የባሕረ ሐሳቡ ደራሲ ቅዱስ ድሜጥሮስ

ጥቅምት ፲፩፤፳፻፲፯ ዓመተ ምሕረት

ከምንባባት ዐውድ

አካሄዱን ሁሉ ከእግዚአብሔር ጋር ያደረገ፣ እርፍ አርቆ፣ ድኮ ታጥቆ፣ ወይን አጽድቆ የሚኖር፣ የቀለም ትምህርት ብዙም ያልነበረው ሰው ድሜጥሮስ በቅን ልቡናው መንፈስ ቅዱስ ገልጾለት ባሕረ ሐሳብን የደረሰ ቅዱስ ሰው ነው፡፡ ጌታ ባረገ በ፻፹(180) ዓ.ም የእስክንድርያ መንበር ዐሥራ ሁለተኛ ሊቀ ጳጳስ ሆኖ ተሹሟል። በሹመቱም ጊዜ በትህርምት ኗሪ ነውና አሁን አጽዋማትንና በዓላትን የምናወጣበትን ይህን የቁጥር ዘመን ባሕረ ሐሳብ ተገልጾለት ደርሶታል፤ ተናግሮታል፤ ተናግሮት ብቻም አልቀረም፤ ለሦስቱ ሊቃነ ጳጳሳት ለሮሙ በቅዱስ ጴጥሮስ መንበር ሥር ለነበረው ለአባ ፊቅጦር፣ በቅዱስ ዮሐንስ መንበር ሥር ለነበረው ለኤፌሶኑ ሊቀ ጳጳስ በቅዱስ ጴጥሮስ ካልእ ሥር ለነበረው ለአንጾኪያው መንበር ለቅዱስ መክሲሞስ ዐራተኛ፣ ለኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ ለአባ አጋብዮስ ልኮላቸዋል። እነርሱም ሐዋርያት ከአስተማሩት ትምህርት ጋር አንድ ቢሆንላቸው ተቀብለው ኑረውበታል፤ አስተምረውበታል፡፡ (ፍትሐ ነገሥት አንቀጽ ፬፥፵፩፣ ስንክሳር ኅዳር ፲)

ባሕርን ዘመን ሲል የት ይገኛል ቢሉ “እስመ በመዳልው ተደለወ ዓለም ወበመሥፈርት ሰፈራ ለባሕር፤ ዓለም በመስፈሪያ ተሰፍሯልና ባሕርንም በመስፈሪያ ሰፈራት” እንዳለ ዕዝራ (ዕዝራ ፪፥፴፯) ቅዱስ ዳዊትም “ዛቲ ባሕር አባይ ወረሐብ፤ ይህች ባሕር ታላቅና ሰፊ ናት” ብሏል፡፡ (መዝሙረ ዳዊት ፻፫፥፳፭) ሐሳብንስ ቁጥር ሲልስ የት ይገኛል ቢሉ ለትኩነኒ ሐሳበ ብላለች ኦሪት፡፡ ነቢዩ ዳዊትም “ብፁዓን እለ ተሐድገ ሎሙ ኃጢአቶሙ ወእለ ኢሐሰበ ሎሙ ኲሎ ጌጋዮሙ፤ መተላለፉ የቀረችለት ኃጢአቱም የተከደነችለት ምስጉን ነው” ብሏል፡፡ (መዝሙረ ዳዊት ፴፩፥፩) ይህን የመሠለው ሁሉ ብዙ ነው። አንድም እንዳለ ባሕረ ሐሳብ ይለዋል፡፡ ባሕር አለው ባሕር እስኪለምዱት ያስፈራል። ከለመዱት በኋላ ግን ዘግጦ ጠልቆ ግጫውን ጭንጫውን ይዞ እስከመውጣት ይደረሳል፡። ይህም ባሕረ ሐሳብ እስኪለምዱት ያስፈራል፡፡ ከለመዱት በኋላ ግን በዓላትን አጽዋማትን አወጣጣቸውን ብቻ ሳይሆን ኢይዐአርግ ኢይወርዳቸውን ሠርቀ መዓልታቸው ሠርቀ ሌሊታቸውንም ያሳውቃልና።

ነገር ግን ከእርሱ በፊት አጽዋማት አይጾሙም፤ በዓላት አይውሉም ማለት አይደለም። ከእርሱ በፊት ገና በመጀመሪያው ክፍለ ዘመን ሐዋርያት በኢየሩሳሌም ሳሉ ከምእመናን ጋር ጾምን ይጾሙ፣ ትንሣኤንም ያከብሩ ነበር። ጌታ አርባ መዓልት አርባ ሌሊት የጾመውን ሥጋ ቅቤ አንቅመስ እንጂ እየዋልን እህል ውኃ ብንቀምስ እዳ እንደማይሆን ትንሣኤንም በመጋቢት በ፳፱ (29) ያከብሩ የነበረውን ከእሑድ አይውጣ እንጂ በሚያዝያ ይሁን ተለይቶ የነበረ ሰሙነ ሕማማት በአንድ ላይ እንዲሆን ያደረጉ ሐዋርያት ናቸው።

አበዊነ ሐዋርያት አፍለስዎ ለጾመ አርብዓ ወአስተላጽቅዎ ምስለ ጾመ ሕማማት፤ አባቶቻችን ሐዋርያት ተለይቶ የነበረውን አርባ ጾም ከጾመ ሕማማት ጋር አንድ አድርገውታል” እንዳለ አቡሻክር። አቆጣጠሩን ግን ለስብከተ ወንጌል ይፋጠኑ ስለነበር አንድም ወደፊት ድሜጥሮስ እንደሚነሣ በመንፈስ ቅዱስ አውቀው ለይተው አላስተማሩም። ከሐዋርያትና ከ፸(70) አርድዕት በኋላ የተነሡ መምህራንም እንዲሁ ከዘመን ብዛት የተነሣ ዕለቱ ቢጠፋባቸው ዐቢይ ጾምን የጥምቀት ሳኒታ ጥር ፲፩(11) ቀን ጀምረው በየካቲት ፳(20) ቀን ፈጽመው በዓልን ሳይሹ ያከብሩ ነበር። በዓላትን ሲሹ ደግሞ ሰሙነ ሕማማትን በመጋቢት ፳፪(22) ቀን ጀምረው በመጋቢት ፳፰(28) ቀን ፈጽመው በ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን ትንሣኤን ያከብሩ ነበር። ከዚህም የተነሣ ዐቢይ ጾም ከእሑድ ውጭ በሌሎችም ቀን ሰኞም ማክሰኞም ይውል ነበር። በዚህ መንገድ ሲያያዝ መጥቶ ከቅዱስ ድሜጥሮስ ደርሷል። ይህም ድሜጥሮስ ከላይ እንዳልነው በሊቀ ጳጳስነቱ  ዘመን ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾምና ጾመ ሐዋርያት ከሰኞ፣ በዓለ ደብረ ዘይት፣ በዓለ ሆሳዕና፣ በዓለ ትንሣኤና በዓለ ጰራቅሊጦስ ከእሑድ፣ በዓለ ርክበ ካህናትና ጾመ ድኅነት ከረቡዕ፣ በዓለ ዕርገት ከሐሙስ፣ በዓለ ስቅለት ከዓርብ ባይወጡ፣ ባይነዋወጡ ይመኝ ነበር፡፡ እነዚህ በዓላት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነበረበት ዘመን በእነዚህ ቀናት ውለዋልና፡፡

የጻድቃን ምኞት በጎ ብቻ ነው ብሎ ጠቢቡ ሰሎሞን እንደተናገረ (ምሳሌ ፲፩፥፳፫)፤ ይህም ቅዱስ ድሜጥሮስ ይህን በጎ ሐሳብ ሲመኝና ሲያስብ ለመንፈስ ቅዱስ የተመኙትን መግለጽ ልማድ ነውና  የታዘዘ መልአክ ወደ እርሱ መጥቶ ነገር በምኞት ይገኛልን? ሱባኤ ገብተህ አግኘው ብሎ ከሌሊቱ ፳፫ (23) ሱባኤ ከቀኑ ሰባት ሱባኤ ግባ” ብሎታል፤ ስለምን “ሌሊቱን አብዝቶ ቀኑን ለምን አሳነሰው” ቢሉ ቀን የታመመ ሲጠይቅ፣ የታሰረ ሲጎበኝ፣ ወንጌል ሲያስተምር ስለሚውል ቀኑን አሳጥሮ ሌሊቱን አስረዝሞታል፡፡ አያይዞም “የሌሊቱንም የቀኑንም ሱባኤ በሰባት እያበዛህ ከ፴ (ሠላሳ) ከበለጠ በ፴ ግደፈው” ብሎታል። እንደሚታወቀው አንድ ሱባኤ ማለት ሰባት ቀናት ናቸው፡፡ ሰባት ጊዜ ሃያ ሦስት መቶ ስድሳ አንድ ይሆናል፡፡ መቶ ስድሳ አንድን በሠላሳ ስንገድፈው/ስናካፍለው/ አምስት ዐውደ ወርኅ ሆኖ ዐሥራ አንድ ይቀራል፡፡ ይህ አበቅቴ ይሁንልህ ብሎታል።

የቀኑን ሰባት ሱባኤ በሰባት ስናባዛው ዐርባ ዘጠኝ ይሆናል፡፡ በሠላሳ ስንገድፈው /ስናካፍለው/ አንድ ጊዜ ደርሶ ዐሥራ ዘጠኝ ይተርፋል፤ ይህንን “መጥቅዕ” ይሁንልህ ብሎታል። በዚህ እየቀመረ በዓላትንና አጽዋማትን አውጥቷል።

የእግዚአብሔር ድንቅ ጥበብ የተገለጠለት ይህ ቅዱስ ሰው ድሜጥሮስ የስሙ ትርጓሜ “መስታወት” ማለት ነው። መስተወት የራቀውን አቅርቦ የረቀቀውን አጉልቶ እንደሚያሳይ እርሱም በባሕረ ሐሳብ ድርሰቱ የራቀውን አቅርቦ የረቀቀውን አጉልቶ ያሳያልና ነው፡፡ አንድም “ፀሐይ” ማለት ነው፡፡ ፀሐይ ጨለማን አጥፍቶ ብርሃን እንደሚሰጥ እርሱም የደነቆረውን ጨለማውን አእምሮ በብርሃን እውቀት ያጠፋዋልና።

ትውልደ ነገዱ ከእስክንድርያ የሆነው ይህ ቅዱስ ሰው አባቱ ደማስቆ ወይም እንድራኒቆስ አጎቱ ደግሞ አርማስቆስ ወይም አስተራኒቆስ ይባላሉ። ሁለቱም በረኃብ ምክንያት ወደ ሞአብ ሀገር ተሰደው ሲኖሩ የልዕልተ ወይን አባት አርማስቆ ሚጠት(መመለስ) ሳይደረግ ዕለተ ሞቱ በደረሰ ጊዜ የልጁን የልዕልተ ወይንን ነገር ከአሕዛብ እንዳያጋባት በመልካም ሥነ ምግባር እንዲያሳድጋት አደራ ሰጥቶት ሞተ። ልዕልተ ወይንም አባቷ ከሞተ በኋላ ከአጎቷ ቤት ከድሜጥሮስ ጋራ በአንድ ላይ አፈር ፈጭተው ውኃ ተራጭተው ዘንባባ ቀጥፈው አደጉ። ሁለቱም ለአካለ መጠን በደረሱ ጊዜ የነበሩበት ቦታ አሕዛብ የበዙበት ምእመናን ያነሱበት ስለነበር ለማን እናጋባቸው ብለው ካወጡ ካወረዱ በኋላ ለአሕዛብ አጋብተናቸው ሕንጻ ሃይማኖት ከሚፈርስ እርስ በእርሳቸው አጋብተናቸው ሕንጻ ሥጋ ቢፈርስ ይሻላል ብለው እርስ በእርሳቸው አጋብተዋቸዋል። ጻድቃን ሳይቀጣጠሩ ይገናኛሉ፤ እንደሚባለው ሁለቱም ፈቃዳቸው አልነበረምና ትዳሩን ካፈረሱ ለሌላ እንዳይድሯቸው አብረው ለመኖር ተስማምተው በአንድ አልጋ ተኝተው፣ አንድ መጋረጃ ጥለው፣ አንድ አንሶላ ለብሰው፣ ወንዶችና ሴቶች በሚተዋወቁበት ግብር ሳይተዋወቁ ፵፰/48/ ዓመት ኑረዋል።

በዚህ ግብርም ሲኖር የሕዝቡ ኃጢአት ተገልጾ እየታየው ሊቆርቡ ሲመጡ “አንተ በቅተሃል ቊረብ፤ አንተ አልበቃህም ቆይ” ባላቸው ጊዜ  በዚህም “በንጹሑ በማርቆስ ወንበር ሚስቱን ይዞ እያደረ ሲሾም ዝም ብንለው ደግሞ እንዲህ ይለን ጀመር” ብለው አምተውታል፡፡

በዚህ ጊዜ መልአኩ ቅዱስ ሚካኤል ተገልጾ “ኢትፍቅድ አድኅኖ ርእከ አላ ክሥት ሎሙ ክብረከ ዘሀሎ ማዕከሌከ ወማዕከለ ብሲትከ ከመ ኢይትሀጐሉ ሕዝብ በእንቲኣከ። ሕዝቡ አንተን እያሙ እንዳይጎዱ በአንተና በሚስትህ መካከል ያለውን ግለጽላቸው” ብሎታል። እርሱም “የእግዚአብሔር ፈቃድ ከሆነማ ብሎ ሕዝቡን  እንጨት እንዲያመጡ አዘዛቸው። ያን አስደምሮ በእሳት አቃጥሎ ቅዳሴ ገባ፤ ቅዳሴውን ሲጨርስ ልብሰ ተክኖውን እንደለበሰ ማዕጠንተ ወርቁን ይዞ በእሳቱ መካከል ያጥን ነበር። አንድም “ከደመራው ላይ ቁሞ በእሳት አቃጥሉት” አላቸው። “በምን ምክንያት እንሽረዋለን ስንል በፈቃዱ ገብቶ ሊሞትልን ነው” አሉት። እርሱ ግን ምንም ሳይሆነው በመካከሉ እየተመላለሰ ያጥንና ይጸልይ ጀመር። ሚስቱንም ከምቅዋመ አንስት ከመካነ ደናግል ነበረችና አስጠርቶ ስትመጣ “ስፍሒ አጽፈኪ፤ ልብስሽን ዘርጊ” ብሎ ከፍሕሙ በእጁ እያፈሰ ከአጽፋ ላይ አደረገላትና አስታቅፎ “እየዞርሽ ተናገሪ” አላት፡፡ እርሷም ሦስት ጊዜ እየዞረች ፵፰ /48/ ዓመት ሲኖሩ በልማደ መርዓት ወመርዒዊ እንደማይተዋወቁ ገለጸችላቸው። ሕዝቡም ከጫማው ሥር ወድቀው “ኅድግ ለነ አበሳነ፤ አባታችን በድለናል ይቅር በለን” አሉት። እርሱም “ይኅድግ ይፍታሕ፤ እግዚአብሔር ይፍታ” ብሎ ናዟቸዋል፤ ኑዛዜም የተጀመረ በዚህ ጊዜ ነው።

የአባታችን ቅዱስ ድሜጥሮስ ጸሎት፣ ምልጃ እና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

 

 

 

 

 

 

 

የንሂሳው ኮከብ

ጥቅምት ፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

በዐፄ ላሊበላ ዘመነ መንግሥት፣ ዐሥራ ሦስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ወደ ሀገራችን ኢትዮጵያ የመጡት ግብጻዊው ቅዱስ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የትውልድ ስፍራቸው በላዕላይ ግብጽ ንሂሳ እንደሆነ ገድላቸው ይጠቅሳል፡፡

አባታቸው ስምዖን እናታቸው አቅሌስያ የተባሉት ወላጆቻቸው እግዚአብሔርን የሚፈሩ ደጋግ ሰዎች እንደነበሩ ሆኖም ልጅ አጥተው ፴ (ሠላሳ) ዘመን ሲያዝኑ መኖራቸውንም ታሪካቸው ያነሣል፡፡ ከዕለታት በአንዱ ቀንም እናታቸው አቅሌሲያ ቤተ እግዚአብሔር ገብታ ከሥዕለ ሥላሴ ሥር ወድቃ ስትማጸን ክብሩ ከሰማይ ከፍታ የሚበጥ ልጅ እንኪ ተቀበይ የሚል ድምጽ ሰማች፡፡ ‹‹ሥልጣኑ ከሰማይ ከፍታ ከፍ የሚል ንጽሕናው ከሚካኤል ከገብርኤል የሚተካከል ክህነቱ እንደ መልከጼዴቅ እንደ መጥምቁ ዮሐንስ እንደ ነቢይ ኤልያስ የሆነ ልጅ እንቺ ተቀበይ›› አላት፡፡ አቅሌስያም በመጋቢት ፳፱ ቀን ፀንሳ በታኅሣሥ ፳፱ ቀን ደም ግባቱ እጅግ የሚያምር ወንድ ልጅ እንደወለደች መልአኩ ቅዱስ ገብርኤል በሰው አምሳል መጥቶ ‹‹የዚህ ልጅሽ ስሙ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ይሁን›› አላት፡፡ ወዲያውም ሕፃኑ ተነሥቶ ከእናቱ ጭን ወርዶ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ሦስት ጊዜ ሰገደ፡፡ ዳግመኛም ‹‹ከጨለማ ወደ ብርሃን ለአወጣኸኝ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይሁን›› አለ፡፡

አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ የተፀነሱት መጋቢት ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን፣ የተወለዱት ደግሞ ታኀሣሥ ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ)  ነው፡፡ አባታችን ዓይን በገለጡ ጊዜ ከሚታይ ነገር ላይ እንዲያርፍ እርሳቸውም በተወለዱ ጊዜ ተነሥተው «ስብሐት ለአብ ስብሐት ለወልድ ስብሐት ለመንፈስ ቅዱስ ዘዓውፃእከኒ እምጽልመት ውስተ ብረሃን» ብለው አመስግነዋል። አባታችን ለአምላክ ሰግደው አብ ወልድ መንፈስ ቅዱስ ካመሰገኑ በኋላ እናታቸው አላቀፈቻችውም፤ ጡትም አልጠቡም፡

ጻድቁ አባታችን አኗኗራቸው እንደ መላእክት በምድረ በዳ የነበር፣ በዝቋላ ተራራ ባለው ባሕር ውስጥ ፻ (መቶ) ዓመት ተዘቅዝቀው ለኢትዮጵያ ሰዎች ምሕረትን የለመኑና ምሕረትን ያሰጡ ቅዱስ ናቸው፡፡ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ከ፭፻ (አምስት መቶ ዓመታት) በላይ በዚህ ምድር ላይ መኖራቸውንና ከትግራይ እስከ ሸዋ ባለው ክፍል ተዘዋውረው ማስተማራቸውን ገድላቸው ያትታል፡፡ በዚህም ምክንያት ዝቋላ ደብረ ከዋክብት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስንና ምድረ ከብድ ገዳማትን መትከላቸውን ታሪካቸው ያሳያል፡፡ ያረፉት በዐፄ ሕዝብ ናኝ ዘመን መጋቢት አምስት ቀን ነው፡፡ የምሕረት ቃልኪዳን የተቀበሉት ደግሞ ጥቅምት አምስት ቀን ነው፡፡ የከበረው በድነ ሥጋቸውም በምድረ ከብድ ይገኛል፡፡ ጻድቁ በትግራይ አቡዬ፣ በአማራው አቡነ፣ በኦሮሞዎች ዘንድ ደግሞ አቦ በመባል ይታወቃሉ፡፡

የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ረድኤት በረከታቸው ይደርብን፤ በጸሎታቸው ይማረን!

ምንጭ፡ – ገድለ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ፣ ተስፋ ገብረ ሥላሴ ፲፱፻፺፪ .

 

የእምነት አርበኛ

መስከረም ፳፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ጽኑ ሰማዕት የእምነት አርበኛ፣ ጠላትን ተዋጊና ድል አድራጊ እናታችን ቅድስት አርሴማ የሰማዕትነት አክሊል የተቀበለችበት የከበረች በዓል መስከረም ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በድምቀት ይከበራል፡፡

እጅግ መልከ መልካም የነበረችው ሮማዊቷ ዕንቁ ከልጅነቷ ጅምሮ ራሷን በድንግልና ሕይወት ጠብቃ የኖረች ቅድስት እንደነበረች ታሪክ ይነግረናል። በዘመኑ ነግሦ የነበረው ከሀዲው ድዮቅልጥያኖስም መልኳ ውብ የሆነች ድንግል ሊያገባ ፈልጎ ከየሀገራቱ ቆንጆ መርጠው ያመጡለት ዘንድ አገልጋዮቹን አዘዛቸው፡፡ እነርሱም በፍለጋቸው በሮሜ አገር ባለች ቤተ ክርስቲያን ቅድስት አርሴማን በማግኘት ሥዕሏን ሥለው ለንጉሡ ላኩለት፡፡ እርሱም በእጅጉ ተደስቶ እንዲያመጧት በማዘዝ ወደ ሰርጉም እንዲመጡ ለመኳንንቱ ላከ፡፡ እርሷና አብረዋት የነበሩትም ደናግል ይህነን በሰሙ ጊዜ በማዘን ድንግልናቸውን ይጠብቅላቸው ዘንድ ወደ እግዚአብሔር በመለመን ከሮም ተነሥተው በስውር የንጉሥ ድርጣድስ ግዛት ወደነበረችው ወደ አርመን ሸሽተው ሄዱ፡፡

ቅድስት አርሴማም ወደ አርመንያ ሀገር በገባች ጊዜ ከሃድያኑ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን የሚያምኑትን ክርስቲያኖችን ላይ መከራን ሲያጸኑባቸው ተመለከተችና አምላካችን ክርስቶስ “እኔ በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነትን የማምን ክርስቲያን ነኝ” በማለት መሰከረች፡፡ የመልኳን ደም ግባትም በማየት ንጉሥ ድርጣድስም ለራሱ ስለተመኛት አምላክን እንድትክድ በብዙ ሽንገላን ሊሸነግሏት ቢሞክሩም አልሆነላቸውም፤ ፈርታ ትክዳለችም ብለው በማሰብ ክርስቲያኖች ለአናብስት ወደሚጣሉበት አደባባይ በመውሰድ የተራቡ አናብስትን በላያቸው ለቀቁባቸው፤ ቅድስት አርሴማ በዚህ ጊዜ ወደ አምላክ ጸሎት አደረገች፤ ድንቅ በሆነው ተአምሩም እግዚአብሔር አናብስቱ ወደ ቅድስቷ ሳይሆን  ወደ ንጉሡ ወታደሮች በመወርወር ብዙዎችን እንዲገድሉ አደረገ፤ በኋላም ተንበርክከው ሰገዱላት፡፡

ንጉሡም በሌላ መንገድ የቅድስት አርሴማን ሐሳብ ለማስቀየርና በግድ ለጣዖታቱ እንድትሰግድ ለማድረግ አሳስሮ አማልክቱ ወዳሉበት ቤተ ጣዖት ወሰዳት፤ ይህን ጊዜ በመስቀል ምልክት ብታማትብ በጣዖታቱ ላይ አድረው ሰዎችን የሚያስቱ አጋንንት እየጮኹ ሲወጡ ጣዖታቱ በመላ እየተሰባበሩ ወድቁ፤ ዳግመኛም እስር ቤት አስገብቶ ሊያስርባት ቢጥርም የእግዚአብሔር መልአክ እንደ ነቢዩ ኤልያስ ኅብስትን መገባት፡፡ ቀጥሎም ንጉሡ ወዳለበት እየጐተቱ ወስደው ሲያቆሟት ንጉሡ ይዞ ወደ እልፍኙ ሊያስገባት ከአደባባይ ተነሥቶ ድንግል አርሴማን በያዛት ጊዜ ቅድስቷ በላይዋ ላይ ባደረው የእግዚአብሔር ኀይል በምድር ላይ ጣለችው፤ ያን ጊዜ በንዴትና በአፍረት አገልጋዮቹን ራሳን እንዲቈርጡ አዘዛቸው። በዚህ ጊዜ የክብር ባለቤት ጌታችን እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያምን አስከትሎ ተገለጸላት። ስሟን ለሚጠራ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ምሕረትን እንደሚያደርግ ቃል ኪዳንን ገባላት፡፡ በክርስቶስ ፍጹም ፍቅር፣ በእምነት ጽናትና ተጋድሎ ዕጹብ ድንቅ የሆነው ገድሏን ፈጽማ አንገቷን በመሰየፍ መስከረም ፳፱ (ሃያ ዘጠኝ) ቀን የሰማዕትነት አክሊልን ተቀዳጅታለች።

የቅድስት አርሴማ ረድኤት በረከቷ ይደርብን፤ በጸሎቷ ይማረን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር!

የኒቂያ ጉባኤ

መስከረም ፳፪፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የአርዮስ ክህደት በተስፋፋበት በ፫፻፳፭ ዓ.ም የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት የማይቀበሉ መናፍቃን ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ ጊዜውም ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ስለነበር ንጉሡ በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሄድ በየአገሩ ለነበሩ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡

ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ሊቃውንቱ በሱባኤና በጸሎት ከቆዩ እስከ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይሁን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት ፫፻፲፰ቱ የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው /ዘፍ.፲፬፥፲፬/፡፡

፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡

የቅዱሳን አባቶቻችን ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

 

ግሸን ማርያም

መስከረም ፳፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የግሸን ማርያም ደብር መመሥረት ከግማደ መስቀል ጋር የተያያዘ ዋነኛ ምክንያት አለው፡፡ ግማደ መስቀሉ ከእስክንድርያ የገባው መስከረም ፲ ቀን ቢሆንም ኢትዮጵያ ‹‹ግሸን አምባ›› የገባበት፣ መቅደስ ተሠርቶ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረውና ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ለመላው ኢትዮጵያ በጽሑፍ በመዘርዘር የገለጹበትም መስከረም ፳፩ ቀን ነው፡፡

በየዓመቱ መስከረም በባተ በ፳፩ኛው ቀንም በግሸን ደብር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች ከበረከተ መስቀሉና ከቅዱሳን ዐፅም በረከት ለማገኘት ከየክፍለ ሀገራቱ እየመጡ ያከብራሉ፡፡ ምእመናንም በግሸን ማርያም ለመገኘት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ይሄዳሉ፡፡ ኃጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ሁሉ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ‹‹ጤፉት›› በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡

አምላካችን እግዚአብሔር ከበረከተ መስቀሉ ያሳትፈን፤ አሜን!!!

 

መስቀል

መስከረም ፲፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ፍጹም ድንቅ የሆነው የጌታ ፍቅር የተገለጸበት፣ ሰላም የተበሠረበት፣ የነጻነታችን መገለጫ፣ የድኅነታችን መረጋገጫ ቅዱሱ መስቀል የተገኘበት ዕለት የከበረ ነውና በየዓመቱ በድምቀት ይከበራል፡፡ የመጀመሪያው ሰው አዳም በበደሉ ምክንያት ዕዳውን ይከፍለለት ዘንድ ሰው ሆኖ በሞቱ ሕይወትን የሰጠን አምላክ በመስቀል ተሰቅሎ ስለሆነም የመስቀሉ ነገር ለክርስቲያኖች ብዙ ትርጒም አለው፡፡

ለሰው ዘር በሙሉ በተገባለት ቃል ኪዳን መሠረት ጌታችን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ፣ ሰው ሆኖ፣ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ድኅነትን ለሰው ልጆች ሰጥቶ፣ በመስቀሉ ተጣልተው የነበሩ ሰባቱን መስተፃርራን (ሰውና እግዚአብሔርን መላእክትና ሰውን፣ ነፍስና ሥጋን፣ ሕዝብና አሕዛብን) አስታርቋል፡፡

በሐዲስ ኪዳን መስቀል የመዳን ምልክት መሆኑ የተረጋገጠበት በክርስቶስ ደም የተቀደሰ፣ የጠብ ግድግዳን ያፈረሰ፣ ቅድስናና ክብር ያለው የአበው ተስፋ የተፈጸመበት፣ ሰው ከውድቀቱ የተነሣበት መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ ነቢዩ ዳዊት ‹‹እግዚአብሔር ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማእከለ ምድር … እግዚአብሔር ግን ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድርም መካከል መድኃኒትን አደረገ›› (መዝ. ፸፫፥፲፪) እንዳለው መድኃኒት የሆነው አምላካችን በመስቀሉ አዳነን፡፡ (ዮሐ. ፲፱፥፲፯፣ኤፌ. ፪፥፲፮፣ ቆላ. ፩፥፳)

ከበዓሉ በረከት ይክፈለን፤ አሜን!!!

 

ደመራ

መስከረም ፲፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ እናት ንግሥት እሌኒ ከቁስጥንጥንያ ተነሥታ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል ከተቀበረበት ለማውጣት ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች፡፡ በደረሰች ጊዜ የጌታችን መስቀል ተአምራትን እንዳያደርግ አይሁድ በምቀኝነት ቀብረውት ነበርና የተቀበረበትን ቦታ የሚያሳያት አጥታ በመፈለግ ብዙ ጊዜ አሳለፈች፡፡

ኪራኮስ የሚባለው አረጋዊ ሰው መስቀሉ የተቀበረበትን በሥቃይና በመከራ አስጨንቃ ስትይዘው እንደነገራት ታሪኩ ያስረዳናል፤ ቁፋሮ ልታደርግበት የምትችለውን አካባቢም ሲጠቁማት ደመራ አስደምራ ዕጣን አጢሳ ወደ ፈጣሪዋ ተማፀነች፡፡ የዕጣኑ ጢስ ወደ ሰማይ ከወጣ በኋላ መንበረ ጸባዖት ደርሶ ተመልሶ መስቀሉ የተቀበረበትን ስፍራ አመለከታት፡፡ ንግሥቷም በምልክቱ መሠረት ማስቆፈር ጀመረች፡፡ ለማስቆፈር የወሰደባት ጊዜም ከመስከረም ፲፯ እስከ መጋቢት ፲ ነበር፡፡ በቁፋሮውም መጨረሻ ሦስት መስቀሎችን አገኘች፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እነዚህ መስቀሎች አንዱ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ክቡር መስቀል እንደሆነ ሌሎቹ ሁለቱ ደግሞ ፈያታዊው ዘየማንና ፈያታዊው ዘጸጋ ሁለቱ በጌታ ቀኝና ግራ የተሰቀሉት ወንበዴዎች እንደሆኑ ይገልጻሉ፡፡

ንግሥት እሌኒ ሦስቱን መስቀሎች ካገኘች የጌታችን መስቀል ለይታ ለማወቅ የሞተ ሰው አስከሬን አምጥታ በላያቸው ላይ አደረገቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ጌታ የተሰቀለበት መስቀል ሙቱን አስነሣው፡፡ ይህን ጊዜ ለይታ ያወቀችውን መስቀል በክብር ወስዳ የቤተ ክርስቲያኑም መሠረት ወዲያው እንዲጣል አደረገች፤ የደመራ ሥርዓት ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚከበር ነው፡፡

ደመራ ማለት “መጨመር፣ መሰብሰብ መከመር” ነው፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም የቃሉን ፍቺ  “ደመረ” ከሚለው የግእዝ ቃል አውጥተው ደመራ ግእዝና አማርኛን የአስተባበረ መሆኑን ይናገራሉ፤ አያይዘውም የበዓለ መስቀል ዋዜማ እንጨቶች የሚደመሩበት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ (ሰዋሰወ ግእዝ ወግስ መዝገበ ቃላት) በየዓመቱ የመስቀልን በዓል ስናከብር ደመራ የምንደምረውና የምናበራው ቅድስት ዕሌኒን አብነት በማድረግ ነው፡፡

የበረከት በዓል ያድርግልን፤ አሜን!!!

 

ተአምረኛዋ ሥዕል

መስከረም ፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

እጅጉን የሚያስደንቀው የአምላክ ሥራ የተገለጠበት፣ ለሰው ልጆች ተስፋ፣ ፈውስ ሥጋ እንዲሁም ፈውስ ነፍስን ሊሰጠን በፈቀደ እርሱ ድንቅ ተአምራትን በምድር አደረገ፤ ጌታ በትስብእቱ በዓለም ተገልጦ ካደገጋቸው ተአምራትም በተጨማሪ እርሱ ካረገ በኋላም በሰዎች አድሮ ላይ አድሮም ይሁን በተለያዩ መንገዶች ዕጹብ ሥራውን አሳይቶናል፡፡

ከዚሀ ሁሉም በበለጠ መልኩ በክብርት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም የተደረገው ምሥጢር እጅግ ይልቃል፤ ነገረ ድኅነቱን የፈጸመባት እመቤታችን ለአዳም ዘር በሙሉ ተስፋ በመሆኗ ጌታ ከእርሷ በለበሰው ሥጋ ተገልጦ ያደረገልንን ለመግለጽ ቃላት ባይኖርም ምስጋና ግን ማቅረብ የሁላችንም ፈንታ ነው፡፡ አልፎ ተርፎም እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታ ካረገች በኋላ ድንቅ ተአምርም በእርሷ ተደርጓል፡፡ ቅዱሳት መጽሐፍት በተለያዩ ጊዜ እመቤታችን ያደረገችውን ተአምር ገልጸው ጽፈዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል በመጽሐፈ ስንክሳር መስከረም ፲ ቀን ተመዝግቦ የምናገኘው አንድ ተአምረኛ ሥዕል እንዳለ ነው፤ ታሪኩም እንዲህም ይነበባል፡፡

አንዲት ማርታ የምትባል ሴት እመቤታችን ድንግል ማርያምን የምትወድና በሚቻላትም ሁሉ የምታገለግላት፣ ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባሉ ኢትዮጵያዊ መነኰስ ከእርሷ ዘንድ በእንግድነት አድረው በማግሥቱ ከቤቷ ሲወጡ ማርታ የሚሔዱበትን አገር በጠየቀቻቸው ጊዜ እርሳቸውም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ቅዱሳት መካናትን እንደሚሳለሙ ነገሯት፡፡ ማርታም ከእርሷ ገንዘብ ወስደው የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተው ይዘውላት እንዲመጡ ለመነቻቸው፡፡ መነኵሴውም በራሳቸው ገንዘብ ሥዕሉን ገዝተው እንደሚያመጡላት ቃል ገቡላት፡፡

አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሰው ቅዱሳት መካናትን ከተሳለሙ በኋላ ሥዕሏን ሳይገዙ ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ጉዞ ጀመሩ፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ?›› የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰምተው ተመልሰው መልኳ ያማረና የተወደደ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ገዝተው በሐርና በንጹሕ ልብስ ጠቅልለው ይዘው እየተጓዙ ሳሉ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ሲደርሱ ወንበዴዎች ተነሱባቸው፡፡ ሊሸሹ ሲሉም ‹‹መንገድህን ሒድ›› የሚል ቃል ከሥዕሏ ወጣ መነኵሴውም መንገዳቸውን በሰላም ተጓዙ፡፡ ሁለተኛም አንበሳ ሊበላቸው በተነሣባቸው ጊዜ ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረላቸው፡፡

አባ ቴዎድሮስ ይህን ኹሉ ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜም ያቺን ሥዕል ለማርታ ከመስጠት ይልቅ ወደ አገራቸው ሊወስዷት ወደዱ፡፡ በመርከብ ተሳፍረው በሌላ አቅጣጫ ሲሔዱም ታላቅ ነፋስ ተነሥቶ ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያ ወሰዳቸው፡፡ ከመርከብም ወርደው ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ደረሱ፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን ለማርታ አልገለጡላትም ፤ እርሷም አላወቀቻቸውም ነበር፡፡

በማግሥቱም ተሠውረው ወደ አገራቸው ሊሔዱ ሲሉ የቅፅሩ ደጃፍ ጠፍቶባቸው ሲፈልጉ ዋሉ፤ በመሸባቸው ጊዜም ወደ ማደሪያቸው ተመለሱ፡፡ ማታ ማታ በሩን ያዩታል፤ ነግቶ መሔድን ሲሹ ግን የበሩ መንገድ ይሠወርባቸዋል፡፡ እንዲህም ኾነው እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቆዩ፡፡ ማርታም ‹‹አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን? ስትቅበዘበዝ አይሃለሁና ምን ሆነህ ነው?›› ስትል ጠየቀቻችው፡፡ እርሳቸውም ከእመቤታችን ሥዕል የተደረገውን ተአምር ሁሉ ነገሯት፤ ራሳቸውንም ገለጡላትና ሥዕሏን ሰጧት፡፡ እርሷም የእመቤታችንን ሥዕል ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ልብስ በፈታችው ጊዜ ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋ ብዛት የተነሣም የአባ ቴዎድሮስን እጃቸውንና እግራቸውን ሳመች፡፡ ሥዕሏም ቅዱስ ሉቃስ የሳላት ነበረች፡፡

 

አንኳን ለበዓለ ጼዴንያ ማርያም አደረሳችሁ!

 

 

ርእሰ ዐውደ ዓመት

በእንተ ዕረፍቱ ለተክለ ሃይማኖት

የስሙ መነሻ ፊደሉ ትእምርተ መስቀል የሆነው፣ የወንጌል ተቀዳሚ ስም ማቴዎስ፣ የቅዱስ ወንጌል ጸሐፊዋና ሰባኪዋ ማርቆስ፣ የነፍስና የሥጋ ሐኪም ሉቃስ፣ ከሁሉ ይልቅ ሥልጣኑ ከፍ ያለ ጴጥሮስ፣ ሰማያዊ አርበኛ ሚናስ፣ አነዋወሩ በብቸኝነትና በንጽሕና የሆነ ኤልያስ፣ የቤተ ክርስቲያን የልጆቿ አባት ባስልዮስ፣ የቤተ ራባው ጸዋሚ ተሐራሚ ዮሐንስ፣ ዐሥረኛው የአርማንያው ጎርጎርዮስ፣ ግሙደ እግር ያዕቆብ ሐዋርያ፣ እንግዳ መቀበል ፍጹም ተግባሩ የሆነ አብርሃም፣ ጸሐፊ ምሥጢራት ወጥበባት ሄኖክ፣ መሥዋዕቱ የሠመረለት አቤል፣ ሕዝብን የሚያስተዳድር ዮሴፍ፣ እግዚአብሔርን በንጹሕ ልቡና የሚያመሰግን ዳዊት፣ ከሐዲዎችን የሚበቀል ቄርሎስ፣……………..