤ መዛግብትና ቁሳቁስ፤ የፎግራፍና የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ዘርፍ እንቅስቃሴን ይዳስሳል፡፡ ዐውደ ርዕዩ እሰከ ነሐሴ 28 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ የሚቆይ ሲሆን ምእመናን አራት ኪሎ በሚገኘው በማኅበሩ ሕንፃ ላይ ከጠዋቱ 4፤00 ሰዓት እስከ ምሽቱ 2፤00 ሰዓት ድረስ እንዲመለከቱ ተጋብዘዋል፡፡

የሰው ሰውነት ክፍሎች

ሐሴ 23 ቀን 2005 ዓ.ም. 

በመ/ርት ኖኀሚን ዋቅጅራ

ባለፈው ግእዝን ይማሩ አምዳችን ላይ የግእዝ ቁጥሮችን አጻጻፍና የንባብ ስያሜአቸውን ማቅረባችን የሚታወስ ነው፡፡ ዛሬ ደግሞ የሰውነት ክፍሎችን ማቅረባችንን እንቀጥላለን፡፡

የሰውነት ክፍሎች፣ ከአንገት በላይ የአካል ክፍሎች፣ /ክፍላተ አካላት ዘላዕለ ክሳድ/

የአንገት በላይ የአካል ክፍሎች ማለት ከእራስ ፀጉራችን ጀምሮ እስከ አንገታችን ድረስ ያሉትን የአካል ክፍሎች ያካተተ /የያዘ/ ክፍል ማለት ነው፡፡ እነዚህንም የአካል ክፍሎች ከዚህ በመቀጠል እንመለከታለን፡፡
ሰብእ – ሰው

– ሰብእ ዘተፈጥረ እምነ ሠለስቱ ባሕርየተ ነፍስ ምስለ አርባዕቱ ባሕርያተ ሥጋ ውእቱ
    ሰው የተፈጠረው ከሦስቱ ባሕርያተ ነፍስ እና ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ ነው፡፡

– ሠለስቱ ባሕርያተ ነፍስ ብሂል
    ሦስቱ ባሕርያተ ነፍስ ማለት

፩. ሕያዊት – ሕዋሳትን የምታንቀሳቅስ ሕይወት ያላት
፪. ለባዊት – ልብ የምታደርግ /የምታስብ/
፫. ነባቢት – የምትናገር

አርባዕቱ ባሕርያተ ሥጋ ብሂል
 አራቱ የሥጋ ባሕርያት ማለት 

  • ነፋስ –  የነፋስነት ባሕርይ           – አፍ – አፍ
  •   እሳት – የእሳትነት ባሕርይ          – ስን – ጥርስ
  • ማይ – የውኃነት ባሕርይ            – ልሳን – ምላስ
  •   መሬት – የመሬትነት ባሕርይ        – ቃል – ቃል
  •   ድማሕ /ናላ/ – መሀል ራስ /አናት/  – ዕዝን – ጆሮ
  • ናላ – አናት                          – መልታህ – ጉንጭ
  •  ስእርት – የራስ ፀጉር                – አንፍ – አፍንጫ  
  • ጽፍሮ – ሹርባ                       – ከንፈር – ከንፈር
  • ድንጉዝ – ጥቅል ሥራ               – ሕልቅ – አገጭ
  • ድምድማ – የተበጠረ ጎፈሬ          – ጽሕም – ጢም
  • ሲበት – ሽበት                       – ክሳድ – አንገት
  •  ገጽ – ፊት                           – ምጉንጳ – የዐይን ሽፋን
  • ፍጽም – ግንባር                     – ዓይን – ዐይን
  • ከዋላ – ኋላ                                     የድምጽ ክፍላት
  • ቅርንብ – ቅንድብ                   – ፋጻ – ፍጨት            
  • ዕዝን – ጆሮ                         – ጒሕና – ጎርናና /ወፍራም/ ድምጽ   
  •  መልታህ – ጉንጭ                  – ቃና – የዜማ ድምጽ,  እስትንፋስ – ትንፋሽ 

ክርስትና “አክራሪነት”ን የሚያበቅል ነገረ ሃይማኖታዊ መሠረት የለውም

ነሐሴ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.
 
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገራችን የሃይማኖት “አክራሪነት” ስጋት እንዳለ በተለያዩ ወገኖች የሚነሣ ሐሳብ አለ፡፡ የ “ሃይማኖት አክራሪነት” በሀገራችን የለም የሚል እምነት አይኖርም፡፡ “አክራሪነት” የሚተረጎመውም የራስን የሃይማኖት የበላይነት ለማስፈን ሲባል ሌላው የሃይማኖት ሐሳቡን እንዳይ ገልጥ፣ ተግባራዊ የአምልኮ ሥርዓቱን እንዳይፈጽም ማድረግ፣ በኃይል ወይም በዐመፅ ቦታ ማሳጣት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ አንድ ቤተ እምነት ራሱ ከሚከተለው እምነት ውጪ ያሉ በቁጥር ትንሽ ወይም ብዙ ተከታይ ያሏቸው እምነቶች በአንድ ሀገር ወይም ቦታ መኖር የለባቸውም ብሎ ማመን ወይም ማድረግ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ይህ ደግሞ የሰዎችን የፈቃድ ነጻነት፣ ምርጫ አለማክበር፤ አለመጠበቅ ነው፡፡

ከላይ የተጠቀሰው አስተሳሰብ ደግሞ በምንም መስፈርት ቢመዘን ክርስትና ሊሸከመው የሚችለው አይደለም፡፡ የሚጋጨውም ከክርስትና መሠረታዊ ባሕርይና አካሔድ ጋር ነው፡፡ ክርስትና ወደ ሰዎች የመጣው በራሱ በሥግው አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ሥራና ቃል ነው፡፡ ጌታችን ወደ ሰዎች ቀርቦ ወደ እርሱ እንዲመጡ የሳባቸው የፈቃድ ነጻነታቸውን ጠብቆ ነው፡፡ በደዌ ነፍስ የተያዙትን በትምህርቱ፣ በደዌ ሥጋ የተያዙትን በተኣምራቱ ሲፈውስ ሁሉንም “ልትድን ትወዳለህን” እያለ ፈቃዱን ጠይቆ የፈጸመው ነበር፡፡ ልባቸው ወደ እርሱ ያዘነበሉትን “ተከተሉኝ” ብሎ ወደ መንግሥቱ እየጋበዘ ከእርሱ ኅብረት ደምሯቸዋል፡፡ “ሸክማችሁ የከበደ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም ዐሳርፋችኋለሁ” ብሏቸዋል፡፡

ጌታችን ያለፈቃዳቸው ከጉባኤው የደመራቸው ወገኖች አልነበሩም፡፡ ተሰብስበውም ከነበሩት የሚያስተምረው ኃይለ ቃል ከምስጢሩ ታላቅነት የተነሣ የጸነናቸው ታዳሚዎች እንኳን ጥለውት በሔዱ ጊዜ አልተቃወመም፡፡ በእግሩ ስር የቀሩ ሐዋርያቱንም “እናንተስ ልትሔዱ ትወዳላችሁን” እያለ ደቀመዛሙርቱን እንኳን ፈቃዳቸውን ያረጋግጥ ነበር እንጂ፤ ከዋልኩበት ውላችሁ፣ ካደርኩበት አድራችሁ፤ አበርክቼ አብልቼ፣ በፍቅሬ ረትቼ፤ በተአምራቴ ፈውሼ፣ ተኣምራት የምትሠሩበትን ኃይል አልብሼ ካቆየኋችሁ በኋላ ስለምን ትተውኛላችሁ ብሎ አምላካዊ ሥልጣኑን ተጠቅሞ ሊጫናቸው አላሰበም፡፡ በመሆኑም ክርስትና “ከአንተ ወደ ማን እንሔዳለን” ያሉ ቅዱሳን ሐዋርያትና በሐዋርያት ትምህርት የጸኑ፣ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚነሡ ምእመናን በፈቃዳቸው የሚኖሩበት ሃይማኖት ነው፡፡   

ጌታችን እንድንቃወም ያስተማረን ሌሎችን በኃይል ወደ እርሱ መሳብን ብቻ ሳይሆን ሊያስገድዱን የሚመጡ፣ መልካሙን እንዳንፈጽም የሚከለክሉንንም ቢሆን በኃይል ለመቋቋም መሞከርንም ነው፡፡ ጌታችን ለጴጥሮስ “ሰይፍን የሚያነሡ በሰይፍ ይጠፋሉ፤ ሰይፍህን ወደ ሰገባው መልስ” ያለው ለዚህ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ክርስትና በባሕርዩ “አክራሪነት”ን የሚያስተ ናግድበት መስክ የለውም፤ በጽኑም ይቃወመዋል፡፡

ክርስትና ሰዎች የእምነት ሐሳባቸውን እንዳይገልጹ አይገ ድብም፡፡ ሌሎች በእምነቱ ላይ ያላቸውን ጥያቄ እንዳያቀርቡም አይከለክልም፡፡ ስለያዘው እውነት በራሱ የሚተማመን ሃይማኖት ነው፡፡ ስለሆነም እርሱም ይሔንኑ መብት በጽኑ ይፈልገዋል፡፡ ለሚጠይቁት ሁሉ መልስ ለመስጠት የተዘጋጀ፣ የራሱን የድኅነት መንገድ ለመመስከር የተሰማራ ሃይማኖት ነው፡፡ የክርስቶስን መንግሥቱንና ጽድቁን ለሚሹ ሁሉ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” እያለ ይጮኻል፡፡ ስለዚህ ክርስትና የ “አክራሪነት” ሐሳብ ከመሠረቱ ሊበቅልበት የማይችል ሃይማኖት ነው፡፡

በተግባርም ቢሆን ከቤተልሔም ዋሻ አንሥቶ እስከ ምድር ጥግ እንዲስፋፋ ያስቻለው በረድኤተ እግዚአብሔር ተደግፎ፣ በፍቅር ስቦ፣ በመግደል ሳይሆን በመሞት የብዙዎችን ነፍስ ለመታደግ የሚኖር ሃይማኖት በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ የቃለ ሃይማኖቱን ኃይል የተአምራቱን ብዛት የአማኞቹን ጽናት አይተው የራሳቸውን እምነትና ፍልስፍና ለመጫን የሞከሩበትን አምልኮ ባዕዳንን ይከተሉ ከነበሩ ወገኖች ጀምሮ ሃይማኖትን የዕድገት፣ የነጻነት፣ የፍትሕ፣ የእኩልነት ወዘተ ጸር አድርገው እስከሚያስቡ የማርክሲዝም ሌኒንዝም ተከታዮች ድረስ የነበሩ “አክራሪዎች” ክርስትናን ሊያጠፉት ሲሞክሩ ታይቷል፡፡ ነገር ግን ሰይፋቸውን በትዕግስት ተቋቁሞ፣ እነርሱ እያለፉ እርሱ ሳያልፍ ዘላለማዊ ሆኖ እዚህ የደረሰ ሃይማኖት ሆኗል፡፡

ክርስትና በ“አክራሪነት” ሲመላለስ አልኖረም፡፡ በክር ስትና ስም የሚፈጸሙ ወይም በታሪክ ወስጥ የተፈጸሙ አሁን “አክራሪነት” ያልነው ጠባይ የተንጸባረቀባቸው አጋጣሚዎች ቢኖሩ እንኳን በክርስትና ስም ልንቀበለው የምንችለው አይሆንም፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም “ቢቻላችሁስ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ” የሚል የፍቅር ቃል ሰጥተውናል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንም ሐዋርያዊ ውርስ ያላት ጥንታዊ ቤተክርስቲያን ስትሆን እነዚህ ከላይ የተሰጡ፣ ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረውን ትምህርትና ቅዱሳን ሐዋርያት ያስተላለፉትን መልእክት ታከብራለች፤ ትጠብቃለች፤ ነገረ ሃይማኖታዊ መሠረቷም ይኸው ነው፡፡

ስለዚህ ቤተክርስቲያን የእኔ ናቸው በምትላቸው ሕጋዊ መዋቅሮቿ፣ በመዋቅሮቿም ላይ የሚያገለግሉ አገልጋይ ካህናትና ምእመናን ሰንበት ትምሀርት ቤቶችና ማኅበራት ሁሉ ከላይ ከተጠቀሰው ክርስቲያናዊ መንገድ የወጣ በ”አክራሪነት” የሚታሰብባቸውን ተግባራት ሊፈጽሙ አይችሉም፤ ካደረጉም ቤተ ክርስቲያኒቱ ባላት ቀኖናዊ ሕግ መሠረት ይዳኛሉ፡፡ ይታረማሉ፤ ካልሆነም ይለያሉ፡፡

ቤተክርስቲያን ያላት ነገረ ሃይማኖታዊ ሐሳብ ይህ መሆኑን ከተስማማን፣ በዚህ መሠረታዊ አስተምህሮዋ ላይ ቅሬታ የሌለን ከሆነ፣ መልካምነቱን የምንረዳ ከሆነ፣ በዚህ ላይ ያልበቀለ፣ ያላፈራ፣ መልካም ያልሆነ የቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ ካለ መመርመር ይገባል፡፡ በዚህ ጊዜ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራልና፤ ክፉ ዛፍም ክፉ ፍሬን ያፈራል፤ መልካም ዛፍ ክፉ ፍሬን ማፍራት፣ ክፉ ዛፍም መልካም ፍሬን ማፍራት አይችልም፤ መልካም ፍሬን የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል እግዲህ ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ” /ማቴ 7፥17/ ያለው ቃሉን እናስባለን፡፡ 

 
ማኅበረ ቅዱሳንም ከዚህ የወጣ አካሒድ ሊኖረው አይችልም፡፡ በቤተክርስቲያኒቱ መዋቅር ውስጥ ያለ ሓላፊነት የሚሰማው የአገልግሎት ማኅበር ነውና፡፡ “አክራሪነት”ን በመቃወምና የሃይማኖቶችን መከባበር ተገቢነት አስመልክቶ በተደጋጋሚ በገለጻቸው አቋሞቹ አስታውቋል፡፡ ለዚህም በሐመር መጽሔት በግንቦት ወር 2001 ዕትም፣ ስምዐ ጽድቅ በርእሰ አንቀጹ በጥቅ ምትና በኅዳር 1999 ዕትም፣ መጽሔተ ተልእኮ ዘማኅበረ ቅዱሳን በምንለው የማኅበሩ የሕዝብ ግንኙነት መጽሔት በነሐሴ 2004 ዓ.ም ዕትም በዚሁ ጉዳይ ያለውን አቋም ገልጿል፡፡  

ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ “አክራሪነት” እንዳለና አልፎ አልፎም “ማኅበረ ቅዱሳን” ብለው በስም ጠቅሰው ለመፈረጅ የሞከሩ በአንዳንድ አካባቢ ያሉ መንግሥት ያዘጋጀውን የውይይት መድረክ የተጠቀሙ አስፈጻሚዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ አልፎ አልፎ መንግሥት “አክራሪነት”ን ለመከላለከል ለሚወስዳቸው እርምጃዎች አጋዥ የሚሆን ውይይት በየደረጃው በሚያደርግበት አጋጣሚ የማኅበረ ቅዱሳንን ስም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ይታያል ላሉት “አክራሪነት” ማሳያ አድርገው ማቅረባቸው ለማኅበሩ አባላት ደስ የሚያሰኝ አልነበረም፡፡

“አክራሪነት” ከላይ በጠቀስነው እሳቤ መሠረት የሚታይ ከሆነ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ላሳዩት የ‹‹አክራሪነት›› ጠባይ ግልጽና ተጨባጭ ማስረጃ ማቅረብ ያሻል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ ቀደምም ከማንም በፊት በሀገራችን የአክራሪነት ዝንባሌዎች እንዳሉ በማመልከት በኩል ግንባር ቀደም ሚና ተጫውቷል፡፡ “አክራሪዎች” በተለያዩ አካባቢዎች አብያተክርስቲያናትን ሲያቃጥሉ ክርስቲያኖችን ሲያርዱ አካሔዱ መልካም አለመሆኑን በመጠቆም እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ በማሳሰብ ሀገራዊ ሓላፊነቱን ለመወጣት ሞክሯል፡፡ የሃይማኖቶች መከባበር በመላው ሀገሪቱ እንዲሰፍን ያለውን ቁርጥ አቋምም አንጸባርቋል፡፡

በእርግጥ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተክርስቲያናችን ጠንካራ የአስተዳደር፣ የአሠራር፣ የአገልግሎት አካሔድ እንዲኖራት አቋም ይዞ የሚያገለግል ማኅበር ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ካህናትና ምእመናን ሁሉ የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቃል አክብረው፤ የሐዋርያትን የሊቃውንት አባቶችን የሃይማኖት ትምህርት፣ ሥርዓት፣ ታሪክና ትውፊት አውቀው እንደ ሃይማኖቱ ሕግና ሥርዓት እንዲመላለሱ ያተጋል፡፡ የተዘጉ አብያተ ክርስቲ ያናት እንዲከፈቱ፣ ሊቃውንቱ በረሃብ በችግር ተፈተው ከአገልግሎት እንዳይቦዝኑ ለማድረግ ይተጋል፡፡ የሌላ ቤተእምነት ተከታዮች በቤተክርስቲያን ትምህርት ላይ ለሚያነሧቸው ጥያቄዎች መልስ በመስጠት የዕቅበተ እምነት ሥራ ይሠራል፡፡

 

በኮሌጅና በዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ ያሉ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ካደጉበት መንደር /ቀዬ/ ርቀው ወደ ተለያዩ ትምህርት ተቋማት ሲመጡ በአቅራቢያ በሚገኙ አጥቢያዎች ሰብስቦ በሃይማኖታቸው ተጠብቀው እንዲኖሩ፣ በመልካም ሥነምግባር ታንጸው ሀገራቸውንና ቤተክርስቲ ያናቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ፣ ከሱስና ከዝሙት ተጠብቀው ከደዌ ሥጋ ደዌ ነፍስ እንዲርቁ ያደርጋል፡፡ በጠረፋማ አካባቢዎች ስብከተ ወንጌልን ያስፋፋል፡፡ በጤናና ትምህርት ጉዳዮችም በማኅበራዊ አገልግሎት ተሳትፎ እንዲኖረው እየጣረ ነው፡፡ እነዚህ ተግባራቱ ሁሉ ከቤተክርስቲያኒቱ የአገልግሎት መንፈስ የተቀዱ ናቸው፡፡ ለየትኛውም ወገን ቢሆን የሚጠቅሙ እንጂ ስጋት የሚሆኑ ተግባራት አይደሉም፡፡ በሃያ ዓመት የአገልግሎት ቆይታውም ያስመዘገባቸው ውጤቶች በስጋት ሳይሆን በአስፈላጊነት ሊያስፈርጀው የሚችል ነው፡፡

ስለዚህ የትኛውም ወገን ቢሆን እውነታውን ለመረዳት ጥረት ማድረግ ይገባዋል፡፡ ቸግሮች አሉ ቢባሉ እንኳን ተገቢነት ከሌላቸው ዘመቻዎች ቆጠብ ብሎ ከቤተክርስቲያኒቷ አባቶችና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር አግባብነት ያላቸው ውይይ ቶችን ማድረግ በቂ ይሆናል፡፡ ማኅበሩ የቤተክርስቲያኒቱ ሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤት የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲሠራ ከሰጠው ተግባራት ውስጥ ወደ ‹‹አክራሪነት›› አምባ ያስገባውን ወሰን አለፈ ያስባሉትን ነጥቦች ነቅሶ ማሳየት፣ እንዲህ የሚያስብሉ የተፈጸሙ ተግባራትንና ተግባራቱን ማኅበሩ ሓላፊነት ወስዶ የፈጸመው ተግባር መሆኑን የሚያሳዩ ማስረጃዎችን ማቅረብ አግባብ ይሆናል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ሁልጊዜም ቢሆን የሃይማኖት አባቶች የሚያዙትን እንጂ ከዚያ ተላልፎ በራሱ ፈቃድ የሚፈጽመው አንዳችም ተግባር አለመኖሩን መረዳት ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 4 ነሐሴ 2005 ዓ.ም.

 

debre tabor

የምሥጢር ቀን

ነሐሴ 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐ ኮነ መላክ  
በምዕ/ጐጃም ሀገረ ስብከት የ፬ቱ ጉባኤያት መምህር

debre taborየአምላክ ሰው መሆን አንዱ ምክንያት ምሥጢረ መለኮት ለተሰወረበት ዓለም ምሥጢረ መለኮትን መግለጥ ነው፡፡ ክፉውንና ደጉን ለይቶ ከሚያስታውቀው ዛፍ የተነሳ ከ8ኛ መዐርግ  ላይ ሆኖ በመፈጠሩ የተሰጠውን ከፍተኛ የዕውቀት ፀጋ ክፉ ዕውቀት ስለተጨመረበት ለነፍሱ ምሥጢረ መለኮትን ማወቅ የሰው ልጅ ተስኖት ነበር ፡፡ ጌታችን ወደዚህ ዓለም ሲመጣ  ዓለም ምንም ምሥጢር የላትም ነበር፡፡ ምሥጢራት ሁሉ በልበ መለኮት ተሰውረው ይኖሩ ነበር እንጂ፡፡ በሌላ አነጋገር የተፀነሰ ምሥጢር እንጂ የተወለደ ምሥጢር አልነበረም ማለት ነው፡፡ ለዚህ አይደል መድኀኒታችን እየሱስ ክርስቶስ  ለደቀ መዛሙርቱ ከሕዝብ ለይቶ ምሥጢራትን ይነግራቸዉ የነበረው ማቴ.13 ፥11፡፡ በቀዳማዊው ሰው በአዳም በኩል ለሰው ልጀች ሁሉ የተሰጠው የመንግሥቱ ምሥጢር ዳግም በሁለተኛው ሰው በክርስቶስ በኩል ካልተገለጠ በሌላ በምን ይገለጣል!!  ለዚህም በአብ ልብነት ተሰውሮ ይኖር የነበረው ብቸኛ ምሥጢር እርሱ ሆኖ  ሳለ ከልደቱ ጀምሮ የመንግሥቱን ምሥጢር በብዙ መንገድ ገለጠ፡፡

ሐዋርያው ጳውሎስ እንደተናገረው ለቀደሙት ሰዎች በብዙ መንገድ በብዙ ኅበረ አምሳል ምሥጢራትን ይናገር  የነበረ እግዚአብሔር አወጣጡ ከጥንት በሆነውና  ተቀዳሚ ተከታይ በሌለው በአንድ ልጁ  በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ተናገረን ዕብ 1፥1-2 ፡፡ ማንም ያየው የሌለ እግዚአብሔርነቱን ወደ ዓለም መጥቶ ተረከው፡፡ በልደቱ ቀን ከገለፀልን የተነሳ “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት” ብለን ዘመርን፡ እግዚአብሔር ገለጠልን፡፡ “ይህንን ምሥጢር እናይ ዘንድ ኑ! እስከ ቤተልሔም እንሒድ” ሉቃ.2፡15 ብለው ሲናገሩ ከእረኞች አፍ መስማታችንስ ልደቱ ሊያዩት የሚገባ ምሥጢር መሆኑን የሚያሳይ አይደል፡፡ የሶርያው ሊቅ ቅዱስ ኤፍሬም ይህን ሲያፀናልን “ንዑ ርዕዩ ዘንተ መንክረ ይህን ድንቅ ምሥጢር ታዩ ዘንድ ኑ!” በማለት ምሥጢርነቱን በማወጅ ሕዝቡን ይጠራል፡፡

በሰው ሊገለጥ ያለው ምሥጢር ይህ ብቻ  አልነበረም፡፡ በቤተ ኢያኢሮስ በአደረገው የማዳን ሥራ ምሥጢረ ድኅነትን፤ በቤተ አልዓዛር በአደረገው ሞትን የማሸነፍ ሥራ ምሥጢረ-ትንሣኤ ሙታንን፤ ወዙ እንደ ደም ወይቦ እስኪወርድ ድረስ በጌቴ ሴማኒ ምሥጢረ ጸሎትን ካሳየ በኋላ ደገኛውን ምስሥጢር በዕለተ አርብ መጋረጃው ተቀዶ የሰው ልጅ ባሕረ እሳትን ተራምዶ እስክናይ ድረስ ታላቅ ምሥጢርን በደብረ ታቦር ገለጠልን፡፡

ጌታ ሊገልጠው የፈለገውን ማንኛውንም ምሥጢር ሦስት ነገሮችን መምረጥ የሁልጊዜ ተግባሩ ነው፡፡ ምሥጢሩን የሚገልጥበት ቦታ፣ ጊዜ እና ሰው ናቸው፡፡ በደብረ ዘይት የገለጠውን በደብረ ታቦር፣ በጌቴ ሴማኒ የገለጠውን በዮርዳኖስ፤ ለነቢያት የገለጠውን ለሐዋርያት አይገልጠውም፡፡  በተለይ በሐዋርያት ልቦና ቆልፎ ያኖረውን ከሁሉም በላይ ደግሞ በእመቤታችን ልቦና የሰወረውን ምሥጢሩን ማን ያውቀዋል?? አበው እንደነገሩን በልበ ሐዋርያት ተሰውሮ የቀረውን የወንጌል ምሥጢር እስከ ዓለም ፍፃሚ  የሚያውቀው የለም ብለውናል፡፡  ምክንያቱም የሐዋርያትን ክብር ከላገኙ ሐዋርያት ያወቁትን ማወቅ ስለማይቻል ነው፡፡ ከሐዋርያት በኋላ ተነስቶ  ወደ ሐዋርያት መዐርግ  መድረስ ከተቻለው ከቅዱስ ጳዉሎስ በቀር የተሳካለት ማንም የለም፡፡ ዛሬ ክብር ይግባውና መድኃኒዓለም ክርስቶሰ በደቀ መዛሙርቱ ልብ ሊያስቀምጠው የፈለገው አንድ ታላቅ ምሥጢር አለው በጊዜው ጊዜ የሚነገር ከትንሣኤ በኃላ በሚዘከር እንጂ በማንኛውም  ጊዜ የማይነገር አዲስ ምሥጢር ነው፡፡ ታዲያ ለዚህ ታላቅ ምሥጢር መገለጫ ትሆን ዘንድ የተመረጠችው ደግሞ ደብረ ታቦር ተራራ ናት ፡፡

ደብረ ታቦር ለምን ተመረጠ?
1.    ትንቢቱ፤ ምሳሌው ሊፈፀም፡-  
በቀደመው ዘመን ነቢያት ትንቢት ከተናገሩላቸዉ ቅዱሳት መካናት አንዱ ደብረ ታቦር ነው፡፡ ነቢዩ ዳዊት በመዝሙሩ “ታቦር ወአርሞንኤም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ ታቦርና አርሞንኤም በአንተ ስም ደስ ይላቸዋል” መዝ፡ 188÷12 በማለት ከደብረ ታቦር እስከ አርሞንኤም በደረሰው የመለኮት ብርሃን የተፈጠረውን ደስታ ሲገልጥ እንሰማዋለን፡፡ ምንድን ነው ይህ ደስታ? ሊባል ይችላል፡፡ ነብዩ ከአንድ ሺህ ዓመት በኋላ ስለሚደረገው ተራሮችንና ኮረብቶችን ሳይቀር ያስፈነደቀ ደስታ በእውነት ይህን ተናገረ፡፡ ምናልባት “በአንተ ስም ደስ ይላቸዋል” ብሎ ለሰው በሚናገር መልኩ ግዑዛን ለሆኑ ተራሮች መናገሩ ሊያስገርም ይችል ይሆናል፡፡  የሰው የደስታው መገለጫ የገፁ ብሩህነትም አይደል? እነዚህም ተራሮች በዚህ ዕለት በተገለጠው የመለኮታዊ ክብሩ ነፀብራቅ ጨለማ ተወግዶላቸዉ የፀሐይን ብርሃን በሚበዘብዘው አምላካዊ ብርሃን፣ ብርሃን ሆነው የዋሉበት ቀን ነውና ነቢዩ ለሰው በሚናገርበት ግስ ይናገርላቸዋል፡፡ ሌላም ምሥጢር አለው ይላሉ ሊቃውንቱ፡፡

 

በተራሮች ስም የተጠሩት ልዑላኑ የጌታ ደቀ መዛሙርት ነቢያትና ሐዋርያት እና ልዑላኑ አገልጋዩችህ በጌታ ስም ደስ ይላቸዋል ማለት ነው ብለውታል፡፡ ምሳሌ በአባቶቻችን ዘመን በዚህ ቅዱስ ተራራ ጽኑ ሰልፍ እንደተደረገ የመሳፍንቱ ታሪክ በተፃፍበት መጽሐፍ እናነባለን መሳ.4 ፥1፡፡ በእሥራኤል ላይ ገዥ ሆኖ የተነሣው በክፉ አገዛዙም ምክንያት እሥራኤልን ያስለቀሰው አሕዛባዊው የሠራዊት አለቃ ድል የተነሳው በዚሁ ሥፍራ ነበር፡፡ ደብረ ታቦር 9 የብረት ሠረገሎች የነበሩትን ባለ ሠራዊት ሰው ሲሳራን ድል ለማድረግ ምቹ ቦታ ነበር፡፡ ያውም በጥቂት ኃይል በሴቲቱ ነብይት በዲቦራ በሚመራ የጦር ሰራዊት ፡፡ ይህ በእውነት በኋለኛው ዘመን ለሚደረገው የድል ዘመን ጥላ አባቶቻችንን በብረት በትር ቀጥቅጦ የገዛውን ባለ ብዙ ሠራዊት ዲያብሎስን ከሴቲቱ ነብይት የተወለደው የይሁዳ አንበሳ ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ቅዱስ ሥፍራ ድል እንደሚያደርግላቸዉ እሥራኤል ዘነፍስም ነፃ እንደሚያወጣቸው የሚያሳይ ምሥጢር ነበረው፡፡ ሲሳራን፤ ባራቅ እና ዲቦራ ድል ያደርጉታል ተብሎ ታስቦ ነበርን ? ይልቁንም ሲገዛን ሊኖር አስቦ አልነበረምን? የድንግል ልጅ መድኀኒታችን ክርስቶስ ግን የሲዖልን በሮች ሰብሮ ጠላታችንን በጽኑ ሥልጣን አስሮ እኛን ነፃ አወጣ፡፡ ታዲያ ምሳሌው አማናዊ የሚሆንበትን ዘመን መድረሱን ሊያበስራቸዉ ወደ ደብረ ታቦር ወጣ፡፡ 

2.     ደብረታቦር ሁሉን የሚያሳይ ቦታ ስለነበር፡-
ደብረ ታቦር ሆኖ ዓለምን ቁልቁል መመልከት ይቻላል፡፡ የተራራው ጫፍ ላይ ሆኖ  ሲመለከቱ ሁሉም ግልጥ ነው ፡፡ ለዚህ ነው ቅዱስ ዼጥሮስ  በዚህ ቦታ መኖርን የተመኘው “ሰናይ ለነ ሀልወ ዝየ- በዚህ መኖር መልካም ነው” (ማቴ.17÷5) ሲል ነበር ፍላጐቱን የገለጠው፡፡  ከሁሉ በላይ ሆኖ ሁሉን እያዩ ሚኖሩበት ከፍ ያለ ቦታ ነውና፡፡ እግዚአብሔር ግን ይህንን በምሥጢር አደረገ፡፡ ከዘመናት አስቀድሞ የተሰወረውን ምሥጢር ለሁሉ ግልጽ ሊያደርግ አስቦ ሁሉን ወደሚያሳየው ቦታ ወሰዳቸዉ፡፡ በክርስቶስ ሰው መሆን ያልታየ ምሥጢር ያልተገለፀ ድብቅ ነገር የለምና፡፡  ለዚህ አፈ- በረከት ተብሎ የሚጠራው ቅዱስ ኤፍሬም በረቡዕ ውዳሴ ማርያም ላይ “የማይታወቅ ተገለጠ የማይታይ ታየ” ሲል የተናገረው፡፡ አሁን  የማይታየውን እግዚአብሔርን የምናይባት ድብቁን የእግዚአብሔርን ነገር በእምነት የምናስተውልባት አማናዊቷ የታቦር ተራራ ቤተ ክርስቲያን፡፡ በእርሷ ውስጥ የሚኖሩ ሁሉ ዓለምን ቁልቁል እየተመለከቱ ጣዕሟን ሲንቁባት ይኖራሉ፡፡ ከሷ ተለይቶ ከላይ ሆነው ከተራራው ጫፍ ስለሚመለከቷት ቤታቸዉን በተራራው ለማድረግ ይመኛሉ፡፡ ሁልጊዜም “እግዚአብሔርን አንዲት ልመና ለመንሁት እሷንም እሻለሁ በህይወቴ ዘመን ሁሉ በእግዚአብሔር ቤት እኖር ዘንድ” መዝ ፡ 26፡4  እያሉ ይዘምራሉ፡፡ ምክንያቱም በዚህ ዓለም ውስጥ ሁኖ ታቦርን ማየት አይቻልም፡፡ በታቦር ላይ ሆኖ የዓለምን ምሥጢር ማወቅ  ይቻላል፡፡ 

3.    በተራራ የተነጠቅነውን ፀጋ በተራራ ለመመለስ
አዳም እንደ አጥቢያ ኮከብ የሚያበራ ግርማው የሚያስፈራ ብርሃናዊ ፍጡር እንደ ነበር፤ ስነ ተፈጥሮውን የሚናገሩ መጽሐፍት ምስክሮቻችን ናቸዉ፡፡ ይህንን ብርሃናዊ የፀጋ ልብሱን ተጐናጥፎ የተቀመጠው በእግዚአብሔር ተራራ በገነት ነበር፡፡ ከመጀመሪያው ጀምሮ የጠላት ዐይን አርፎበት ኖሮ ከጥቂት አመታት በኃላ ይህን ብርሃናዊ ልብሱን ለብሶ እንደ ማለዳ ኮከብ ሲያበራ መኖር አልተቻለውም፡፡ እናም በዚያው በእግዚአብሔር ቅዱስ ተራራ ላይ ሳለ ይህን ፀጋውን ባለማወቅ ተገፈፈ፡፡ የክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መምጣት የተቀማነውን ለማስመለስ አይደል፡፡ ስለዚህም በዚህ ቅዱስ ተራራ ላይ ለደቀ መዛሙርቱ በገለጠው ብርሃን ላይ ተስፋን አስጨበጠን፡፡ ቅዱስ ወንጌል እንደተናገረው በዚህ ዕለት ሐዋርያት ነቢያት በተገኙበት በዚህ ሥፍራ የክርስቶስ ሦስት ክንድ ከስንዝር አካሉ ብሩህ ሆነ፤ ልብሱም ከበረዶ ይልቅ ነጭ ሆነ፡፡

 

የሰው ልጅ ከቅዱስ ተራራ ከገነት ከወጣበት ጊዜ ጀምሮ እንዲህ ሆኖ  አያውቅም፡፡ ሰውነቱ በኀጢያት በልዞ በበደል መግነዝ ተገንዞ የሚያስቀይም መልክ ነበር እንጂ እንደዚህ የአማልእክት ልጆችን አይነት መልክ መች ነበረው? ዛሬ ግን  እንደዚያ አይደለም፡፡ የአዳም አካል መልኩ ተለውጧል፡፡ ከጥቁረቱ ነጥቷል፡፡ ወንጌላውያን ይህን ሲገልጡት “ወተወለጠ ራዕዩ በቅድሜሆሙ፣ መልኩ በፊታቸዉ ተለወጠ” ማቴ17፥2፤ማር 9፥2፡፡ ኢትድጵያዊ ቄርሎስ ተብሎ የሚጠራው የሀገራችን ሊቅ ቅዱስ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ይሄን ሲተረጉም ክርስቶስ በዚህ ዕለት የተገለጠው አዳም ከበደል በፊት በነበረው መልኩ እንደነበረ መጽሐፈ  ምስጢር በተሰኘው  ድርሳኑ ይናገራል፡፡ ያማ ባይሆን ኖሮ ደብረ ታቦር እንደምን ልፍረስ አልፍረስ አላለችም፡፡ ምክንያቱም ሊጦን በተሰኘው ምስጋናችን ውስጥ ስለእግዚአብሔር ስንናገር የምንለውን እናውቃለን፡ “ዘይገሥሶሙ ለአድባር ወይጠይሱ – ተራሮችን በእጁ ሲዳስሳቸው የሚጤሱት” ብለን አይደል የምናመሰግነው፡፡ 

ታቦር ታዲያ እንደምን አልተናወጠችም? ለሙሴ እንኳን በተገለጠበት በዚያ በመጀመሪያው ተራራ የተደረገው እንደዚህ አልነበረም፡፡ ሕዝቡ የሚደርሱበትን አጥንው  እስኪንቀጠቀጡ ድረስ  ከባድ የመብረቅና  የነጐድጓድ  ድምፅ  በተራራው ላይ  ነበር ዘጸ.19÷18፡፡ የዛሬው ግን ከዚያ  ልዩ ነው፡፡ ምንም እንኳን ከተገለጠው ክብር የተነሳ በዙሪያ የነበሩትን እንደ በድን ያደረገ የብርሃን ነፀብራቅ ቢኖርም ቅሉ ለቀደመው ሰው ለአዳም ከመርገም በፊት የነበረውን የፀጋ ግርማ ሞገስ የሚያሳይ ነው እንጂ ሌላ ምን ይሆናል? አብርሃም ዮርዳኖስን ተሻግሮ የተገናኘውን ሰው የመልከጸዴቅን ግርማ በአይኖቹ መመልከት አልችል ብሎ መልከጸዴቅ ቀርቦ እስኪያነሳው ድረስ በፊቱ እንደ በድን ሆኖ የወደቀ አይደለምን? ከእግዚአብሔር ይነጋገር የነበረው የሙሴን ፊት ማየት ተስኗቸዉ የእስራኤል ልጆች አልፈሩምን? ይህማ ምን ይገርማል በእውነቱ ይህ ሁሉ የሆነው በቅዱሱ የእግዚአብሔር ተራራ በገነት የተነፈግነው ልጀነታችንን የሚያስፈራና የሚያስደነግጥ ግርማ ሞገሳችንን እንደመለሰልን ለማጠየቅ ነው፡፡ በመጀመሪያው ሰው ያጣነው የልጅነት መልካችንን በሁለተኛው ሰው አገኘነው፡፡

ዛሬ እስከ ዓለም ፍፃሜ ድረስ በቤተ ክርስቲያን በኩል ይህ ዕድል ሲታደል ይኖራል፡፡ ወንዶቹ በ4ዐ ቀን ሴቶቹ በ8ዐ ቀን ወደ ቤተ ክርስቲያን መጥተው በማየገቦ ተጠምቀው ዳግመኛ ከብርሃን ተወልደው ሰይጣንን የሚያስደነግጥ መልክ ይዘው እንደሚመለሱ በፍትሕ መንፈሳዊ በ3ኛው አንቀጽ ተመዝግቧል፡፡

ያስተውሉ!! ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት፡፡ በደብረ ታቦር ነቢያትና ሐዋርያት  መዐስባንና ደናግል፣ አረጋውያንና ወጣቶች እንደተገኙ ሁሉ ቤተ-ክርስቲያንም በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ የታነፀች ናት፡፡ ለመዐስባንና ለደናግል፣ ለአረጋውያንና ለወጣቶች የተዘጋጀች የእግዚአብሔር መገለጫ ተራራ ነቸ፡፡ ከነቢያት 2ቱ ከሐዋሪያት 3ቱ መገኘታቸዉ ዛሬ በቤተ መቅደስ የሚያገለግሉት አምስት ልዑካን ምሳሌ ነው፡፡ እነዚያ ክርስቶስን እንደ  ታቦት በመሀል አድርገው ነበር የተገኙት፡፡ በቤተክርስቲያንም በቃል ኪዳኑ ታቦት ዙሪያ የክብሩን ዙፋን ከበው የሚቆሙት አገልጋዮች  በነዚያኞቹ አምሳል  የቆሙ ናቸው፡፡

egy fir

በግብፅ አብያተ ክርስቲያናትና ክርስቲያኖች የጥቃት ሰለባ እየሆኑ ነው

ነሐሴ 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

egy firየፕሬዚዳንት ሙሐመድ ሙርሲ ደጋፊዎች የሆኑት የሙስሊም ወንድማማቾች በግብፅ ኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንና ክርስቲያኖች ላይ ከፍተኛ ጥቃት እየፈጸሙ እንደሚገኙ ዓለም አቀፍ የመረጃ ምንጮች በመግለጽ ላይ ናቸው፡፡ በተለይም በዲልጋ፤ ሚና፤ እና ሶሃግ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት የጥቃቱ ሰለባ እየሆኑ ነው፡፡ የሚና ቅድስት ማርያምና የአብርሃም አብያተ ክርስቲያናት የሙስሊም ወንድማማቾችና ደጋፊዎች በእሳት አያይዘዋቸዋል፡፡ ተቀጣጣይ ፈንጂዎችንም ሶሃግ በሚገኘው ማር ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ላይ ወርውረዋል፡፡

ከካይሮ የሚወጡ አዳዲስ መረጃዎች እንደሚያመለክቱት በአንዳንድ አብያተ ክርስቲያናት ላይ የአልቃይዳ መለያ የሆነው ጥቁር ባንዲራ እየተሰቀለባቸው ሲሆን በተለይም የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ይገኝበታል፡፡

በላይኛው ግብፅም በርካታ አብያተ ክርስቲያናት እየተቃጠሉና ጥቃት እየደረሰባቸው ሲሆን ክርስቲያኖችም መገደላቸውን ከግብፅ የሚወጡ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ የኮፕት ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ታዎድሮስ ከመንበረ ፓትርያርክ ቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ለመውጣት መገደዳቸውንም እነዚሁ ምንጮች ይገልጻሉ፡፡
አልጀዚራ እንደዘገበው ሊቢያዊው ታማር ረሻድ የተባለው ተቃዋሚ “ለፓትርያርክ ታዎድሮስ መልካም ዜና ልነግራቸው እፈልጋለሁ፡፡ በግብፅ ምድር ክርስቲያኖችና አብያተ ክርስቲያናት የማይኖሩበት ጊዜው ደርሷል” በማለት ለቴሌቪዥን ጣቢያው ሲናገር ተደምጧል፡፡

በላይኛው ግብፅ ከሚገኙት ሚና፤ አስዩትና ሶሃግ በተጨማሪ የክርስቲያኖች መኖሪያና የሥራ ቦታዎች በእሳት ተያይዘዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ሕይወታቸው አደጋ ላይ ወድቋል፡፡ አብያተ ክርስቲያናቱም አገልግሎታቸውን ማቋረጣቸውን ዓለም አቀፍ የዜና ምንጮች እየዘገቡ ይገኛሉ፡፡