ወርኃ ግንቦት
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ዘጠነኛው ወር “ግንቦት” በመባል ይታወቃል፡፡ ግንቦት “ገነበ፣ ገነባ፣ ሠራ፣ ቆፈረ፣ ሰረሰረ” ከሚለው የግእዝ ቃል የወጣ ሲሆን ትርጒሙም “ገቦ፣ ክረምት፣ የክረምት ጎን፣ ጎረ ክረምት (የክረምት ጉረቤት)” ይባላል። ይህንም ስም የሰጡት የክረምት መግቢያ ምድር ለእርሻ የምትዘጋጅበት ወቅት በመሆኑ ነው።
አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላት መጽሐፋቸው ውስጥ የዚህን ወር ቃል ሲተረጒሙ “ስመ ወርኅ፣ ታስዕ እመስከረም፣ ገቦ ክረምት፣ ጎረ ክረምት” ይልና በግንብ ዘይቤ ሲፈቱት ግን “ወርኀ ሡራሬ” ያሰኛል፡፡ የባቢሎን ግንብ ሳይቀር ሁለቱ መቅደሶች በግንቦት ወር ተመሥርተዋል፡፡ (፫ኛ ነገ.፮፥፩፣ ዕዝ.፫፥፰) ይሉታል። (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፫፻፳፪)