ለአብነት ተማሪዎች የአልባሳት ድጋፍ ተደረገ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ከደሴ ማእከል

በማኅበረ ቅዱሳን ደሴ ማእከል የቅዱሳት መካናት ማኅበራዊ አገልግሎትና ልማት ክፍል አስተባባሪነት በሰሜን ወሎ ደላንታ እና መሀል ሳይንት ለሚገኙ የአብነት ተማሪዎች የአልባሳት ድጋፍ ተደረገ፡፡

በነዚህ ወረዳዎች ብዛት ያላቸው የአብነት ተማሪዎች የሚገኙ ሲሆን፤ ከሚያጋጥሟቸው ችግሮች አንዱ የሆነውን የአልባሳት ችግር ለመቅረፍ ከማእከሉ አባላት፣ ከግቢ ጉባኤያት እና ከምእመናን አልባሳትን በማሰባሰብ ድጋፍ ማድረጉን ማእከሉ ገልጿል፡፡

ማእከሉ በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የአብነት መምህራንና ተማሪዎች የሚያጋጥሟቸውን ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ችግሮች ለመቅረፍ ጊዜያዊ እና ቋሚ ፕሮጀክቶችን ቀርጾ ተግባራዊ እያደረገ የሚገኝ ሲሆን፤ በአሁኑ ወቅት በዘመናዊ ትምህርት፣ በጤና አጠባበቅ እና በአልባሳት ከሚደረጉ ድጋፎች በተጨማሪ ለዘጠኝ (9) የአብነት መምህራን ለእያንዳንዳቸው ብር 200.00 ወርሃዊ ድጎማ በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡ ለአንድ የአብነት ት/ቤትም ቋሚ የገቢ ማስገኛ ፕሮጀክት ቀርጾ ተግባራዊ በመደረግ ላይ መሆኑን ማእከሉ ገልጿል፡፡

 

በሊቢያ ለተሠዉ 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች የመታሰቢያ ጉባኤ ተካሄደ

ግንቦት 3 ቀን 2007 ዓ.ም.

ዲ/ን ዘአማኑኤል አንተነህ(ከጎንደር ማእከል)

በሊቢያ ለተሠዉ 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች በጎንደር ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ለ3 ቀናት የቆየ የመታሰቢያ ጉባኤ ተካሄደ፡፡

ጉባኤውን ያዘጋጁት የጎንደር ከተማ የሰንበት ት/ቤቶች አንድነት፣ በማኅበረ ቅዱሳን የጎንደር ማእከል እና የጎንደር ከተማ የጥምር መንፈሳዊ ማኅበራት በጋራ በመተባበር ሲሆን፤ ከሚያዚያ 24 – 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ጉባኤው ተካሂዷል፡፡

ጉባኤው የተጀመረው ቅዳሜ ሚያዝያ 24 ቀን 2007 ዓ.ም. ከ7፡00 ሰዓት ጀምሮ ሲሆን፤ ለሦሰት ቀናት በቆየው ጉባኤ በሰባኪያነ ወንጌል ትምህርት፤ ሰማዕታቱን የሚዘክሩ መነባንብ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ቅኔ፤ ከምእመናን ለቀረቡ ጥያቄዎች በሊቃውንተ ቤተ ክረስቲያን መልስ፤ መዝሙር በጎንደር ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት እና በተጋባዥ መዘምራን፤ የጧፍ ማብራት ሥነ ሥርዓት ተከናውኗል፡፡

በተያያዘ ዜና የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በሊቢያ ለተሠዉት 30 ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖች የከተማው ምእመናን በተገኙበት ሚያዚያ 16 ቀን 2007 ዓ.ም. በርዕሰ አድባራት አደባባይ ኢየሱስ ቤተ ክርስቲያን ጸሎተ ፍትሐት ተደርጎላቸዋል፡፡ በዕለቱም 30 ሻማዎች በርተዋል፡፡

የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

001sinoddd

ሚያዝያ 27 ቀን 2007 ዓ.ም. ከቀኑ 10፡00 ሰዓት በጸሎት የተጀመረው የርክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ሲካሔድ ቆይቶ ዛሬ ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም. ረፋድ ላይ ተጠናቅቆ የሚከተለውን መግለጫ ሰጥቷል፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 ላይ በተደነገገው ቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ ይካሄዳል፡፡

ከሁለቱ አንዱ ከጌታችን ከአምላካችንና ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን በዕለተ ረቡዕ የሚውለው የርክበ ካህናት ጉባኤ ነው፡፡

በመሆኑም የርክበ ካህናቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ሚያዝያ 27 ቀን ከሰዓት በኋላ በጸሎት ተከፍቶአል፡፡

በመቀጠልም ሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም መደበኛ ስብሰባን በጸሎትና በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ የመክፈቻ ንግግር ተጀምሮ ለሦስት ቀናት ሲካሄድ ሰንብቶአል፡፡ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችንና መመሪያዎችንም አስተላልፎአል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ለዐራት ቀናት ያህል ባካሄደው ቀኖናዊ ጉባኤ፡-

-ለቤተ ክርስቲያናችንና ለሀገራችን የሚጠቅሙትን፣

-ለልማትና ለሰላም የሚበጁትን፣

-ከሀገር ውጭ ለሚገኙና በሀገር ውስጥ ላይ ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችን ሁለንተናዊ ሕይወት መጠበቅ የሚያስችሉትን ርእሰ ጉዳዮች በማንሣት በስፋትና በጥልቀት አይቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፎአል፡፡

1.ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ በጉባኤ መክፈቻ ያደረጉት ታሪካዊ ንግግር የቤተ ክርስቲያንን ሁለንተናዊ ሕይወት የቃኘ የሀገራችን ዕድገትንና የሰላም አስፈላጊነት በስፋት የገለጸ በመሆኑ ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ተቀብሎታል፡፡

2.ምልአተ ጉባኤው በቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ተዘጋጅቶ የቀረበውን ዓመታዊ የሥራ መግለጫ ሪፖርት አዳምጦ አንዳንድ ማስተካከያዎችን በማድረግ በሙሉ ድምፅ ተቀብሎታል፡፡

3.ምንም ጥፋትና በደል ሳይኖርባቸው ክርስቲያኖች በመሆናቸው ብቻ በሊቢያ ሀገር አይ ኤስ በተባለ የአሽባሪዎች ቡድን በግፍና በሚዘገንን ሁኔታ የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ክርስቲያኖችንና የግብፅ ኦርቶዶክስ ክርስቲያኖችን በተመለከተ ቋሚ ሲኖዶስ ቀደም ሲል በሟቾቹ መንፈሳዊ ሕይወት ላይ ተወያይቶ ባቀረበው ሐሳብ መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ያለውን ሁኔታ በጥልቀት ከተረዳ በኋላ ሟቾቹ የዘመኑ ሰማዕት እንዲባሉ ተስማምቶ ወስኗል፡፡

4.እንዲሁም እንደ ኢትዮጵያውያን አቆጣጠር ሚያዝያ 11 ቀን 2007 ዓ.ም በሊቢያ የተሠውት 30 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አማኞች ልጆቻችን እና እንደ አውሮፓውያን አቆጣጠር የካቲት 15 ቀን 2015 ዓ.ም በሊቢያ የተሠውት 21 የኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባላት ክርስቲያኖች በሁሉቱም አብያተ ክርስቲያኖች ሲኖዶስ የሰማዕትነት ክብር የተሰጣቸው ስለሆነ፣ የሁለቱ አኃት አብያተ ክርስቲያናት የ21ኛው ክፍለ ዘመን ሰማዕታት ተብለው በአንድነት እንዲታሰቡ ቅዱስ ሲኖዶስ ተስማምቷል፡፡

5.በልዩ ልዩ ምክንያት ከኢትዮጵያ ሀገራቸው ወጥተው በባዕድ ሀገር የሚገኙትንና ወደ ሀገራቸው በመመለስ ላይ ያሉትን ኢትዮጵያውያን ወገኖቻችንን ከማንኛውም ጥቃት ለመከላከልና ለማቋቋም ቤተ ክርስቲያናችን መንግሥት ከሚያደርገው ጥረት በመቀናጀት አስፈላጊውን ሁሉ እንድታደርግ፣ ይህን በተመለከተ ጉዳዩን የሚከታተል ኮሚቴ የቤተ ክርስቲያናችን የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽንም እርዳታ ሰጪዎችን በማስተባበር ኃላፊነቱን ወስዶ በንቃትና በትጋት እንዲሠራ ጉባኤው ወስኖአል፡፡

6.ሀገራችን ኢትዮጵያ በአሁኑ ጊዜ አምስተኛውን ሀገራዊ ምርጫ ለማከናወን በሂደት ላይ መሆኗን ቅዱስ ሲኖዶስ አውስቶ ምርጫው ሰላማዊና ፍትሐዊ ሆኖ በሰላም ይጠናቀቅ ዘንድ ቤተ ክርስቲያናችን በጸሎት እንድትተጋ ጉባኤው መልእክቱን አስተላልፏል፡፡

7.ኢትዮጵያ ሀገራችን ለብዙ ዘመናት ተጭኖአት ከቆየ የድህነት አረንቋ በተጨማሪ የእርስ በእርስ ግጭት ጥሎባት ባለፈ ጠባሳ ክፉኛ የተጎዳች ብትሆንም በተገኘው ሰላም ምክንያት ባሳለፍናቸው ዓመታት እየታዩ ያሉ የልማትና የዕድገት፣ የእኩልነትና የአንድነት እመርታዎች የሰላምን ጠቃሚነት ከምንም ጊዜ በላይ መገንዘብ የተቻለበት ስለሆነ፤ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ከምንም በላይ ሰላሙንና አንድነቱን አጽነቶ በመያዝ ሀገሩን ከአሸባሪዎችና ከጽንፈኞች ጥቃት ነቅቶ እንዲጠበቅ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦት ያሳስባል፤

8.ሀገራችን ኢትዮጵያ የቴክኖሎጂና የካፒታል እጥረት እንደዚሁም በሀገር ውስጥ ሠርቶ የመበልፀግ ግንዛቤ ማነስ ካልሆነ በቀር በተፈጥሮ ሀብትም ሆነ በማናቸውም መመዘኛ ከሌላው የተሻለች እንደሆነች የታወቀ ስለሆነ፤ ወጣቶች ልጆቻችን ወደ ሰው ሀገር እየኮበለሉ ራሳቸውን ለአደጋ ከሚያጋልጡ በሀገራቸው ሠርተው የተሻለ ኑሮ እንዲኖሩ ኅብረተሰቡም ይህንን ከግንዛቤ ውስጥ አስገብቶ በሰፊው እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ መልእክቱን አስተላልፏል፤

9.ለሀገራችንና ለሕዝቦቻችን ችግሮች ቁልፍ መፍትሔ ሊሆን የሚችለው ልማትን በማጠናከርና ዕድገትን በማረጋገጥ ድህነትን ማስወገድ ስለሆነ ሕዝባችን ይህን ከልብ ተቀብሎ በየአቅጣጫው የተጀመሩትን የልማት ሥራዎች በመደገፍ ሀገሪቱን መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገሮች እኩል ለማሰለፍ የሚደረገውን ሀገራዊ ርብርቦሽ ለማሳካት በርትቶ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፤

10.በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያ ክርስቲያናት በየቤተ ክርስቲያኑ ዙሪያ ሁሉ የአረንጓዴ ልማትና የራስ አገዝ ልማት በማካሄድ ልማትን እንዲያፋጥኑ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ መመሪያ አስተላልፎአል፡፡

11.በውጭ ሀገር ከሚገኙ አባቶች ጋር ተጀምሮ የነበረው የእርቀ ሰላም ድርድር ለሀገራችን ልማትና ለሕዝባችን አንድነት የሚሰጠው ጥቅም የማይናቅ ስለሆነ የቤተ ክርስቲያናችን በር ለሰላምና ለእርቅ ክፍት መሆኑን ምልዓተ ጉባኤው ገልጿል፡፡

12.ቅዱስ ሲኖዶስ ከዚህ በላይ በተገለፁትና በሌሎችም መንፈሳዊ፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ሲወያይ ሰንብቶ ስብሰባውን በዛሬው ዕለት በጸሎት አጠናቆአል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችን ለሕዝባችንና ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣ ምሕረቱንና ፍቅር አንድነቱን ይስጥልን፤

እግዚአብሔር ይባርካችሁ ይቀድሳችሁ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ሚያዝያ 30 ቀን 2007 ዓ.ም.

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

የጅማ ማእከል የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር እንደሚያካሄድ ገለጸ

ሚያዝ 29 ቀን 2007 ዓ.ም.

በጅማ ማእከል

001jimaaበማኅበረ ቅዱሳን የጅማ ማእከል ሁለተኛውን የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ግንቦት 2 ቀን 2007 ዓ.ም. በሊሙ ኮሳ ወረዳ ቤተ ክህነት በምትገኘው ጥንታዊና ታሪካዊ በሆነችው ኮሳ ቅደስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እንደሚያካሄድ ገለጸ፡፡

የኮሳ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ከጅማ 50 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኝ ሲሆን፤ የትኬቱ ዋጋ ምሳን ጨምሮ 150፡00 ብር መሆኑን ማእከሉ ገልጿል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የወንጌል ትምህርት በተጋባዥ መምህራን፤ ያሬዳዊ ወረብ እና ቅኔ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ምክረ አበው /ከምእመናን ለሚጠየቁ ጥያቄዎች ምላሽ የሚሰጥበት/፤ ያሬዳዊ ዝማሬ በማእከሉ መዘምራን፤ በተጋባዥ ዘማርያንና በአጥቢያው ሰንበት ትምህርት ቤቶች መዘምራን ይቀርባል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ተወካዮች፤ የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ስብከተ ወንጌል ሓላፊዎች፤ የሊሙ ሰቃ፤ የሊሙ ኮሳ፤ የአጋሮና ቀርሳ እንዲሁም የጅማ ከተማ ምእመናን በመርሐ ግብሩ ላይ ይሳተፈሉ ሲል ማእከሉ አስታወቋል፡፡

ጥያቄ ለመጠየቅ ለሚፈልጉ ምእመናን በሚከተለው የኢሜል አድራሻ መላክ እንደሚችሉ ማእከሉ አሳስቧል፡፡

jimmamkhh2@gmail.com ወይም aynisha5@gmail.com

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ያስገነባው መንበረ ጵጵስና እና ጽ/ቤት ተመረቀ

ሚያዝያ 28 ቀን 2007 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

001deb002deb

የሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በደብረ ብርሃን ከተማ ያስገነባው ለመንበረ ጵጵስና እና ለጽ/ቤት አገልግሎት የሚውል ባለ ሁለት ፎቅ ሕንፃ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ሚያዝያ 25 ቀን 2007 ዓ.ም. ተመረቀ፡፡

በሀገረ ስብከቱ የተገነባውን ሕንፃ ለመመረቅ ቅዱስ ፓትርያርኩ፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና የጠቅላይ ቤተ ክህነት የልዩ ልዩ መምሪያ ሓላፊዎች ከአዲስ አበባ ወደ በደብረ ብርሃን ሲመጡ በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ የሃያ ዘጠኝ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቃነ ካህናትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ የዞኑ እና የከተማው የመንግሥት ባለሥልጣናት፤ እንዲሁም የደብረ ብርሃን ከተማ ምእመናን አቀባበል አድርገውላቸዋል፡፡

003deb004deb

ቅዱስነታቸው ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በመሆን ሕንፃውን ከመረቁ በኋላ አገልግሎት የሚሰጡትን ክፍሎች በሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ኤፍሬምና በሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ እየተመሩ ጎብኝተዋል፡፡

በዐፄ ዘርዓያዕቆብ ደባባይ በተከናወነው መርሐ ግብር ቅዱስነታቸው ባስተላለፉት መልእክት በደብረ ብርሃን ከተማ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ እየተሠሩ ያሉ የልማት ሥራዎች የሚያስደስቱ ናቸው፡፡ ከመንበረ ጵጰስናው ግንባታ በተጨማሪ በዐፄ ዘርዓ ያዕቆብ ደባባይ እየተገነባ የሚገኘው ባለ 5 ፎቅ ሕንፃም ሀገረ ስብከቱ ለሚያከናውነው መንፈሳዊ አገልግሎት ጠቀሜታው የጎላ ነው፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ተጨማሪ ሀብት የሚያስገኝ በመሆኑ ሌሎችም አህጉረ ስብከቶች ከዚህ ልማት ሊማሩ ይገባል ብለዋል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ አባ ዘውዱ በየነ ባቀረቡት ሪፖርት በሀገረ ስብከቱ 29 ወረዳ ቤተ ክህነት፤ 2000 አብያተ ክርስቲያናት እንዳሉ የገለጹ ሲሆን፤ ከእነዚህ ውስጥ ከ360 በላይ አብያተ ክርስቲያናት ብፁዕ አቡነ ኤፍሬም ወደ ሀገረ ስብከቱ ከመጡ በኋላ እንደታነጹ አብራርተዋል፡፡

006deb005deb

ለካህናት ሥልጠና በመስጠት፤ የሰበካ ጉባኤ ክፍያን በማሳደግና በማሰባሰብ፤ ስብከተ ወንጌል በማስፋፋት፤ መምህራንን በማፍራትና በመመደብ፤ በአረንጓዴ ልማት፤ በደብረ ብርሃን ሥላሴ ሰባት መምህራንን በመመደብ በአብነት ትምህርት በርካታ ደቀ መዛሙርትን በማፍራት፤ የካህናት ደዝን በማሳደግ ሀገረ ስብከቱ አገልግሎቱን በማፋጠን ላይ እንደሚገኝ ሥራ አስኪያጁ ገልጸዋል፡፡

ቀድሞ የነበረው የሀገረ ስብከቱ መንበረ ጵጵስና በንግድ ማእከላት አካባቢ በመሆኑና ምቹ አገልግሎት ለመስጠት ባለማስቻሉ ሌላ ባለ ሁለት ፎቅ መንበረ ጵጵስና እና ጽ/ቤትን አጠቃሎ የያዘ ሕንፃ በመገንባት ለዛሬው ምረቃ መብቃቱን ያብራሩት ሥራ አስኪያጁ ባለ አምስት ፎቅ ሁለገብ ሕንፃም በመጠናቀቅ ላይ እንደሚገኙ በሪፖርታቸው ከተዳሰሱት ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ተጀምሮ፤ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ያሬዳዊ ወረብ፤ በሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ያሬዳዊ መዝሙር፤ በደብረ ብርሃን ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የቅኔ መምህር ቅኔ ቀርቧል፡፡

010de009deb

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ በጸሎት ተጀመረ

ሚያዝያ 27 ቀን 2007ዓ.ም

100sinodossበዓመት ሁለት ጊዜ የሚደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ዛሬ ሚያዝያ 27 ቀን 2007ዓ.ም. ከቀኑ ዐሥር ሰዓት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም በጸሎት ተጀመረ፡፡

የቅዱስ ጊዮርጊስ ሰማዕትነት በመጽሐፈ ስንክሳር

ሚያዝያ 22 ቀን 2007 ዓ.ም.

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አምላክ አመ ዕሥራ ወሠሉሱ ለሚያዝያ በዛቲ ዕለተ ኮነ ፍጻሜ ስምዑ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሰማዕት ዐቢይ ወክቡር ዘተሰምየ ፀሐየ ወኮከበ ጽባሕ፡፡

አንድ አምላክ በሚሆን በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም ሚያዝያ ሃያ ሦስት በዚች ቀን ፀሐይና የአጥቢያ ኮከብ የተባለ ታላቅና ክቡር የሆነ የሰማዕቱ የቅዱስ ጊዮርጊስ የምስክርነት ፍጻሜ ሆነ፡፡

የዚህም ቅዱስ አባቱ መስፍን ነው፡፡ ስሙም አንስጣስዮስ ይባላል፡፡ ከቀጰዶቅያ አገር ነው፡፡ የእናቱም ስም ቴዎብስታ ይባላል ከፍልስጥዔም አገር ናት ታናሽ ሆኖ ሳለ አባቱ ዐረፈ፡፡

ሃያ ዓመትም በሆነው ጊዜ የአባቱን ሹመት ሊቀበል ወደ ንጉሥ ዱድያኖስ ዘንድ ሔደ፡፡ ንጉሡም ጣዖትን እንዲአመልኩ ሰዎችን ሁሉ ሲያስገድዳቸው አገኘው፡፡

ይህንንም አይቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ እጅግ አዘነ በእርሱ ዘንድ ያለውን ገንዘቡን ሁሉ ለድኆች፣ ለምስኪኖች ሰጠ ባሮቹንም ነፃ አወጣቸው፡፡

ከዚህ በኋላ በንጉሥ ፊት ቁሞ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ታመነ፡፡ ንጉሡም አባበለው ብዙ ቃል ኪዳንም ገባለት እርሱ ግን አልተቀበለውም፡፡

ለመስማት እንኳ የሚያስጨንቅ ሥቃይን አሠቃየው ጌታችን ግን ያጸናዋል ቍስሉንም ያድነዋል ሦስት ጊዜም እንደሚሞት እርሱም እንደሚአስነሣው በአራተኛውም የምስክርን አክሊልን እንደሚቀበል ነገረው፡፡ ቃል ኪዳንም ሰጠው ስሙ በዓለሙ ሁሉ የተገለጠ ይሆን ዘንድ በተጋድሎና መከራ በመቀበልም ጽኑዕ በሆነ ሥቃይም ሰባት ዓመት እንደሚኖር መላእክትም እንደሚአገለግሉት ነገረው፡፡

ንጉሡም ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለመታዘዙና ባለመመለሱ እጅግ አዘነ፡፡ ስለዚህም አትናስዮስ የሚባል ታላቅ ሥራየኛ አመጣ፡፡ እርሱም መርዝን ቀምሞ በጽዋ መልቶ አስማት ደግሞ እንዲጠጣ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ሰጠው፡፡ ወዲያውኑ የሚሞት መስሎት ነበር፡፡ ቅዱሱም ያንን ጽዋ ጠጣው ምንም ጉዳት አልደረሰበትም፡፡

ያ መሠርይም በክብር ባለቤት በጌታ በኢየሱስ አምኖ በሰማዕትነት ሞተ፡፡ ከእርሱም ጋር ሌሎች ብዙዎች ሰዎች በሰማዕትነት ሙተው የሕይወት አክሊል ተቀበሉ ቁጥራቸውም ሠላሳ ሺህ ሰባት መቶ ነፍስ ነው፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስም በዱድያኖስና በሰባ ነገሥታት ፊት በቆመ ጊዜ በዚያም የተቀመጡባቸው የዕንጨት ወንበሮች ነበሩ፡፡ ቅዱሱንም እሊህን የተቀመጥንባቸውን ወንበሮች እንዲበቅሉ እንዲአብቡና እንዲአፈሩ ታደርጋቸው ዘንድ ከአንተ እንሻለን አሉት፡፡ በዚያን ጊዜ ጸለየ እንዳሉትም አደረጋቸው ይህንንም ድንቅ ሥራ አይተው ቍጥር የሌላቸው ብዙ አሕዛብ በጌታችን አመኑ፡፡

ከዚህም በኋላ ቅዱሱን ወስደው በጐድጓዳ ብረት ምጣድ ውስጥ አበሰሉት፡፡ አቃጥለው አሳርረውም ሥጋውንና ዐጥንቱን ፈጭተው አመድ አድርገው ከረጅም ተራራ ላይ በተኑት፡፡ ጌታችንም ነፍሱን ወደ ሥጋው መልሷት ደግሞ አስነሣው፡፡ ወደ ነገሥታቱም ተመልሶ በክብር ባለቤት በጌታችን ኢየሱስ ስም ሰበከ፡፡ ቍጥር የሌላቸው አሕዛብ አይተው አደነቁ በጌታችንም አምነው በሰማዕትነት ሞቱ፡፡

ነገሥታቱም ደግመው ሙታኖችን ብታሥነሣ አምላክህ ዕውነተኛ አምላክ እንደሆነ እናውቃለን፡፡ በእርሱም እናምናለን አሉት፡፡ ቅዱሱም ጸለየ ከጒድጓድም ውስጥ ወንዶችና ሴቶችን ጐልማሶችንም አስነሣላቸው እነዚያም በክብር ባለቤት በጌታችን ስም አስተማሩ የገሀነምንም ወሬ ተናገሩ ጥምቀትንም ተቀብለው ተመልሰው ዐረፉ፡፡

ከሀድያን ነገሥታት ግን ሙታንን ያስነሣህ አይደለም የረቀቁ ሰይጣናትን አሳየህ እንጂ ብለው ተከራከሩ፡፡ ከዚያም ከጭንቀታቸው ብዛት የተነሣ ከአንዲት ድኃ ሴት ዘንድ አስጠበቁት እርሷም እንጀራ ልትለምንለት ወጣች የእግዚአብሔርም መልአክ በላዩ ከበጎ ነገር ሁሉ የተመላ ማዕድን አቀረበለት፡፡ የዚያች መበለትም የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍን አበቀለ ታላቅ ዛፍም ሆነ፡፡

ያቺም መበለት በተመለሰች ጊዜ የቤቷ ምሰሶ ቅርንጫፍ አብቅሎ ታላቅ ዛፍ እንደሆነ ስለ ማዕዱም ይህን ታላቅ ምልክት አይታ የክርስቲያኖች አምላክ ሰው ተመስሎ ወደ እኔ መጣ አለች፡፡ ቅዱስም እኔ አምላክ አይደለሁም፡፡ የአምላክ ባሪያ ነኝ እንጂ አላት፡፡ እርሷም እንዲህ ብላ ለመነችው የአምላክ አገልጋይ ከሆንክ ቸርነትህ እንድትደርሰኝ እለምንሃለሁ፡፡ ዕውር ደንቆሮ ዲዳ ጐባጣ የሆነ ልጅ አለኝና ታድንልኝ ዘንድ እለምንሃለሁ፡፡ ስለ ጌታችን እምነትም አስተማራትና በመስቀል ምልክት አማተበው ያን ጊዜም አየ፡፡ ቅዱሱም በሌላ ጊዜ እንዲሰማ እንዲናገርና እንዲሔድ እንዲአገለግለኝም እኔ እሻለሁ አላት፡፡

በዚያን ጊዜ ንጉሡ በአገሩ ሜዳ ውስጥ ሲዘዋወር ያቺን ዛፍ አይቶ አደነቀ ስለ እርሷም ጠየቀ ቅዱስ ጊዮርጊስ በእርሷ ዘንድ የተቀመጠባት የዚያች መበለት የቤቷ ምሰሶ እንደሆነ ነገሩት፡፡ ንጉሡም ተቆጣ ቅዱሱንም ከዚያ ወስዶ አስገረፈው በመንኰራኵርም አበራዩት ሙቶም ከከተማ ውጭ ጣሉት ጌታም ከሞት አስነሣው ወደ ነገሥታቱም ተመለከተ ንጉሡም አይቶ ደነገጠ ስለ ሕይወቱም አደነቀ፡፡

ከዚህም በኋላ ይሸነግለው ዘንድ ጀመረ በመንግሥቱ ላይም ሁለተኛ ያደርገው ዘንድ ቃል ገባለት ቅዱስ ጊዮርጊስም እየዘበተበት ነገ በጥዋት ለአማልክቶችህ መሥዋዕትን አቀርባለሁ አንተም ሕዝቡ እንዲሰበሰቡ እዘዝ እኔ ስሠዋ እንዲአዩ አለው፡፡ ንጉሡም ዕውነት የሚሠዋ መስሎት ደስ አለው ወደ ቤተ መንግሥቱም እልፍኝ አስገብቶ አሳደረው፡፡

ለጸሎትም ተነሣ የዳዊትንም መዝሙር አነበበ የዱድያኖስ ሚስቱ እለስክንድርያ ንግሥት ሰምታ ቃሉ ደስ አሰኛት የሚያነበውንም ይተረጒምላት ዘንድ ለመናቸው፡፡ እርሱም እግዚአብሔር ዓለምን ከፈጠረበት ሰው እስከሆነበት ጊዜ የሆነውን ሁሉ ሊያስረዳትና ሊያስገነዝባት ጀመረ፡፡ ትምህርቱም በልቡዋ ተቀርጾ በክብር ባለቤት በጌታችን አመነች፡፡

በማግሥቱም ቅዱስ ጊዮርጊስ ለአማልክት ሲሠዋ ለማየት ሰው ሁሉ እንዲሰበሰብ ዐዋጅ ነጋሪ ዞረ የቤቷን ምሰሶ ያበቀለላት ያቺ መበለት ሰምታ ዕውነት መስሏት እጅግ እያዘነች ልጅዋን ተሸክማ እያለቀሰችም ወጣች፡፡

ቅዱስ ጊዮርጊስም በአያት ጊዜ ፈገግ አለ ልጅሽን በምድር ላይ አኑሪው አላት፡፡ ከዚያም ልጅዋን ጠርቶ ወደ አጵሎን ሒድ ወደእኔም ይመጣ ዘንድ በክብር ባለቤት በጌታዬ ኢየሱስ ስም እዘዘው አለው፡፡ ያን ጊዜ ያ ልጅ ድኖ ቅዱስ ጊዮርጊስ እንዳዘዘው ወደ ጣዖቱ ቦታ ሒዶ አዘዘው፡፡ በጣዖቱ ያደረ ያ ርኵስ መንፈስም ከማደሪያው ወጥቶ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወደ አለት መጥቶ እኔ ሰውን ሁሉ የማስት እንጂ አምላክ አይደለሁም ብሎ በሕዝቡ ሁሉ ፊት አመነ፡፡ ቅዱሱም ትውጠው ዘንድ ምድርን አዘዛትና ወዲያውኑ ዋጠችው ጣዖታቱንም ከአገልጋዮቻቸው ጋራ አጠፋቸው ንጉሡም ከወገኖቹ ጋር ዐፈረ፡፡

ብስጭትና ቁጣንም እንደተመላ ወደ ንግሥት ሚስቱ ዘንድ ገባ፡፡ እርሷም አምላካቸው ጽኑዕና ኃያል ነውና ክርስቲያኖችን አትጣላቸው አላልኩህምን አለችው፡፡ ይህንንም ከእርስዋ ሰምቶ በእርሷ ላይ እጅግ ተቆጣ ወደ ክብር ባለቤት ክርስቶስ እምነት የከበረ ጊዮርጊስ እንደአስገባት አወቀ፡፡

ከዚህም በኋላ ከከተማ ውጭ እንዲጐትቷትና በመጋዝም እንዲሰነጥቋት አዘዘ፡፡ የሰማዕትነት አክሊልንም በመንግሥተ ሰማያት ተቀበለች፡፡

በዚያም ጊዜ ስለ ቅዱስ ጊዮርጊስ ሥራ ነገሥታቱ ሁሉም ደነገጡ ኀፍረት ደግሞ እንዳይጨምርባቸው ከእርሱም እንዲአርፍ ራሱን በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ እንዲጽፍ ንጉሥ ዱድያኖስን መከሩት፡፡

ያን ጊዜም የክቡር ጊዮርጊስን ራስ በሰይፍ ይቆርጡ ዘንድ አዘዘ፡፡ ድል አድራጊ ጊዮርጊስም እጅግ ደስ አለው፡፡ እሳት ከሰማይ አውርዶ ሰባውን ነገሥት ያቃጥላቸው ዘንድ መከራውም ከክርስቲያን ወገን ጸጥ ይል ዘንድ ጌታችንን ለመነው፡፡ ወዲያው እሳት ወርዶ ከሠራዊታቸው ጋር ሰባውን ነገሥታት አቃጠላቸው፡፡

ከዚህም በኋላ የክብር ባለቤት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ተገልጾ ብዙ ቃል ኪዳን ሰጠው፡፡ በምድር መታሰቢያህን ለሚያደርግ ሁሉ እኔ ኃጢአቱን ሁሉ እደመስሳለሁ በመከራም ውስጥ ሁኖ በባሕርም ሆነ በየብስ ወይም በደዌ በስምህ የሚለምነኝን እኔ ፈጥኜ ከመከራው አድነዋለሁ፡፡ ይህንንም ጌታችን ተናግሮ በክብር ወደ ሰማይ ወጣ፡፡

ከዚህ በኋላ ራሱን ዘንበል አድርጎ በሰይፍ ቆረጡት በመንግሥተ ሰማያት አክሊላትን ተቀበለ፡፡ ከአገልጋዮቹም የቀሩት ሥጋውን ወስደው በልብስ ጠቀለሉት ወደሀገሩ ልዳም ወሰዱት፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ሠርተው በውስጥዋ አኖሩት ከእርሱም ቍጥር የሌላቸው ብዙዎች ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ፡፡

ለእግዚአብሔርም ምስጋና ይሁን የቅዱስ ጊዮርጊስም በረከቱ ረድኤቱ ሁላችን የክርስቲያን ወገኖችን ከሥጋና ከነፍስ መከራ ይጠብቀን ለዘላለሙ አሜን፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሰማዕታቱን ቤተሰቦችንና ምእመናንን አጽናኑ

ሚያዝያ15 ቀን 2007ዓ .ም.

dscn6308ሚያዝያ ፲፫ ቀን ፳፻፯ ዓ.ም. በደብረ ፍሥሓ መካነ ሰማዕት ቅዱስ ቂርቆስ አካባቢ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የሰማዕታቱን ኢያሱ ይኵኖ አምላክና ባልቻ በለጠ ቤተሰቦችንና ምእመናንን ሊያጽናኑ፤ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፣ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፣ ብፁዕ አቡነ ማትያስ ዘካናዳ፣ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፣ ብፁዕ አቡነ ኖክና ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሄደዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ

ልጆቻችን የምንኮራባቸው መጻሕፍቶቻችን ናቸው፡፡ ልጆቻችን ሰማዕታቶቻችን ናቸው፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የውድ ልጆቻችን የሰማዕታቱ፣ የታማኝ ልጆቻችን፣ የጀግኖች ልጆቻችን፣ በኢትዮጵያዊ ባህላቸው፣ በኢትዮጵያዊ ትውፊታቸው፣ በእምነታቸው፣ በሥርዐታቸው፣ በወጋቸው ጸንተው፣ ለማንም ሳይበገሩ እና ለማንም ሳይደለሉ፣ ለሌላ እጃቸውን ሳይሰጡ፣ ሳይቀለበሱ ጀግንነትን ያስተማሩ ልጆቻችን፣ መጻሕፍት የኆኑ ልጆቻችን ወላጆች እና እዚኅየተሰበሰባችሁ ውድ ወገኖቼ፡-

ከክርስቶስ ልደት በፊት ሰባት መቶ ዓመታት ቀድሞ የነበረው ነቢዩ ኤርያስ፣ በዚያን ጊዜዋ ባቢሎን በዛሬዋ ኢራቅ፤ በዚያን ጊዜዋ ፋርስ በዛሬዋ ኢራን እየዘዋወረ ባስተማረበት ዘመን ስለ ኢትዮጵያውን አድናቆት፣ ክብር፣ ጀግንነት፣ አይበገሬነት በትንቢቱ ምዕራፍ 13 ቁጥር 23 ላይ እንዲኽ ብሏል፡-ኢትዮጵያዊ መልኩን ነብር ዝንጉርጉርነቱን ሊለውጥ ይችላልን?

dscn6309ኢትዮጵያዊ ባህሉን፣ ኢትዮጵያዊ እምነቱን፣ ኢትዮጵያዊ አንድነቱን፣ ኢትዮጵያዊ ጀግንነቱን፣ ኢትዮጵያዊ ትውፊቱን በሌላ ሊቀይር ይችላልን? አይቀየርም፡፡ ነቢዩ ቆቃው ኤያስ በተባለ መጽሐፉም ይህን በስፋት እየገለጸ ይናገራል፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ ልጆቻችን እኮ ጀግኖች ናቸው፤ ልጆቻችን እኮ እጃቸውን አልሰጡም፤ ልጆቻችን እኮ አልተንበረከኩም፤ ልጆቻችን እኮ መጻሕፍቶቻችን ናቸው፤ ልጆቻችን እኮ አርበኞቻችን ናቸው፤ አልተማረኩም፤ የጀግና እናት አታለቅስም እንደተባለው ሁሉ፣ እናንተም የጀግኖች እናቶች ናችሁ፤ ልትኮሩ ይገባችኋል፤ ስማቸውን ለውጠው፣ ሃይማኖታቸውን ለውጠው፣ ሥርዐታቸውን ለውጠው፣ ተማርከው ቢሆን ኖሮ ነበር ማልቀስ የሚገባን፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ የጀግኖች ወላጆች ናችኹና ልትኮሩ፣ ልትጽናኑ ይገባችኋል፡፡ እሰይ ልጄ፤ ተባረክ ልጄ፤ ለመንግሥተ ሰማያት ያብቃኽ ብላችሁ ልትመርቁ፣ ልትጸልዩ፣ ልትጽናኑ ይገባል፡፡ የመጽናኛ ዕለት ነው፤ ልጆቻችን አስተምረውናል፤ ልጆቻችን አኩርተውናል፤ ልጆቻችን አስከብረውናል፤ አስወድደውናል፤ በዓለም ደረጃ አገራችንን አስተዋውቀዋል፡፡

ውድ ወገኖቼ፤ እንዲኽ ላሉት ነው እንዴ የሚለቀሰው? አገር አጥፍቶ ለሔደ፣ በሙስና ተዘፍቆ ለሔደ፣ ሰክሮ ለሔደ፣ አመንዝሮ ለሔደ፣ ቀምቶ ለሔደ በምድር ኑሮው ተበላሽቶ፣ በሰማይ እንዴት ይኾን ከቶ ተብሎ የሚለቀስለት ለዚኽ ነው፡፡ ብዙ ልጆቻችን በየመልኩ ኸሉም አርበኛ ነው፡፡ አካሉን፣ ሕይወቱን፣ ወላጁን፣ ልጁን፣ ዘመኑን፣ ንብረቱን የሰጠ ስንት አለ? ውድ ወገኖቼ፤ እንዴ፣ እነዚኽማ ልጆቻችን የምንኮራባቸው መጻሕፍቶቻችን ናቸው!! የምንማርባቸው ዩኒቨርስቲዎቻችን ናቸው ልጆቻችን!! ብርሃናችን ናቸው ልጆቻችን!! ማዕተቤን አልበጥስም፤ ወደ ሌላ አንለወጥም፤ አንበገርም አሉ፤ ይኼ ነው ወይ የሚያስለቅሰው? የሚለቀስበትን ነገር እንወቅ እንጂ!

ውድ ወገኖቼ፤ ስለዚህ ልጆቻችንን በሰማዕትነታቸው፣ በጀግንነታቸው ልናከብራቸው፣ ልንማርባቸው፣ ምሳሌአቸውን ልንወስድ፣ ልናወድሳቸው ይገባል፡፡ ስለዚኽ ይኼ የመረጋጋት፣ የሰላም የፍቅር ቦታ ነው፡፡ ልጆቻችን የአገር ፍቅር፣ የአገር ሰላም፣ የአገር አንድነት አስተምረውናል፡፡ በልጆቻችን ተምረናል፤ ጠግበናል፤ ረክተናል፤ ኮርተናል፡፡

የልጆቻችንን ነፍስ በገነት በመንግሥተ ሰማያት ያሳርፍልን፤ ይማርልን፤ ወላጆቻቸውን ይጠብቅልን፤ ከክፉ ነገር ይሰውረን፤ መልካሙን ነገር ያምጣልን፤ ልጆቻችንና ወገኖቻችንን በሰላም ወደ ቤታቸው ይመልስልን፡፡ ሁላችንም ተጽናንተን የሚያኮራ ሥራ እንድንሠራ ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡ ነፍሰ ገብሩ ኃይለ ኢየሱስ፣ ኃይለ ሚካኤል ሀገረ ሕይወትን መንግሥተ ሰማያትን ያውርስልን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን የሐዘን ዳርቻ ያድርግልን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን የቤተሰቡን ሕይወት፣ የቤተሰቡን ሐዘን በመልካም ነገር፣ በፍቅር ነገር ይለውጥልን፡፡ ቤተሰቡን ያለምልምልን፡፡ ቤተሰቡን ያጽናልን፡፡ ደግ ያልኾኑ ሰዎችን ወደ ደግነት፣ ወደ ምሕረት፣ ወደ ቸርነት ይመልስልን፡፡ ለዓለሙ ኹሉ ሰላም መረጋጋትን ያድልልን፡፡ አገራችን ኢትዮጵያን በክብር በረድኤት ይጠብቅልን፡፡

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ

dscn6312ያለንበት አካባቢ ቤተ መቅደሱ ቂርቆስ ነው፡፡ እንደምታውቁት ቂርቆስ ሕፃን ነው፡፡ በምን መልክ እንደ ዐረፈ ታውቃላችሁ፡፡ ሕፃኑ ቂርቆስ፣ ዓላውያን ነገሥታት በእኛ እምነት እመን፤ እኛ የምናዝዝህን ፈጽም ባሉት ሰዓት አልተቀበላቸውም፡፡ እሳት ነደደ፤ በበርሜል ውስጥ ውኃ ፈላ፡፡ በዚህ ሰዓት እናቱ ደንግጣ ወደ ፈላው ውኃ ለመግባት ስትፈራ ሕፃኑ ቂርቆስ፣ እናቴ ጨክኚ፤ ዛሬ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበት ቀን ነው፡፡ አባቶቻችን በሰጡን፣ ባወረሱን፣ ባስተማሩን እምነት ጸንተን ወደ መንግሥተ ሰማያት የምንገባበት ነውና ከዓላዊው ንጉሥ አትፍሪ ብሎ እናቱን ወደ እሳት የጋበዘ ነው፡፡ እስከ መጨረሻው እስከ ዘላለሙ ሰማዕቱ ቂርቆስ ሲባል ይኖራል፤ ታሪክ ሲዘክረው ይኖራል፤ ታሪክ አይደመሰስም፡፡

አሁንም እነዚህ ወንድሞቻችን፣ ወገኖቻችን ሰማዕታት የታሪክ ባለቤቶች ስለኾኑ፣ ታሪክ አትርፈው ስለሔዱ ከእነርሱ በፊት እንደነበሩት ኹሉ ለዘላለም ስማቸው፣ ሥራቸው ሲወሳ ይኖራል፡፡ ሐዘን ሁልጊዜ ሲያነሡት ልብ ይሠቀጥጣል፡፡ ይኼን እያነሡ መናገር በጣም ይከብዳል፡፡ ጭንቅላት ሊሸከመው አይችልም፡፡ እናም እዚህ ያሉትን እያጽናናችኹ፣ እዚያ የቀሩት ደግሞ በሰላም እንዲወጡ ምህላ እያደረግን ልንጸልይ ይገባል፡፡ እኛ እዚኽ ፀሐይ እየሞቅን፣ እየተነጋገርን እናዝለን፤ እዚያ እነርሱ ከወጡበት ሰውነታቸው አልቆ ነፍሳቸው የምትጨነቅ አለችና በሰላም እንዲያወጣቸው ላለፉት ብቻ ሳይኾን ለቀሩትም ጸሎት እያደረጋችኹ በዚኽ እንድትጽናኑ ነው አደራ የምንለው፡፡

ወላጆች ወለዱ እንጂ የሁላችን ልጆች ናቸው፤ ሐዘኑ የኢትዮጵያ ነው፤ እግዚአብሔር ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጽናቱን ይስጥልን፡፡ እዚያ የቀሩትንም በሰላም ያውጣልን፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በሐዘንተኞቹ ቤት ተገኝተው በማጽናናት ላይ ይገኛሉ

ሚያዝያ 13 ቀን 2007 ዓ.ም.

001 papasat 002በዛሬው ዕለት ከቀኑ ዐሥር ሰዓት ጀምሮ ከስድስት በላይ ሊቃነ ጳጳሳት ሰማእቱ ቅዱስ ቂርቆስ ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በሚገኘው በሊቢያ በግፍ በአሰቃቂ ሁኔታ የተገደሉትን ወጣቶች ቤተሰቦችን ለማጽናናት በመኖሪያ ቤታቸው ተገኝተዋል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳቱ በጥልቅ ሐዘን ላይ ለሚገኙት የሰማእታቱ ቤተሰቦችን፤ ዘመድ ወዳጆቻቸውን እንዲሁም ምእመናንን በቃለ እግዚአብሔር በማጽናናት ላይ ይገኛሉ፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፤ ብፁዕ አቡነ ማትያስ፤ ብፁዕ አቡነ ቀሌምንጦስ፤ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ፤ ብፁዕ አቡነ ሔኖክ ተገኝተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ሉቃስ በሰጡት የወንጌል ትምህርት €œልጆቻችን ብርሃን፤ መጻሕፍቶቻችንና ጀግኖቻችን፤ እንዲሁም የሃማኖትም የሀገርም አርበኞች ናቸው፡፡€ ብለዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ በበኩላቸው የሰማእቱ ቅዱስ ቂርቆስንና የእናቱን የቅድስት ኢየሉጣን ታሪክ መነሻ በማድረግ ሰፊ የማጽናኛ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ሚዲያ ክፍል አባላትም በቦታው ተገኝተዋል፡፡

ሕማማተ እግዚእነ በልሳነ አበው /የጌታችን መከራ በሊቃውንት አንደበት/

ሚያዝያ 1 ቀን 2007 ዓ.ም.

005sikletየእስክንድርያው ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ ቄርሎስ እንዲህ አለ

ታመመ፤ ሞትን ከተቀበለበት ከሥጋ ተዋሕዶ በመስቀል ላይ በፈቃዱ ለሥጋውያን ሞተ፣ ባሕርየ መለኮት ሥጋን ተዋሕዶ በማኅፀን ካደረ ጀምሮ ሥጋ ገንዘቡ እንደመሆኑ በሥጋ ይኸንን ሥርዓት ፈጸመ፡፡

ለማይመረመር ለመለኮቱ ባሕርይ እንደሚገባ ደግሞ እርሱ ኅብስት አበርክቶ ሁሉን ያጠግባል፡፡ አይራብም፣ አይጠማም፣ አይደክምም፣ አያንቀላፋም፣ አይታመምም፣ አይሞትም ሕይወትን ለሁሉ ይሰጣል፡፡ ዳግመኛ በዚያ በሲኦል ተገዝተው ያሉ ነፍሳትን ያድን ዘንድ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወረደ በመለኮቱም ሲኦልን በዘበዘ፡፡

ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ የወልድን ነገር በተናገረበት ድርሳኑ እንዲህ አለ

እጆቹን፤ እግሮቹን በተቸነከረባቸው ችንካሮች መወጋቱንም እናምናለን፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ እርሱ ደዌያችንን ወሰደ ሕማማችንንም ተሸከመ፤ እኛን ለማዳን ኃጢአታችንንም ለማስተስረይ መከራ ተቀበለ እንዳለ፤ በባሕርዩ ሕማም የሌለበት ሲሆን በሥጋ የታመመ ነው፡፡ በእርሱ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ ድነናል አለ፡፡ በተገረፈና በተቸነከረም ጊዜ በመከራው ሁሉ መለኮትን ሕማም ተሰማው የሚል ሰው ቢኖር የተለየ የተወገዘ ይሁን፡፡

የአንጾኪያው ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ዲዮናስዮስ ከላከው ሲኖዶሳዊ መልእክት የተገኘ

እርሱ መቼም መች ከመለኮቱ ሳይለይ የሰውነትን ሥራ ሁሉ ገንዘቡ አደረገ፡፡ ይኸውም መራብ፣ መጠማት፣ መንገድ በመሔድ መድከም፣ በመስቀል ላይ መሰቀል፣ በብረት ችንካር መቸንከር ነው፡፡ በሰውነቱ መቸም መች ሰው ነው፣ በአምላክነቱም ሰውን የፈጠረ ነው፡፡ ግን ከማይከፈል ተዋሕዶ በኋላ መከፈል የለበትም፡፡ ሰው እንደ መሆኑ ስለ እኛ የታመመው የሞተው እርሱ ነው፡፡ በመለኮቱ ግን መቸም መች አይታመምም አይሞትም፣ ሕማምንና ሞትንም አይቀበልም፡፡ በሞቱ ሞትን ያጠፋው እርሱ ነው፡፡ ሲኦልንም የበዘበዘው እርሱ ነው፡፡

የእስክንድርያው ሊቀ ጳጳስ ሐዋርያው ቅዱስ አትናቴዎስ እንዲህ አለ

ነፍሱን ከሥጋው በለየ ጊዜ ያን ጊዜ በሲኦል ፈጥኖ ብርሃን ታየ፡፡ ጌታችን በአካለ ሥጋ ያይደለ በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ሔደ፡፡

ሲኦል ተነዋወጠች፣ መሠረቶቿም እፈርስ እፈርስ አሉ፣ ምድርን ያለ ጊዜዋ እንዳታልፍ ክብርት ደሙን በምድር ላይ አፈሰሰ፡፡ ከኅልፈት ጠበቃት በርሷ ያለውንም ሁሉ ጠበቀ፡፡

ስለ ፍጥረት ሁሉ ሥጋውን በመስቀል እንደተሰቀለ ተወው፡፡ ነፍሱ ግን ወደ ሲኦል ወረደች ከዚያ ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን አዳነች፤ ሲኦልንም በዘበዘች፤ ፍጥረትንም ሁሉ ገንዘብ አደረገች፡፡ ሥጋውም በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፡፡

ሃይማኖታቸው የቀና ሦስት መቶ ዐሥራ ስምንት ሊቃውንት በአንድ ልብ እንዲህ አሉ

ከብርሃን የተገኘ ብርሃን፣ ከባሕርይ አምላክ የተገኘ የባሕርይ አምላክ፣ የተወለደ እንጂ የተፈጠረ ያይደለ፣ በባሕርዩ ከአባቱ ጋር አንድ የሚሆን፡፡ ሁሉ የተፈጠረበት ያለ እርሱ ግን ምንም ምን የተፈጠረ የሌለ፣ በሰማይ በምድር ያለውም ቢሆን፡፡

እኛን ስለማዳን ከሰማየ ሰማያት ወርዶ በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ፍጹም ሰው ሆነ፡፡

የሠላሳ ዘመን ጎልማሳ ሆኖ በጶንጦስ ሰው በጲላጦስ የሹመት ዘመን ስለ እኛ ተሰቀለ፣ ስለ እኛም ታመመ ሞተ ተቀበረ፡፡

የቂሣርያ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ባስልዮስ እንዲህ አለ

ምትሐት ያይደለ በእውነት ተራበ፣ ተጠማ እንጂ፡፡ ዳግመኛም ከኃጥአን ከመጸብሐን ጋር በላ ጠጣ፣ ያቀረቡለትንም በላ፡፡ ራሱን አሳልፎ ለመስቀል ሰጠ፣ እጁን እግሩን ተቸነከረ፣ ጎኑን በጦር ተወጋ፣ ከእርሱም ቅዱስ ምስጢር የተገለጠበት ደምና ውኃ ፈሰሰ /ወጣ/፡፡

የኑሲስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ጎርጎርዮስ እንዲህ አለ

የሚሠዋ በግ እርሱ ነው፣ የሚሠዋ ካህን እርሱ ነው፡፡ ከባሕርይ አባቱ ከአብ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋርም መሥዋዕት የሚቀበል እርሱ ነው፡፡ በፈቃዱ መከራን በሥጋው የተቀበለ መከራንም ሁሉ የታገሠ እርሱ ነው፡፡ እንደ በግ ሊሠዋ መጣ፣ በግ በሚሸልተው ሰው ፊት እንዳይናገር አልተናገረም፣ በአንደበቱ ሐሰት አልተገኘበትም፡፡

ሰማዕት የሆነ ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ፊልክስ እንዲህ አለ

በሥጋ መወለድ፣ በመስቀል መከራ መቀበል፣ መሞት መነሣት፣ ገንዘቡ የሆነ እርሱ እግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ ስለዚህ በመስቀል ላይ ሳለ ከጥንት ጀምሮ በመቃብር ያሉ ሙታንን ሁሉ አስነሣ፡፡

የሮማ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ አቡሊዲስ እንዲህ አለ

ሙሴም ሞትን ያጠፋ ዘንድ አልቻለም፣ እርሱንም ይዞ ገዛው እንጂ፣ ከእርሱም በኋላ የተነሡ ነቢያትንም ሁሉ ሞት ገዛቸው እንጂ፡፡ ክርስቶስ ግን በቸርነቱ ለሁሉ ሕይወትን ሰጠ፡፡

የሮሜ ሊቀ ጳጳሳት ቅዱስ አዮክንድዮስ እንዲህ አለ

በመስቀል በሥጋ ተሰቅሎ ሳለ ለመለኮት ከሥጋ መለየት የለበትም፡፡ አንዲት ሰዓትም ቢሆን የዐይን ጥቅሻ ያህል ስንኳ ቢሆንም መለኮት ከትስብእት አልተለየም፣ በመቃብር ውስጥ በሰላም መለኮት ከትስብእት አልተለየም፡፡

የኪስኪስ ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤራ ቅሊስ እንዲህ አለ

ከአብ ጋር አንድ እንደ መሆንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ ከእኛ ጋር አንድ እንደመሆንህ በፈቃድህ የሞትክ አንተ ነህ፡፡

በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፣ በኪሩቤል ላይ ያለህ አንተ ነህ፡፡ ከሙታን ጋር በመቃብር የነበርክ አንተ ነህ፣ በአንተ ሕማምና ሞትም ድኅነት ተሰጠ፡፡

ከሙታን ጋር የተቆጠርክ አንተ ነህ፣ ለሙታንም ትንሣኤን የምትሰጥ አንተ ነህ፣ ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ያደርክ አንተ ነህ፣ በዘመኑ ሁሉ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የምትኖር አንተ ነህ፡፡

በመለኮት ሕማም ሳይኖርብህ በሥጋ የታመምክ አካላዊ የእግዚአብሔር ቃል አንተ ነህ፡፡

የኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ አለ

ኃጢአታችንን ለማሥተሰረይ በሥጋ እንዲህ ታመመ፣ እንደሞተ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ሥጋውን እንደ ገነዙ እናምናለን፡፡

የቆጵሮስ ደሴት ኤጲስ ቆጶስ ቅዱስ ኤጲፋንዮስ እንዲህ አለ

ነብይ ዳዊትም ነፍሴን በሲኦል አትተዋትም የባሕርይ ልጅህንም ሙስና መቃብርን ያይ ዘንድ አሳልፈህ አትሰጠውም አለ፡፡ ይህም ጌታ በተዋሐደው አካል ያለውን የነፍስና የሥጋ ተዋሕዶ ያስረዳል፣ የቀና ልቡና ዕውቀት በእርሱ ጸንቶ ይኖር ዘንድ፡፡ ዳዊት እንደተናገረው እውነት ሆነ፣ ነፍስ መለኮትን ተዋሕዳ ወደ ሲኦል ወርዳለችና፣ ሥጋም ሦስት መዓልት ሦስት ሌሊት በመቃብር ሳለ መለኮት ከሥጋ አልተለየም፡፡ አምላክ ሰው የመሆኑን እውነት ያስረዳ ዘንድ፣ መለኮት ነፍስን ተዋሕዶ በአካለ ነፍስ የሲኦል ምስጢርን ገልጦ ፈጽሟልና በሲኦልም በቁራኝነት አልተያዘምና፡፡

ምንጭ ስምዐ ተዋሕዶ፤ ሚያዝያ 1-5 ቀን 2007 ዓ.ም.