የማይስማሙትን እንዲስማሙ አድርጎ ፈጠራቸው

ሊቀ ሊቃውንት ስምዐኮነ መልአክ

እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥረው ከሰባት እርስ በርሳቸው ከማይስማሙ ነገሮች ፈጥሮታል:: አራቱ ባሕርያት እግዚአብሔር በጥበቡ ካላስማማቸው በቀር መቼም የማይስማሙ ባላንጣዎች ናቸው፡፡ ምን አልባት ተስማምተው ከተገኙም በጽርሐ አርያም ባለው የእግዚአብሔር ማደሪያ ብቻ ሊሆን ይችላል፡፡ በዚያ ግን ባለጠጋው እግዚአብሔር የውኃ ጣራ፤ የእሳት ግድግዳ ያለው አዳራሽ ሠርቷል፤ ዓለም ከተፈጠረ እስከ ዛሬ ተስማምተው ይኖራሉ እንጂ አንዱ ባንዱ ላይ በክፋት ተነሳስቶ ውኃው እሳቱን አሙቆት፤ እሳቱም ውኃውን አጥፍቶት አያውቅም፡፡ ይህ ትዕግስታቸው በፍጥረት ሁሉ አንደበት ሠሪያቸውን እንዲመሰገን አድርጎታል::

በታች ባለው ምድራዊ ዓለምም ያለው ብቸኛው የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የሰው ልጅ ነውና እነዚህ እርስ በእርስ የማይስማሙ መስተጻርራን ነገሮች ተስማምተው የሚኖሩበት ዓለም ሆኗል፡፡ እሳት ከውኃ፤ ነፋስ ከመሬት ጋር የሚያጣብቃቸውን የፍቅር ሰንሰለት የሰው አዕምሮ ተመራምሮ ሊደርስበት የማይችል ታላቅ ምሥጢር ነው፡፡ ግን እንዴት ይሆናል? ነፋስ መሬትን ሳይጠርገው፤ መሬትም ነፋስን ገድቦ ይዞ መላወሻ መንቀሳቀሻ ሳያሳጣው፤ ተስማምተው እንዲኖሩ ያደረገ እግዚአብሔር ታላቅ ነው፡፡ ውኃና እሳት ተቻችለው አንድ ቤት ውስጥ መኖር ችለዋል፤ የጥንት ጠላትነታቸውን በጥበበ እግዚአብሔር አስታራቂነት እርግፍ አድርገው ትተው ከሞት በቀር ማንም ላይለያቸው በቃል ኪዳን ተሳስረዋል፡፡

አሁን እሳት ውኃን በቁጣ ቃል አይናገረውም ውኃም በእሳት ፊት ሲደነግጥ አይታይም እንዲያው ሰው በሚባለው ዓለም ውስጥ በሰላም ይኖራሉ እንጂ፡፡ የነቢዩ ዳዊት ቃል ለነርሱ ያለፈ ታሪክ ማስታወሻ ቃል ነው፡፡ “ከመጸበል ዘይግህፎ ነፋስ እምገጸ ምድር፤ ከምድር ገጽ ላይ ነፋስ እንደሚበትነው አፈር…..” ይባል ነበር አባቶቻችንም ስለ ወንጌላዊው ማቴዎስ ሲተርኩልን “ሶቤሃኬ ተንሥአ ማቴዎስ ወንጌላዊ ከመ ተንሥኦተ ማይ ላዕለ እሳት፤ ውኃ በእሳት ላይ በጠላትነት እንዲነሣ ወንጌላዊው ማቴዎስም ተናዶ ተነሣ” በማለት ወንጌልን ለመጻፍ የተነሣበትን ምሥጢር አጫውተውናል፡፡ ማንኛውም ነገር አጥፊና ጠፊ ሆኖ ከተነሣ በእሳትና በውኃ መመሰል የተለመደ ጉዳይ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልዩ ሥነ ተፈጥሮ ባረፈበት የሰው ሕይወት ግን እንዲህ አይደለም፡፡ እሳትና ውኃ እስከ መቃብር የሚዘልቅ የፍቅር መንገድ ጀምረዋል ነፋስና መሬትም እስከ ፀኣተ ነፍስ ላይለያዩ ወስነዋል፡፡ ይህ የፍቅር ኑሯቸው ደግሞ ሌላ አዲስ ነገር ፈጠረላቸው ለመላእክት እንኳን ያልተደረገ አዲስ ነገር እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ላይ እንዲያደርግ አስገድዶታል፤ የማትሞትና የማትበሰብስ ነፍስን በሥጋ ውስጥ አኖራት፡፡ ሌላ አስደናቂ ነገር ነው፡፡ የአራቱ መስተጻርራን መዋሐድ የፈጠረው ሌላ አስደናቂ መዋሐድ፡፡

በጥቂቱም ቢሆን ከመላእክት ጋር ዝምድና ያላት ነፍስ በእጅጉ ከማይስማማት የሥጋ ባህርይ ጋር ተስማምታ መኖሯ አስደናቂ ነገር ነው፡፡ አራቱ ባህርያት ልዩነታቸውን አጥፍተው በፍቅር ተስማምተው ብታይ እሷም ሁሉን ረስታ ከሥጋ ጋር ተስማምታ ለመኖር ወሰነች እናም ሥጋ ብዙ ድካሞች እንዳሉበት ብታውቅም ከነድካሙ ታግሳው አብራው ትኖራለች፡፡ ሥጋ ይተኛል ያንቀለፋል፤ እሷ ግን በድካሙ ሳትነቅፈው እንዲያውም ተኝቶም በሕልም ሌሎችን የሕልም ዓለማት እንዲጎበኝ በተሰጣት ጸጋ ይዛው ትዞራለች፡፡ በሕልም ሠረገላ ተጭኖ በነፍስ መነጽርነት አነጣጥሮ የተመለከተውን አንዳንዱን ሲደርስበት ሌላውንም በሩቅ አይቶ ተሳልሞ ሲተወው ይኖራል፡፡

ያዕቆብ እንዳየው የተጻፈው ሕልም አስገራሚ ከሚባሉት ሕልሞች ዋናው ነው፡፡ ምክንያቱም በምድር ያለ ሰው የእግዚአብሔርን ዙፋን በሕልም ያየበትና የሰማይ መላእክትን የአገልግሎት ሕይወት የተካፈለበት ሕልም ስለሆነ ነው ዘፍ28÷10፡፡ ያዕቆብ በነፍሱ ያየው ይህ አስደናቂ ሕልም ከሦስት ሺህ የሚበዙ ዓመታትን አሳልፎ ፍጻሜውን በክርስቶስ ልደት አይተናል ዮሐ1÷50፡፡ ታዲያ ነፍሳችን በዘመን መጋረጃ የተጋረዱ ምሥጢራትን ሳይቀር አሾልካ መመልከት የምትችል ኃይል ናት ማለት ነው፤ እሷም የፍቅር ውጤት ናት፡፡ ተፈጥሮአችን ከምታስተምረን ነገሮች አንዱ ትዕግስት ነው፡፡ ሁልጊዜ ትዕግስት ፍቅርን፤ ፍቅር ደግሞ ሁሉን ሲገዛ ይኖራል ሰማያዊም ሆነ መሬታዊ ኃይል ለነዚህ ነገሮች ይሸነፋል ምን አልባት ሰው ሁሉን አሸንፎ የመኖሩ ምሥጢር ይህ ሊሆን ይችላል፡፡ ተፈጥሮው ትዕግስትን፤ ትግስት ደግሞ ፍቅርን ወልዳለታለች ከዚህ የተነሣ ተፈጥሮን መቆጣጠር የቻለ እንደሰው ያለ ማንም የለም፡፡ እስኪ ልብ በሉት ሞትን በቃሉ የሚገስጽ፣ ደመናትን በእጆቹ የሚጠቅስ፣ የሰማይን መስኮቶች የሚመልስ፤ እስከ ሰባተኛው ሰማይ ወጥቶ የሚቀድስ የሰው ልጅ አይደል? ባንድም ሆነ በሌላ መንገድ ሁሉም ነገር ለሰው አገልግሎት ሲባል የተፈጠረ ነው፡፡ የማይስማሙትን አስማምቶ ባንድ ላይ ማኖር መቻል ትልቅ ጥበብ ከመሆኑም በላይ ትዕግስት ካለ ሁሉም ፍጥረት ተቻችሎ ባንድነት መኖር እንደሚችልም አመላካች ነው፡፡

ተቻችለው የመኖራቸው ምሥጢር፡-
እያንዳንዳቸውን ብንመለከት አራቱም ባህርያት ለያንዳንዳቸው ሁለት ሁለት ባሕርያት አሏቸው፡- የእሳት ባህርይ ውእየትና /ማቃጠል/ ይብሰት /ደረቅነት/ ሲሆን፤ የውኃ ደግሞ ቆሪርነትና /ቀዝቃዛ/ ርጡብነት /ርጥብነት/ ናቸው፡፡ እነዚህ ሁለቱም ባህርያት በምንም ይሁን በምን መስማማት አይቻላቸውም እግዚአብሔር ግን በሌላ በኩል የእርቅ መንገድ ፈልጎ ሲያስታርቃቸው እንመለከታለን፡፡ ይሄውም በነፋስና በመሬት በኩል ነው፤ የነፋስ ባህርያት ውእየትና ቆሪርነት ሲሆን የመሬት ባህርያት ደግሞ ይቡስነትና ርጡብነት ናቸው፡፡ አሁን ዝምድናውንና ማንን በማን እንዳስታረቀ ስንመለከት እሳትና ውኃን በነፋስ አስታርቋቸዋል፡፡ ነፋስ በውዕየቱ ከእሳት፤ በቆሪርነቱ ከውኃ ጋር ተዘምዶ አለው፤ በመካከል ለሁለቱም ዘመድ ሆኖ በመገኘቱ እሳትን ከውኃ ጋር አንገቱን ደፍቶ እንዲኖር አድርጎታል፡፡ የመሐል ዳኛ ባይኖራቸው ኖሮ እሳቱ ውኃውን እንደ ክረምት ነጎድጓድ አስጩሆት ውኃውም እሳቱን እንደ መብረቅ ሳይታሰብ በላዩ ላይ ወርዶበት ተያይዘው በተላለቁ ነበር፡፡

ነፋስና መሬትን ደግሞ ውኃን ሽማግሌ አድርጎ ሲገላግላቸው እናያለን ውኃ በቀዝቃዛነቱ፤ ነፋስን በርጥበቱ መሬትን ይዘመዳቸዋል ይህን ዝምድናውን ተጠቅሞ ሁለቱን መስተጻርራን በትዕግስት አቻችሏቸው ይኖራል፡፡ አብረው በመኖራቸው ደግሞ ነፋስ ከመሬት ትእግስትን ተምሯል አብሮ መኖር ከሰይጣን ጋር ካልሆነ ከማንኛውም ፍጥረት ጋር ካወቁበት ጠቃሚ ነው፤ አብሮነት የለወጣቸው ህይወቶች ብዙ ናቸው፡፡ ዐስራ ሦስቱን ሽፍቶች ያስመነነው አንድ ቀን ከናፍርና ከሚስቱ ጋር የተደረገ ውሎ ነው፤ ያውም ገንዘብ ሊዘርፉና አስካፍን ሊማርኩ ሄደው ህይወታቸውን አስማረኩ፤ የጦር መሣሪያ ታጥቀው ሄደው ላልታጠቀው ተንበረከኩ፡፡ ክርስትና እንዲህ ሲሆን የእውነተኛነቱ ማረጋገጫ ነው ምክንያቱም ክርስትና ማለት አንዱ ብዙዎችን የሚያሸንፍበት፤ ወታደሩ ንጉሡን የሚማርክበት፤ ገረድ እመቤቷን የምታንበረክክበት ያሸናፊዎች ሕይወት ነውና፡፡ ሳይታኮሱ ደም ሳያፈሱ አብሮ በመዋል ብቻ ከህይወታቸው በሚወጣው የሕይወት መዓዛ ብቻ የሰውን አካሉን ብቻ ሳይሆን ልቡን ጭምር መማረክ ያስችላል፡፡ ዐስራ ሦስት ሰው ባንድ ጊዜ እጅ የሰጠውም ከዚህ የተነሣ ነው እናም አብሮነት የሚጎዳው ከሰይጣን ጋር ብቻ ከሆነ ነው፡፡ ከዚያ ውጭ ግን የአትናስያን ሕይወት የለወጠ፤ ኃጢአቷን ከልቧ እንደ ሰም ያቀለጠ፤ ላንዲት ሰዓት ከዮሐንስ ሐጺር ጋር የነበራት ቆይታ ነው፡፡ እነ ማርያም ግብፃዊትን ከዘማዊነት ወደ ድንግልና ሕይወት የለወጠስ ላንድ ቀን ብቻ ወደ ኢየሩሳሌም ከሚሄዱ ሰዎች ጋር የተደረገ ውሎም አይደል? ያን የመሰለ የቅድስና ሕይወት ባንድ ጀንበር የገነባ አብሮነት በመሆኑ የሕይወት ትምህርት ቤት ነው፡፡

በእርግጥ እግዚአብሔር ያልባረካት ሕይወት ከማንም ጋር ብትውል ለውጥ እንደሌላት በይሁዳ፣ በዴማስ፣ በግያዝ ሕይወት ማወቅ ይቻላል፡፡ ይህ ማለት ግን የተሰበረ መንፈስ ለሌላቸው ቅንነት ለጎደለባቸው ማለት እንጅ አብሮ በመኖር የሚገኘውን ጥቅም የሚተካ ሌላ ነገር አለ ማለት አይደለም፡፡ ነፋስን በቅጽበት ዓለማትን መዞሩን ትቶ ባህሩን የብሱን መቆጣቱን ረስቶ ተረጋግቶ እንዲኖር ያደረገው ከመሬት ጋር አብሮ መኖሩ እኮ ነው ፡፡

መሬትም በአንጻሩ ከነፋስ ጋር በመኖሩ ፈጣን ደቀ መዝሙር ሆኗል፡፡ መሬትን የምናውቀው የማይንቀሳቀስ ፅኑ ፍጥረት መሆኑን እንጂ መሬት ሲንቀሳቀስ የምናውቀው አይደለምን? በሰው ባህርይ ውስጥ የመሬትን ባህርይ ተንቀሳቃሽ ያደረገው ከነፋስ ጋር አብሮ መሠራቱ ነው እንጂ ሌላ ምን አለው መጽሐፍ ስለ መሬት ሲናገር የተናገረው እንዲህ ነበር፡፡ ”ዘአጽንኣ ለምድር ዲበ ማይ፤ ምድርን በውኃ ላይ ያጸናት” መዝ 135÷6 በማለት የምድርን ፅናት ይመሰክራል፡፡ ሰውን ስንመለከተው ሌላ አዲስ ፍጥረት ይመስለን ይሆናል እንጂ በመጀመሪያ እግዚአብሔር ከፈጠራቸው ሁለት ፍጡራን አንዷ ከሆነቸው ምድር የተገኘ ምድራዊ ፍጥረት ነው፡፡ ነገር ግን የሚንቀሳቀስ ምድር መሆኑ አስገራሚ ፍጥረት ያደርገዋል የዚህ ምሥጢር ደግሞ የተሠራበትን ምድር በነፋስ ሠረገላ ላይ ጭኖ የፈጠረው መሆኑ ነው የተጫነበት ሠረገላ ፈጣን ከመሆኑ የተነሣ የማይንቀሳቀሰውን እንዲንቀሳቀስ ያደርገዋል፡፡

መሬትም ለፈጣኑ የነፋስ እግሮች ጭምትነትን ያስተምርለታል፡፡ ባጭር ጊዜ አድማሳትን ማካለል የሚቻለው ነፋስ ጭምትነትን ገንዘብ ሲያደርግ ትዕግስትን ለብሶ ሲመላለስ ማየት ምንኛ ድንቅ ነው፡፡ ከዚያም በላይ አራቱንም በሌላ ሁለት ነገር እንከፍለዋለን፡- ቀሊልና ክቡድ ብለን፡፡ ቀሊላኑ እሳትና ነፋስ ሲሆኑ ክቡዳኑ መሬትና ውኃ ናቸው፡፡ እንደ ውኃና ነፋስ ምን ቀላል ነገር ይኖራል? እንደ መሬትና ውኃስ ማን ይከብዳል? ቢሆንም ግን አብረው ይኖራሉ እንዲያውም ክቡዳኑ መሬትና ውኃ ከላይ የተቀመጡ ሲሆን ቀሊላኑ እሳትና ነፋስ ግን ከስር ሆነው ክቡዳኑን ሊሸከሙ ከእግዚአብሔር ተወስኖባቸዋል፤ ሁለቱም እርስ በእርስ ተጠባብቀው ይኖራሉ፡፡ ነፋስና እሳት ቀላል ከመሆናቸው የተነሣ ወደ ላይ እንዳይወጡ መሬትና ውኃ ከላይ ሆነው ይጠብቃሉ፤ መሬትና ውኃ ደግሞ ከባዶቹ ናቸውና ወደታች እንውረድ ሲሉ ነፋስና እሳት ሓላፊነቱን ወስደው ከመውደቅ ይታደጓቸዋል፡፡ ይህ የተፈጥሮ ስጦታ ሰውን ወደታች ወርዶ እንጦርጦስ እንዳይገባ፤ ወደ ላይም ወጥቶ እንዳይታበይ ማእከላዊ ፍጡር አድርጎ ሲጠብቀው ይኖራል፡፡ ፈጡራንን ሲፈጥር በመካከላቸው መረዳዳትን የግድ ባያደርገው ኖሮ ማንኛውም ፍጡር አብሮ ለመኖር ባልተስማማ ነበር፡፡ ምንም ላንጠቅመው የሚወደንና የሚጠብቀን የሰማዩ አምላክ ብቻ ይሆናል፡፡ ፍጥረታት ግን እርስ በእርስ ተጠባብቀው የሚኖሩት አንዱ ያለ አንዱ መኖር ስለማይችል ብቻ ነው፡፡

እንደዚያማ ባይሆን ኖሮ ነፋስ እሳቱን አግለብልቦ አንድዶት እሳቱም በፋንታው ውኃውን አንተክትኮት ውኃም መሬትን ሰነጣጥቆ ጥሎት አልነበረምን? ግን ይህ ሁሉ ከመሆኑ አስቀድሞ ከእግዚአብሔር የተሰወረ አልነበረምና አራቱንም ኑሯቸውን እርስ በእርስ የተሳሰረ አድርጎታል፡፡ መሬትና በውስጧ የሚኖሩ አራቱ ባህርያት ተስማምተው መኖራቸው ከመሬት በላይ የሚኖሩ ፍጥረታት ተስማምተው እንዲኖሩ አድርጓቸዋል፡፡ አንዱ ሌላውን በመታገሱ የተከሰተ ነውና ለሁሉም ነገር መሠረቱ ትዕግስት መሆኑ የማይካድ ሀቅ ነው፡፡

ከዕለታት አንዳንድ ቀናት አሉ አራቱ ባህርያት የማይስማሙባቸው፡፡ ታዲያ በነዚህ ቀናት ሰው ተኝቶም እንኳን አይተኛም፤ የነፋስ ባህርይ የበረታ እንደሆነ ሲያስሮጠው ከቦታ ቦታ ሲያንከራትተው ያድራል፤ የመሬት ባህርይ ቢጸና ደግሞ ከገደል ሲጥለው፤ ተራራ ተንዶ ሲጫነው ያያል፤ እሳታዊ ባህርይም በእሳት ተከበን፤ እሳት ቤታችንን በልቶ ሲያስለቅሰን ያሳያል፤ ውኃም እንደሌሎቹ ሁሉ ሰውን በባህሩ ሲያጠልቀው ውኃ ለውኃ ሲያመላልሰው ያድራል፡፡ እያንዳንዳቸው ተስማምተው እንዲኖሩ ባያደርጋቸው ሰው በመኝታው እንኳን እረፍት ማግኘት እማይችል ፍጡር ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ትዕግስት ለማንኛውም ነገር መሠረት ነው፡፡

ሁሉም በጎ ነገሮች በሰማይም በምድርም የሚገኙት የትዕግስት ውጤቶች መሆናቸውን ልብ ይሏል፡፡ ሰው በራሱ የትዕግስት ውጤት መሆኑን ካየን የምንጠብቀው አዲሱ ዓለም መንግሥተ ሰማይ የትዕግስት ስጦታ ነው፤ ምክንያቱም መጽሐፍ የሚለው “እስከ መጨረሻው የታገሰ ይድናል” ነውና፡፡ ሞታችንን የገደለው፤ ጨለማን የሳቀየው ማነው? ክርስቶስ በዕለተ አርብ በህማሙ ወቅት ያሳየው ትእግስትም አይደል! ይሄ ትዕግስት ፍጥረቱን ሁሉ ያስደነቀ ትዕግስት ነበር፡፡ ከቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት አንዱ “ኦ! ትዕግስት ዘኢከሠተ አፉሁ በሕማሙ በቅድመ እለ ይረግዝዎ፤ በመከራው ወቅት በሚወጉት ሰዎች ፊት የማይናገር ትዕግስት” ሲል በቅዳሴው ያደንቃል፡፡ በዚህ አስደናቂ ትዕግስቱ እኮ ነው ኃይለኛውን እስከ ወዲያው ጠርቆ ያሰረው ማቴ12÷29፡፡ ኃይለኛውን አስሮ ቤቱ ሲዖልን በርብሮ አወጣን፡፡ እንግዲያውስ ትዕግስት ጉልበት ነው፤ ትዕግስት ውበት ነው፡፡ በዓለም ላይ በጦርነት ከተሸነፉት በትዕግስት የተሸነፉት ይበዛሉ፤ ባለ መቶ ሰማንያ አምስት ሺህ ጦር የነበረው ሰናክሬም በሕዝቅያስ ትዕግስት መሸነፉን አንዘነጋውም፡፡

 

“አትሮንስ” የመጻሕፍት ውይይት መርሐ ግብር ሊጀመር ነው

 ጥቅምት 26 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በእንዳለ ደምስስ

books 26ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መጻሕፍት የንባብ ባሕልን ለማዳበር በየደረጃው ከሚሠራቸው ተግባራት በተጨማሪ “አትሮንስ” የተሰኘ በመጻሕፍት ላይ የሚደረግ የውይይት መርሐ ግብር ኅዳር 1 ቀን 2006 ዓ. ም. በማኅበሩ ኤዲቶሪያል ቦርድ አስተባባሪነት ይጀመራል፡፡

ንባብ ዕውቀትን ለማዳበር፤ አስተሳሰብን ለማስፋት፤ ሚዛናዊ ብያኔን ለመሥጠት፤ የአባቶችን ሕይወትና ትምህርት ለማወቅ ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ መሆኑን የሚገልጸው የኤዲቶሪያል ቦርድ ክፍል፤ መንፈሳዊ መጻሕፍትን ማንበብ ዘላለማዊ ሕይወት ማግኛ መንገድን የሚጠርግና ጠቀሜታው የላቀ መሆኑን በመገንዘብ ተግባራዊ እንደሚደረግ አስታውቋል፡፡

የመርሐ ግብሩ ዋነኛ ዓላማም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን የሚመለከቱ የነገረ ሃይማኖት፤ የታሪክና የአስተዳደር መጻሕፍትን ማስተዋወቅ፤ የመንፈሳዊ መጻሕፍት የንባብ ባሕልን ማዳበር፤ በንባብ ባሕል ላይ የላቀ ልምድ ያላቸውን ሊቃውንት ልምዳቸውን እንዲያካፍሉ ማድረግ፤ በመንፈሳዊ መጻሕፍት ላይ የውይይት ባሕልን ማሳደግና የልምድ ልውውጥን ማጠናከር ላይ ትኩረት አድርጎ የተዘጋጀ መርሐ ግብር መሆኑን ከማኅበሩ ኤዲቶሪል ቦርድ ክፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

መርሐ ግብሩ ሳይቋረጥ እንዲቀጥል በኤዲቶሪያል ቦርድ የመጻሕፍት አርትዖት ክፍል ሥር ራሱን የቻለ ማስተባበሪያ ሆኖ እንደሚደራጅ የተገለጸ ሲሆን ዕቅድና ሪፖርት፤ አስፈላጊው በጀትም እንደሚኖረው ተጠቅሷል፡፡

“አትሮንስ” የመጻሕፍት ውይይት መርሐ ግብር ወር በገባ በመጀመሪያው እሑድ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት እስከ 11፡00 ሰዓት በማኅበሩ ሕንፃ ላይ በየወሩ እንደሚዘጋጅ ክፍሉ አስታውቋል፡፡ ኅዳር 1 ቀን 2006 ዓ.ም. በሚካሄደው መርሐ ግብርም “የኢትጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ” የተሰኘውና በረዳት ፕሮፌሰር ሉሌ መላኩ የተጻፈው መጽሐፍ ውይይት ይካሄድበታል፡፡

ምእመናን በተጠቀሰው ቀን፤ ሰዓትና ቦታ በመገኘት መርሐ ግብሩን መከታተል እንደሚችሉም የማኅበረ ቅዱሳን የኤዲቶሪያል ቦርድ ክፍል ጥሪውን አስተላልፏል፡፡

 

ትኩረት ለፊደላት

 

ጥቅምት 25 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በዳዊት ደስታ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለሀገራችን በርካታ ነገሮችን አበርክታለች፡፡ ከዚህም ካበረከተቻቸው ነገሮች ውስጥ አንዱ ኢትዮጵያ የራሷ ፊደል እንዲኖራት በማድረግ ነው፡፡ የቅርሳቅርስ ጥናት ሊቃውንትና ታሪክ ጸሐፊዎች እንደሚያረጋግጡት የአጻጻፍ ስልት በኢትዮጵያ የተጀመረው ከጌታ ልደት በፊት እንደነበር ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጭር የታሪክ የሃይማኖትና የሥርዐት መጽሐፍ ይገልጻል፡፡ /ገጽ. 9-11/

በአክሱም ዘመነ መንግሥት የሳባውያንና የአግዓዝያን ፊደላት በኅብረት ይሠራባቸው ነበር፡፡ በአክሱም ዘመነ መንግሥት ግን የግእዝ ፊደልና የግእዝ ቋንቋ እያደገ ስለመጣ በክርስቲያን ነገሥታት በአክሱም ዘመነ መንግሥት በሐውልቶችና በሌላም መዛግብት የተጻፉ ጽሑፎች በግእዝ ፊደልና በግእዝ ቋንቋ ተጽፈው እናገኛለን፡፡ የጽሑፍ መሠረት የሆነው ፊደልና የጽሑፍ ስልት በደንብ የታወቀው የክርስትና ሃይማኖት ማለት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት በኢትዮጵያ መስፋፋት በጀመረበት ወቅት መሆኑ ግልጽ ነው፡፡

የፊደል መነሻ
የግእዝ ፊደል መነሻ መልክእንና ቅርፅን በመስጠት እንዲስፋፋ ያደረጉት በአክሱም ዘመነ መንግሥት የነበሩ የቤተ ክርስቲያን /የቤተ ክህነት/ ሰዎች መሆናቸው የታመነ ነው፡፡ በሥነ ጽሑፍ የምትታወቀው ሀገራችን ኢትዮጵያ መሠረቷና መነሻዋ ፊደል ነው፡፡ ፊደል ያልተቀረፀለት ፣ጽሑፍ ያልተሰጠው ማንኛውም ቋንቋ ሁሉ መሠረት ስለሌለው የሚሰጠው አገልግሎት ያልተሟላ ነው፡፡ መሠረታዊ ቋንቋ ታሪካዊ ቋንቋ ተብሎ የሚሰየመው ፊደል ተቀርጾለት የምርምርና የሥነ ጽሑፍ መሠረት በመሆን ለትውልድ ሲተላለፍ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የታሪክ ማኅደር እንደመሆኗ ለግእዝና ለአማርኛ ቋንቋ መሠረትና መነሻ የሆነውን ፊደል ቅርጽና መልክ ሰጥታ ሕዝቡ እንዲጠቀምበት፣ ሥነ ጽሑፍ እንዲስፋፋና ታሪክ እንዲመዘገብ፣ ያለፈውን የማንነት አሻራ እንድናውቅ፣ አሁን ያለንበትን እንድንረዳና ወደፊት ስለሚሆነውም ዝግጅት እንድናደርግ በፊደል አማካኝነት ድርሳናትን ጽፈን እንጠቀም ዘንድ ፊደል መጠቀም ተጀመረ፡፡

ምክንያተ ጽሕፈት
ለዚህ ጽሑፍ መነሻ የሆነኝ በመስከረም ወር ስለ ኢትዮጵያ ፊደል መሻሻል በሚዩዚክ ሜይዴይ አዘጋጅነት ለውይይት የሚረዳ መነሻ ጽሑፍ ቀርቦ ነበር፡፡ የዚህ ጽሑፍ አቅራቢ አማርኛ ፊደል ለመሻሻሉ መነሻ ያሉትን ምክንያትና የሌሎች ሀገራትን ተሞክሮ በማንሳት አሁን ያለው እየተገለገልንበት ያለው ፊደል ችግር አለው ያሉበትን ምክንያት አቅርበዋል፡፡ ፊደላቱ ተመሳሳይነት ድምጽ ስላላቸው ሊቀነሱ ይገባል በማለት ጽሑፋቸውን አቅርበዋል፡፡በዕለቱ የተለያዩ ምሑራን በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው ስለነበር ጽሑፍ አቅራቢውን ሞግተዋቸዋል፡፡ የእኛም ዝግጅት ክፍል ፊደላት መቀነሳቸው/መሻሻላቸው/ የሚያመጣው ችግር ምን እንደሆነ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን በመጠየቅ ምላሻቸውን አአስነብበናችሁ ነበር፡፡ ከዚህም በተለጨማሪ የቋንቋ ባለሙያዎች በእንደዚሁ ዓይነት የውይይት መድረኮች በመገኘት ምላሽ ሰጥተው በጽድፎቻቸውም በመጽሐፋቻቸውም ትክክለኛውን ለንባብ አብቅተውልናል፡፡

ይኼ ጽሑፍ የግእዝ ፊደል አመጣጥን የሚተርክ ሳይሆን ፊደላቱ ይሻሻሉ የተባለበትን መንገድ መሠረት አድርገን ምላሽ ብለን የምናስበውን የመፍትሔ ሐሳብ ለመጠቆም ነው፡፡ ተመሳሳይነት ያላቸውን ፊደላት ይቀነሱ፣ ይሻሻሉ…ወዘተ የሚሉ አሳቦች መቅረብ ከጀመሩ ቆይተዋል፡፡ ለዚህም እነ ዶ/ር ሐዲስ አለማየሁ “ፍቅር እስከ መቃብር” በሚል መጽሐፋቸው የተወጠነው፣ በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማእከል የተዋሀደው ፊደላትን የመቀነስ ዘመቻ በመጽሔቶችና ጋዜጦች ብቻ ሳይሆን በጥናታዊ ጽሑፎችና በፈጠራ ድርሰቶች ሳይቀር ይዞታውን እያስፋፋ እንደመጣ /ሊቀ ኅሩያን በላይ መኮንን ሥዩም፣ ትንሣኤ አማርኛ፣ ግእዝ መዝገበ ቃላት/ በሚለው መጽሐፋቸው ላይ ገልጸዋል፡፡

የዚህ ፊደል የማሻሻል ዘመቻ የፊደል ገበታችን አካል የሆኑት “ሀ፣ ሐ፣ ኀ፣ ሠ፣ሰ፣አ፣ዐ እና ጸ” ፊደላቱ ከትውልዱ አእምሮ ውስጥ መፋቅ /መጥፋት/አለባቸው የሚል አሳብ የያዘ ይመስላል፡፡ ይህን ዘመቻ በመቃወም ብዙ ሊቃውንት ብዕራቸውን አንስተዋል፣ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም በኅትመት ውጤቶቹ በሆኑት ሐመርና ስምዐ ጽድቅ ላይ የቋንቋ ምሁራንና የቤተ ክርስቲያናችንን ሊቃውንት በማናገር ምላሽ ብሎ ያሰበውን በተከታታይ ኅትመቶች አስነብቦናል፡፡

እነዚህ ፊደላት ተመሳሳይነት አላቸው የተባሉት የ“ሀ፣ ሐ፣ ኀ፤ ሠ፣ ሰ፤ አ፣ ዐ እና ጸ፣ ፀ” ፊደላት ቀደም ባለው ጊዜ በግእዝ፣ በተለይ ደግሞ በትግርኛ ቋንቋዎች የየራሳቸው መካነ ንባብና ድምፀት ስላላቸውና እልፍ አእላፋት የሥነ ጽሑፍ ሥራዎችም ስለተሠሩባቸው ፊደላቱን መቀነስ ኪሣራ እንጂ ትርፍ የለውም የሚል አስተያየት ከብዙ ምሁራን ተሰጥቶበጣል ፡፡

ከዚህ በመነሣት የፊደል ይቀነሱ፣ይሻሻሉ የሚሉት ጥያቄዎች ስናጤነው አንድን ፊደል በሌላ ፊደል ማጣፋት፣ ከቃላት ወይም ሐረጋት ፍቺ እንዲያጡ ወይም የተዛባ ፍቺ እንዲሰጡ ማድረጉ አይቀሬ ነው፡፡ ለዚህም አንድ ቀላል ምሳሌ ማንሳት እንችላለን፡፡ በግእዝ ቋንቋ “ሠረቀ” ማለት ወጣ፣ ታየ፣ ተገለጠ ማለት ሲሆን፣ “ሰረቀ” ማለት ደግሞ ሰረቀ፣ ቀጠፈ፣ አበላሸ ማለት ነው፡፡ የቃሉ ማእከላዊ ድምፅ “ረ” በሁለቱም አይጠብቀም፡፡ ጠብቆ ከተነበበ ስድብ ይሆናል፡፡ “ሠረቀ” የሚለውን ቃል የተወሰኑ ሰዎች ሲጠሩበት እናውቃለን፡፡ የአባት ስም ብርሃን፣ ፀሐይ ሕይወት ወዘተ ቢሆንና ሙሉ ስም አድርገን ስንጠራቸው ሠረቀ ብርሃን፣ ሠረቀ ፀሐይ፣ ሠረቀ ሕይወት እንላቸዋለን፡፡ ነገር ግን ንጉሡን “ሠ” በእሳቱ “ሰ” ቀይረን ብንጽፍ “ሌባው ብርሃን፣ ሌባው ፀሐይ. . .” እያልን የስድብ ቃል/ትርጉም/ ስለሚያመጣ ፊደላቱን አገባባቸውን የሚሰጡትን ትርጉም ካላወቅን ችግሮች ይፈጠራሉ፡፡

ሌላው ግእዝ “ሀ” በራብዕ “ሃ” አና “አ” በ”ኣ” መተካቱ ደግሞ “ሳይቸግር ጨው ብድር” የሚለውን የሀገራችንን አባባል የሚያስታውሰን ይመስለኛል፡፡ ሌላም እንመልከት ሀብታም ስንል ባለፀጋ ማለት ሲሆን ‹‹ሐብታም›› ካልን ደግሞ ዘማዊ ይሆናል፡፡ሰገል ጥበብ ማለት ሲሆን ሠገል ጥንቆላ ማለት ነው፡፡ ሰብዓ ፸ ቁጥር ሲሆን ሰብአ ሰዎች ማለት ነው፡፡ ሰአለ ለመነ ማለት ሲሆን ሠዓለ ሲሆን ደግሞ ሥዕል ሳለ ማለት ነው፡፡ ፊደላቱ አንዱ ባንዱ መቀየራቸው ወይም መተካታቸው ችግሮች እንደሚፈጥሩ ከላይ ያየነው ምሳሌ ጥሩ አድርጎ ያስረዳናል፡፡

ለዚህም አንዱ ከሌላው የሚሰጠውን የተለየ ትርጉም አለማወቅ የሚያመጣውን ችግርን አስመልክቶ ወጣቱ ገጣሚ ኤፍሬም ሥዩም “ሶልያና” በተሰኘው የግጥም የድምፅ መድብሉ በቅኔ መልክ ያቀረበውን ማንሳት ያስፈልጋል፡፡ የግጥሙ ርእስ “እሳቱ ሰ” የሚል ነው፡፡

“ይኼው በጉብዝናም በፈቃድ ስተት
ትርጓሜው አይደለም አንድ ነው ማለት
እጽፋለሁ ጽፈት እስታለሁ ስተት
እሳት ስባል ንጉሥ፣ ንጉሥ ስባል እሳት”

እያለ ገጣሚው ፊደላት ያለ አገባባቸው ቢገቡ፣ የሚፈጥረውን የአሳብና የትርጉም ስሕተት እንደሚያመጣ ከፊደል ገበታ እንዲሠረዙ መደረጉ ያሳደረበትን የቁጭት ስሜት አሰምቶናል፡፡ ፊደላችን ይቀነስ፣ ይሻሻል የሚሉ አሳቦችን ከማንሳት በፊት ቀድሞ ሊነሣ የሚገባው ፊደላቱ የሚሰጡትን ድምጽና ትርጉም ማወቅ ከዚያም መቀነሳቸው ወይም መሻሻላቸው በኢትዮጵያ ሥነ ጽሑፍ ውስጥ የሚያመጣውን ተፅዕኖ ማየት ያስፈልጋል፡፡ከዚህም በተጨማሪ የታሪክና የቅርስ ማጥፋት ሥራ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ፊደላቱ የሚሰጡትን ድምጽና ትርጉም አውቆ የአንዱ ፊደል መውጣት መሻሻል ለረጅም ዘመናት የተጻፉ መጻሕፍት የአሳብ፣ የትርጉም፣ የቅርስ ጥፋት እንደሚያመጣ ማወቅ ይሻል፡፡ጉዳዩ የሚመለከታቸው ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ምሁራን ዳግም ጥያቄ በማያስነሳ መልኩ ትክክለኛውን ነገር ሊያስቀምጡና ጥናት በማጥናት ምላሻቸውን ሊሰጡ ይገባል፡፡ ከዚህም በላይ ደግሞ ባለድርሻ የሆነችው ቅደስት ቤተ ክርስትያን ምላሿን ማሳወቅ እንደሚገባት የጥያቄው መብዛት አፋጣኝ እንደሆነ ያመላክታል፡፡

 

ማእከሉ Tewahedo/ተዋሕዶ /የተሰኘ የስልክ አፕ አዘጋጀ

 

ጥቅምት 22 ቀን 2006 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

 

የማኅበረ ቅዱሳን የሰሜን አሜሪካ ማእከል የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ዘመኑን የዋጀ እንዲሆን Tewahedo /ተዋሕዶ የተሰኘ የስልክ አፕ/ በአይቲ ክፍል አዘጋጀ፡፡

 

በማእከሉ የተዘጋጀው አፕ የኢትዮጵያና የጎርጎሮሳዊያንን የዘመን አቆጣጠር አጣምሮ የያዘ ነው፡፡ የፈለጉትን ዓመት የበዓላት እና አጽዋማት ቀናት በቀላሉ ማየት ያስችላል፡፡ የየቀናቱን የቅዳሴ ምንባብ በመጽሐፈ ግጻዌ መሠረት ያሳያል፡፡ በመቶዎች የሚቆጠሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥርዓት የጠበቁ መዝሙራት፣ ስብከቶች፣ ትረካዎች እና የሬዲዮ ስርጭቶች ለአድማጭ እንዲመቹ በዓይነት ከፋፍሎ ያቀርባል፡፡ አፑን በመጠቆም የቤተ ክርስቲያንን ድምጽ በየትኛውም ጊዜና ቦታ /በመንገድ ላይ ሥራዎችን እያከናወኑ፣ በእረፍትና በመዝናኛ ቦታዎች/ ሆነው በስልክ እነዚህን መረጃዎች እንደሚያገኙ ማእከሉ በላከልን መረጃ ለማወቅ ተችሏል፡፡

 

ሌላው በሰሜን አሜሪካ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መረጃ እንዲያገኙ የሚያግዝ ሲሆን በቀጣይ በሀገር ውስጥና በውጭ ላሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በቀላል መንገድ ቤተ ክርስቲያንን የሚያውቁበትና ትምህርቷን የሚከታተሉበት የቴክኖሎጂ ውጤቶች በስፋት እንደሚሠሩ ማእከሉ አሳውቋል፡፡

 

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችን በማሳለፍ አጠናቀቀ፡፡

 

1 abune mathias
ጉባኤው ከጥቅምት 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ ላለፉት 10 ቀናት ተወያይቶ ያሳለፋቸውን ውሳኔዎች አስመልክቶ ዛሬ ከሰዓት በኋላ ቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በተገኙበት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ጋዜጣዊ መግለጫ ተሰጥቷል፡፡ የመግለጫውን ሙሉ ቃል እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

 01 sts02 sts03 sts04 sts

 

የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር እንደሚካሔድ ተገለጸ

 ጥቅምት 19 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በእንዳለ ደምስስ

 

ማኅበረ ቅዱሳን ሐዊረ ሕይወት /የሕይት ጉዞ/ የተሠኘውንና ምእመናንን በማሳተፍ በተመረጡ ቅዱሳት መካናት የሚያካሒደውን መርሐ ግብር ታኅሣሥ 6 ቀን 2006 ዓ.ም. በደብረ ዘይት ደብረ መድኀኒት ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያን እንዳዘጋጀ የመርሐ ግብሩ አስተባባሪ ኮሚቴ ገለጸ፡፡

አቶ ግርማ ተሾመ የማኅበረ ቅዱሳን ምክትል ዋና ጸሐፊና የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር አስተባባሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ ዝግጅቱን አስመልክቶ በሰጡት ማብራሪያ በመርሐ ግብሩ ላይ ከ5000 በላይ ምእመናን ይሳተፋሉ ተብሎ እንደሚጠበቅና የቲኬት ሽያጩንም በማሰራጨት ላይ እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡ ምእመናን ቲኬቱን በማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከል ጽ/ቤት፤ በማኅበሩ የንዋያተ ቅዱሳት ማከፋፈያና መሸጫ ሱቆች እንደሚያገኙ የተናገሩት አቶ ግርማ የቲኬት ሽያጩም ኅዳር 25 ቀን 2006 ዓ.ም. እንደሚጠናቀቅ አሳውቀዋል፡፡

በእለቱም ሰባኪያንና ዘማሪያን የሚገኙ ሲሆን ከምእመናን ለሚቀርቡ በመንፈሳዊ ሕይወት ዙሪያ ያተኮሩ ጥያቄዎች በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምላሽ ይሰጥባቸዋል፡፡
የትራንስፖርት ክፍያን ከግምት ውስጥ በማስገባትና ከዚህ በፊት ከተካሔዱት የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብራት ተሞክሮዎች በመነሳት የተሻለ አገልግሎት ለምእመናን ለመሥጠት ጥረት እየተደረገ መሆኑን የሚገልጹት አቶ ግርማ የምሣ መስተንግዶን ጨምሮ የቲኬት ዋጋው 195.00 /አንድ መቶ ዘጠና አምስት ብር መሆኑን አስታውቀዋል፡፡

 

የቲኬት ሽያጩ ከተጠናቀቀ በኋላ ምእመናን ቱኬቱን ለመግዛት ጥያቄ በማቅረብ በአገልግሎት ላይ ከፍተኛ ጫና እየተፈጠረ እንደሚገኝ ካለፉት ተሞክሮዎች ኮሚቴው የተረዳ በመሆኑ በተያዘለት መርሐ ግብር መሠረት ምእመናን ቲኬቱን እንዲገዙ ኮሚቴው አሳስቧል፡፡

 

የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ከ2003 ዓ.ም. ጀምሮ ለአራት ጊዜያት መከናወኑ ይታወሳል፡፡

 

ቅዱስ ሲኖዶስ ችግሮችን በውይይት መፍታት እንዳለበት ተገለጸ

 ጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በእንዳለ ደምስስ

meglecha 11
ቅዱስ ሲኖዶስ ችግሮችን በውይይትና በውይይት ብቻ በጋራ የመፍታት ባሕልን መደገፍና ማጎልበት እንደሚገባው ተገለጸ፡፡

በዛሬው ዕለት ጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም. ጠዋት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ከመጀመሩ በፊት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ በአሁኑ ጊዜ በጥልቀት፣ በማስተዋልና የሓላፊነት መንፈስ በተላበሰ ወኔ፣ አጥብቆ ሊወያይባቸውና ሊወስንባቸው፤ ከውሳኔ በኋላም ለተግባራዊነታቸው ሊረባረብባቸው የሚገቡ በርከት ያሉ ጉዳዮች እንዳሉ አመልክተዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ልጆቿን ከጉያዋ እየተነጠቁ ወደ ሌላ ካምፕ ሲወሰዱ የወላድ መካን መሆን እንደሌለባት ያወሱት ቅዱስነታቸው የታሪክ ተወቃሽ ከመሆን ለመዳን አስተማማኝና ዘላቂ መፍትሔ ሊፈለግለት እንደሚገባ ገልጸዋል፡፡ ከአስተዳደር ጋር በተያያዘም “ከአድልዎና ከወገንተኝነት ሙሉ በሙሉ ያልተላቀቀው አስተዳደራችን የቤተ ክርስቲያናችን ታላቅነትና ተሰሚነትን ክፉኛ እየጎዳው መሆኑ አሌ ልንለው አይገባም” ብለዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያኗ የተማረና የሰለጠነ የሰው ኃይል ከማፍራት አንጻርም የአብነት ትምህርት ቤቶች፤ የማሠለጠኛና የከፍተኛ ትምህርት ተቋሞቿን በብዛትም፤በጥራትና በአደረጃጀት ተማሪውን ለመለወጥና ለመቅረጽ በሚያስችል አዲስ አሠራር ማስተካከልና ማብቃት እንደሚገባም ጠቁመዋል፡፡

የመግለጫው ሙሉ ቃል እንደሚከተለው ይቀርባል፡፡

 

 meglecha 12

የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ መክፈቻ በምሕላ ጸሎት ተጀመረ

 

 

ጥቅምት 11 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በእንዳለ ደምስስ

የጥቅምት 2006 ዓ.ም. የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በዛሬው እለት ጥቅምት 11 ቀን 2006 ዓ.ም. ከቀኑ ዐሥር ሰዓት ጀምሮ ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳምabatoch በምሕላ ጸሎት ተጀመረ፡፡

 

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ከጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም. ጀምሮ በሚያካሒደው ስብሰባ ለቤተ ክርስቲያን የሚጠቅሙ ውሳኔዎችን ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

 

ለቅዱሳን ፓትርያርኮችና ለብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት መታሰቢያ ጸሎተ ፍትሐት ተደረገ

ጥቅምት 8 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በእንዳለ ደምስስ

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ሲመሩ ለነበሩና ከዚህ ዓለም በሞት ለተለዩ ቅዱሳን ፓትርያርኮችና ሊቃነ ጳጳሳት በመንበረ ጸባዖት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ጥቅምት 10 ቀን 2006 ዓ.ም. የመታሰቢያ ጸሎተ ፍትሐትና ቅዳሴ ተካሔደ፡፡

በጸሎተ ፍትሐትና ቅደሴ ሥነ ሥርዓት ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የ32ኛው የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተሳታፊዎች በመርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተዋል፡፡

ጸሎተ ፍትሐቱ በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ካህናት የተመራ ሲሆን ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት ቃለምእዳን “ይህ ታላቅ በዓል ነው፡፡ ቅዱሳን ፓትርያርኮቻችንና ብፁዓን አባቶቻችንን ልንዘክር ይገባል” በማለት የተናገሩ ሲሆን ከዚህ ዓለም በሞት የተለዩትን የአራቱን ቅዱሳን ፓትርያርኮችና የብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ስም በመጥራት ታስበዋል፡፡

በእለቱ ምሽትም ማኅበረ ቅዱሳን በየዓመቱ የሚያዘጋጀውን የቅዱሳን ፓትርያርኮችና ሊቃነ ጳጳሳት መታሰቢያ /ዝክረ አበው/ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ የእራት መርሐ ግብር ተካሒዷል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይም ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ ሊቃነ ጳጳሳትና የ32ኛው መንፈሳዊ ጉባኤ ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሰሜን ወሎና የዋግ ሕምራ አኅጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ባስተላለፉት መልእክት “የሃይማኖት ጉዳይ በመምሰል ሳይሆን በመሆን ነው የሚገለጸው፡፡ መከራውን የምትጋፈጡት የሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፤ ወረዳ ሥራ አስኪያጆችና በየአጥቢያው ያላችሁት ናችሁ፡፡ ነገር ግን የስብከተ ወንጌል ጉዳይ ትኩረት ሊሰጠው ይገባል፡፡ ስብከተ ወንጌል በቄሱ፣ በሰባኪያኑና በዲያቆናቱ መሰበክ አለበት፡፡ ቤተ ክርስቲያን ራሷን ቻለች የምንለው ቄሱም፣ ሰባኪውም ሆነ ዲያቆናቱም መስበክ ሲችሉ ነው” ብለዋል፡፡

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ናትናኤል በሰጡት ቃለምዕዳን “ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ የተመሠረተ የቤተ ክርስቲያን አርበኛ ነው፡፡ በርቱ” በማለት ማኅበሩ በአገልግሎት እንዲበረታ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡
በተያያዘ ዜና ጥቅምት 9 ቀን 2006 ዓ.ም. ምሽት የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ለ32ኛው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተሳታፊዎች ባዘጋጀው የእራት መርሐ ግብር ጉባኤውን ለማካሔድ ድጋፍ ላደረጉ አካላት የምሥክር ወረቀት ሰጠ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ዋናው ማእከልም የተዘጋጀለትን የምሥክር ወረቀት ከቅዱስ ፓትርያርኩ እጅ ተቀብሏል፡፡
የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያው ለብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ያዘጋጀውን የመስቀል ሥጦታ የማኅበረ ቅዱሳን ልማት ተቋማት አስተዳደር ጽ/ቤት 24 ሺህ ብር የሸፈነ ሲሆን ቀሪውን /ግማሹን/ ደግሞ በመምሪያው ወጪ መደረጉን የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ ለጉባኤው ገልጸዋል፡፡ ለጉባኤው መሳካትም ትብብር ላደረጉ አካላት ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ለሊቀ ማእምራን ፋንታሁን ሙጬ ለጉባኤው መሳካት ላደረጉት ከፍተኛ አስተዋጽኦ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ መምሪያ ሠራተኞችና የስብከተ ወንጌል መምሪያ ሥጦታ አበርክተውላቸዋል፡፡

 

መንፈሳዊ ኮሌጆች ወጥ የሆነ ሥርዓተ ትምህርት ሊኖራቸው እንደሚገባ ተጠቆመ

 

ጥቅምት 11 ቀን 2006 ዓ.ም. 

በይብረሁ ይጥና

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥር የሚገኙት መንፈሳዊ ኮሌጆች አንድ ወጥ የሆነ ሥርዓተ ትምህርትና የትምህርት ጥራት ሊኖራቸው እንደሚገባ ተገለጠ፡፡

 

ከጥቅምት 4-11 ቀን 2006 ዓ.ም. በተካሄደው የ32ኛ መንፈሳዊ የሰበካ ጉባኤ መደበኛ ስብሰባ ላይ በተሳታፊዎች ተደጋግሞ እንደተነሣው የአቋም መግለጫው እንደሚያመለክተው የቅድስት ሥላሴ፣ የሰዋሰወ ብርሃን ቅዱስ ጳውሎስና የቅዱስ ፍሬምናጦስ አባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጆች በርካታ ደቀ መዛሙርትን ድኅረ ምረቃ፣ በዲግሪ፣ ዲፕሎማና ሠርተፍኬት በማስተማር እንደሚያስመርቁ ተገልጿል፡፡

 

ነገር ግን ከአቀባበል፣ የትምህርት አሰጣጥ ክትትልና ምዘና ክፍተት የሚታይባቸው በመሆኑ ሁሉም ኮሌጆች ወጥ የሆነ ሥርዓተ ትምህርትና የትምህርት ጥራት ሊከተሉ እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡

 

በተጨማሪም ከመንፈሳዊ ትምህርቱ ጎን ለጎን የሥራ ተነሳሽነት ያለው ትምህርትና በቤተ ከርስቲያን ሁለንተናዊ አገልግሎት የሚያበረክቱበት ሥልጠና ለተማሪዎች አብሮ መሰጠት እንዳለበት ተወስቷል፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘ በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በተደጋጋሚ እየተከሰተ ያለው አስተዳደራዊ ችግር ተጠንቶ እልባት እንዲያገኝም የአቋም መግለጫው ያመለክታል፡፡