«በህልምም ተረድቶ ወደገሊላ ሀገር ሄደ፤……. ናዝሬት ወደምትባልም ከተማ መጥቶ ኖረ»

ሕዳር 6 ቀን እመቤታችን ጌታን ይዛ ከግብጽ /ከስደት/ ወደ ኢየሩሳሌም መመለሷ ይታሰባል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቀጥሎ ካለው የማቴዎስ ወንጌል ምንባብ በመነሳት ይህንን አስመልክቶ በማቴዎስ ወንጌል ትርጓሜው ላይ ያስተማረውን ትምህርት እናቀርባለን፡፡
«ሄሮድስም ከሞተ በኋላ እነሆ የጌታ መልአክ በግብጽ ለዮሴፍ በህልም ታይቶ የሕፃኑን ነፍስ የፈለጉት ሞተዋልና ተነሳ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ አለው፡፡ ዮሴፍም ተነስቶ ሕፃኑንና እናቱን በመያዝ ወደ እስራኤል ምድር ተመለሰ፤ ነገር ግን አርኬላዎስ በአባቱ ፈንታ በይሁዳ መንገሱን በሰማ ጊዜ ወደዚያ መሄድ ፈራ፤ በህልምም ተረድቶ ወደገሊላ ሀገር ሄደ፤ በነቢያት ናዝራዊ ይባላል የተባለው ይፈጸም ዘንድ ናዝሬት ወደምትባል ከተማ መጥቶ ኖረ» /ማቴ. 2-19-23/፡፡

ዮሴፍ የሕፃናቱ ገዳይ መሞቱን ሰምቶ ከስደት ተመልሶ ወደ ሀገሩ ተመልሶ መጣ፡፡ ነገር ግን ገና እግሩ ሀገሩን እንደረገጠ በድጋሚ የቀደመውን አደጋ ቅሪት /ተረፍ/ አገኘ፤ የክፉው ገዢ ልጅ ንጉስ ሆኗል፡፡

ሄሮድስ በንጉስነት የሚመራትን ሀገር /እስራኤልን/ ለሦስት ከፋፍሎ ሦስቱ ልጆቹ በእርሱ ስር ሆነው በሀገረ ገዢነት እንዲመሯት አድርጎ ነበር፡፡ እርሱ ከሞተ በኋላ ቆይተው እነዚህ ልጆቹ መንግስቱን ለሦስት ተካፍለውታል፡፡ የበላይ ንጉስም አልነበረም፡፡ አሁን ግን ሄሮድስ ገና መሞቱ ስለሆነ መንግስቱ ገና አልተከፋፈለምና ልጁ አርኬላዎስ ለጥቂቱ ለጊዜው መንግስቱን ተቀብሎ ንጉስ ሆነ፡፡

ዮሴፍ በአርኬላዎስ ምክንያት ይሁዳ መቀመጥ ከፈራ /ቤተልሔም የምትገኘው በይሁዳ ነው/ በወንድሙ በሄሮድስ አንቲጳስ ምክንያት ናዝሬት መቀመጥን ለምን አልፈራም? /ናዝሬት የምትገኘው የሄሮድስ አርኬላዎስ ወንድም ሄሮድስ በአንቲጳስ በሚገዛት በገሊላ ነው/ ይህ በቂ ምክንያት አይሆንም?

ቦታውን በመቀየር ጉዳዩ እንዲሸፈን፣ እንዲረሳ ለማድረግ ነው፡፡ ምክንያቱም ጥቃቱ / ግድያው/ ሙሉ በሙሉ የተካሄደው «በቤተልሔምና በአውራጃዋ» ነው /ማቴ. 2-6/፡፡ ስለዚህ ግድያው ከተፈፀመ በኋላ ወጣቱ አርኬላዎስ የሚያስበው ሁሉም እንደተፈፀመ እና እርሱም /ጌታም/ ከብዙዎቹ ሕፃናት ጋር አብሮ እንደተገደለ ነው፡፡

ስለዚህ ዮሴፍ ወደ ናዝሬት መጣ፡፡ በአንድ በኩል አደጋውን ለማስቀረት፤ በሌላ በኩል ደግሞ በቀድሞ /native/ ቦታው ለመኖር፡፡ ተጨማሪ ድፍረት እንዲሆነውም በጉዳዩ ላይ ከመልአኩ ምክር ተሰጠው፡፡ «በህልምም ተረድቶ ወደ ገሊላ ሀገር ሄደ»

ታዲያ ቅዱስ ሉቃስ ወደ ናዝሬት የሄዱት እንዲህ ባለ መልኩ ነው ለምን አላለም? ምክንያቱም ከጌታችን ልደት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም እንደሄዱ ከነገረን በኋላ እንዲህ ይላል፡፡ «በዚያም በእግዚአብሔር ሕግ የተጻፈውን ሁሉ ከፈጸሙ በኋላ ወደ ገሊላ ከተማቸው ወደ ናዝሬት ተመለሱ » /ሉቃ. 2-39/ ወደ ናዝሬት የሄዱት ከግብጽ ሲመለሱ መሆኑን አይነግረንምን?

ቅዱስ ሉቃስ እየተናገረ ያለው ወደ ግብጽ ከመውረዳቸው በፊት ካለው ጊዜ ነው፡፡ ምንም ነገር ከህጉ ውጭ እንዳይፈጸም ከጌታችን ልደት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ሄደው ሕጉ የሚያዘውን ሁሉ ፈጽመዋል፡፡

«እንደ ሙሴ ህግ የመንጻታቸው /ማለትም 40 ቀን/ በተፈጸመ ጊዜ በጌታ ሕግ የበኩር ልጅ ወንድ ልጅ ሁሉ ለጌታ የተቀደሰ ይባላል ተብሎ እንደተጻፈ፣ በጌታ ፊት ሊያቆሙት በጌታም ሕግ ሁለት ዋልያ ወይም ሁለት የርግብ ጫጩቶች እንደተባለ መስዋዕት ሊያቀርቡ ወደ ኢየሩሳሌም ወሰዱት» /ሉቃ.2-21-24/ «ሁሉንም እንደህጋቸው ከፈፀሙ በኋላ ወደ ገሊላ ከተማቸው ወደ ናዝሬት ተመለሱ፡፡ /ሉቃ.1-39/ ጌታ «ኦሪትና ነቢያትን ልፈጽማቸው እንጂ ልሽራቸው አልመጣሁም» /ማቴ.5-17/ እዳለው፡፡ ይህ ከመደረጉ /ሕጉ ከመፈጸሙ/ በፊት ወደ ግብጽ እንዲወርዱ አልሆነም፡፡ ይህ እስኪሆን ተጠበቀ ከዚያ ወደ ናዝሬት ሄዱ፤ ከዚያ በኋላ ወደ ግብጽ እንዲወርዱ፡፡

ግብጽ ደርሰው ከመጡ በኋላ ግን ቅዱስ ማቴዎስ እንደተናገረ መልአኩ ወደ ናዝሬት እንዲወርዱ ያዘቸዋል፡፡ መጀመሪያ ወደ ናዝሬት የሄዱት ግን ትዕዛዝ ተሰጥቷቸው ሳይሆን ቅዱስ ሉቃስ እንዳለው የመኖሪያ ቦታቸው /ከተማቸው/ ስለነበረ ነው፡፡ ምክንያቱም ወደ ቤተልሔም የሄዱት ለሕዝብ ቆጠራው እንጂ እዚያ ለመቆየት አይደለም፡፡ ስለዚህ ቤተልሔም የሄዱበትን ምክንያት ሲፈጽሙ ወደ ናዝሬት ተመለሱ፡፡

ወንጌላዊው ቅዱስ ማቴዎስ ወደ ናዝሬት የሄዱበትን ሌላም ምክንያት ይነግረናል፤ ትንቢት፡፡ «በነቢያት ልጄ ናዝራዊ ይባላል የተባለው ይፈጸም ዘንድ ናዝሬት ወደምትባል ከተማ መጥቶ ኖረ» /ማቴ.2-23/

ይህንን የተናገረው የትኛው ነቢይ ነው» አትጓጉ አትጨነቁም፡፡ ምክንያቱም ከትንቢት ጽሑፎች ብዙዎች ጠፍተው ነበርና፡፡ ይህንንም በመጽሐፈ ዜና መዋዕል ከተመዘገበው ታሪክ ማወቅ እንችላለን፡፡
«የቀረው ፊተኛውና ኋለኛው የሰሎሞን ነገር በነቢዩ በናታን ታሪክ በአኪያ ትንቢት ስለ ናባጥም ልጆች ስለ ኢዮርብዓም ባየው በባለ ራእዩ በኢዩኤል ራእይ የተጻፈ አይደለምን?» እነዚህ ሁሉ ተጽፈዋል የተባሉት ትንቢቶች ግን ዛሬ በእኛ ዘንድ አልደረሱም፡፡

ምክንያቱም አይሁድ ስለ መጻሕፍቱ ቸልተኛ ስለነበሩና በተደጋጋሚ ከአምልኮተ እግዚአብሔር ይወጡ ስለነበር አንዳንዶቹ ጠፍተው ነበር፡፡ ሌሎቹንም ራሳቸው አቃጥለዋቸው ቀዳደዋቸው ነበር፡፡ ሁለተኛው መቃጠላቸው እንደተፈፀመ ነቢዩ ኤርምያስ በትንቢት መጽሐፍ ይነግናል፤

«ንጉሱም /ሴዴቅያስም/ ክርታሱን /የነቢዩ የኤርምያስን ትንቢት የያዘ/ያወጣ ዘንድ ይሁዳን ላከ፤ እርሱም ከጸሐፊው ከኤሊሳማ ክፍል ወሰደው፡፡ ይሁዳም በንጉሱ አጠገብ በቆሙት አለቆች ሁሉ ፊት አነበበው፡፡ ንጉስም በክረምት በሚቀመጥበት ቤት ተቀምጦ ነበር፤ ከፊቱም እሳት ይነድድ ነበር፡፡ ይሁዳም ሦስትና አራት ዐምድ በአነበበ ቁጥር ንጉሱ በብርዕ መቁረጫ ቀደደው፡፡ ክርታሱንም በምድር ውስጥ ባለው እሳት ፈጽሞ እስኪቃጠል ድረስ በምድጃ ውስጥ ወደ አለው እሳት ጣለው፡፡» /ኤር.30-23/

የመጀመሪያውን /መጥፋታቸውን/ በተመለከተ ደግሞ የመጽሐፈ ነገሥት ፀሐፊ የኦሪት ዘዳግም መጽሐፍ አንድ ቦታ ተቀብሮ ተደብቆ ቆይቶ በችግር መገኘቱን ይነግረናል፡፡ «ታላቁ ካህን ኬልቅያስ ፀሐፊውን ሳፋንን የጠፋውን «የሕጉን መጽሐፍ በእግዚአብሔር ቤት አግኝቻለሁ» አለው»፡፡ /2ኛ ነገ.12-8/

ምንም ቀኝ ገዥ ባልነበረበት ጊዜ መጽሐፎቻቸው መጠበቅ እንዲህ ከከበዳቸው በግዞት ስር በነበሩባቸው ዘመናትማ የበለጠ ጥፋት ይኖራል፡፡

አንድ ነቢይ ይህንን ትንቢት በእርግጠኝነት እንደተናገረው ለማወቅ ግን ሐዋርያቱ በተለያየ ቦታ እርሱን ናዝራዊ ብለው መጥራታቸው ማስረጃ ነው፡፡

«ጴጥሮስም «ወርቅና ብር የለኝም፤ ያለኝን ግን እሰጥሃለሁ፤ እነሆ በናዝሬቱ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ተነስተህ ሂድ» አለው» /ሐዋ.3-6/

«እንግዲህ እናንተ ሁላችሁ የእስራኤልም ወገን ሁሉ በናዝሬቱ በኢየሱስ ስም ይህ ሰው እንደዳነና በፊታችሁ በእውነት እንደቆመ እወቁ» /ሐዋ.4-10/

ታዲያ ይህ ስለ ቤተልሔም የተነገረው ትንቢት ላይ ጥላ ማጥላት አይሆንምን? ሊባል ይችላል፡፡ ምክንያቱም ነቢዩ ሚኪያስ ክርስቶስ /መሲሕ/ ከቤተልሔም እንዲወጣ ተናግሯል፡፡ በፍጹም ምክንያቱም መጀመሪያ ነቢዩ ያለው «በቤተልሔም ይኖራል» ሳይሆን ከቤተልሔም ይወጣል» ነው፡፡
ጌታችን በናዝሬት መኖሩ ናዝራዊም መባሉ የሚያስተምረን ታላቅ ነገር አለ፡፡ ይህች ቦታ /ናዝሬት/ በጣም ዝቅተኛ ግምት የሚሰጣት ቦታ ነበረች፡፡ ለምሳሌ ናትናኤል «በውኑ ከናዝሬት ደግ ሰው ይወጣልን?» ብሎ ጠይቋል /ዮሐ. 1/ እንዲሁም የናዝሬት ከተማ ብቻ ሳትሆን አጠቃላይ የገሊላ አውራጃ የተናቀ ነበር፡፡ ስለዚህም ነው ፈሪሳውያኑ «ከገሊላ ነቢይ እንደማይነሳ መርምርና እይ» /ዮሐ. 6-52/ ያሉት፡፡ እርሱ ግን ከእነዚህ ቦታዎች ወጣ መባልን አያፍርበትም ደቀ መዛሙርቱንም የመረጠው ከገሊላ ነው፡፡ ይህም ጽድቅን ገንዘብ ካደረግን /ከሰራን/ አፍአዊ /ውጫዊ/ የሆነ የክብርና የሞገስ ምንጭ እንደማያስፈልገን ለማሳየት ነው፡፡ በዚሁ ምክንያት ለራሱ ቤት እንኳን እንዲኖረው አልፈለገም፤ «የሰው ልጅ ግን አንገቱን የሚያስገባበት የለውም» ብሏል፤ ሄሮድስም በእርሱ ላይ ሴራ ሲጎነጉንበት ተሰዷል፤ ልደቱ በከብቶች በረት ሲሆን የተኛውም በግርግም ነው፤ እናቱ እንድትሆን የመረጠውም በዚህ ምድር መስፈርት ዝቅ ያለችውን ትንሽ ብላቴና ነው፤ ይህ ሁሉ እንዲህ ያሉ ነገሮችን እንደ መዋረድ እንዳንቆጥርና እያስተማረንና ራሳችንን ለመልካም ምግባር ብቻ እንድንሰጥ ግድ እያለን ነው፡፡

ስለዚህ በእነዚሁ ሁሉ ነገሮች «እኔ ለዓለሙ ሁሉ ባይተዋር እንድትሆኑ ሳዛችሁ እናንተ በተቃራኒው በሀገራችሁ፤ በወንዛችሁ በዘራችሁ፣ በአባቶቻችሁ የምትኮሩት ለምንድን ነው?» እያለን ነው፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ምንም ምግባር ሳይኖራቸው በአባቶቻቸው ይመኩ የነበሩትን እንዲህ ብሏቸዋል «አብርሃም አባት አለን በማለት የምትድኑ አይምስላችሁ» /ማቴ.3-9/ ቅዱስ ጳውሎስም እንዲህ ይላል «ከእስራኤል የተወለደ ሁሉ እስራኤላዊ አይደለም፤ ከአብርሃም ዘርም ስለሆኑ ሁሉም ልጆች አይደሉም» /ሮሜ. 8-6-8/

እስኪ ንገሩኝ የሳሙኤል ልጆች እነርሱ የአባታቸውን የመልካም ምግባር ሕይወት ወራሾች ሳይሆኑ፤ በአባታቸው መልካምነት /ታላቅነት/ ምን ተጠቀሙ? የሙሴስ ልጆች የእርሱን ፍጹምነት ሳይደግሙ በእርሱ መልካምነት ብቻ ምን ተጠቀሙ? እነርሱ /የሙሴ ልጆች/ መንግስቱን አልወረሱም፤ ነገር ግን መሪ የነበረው ሙሴ አባታቸው ሁኖ ሳለ መንግስቱ የተላለፈው በምግባሩ የሙሴ ልጅ ለሆነው ለሌላው /ለኢያሱ/ ነው፡፡

ጢሞቲዎስስ የተወለደው ከግሪካዊ አባት መሆኑ /ዕብራዊ አለመሆኑ/ ምን ጎዳው) ወይም የኖህ ልጅ /ከነአን/ ባርያ ሆነ እንጂ በአባቱ መልካም ምግባር ምን ተጠቀመ? ኤሳውስ ቢሆን የያቆብ ልጅ አልነበረምን? አባቱስ በእርሱ ጎን አልነበረምን? አዎ አባቱ እርሱ በረከቱን እንዲቀበል ፈልጎ ነበር፤ እርሱ ለዚህ ብሎ አባቱ ያዘዘውን ሁሉ አድርጎ ነበር፡፡ ነገር ግን ክፉ ስለነበረ እነዚህ ሁሉ ነገሮች አልጠቀሙትም፤ ቀድሞ የተወለደ  ቢሆንም፤ አባቱም በዚህ ረገድ ያሉትን ነገሮች ለማድረግ ከእርሱ ጋር ቢሆንም ፣ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ስላልነበር፣ ሁሉን ነገር አጣ፡፡

ስለ ሰዎች ብቻ ለምን እናገራለሁ አይሁድ የእግዚአብሔር ሕዝቦች /ልጆች/ ነበሩ፤ በዚህ ታላቅ ልደት ግን ምንም አልተጠቀሙም፡፡ እንግዲህ አንድ ሰው የእግዚአብሔር ልጅ ሁኖ ለዚህ የተከበረ ልደት የሚገባ መልካምነት ከሌላው የበለጠ የሚቀጣ ከሆነ ለምን የቅርብ እና የሩቅ አባቶቻችሁን እና አያቶቻችሁን ትቆጥራላችሁ»

ይህ የሚሆነው በብሉይ ኪዳን ብቻ ሳይሆን በሐዲስ ኪዳንም ነው፡፡ ያመኑና የተጠመቁ ሰዎች የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው፤ ነገር ግን ከእነዚህ መካከል ወደ እግዚአብሔር መንግስት የማይገቡ አሉ፡፡ እንግዲህ የእግዚአብሔር ልጅ መሆን እንኳን ያለ ምግባር ብቻውን የማይጠቅም ከሆነ፤ እንዴት ከሰዎች መወለድ ሊጠቅም ሊያኩራራ ይችላል? ስለዚህ ከታላላቅ ሰዎች በመወለድ በሃብት፣ በዘር፣ በሀገር ራሳችንን አናኩራራ፤ ይልቁንም እንዲህ የሚያደርጉትን እንገስጻቸው፡፡ በድሕነትና /ድሀ በመሆንና/ እነዚህን ነገሮች በማጣትም አንዘን፤ እነዚህ ነገሮች በእግዚአብሔር መንግስት አይጠቅሙንምና፤ ይልቁንም የመልካም ምግባር ባለሀብቶች ለመሆን እንጣር፤ . . . .

ምንጭ /Saint Jhon Chrysostome, homily 9 on the Gospel of St. Mathew/

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ጉባኤው ባለ 26 ነጥብ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ አሳለፈ

ለቤተክርስቲያን ልማት የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ተሸለሙ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መንበረ ፓትርያርክ 28ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ባለ 26 ነጥብ የጋራ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ በማቅረብ ተጠናቀቀ፡፡

ከጥቅምት 6-11 ቀን 2002 ዓ.ም ሲካሔድ የሰነበተው ይህ ስብሰባ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳዉሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንት የዓለም ሃይማኖቶች የክብር ፕሬዚዳንት በሀገር ውስጥና በወጪ ሀገር የሚገኙ ሊቃነ ጳጳሳት፣ የየአህጉረ ስብከቱ የሥራ ሓላፊዎች፣ የምእመናንና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች በተገኙበት ነው፡፡

ጉባኤውን በጸሎት የከፈቱት ቅዱስነታቸው፤ የቤተክርስቲያን ዓላማ ሰላም በመሆኑ በሥልጡንና ሰላማዊ በሆነ መንገድ ጉባኤውን ማካሔድ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ «ሰላማዊ በሆነ መንገድ የሚካሔድ ውይይት የጎደለን ይሞላል የተጣመመን ያቃናል» ያሉት ቅዱስነታቸው «ቤተክርስቲያናችንን በልማቱ ለማሳደግ ጠንክሮ መሥራት ያስፈልጋል» በማለት ጉባኤውን አስጀምረዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ የጠቅላይ ቤተክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅና የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በ2001 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተክህነቱና በየአህጉረ ስብከቶች የተከናወኑትን ዐበይት ጉዳዮች የተመለከተውን ዘገባ በንባብ አሰምተዋል፡፡

ዘገባውን ወንጌላዊው ቅዱስ ሉቃስ በሐዋርያት ሥራ በጻፈው መልእክት /ም.5-42/ የጀመሩት ሥራ አስኪያጁ፤ ለቤተክርስቲያን የደም ሥር፣ ለምእመናን የጀርባ አጥንት የሆነው ስብከተ ወንጌልን በስፋትና በአግባቡ እንዲሰበክ፤ ምእመናን በእምነታቸው እንዲጸኑ፣ በሥነ ምግባር እንዲጎለብቱ፣ ከባዕድ ሃይማኖት ራሳቸውንና ቤተሰቦቻቸውን እንዲጠብቁ፣ ሰበካ ጉባኤያት እንዲስፋፉና እንዲጠናከሩ፣ የልማትና የምግባረ ሠናይ ሥራዎች እንዲሠሩ፣ ድህነትና ድንቁርና ከሕዝባችን ጫንቃ እንዲወርዱ ለማድረግ ሁሉም ጥረት ማድረግ ወቅቱ የሚጠይቀው ዐቢይ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል፡፡

ዓመታዊ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በዚህ ሁኔታ ሲካሔድ ሃያ ስምንተኛ ዓመቱን መያዙን የተናገሩት ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ «ጉባኤው ከወጣኒነት ወደ ፍጹምነት መሸጋገር እንደሚኖርበት የሁላችንም እምነት ነው፡፡» ብለዋል፡፡ ስለሆነም መለኪያው ከማእከል እስከ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የሚቀርበው ዘገባና ውጤት ተኮር ሥራ ተሠርቶ ሲገኝ ብቻ መሆኑን አመልክተው፤ ይህ ካልሆነ ግን በየዓመቱ የሚደረገው ስብሰባ ልማዳዊ እንዳይሆን በብርቱ ማጤን እንደሚገባ አስገንዝበዋል፡፡

በመቀጠልም ሥራ አስኪያጁ ለግምገማና ለውይይት እንዲያመች ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ ከመንበረ ፓትርያርከ ጠቅላይ ጽ/ቤት፣ ከየአህጉረ ስብከቱ ጽ/ቤቶች በ2001 ዓ.ም የተከናወነውን የሥራ ክንውን ዘገባ አቅርበዋል፡፡

የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤትን በተመለከተው ዘገባ ቅዱስ ፓትርያርኩ በሀገር ውስጥና በውጪ ሐዋርያዊ አገልግሎትና ልዩ ልዩ የሥራ ክንውኖችን ማድርጋቸውን አመልክቷል፡፡ ከነዚህ  ውስጥ ሐምሌ 22 ቀን 2000 ዓ.ም የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን የቅዱስ ላሊበላን ታሪካዊ መካናት እንዲጎበኙ መደረጉና በኋላም ከቅዱስ አባታችን ጋር ተወያይተው ለቤተክርስቲያናችን አድናቆት መቸራቸው ገልጸዋል፡፡ ነሔሴ 29 ቀን 2000 ዓ.ም ቅዱስ አባታችን የሀገሪቱ ፕሬዚዳንትና ልዩ ልዩ የሀገር ውስጥና የውጪ ሀገር እንግዶች በተገኙበት ከጣሊያን መጥቶ አክሱም በቀድሞ ቦታው በተተከለው የአክሱም ሐውልት ሥነ ሥርዓት ላይ በክብር መገኘታቸው ተጠቅሷል፡፡

በመስከረም 13 ቀን 2001 ዓ.ም በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት በናዝሬት ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን የተሠራውን ሕንፃ መመረቃቸው፣ መስከረም 24 ቀን 2001 ዓ.ም በምዕራብ ሸዋ አምቦ በጃን መንግሥት የተሠራውን ትምህርት ቤት ምረቃ ወቅት መገኘታቸውና መስከረም 16 ቀን 2001 ዓ.ም የሚከበረውን የመስቀል ደመራ በዓል በበለጠ ተጠናክሮ እንዲውል ጉዳዩ ለሚመለከተው አመራር መስጠታቸው በዘገባው ተመልክቷል፡፡

በቅዱስነታቸው ሰብሳቢነት የተመራው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ የተለያዩ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ እንዲያስተላልፍ ሁኔታዎች መመቻቸታቸው፣ በቅዱስነታቸው መመሪያ ሰጪነት ሸንኮራ ዮሐንስን ጨምሮ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙና አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናትና ቅዳሴ ቤት ተገኝተው እንዲከበር መደረጉ ተጠቅሷል፡፡

ልዑል አክሊለ ብርሃን መኮንን ኃይለ ሥላሴ የተባሉ በጎ አድራጊ ለቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ግንባታ የሚውል አንድ ሚሊዮን፣ ለአክሱም ጽዮን ቅድስት ማርያም ቤተመጻሕፍት ወቤተመዘክር የሚውል አምስት መቶ ሺሕ ብር እርዳታ ሲለግሱ ቅዱስነታቸው በመገኘት ርዳታው ለተሰጣቸው ማስረከባቸው በልዩ ጽ/ቤቱ የተሠሩ ዐበይት ጉዳዮች መሆናቸው በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡

በውጪ ሀገርም በቅዱስነታቸው የተመረጡ ልዑካን ከኅዳር 5-16 ቀን 2001 ዓ.ም ድረስ ቦነስአይረስ በተካሔደው ዓለም አቀፍ ጉባኤ ላይ መሳተፍ፣ ከስብሰባው መልስም በሶርያ በመገኘት ከፕሬዝዳንቱ ዶ/ር በሽር አል አሳድ ጋር ስለ ዓለም ሰላም ጉዳይ መወያየታቸው፣ ከሶርያም ወደ ሊባኖስ በመጓዝ በቤሩት በሚገኙ ምእመናን የተገነባውን ቤተ ሳይዳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተክርስቲያን በመገኘት ሕንፃውን ባርከው ቅዳሴ ቤት መክበሩ፤ እንዲሁም ወደ ግብጽ በማምራት ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ሳልሳዊ እስክንድርያ ሊቀ ጳጳስ ጋር በሁለቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት ግንኙነት መወያየታቸው በውጪው ዓለም ካከናወኑት ዐበይት ጉዳዮች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

ስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ በተመለከተ ዋና ሥራ አስኪያጁ ባቀረቡት ዘገባ፤ በዋናው መሥሪያ ቤት ያሉትን ሰባክያነ ወንጌልንና በሰዋሰው ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስ፣ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በአዲስ አበባ የሚገኙትን ጨምሮ በማስተባበር በ26 አህጉረ ስብከት የስብከተ ወንጌል ሥምሪት መደረጉን አስታውቀዋል፡፡

ስበከተ ወንጌልን ይበልጥ ለማስፋፋት እንዲረዳ በደቡብ ኦሞ፣ በሽሬ፣ በደቡብ፣ በሰሜንና በምዕራብ ወሎ፣ በሶማሌ፣ በወላይታና በዳውሮ፣ በጉራጌ፣ በምሥራቅ ሐረርጌ፣ በአዲግራት፣ አክሱም፣ በአፋርና በምሥራቅ ጎጃም አህጉረ ስብከት 1ሺሕ228 ያህል ሰባክያነ ወንጌል መመደባቸውንም ሥራ አስኪያጁ አብራርተዋል፡፡

ገቢና ወጪን አስመልክቶ ከቁልቢ ንዋየ ቅድሳት ማደራጃ ከስብከተ ወንጌል ጉባኤ አንድ በመቶ አስተዋጽኦና ከመጽሔት ሽያጭ 238¸616.77 ገቢ ሲሆን ጠቅላላ ወጪው ደግሞ 238¸325.52 መሆኑን ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ አመልክተዋል፡፡

በሊቃውንት ጉባኤ በኩል በ2001 ዓ.ም ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ ከአምስት የቤተክርስቲያናችን ክፍሎች፣ ከተወካዮች ምክር ቤት እና ከልዩ ልዩ ድርጅቶች፣ ከአራት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናትና አምስት ግለሰቦች የተዘጋጁ በድምሩ 192 የሆኑ በጥልቅ ታይተው እንዲታረሙ የተላኩትን ታላላቅ መጻሕፍት፣ መለስተኛ ጽሑፎችንና ጥያቄዎች ተመ ልክቶ ከአስተያየት ጋር ወደ በላይ አካል መመለሱን እንዲሁም ተጠቃሎ እንዲታተም የተጀመረውን የግእዝ መጽሐፍ ቅዱስ እያመሳከረ በመጀመሪያ የማጣራት ሥራ ላይ እንደ ሚገኝም ሥራ አስኪያጁ አስረድተዋል፡፡

ትምህርትና ማሠልጠኛን በተመለከተ ለ22 አህጉረ ስብከት አብነት ትምህርት ቤቶች አንድ ሚሊዮን 69 ሺሕ ብር፣ ለ14 አህጉረ ስብከት ንባብና ቅዳሴ ቤት 260 ሺሕ ብር፣ ለ21 አህጉረ ስብከት ካህናት ማሰልጠኛ 750 ሺሕ ብር በድምሩ 2 ሚሊዮን 79 ሺሕ ብር መላኩን ገልጸዋል፡፡

በጀትና ሒሳብን አስመልክተው ባቀረቡት ዘገባ ከቤተክርስቲያኒቱ የገቢ ርዕሶች 48 ሚሊዮን 631 ሺሕ 40 ብር ለማስገባት ታቅዶ 45 ሚሊዮን 711 ሺሕ 685 ብር ብቻ እንደተገኘና ከዚህም ውስጥ 39 ሚሊዮን 566 ሺሕ 487 ብር ወጪ ሆኖ በሥራ ላይ እንደዋለ አስረድ ተዋል፡፡

ጠቅላይ ቤተክህነቱ በስድስት መምሪያዎች እና በ10 የጠቅላይ ቤተክህነቱ ድርጅቶች፣ አራት አህጉረ ስብከቶችና የቁልቢ ደብረ ኃይል ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ሒሳብ ተመርምሮ 387 ሚሊዮን 431 ሺሕ 782 ብር ገቢ፣ 344 ሚሊዮን 674 ሺሕ 313 ወጪ ሲሆን አራት ሺሕ 496 ብር ጉድለት መገኘቱን ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ በዘገባቸው አመልክተዋል፡፡

በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ በኩል በ 2001 ዓ.ም ያሬዳዊ ዜማ የካሴትና የመጽሔት ሥርጭትን በተመለከተ ወጥ የሆነ ያሬዳዊ መዝሙር እንዲዘመር ጥረትና እንቅስቃሴ መደረጉን፣ ሐምሌ 5 ቀን 2000 ዓ.ም የተከበረውን የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ 16ኛ ዓመት በዓለ ሲመት ወጣቶችን የማስተባበር ሥራ መሠራቱን፣ ከነሐሴ 1-16 ቀን 2000 ዓ.ም ድረስ በጾመ ፍልሰታ ለማርያም ሱባኤ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በየአብያተ ክርስቲያናቱ በመገኘት ተገቢውን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲሰጡ በመምሪያው በኩል ትእዛዝ መተላለፉን ዘገባው አመልክቷል፡፡

በተጨማሪም ማደራጃ መምሪያው መስከረም 1 ቀን 2001 ዓ.ም የዘመን መለወጫ በዓልን አስመልክቶ የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ የእንኳን አደረሰዎ በዓል ላይ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት አገልግሎት እንዲሰጡ መመሪያ ማስተላለፉንና፣ የመስቀል ደመራ በዓል በደማቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዐት እንዲከበር የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትን በማሠልጠን የሚጠበቀውን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲያበረክቱ ማድረጉን ሥራ አስኪያጁ ጠቁመዋል፡፡

በማኅበረ ቅዱሳን በኩል ደግሞ በዋናው ማዕከል አማካኝነት ብቻ ለ22 ሕዝባዊ ጉባኤያት፣ በዐሥር የተለያዩ የወረዳ ከተሞች ሐዋርያዊ ጉዞ መደረጉን፣ ስብከተ ወንጌል ካልደረሰባቸው ጠረፋማ አህጉረ ስብከት ለተውጣጡ 40 ወጣቶችና በዝዋይና በጅማ ካህናት ማሠልጠኛ 135 ልዑካን ሥልጠና መስጠቱን፣ ትምህርተ ሃይማኖት እና መንፈሳዊ መልእክት የያዙ 325 ሺሕ የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 225 ሺሕ ሐመር መጽሔትና ሰባት ሺሕ ልዩ እትም ሐመረ ተዋሕዶ በ2001 ዓ.ም ማኅበሩ ማሰራጨቱን ሥራ አስኪያጁ በዘገባቸው ገልጸዋል፡፡

በተጨማሪም ማኅበሩ ልዩ ልዩ የቤተክርስቲያን ትምህርት የያዙ ዘጠኝ መጻሕፍትን በአማርኛና ኦሮምኛ ቋንቋዎች አሳትሞ ከ 57 ሺሕ ቅጂዎች በላይ ማሠራጨቱን፣ በድምፅና በምስል ልዩ ልዩ ወቅታዊነት ያላቸውን ጽሑፎች በአማርኛና በእንግሊዚኛ ቋንቋዎች በዌብሳይቱ /መካነ ድሩ/ ማስተላለፉን፣ በሀገር ውስጥ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተከታታይ ትምህርትና ሥልጠና መስጠቱ፣ ለአብነት ትምህርት ቤቶች 300 ደቀመዛሙርት የመሠረታዊ ትምህርትና የስብከት ዘዴ፣ በአፍሪካ፤ በግብጽ፣ በኬንያና በአውሮፓ 11 ከተሞች መምህራንን ልኮ ሐዋርያዊ አገልግሎት መስጠቱን የሥራ አስኪያጁ ዘገባ አመልክቷል፡፡

እንዲሁም ለአብነት ትምህርት ቤቶች ደቀመዛሙርት፣ ለንዋየ ቅድሳትና ለአህጉረ ስብከት ድጋፍ፣ ለቅኔ ትምህርት ማስተዋወቅ፣ በተለያዩ አህጉረ ስብከት ርክክብ ለተደረገባቸው ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያና ገና እየተሠሩ ላሉ ፕሮጀክቶች፣ ለአብያተ ክርስቲያናት በነፃ ለተሠሩ የአሠራር ንድፎች /ዲዛይኖች/ በጠቅላላ ከብር 2 ሚሊዮን 760 ሺሕ 186 በላይ ወጪ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡

በቅርሳ ቅርስ ምዝገባና ጥበቃ በኩልም በበጀት ዓመቱ ብዙ ጥረት መደረጉን በዘገባቸው ያመለከቱት ሥራ አስኪያጁ በቅርሳቅርስ ቀላጤዎች ተሰርቀው የነበሩ መጻሕፍትንና ንዋየ ቅድሳትን ለማስመለስ በተደረገ ጥረት 22 ጥንታውያን መጻሕፍትን፣ 10 የተለያዩ ንዋያተ ቅዱሳትንና ሁለት ጽላቶችን ለማስመለስ መቻሉን አስረድተዋል፡፡

ግምታቸው 223 ሺሕ 780 ብር የሆኑ ባለሥዕል የብራና ተአምረ ኢየሱስ፣ አንድ የብራና ተአምረ ማርያምና አንድ ድርሳነ ሚካኤል መጽሐፍ በፖሊስ ጣቢያ በኤግዚቢት ተይዘው በምርመራ ላይ ስለሆኑ ቅርሶቹ ወደቦታቸው እንዲመለሱም ክትትል እየተደረገ መሆኑን ዘገባው አመልክቷል፡፡

ዋና ሥራ አስኪያጁ የዋናውንና የየአህጉረ ስብከቶቹን የሥራ እንቅስቃሴ በዝርዝር ያቀረቡ ሲሆን በመ ምሪያዎች፣ በድርጅቶችና በ45 አህጉረ ስብከት አሉ ያሏቸውንም ችግሮች ገልጸዋል፡፡

ካጋጠሙ ችግሮች መካከል በጠቅላይ ቤተክህነቱ ያለው የገንዘብ ወጪ ጫና፣ ከየአህጉረ ስብከቱ ለሚዘዋወሩ ሠራተኞች ደሞዝ ከጠቅላይ ቤተክህነት መከፈሉ፣ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ለሚመረቁ ደቀ መዛሙርት የሚመደበው አዲስ በጀትና የተቋማቱ የውስጥ ገቢ አለመፍጠር፣ ከበጀት ውጪ የሚቀርበው የገንዘብ ጥያቄና ከበቂ በላይ ሠራተኞች እያሉ ተጨማሪ ሠራተኞች ያለ ሥራ መመደብና መቅጠር ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በተጨማሪም ወደ ውጪ ሀገርና ሀገር ውስጥም ለአገልግሎት የሚመደቡና የሚላኩትም ወጪያቸው ከዚያው እንዲሸፈን አለመደ ረጉ ይገኙበታል፡፡

የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤን የ 27 ዓመት ጉዞን የሚያሳይ ዐውደ ርእይ የቀረበ ሲሆን ዐውደ ርእዩም በቅዱስ ፓትርያርኩና በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ተባርኮ ተከፍቷል፡፡ ዓውደ ርእዩ ከጥቅምት 6-15 ቀን 2002 ዓ.ም ለዘጠኝ ቀናት ለሕዝብ ክፍት ሆኖ እንደሚቆይ ታውቋል፡፡ ዓውደ ርእዩን የተመለከቱት ተሳታፊዎች በሰጡት አስተያየት የቤተክርስቲያኒቱን ታላቅ ጉባኤ የሚያመለክት በመሆኑ ተጨማሪ የመጎብኛ ጊዜያት እንዲሰጡ ጠይቀዋል፡፡

በስብሰባው ማጠናቀቂያ ላይ ከቤተክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ጎን ለጎን አገልግሎቷን ለማቀላጠፍ በልማቱ ዘርፍ የላቀ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ሀገረ ስብከቶችና አብያተ ክርስቲያናት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡ ለተመረጡት አብያተ ክርስቲያናት ሽልማት የሰጡት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እንደተናገሩት፤ ቤተ ክርስቲያን በልማቱ ዘርፍ በማሳተፍ ለሀገር ዕድገት የበኩሏን አስተዋጽኦ እያደረገች ነው፡፡

ይህንንም አስተዋጽኦ የበለጠ አጠናክራ እንደምትቀጥል ቅዱስነታቸው ተናግረዋል፡፡ በሠሩት የልማት ሥራ ለሽልማት የበቁት አብያተ ክርስቲያናት የተመረጡት ከመላው ሀገሪቱ ሲሆን አህጉረ ስብከቶቹና የሰበካ ጉባኤ አባላቱ ልማቱን የበለጠ አጠናክረው እንዲቀጥሉ ጄኔሬተር፣ የውኃ ¬ምፕና ኮሚፒዩተር መሸለማቸው ታውቋል፡፡

ለሽልማት ከበቁት ውስጥ የባሌ፣ የሰሜን ሸዋ፣ የምሥራቅ ሸዋና የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ይገኙበታል፡፡

ጉባኤው ሲጠናቀቅም የጉባኤውን ሒደት በቅደም ተከተል እንዲካሔድ የተሰየመው የቃለ ጉባኤ አርቃቂ ኮሚቴ ባለ 26 ነጥብ ያለው የጋራ የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ አቅርቧል፡፡

ኮሚቴው ባቀረበው የአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ እንዳመለከተው ቅዱስነታቸው በጉባኤው መክፈቻ ላይ የሰጡት የሥራ መመሪያና በተለይ በሀገራችን ሊከናወን ስለሚገባው ልማታዊ ሥራ፣ ለዚህ ተግባራዊነትም ሊኖር ስለሚገባው ሰላም አስመልክቶ ያስተላለፉት መልእክት ጉባኤው በአድናቆትና ከልብ እንደተቀበለውና ለተግባራዊነቱም እንደሚሠራ ገልጸዋል፡፡

ቅዱስነታቸው በተገኙበት ከየካቲት 9-10 ቀን 2001 ዓ.ም በመንበረ ፓትርያርክ የስብከተ ወንጌል አስተባባሪነት የተካሔደው ዓውደ ጥናት ጠቃሚ ትምህርት የተገኘበት፣ ነፃና ግልጽ በሆነ መንገድ ውይይት የተደረገበትና ተሳታፊዎቹን የበለጠ ለሥራ ያተጋ በመሆኑ ሊበረታታ የሚገባው ጉዳይ መሆኑን የአቋም መግለጫው አመልክቶ መምሪያው በ2002 ዓ.ም ያቀረበው ዕቅድ ተግባራዊ እንዲሆን ጉባኤው መጠየቁን አመልክቷል፡፡

ከጣና ቂርቆስ ገዳም ወደ ፈረንሳይ ተወስዶ በሪስ ሙዚየም ለብዙ ዓመታት የቆየው ቅዱስ መስቀል በቅዱስ ፓትርያርኩ ጥረት ግንቦት 28 ቀን 2001 ዓ.ም መመለሱን ጉባኤው አድንቆና ምስጋና አቅርቦ በቀጣይም በባዕድ ሀገር የሚገኙ ቅርሶችን ወደ ሀገር ቤት ለማስመለስ የሚደረገው ጥረት እንዲጠናከር ጠይቋል፡፡

በአንዳንድ አህጉረ ስብከት ያለው የአብነት ትምህርት ቤት መዳከም ምክንያቱ የአብነት ትምህርት ቤቶች በብዛት የሚገኙት በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል መሆኑን የጠቆመው የአቋም መግለጫው ለነዚህም በቂ በጀት አለመመደቡ ይልቁንም በአብዛኛው አህጉረ ስብከት ትምህርት ቤቶች አለመኖራቸው ባሉበትም ቢሆን የሚ ሰጠው ትምህርት ወቅታዊና ዘመናው በሆነ መልኩ ሊካሔድ አለመቻሉን ጉባኤው ግንዛቤ መውሰዱን አመል ክቷል፡፡

ለዚህም በምክንያት የሚጠቀሰው ትምህርትና ማሠልጠኛ መምሪያ በበቂ የሰውና የገንዘብ ኃይል ያልተደራጀ መሆኑ ግንዛቤ መያዙን ኮሚቴው አመልክቶ፤ በዚህ መሠረታዊ በሆነ የቤተክርስቲያን ጉዳይ ላይ ቅዱስ ሲኖዶስ ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ጉባኤው ማሳሰቡን አስረድቷል፡፡

የነገይቱን ቤተክርስቲያን የሚረከቡና ዛሬም የቤተክርስቲያን ውበት የሆኑት የሰንበት ትምህርት ቤቶች ወጣቶችን በመንከባከብ፣ በማስተማርና ከጠላት ወረራ እንደጠበቁ ለማድረግ፣ ከአባቶች የተማሩትን ንጹሕ ትምህርት ለፍሬ እንዲያበቁ በየአጥቢያ ቤተክርስቲያኑ የሚገኙትን ሰንበት ትምህርት ቤቶች ሁሉ ለማስተማር ያሉትን እያጠናከርን ባልተቋቋመባቸው አብያተ ክርስቲያናትም ለማቋቋም ጥረቱ እንደሚቀጥል የአቋም መግለጫው አመልክቷል፡፡

በበጀት ዓመቱም በተከናወኑ የልማት ሥራዎች በማኅበረ ቅዱሳን በኩል በየአህጉረ ስብከቱ በሚገኙ ወረዳዎችና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ለልማት ሥራ የሚውል የገንዘብ ድጋፍ መደረጉን በጥንታዊ ትምህርት ቤቶችና በሐዋርያዊ አገልግሎት ተዛማጅ ሥራዎች እንደተከናወኑ ከዘገባው መገንዘቡን በአቋም መግለጫና የውሳኔ ሐሳብ ተጠቁሟል፡፡

በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያን ባደረገው እገዛ ጉባኤው እያመሰገነ ወደፊትም ማእከላዊ አሠራርን በጠበቀ መልኩ ማኅበሩ እገዛውን እንዲቀጥል ጉባኤው ማሳሰቡን መግለጫው አስረድቷል፡፡

ኮሚቴው ባቀረበው ባለ 26 ነጥብ የአቋም መግለጫ ሕጋዊ ባልሆኑና ባልተፈቀደላቸው ሰባክያን በየመንደሩም ሆነ በየአብያተ ክርስቲያናቱ የሚካሔዱ ስብከቶች ማዕከላዊ አሠራርን ያልተከተሉ መሆናቸውን፣ በውጪው ዓለም ባለው መለያየት ጉባኤው እንደሚያዝንና በተለይ በሰሜን ምዕራብና ካሊፎርኒያ ሀገረ ስብከት የቀረበው ዘገባ አባቶችን ለማቀራረብ እየተደረገ ያለውን ጥረት እንደሚያደንቁና ጉባኤውም ሰላም እንዲገኝ ሙሉ ድጋፍ እንዳለው በአቋም መግለጫው ተገልጿል፡፡

ማኅበሩ የደብረ ጽጌ ገዳም የአብነት ትምህርት ቤትን በ1 ነጥብ 2 ሚሊዮን ብር ለማደስና ለማስፋፋት ስምምነት ተፈራረመ

በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ፍቺ ሀገረ ስብከት የሚገኘው ደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ማርያም አንድነት ገዳም የአብነት ትምህርት ቤትን ለማጠናከር በማኅበረ ቅዱሳንና በሀገር ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የአንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ብር የፕሮጀክት ስምምነት ተፈራረመ፡፡
ጥቅምት 1 ቀን 2002 ዓ.ም ወደ ስፈራው በተደረገው ሐዋርያዊ ጉዞ ወቅት በማኅበረ ቅዱሳን የፍቺ ማዕከልና የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቆስጦስ የተከናወነው ይኸው የፕሮጀክት ስምምነት አንድ ነጥብ ሁለት ሚሊዮን ብር የሚፈጅ ሲሆን፤ ፕሮጀክቱ ከ3-4 ዓመታት ባለው ጊዜ ውስጥ ይጠናቀቃል፡፡

በፊርማ ሥነ ሥርዓቱ ወቅት በማኅበረ ቅዱሳን የማኅበራዊ አገልግሎት ልማት ዋና ክፍል የቅስቀሳና ገቢ አሰባሰብ ሓላፊ ወ/ሮ ዓለም ፀሐይ መሠረት እንደገለጹት፤ ይኸው የስምምነት ሰነድ የተዘጋጀው ማኅበሩ በነዚህ ዓመታት በአቅም እጥረትና በእርጅና ምክንያት ሳይታደስ በመፈራረስ ላይ የሚገኘውን የአብነት ትምህርት ቤት ለማጠናከር፣ ሦስት አዲስ ቤት ለመገንባት እና ሰባት የጥገና ማስፋፋት ለማካሄድ ነው፡፡

የፕሮጀክቱ አጠቃላይ ወጪ የማኅበሩን የሞያ አገልግሎት እንደማያካትት የገለጹት ወ/ሮ ዓለምፀሐይ፤ እግዚአብሔር ፈቅዶ ፕሮጀክቱን በወቅቱ ለማጠናቀቅ ጥረት እንደሚደረግ አስታወቀዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቆስጦስ በዚህ ወቅት እንደ ተናገሩት የቤተክርስቲያኒቱ የነገ ተስፋ የሚፈሩበት ይህ የአብነት ት/ቤት ፈርሶ ቢቀር ከፍተኛ ሐዘን ይሰማቸው እንደነበር ጠቅሰው፤ ማኅበሩ ይህን በማሰብ ያከናወነው ተግባር የሚያሰመሰግነው መሆኑን ተናግርዋል፡፡

ለፕሮጀክቱ ተግባራዊነት በዋናነት በሓላፊነት እንደሚንቀሳቀሱና ለግንባታውም ባላቸው አቅም በገንዘብ እንደሚራዱ የጠቀሱት ብፁዕነታቸው፤ ምእመናን በሥራው እገዛ እንዲያደርጉ ጠይቀዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ወደ ማኅበረ ምእመናን እያደገ እንደሚገኝም ገልጸዋል ከፕሮጀክቱ ስምምነቱ በተጨማሪም ማኅበሩ ከምእመናን ያሰባሰበውን 13 ሺሕ 200 ብር ግምት ያላቸው 108 መንፈሳ ውያን መጻሕፍት፣ መጽሔትና ጋዜጦች ለገዳሙ  የአብነት ት/ቤት በስ ጦታ አበርክተዋል፡፡

ከዛሬ 50 ዓመታት በፊት የተቋቋሙ ይኸው የአብነት ት/ቤት የተመሠረተው በብፁዕ አቡነ ባስልዮስ መሆኑ በፕሮጀክት ስምምነቱ ወቅት ተጠቁሟል፡፡

በእንግድነት የተገኙት የታዕካ ነገሥት ባዕታ ለማርያም ገዳም እና የመንበረ መንግሥት ቅዱስ ገብርኤል የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ስምኦን እና የመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም የበላይ ጠባቂ ብፁዕ አቡነ ኤርምያስ በበኩላቸው ባስተላለፉት መልእክት፣ ነገ የቅድስት ቤተክርስቲያንን አገልጋይ መፍለቂያ የሚሆኑት የአብነት ት/ቤቶ ችን ለማጠናከር እየተደረገ ያለው ጥረት የሚበረታታ መሆኑን ጠቅሰው፤ ለፕሮጀክቱ ማስፈጸሚያ እነርሱም በየግላቸው የበኩላቸውን አስተዋጽኦ እንደሚያደረጉ ቃል ገብተዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ጸሐፊ አቶ ዳንኤል ተስፋዬ በበኩላቸው ማኅበሩ ገዳማትና አድባራትን በመደገፍ እንዲሁም የአብነት ት/ቤቶችን ከማጠናከር በተጨማሪ በርካታ ማኅበራዊና መንፈሳዊ አገልግሎቶችን እየሰጠ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በርካታ የአብነት ት/ቤቶች እየተዳከሙ እንደሚገኙ የገለጹት ዋና ጸሐፊው ይህን ችግር ለመቅረፍ ማኅበሩ በጎ አድራጊ ግለሰቦችንና ማኅበራትን እንዲሁም ምእመናንን በማስተባበር ፕሮጀክት ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን አብራርተዋል፡፡

በዚህ መንፈሳዊ ጉብኝት እና የፕሮጀክት ስምምነት ወቅት ከ300 በላይ የበጎ አድራጊ ግለሰቦች እና የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች የተገኙ ሲሆን የአብነት ት/ቤቶችን ለማጠናከር በሚደረገው ጥረት ውስጥ ከማኅበረ ቅዱሳን ጎን እንደሚቆሙ ቃል ገብተዋል፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መጠናከር የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት መሠረት ነው

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስተያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት፣ አገልጋዮቿን መዝግባ ይዛ ሥምሪት እና ምደባ ለመስጠት፣ ችሎታቸውንና ኑሮአቸውን ለማሻሻል፣ ምእመናንን ለማብዛትና በመንፈሳዊ እውቀት ጎልምሰው፣ በምግባርና በሃይማኖት ጸንተው እንዲኖሩ ለማድረግ፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደር ለማሻሻልና በሚያስፈልጋት ማንኛውም ጉዳይ ራሷን ለማስቻል ከአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ጀምሮ እስከ መንበረ ፓትርያርክ ድረስ በየደረጃው የሚቋቋም የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መዋቅርና አሠራር በቃለ ዓዋዲው መሠረት ዘርግታ ትገኛለች፡፡
የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች በሕዝብ በሚመረጡ ካህናት፣ ምእመናን እና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ተሳትፎ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋትና አስፈላጊ የሆነውን አቅም ለማጐልበት የሚመክርባቸው፣ የሥራ ክንዋኔዎችና ችግሮች እየቀረቡ የሚገመገሙባቸውና ልምዶች የሚወስዱባቸው፣ ቀጣይ አቅጣጫዎችም እግዚአብሔር ቢፈቅድ በሚል የሚታይባቸው በመሆናቸው፤ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መዋቅር ለቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት መስፋፋት ወሳኝነት ያለው ነው፡፡

ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን በዓለም ላይ በሚገኙ በአኀት አብያተ ክርስቲያናትም በእንግሊዘኛው አጠራር /ሪሽ ካውንስል/ በሚል ስያሜ እየተሠራበት የሚገኝ ዘመናዊ የቤተ ክርስቲያን አስተዳደራዊ መዋቅር ነው፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ /ሪሽ ካውንስል/ መዋቅርና አሠራር ሀገር አቀፍና ዓለም አቀፍ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ለውጦች በምእመናን ላይ የሚያስከትሉትን ተጽዕኖና መልካም አጋጣሚ ባገናዘበ ሁኔታ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት ማስፋፋትና ለዚህም የሚያስፈልገውን ዐቅም መፍጠርና ማጠናከር፣ የምእመናን ችግር መፍቻ እንዲሆኑ ለማድረግ አብያተ ክርስቲያናት፡- አካባቢያዊ እና የምእመናንን አኗኗር ሁኔታዎች እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን ማድረግ የሚገባትን ዘመኑን የዋጀ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ /ሪሽ ካውንስል/ መዋቅርና አሠራር ለመዘርጋት ተጨባጭና ነባራዊ ሁኔታዎችን የተከተሉ የሕግና የመዋቅር ማሻሻያዎችን ያደርጋሉ፡፡ የአሠራር ስልቶችን በየጊዜው ያዳብራሉ፡፡

ከዚህ አኳያም በ1991 ዓ.ም ለሦስተኛ ጊዜ ተሻሽሎ በሚገኘው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰበካ መንፈሳዊ ደንብ /ቃለ ዓዋዲ/ አንቀጽ 61  /2/ /ሀ/ ላይ የሰበካ ጉባኤ የሚኖረውን የምእመናን ድርሻ በተመለከተ፡- «የሰበካ ምእመናን በገንዘብ አስተዋጽኦ፣ በአስተዳደር፣ በትምህርት፣ በልማትና በማኅበራዊ ኑሮ አገልግሎት በጠቅላላው በሀብት፣ በዕውቀትና በጉልበት በመረዳት በሰበካው ልዩ ልዩ የክፍል ሥራዎች ውስጥ በመሳተፍ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ማገልገል ክርስቲያናዊ ግዴታቸው ነው፡፡» በማለት በተደነገገው መሠረት ምእመናን ለቤተ ክርስቲያናቸው የሚጠበቅባቸውን አገልግሎት ሲሰጡ ለሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓላማ መሳካት ትልቅ ድርሻ ያለው ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያናችን ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ደንብ /ቃለ ዓዋዲ/ መሠረት በአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የሚከተሉት ክፍሎች ይኖራሉ፡-

ሀ/ የስብከተ ወንጌል ክፍል
ለ/ የመንፈሳዊ ትምህርት ክፍል
ሐ/ የካህናት አገልግሎት ክፍል
መ/ የሰንበት ት/ቤት ክፍል
ሠ/ የእቅድና ልማት ክፍል
ረ/ የምግባረ ሠናይ /በጐ አድራገት/ ክፍል
ሰ/ የሕግና ሥነ ሥርዓት ክፍል
ሸ/ የንብረት፣ የዕቃ ግምጃ ቤትና የታሪካዊ ቅርስ ክፍል
ቀ/ የሒሳብ ክፍል
በ/ የገንዘብ ቤት
ተ/ የቁጥጥር ክፍል
ቸ/ የሕንፃ ሥራ፣ እድሳትና ጥገና ክፍል
ኀ/ የስታቲስቲክስ ክፍል

በሚል የተዋቀሩ የሥራ ክፍሎች ያሉት ሆኖ ምእመናን በችሎታቸው በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መሳተፍ እንዲችሉ የሚያደርግ ሲሆን ዳር ቁመን የምንመለከተው ወይም እገሌ ይሠራዋል፤ በሚል ልንሸሸው የማይገባ፣ ተሳታፊ በመሆን በረከት የምናገኝበት እና የቤተ ክርስቲያን ችግር የሚቀረፍበት መዋቅር ነው፡፡

በመሆኑም በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ደንብ መሠረት የሚጠበቅብንን  የድርሻችንን ካልተወጣንና ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅመውን በወቅቱ ካላደረግን ደንቡና መዋቅሩ ብቻውን ትርጉም ሊኖረው ስለማይችል በተሰጠን ጸጋ ልናገለግል ይገባል፡፡ እግዚአብሔርም ከእኛ ብዙ ይጠብቃል፡፡ የተቀበልነው መክሊት ነውና በተሰጠን መጠን ይፈለግብናል /ማቴ. 25-14-30/፡፡

በጉባኤ ደረጃ ያለውን ኃላፊነት ስንመለከት የአጥቢያ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፤ የአጥቢያው ካህናት፣ ምእመናን እና የሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች የሚሳተፉበት በዓመት ሁለት ጊዜ የሚካሄድ ጠቅላላ ጉባኤ ያለው ሲሆን፤ የወረዳ፣ የሀገረ ስብከት እና የመንበረ ¬ፓትርያርክ ሰበካ ጉባኤዎችም በየደረጃቸው በዓመት አንድ ጊዜ በመሰብሰብ አፈጻጸማቸውን በማቅረብ ውይይት የሚያደርጉባቸው የሰበካ መንፈሳዊ ጠቅላላ ጉባኤዎች የሏቸው ስለሆነ፤ እኒህ በተለያየ ደረጃ የሚደረጉት ጠቅላላ ጉባኤዎች የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ ለማድረግ ቅድመ ዝግጅት እና ከጉባኤዎቹ በኋላም ቢሆን ክትትል ማድረግን የሚሹ ናቸው፡፡

በዚህም መሠረት የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎችን በማጠናከር የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማስፋፋት ከቀደምት ተሞክሮዎች አንፃር

ምእመናን፣ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማገዝ በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ድርሻ ስላላቸው፡- በሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ በመምረጥና በመመረጥ ቢሳተፉና የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያቸውን በገንዘባቸው፤ በሙያቸው እና በጉልበታቸው ቢያገለግሉና ሌሎች ምዕመናንን የቤተ ክርስተያንን ችግር ለመቅረፍ የሰበካ ጉባኤ ተሳትፎ ወሳኝ እንደሆነ አጽንኦት ቢሰጡ፤

በቃለ ዓዋዲው የተገለጸው እንደተጠበቀ ሆኖ በየደረጃው ለሚገኙ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች ችግር ፈቺ  የሆነ፣ ዘመኑን የሚዋጅ ስትራተጂክ እቅድ እንዲወጣላቸው እና ከጉባኤዎቹ ስብሰባ በፊትና በኋላ አፈጻጸሙ ጽኑ ክትትል የሚደረግበት ሁኔታ ቢጠናከር፤

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያት የእስካሁን አፈጻጸም ምን እንደሚመስል እና በቀጣይ መሻሻል የሚገባቸው አሠራሮች ምን እንደሆኑ የሚያወያዩ ጥናት በየደረጃው እንዲቀርብ ቢደረግ፤

የሰበካ መንፈሳዊ አጠቃላይ ጉባኤያት የበለጠ ውጤታማ እንዲሆኑ ለማድረግ ጉባኤዎቹ ሪፖርቶች ማዳመጥ ብቻ ሳይሆን ችግር ፈቺ በሆኑ ጉዳዮች ላይ የጠነከረ ውይይት ሊያደርጉ ስለሚችሉበት ሁኔታ በሁሉም ደረጃዎች ወጥነት እንዲኖረው ቢደረግ፤

በሰበካ መንፈሳዊ ጠቅላላ ጉባያት የሚወሰኑ ጉዳዮች ጊዜ በማይወሰድ ሁኔታ ታች በየደረጃው ለሚገኙ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤያት ለአፈጻጸም እና ለግንዛቤ እንዲደርሱ አሠራሩ የተጠናከረ እንዲሆን ቢደረግ፤ እና በአንዳንድ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤዎች የሚፈጠሩ አለመግባባቶችን አጣርቶ የመፍትሔ እና የውሳኔ ሐሳብ የሚያቀርብ ትጉህ እና ለችግሮች ገለልተኛ የሆነ ምእመናን የሚሳተፉበት አሠራር መዋቅራዊ እንዲሆን ቢደረግ፤

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤን ዓላማና ተግባር ለማሳካት አስተዋጽኦ ስለሚኖረው፤ ያልፈጸምነውን አጉልተን በማየት፣ ቅድመ ዝግጅት እና ተሳትፎ በማድረግ የሚጠበቅብንን ልንወጣ ይገባል፡