ኃጢአተኛዋ/ውን ማረኝ

በድሮ ዘመን ወንጀል የሚሠሩ አመጸኞች ተይዘው ሲታሰሩ በግራና ቀኝ እጃቸው መቅዘፊያ ይዘው በጉልበታቸው ኃይል እየቀዘፉ የመንግስትን መርከቦች በባህር ላይ እንዲነዱ ይገደዱ ነበር።

አንድ ቀንም አንድ ንጉሥ ክፉ ሥራ የሠሩ ወንጀለኞች ታሥረው ወደ ሚገኙበት መርከብ ገባ። እስረኞቹም የታሰሩበትን ከባድ ሰንሰለት ሲመለከት እጅግ አዘነላቸው። በልቡም “ከእነዚህ አንዱን ልፍታ” ሲል አሰበ።

መፈታት የሚገባውንም ለማግኘት “አንተ ወደዚህ የመጣህበት ምክንያት ምንድነው?” እያለ እያንዳንዱን ሲጠይቅ እና ሲመረምር እያንዳንዳቸው እያዘኑ “ምንም ሳላጠፋና ሳልበድል ክፉ ሰዎች ነገር ሠርተው ወደ ሹማምንት አደረሱኝ እንጂ ከተባለብኝ ነገር ንጹህ ነኝ ጌታዬ ሆይ ምሕረት አድርጉልኝ ከዚህም ሥፍራ ያውጡኝ እያሉ አጠንክረው ለመኑ ።

ንጉሡም እያለፈ ሲመረምር ወደ አንድ ወጣት ደረሰና “አንተ ምን አድርገህ ነው” ቢለው ወጣቱ መልሶ “ምሕረተኛ ጌታዬ ሆይ እኔ እጅግ ክፉ አሽከር ነኝ ለአባቴና ለእናቴ አልታዘዝም በማለት ብዙ ጊዜ ኮበልኩባቸው፤  እጅግ ክፉ ሥራም ሠራሁ ፣ ሰረቅሁ ፣ አታለለሁም ፣ ያደረግሁትን ክፋት ሁሉ ዘርዝሬ ለመተረክ እጅግ ብዙ ነው።  የተገባኝን አግኝቻለሁ ይህን ቅጣት ደስ እያለኝ እሸከማለሁ ከዚህ ሺህ ጊዜ የሚበልጥ እንደሚገባኝ ተረድቻለሁ” ብሎ ኃጢአቱን ተናዘዘ።

ንጉሡ ግን እያንዳንዱ እስረኛ ለጥፋቱ የተገባውን ቅጣት እንደተቀበለ አረጋግጦ በቀልድ ሲዘልፋቸው “ኧረ በእነዚህ ደጋግ ሰዎች መካከል ይህ ክፉ እንዴት ገባ! እነዚህን ደህና ሰዎች እንዳያበላሽ ቢወጣ ይሻላል” በማለት በክፉ ሥራው አፍሮ ለተናዘዘው ምሕረት አደረገለት ፤ እርሱም ደስ ብሎት ሄደ።

የሠራነውን ኃጢአት ለመደበቅ ፣ ራሳችንን ለማጽደቅ የምንወድ ሰዎች ዛሬም አለን። ልባችንን የሚያውቅ አምላካችን ግን በቃሉ ንስሐ እንድንገባ ፣ ኃጢአታችንን እንድንናዝ ፣  ክፉ ማድረግንም እንድንተውና መልካም ማደረግን እንድንማር አዝዞናል።

ስለዚህ የሚያጸድቀው ከልብ “እኔን ኃጢአተኛዋ/ውን ማረኝ” የሚለው ብቻ ነው።

“ኃጢአቱን የሚሰውር አይለማም ፣ የሚናዘዝባትና የሚተዋት ግን ምሕረትን ያገኛል”

ምሳ 28 ፣13