የሕፃኑን ነፍስ የሚሹ ሙተዋልና÷ ተነሥተህ ሕፃኑንና እናቱን ይዘህ ወደ እስራኤል ሀገር ሂድ። ማቴ. 2÷20

ኅዳር ፮ በዚህች ዕለት ክብርት እመቤታችን ከተወደደ ልጇ ጋር ከስደት በሚመለሱበት ጊዜ ደብረ ቁስቋም ገብተው ካገኛቸው ድካም ያረፉበት ነው። ይህ የቍስቋም ተራራ በግብጽ ከሚገኙ ተራራዎች አንዱ ሆኖ እመቤታችን በሚጠቷ (ከስደት በምትመለስ ጊዜ) ከተወደደ ልጇና ከቅዱስ ዮሴፍና ቅድስት ሰሎሜ ጋር ያረፈችበት ቦታ ነው።

መዘምር ወመተርጕም ቅዱስ ያሬድ መድኃኔዓለም ክርስቶስ ከእናቱ ከእግዝእትነ ማርያም ጋር በዚህ ቦታ ላይ ማረፉንና የቦታውን ታላቅነት በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ይናገራል። ቅዱስ ያሬድ ስለቦታው ታላቅነት ሲናገር <<ይቤ ቴዎፍሎስ ሊቀ ጳጳሳት ሶበ ቦዕኩ ውስተ ዝንቱ ቤት አዕረፈት ነፍስየ እምጻማ ዘረከበኒ በፍኖት ኀበ ኃደረት ቅድስት ድንግል ምስለ ፍቁር ወልዳ ኢየሱስ ክርስቶስ : የጳጳሳት አለቃ ቴዎፍሎስ ቅድስት ድንግል ከተወደደ ልጇ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ወዳረፈችበት ወደዚህ ቦታ በገባሁ ጊዜ በመንገድ ካገኘኝ ድካም ሰውነቴ አረፈች አለ>> ይልና <<መንግሥቱ ሰፋኒት ዘእምቅድመ ዓለም ወልደ ቅድስት ማርያም ኃሠሠ ምዕራፈ ከመ ድኩም ንጉሥ ዘለዓለም ግሩም እምግሩማን ብርሃነ ሕይወት ዘኢይጸልም ኃደረ ደብረ ቍስቋም ኃይል ወጽንዕ ዘእምአርያም : ዓለም ሳይፈጠር በመንግሥቱ ያለ በንግሥናው የነበረ (መዝ.፸፫÷፲፫) ቅድስት የምትሆን የማርያም ልጅ እንደ ደካማ ማረፊያን ፈለገ (ማረፍን የሚሻ ሥጋን ለብሷልና) ፍጥረታቸው ግሩም ከሆነ ከቅዱሳን መላእክት እጅግ የረቀቀ ግሩም : የማይጨልም ብርሃኑ ዘለዓለማዊ የሆነ የሕይወት ብርሃን(ዮሐ. ፩÷፱) በአርያም ላሉ ለሰማያውያን መላእክት ሁሉ ኃይላቸው ብርታታቸው የሆነ እርሱ በቍስቋም ተራራ ላይ አደረ>> በማለት እርሱ የመላእክት ንጉሣቸው (ሃይ. አበ ዘሄሬኔዎስ ምዕ. ፯÷፯) የሆነ በዚህ ተራራ ላይ ራሱን ዝቅ አድርጎ በትሕትና መገለጡን ይመሰክራል።

ይህች ዕለት ቅዱሳን መላእክት በቍስቋም ተራራ ላይ ክንፋቸውን በእመቤታችንና በተወደደ ልጇ ላይ የዘረጉበትና በሰማይ ምስጋና በምድርም ሰላም ይሁን እያሉ የዘመሩባት ናት።

ዳግመኛም በኋለኛው ዘመን ጌታችን በዚህ በደብረ ቍስቋም ቅዱሳን ሐዋርያቶቹን ሰበሰባቸውና ታቦትንና ቤተ ክርስቲያንን አክብሮ የቍርባን መሥዋዕትንም ሠርቶ ቅዱስ ሥጋውንና ክቡር ደሙን ለወገኖቹ ሰጣቸው፡፡ ለዚህም ነገር የእስክንድርያ አገር ሊቃነ ጳጳሳት ቅዱሳን አባቶቻችን ቄርሎስና ቴዎፍሎስ ምስክሮቹ ሆኑ፡፡

ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን። እኛንም በእመቤታችን በቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት ይማረን። በረከቷም ከሁላችን ጋር ይኑር። ለዘለዓለሙ አሜን።

ምንጭ፦ ስንክሳር ዘኅዳር ፮፣ ዝክረ ቃል ዘቅዱስ ያሬድ (ዘቍስቋም)

እንኳን ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ ጥንተ ስቅለቱ መታሰቢያ በዓል አደረሳችኹ።

ጥቅምት ሃያ ሰባት በዚህች ዕለት የአምላካችን የመድኃኔዓለም የስቅለቱ መታሰቢያ ነው። መድኃኒታችን ለስም አጠራሩ ክብር ይግባውና በቸርነቱ ስለኹላችን ድኅነት ሲል ራሱን ወድዶ ፈቅዶ ለሞት አሳልፎ በመስጠት ፍጹም ፍቅሩን አሳይቶናል። በቅዱስ ወንጌልም እርሱም መድኃኒታችን “ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም” ብሎ ነግሮናል። እውነት ነው፣ ራስን አሳልፎ ከመስጠት በላይ ምን ድንቅ ነገርና ምን ድንቅ ፍቅር አለ?

ቸሩ አምላካችንን የአስቆሮቱ ይሁዳ ሊያስይዘው የሊቃነ ካህናቱን አገልጋዮች እየመራ አመጣቸው። እነርሱንም ማንን ትፈልጋላችሁ ሲላቸው የናዝሬቱ ኢየሱስን አሉት፣ እኔ ነኝ ቢላቸው የቸሩን አምላክ ድምጽ ሰምቶ አይደለም መቆም በሕይወት መጽናት የሚቻለው የለምና ወደ ኋላቸው ተስፈንጥረው ወደቁ። ደጋግሞም እንዲህ ኾነ። በኋላ ይሁዳ ስሞ አሳልፎ ሰጣቸው።

ከያዙት በኋላ እያዳፉና እየጎተቱ በሰንሰለት አስረው ወደ ቀያፋና ሐና ግቢ ወሰዱት፣ እስከ ሦስት ሰዓትም አላሳረፉትም ሲያሰቃዩት አድረዋል፣ በራሱም ላይ ሰባ ሦስት ስቊረት ያለው ወደ ሦስት መቶ እሾኾችን የያዘ የእሾህ አክሊል ጎንጉነው ቢያደርጉበት የራስ ቅሉን ቀዶ ገብቶ እስከ ልቡ ዘልቋል። እንደምን ጭንቅ ነው? እንዲህም አድርገው ደግሞ እያፌዙ ርኲስ ምራቃቸውን ይተፉበትና በዘንግም ደጋግመው ይመቱት ነበር። እየተፈራረቁ ያለ ምንም ርኅራኄ ቸሩን አምላክ ሥጋው እየተቆረጠ እስኪወድቅ ድረስ ስድስት ሺህ ስድስት መቶ ስድሳ ስድስት ጽኑዕ ግርፋትን ገርፈውታል። የገረፉበትም ጅራፍ በላዩ ላይ ሥጋን እየጎመደ የሚጥል፣ ሕመሙ አንጀት ሰርሥሮ የሚገባ ስለት የተያያዘበት ነበር።

በኋላም አላሳረፉትም እንዲህ አድርገውትም በሊቶስጥራ አደባባይ ያንን ዕርጥብ መስቀል አሸክመው ወደ ቀራንዮ ወሰዱት። እርሱ ግን ይህን ኹሉ ግፍ ሲያደርሱበት አንድም አልተናገረም ነበር። በቀራንዮም በአምስት ጽኑዕ ቅንዋት (ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ እና ሮዳስ) ቸንክረው ዕርቃኑን ሰቀሉት።

በዚህች ቀን ድንግል ማርያም ልቧ በሐዘን ተሰበረ መጽናናትንም አልፈለገች ነበር፤ ወዳጁ ቅዱስ ዮሐንስም ፍፁም ለቅሶን አለቀሰ እናቱንም እናት ትሆነው ዘንድ በእግረ መስቀሉ አደራን ተቀበለ። ቅዱሳት አንስት በፍጹም ሀዘንና በዋይታ ዋሉ። በስልጣኑም ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለየ። ሰባት ድንቅ የኾኑ ተአምራትንም አድርጎ አምላክ መኾኑን ገለጠ። ይህም ጽኑዕ የኾነ ለሰማይ ለምድር የከበደ ነገር ሲከሰት ፀሐይ አምላኬን ዕርቃኑ እንዴት አያለሁ ብላ ጨለመች። ጨረቃ ደም ኾነች፣ ከዋክብቱም ረገፉ፣ ንዑዳን ክቡራን ንጹሐን መላእክትም ትዕግስቱን እያደነቁ በጽኑዕ ሐዘንና መደነቅ ከዕፀ መስቀሉ ፊት እንደሻሽ ተነጠፉ።

አስራ አንድ ሰዓት በሆነም ጊዜ ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ከታላቅ ክብርና ሐዘን ጋር ቅድስት ሥጋውን ከመስቀሉ አውርደው በክብር ገንዘው በአዲስ መቃብር ቀበሩት። በሦስተኛውም ቀን እንደተናገረ ተነሳ።

በዛሬዋ ቀን ቤተ ክርስቲያን የመድኃኔዓለምን የስቅለት በዓል በደማቁ ታከብራለች፤ ይህም የለውጥ በዓል ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን እየሱስ ክርስቶስ ደሙን ያፈሰሰው ስጋውን የቆረሰው መጋቢት 27 ቀን ነው። ይህ በዓል ግን በዐቢይ ጾም ስለሚውል በዐቢይ ጾም ሀዘን እንጂ ደስታ ስለሌለና በዓል ማክበር ስለማይፈቀድ፤ ወደ ጥቅምት 27 ተዛውሮ ደስ ብሎን እንድናከብረው ቤተ ክርስቲያን ስርዓት ሰርታልናለች።

እንዲሁም ይች ዕለት የጻድቁ አባ መብዓ ጽዮን የቃልኪዳን ቀን፣ የማህሌተ ጽጌ ደራሲው አባ ጽጌ ድንግል የእረፍታቸው መታሰቢያ ናት።

ምንጭ:- ዘወርኃ ጥቅምት ፳፯ ስንክሳር

እግዚአብሔር የመረጠው ጾም

ለተወሰነ ሰዓት ከምግበ ሥጋ የመከልከላችን ዓላማ ራሳችንን መግዛት እንድንችል ነው፡፡ ስለዚህ ‘እየጾምኩ ነው’/የሚል ሰው ካለ ከምንም በፊት ትዕግሥተኛ ፣ ልበ ትሑትና የዋህ ፣ እግዚአብሔርን የሚፈራ ልቡና ያለው ፣ የፍትወታትን ጅረት ከኹለንተናው የሚያስወግድ ፣ ዘወትር በልቡናው ዕለተ ምጽአትን የሚያስብ ፣ በእግዚአብሔር የፍርድ ዙፋን ፊት እንደሚቆም የማይረሳ ፣ በፍቅረ ንዋይ ወጥመድ ተይዞ ምጽዋትን የማይጠላ፣ ወንድሙን ከልቡ የሚወድ ይኹን፡፡ እውነተኛ ጾም ማለት ይኽ ነውና፡፡

“ሰው ራሱን ቢያሳዝን ፣ አንገቱንም እንደ ቀለበት ቢያቀጥን ፣ ማቅ ለብሶ በአመድ ላይ ቢተኛም ይህ ጾም እግዚአብሔር ዘንድ የተመረጠ አይደለም” “ታዲያ እግዚአብሔር የመረጠው ጾም እንዴት ያለ ነው?” ትሉኝ እንደ ኾነም ነቢዩ ኢሳይያስ የእግዚአብሔር አፈ ንጉሥ ኾኖ እንዲህ ሲል ይመልስልናል፡

“የበደልን እስራት ፍታ ፡ ለተራበው እንጀራህን አጥግበው ፡ ድኾችን ወደ ቤትህ አስገብተህ አሳድራቸው ” እንዲህ ስታደርግ ፡- “ያን ጊዜ ብርሃንህ እንደ ንጋት ይበራል፡፡ ፈውስህም ፈጥኖ ይወጣል” ትን.ኢሳ.58 ፥ 5-8

†ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ†

ምንጭ -ኦሪት ዘፍጥረት መፅሐፍ – በገብረ እግዚአብሔር ኪደ

ጰ ራ ቅ ሊ ጦ ስ

¹ በዓለ ሐምሳ የተባለውም ቀን በደረሰ ጊዜ፥ ሁሉም በአንድ ልብ ሆነው አብረው ሳሉ፥

² ድንገት እንደሚነጥቅ ዓውሎ ነፋስ ከሰማይ ድምፅ መጣ፥ ተቀምጠው የነበሩበትንም ቤት ሁሉ ሞላው።

³ እንደ እሳትም የተከፋፈሉ ልሳኖች ታዩአቸው፤ በያንዳንዳቸውም ላይ ተቀመጡባቸው።

⁴ በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው ፥ መንፈስም ይናገሩ ዘንድ እንደ ሰጣቸው በሌላ ልሳኖች ይናገሩ ጀመር።

እ ን ኳ ን ለቅዱስ ሚካኤል ዓመታዊ በዓል በሰላም አ ደ ረ ሳ ች ሁ።

ተአምራትን በሚያደርግ በከበረ በቅዱስ ሚካኤል በዓል ቀን መታሰቢያን የሚያደርግ ኹሉ ለቤተክርስቲያን ዕጣን የሚሰጥ ቢኾን መስዋዕትን የሚያቀርብ ቢኾን የተራበውን ያበላ የተጠማውን ያጠጣ ቢኾን የታረዘም ያለበሰ ቢኾን ያዘነውን ያረጋጋ የተከዘውን ደስ ያሰኘ የታመመውን የጎበኘ ቢኾን ስለከበረ ስለ መላእክት አለቃ ስለ ቅዱስ ሚካኤል ስም በጭንቅ በመከራ ያለውን እሥረኛን የጠየቀም ቢኾን ገሃነምን አያያትም።

በዚኽ ዓለም እግዚአብሔር ከበጎ ነገር ኹሉ አያሳጣውም። በሞተ ጊዜም ነፍስን እያካሰሱ ወደ ሲዖል የሚያደርሱ አጋንንት በሰማይ በር ሊከራከሩት አይችሉም።

ይኸው ቅዱስ ሚካኤል በብሩሃን ክንፎቹ ተሸክሞ የእሳት ባሕርን ያሻግረዋል። በልዑል እግዚአብሔር ዙፋን ፊት ያቆመዋል። ነፍስ ለልዑል እግዚአብሔር ትሰግዳለች። ከዚኽ በኋላ ወደ ተድላ ገነት ይወስዳታል። እርሱ ራሱ ጌታችን በማይታበል ቃሉ ተናግሯልና። ለወዳጆቹም ኹሉ ቃል ኪዳን ሰጥቶአቸዋልና እንዲኽ ብሎ ከወዳጆቼ ጋር ቃል ኪዳን አደረግኹ።”

† ድርሳነ ሚካኤል †

ሰላም ለዝክረ ስምከ ምስለ ልዑል ዘተሳተፈ ፣ ወልደ ያሬድ ሄኖክ በከመ ጸሐፈ ፣ ሶበ እጼውእ ስመከ ከሢትየ አፈ ፣ ረዳኤ ምንዱባን ሚካኤል በከመ ታለምድ ዘልፈ ፣ ለረዲኦትየ ነዓ ሰፊሐከ ክንፈ ።

የቅዱስ ሚካኤል ምልጃና ረዳትነቱ አይለየን

ይ ቅ ር ታ

በአንዲት ሀገር አንድ ንጉሥ ነበር ። ይህ ንጉሥ በቤተ-መንግስት ውስጥ ብዙ አገልጋዮች አሉት – ያሉት አገልጋዮችም ምንም አይነት ስህተት እንዲሰሩ አይፈቅድም ። ትንሽ ጥፋት ሲያጠፉ ተለይቶ በተዘጋጀው ስፍራ ሰው እያያቸው ታስረው በተራቡ ጨካኝ የጫካ ውሾች ተበልተው እንዲሞቱ ያደርግ ነበር ። ከእለታት በአንዱ ቀን ንጉሡን ለ25 ዓመታት ያገለገው ባርያ ጥፋት ያጠፋና በንጉሡ ፊት ያቀርቡታል ። ንጉሡም በውሾች ተበልቶ እንዲሞት ፈረደበት ። ይህ ባርያ በተፈረደበት ፍርድ ከመሞቱ በፊት አሥር ቀን በቤተ-መንግስት ውስጥ እንዲያገለግል ንጉሡን ለመነ እናም ተፈቀደለት ።

ታዲያ ይህ ባርያ በተሰጠው አሥር ቀን ንጉሡን ብቻ ሳይሆን ውሾቹን ማገልገል ጀመረ ፣ ምግብ ይሰጣቸዋል ፣ ውኃ ይሰጣቸዋል ፣ ያጫውታቸዋልም ። ከዚያም በኋላ የተፈቀደለት አሥር ቀኑ አልቆ ያ ባርያ ለፍርድ በተዘጋጀው ስፍራ ታስሮ ቀረበ ፣ ውሾቹም ባርያውን እንዲነክሱት ተለቀቁ ነገር ግን አልነኩትም – ይልቅ ይልሱትና ያጫውቱት ጀመር።

በዚህ የተገረመው ንጉሡ ባርያውን አስጠርቶ ለምን እንዳልበሉት ጠየቀው ። ባርያውም “ንጉሥ ሆይ ሺ ዓመት ይንገሡ ፣ በቤተመንግሥትዎ ውስጥ 25 ዓመታትን በታማኝነት አገልግያለሁ በዚህም እርስዎ ደስተኛ እንደነበሩ በስጦታዎ ገልጸውልኛል ነገር ግን አንድ ቀን በሰራሁት ጥፋት ምክንያት እንድሞት ፈረዱብኝ ፤ ከአሳለፍናቸው 25 ዓመታት የአንድ ቀን ጥፋቴን አስበው ለሞት ሰጡኝ ። እነዚህን ውሾች ግን ለአሥር ቀን ብቻ አገለገልኳቸው ነገር ግን እርቧቸው እንኳ ሊበሉኝና ሊገድሉኝ አልወደዱም” አላቸው። ንጉሡም እስከ ዛሬ የሰራው ስራ ልክ እንዳልነበረ አስተዋለ ተጸጸተ ባርያውንም በይቅርታ አለፈው!

ለዘመናት ከእኛ ጋር በፍቅር ከኖሩ ወዳጆቻችን ፣ ቤተሰዎቻችን ፣ ዘመዶቻችን ፣ ጓደኞቻችንና ጎረቤቶቻችን ጋር ተጣልተን ሳለ በፍቅር የኖርንበት ጣፋጭ ዘመንን ነው የምናስበውና የምናወራው ወይንስ የተጣላንበትን ቀንና ምክንያት?  እነሆ ልባችን ለይቅርታ እንዲከፈት በፍቅር የኖርንበትን ዘመን ፣ መልካም ጊዜያትን በማሰብ ብንነጋገር ምክራችን ነው።

ኃጢአተኛዋ/ውን ማረኝ

በድሮ ዘመን ወንጀል የሚሠሩ አመጸኞች ተይዘው ሲታሰሩ በግራና ቀኝ እጃቸው መቅዘፊያ ይዘው በጉልበታቸው ኃይል እየቀዘፉ የመንግስትን መርከቦች በባህር ላይ እንዲነዱ ይገደዱ ነበር።

አንድ ቀንም አንድ ንጉሥ ክፉ ሥራ የሠሩ ወንጀለኞች ታሥረው ወደ ሚገኙበት መርከብ ገባ። እስረኞቹም የታሰሩበትን ከባድ ሰንሰለት ሲመለከት እጅግ አዘነላቸው። በልቡም “ከእነዚህ አንዱን ልፍታ” ሲል አሰበ።

መፈታት የሚገባውንም ለማግኘት “አንተ ወደዚህ የመጣህበት ምክንያት ምንድነው?” እያለ እያንዳንዱን ሲጠይቅ እና ሲመረምር እያንዳንዳቸው እያዘኑ “ምንም ሳላጠፋና ሳልበድል ክፉ ሰዎች ነገር ሠርተው ወደ ሹማምንት አደረሱኝ እንጂ ከተባለብኝ ነገር ንጹህ ነኝ ጌታዬ ሆይ ምሕረት አድርጉልኝ ከዚህም ሥፍራ ያውጡኝ እያሉ አጠንክረው ለመኑ ።

ንጉሡም እያለፈ ሲመረምር ወደ አንድ ወጣት ደረሰና “አንተ ምን አድርገህ ነው” ቢለው ወጣቱ መልሶ “ምሕረተኛ ጌታዬ ሆይ እኔ እጅግ ክፉ አሽከር ነኝ ለአባቴና ለእናቴ አልታዘዝም በማለት ብዙ ጊዜ ኮበልኩባቸው፤  እጅግ ክፉ ሥራም ሠራሁ ፣ ሰረቅሁ ፣ አታለለሁም ፣ ያደረግሁትን ክፋት ሁሉ ዘርዝሬ ለመተረክ እጅግ ብዙ ነው።  የተገባኝን አግኝቻለሁ ይህን ቅጣት ደስ እያለኝ እሸከማለሁ ከዚህ ሺህ ጊዜ የሚበልጥ እንደሚገባኝ ተረድቻለሁ” ብሎ ኃጢአቱን ተናዘዘ።

ንጉሡ ግን እያንዳንዱ እስረኛ ለጥፋቱ የተገባውን ቅጣት እንደተቀበለ አረጋግጦ በቀልድ ሲዘልፋቸው “ኧረ በእነዚህ ደጋግ ሰዎች መካከል ይህ ክፉ እንዴት ገባ! እነዚህን ደህና ሰዎች እንዳያበላሽ ቢወጣ ይሻላል” በማለት በክፉ ሥራው አፍሮ ለተናዘዘው ምሕረት አደረገለት ፤ እርሱም ደስ ብሎት ሄደ።

የሠራነውን ኃጢአት ለመደበቅ ፣ ራሳችንን ለማጽደቅ የምንወድ ሰዎች ዛሬም አለን። ልባችንን የሚያውቅ አምላካችን ግን በቃሉ ንስሐ እንድንገባ ፣ ኃጢአታችንን እንድንናዝ ፣  ክፉ ማድረግንም እንድንተውና መልካም ማደረግን እንድንማር አዝዞናል።

ስለዚህ የሚያጸድቀው ከልብ “እኔን ኃጢአተኛዋ/ውን ማረኝ” የሚለው ብቻ ነው።

“ኃጢአቱን የሚሰውር አይለማም ፣ የሚናዘዝባትና የሚተዋት ግን ምሕረትን ያገኛል”

ምሳ 28 ፣13

የዘይቱ ነገር

አንድ ሰው በጣም የሚወደው ልጅ ነበረው፡፡ ለዚህ ልጁ ሕይወትን ሃይማኖትን ከምግባር አስተባብሮ እንዴት መኖር እንደሚችል ሊያስተምረው ይጥር ነበር፡፡ ነገር ግን ብዙም የተሳካለት አልመሰለውም፡፡ ልጁ በፊቱ የመጣለትን ነገር በማድረግ የሚነዳና ምንም አይነት መንፈሳዊነትና ጥበብ የሞላው ሕይወት እንዳላዳበረ ገባው፡ በአካባቢው በጥበቡ የታወቀ አንድ አባት ነበረና የሕይወት ጥበብ እንዲማር ወደዚያ ጠቢብ አባት ላከው፡፡

ልጁ ወደጠቢቡ አባት በመሄድ እንዲህ አለው፣ “ሕይወቴን መንፈሳዊነትና ጥበብ በተሞላው ሁኔታ እንዴት መምራት እንዳለብኝ ለመማር ነው የመጣሁት”፡፡ ጠቢቡ “አሁን ትንሽ ስራ አለብኝ ፣ ከሁለት ሰዓታት በኋላ ቆይተህ ተመለስ፡፡ እስከዚያው ግን አንድን ነገር እንድታደርግ ስራ ልስጥህ” በማለት፣ በእጁ አንድን የሻይ ማንኪያ ሰጠውና በማንኪያው ላይ ዘይትን ሞላበት፡፡ ከዚያም እንዲህ አለው ፣ “በቤተክርስቲያን ውስጥ እየተዘዋወርክ ያሉትን ድንቅ ቅርሶች በመመልከት ሁለት መጠበቅ ያለብህን ሰዓታት አሳልፍ፡፡ አንድ ነገር ግን ተጠንቀቅ፣ በፍጹም ይህ በማንኪያው ላይ ያለው ዘይት መፍሰስ የለበትም”፡፡ ልጁ አደራውን ተቀብሎ፣ ስንት ሰዓት እንደሆነ ከቃኘ በኋላ ቤተክርስቲያኑን ለመጎብኘት በእጁ ዘይት የሞላበትን ማንኪያ ይዞ በቀስታ በመራመድ ወጣ፡፡

ልጁ ከሁለት ሰዓት በኋላ ወደ ጠቢቡ አባት ተመለሰ፡፡ ጠቢቡ ካስገባው በኋላ ፣ “በቤተክርስቲያኑ ውስጥ በግድግዳው ላይ የተሰቀለውን የጥንት ስእል አየኸው? የታወቁ የገዳሙ አባቶች አስር ዓመት የፈጀባቸውን የአትክልት ስፍራ አየኸው? የዓለምን እውቀት በሙሉ የያዘውንስ የመጽሐፍት ቤት አየኸው?” ልጁ አፍሮ አንገቱን አቀረቀረ፡፡ ለካ ለሁለት ሰዓታት ሲዘዋወር ትኩረቱ ሁሉ በእጁ የያዘው ማንኪያ ላይ የተቀመጠው ዘይት እንዳይፈስ ነበር፡፡ ጠቢቡ ሊያስተምረው የፈለገው ነገር እንደተሳካለት ገባውና፣ “እንደገና በማንኪያ ያለውን ዘይት ይዘህ ሂድና እነዚህ የነገርኩህንና ሌሎችም አስገራሚ ቅርሶች እንደገና ተመልክተህ ተመለስ” አለው፡፡

ሁለተኛ እድል ስላገኘ ትንሽ ተንፈስ ያለው ወጣት ተመልሶ ወጣ፡፡ ለሁለት ሰዓታት ጉብኙቱን ካጧጧፈ በኋላ በፈገግታ ተመለሰና ያየውን ሁሉ ለጠቢቡ ነገረው፡፡ እስኪጨርስ ጠብቆ ጠቢቡ፣ “እንዳይፈስስ ያልኩህ ዘይት የት አለ?” አለው፡፡ ልጁ፣ ጎንበስ ብሎ በእጁ የያዘውን ማንኪያ ሲያየው ለካ ዙሪያውን በመመልከት ሲደነቅ ዘይቱን ችላ ስላለው ዘይቱ ሙልጭ ብሎ ፈስሷል፡፡ ጠቢቡ አባትም እንዲህ አለው፣ “ስኬታማ ሕይወት ማለት እምነትና ምግባር የተሞላውን ሕይወት መኖር ማለት ነው፡፡

እምነትና ጥበብ የተሞላበት ሕይወት ማለት ዙሪያህን እያየህ በማድነቅ ስትኖር በእጅህ ላይ ያለውን አደራ አለመዘንጋት ነው”፡፡ በሕይወታችን ልክ እንደ ዘይቱ በጥንቃቄ መያዝ ያለብን አደራዎች አሉን፡፡ ከዚያው ጋር ደግሞ ልክ በቤተክርስቲያኑ ውስጥ እንዳሉት አስደሳች ጥንታዊ ቦታዎች የመደሰትን እድል የሚሰጡን ሁኔታዎች አሉ፡፡ እውነተኛ ሰው እነዚህን ሁለቱን በሚዛናዊነት የያዘ ሰው ነው፡፡

ስንጫወት ፣ ስንዝናና ፣ ስንደሰትና በማሕበራዊው ግንኙነታችን ውስጥ ያለውን ደስ የሚያሰኝ ሁኔታ ስንፈነድቅበት ፣ ከዚያ የተነሳ በእጃችን ላይ ያለው አደራ ችላ እንዳይባልና ዘይቱ እንዳይፈስ መጠንቀቅ የጥበብ ሁሉ ጥበብ ነው፡፡ ልክ ይህ ወጣት በእጁ ያለውን ዘይት በዙሪያው ካለው ታላላቅ ነገርን የማየት እድል ጋር አስታርቆና ሚዛናዊ አድርጎ መውጣትና መግባት እንደነበረበት እኛም እንዲሁ! በዙሪያችን ካለው ጨዋታና መዝናናት ብዛት የተነሳ የተለመዱ ችላ በማለት ማፍሰስ የማይገቡን የአደራ “ዘይቶች” . . .

” ልባሞቹ ግን ከመብራታቸው ጋር በማሰሮአቸው ዘይት ያዙ።”

†የማቴዎስ ወንጌል 25:4†

ምንጭ-ቬነሲያ ገጽ

ኢትዮጵያዊው ቅዱስ ያሬድ

ቅዱስ ያሬድ ውልደትና እድገቱ ኢትዮጵያ ወስጥ ፤ አክሱም ከተማ ከአባቱ ከአብዩድና ከእናቱ ታውክሊያ ነው ፤ ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ እናቱ መምህር ወደ ሆነው አጎቱ አባ ጌዲዬን ትወስደዋለች፡፡ እርሱ ግን በመጀመሪያ ትምህርት ሊገባው አልቻለም፡፡ ከዕለታት በአንድ ቀን መምህር ጌዲዬን ያሬድን ሲገርፈው በምሬት አለቀሰ ፤ ማይኪራህ ወደምትባል ቦታም ተጓዝ፤ በመንገድ ላይ ሳለ ውሃ ስለጠማ በዚያች ስፍራ ካለ ምንጭ ውሃ ጠጥቶ በዛፉ ሥር ለማረፍ ቁጭ አለ፤ ወደ ላይም በሚመለከትበት ጊዜ ከዛፉ ላይ አንዲት ትል ከታች ወደ ላይ ስትወጣ ስትወርድ ተመለከተ፡፡ እርሱም ትኩር ብሎ አያት ፤ ትሏም ያለመሰልቸት ከወጣች ከወረደች በኋላ ዛፉ ላይ መድረስ ቻለች፡፡
በዚያን ወቅት ቅዱስ ያሬድ አሰበ ፤ እንዲህም አለ፤ «ይህች ትል ዛፉ ላይ ለመድረስ እንዲህ ከተጋች እኔም ትምህርት ለመማር ብታጋ እግዚአብሔር አምላክ ይገልጽልኛል»፡፡ ወደ ጉባኤው ተመልሶ መምህሩን ይቅርታ ከጠየቀ በኋላ መማር ጀመረ ፤ እግዚአብሔር አምላክም የ፹፤፩ መጽሐፍትንና የሊቃውንት መጽሐፍትን እንዲሁም ሌሎች ቤተ ክርስቲያን የተቀበለቻቸውን የቅዱሳት መጻሕፍትን ምሥጢር ገለጸለት ፤ መምህር ጌዲዬን ሲሞት የእርሱን ቦታ ተረክቦ ማሰተማር ቀጠለ፡፡
በ534 ዓ.ም. ኅዳር 6 ቀን ፤ ወደ ሰማይ ተመነጠቀ፤ በሰማይ ቅዱሳን መላእክት እግዚአብሔርን ልዩ በሆነ ጣዕመ ዝማሬ ሲያመሰግኑ ሰማ፡፡ ወደ ምድርም በተመለሰ ጊዜ አክሱም ጽዮን ውስጥ ወደ ምስራቅ በኩል በመዞር ከሰማይ የሰማውን ዝማሬ ዘመረ፤ አርያም ብሎም ሰየመው፡፡ በዚሁም በ538 ዓ.ም. ቅዱስ ያሬድ ማኅሌትን ጀመረ፡፡ ታህሳስ 1 ፤ በዕለተ ሰኞ ምህላ ያዘ ፤ እሰከ ታህሳስ 6 ፤ ቀዳሚት ሰንበት ድረስም ዘለቀ ፤ በዚያች ዕለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል አንደተሰቀለ ሆነ ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገለጸለት፡፡
ቅዱስ ያሬድም ጌታ የተገለጸለትን የመጀመሪያውን ሳምንት ‹ስብከት› ብሎ ሰየመው ፤ በሳምንቱም እንደገና በብርሃን አምሳል ስለተገለጸለት ያን ዕለት ‹ብርሃን› ብሎ ሰየመው፤ በሶስተኛው ሳምንት እንዲሁ በአምሳለ ኖላዊ ስለተገለጸለት ‹ኖላዊ› ብሎ ሰየመው፤ በመጨረሻም ሳምንት በአምሳለ መርዓዊ ሲገለጽለት ዕለቱን ‹መረዓዊ› ብሎ ሰይሞታል፡፡
ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሬድ 5 የዜማ መጻሕፍትን ደረሰ ፤ እነዚህም ድጓ ፤ ጾመ ድጓ ፤ ምዕራፍ ፤ ዝማሬና መዋሥዕት ናቸው፡፡ ከደረሳቸው የዜማ መጻሕፍትም ውስጥ ትልቁ ድጓ ነው ፤ በሦስትም ይከፈላል ፤ ዮሐንስ፤ አስተምህሮና ፋሲካም ይባላሉ፡፡በንባባት ብቻ ይቀደስባቸው የነበሩትን ፲፬ቱ ቅዳሴያት በዜማ የደረሳቸው ቅዱስ ያሬድ ነው፤ ዝማሬም በ5 ይከፈላል ፡ ኅብስት ፡ ጽዋዕ ፡መንፈስ ፡ አኮቴትና ምሥጢር ይባላል፡፡
ይህ ቅዱስ ደራሲ በተወለደ በ75 ዓመቱ በሰሜን ተራራ ውስጥ ደብረ ሐዊ ከሚባል ገዳም ግንቦት 11 ቀን ተሠውሯል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባለውለታ ቅዱስ ያሬድ መምህር ወሐዋርያ ፤ መጻሕፍትን በጣዕመ ዜማ የደረሰ ፤ መዝሙረ ዳዊትን ጨምሮ ሌሎችንም ቅዱሳት መጻሕፍትን በዜማው ያመሠጠረ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሊቅ ነው፡፡

እብድ መነኲሲት

ስለ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ  ክርስቶስ ውለታና ፍቅር ራሷን እብድ  ያደረገችው መነኲሲት

ቅዱስ ጳኩሚስ ከመሠረታቸው የታቤኔዝ (ታቤኔሲዮት) ገዳማት መካከል ከወንዶች ገዳማት ራቅ ብሎ የተመሠረተ የሴቶች ገዳም ነበር። በዚያም ውስጥ አራት መቶ ሴቶች መነኮሳይያት ይኖሩ ነበር። በዚያ ገዳም ውስጥ ራሷን እንዳበደችና ርኲስ መንፈስ እንደያዛት የምታስመስል ድንግል ሴት ነበረች።

ሌሎቹ እርሷን ከመጸየፋቸው የተነሣ አብረዋት እንኳን አይበሉም ነበር ፤ እርሷ ግን ይህን ወደደችው። በምግብ ማዘጋጃ ቤት ውስጥ ወዲያ እና ወዲህ ትንከራተታለች፣ ሌሎች የተዉትንና የተናቀውን ማንኛውም ሥራ ትሠራለች፣ እነርሱ እንደሚሉት “የገዳሙ ቆሻሻ አስወጋጅ” ነበረች።

በሕይወት ዘመኗ ሁሉ ከእህቶች መነኮሳይያት መካከል ማንም በአፏ ስታላምጥ አይተዋት አያውቁም፣ በማዕድም ተቀምጣ አታውቅም ነበር። ከማዕድ የሚወድቀውን ፍርፋሪና የማዕድ ቤት እቃዎችን ስታጥብ ከዚያ በሚገኘው ነገር ብቻ ትኖር ነበር። ማንንም ተሳድባ ወይም ትንሽም ሆነ ብዙ አውርታ አታውቅም፤ ምንም እንኳ ብዙ ትሰደብ፣ ትነቀፍና ትረገም የነበረች ብትሆንም።

የእግዚአብሔር መልአክ ፒተሮአም ለሚባል ታላቅና ታዋቂ ለነበረ ታላቅ ባሕታዊ ተገለጠለትና እንዲህ አለው፦ “እንዲህ ባለ ቦታ ስለመኖርህና ስለ ሃይማኖተኛነትህ ለምን በራስህ ትመካለህ? ከአንተ የበለጠ ሃይማኖተኛና ፍጹም የሆነችን ሴት ማየት ትፈልጋለህ? ወደ ታቤኔሲዮት ገዳም ሴቶች ሂድ በዚያም በራሷ ዘውድ የደፋች ሴት ታገኛለህ። እርሷ ከአንተ የበለጠች ናት፤ በብዙዎች መካከል ብትሆንም ልቧ ከፈጣሪዋ ከእግዚአብሔር ውጪ እንዲሄድ ፈጽሞ ፈቅዳለት አታውቅምና፣ አንተ ግን እዚህ ተቀምጠህ በሃሳብ በተለያዩ ቦታዎች ትዞራለህና” አለው።

ይህን ሲሰማ ከበኣቱ ወጥቶ የማያውቅ የነበረው ባሕታዊ ወደዚያ ገዳም ሄደና ወደ ገዳሙ ለመግባት ጠየቀ። የታወቀና በዕድሜው የገፋ አረጋዊ ባሕታዊ ስለነበር ወደ ሴቶቹ ገዳም እንዲገባ ፈቀዱለት። በዚያም ሁሉንም መነኮሳይያት ያያቸው ዘንድ ጠየቀ። ሆኖም እርሷ አልመጣችም። በመጨረሻም፦ “የቀረች አንዲት አለችና ሁሉንም አምጡልኝ” አላቸው።

እነርሱም፦ “በማዕድ ማዘጋጃ ቤት ያለች አንዲት እብድ ብቻ ናት የቀረችው” አሉት። እርሱም፦ “እርሷንም ጭምር አምጡልኝና ልያት” አላቸው። ሊጠሯት ሄዱ እርሷ ግን ነገሩን አውቃው ይሁን ወይም ጉዳዩ ተገልጦላት መልስ አልሰጠቻቸውም።

በግድ ጎተቷትና፦ “ታላቁ ፒተሮአም ሊያይሽ ይፈልጋል” አሏት። በመጣች ጊዜ ከራሷ ላይ ያለውን ብጣሽ ጨርቅ አሰበና ከእግሯ ላይ ወድቆ “ባርኪኝ” አላት። እርሷም እንዲሁ ከእግሩ ላይ ወድቃ “አባቴ ሆይ አንተ ባርከኝ” አለችው። ሁሉም መነኮሳይያት ተገረሙና፦ “አባ እንዳትሰድብህ ተጠንቀቅ እብድ ናት” አሉት። አባ ፒተሮአምም ሁሉንም፦ “እብዶችስ እናንተ ናችሁ እርሷ ግን የእኔም የእናንተም እናት ናት። በፍርድ ቀንም እንደርሷ የተዘጋጀሁና የተገባሁ ሆኜ እገኝ ዘንድ ምኞቴ ነው” አላቸው።

እነዚህን ነገሮች ከዚህ አባት ሲሰሙ ሁሉም ያደረጉባትን ነገር እየተናዘዙ ከእግሩ ላይ ወደቁ። አንዲቱ የውኃ እጣቢ አፍስሼባታለሁ ትላለች፣ ሌላዋ ደግሞ መትቻታለሁ ትላለች፣ ብቻ ብዙዎች አንዷ አንድ ሌላዋ ደግሞ ሌላ ነገር እንደፈጸሙባት በመናገር ይናዘዙ ጀመር። እርሱም ከጸለየላቸው በኋላ ሄደ።

ከጥቂት ቀናት በኋላ በእህቶቿ መነኮሳይያት የሚደረግላትን ክብር መሸከም ስለከበዳት እንዲሁም ፊት በበደሏት ነገር ሁሉ ይቅርታ አድርጊልን የሚሉት ነገራቸው ስለበዛባት ገዳሙን ጥላ ጠፋች። ወዴት እንደሄደችም ሆነ የት እንደተሰወረች ወይም እንዴት እንደሞተች ግን ማንም ያወቀ የለም።

በረከቷ ይደርብን!

በዲ/ን ያረጋል አበጋዝ