ወርኃ ጳጉሜን
ወርኃ ጳጉሜን በዓመቱ መጨረሻ የምትገኝ በአገራችን ኢትዮጵያ እንደ ዐሥራ ሦስተኛው ወር የምትቆጠር ናት፤ ወርኃ ጳጉሜን አምስት ቀናት ያሏት ስትሆን በአራት ዓመት አንድ ጊዜ በዘመነ ሉቃስ መውጫ በዘመነ ዮሐንስ መግቢያ ያለው ስድስት ቀን ይሆናል፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላታቸው ጳጉሜን እንዲህ ይተረጉሟታል፤ ጳጉሜን ማለት ጭማሪ ተውሳክ፣ አምስት ቀን፣ ከሩብ፣ ከዐውደ ወር ተርፎ በዓመቱ መጨረሻ የተጨመረ ስለሆነ ትርፍ ተጨማሪ ማለት ነው፡፡ (አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መዝገበ ቃላት፣ ገጽ ፱፻፭)