የኒቂያ ጉባኤ

መስከረም ፳፪፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የአርዮስ ክህደት በተስፋፋበት በ፫፻፳፭ ዓ.ም የእግዚአብሔር ወልድን የባሕርይ አምላክነት የማይቀበሉ መናፍቃን ቁጥር እየጨመረ በመምጣቱ ጊዜውም ታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ‹‹አብያተ ጣዖታት ይትአጸዋ አብያተ ክርስቲያናት ይትረኀዋ፤ የጣዖታት ቤቶች ይዘጉ! አብያተ ክርስቲያናት ይከፈቱ!›› የሚል ዐዋጅ የነገረበት ስለነበር ንጉሡ በኒቅያ የሃይማኖት ጉባኤ እንዲካሄድ በየአገሩ ለነበሩ ሊቃውንት መልእክት አስተላለፈ፡፡

ከሚያዝያ ፳፩ ቀን ጀምሮ እስከ መስከረም ፳፩ ቀን ድረስ ፳፫፻፵፰ (ሁለት ሺሕ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንት) ሊቃውንት በኒቅያ ተሰበሰቡ፡፡ ሊቃውንቱ በሱባኤና በጸሎት ከቆዩ እስከ ኅዳር ፱ ቀን በንጉሥ ቈስጠንጢኖስ ሊቀ መንበርነት፣ በእለእስክንድሮስ አፈ ጉባኤነት ጉባኤው ተጀመረ፡፡ ንጉሡ ሊቃውንቱን ‹‹ስማችሁን፣ አገራችሁንና ሃይማኖታችሁን ጽፋችሁ ስጡኝ›› ባላቸው ጊዜም ከ፳፫፻፵፰ቱ መካከል ፫፻፲፰ (ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንቱ) ሊቃውንት ሃይማኖታቸውን ሲገልጹ እንደ አንድ ልብ መካሪ፣ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው ‹‹ዘዕሩይ ምስለ አብ በመለኮቱ፤ ወልድ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር በመለኮት፣ በሥልጣን፣ በፈቃድ፣ በህልውና አንድ ነው›› ብለው ጽፈው ሰጡት፡፡ ንጉሡም ‹‹ሃይማኖት እንደ ፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት ይሁን›› ብሎ ዐዋጅ አስነግሯል፡፡ እነዚህ ሊቃውንት በኦሪት ዘፍጥረት የተጠቀሱት ፫፻፲፰ቱ የአብርሃም ብላቴኖች ምሳሌዎች ናቸው /ዘፍ.፲፬፥፲፬/፡፡

፫፻፲፰ቱ ሊቃውንት በጉባኤው አርዮስን አውግዘው በመለየት ‹‹ነአምን በአሐዱ አምላክ፤ በአንድ አምላክ እናምናለን›› የሚለውን የሃይማኖት ጸሎት (የሃይማኖት መሠረት) እና ሌሎችንም የሃይማኖት ውሳኔዎችን ደንግገዋል፡፡

የቅዱሳን አባቶቻችን ጸሎት፣ አማላጅነትና ተራዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

 

ግሸን ማርያም

መስከረም ፳፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የግሸን ማርያም ደብር መመሥረት ከግማደ መስቀል ጋር የተያያዘ ዋነኛ ምክንያት አለው፡፡ ግማደ መስቀሉ ከእስክንድርያ የገባው መስከረም ፲ ቀን ቢሆንም ኢትዮጵያ ‹‹ግሸን አምባ›› የገባበት፣ መቅደስ ተሠርቶ ቅዳሴ ቤቱ የተከበረውና ዐፄ ዘርዐ ያዕቆብ ለመላው ኢትዮጵያ በጽሑፍ በመዘርዘር የገለጹበትም መስከረም ፳፩ ቀን ነው፡፡

በየዓመቱ መስከረም በባተ በ፳፩ኛው ቀንም በግሸን ደብር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች ከበረከተ መስቀሉና ከቅዱሳን ዐፅም በረከት ለማገኘት ከየክፍለ ሀገራቱ እየመጡ ያከብራሉ፡፡ ምእመናንም በግሸን ማርያም ለመገኘት ከዚያን ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ ይሄዳሉ፡፡ ኃጢአታቸውን ለካህን ተናዘው፣ ንስሐ ገብተው በዚህ ዕለት ወደ ግሸን ደብረ ከርቤ በመሔድ የሚጸልዩና የሚማጸኑ ሁሉ እስከ ሰባት ትውልድ ድረስ የምሕረት ቃል ኪዳን እንደሚያገኙም ‹‹ጤፉት›› በተባለችው መጽሐፍ ተጠቅሷል፡፡

አምላካችን እግዚአብሔር ከበረከተ መስቀሉ ያሳትፈን፤ አሜን!!!

 

መስቀል

መስከረም ፲፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

ፍጹም ድንቅ የሆነው የጌታ ፍቅር የተገለጸበት፣ ሰላም የተበሠረበት፣ የነጻነታችን መገለጫ፣ የድኅነታችን መረጋገጫ ቅዱሱ መስቀል የተገኘበት ዕለት የከበረ ነውና በየዓመቱ በድምቀት ይከበራል፡፡ የመጀመሪያው ሰው አዳም በበደሉ ምክንያት ዕዳውን ይከፍለለት ዘንድ ሰው ሆኖ በሞቱ ሕይወትን የሰጠን አምላክ በመስቀል ተሰቅሎ ስለሆነም የመስቀሉ ነገር ለክርስቲያኖች ብዙ ትርጒም አለው፡፡

ለሰው ዘር በሙሉ በተገባለት ቃል ኪዳን መሠረት ጌታችን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ፣ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍሷ ነፍስ ነሥቶ፣ ሰው ሆኖ፣ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በመስቀል ተሰቅሎ፣ ድኅነትን ለሰው ልጆች ሰጥቶ፣ በመስቀሉ ተጣልተው የነበሩ ሰባቱን መስተፃርራን (ሰውና እግዚአብሔርን መላእክትና ሰውን፣ ነፍስና ሥጋን፣ ሕዝብና አሕዛብን) አስታርቋል፡፡

በሐዲስ ኪዳን መስቀል የመዳን ምልክት መሆኑ የተረጋገጠበት በክርስቶስ ደም የተቀደሰ፣ የጠብ ግድግዳን ያፈረሰ፣ ቅድስናና ክብር ያለው የአበው ተስፋ የተፈጸመበት፣ ሰው ከውድቀቱ የተነሣበት መሆኑ ተረጋግጧል፡፡ ነቢዩ ዳዊት ‹‹እግዚአብሔር ንጉሥ ውእቱ እምቅድመ ዓለም ወገብረ መድኃኒተ በማእከለ ምድር … እግዚአብሔር ግን ከዓለም አስቀድሞ ንጉሥ ነው፤ በምድርም መካከል መድኃኒትን አደረገ›› (መዝ. ፸፫፥፲፪) እንዳለው መድኃኒት የሆነው አምላካችን በመስቀሉ አዳነን፡፡ (ዮሐ. ፲፱፥፲፯፣ኤፌ. ፪፥፲፮፣ ቆላ. ፩፥፳)

ከበዓሉ በረከት ይክፈለን፤ አሜን!!!

 

ደመራ

መስከረም ፲፬፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

የታላቁ ንጉሥ ቈስጠንጢኖስ እናት ንግሥት እሌኒ ከቁስጥንጥንያ ተነሥታ ከጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን መስቀል ከተቀበረበት ለማውጣት ወደ ኢየሩሳሌም ተጓዘች፡፡ በደረሰች ጊዜ የጌታችን መስቀል ተአምራትን እንዳያደርግ አይሁድ በምቀኝነት ቀብረውት ነበርና የተቀበረበትን ቦታ የሚያሳያት አጥታ በመፈለግ ብዙ ጊዜ አሳለፈች፡፡

ኪራኮስ የሚባለው አረጋዊ ሰው መስቀሉ የተቀበረበትን በሥቃይና በመከራ አስጨንቃ ስትይዘው እንደነገራት ታሪኩ ያስረዳናል፤ ቁፋሮ ልታደርግበት የምትችለውን አካባቢም ሲጠቁማት ደመራ አስደምራ ዕጣን አጢሳ ወደ ፈጣሪዋ ተማፀነች፡፡ የዕጣኑ ጢስ ወደ ሰማይ ከወጣ በኋላ መንበረ ጸባዖት ደርሶ ተመልሶ መስቀሉ የተቀበረበትን ስፍራ አመለከታት፡፡ ንግሥቷም በምልክቱ መሠረት ማስቆፈር ጀመረች፡፡ ለማስቆፈር የወሰደባት ጊዜም ከመስከረም ፲፯ እስከ መጋቢት ፲ ነበር፡፡ በቁፋሮውም መጨረሻ ሦስት መስቀሎችን አገኘች፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እነዚህ መስቀሎች አንዱ የጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ክቡር መስቀል እንደሆነ ሌሎቹ ሁለቱ ደግሞ ፈያታዊው ዘየማንና ፈያታዊው ዘጸጋ ሁለቱ በጌታ ቀኝና ግራ የተሰቀሉት ወንበዴዎች እንደሆኑ ይገልጻሉ፡፡

ንግሥት እሌኒ ሦስቱን መስቀሎች ካገኘች የጌታችን መስቀል ለይታ ለማወቅ የሞተ ሰው አስከሬን አምጥታ በላያቸው ላይ አደረገቻቸው፡፡ በዚህም ጊዜ ጌታ የተሰቀለበት መስቀል ሙቱን አስነሣው፡፡ ይህን ጊዜ ለይታ ያወቀችውን መስቀል በክብር ወስዳ የቤተ ክርስቲያኑም መሠረት ወዲያው እንዲጣል አደረገች፤ የደመራ ሥርዓት ከዚህ ጋር ተያይዞ የሚከበር ነው፡፡

ደመራ ማለት “መጨመር፣ መሰብሰብ መከመር” ነው፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም የቃሉን ፍቺ  “ደመረ” ከሚለው የግእዝ ቃል አውጥተው ደመራ ግእዝና አማርኛን የአስተባበረ መሆኑን ይናገራሉ፤ አያይዘውም የበዓለ መስቀል ዋዜማ እንጨቶች የሚደመሩበት መሆኑን አስረድተዋል፡፡ (ሰዋሰወ ግእዝ ወግስ መዝገበ ቃላት) በየዓመቱ የመስቀልን በዓል ስናከብር ደመራ የምንደምረውና የምናበራው ቅድስት ዕሌኒን አብነት በማድረግ ነው፡፡

የበረከት በዓል ያድርግልን፤ አሜን!!!

 

ተአምረኛዋ ሥዕል

መስከረም ፰፤፳፻፲፰ ዓ.ም.

እጅጉን የሚያስደንቀው የአምላክ ሥራ የተገለጠበት፣ ለሰው ልጆች ተስፋ፣ ፈውስ ሥጋ እንዲሁም ፈውስ ነፍስን ሊሰጠን በፈቀደ እርሱ ድንቅ ተአምራትን በምድር አደረገ፤ ጌታ በትስብእቱ በዓለም ተገልጦ ካደገጋቸው ተአምራትም በተጨማሪ እርሱ ካረገ በኋላም በሰዎች አድሮ ላይ አድሮም ይሁን በተለያዩ መንገዶች ዕጹብ ሥራውን አሳይቶናል፡፡

ከዚሀ ሁሉም በበለጠ መልኩ በክብርት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም የተደረገው ምሥጢር እጅግ ይልቃል፤ ነገረ ድኅነቱን የፈጸመባት እመቤታችን ለአዳም ዘር በሙሉ ተስፋ በመሆኗ ጌታ ከእርሷ በለበሰው ሥጋ ተገልጦ ያደረገልንን ለመግለጽ ቃላት ባይኖርም ምስጋና ግን ማቅረብ የሁላችንም ፈንታ ነው፡፡ አልፎ ተርፎም እርሷም እንደ ልጇ ተነሥታ ካረገች በኋላ ድንቅ ተአምርም በእርሷ ተደርጓል፡፡ ቅዱሳት መጽሐፍት በተለያዩ ጊዜ እመቤታችን ያደረገችውን ተአምር ገልጸው ጽፈዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል በመጽሐፈ ስንክሳር መስከረም ፲ ቀን ተመዝግቦ የምናገኘው አንድ ተአምረኛ ሥዕል እንዳለ ነው፤ ታሪኩም እንዲህም ይነበባል፡፡

አንዲት ማርታ የምትባል ሴት እመቤታችን ድንግል ማርያምን የምትወድና በሚቻላትም ሁሉ የምታገለግላት፣ ቤቷንም ለእንግዳ ማደሪያ ያደረገች ነበረች፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቴዎድሮስ የሚባሉ ኢትዮጵያዊ መነኰስ ከእርሷ ዘንድ በእንግድነት አድረው በማግሥቱ ከቤቷ ሲወጡ ማርታ የሚሔዱበትን አገር በጠየቀቻቸው ጊዜ እርሳቸውም ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ቅዱሳት መካናትን እንደሚሳለሙ ነገሯት፡፡ ማርታም ከእርሷ ገንዘብ ወስደው የእመቤታችንን ሥዕል ገዝተው ይዘውላት እንዲመጡ ለመነቻቸው፡፡ መነኵሴውም በራሳቸው ገንዘብ ሥዕሉን ገዝተው እንደሚያመጡላት ቃል ገቡላት፡፡

አባ ቴዎድሮስ ኢየሩሳሌም ደርሰው ቅዱሳት መካናትን ከተሳለሙ በኋላ ሥዕሏን ሳይገዙ ወደ ሀገራቸው ለመመለስ ጉዞ ጀመሩ፡፡ ያን ጊዜም ‹‹ሥዕል መግዛትን ለምን ረሳህ?›› የሚል የሚያስደነግጥ ቃልን ሰምተው ተመልሰው መልኳ ያማረና የተወደደ የእመቤታችን ማርያምን ሥዕል ገዝተው በሐርና በንጹሕ ልብስ ጠቅልለው ይዘው እየተጓዙ ሳሉ ከሚያስፈራ ዱር ውስጥ ሲደርሱ ወንበዴዎች ተነሱባቸው፡፡ ሊሸሹ ሲሉም ‹‹መንገድህን ሒድ›› የሚል ቃል ከሥዕሏ ወጣ መነኵሴውም መንገዳቸውን በሰላም ተጓዙ፡፡ ሁለተኛም አንበሳ ሊበላቸው በተነሣባቸው ጊዜ ከዚያች ሥዕል የሚያሥፈራ ድምፅ ወጥቶ አንበሳውን አባረረላቸው፡፡

አባ ቴዎድሮስ ይህን ኹሉ ድንቅ ተአምር ባዩ ጊዜም ያቺን ሥዕል ለማርታ ከመስጠት ይልቅ ወደ አገራቸው ሊወስዷት ወደዱ፡፡ በመርከብ ተሳፍረው በሌላ አቅጣጫ ሲሔዱም ታላቅ ነፋስ ተነሥቶ ወደ ማርታ አገር ወደ ጼዴንያ ወሰዳቸው፡፡ ከመርከብም ወርደው ከብዙ እንግዶች ጋር ወደዚያች መበለት ቤት ደረሱ፡፡ ነገር ግን ማንነታቸውን ለማርታ አልገለጡላትም ፤ እርሷም አላወቀቻቸውም ነበር፡፡

በማግሥቱም ተሠውረው ወደ አገራቸው ሊሔዱ ሲሉ የቅፅሩ ደጃፍ ጠፍቶባቸው ሲፈልጉ ዋሉ፤ በመሸባቸው ጊዜም ወደ ማደሪያቸው ተመለሱ፡፡ ማታ ማታ በሩን ያዩታል፤ ነግቶ መሔድን ሲሹ ግን የበሩ መንገድ ይሠወርባቸዋል፡፡ እንዲህም ኾነው እስከ ሦስት ቀን ድረስ ቆዩ፡፡ ማርታም ‹‹አባቴ ሆይ አእምሮህ ተነክቷልን? ስትቅበዘበዝ አይሃለሁና ምን ሆነህ ነው?›› ስትል ጠየቀቻችው፡፡ እርሳቸውም ከእመቤታችን ሥዕል የተደረገውን ተአምር ሁሉ ነገሯት፤ ራሳቸውንም ገለጡላትና ሥዕሏን ሰጧት፡፡ እርሷም የእመቤታችንን ሥዕል ተቀብላ የተጠቀለለችበትን ልብስ በፈታችው ጊዜ ወዝ ከሥዕሊቱ ሲንጠፈጠፍ አገኘች፡፡ ከደስታዋ ብዛት የተነሣም የአባ ቴዎድሮስን እጃቸውንና እግራቸውን ሳመች፡፡ ሥዕሏም ቅዱስ ሉቃስ የሳላት ነበረች፡፡

 

አንኳን ለበዓለ ጼዴንያ ማርያም አደረሳችሁ!

 

 

ርእሰ ዐውደ ዓመት

በእንተ ዕረፍቱ ለተክለ ሃይማኖት

የስሙ መነሻ ፊደሉ ትእምርተ መስቀል የሆነው፣ የወንጌል ተቀዳሚ ስም ማቴዎስ፣ የቅዱስ ወንጌል ጸሐፊዋና ሰባኪዋ ማርቆስ፣ የነፍስና የሥጋ ሐኪም ሉቃስ፣ ከሁሉ ይልቅ ሥልጣኑ ከፍ ያለ ጴጥሮስ፣ ሰማያዊ አርበኛ ሚናስ፣ አነዋወሩ በብቸኝነትና በንጽሕና የሆነ ኤልያስ፣ የቤተ ክርስቲያን የልጆቿ አባት ባስልዮስ፣ የቤተ ራባው ጸዋሚ ተሐራሚ ዮሐንስ፣ ዐሥረኛው የአርማንያው ጎርጎርዮስ፣ ግሙደ እግር ያዕቆብ ሐዋርያ፣ እንግዳ መቀበል ፍጹም ተግባሩ የሆነ አብርሃም፣ ጸሐፊ ምሥጢራት ወጥበባት ሄኖክ፣ መሥዋዕቱ የሠመረለት አቤል፣ ሕዝብን የሚያስተዳድር ዮሴፍ፣ እግዚአብሔርን በንጹሕ ልቡና የሚያመሰግን ዳዊት፣ ከሐዲዎችን የሚበቀል ቄርሎስ፣……………..

‹‹እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?››

ከነገደ ብንያም የተወለደው ነቢዩ ሚክያስ የስሙ ትርጓሜ ‹‹እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው?›› ነው። እንደ ስሙ ትርጕምም የእግዚአብሔር ቸርነት ከየትኛውም ኃጢአትና ከየትኞቹም በቊጥር የበዙ ኃጢአተኞች ይልቅ ታላቅ መሆኑን፣ ይልቁንም እግዚአብሔር ኃጢአትን እንጂ ኃጢአተኞችን የማይጸየፍ እንደሆነ አስተምሯል። በሰባት ምዕራፎች በተጠቃለለ ነገረ ድኅነትንና ንስሐን ማዕከል ያደረገ ትምህርቱና ትንቢቱ መሲሑ የሚወለደበትን ስፍራ ሳይቀር ‘ደረቅ ትንቢት’ በግልጽ እንዲህ ሲል “አንቺ ቤተልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘለዓለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል” ተናግሯል።

በእንተ ስምዐ ለማርያም

ዛሬ በፍልሰታዋ በአዛኝት የጾም ወራት

ልመናዬ አይደለም ፍርፋሪ ኩርማን ዱቄት

በደብረ ታቦሩ በዓል በተገለጸበት ምሥጢር

የዕለት ጉርሴን አልጠይቅም ቆሜ በደጅዎ በር

ልለምን . . . በእንተ ስማ ለማርያም

ስለ ወላዲተ አምላክ . . .

ስማችን!

ሕፃን ሆኖ አባቷ፣ አባት ሲሆን ልጇ

በእምነት ያበረታት ወርዶ ከእቅፍ እጇ

ወደ ሞት እንዳትሄድ ሥቃይን ተሰቅቃ

ለልጄ እንዳትል የመከራ እሳት ሞቃ

ቆሞ መሰከረ ድምጹን አሰምቶ

ከአላዊው ንጉሥ በመንፈስ ተሞልቶ