ጾመ ነነዌ

ጥር፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

ቸር፣ መሐሪና ይቅር ባይ የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር የነነዌ ሕዝብ በንስሓ፣ በጾምና በጸሎት ወደ እግዚአብሔር ካልተመለሱ ነነዌ እንደምትጠፋ እንዲያስተምርና እንዲያስጠነቀቅ ሲያዘው ነቢዮ ዮናስ ግን በቸርነቱ ሲምራቸው ሐሰተኛ ነቢይ እንደሚባል አስቦ መሸሽን መረጠ፡፡ ‹‹ተነሥና ወደ ነነዌ ሀገር ግባ፤ በድለውኛልና ነነዌ በሦስት ቀን ትጠፋለች ብለህ ስበክ›› አለው። ዮናስ ግን ‹‹የአንተ ምሕረት እጅግ የበዛ ሲሆን ትጠፋለች ብዬ ተናግሬ እሳት ከሰማይ ሳይወርድ ቢቀር ሐሰተኛ ነቢይ ልባል አይደለምን?››  አለና ሊሸሽ መንገድ ጀመረ። (ዮናስ ፩፥፩-፫)

አምላክም የየዋሁን የዮናስን ልብ ያውቃልና በድንቅ ጥበቡ የጉዞውን አቅጣጫ ቀይሮ ወደ ነነዌ ምድር ወሰደው፡፡  (ዮናስ ፩፥፬-፲፯)  ዮናስም ነነዌ መሬት ላይ መድረሱን ባወቀ ጊዜ ከእግዚአብሔር መሸሽ አለመቻሉን ተረዳ፤ የነነዌ ሰዎችንም ‹‹ንስሐ ግቡ›› እያለ ሰበከ፡፡ የነነዌ ሰዎችም ንስሐ በገቡ ጊዜ እግዚአብሔር ይቅር ብሎ ከጥፋት አድኗቸዋል፡፡ ሐሰት እንዳይባልም እሳቱ እንደ ደመና ሆኖ ከላይ ታይቶአል፡፡ የታላላቁ ዛፍ ቅጠል እስኪጠወልግ ድረስ አድርቆ ለሕዝቡ አሳይቷቸዋል፡፡ ንስሐቸው በከንቱ እንዳልቀረ አስረድቷቸዋል (ትንቢተ ዮናስ)፡፡

ከዚህ በኋላ የተጻፈው ታሪክ እንዲህ ይለናል፤ ‹‹ይህም ዮናስን ከቶ ደስ አላሰኘውም፤ እርሱም ተቈጣ። ወደ እግዚአብሔርም ጸለየና ‹‹አቤቱ፥ እለምንሃለሁ በአገሬ ሳለሁ የተናገርሁት ይህ አልነበረምን? አንተ ቸርና ይቅር ባይ፣ ታጋሽም፣ ምሕረትህም የበዛ፣ ከክፉው ነገርም የተነሣ የምትጸጸት አምላክ እንደ ሆንህ አውቄ ነበርና ስለዚህ ወደ ተርሴስ ለመኰብለል ፈጥኜ ነበር፡፡ አሁንም አቤቱ፥ ከሕይወት ሞት ይሻለኛልና እባክህ ነፍሴን ከእኔ ውሰድ›› አለው። እግዚአብሔርም ‹‹በውኑ ትቈጣ ዘንድ ይገባሃልን?›› አለ።

ዮናስም ከከተማይቱ ወጣ፤ ከከተማይቱም በስተ ምሥራቅ በኩል ተቀመጠ፤ ከተማይቱንም የሚያገኛትን እስኪያይ ድረስ በዚያ ለራሱ ዳስ ሠርቶ ከጥላው በታች ተቀመጠ። እግዚአብሔር አምላክም ቅል አዘጋጀ፤ ከጭንቀቱም ታድነው ዘንድ በራሱ ላይ ጥላ እንድትሆን በዮናስ ላይ ከፍ ከፍ አደረጋት ዮናስም ስለ ቅሊቱ እጅግ ደስ አለው። በነጋው ግን ወገግ ባለ ጊዜ እግዚአብሔር ትልን አዘጋጀ፤ እርስዋም ቅሊቱን እስክትደርቅ ድረስ መታቻት፡፡ ፀሐይም በወጣች ጊዜ እግዚአብሔር ትኩስ የምሥራቅ ነፋስ አዘጋጀ፤ ዮናስ እስኪዝል ድረስም ፀሐይ ራሱን መታው፤ ለራሱም ሞትን ፈለገና ‹‹ከሕይወት ሞት›› ይሻለኛል አለ። እግዚአብሔርም ዮናስን ‹‹በውኑ ስለዚህች ቅል ትቈጣ ዘንድ ይገባሃልን?›› አለው። እርሱም ‹‹እስከ ሞት ድረስ እቈጣ ዘንድ ይገባኛል›› አለ። እግዚአብሔርም ‹‹አንተ ትበቅል ዘንድ ላልደከምህባት ላላሳደግሃትም፣ በአንድ ሌሊት ለበቀለች፣ በአንድ ሌሊትም ለደረቀችው ቅል አዝነሃል። እኔስ ቀኛቸውንና ግራቸውን የማይለዩ ከመቶ ሃያ ሺህ የሚበልጡ ሰዎችና ብዙ እንስሶች ላሉባት ለታላቂቱ ከተማ ለነነዌ አላዝንምን?›› አለው፡፡ (ዮናስ ፬፥፩-፲፩)

ምሕረቱ የበዛው አምላካችን የነነዌ ሰዎችን ይቅር እንዳላቸው ሁሉ እኛንም ጸሎታችንን ሰምቶ፣ ልመናችንን ተቀብሎና ጾማችንን አስቦ ምሕረትን ያደርግልን ዘንድ ከክፋት ርቀን፣ ከቂም በቀል ከጥላቻ ነጽተን፣ በበጎነትና በመልካም ምግባር ጾሙን እንጹም!

አምላካችን እግዚአብሔር ምሕረትን ያድርግልን፤ አሜን!!!

 

 

አማናዊ ብርሃን

ታኅሣሥ ፲፫፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

እውነተኛው ብርሃን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰዎችን ከገቡበት የኃጢአት ባርነትና የጨለማ ዓለም ለማውጣት ወደዚህች ምድር እንደመጣ፣ መከራን ተቀብሎ፣ በመስቀል ተስቅሎ፣ ሞቶ፣ ተነሥቶ ነጻ እንዳወጣን ቅዱሳኑ ነቢያት ሰብከዋል፡፡ ምሥጢረ ሥጋዌውን ነገረ ድኅነትን በሚገባ አስተምረዋል፡፡

ከድንቁርና ወደ ፍጹም ዕውቀት ያደረሰን፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን ያወጣን፣ ከሞት ወደ ሕይወት ያሸጋገረን ጌታ እርሱ ዓለም ብርሃን ነው፡፡ “አነ ውእቱ ብርሃኑ ለዓለም” እንዲል፡፡ (ዮሐ.፰፥፲፪) ነቢያትም ጌታን በብርሃን እየመሰሉ ሥጋዌውን ተናግረዋል፡፡ ነቢዩ ዳዊትም እንዲህ አለ፤ “ብርሃን ለጻድቃን፥ ደስታም ለልበ ቅኖች ወጣ።” (መዝ.፺፯፥፲፩) በመጽሐፈ ኢሳይያስም ደግሞ “ለአሕዛብ ብርሃን አድርጌ ሰጥቼሃለሁ” ተብሎ ተጽፏል፡፡ (ኢሳይያስ ፵፱፥፮)

መጽሐፈ መዝገበ ታሪክ የጌታን ብርሃንነት እንዲህ አስፍሮታል፡፡ “ብርሃንም ቢባል እንደ ፀሐይ እንደ ጨረቃ ብርሃን ጠፈር ደፈር የሚከልክለው መዓልትና ሌሊት የሚፈራርቀው አይደለም፡፡ የማይጠፋ የማይለወጥ አማናዊ ብርሃን ነው እንጂ፤” (ገጽ ፻፮) ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ እንደገለጸው “እግዚአብሔር ብርሃን ነው፤ ጨለማም በእርሱ ዘንድ ከቶ የለም የምትል ይህች ናት።” (፩ኛ ዮሐ. ፩፥፭) ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ይህን ለመዘከር ከታኅሣሥ ፲፬ እስከ ፳ ድረስ ያለውን ወቅት “ብርሃን” ብላ ሰይማዋለች፡፡

ብርሃን የሆነው አምላካችንና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በኃጢአት ማዕበል እየተናወጠች፣ በችግር መከራ ተጨንቃ፣ በነፋሱ ውዥንብር ከግራ ቀኝ እየተማታች፣ በምድር መናወጥ እየተንቀጠቀች፣ በጎርፍ እየሰጠመች፣ በእሳት ውእያት እየተለበለበች ወደ ድቅድቅ ጨለማ ከተለወጠችው ዓለም ያውጣን፤ አሜን!!!

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

ነቢያት ለምን ጾሙ?

ኅዳር ፲፭፤፳፻፲፰ ዓመተ ምሕረት

የአዳም ዘር በሙሉ በኃጢአት ባርነት ተይዞ፣ ለ፶፻፭፻ ዓመታት በፍዳ አረንቋ ውስጥ ሲኖር ተስፋ ሲያደርግ የነበረው የእግዚአብሔር አብ ልጅ እግዚአብሔር ወልድ ለአዳም የገባለትን የመዳን ቃል ኪዳን ነው፡፡ ይህም ይፈጸም ዘንድ ነቢያት አስቀድሞ ትንቢት ተናግረዋል፡፡

ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስለ መወለዱ ፥ ወደ ግብፅ ስለ መሰደዱ ፥ በባሕረ ዮርዳኖስ ስለ መጠመቁ ፥ ብርሃን በሆነው ትምህርተ ወንጌል ጨለማውን ዓለም ስለ ማብራቱ ፥ ለሰው ልጆች ድኅነት ጸዋትወ መከራ ስለ መቀበሉና ስለ መሰቀሉ ፥ ስለ ትንሣኤው ፥ ስለ ዕርገቱና ስለ ዳግም ምጽአቱ ትንቢት ተናግረው አላቆሙም፡፡

ነቢዩ ዳዊት “እጅህን ከአርያም ላክ አድነኝም” በማለት ሲማጸን (መዝ.፻፵፫፥፯) ነቢዩ ኢሳይያስ ደግሞ “እነሆ፥ ድንግል ትፀንሳለች፥ ወንድ ልጅም ትወልዳለች፥ ስሙንም አማኑኤል ብላ ትጠራዋለች” በማለት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከድንግል ማርያም እንደሚወለድ አስቀድሞ ተናግሯል፡፡ (ኢሳ.፯፥፲፬) በዚህም የተስፋ ቃል “ኃይልህን አንሳ፤ እጅህንም ላክ” በማለት ነቢያት እየተማጸኑ ጾመዋል፡፡

የነቢያት ጾም (የገና ጾም) ከኅዳር ፲፭ ጀምሮ ለ ፵፫ ቀናት የሚጾም ሲሆን ፋሲካው (ፍቺው) በልደት በዓል ነው፤ ይህም ጾም በዘመነ ብሉይና በዘመነ ሐዲስ ቅዱሳንና ምእመናን ጾመውታል፡፡ እኛም አምላካችን ቸርነቱን እንዲያበዛልን፣ ከፈተና እንዲያወጣን፣ ወቅታዊውን ሀገራዊ ችግር ይፈታልን ዘንድ፣ ከመከራ ሥጋ ከመከራ ነፍስ እንዲሠውረን ጾሙን እንጹም!

የጌታችን ቸርነት፣ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም እና የቅዱሳን ነቢያት ጸሎት፣ አማላጅነትና ተረዳኢነት አይለየን፤ አሜን!

 

የሐዋርያት ጾም

ሐዋርያት ሙሽራው ክርስቶስ ከእነሱ በተለየ በዐሥረኛው ቀን መንፈስ ቅዱስን ልኮላቸው መንፈስ ቅዱስን በተቀበሉ ማግስት ለአገልግሎታቸው መቃናት ትምህርታቸውን (ስብከታቸውን) በጾም ጀምረውታል፡፡ዛሬም እኛ ቅዱሳን ሐዋርያትን አብነት አድርገን በበዓለ ጰራቅሊጦስ ማግስት እነርሱ የጾሙትን ጾም እንጾመዋለን፡፡

“ሆሣዕና በአርያም” (ማቴ.፳፩፥፱)

ከደቀ መዛሙርቱም ሁለቱን ልኮ ቤተ ፋጌ ከምትባል ቦታ አህያ እና ውርንጫ አስመጥቶ በእነርሱም ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ከተማ ገባ። በዚያን ሰዓት ከይሁዳ አውራጃዎች ሁሉ የፋሲካን በዓል ለማክበር የተሰበሰቡት ሁሉ የኢየሱስን ወደ ኢየሩሳሌም መምጣት ሰምተው በእልልታ እና በዝማሬ “ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው፤ ሆሣዕና በአርያም እያሉ ይጮኹ ነበር።” (ማቴ.፳፩፥፱)

“እርሱም በሌሊት ወደ ጌታችን ኢየሱስ መጣ” (ዮሐ.፫፥፩)

የዓለምን ኃጢአት አስወግዶ፣ ኃጢአተኞችን በፍቅሩ መረብ አጥምዶ፣ በቃሉ ትምህርት ልቡናቸውን ማርኮ፣ በተአምራቱ ኅሊናቸውን ገዝቶ የፈጠራቸውን ሰዎች ወደ ሕይወት መንገድ ሊጠራ የመጣው መሲሕ በአይሁድ ቤት እንደ ባላጋራ ይታይ ነበር። ከዚያም አልፎ የአይሁድ አለቆች የሥልጣናቸውን በትር ተጠቅመው፣ ቀጥቅጠው፣ ከእግራቸው በታች አድርገው ሊገዙት ይሹ ነበር። ተግሣፁን እና የተአምራቱን ኃይል በአዩ ጊዜም በቅንዓት ተነሳሥተው ሊወግሩት ምክንያት ይፈልጉ ነበር። የባሕርይ አምላክነቱን ገንዘቡ እንደሆነ ሲነግራቸው፣ ራሱንም የእግዚአብሔር ልጅ እያለ ሲጠራ ሲሰሙ የቅን ተቆርቋሪ መሳይ ጠባያቸው እስከ መግደል ድረስ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል።

‹‹በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለው›› (ማቴ.፳፭፥፳፩)

በሰዎች ዘንድ መታመን መታደል ነው፤ እምነትን ጠብቆ መገኘት ደግሞ ታላቅነት ነው፡፡ መታመን የተሰጠን አደራ ጠብቆ መገኘት ለክብር ያበቃል፤ በሰውም ሆነ በአምላካችን በእግዚአብሔር ዘንድ መወደድንና መከበርን ያተርፋል፡፡ ለሰዎች ስንታመን እነርሱ ባያዩንም በሁሉ ቦታ ያለ፣ በቦታ የማይወሰን፣ በእርሱ ዘንድ ጨለማ የሌለበት እግዚአብሔር ያየናል፡፡ መታመናችን “ሰው አየን አላየን” ብለን ሳይሆን ለታመንንለት ነገር በፈቃዳችን መገዛት ስንችል፣ የታመነንን ስናከብር በምትኩ ለታላቅ ኃላፊነት እግዚአብሔር ይሾመናል (ይመርጠናል)፡፡

«በደብረ ዘይት ተቀምጦ አስተማረ» (ማር.፲፫፥፫)

በመዋዕለ ስብከቱ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ዘይት ተራራ ላይ ሆኖ ደቀ መዛሙርቱ የቤተ መቅደሱን ሥነ ሕንፃ በትኩረት እያንዳንዱን ነገር በመመልከት ሲያደንቁ እርሱ ግን ቤተ መቅደሱ እንደሚፈርስ፣ ከሞት በኋላ ተነሥቶ እንደሚያርግና ነገር ግን ዓለምን ለማሳለፍ ዳግም እንደሚመጣ ነገራቸው።

በሽተኛው ተፈወሰ!

ሕመም፣ በሽታና ክፉ ደዌ በሰዎች ሕይወት ውስጥ የሚያጋጥሙ የጤና እክሎች ናቸው፡፡ የሰው ዘር በሙሉ ከአዳም ጥፋት በኋላ ይህ ቅጣት እንደመጣበት ቅዱስ መጽሐፍ ይነግረናል፡፡ አዳምና ሔዋን አትብሉ ተብሎ የነበረውን ዕፀ በለስ ከበሉ በኋላ ከደረሰባቸው መርገምት መካከል በሕመምና ሥቃይ እንዲቀጡ ነው፡፡ (ዘፍ.፫፥፲፮-፲፱)

ለምድራዊም ይሁን ለዘለዓለማዊው ሕይወታችን መገኘት፣ ድኅነትም ሆነ ፈውስ የሚገኘው በእግዚአብሔር አምላካችን ስናምንና ለእርሱ ስንታመን እንደሆነ ማወቅ ይገባል፡፡ መፃጉዕ ለጊዜው የተጠየቀው ነገር ከያዘው ደዌ እንዲድን ቢመስልም ጌታችን ግን የነፍሱንም ድኅነት ጠይቆታል፡፡ ‹‹ልትድን ትወዳለህን?›› ብሎ የጠየቀው ስለ እምነቱ ነበር፡፡ ከበሽታው ለመፈወስም እንኳን ቢሆን እምነት ከሌለ ሊድን እንደማይችል በቃሉ አስረድቶታል፡፡ ከዚያም አልፎ ተርፎ የነፍሱንም ነገር እንዲያስብ አሳስቦታል፡፡

“የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉ” (ዮሐ.፪፥፲፮)

በቅዱስ ያሬድ ድጓ ውስጥ የምናገኘው ዐቢይ ጉዳይ አንጽሆ ቤተ መቅደስ ነው። “የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት” እንዲል። ይህ ብቻ አይደለም፤ ተቆጣቸው፤ ገሠጻቸው የሚሉ አስተማሪ ቃላቶችን አካቶ ይዟል። ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ይህንን በተመለከተ እንዲህ ይላል፡፡” በመቅደስም በሬዎችንና በጎችን ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፤ የገመድም ጅራፍ አበጅቶ ሁሉን በጎችንም በሬዎችንም ከመቅደስ አወጣቸው፥ የለዋጮችንም ገንዘብ አፈሰሰ፤ ገበታዎቻቸውንም ገለበጠ፥ ርግብ ሻጪዎችንም። ይህን ከዚህ ውሰዱ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት አላቸው።” (ዮሐ.፪፥፲፬-፲፮)