ይ ቅ ር ታ

በአንዲት ሀገር አንድ ንጉሥ ነበር ። ይህ ንጉሥ በቤተ-መንግስት ውስጥ ብዙ አገልጋዮች አሉት – ያሉት አገልጋዮችም ምንም አይነት ስህተት እንዲሰሩ አይፈቅድም ። ትንሽ ጥፋት ሲያጠፉ ተለይቶ በተዘጋጀው ስፍራ ሰው እያያቸው ታስረው በተራቡ ጨካኝ የጫካ ውሾች ተበልተው እንዲሞቱ ያደርግ ነበር ። ከእለታት በአንዱ ቀን ንጉሡን ለ25 ዓመታት ያገለገው ባርያ ጥፋት ያጠፋና በንጉሡ ፊት ያቀርቡታል ። ንጉሡም በውሾች ተበልቶ እንዲሞት ፈረደበት ። ይህ ባርያ በተፈረደበት ፍርድ ከመሞቱ በፊት አሥር ቀን በቤተ-መንግስት ውስጥ እንዲያገለግል ንጉሡን ለመነ እናም ተፈቀደለት ።

ታዲያ ይህ ባርያ በተሰጠው አሥር ቀን ንጉሡን ብቻ ሳይሆን ውሾቹን ማገልገል ጀመረ ፣ ምግብ ይሰጣቸዋል ፣ ውኃ ይሰጣቸዋል ፣ ያጫውታቸዋልም ። ከዚያም በኋላ የተፈቀደለት አሥር ቀኑ አልቆ ያ ባርያ ለፍርድ በተዘጋጀው ስፍራ ታስሮ ቀረበ ፣ ውሾቹም ባርያውን እንዲነክሱት ተለቀቁ ነገር ግን አልነኩትም – ይልቅ ይልሱትና ያጫውቱት ጀመር።

በዚህ የተገረመው ንጉሡ ባርያውን አስጠርቶ ለምን እንዳልበሉት ጠየቀው ። ባርያውም “ንጉሥ ሆይ ሺ ዓመት ይንገሡ ፣ በቤተመንግሥትዎ ውስጥ 25 ዓመታትን በታማኝነት አገልግያለሁ በዚህም እርስዎ ደስተኛ እንደነበሩ በስጦታዎ ገልጸውልኛል ነገር ግን አንድ ቀን በሰራሁት ጥፋት ምክንያት እንድሞት ፈረዱብኝ ፤ ከአሳለፍናቸው 25 ዓመታት የአንድ ቀን ጥፋቴን አስበው ለሞት ሰጡኝ ። እነዚህን ውሾች ግን ለአሥር ቀን ብቻ አገለገልኳቸው ነገር ግን እርቧቸው እንኳ ሊበሉኝና ሊገድሉኝ አልወደዱም” አላቸው። ንጉሡም እስከ ዛሬ የሰራው ስራ ልክ እንዳልነበረ አስተዋለ ተጸጸተ ባርያውንም በይቅርታ አለፈው!

ለዘመናት ከእኛ ጋር በፍቅር ከኖሩ ወዳጆቻችን ፣ ቤተሰዎቻችን ፣ ዘመዶቻችን ፣ ጓደኞቻችንና ጎረቤቶቻችን ጋር ተጣልተን ሳለ በፍቅር የኖርንበት ጣፋጭ ዘመንን ነው የምናስበውና የምናወራው ወይንስ የተጣላንበትን ቀንና ምክንያት?  እነሆ ልባችን ለይቅርታ እንዲከፈት በፍቅር የኖርንበትን ዘመን ፣ መልካም ጊዜያትን በማሰብ ብንነጋገር ምክራችን ነው።